Administrator

Administrator

Saturday, 24 January 2015 13:24

ፀሎቴ

እንዳላዝን … እንዳልባባ
ለኔ ሲሉ፡- እያነቡ
የኔን ዕንባ
 እኔኑ
በኔው፡- ዕንባ
እያሉኝ እሹሩሩ … እሹሩሩ
ለኔ ሲሉ ፡- ሁልዜም እንደኖሩ
እስከዛሬም .. የሚኖሩ  
ነበሩ፡፡
እንዳላዝን … አባብለውኝ
እንዳልስቅም ፡- አዝነውልኝ
ከርቱዕ አንደበታቸው
ዕንባዬ ፈሶ ከዕንባቸው
ለኔ ብለው
እውነት ለኔ ብለው
የኔን ቁስል ቆስለውልኝ
የኔን ህልም ታመውልኝ፣ ታመውልኝ፡፡
ሞቴንም እንዳይሞቱልኝ
ፀሎት ላይ ነኝ
ለኔ ሲሉ፡- ያልሆኑትን እንዳይሆኑልኝ
(1994 ዲላ)

Saturday, 24 January 2015 12:51

የፖለቲካ ጥግ

ፖለቲካ፤ ለፖለቲከኞች ሊተው የማይችል ትልቅ ቁምነገር ነው     ወደሚል ድምዳሜ ደርሻለሁ፡፡
ቻርልስ ደጐል
* በዲሞክራሲ ሥርዓት አንደኛው ፓርቲ ሁልጊዜ ዋና ጉልበቱን     የሚያውለው ሌላኛው ፓርቲ አገር ለመምራት ብቁ አለመሆኑን     ለማረጋገጥ በመሞከር ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ሁለቱም ይሳካላቸዋል፡፡ ደግሞም     ትክክል ናቸው፡፡
ኤች ኤል ሜንኬን
* ዲሞክራሲ በመጠኑ የምትጠላውን     እጩ እንድትመርጥ የሚፈቅድልህ ሥርዓት ነው፡፡
ሮበርት ባይርኔ
* ፖለቲከኞችና ዲያፐር (የሽንት ሁለቱም በተመሳሳይ ምክንያት በየጊዜው መለወጥ አለባቸው፡፡
ያልታወቀ ፀሐፊ
* ፖለቲከኛ ነገ፣ በሚቀጥለውሳምንት፣ በሚቀጥለው   ወር፣ በሚቀጥለው ዓመት የሚከሰተውን ነገር የመተንበይ ችሎታ ያስፈልገዋል፡ከዚያም በኋላ ያልተከሰተበትን ምክንያት የማስረዳት ችሎታ ሊኖረው ይገባል፡፡
ዊንስተን ቸርችል
* የፖለቲካ ቀልድ ችግሩ፣ የቀለድንባቸው ፖለቲከኞች መመረጣቸው ነው፡፡
ያልታወቀ ግለሰብ
* ፖለቲካ፤ ውሳኔዎች አስፈላጊነታቸው እስኪያበቃ ድረስ የማቆየት ጥበብ     ነው፡፡
ሔንሪ ኪውይሌ
* ልታሳምናቸው ካልቻልክ አደናግራቸው፡፡
ሃሪ ኤስ ትሩማን
* ሰላማዊ ትግል እውን እንዳይሆን የሚያሰናክሉ፣ የትጥቅ ትግልን አይቀሬ ያደርጉታል፡፡
ጆን ኤፍ ኬኔዲ
* ፖለቲካ እጅግ ውድ እየሆነ ከመምጣቱ የተነሳ ለመሸነፍ እንኳን ብዙ ገንዘብ ይፈልጋል፡፡
ዊል ሮጀርስ

Saturday, 24 January 2015 12:47

አስገራሚ የቃላት ፍቺዎች

ተሞክሮ
 ሰዎች ለስህተታቸው የሚሰጡት ስም
አቶሚክ ቦምብ
 ሁሉንም ፈጠራዎች የሚያወድም ፈጠራ
አድርባይ
ድንገት ወንዝ ውስጥ ቢገባ ገላውን መታጠብ የሚጀምር ሰው
ወንጀለኛ  
ከመያዙ በቀር ከሌላው ሰው የማይለይ
ሃኪም
 በሽታህን በክኒን ገድሎልህ፣ አንተን በክፍያ የሚገድልህ ሰው
አለቃ
 ስትዘገይ ቀድሞህ የሚገባ፣ ስትቀድም የሚዘገይ
ኮሚቴ  
በግላቸው ምንም መስራት የማይችሉ ሰዎች በጋራ ምንም መስራት እንደማይቻል ለመወሰን በአንድ ላይ የሚቀመጡበት
ክላሲክ
ሰዎች የሚያወድሱት ግን የማያነቡት መፅሃፍ
የጉባኤ አዳራሽ
 ሁሉም ሰው የሚናገርበት፣ ማንም የማያዳምጥበትና በመጨረሻም ሁሉም የማይስማሙበት ስፍራ
ተስፈኛ
 ከአይፍል ማማ ላይ እየወደቀ ሳለ መሃል ላይ “አያችሁ ገና አልተጎዳሁም” የሚል ሰው
ስስታም
ሃብታም ሆኖ ለመሞት በድህነት የሚማቅቅ ሰው
ፈላስፋ
ሲሞት እንዲወራለት በህይወት ሳለ ራሱን የሚያሰቃይ ጅል
ወዘተ
ሌሎች በትክክል ከምታውቀው በላይ ታውቃለህ ብለው እንዲያምኑ ማድረጊያ ዘዴ

Saturday, 24 January 2015 12:44

የአዘቦት ቀን ጀግኖች

የ14 ዓመቱ ኮሊን ስሚዝ በደረሰበት የመኪና አደጋ መላ ሰውነቱ በድን (ፓላራይዝድ) ከሆነ በኋላ ሃኪሞች የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን የማጠናቀቅ ዕድሉ 20 በመቶ እንደሆነ አርድተውት ነበር፡፡ ኮሌጅ ገብቶ መማርማ እርሳው ነበር ያሉት፡፡ ሆኖም ከ8 ዓመት በኋላ ቢኤ ድግሪውን በኮሙኒኬሽን ከሃይ ፖይንት ዩኒቨርስቲ ለማግኘት ቻለ፡፡ ኮሊን ፈጽሞ የማይታሰበውን ማሳካት የቻለው በዕድሜ 50 ዓመት በሚበልጡትና ጨርሶ በማያቃቸው ደግ አዛውንት እርዳታ ነበር፡፡
እ.ኤ.አ በ2005 ዓ.ም እንዳጋጣሚ ሆኖ ጡረተኛው ኧርነስት ግሪኒና ባለቤታቸው ካትሪን፣ ኮሊንስና ወላጆቹ በሚያመልኩበት በኖርዝ ካሮሊና በሚገኘው የአሼቦሮ ባፕቲስት ቤ/ክርስቲያን ያመልኩ ነበር፡፡ በእርግጥ እኒህ ቤተሰቦች ትውውቅ አልነበራቸውም፡፡ ምክንያቱም የግሪን ቤተሰብ ወደ አካባቢው ከመጣ ዘጠኝ ወር ያህል ቢሆነው ነው፡፡ ሆኖም ኧርነስት በወሬ ወሬ ኮሊን ስለደረሰበት አደጋና ወላጆቹ የሙሉ ጊዜ እንክብካቤ ሊያደርጉለት አለመቻላቸውን ሰሙ፡፡ ይሄ ለእሳቸው የተላከ ጥሪ መስሎ ታያቸው፡፡
“ፈጣሪ እንድረዳው መራኝ” ይላሉ - ኧርነስት ግሪኒ፡፡ እናም በነበራቸው ትርፍ ጊዜ ኮሊንስን ሊረዱት ቆርጠው ተነሱ፡፡
መጀመሪያ የኮሊንን ቤተሰብ በመቅረብ፣ እነሱ ወደ ሥራ በሚሄዱ ወቅት ልጃቸውን ለመንከባከብ ፈቃደኛ መሆናቸውን ተናገሩ፡፡ የኮሊን ወላጆች አላቅማሙም፡፡ እርዳታውን በደስታ ተቀበሉ፡፡ አሁን 23ኛ ዓመት እድሜው ላይ የሚገኘው ኮሊን፤ እንዴት ጨርሶ የማላውቀው ሰው እኔን ለመርዳት መላ ህይወቱን እርግፍ አድርጐ እንደተወ ልረዳ አልቻልኩም ነበር ብሏል፡፡
አዛውንቱ ኧርነስት በቀጥታ ወደ እርዳታ አልገቡም፡፡ መጀመሪያ ለኮሊን እንዴት እርዳታ ማድረግ እንደሚችሉ መጠነኛ ስልጠና ወሰዱ፡፡ ከዚያም ወላጆቹ የሥራ ቀናቸውን በሚጀምሩበት አንድ ሰኞ ማለዳ ላይ እነኮሊን ቤት ከተፍ አሉ፡፡ ኮሊንን ከአልጋ ሲነሳ፣ ሲለባብስና ሲተጣጠብ ያግዙትም ጀመር፡፡ ቁርሱንም ሲመገብ እንዲሁ ይረዱታል፡፡ ከዚህም በላይ በራሳቸው መኪና ት/ቤት ያደርሱታል፡፡ በየቀኑ 9 ሰዓት ላይ ደግሞ ወደ ቤት ይመልሱታል፡፡ ወላጆቹ ከስራ እስኪመለሱም ወይ እሳቸው አሊያም ባለቤታቸው እያጫወቱ ይጠብቁታል፡፡
በዚያ ሰዓት ውስጥ ከኮሊን ጋር ብዙ ያወጉ እንደነበር ኧርነስት ያስታውሳሉ፡፡ መጀመሪያ ላይ በመሃላቸው የነበረው የዕድሜ ልዩነት ፈተና ሆኖባቸው እንደነበር አልሸሸጉም፡፡ በሁለት ትውልዶች መካከል የሚከሰት ልዩነት ነበር፡፡ ለምሳሌ አንዳቸው ራፕ ሲወዱ ሌላኛቸው ምርጫቸው አልነበረም፡፡ ነገር ግን ተቻችሎ መኖርን ተማሩ፡፡
“አዛውንቶች ዕድሜያቸው የገፋ እኛ ማለት ናቸው” የሚለው ኮሊን፤ “ድንቅ ታሪክ ያላቸው የእኛው ዓይነት ሰዎች” ሲል ይገልፃቸዋል፡፡
አንዳንድ ቀናት ከሌሎቹ የተሻሉ ነበሩ፡፡ “ምንም ነገር ራሱን ችሎ ማከናወን ስለማይችል ብዙ ሊያደክም ይችላል” ይላሉ ኧርነስት፡፡ ነገር ግን ፈታኝ ጊዜያትን ለማለፍ ያስቻለው የራሱ የኮሊን ጠንካራ ቁርጠኝነት መሆኑን ኧርነስት ይመሰክራሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ ኮሊን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ከቀሩት የክፍል ጓደኞቹ ጋር በአጥጋቢ ውጤት አጠናቆ በአቅራቢያቸው በሚገኘው ሃይ ፓይንት ዩኒቨርስቲ ለመግባት ቻለ፡፡ በእያንዳንዱ የትምህርት ክፍለ ጊዜ ኧርነስት ከአጠገቡ አይለዩም ነበር፡፡ “የመጀመሪያው ዓመት አስደሳች ነበር” ሲሉ ያስታውሳሉ - ኧርነስት፡፡ “ኮሊን ከሌላው ጐልቶ መታየት አይፈልግም ነበር” ግን ደግሞ ያገኘውን ዕድል በአግባቡ ይጠቀም ነበር - አስተማሪ ሲያስተምር ማስታወሻ ይይዛል፤ ብዙ ጊዜም ክፍል ውስጥ አስተያየት ይሰጥ ነበር፡፡
በምረቃ ቀን ታዲያ ኮሊን ብቻ አልነበረም ዲግሪውን የተቀበለው፡፡ አዛውንቱ ኧርነስትም ላከናወኑት ሰብዓዊ ተግባር ዩኒቨርሲቲው የክብር ዲግሪ ሰጥቷቸዋል፡፡ ያልጠበቁት ስለነበር ትንግርት እንደሆነባቸው ይናገራሉ፡፡
ኮሊን ግን ጨርሶ አልተገረመም፡፡ “ኧርነስት ሰው እንዴት መኖር እንዳለበት መለኮታዊ ምሳሌ የሚሆኑ ሰው ናቸው - ዝምተኛና ትሁት” በማለት ይገልፃቸዋል፡፡
ኮሊን ዛሬ በዚያው ሃይ ፖይንት ዩኒቨርሲቲ፣ የቅርጫት ኳስ ረዳት አሰልጣኝ ሲሆን ዕውቅና በተሰጠው ልዩ የእንክብካቤ ባለሙያ በየቀኑ ድጋፍ ያገኛል፡፡ አዛውንቱ ኧርነስትም አብዛኛውን ጊዜያቸውን ከቤተሰባቸው ጋር ያሳልፋሉ፡፡
አሁን ሁለቱ የተለያየ ትውልድ ጓደኛሞች እምብዛም አይገናኙም፡፡ “ነገር ግን ኮሊንና እኔ ሁልጊዜም ግንኙነታችን ይቀጥላል” ይላሉ - ኧርነስት፡፡ ኮሊንም በዚህ ይስማማል፡፡ “በቀን ከ14-16 ሰዓታት አንድ ላይ ነበር የምናሳልፈው” ሲል ያስታውሳል፡፡ ማሳለፍ ብቻ ሳይሆን አስቸጋሪ ፈተናን በጋራ ተወጥተዋል፡፡ ለዚያም ነው የአዘቦት ቀን ጀግኖች የሚባሉት፡፡
(ሪደር ዳይጀስት - የፌብሯሪ 2015 እትም)

እንዴት ከረማችሁሳ!
በዓላቱ በሰላም አለፉ! በበዓላት ቀናት የሚታይብንን ፈገግታና ደስታ ለሁለም ቀናት ያድርግልንማ!
ስሙኝማ…ህዝቤ ይገለብጠው የለ እንዴ! መቼም ‘አንደኛ’ የምንወጣባቸው ነገሮች እየበዙ አይደል…ከዚህ በፊት እንዳወራነው ትንሽ ቆይቶ በ‘ሲፑም’ ዓለምን ባናስከነዳ ምን አለ በሉኝ፡፡ (“ልጆቼን የማበላው አጣሁ፡፡ ወር ላይ የምመልስልህ አንድ ሁለት መቶ ብር አበድረኝ…” የሚለው ሰው አዲስ ‘ብራንድ’ ቢራ በመጣ ቁጥር “…ተጋፍቶ የሚጠጣው ከየት አምጥቶ ነው!” ምናምን አይነት ጥያቄ መጠየቅ ትተናል፡፡ ልክ ነዋ…አይደለም እኛ ሳይንስም እኮ ገና ያልደረሰባቸው ብዙ ነገሮች አሉ!)
ይቺ ከተማ እኮ እንደ ድሮ በልደታና በአቦ ሳይሆን…ወሩን ሁሉ ‘ሲፕ’ ቤቶቹ ጢም እያሉ የሚጠጣባት ከተማ ሆናለች!
ስሙኝማ…መቼም ‘የቢራዎች ፍልሚያ’ እየተጧጧፈ ነው፡፡ (ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ምን አለ በሉኝ የቢራ ዋጋ ‘እንደዛኛው ዘመን’ በጠርሙስ ብር ከስሙኒ ምናምን ባይገባ፡፡ አሀ…እነኚህ አዳዲስ የሚባሉት ፋብሪካዎች ሁሉ ገበያ ሲገቡ እንዴት አድርገን ነው ያንን ሁሉ ጠጥተን የምንጨርሰው!)
አሁን፣ አሁን አብዛኞቹ ዝግጅቶች ስፖንሰር የሚደረጉትና፣ በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ የሚተላለፉት አብዛኞቹ ማስታወቂያዎች የቢራዎቹ ናቸው፡፡ እሰይ… እንኳንም ኪነ ጥበባዊ ዝግጅቶችን እንደዚሀ ስፖንሰር የሚያደርጉ ድርጅቶች በዙልንማ! ግን አንዳንድ ጊዜ ነገሮች ሲበዙ… አለ አይደል…እነኚህ ነገሮች በአእምሮ ያልበሰሉት ላይ ሊፈጥሩ የሚችሉ ነገሮች ያሳስባችኋል፡፡ አለ አይደል… ‘ቢራ መጠጣት’ አይነት ነገሮች ‘የደስታ ጥግ’ ተደርገው ሲቀርቡ ዕድሜያቸው ያልደረሱ ህጻናት አእምሮ ላይ የተሳሰቱ መደምደሚያዎች እንዳይፈጥሩ የማስታወቂያዎቹ አቀራረብ ይታሰብባቸውማ! ስልጣኔያችን በዝቶ  የሰማንያ ምናምን ዓመት አያትም፣ የዘጠኝ ዓመት የልጅ ልጅም እኩል ቁጭ ብለው እስከ እኩለ ሌሊት ቴሌቪዥን የሚያዩባት አገር መሆኗ አይረሳማ፡፡
እኔ የምለው…የቢራን ነገር ካነሳን አይቀር… ‘ከ18 ዓመት በታች የማይሸጥ’ የሚለው የሆነ ነገር የሚጎድለው አይመስላችሁም! አለ አይደል…ማተኮር ያለበት ከ18 ዓመት በታች ያሉ ታዳጊዎች… እነሱ ገዙትም ማንም ገዛው ‘መጠጣት እንደማይችሉ’ ነው፡፡ እናላችሁ…በዚህ በበዓላት ሰሞን በከተማው ብዙ ቦታዎች ያያነው ነገር ቢኖር አሥራዎቹን ያላገመሱ ልጆች ተሰብስበው ሲጠጡ ነው…ያውም አላፊ አግዳሚው እያያቸው! በቀደም ሰብሰብ ብለው ‘የሎዋን ሲገጩ’ ያየናቸው ታዳጊዎች… አለ አይደል… የሁሉም ታላቅ የሆነችው አሥራ አምስት ዓመት ቢሆናት ነው፡፡
እኔ የምለው…የዘንድሮ ወላጅ…አለ አይደል…የሆነ ‘ፈርስት አሜንድመንት’ ምናምን ነገር ያለው ይመስላል፡፡ የልጆቻቸውን ነፃነት ምናምን የሚገድብ ህግ ‘ማውጣት’ አይችሉማ! ቂ…ቂ…ቂ…
የምር ግን…አለ አይደል…ዘንድሮ በርከት ያሉ ወላጆች በልጆቻቸው አስተዳደግ ላይ ያላቸው አዎንታዊ ተሳትፎ እየቀነሰ ነው ይባላል፡፡ በቃ… የሚበሉትና የሚጠጡት ካቀረቡላቸው፣ ካሽቀረቀሯቸው፣ ለፈለጉት ነገር ሁሉ ገንዘብ ከሰጧቸው የወላጅነት ግዴታቸውንና ኃላፊነታቸውን የተወጡ ይመስላቸዋል፡፡
ስሙኝማ…የተሳትፎ ነገር ካነሳን አይቀር…“በስፖርት ዋናው ነገር መሳተፉ ነው”… የምትባል ነገር አለች፡፡ ይሄ እንግዲህ ያኔ ስፖርት ፈረንካ በማያመጣበት ዘመን ነው፡፡ ዘንድሮ…ልጄ…ያውም በጦቢያ ኳስ… “እከሌ አንድ ሚሊዮን ሦስት መቶ ሺህ ብር ተሸጠ…” የሚባልበት ዘመን ደረስን አይደል! (እንትና… እስቲ የእግር ኳስ ‘ኤጀንትነት’ ምናምን ሞክርማ፡፡ “ምናለ አንድዬ እንደው አንድ ጊዜ ገንዘቡን ዝርግፍ ቢያደርግልኝ…” ስትል የከረምከው ሊሳካልህ ይችላላ!)
ስሙኝማ…የእግር ኳስ ነገር ከተነሳ አንድ ግርም የሚለኝ ነገር አለ…እግር ኳስ ተጫዋቾች ሜዳ ሲገቡ ሲጸልዩ ታዩዋቸዋላችሁ፡፡ የምር…‘ለውሳኔ’ እኮ አስቸጋሪ ነው፡፡ አሀ…ሁሉም… “ዛሬማ ጉድ አታደርገኝም!” እያለ የሚገባ ከሆነ ለማን ‘ሊፈረድ’ ነው፡፡
ኮሚኩ ነገር ምን መሰላችሁ… ገና ሜዳ ሲገባ አራት፣ አምስት ጊዜ የሚያማትበው ተጫዋች ሀያ ደቂቃ ሳይሞላ የተጋጣሚውን ተጫዋች እግር ‘ቀልጥሞ’ ቀይ ካርዱን ይከናነባል፡፡ እኔ የምለው…“እንደው ደህና አድርጌ የምቀለጥመው እግር አመቻችትሀ አቅርብልኝ…” ብለው ነው እንዴ የሚለማመኑት!
እናላችሁ…ኮሚክ ነገር እኮ ነው…ስንኮርጅ እንኳን አያምርብንም፡፡ ‘ሰለጠኑ’ ብለን እየኮረጅናቸው ያሉ አገሮች እኮ ወጣቶቻቸውን ለመከላከል መአት ‘መጠበቂያ’ ህጎች አሏቸው፡፡ ህጎች በወረቀት የሰፈሩ ብቻ ሳይሆኑ በተግባርም የሚፈፀሙ ናቸው፡፡ “አሥራ ስምንት ዓመት ላልሞላቸው ታዳጊዎች መጠጥ አቅርበሀል…” ተብሎ የተጠየቀ ሰው አለ!  “ዕድሜሀ ሳይደርስ መጠጥ ስትጠጣ ተደርሶብሀል…” ተብሎ የተጠየቀ ታዳጊ አለ!
እናላችሁ…የአሥራ አምስት ዓመት ህጻናት የአስተማሪዎቻቸውን ‘የበጀት ጉድለት የሚሞሉባት’ አገር እየሆነች ነው፡፡
ለሁሉም ወላጆች በዓለም ቆንጆዎቹ ልጆች የእነሱ ልጆች ብቻ ናቸው፡፡ እናማ…የሚያጠፉት ይወደድላቸዋል፡፡ የሌላ ሰው ልጅ ሲያጠፋ ግን... አለ አይደል… “ምናለ ቢቆነጥጡት! ምናምን ይባላል፡፡ የራሳቸው ልጆች ሲያጠፉ ግን...“ቢያጠፋስ ምናለበት፣ ልጅ አይደለም እንዴ…” ምናምን ይባላል፡፡ እናማ…ዘንድሮ ነገሮችን የእኛ ልጆች ሲፈጽሟቸውና የሌሎች ልጆች ሲፈጽሟቸው የሚሰጣቸው ትርጉሞች የተለያዩ  ናቸው፡፡
ክብርና ምስጋና ልጆቻቸውን በተገቢው ስነ ስርአት ላሳደጉና ለሚያሳድጉ ወላጆች!
ስሙኝማ…መቼም በምንም ባህል ስለ አማቶች መአት ነገር ይባላል፡፡ እንደውም ከብዙ ትዳሮች መፍረስ ጀርባ ‘የአማቶች እጅ’ አለበት ይባላል፡፡ ባህር ማዶ ያሉት ወገኖቻችን ግን ከአማቶች ጋር ፍቅር የያዛቸው ነው የሚመስለው፡፡ ልክ ነዋ…ስንትና ስንት እናቶች ወልድው፣ አሳድገው፣ “ያውልህ ውሰዳት…” ብለው ሰጥተው በማረፊያቸው ጊዜ እንደገና የልጅ ልጅ “አሳድጉ…” እየተባሉ አይደል እንዴ የሚሄዱት!
የአማቶች ነገር ከተነሳ ይቺን ስሙኝማ…
ሰውየው ለጓደኛው እያማከረው ነው፡፡
“እባክህ ጭንቀት ይዞኛል፡፡”
“ምነው፣ ደህና አይደለህም እንዴ!”
“እኛ በሌለንበት አማቴን ጠላፊዎች ወሰዷት፡፡ 30,000 ዶላር ክፈሉ አሉን፡፡”
“አሀ… 30,000 ዶላር ከየት አመጣለሁ ብለህ ነው የተጨነክኸው!”
“እሱ አይደለም ያስጨነቀኝ፡፡”
“ታዲያ ምንድነው?”
“ገንዘቡን ካልከፈላችሁ መልሰን ቤት እናመጣታለን ስላሉኝ ነው፡፡”
አሪፍ አይደል! ስለ አማቶች ጭማሪ…
ባል ሆዬ ከሚስቱ ተጣልቶ ለጓደኛው እያማከረው ነው፡፡ “እናቴ ቤት እሄዳለሁ አለችኝ፡፡ እኔም… ዛቻ ነው፣ ቃል መግባትሽ ነው ብዬ ጠየቅኋት፣” ይለዋል፡፡ ጓደኝየውም “ምን ልዩነት አለው?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ባል ሆዬ ምን ቢል ጥሩ ነው… “ወደ እናቷ ተመልሳ የምትሄድ ከሆነ ይህ ቃል መግባት ማለት ነው፡፡ እናቷን እኛ ቤት የምታመጣ ከሆነ ግን ዛቻ ነው…”  አለና አረፈው፡፡
የአማቶች መብት አስጠባቂ ማህበር ነገር ይቋቋምልንማ!
እናላችሁ…ስለ ልጆች አስተዳደግ የምር መታሰብ ያለበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ ስለ ልጆቹ መጻኢ ህይወትና ስለነገው ህብረተሰብም ማሰቡ መልካም ነው፡፡ ልጆችን የሚያሳስቱ ነገሮች እየተበራከቱ ባሉበት ሰዓት ወላጆች ከልጆቻቸው ትንሽ ሻል ብለው ማሰብ የሚኖርባቸው አይመስላችሁም!
ይቺን ስሙኝማ…ህጻናት ወንድምና እህት እየተጫወቱ ነው፡፡ እናማ… እህትየው ብቻ ነች የምትጮኸው፡፡ ወንድሟ ምንም ነገር አይተነፍስም፡፡ እናትየውም… “ማሚቱ፣ አንቺ ብቻ ለምን ትጮሂያለሽ! እሱም አንዳንዴ ይናገር እንጂ…” ትላታለች፡፡ ህጻኗ ምን ብትል ጥሩ ነው… “እኔ አንቺ ነኝ፣ እሱ ደግሞ አባዬ ነው…”  ብላት አረፈች፡፡ በቃ ለእሷ የእናት ሥራ አባት ላይ መጮህ፣ የአባት ሥራ ደግሞ ዝም ብሎ ማዳመጥ ሆኗላ! አባት እኮ ዝም ብሎ የሚያዳምጥ እያስመሰለ በሆዱ ይሄኔ ስንትና ስንት እርግማን አውርዶባታል! “እኔ ሚስት አገባሁ ብዬ… ለካስ ያገባሁት ምላስና ሰንበር ነው!” ብሎ ሊሆን ይችላል፡፡ ቂ…ቂ…ቂ….
እኔ የምለው…“አጅሬ፣ እያስመሰልክ የልብህን ትናገራለህ!” ያላችሁኝ ወዳጆቼ…አልገባኝም፡፡ እንዴት ነው ነገሩ…“እንደ ሰዉ አንተም ታስመስላለህ…” “አስመሳይ ነህ…” ምናምን እያላችሁኝ ከሆነ… አለ አይደል…እስቲ ‘ስታተሴን’ መለስ ብዬ አየዋለሁ፡፡ ቂ…ቂ…ቂ… ወይ ‘ማስመሰል!’
እናማ…ልጆች ወደተሳሳተ መንገድ ከመሄድ የሚጠብቃቸው ህጎች በተግባር ላይ ይዋሉማ! “ከአሥራ ስምንት ዓመት በታች የተከለከለ…” የሚሉ አይነት ህጎች ‘ባዶ ቃላት’ መሆናቸው ቢበቃ አሪፍ ነው፡፡
ደህና ሰንብቱልኝማ!

  በመላው አሜሪካ ያሉ ተማሪዎች ባርነት በ19ኛው ክፍለ ዘመን የተወገደ ችግር መሆኑን ይማራሉ፡፡ ይሁንና በሚያሳዝን መልኩ፣ ከ150 ዓመታት በኋላ ዛሬም ችግሩ ሥር እንደሰደደ መሆኑን እንረዳለን፡፡ በእርግጥ ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውር በሚል ስሙንና መልኩን የቀየረ ቢሆንም፤ በአሜሪካና በመላው ዓለም አስከፊና የሰው ልጆችን መሠረታዊ ክብር የሚያዋርድ ወንጀል ሆኗል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ ጃንዋሪ 2015 ብሔራዊ የባርነትና የህገወጥ የሰዎች ዝውውር የሚወገዝበት ወር እንዲሆን አውጀዋል፡፡ አሜሪካ ህገ ወጥ አዘዋዋሪዎችን ለህግ የምታቀርብ ሲሆን፤ የችግሩ ሰለባዎችንም ከችግሩ እንዲያገግሙና መልሰው እንዲቋቋሙ ትረዳለች፡፡ ከዚህም በተጨማሪ መንግሥታችን የጤና ባለሙያዎች፣ የበረራ ሠራተኞችና ሌሎች በግሉ ዘርፍ የተሠማሩ ባለሙያዎች የህገወጥ ዝውውር ሰለባዎችን በተሻለ መልኩ መለየትና መርዳት የሚችሉበትን ሥርዓት ዘርግቷል፡፡
አሜሪካ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ አጋሮችና የሃይማኖት ተቋማት ጋር በመሥራት ህገወጥ የሰዎች ዝውውርን በማስወገድ ዙሪያ የሚደረጉ ጥረቶችን ትደግፋለች፡፡ በዚህ ረገድ የህገ ወጥ ዝውውር ሰለባዎችን ለመጠበቅ፣ ወንጀሉን ለመከላከልና አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ አዳዲስ አሠራሮችን በመደገፍና ተጎጂዎችን አቋቁሞ ራሳቸውን እንዲችሉ በማድረግ ዙሪያ ከእነዚህ አጋር ድርጅቶች ጋር እንሠራለን፡፡
ዘመናዊ ባርነት በዓለማችን ላይ በየትኛውም ሥፍራ ሊከሰት የሚችል በመሆኑ መንግሥታት፣ የንግድ ድርጅቶችና ደንበኞቻቸው ችግሩን የመከላከል የጋራ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ ዓለም አቀፉ የሥራ ድርጅት (ILO) ከ20 ሚሊዮን በላይ ሰዎችን በማሠማራት፣ ህገወጦች 150 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ህገ ወጥ አሠራር ትርፍ እንደሚያገኙ በሪፖርቱ አመልክቷል፡፡  
ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውርን በአቅርቦት ሰንሰለት ላይ መግታት የሸማቾችንም የነቃ ተሳትፎና የግሉን ዘርፍ መሪዎች አጋርነት የሚጠይቅ ነው፡፡ ፕሬዚዳንት ኦባማ፡-“እያንዳንዱ ዜጋ ችግሩን በማጋለጥና የሚለብሰው ልብስ፣ የሚበላው ምግብና ማናቸውም ለሽያጭ የሚቀርቡለት ሸቀጦች ከጉልበት ብዝበዛ በፀዳ መንገድ መመረታቸውን ማረጋገጥ ይችላል” ሲሉ አሳስበዋል፡፡ የንግድና ለትርፍ ያልተቋቋሙ ድርጅቶች መሪዎችም የአቅርቦት ሰንሰለቶቻቸው ከጉልበት ብዝበዛ መፅዳታቸውን በማረጋገጥ ባርነትንና ግዞትን መከላከል እንደሚችሉም ጠቁመዋል፡፡
የአሜሪካ መንግሥት ህገወጥ የሰዎች ዝውውርን በአሜሪካም ሆነ በዓለም ዙሪያ ከምንጩ ለማድረቅ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ በኢትዮጵያም የአሜሪካ መንግሥት፣ ከወርልድ ቪዥንና ከሜኖናይት የኢኮኖሚ ዕድገት አጋሮች ጋር በመተባበር “የህፃናት ጉልበት ብዝበዛን ለመዋጋት የተቀናጁ ኢትዮጵያውያን” በተሰኘ ፕሮጀክት በኩል ለጉልበት ብዝበዛና ለህገ ወጥ ዝውውር ተጋላጭ የሆኑ ወጣቶች ሰፋ ያለ የትምህርት ዕድል እንዲያገኙ በማስቻል ከፍተኛ እንቅስቃሴ አድርጓል፡፡ በተጨማሪም ፕሮጀክቱ ለህገ ወጥ ዝውውር ሊጋለጡ ይችላሉ ለተባሉ ህፃናት ቤተሰቦችም ድጋፍ ያደርጋል፡፡ ከአንድ ወር በፊት ከሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳዮች ሚኒስትር ክቡር አቶ አብዱልፋታህ አብዱላሂ ሐሰን ጋር በመሆን ወደ ደቡብ ኢትዮጵያ በተጓዝኩበት ወቅት ፕሮጀክቱ ህገ ወጥ ዝውውርን ከመዋጋት አኳያ እያበረከተ ያለውን ከፍተኛ አስተዋፅዖ ለማወቅ ችያለሁ፡፡ ባየሁትም አኩሪ ሥራ የተደነቅሁ ሲሆን፤ኢትዮጵያና አሜሪካ አስከፊ የሆነውን የህፃናት ጉልበት ብዝበዛን በጋራ በመዋጋት ያሳዩት ቁርጠኝነት በአርአያነት የሚጠቀስ እንደሆነም ተረድቻለሁ፡፡
በሌላም በኩል የአሜሪካ መንግሥት የህገወጥ ዝውውርን ችግር ከምንጩ ለማድረቅ ከዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት(IOM) ጋር በመተባበር “የማህበረሰብ ውይይት” የተሰኘ ፕሮግራም ያዘጋጃል፡፡ ፕሮግራሙ በኢትዮጵያ በታችኛው የማህበረሰብ ክፍል ህገ ወጥ ዝውውርን በመከላከል ላይ ያተኮረ ፕሮጀክት በማካሄድ ላይ ይገኛል፡፡ ይህ የማህበረሰብ ውይይት ፕሮግራም እያንዳንዱ ማህበረሰብ አባላቱና ነዋሪዎች ለችግሩ እንዳይጋለጡ በማስተማር የህገወጥ ዝውውር ሰለባዎች እንዳይሆኑ ያስችላቸዋል፡፡ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውርና ዘመናዊ ባርነት በአሜሪካና ኢትዮጵያን ጨምሮ በዓለም ዙሪያ በሚገኙ አጋር ሀገራት የተንሰራፋና ከፍተኛ ተፅዕኖ በማሳደር ላይ ያለ ችግር ሆኗል፡፡ ይሁንና ቀጣይነት ባላቸው የተቀናጁ ጥረቶች ህገወጥ አዘዋዋሪዎችን በመዋጋት ብቻ ሳይሆን ችግሩንም ከምንጩ በማድረቅ ተጨባጭነት ያለው ለውጥ ማምጣት እንደምንችል እንተማመናለን፡፡

አንድ አፈ-ታሪክ እንዲህ ይላል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ውብ ልዕልት ነበረች አሉ - ሁሉም የሚያደንቃት ናት፡፡ ግን ማንም ላግባሽ ያላት የለም፡፡ ንጉሡ አባቷ ተስፋ በመቁረጥ አፖሎ የተባለው አምላክ ዘንድ ሄደና አማከረው፡፡ አፖሎም፤ ሳይክ (Psyche) ልዕልቲቱ ወደ ተራራ መውጣት አለባት፡፡ የሐዘን ልብስም ትልበስ፡፡ እዚያም ብቻዋን ትተው፡፡ ቀኑ ከመንጋቱ በፊት አንድ እባብ ይመጣል፡፡ ያገኛታል፡፡ ያገባታልም፡፡”
ንጉሱ ታዘዘው፡፡ ሌሊቱን ሙሉ ልዕልቲቱ ባሏን ልታይ ስትጠብቅ ቆየች፡፡
የሞት ያህል በሚያስፈራ ሁኔታ ውስጥ በአሰቃቂ ቅዝቃዜ በድና መጠበቋን ቀጠለች! በመጨረሻ እንቅልፍ ወሰዳት፡፡
ስትነቃ በአንዳች ቆንጆ ቤተ መንግስት ውስጥ ንግሥት ሆና ራሷን አገኘች! በየማታው ባሏ ይመጣል፡፡ ኢሮስ ይባላል፡፡ ይገናኛታል (ፍቅር ይሰራሉ)፡፡ ግን አንድ ቃል ኪዳን አስገብቷታል፡- “ሳይክ፤ የምትፈልጊውን ሁሉ አደርግልሻለሁ፡፡ ግን ፊቴን መልኬን አታይም፡፡ ሳታይኝ ሙሉ በሙሉ ልታምኚኝ! ይገባል፡፡” ወጣቷ ያላትን ፈፅማ ለረዥም ጊዜ በደስታ ኖረች፡፡
ምቾት አላት፡፡ መወደድ አላት፡፡ ደስተኛ ናት፡፡ በየማታው ከሚጎበኛት ሰው ጋር ፍቅር ይዟታል! ግን አንዳንዴ ከእባብ ጋር የተጋባች የተጋባች ይመስላታል! አንድ ጧት ማለዳ ላይ፤ ባሏ ተኝቶ ሳለ ፋኖሱን ለኮሰችና ባሏን ኢሮስን መልኩን አየችው፡፡ ወደር የሌለው ቁንጅና ያለው ወንድ ነው፡፡ ከጎና ተኝቷል፡፡ የፋኖሱ ብርሃን ቀሰቀሰው፡፡
ያፈቀራት ሴት፤ አንድዬ አደራውን አለማክበሯን አይቶ ኢሮስ ላንዴም ለሁሌም ተሰወረ፡፡ ልዕልቲቱ ባለ በሌለ ኃይሏ ፍቅረኛዋን ዳግም ለመመለስ ስትፍረመረም አፍሮዳይት የተባለች የባሏን እናት አግኝታ ጥፋቷን አምና ለመነቻት፡፡ ከእንግዲህ ብዙ ልትፈፅማቸው የሚገቡ ነገሮች እንዳሉ አውቃ፣ ተቀብላ ልትኖር ቃል ገባች፡፡
ምራቷ ግን በልዕልት ውበት ቅናት ይዟት ኖሮ፤ የሁለቱን ፍቅረኞች ዳግም መገናኘት ለመቀልበስ/ ለማነቀፍ ያልፈነቀለችው ድንጋይ አልነበረም፡፡ ልዕልት ሳይክ፤ በተቀበለችው የቤት ስራ መሰረት አንድ ሳጥን ከፈተች፡፡ ለካ ያ ሳጥን ከባድ እንቅልፍ የሚያስወስድ አስማታዊ ሚስጥር ኖሮታል፡፡ ድብን አድርጎ እንቅልፍ ወሰዳት፡፡
መቼም ሳይደግስ አይጣላምና ኢሮስ ደግሞ ከባድ ፍቅር ይዞት ኖሮ እጅግ አድርጐ ተፀፅቷል፡፡ እንደምንም ብሎ ወደ ቤተመንግስቱ ህንፃ ገብቶ ሚስቱን በቀስቱ ጫፍ ጭሮ ቀሰቀሳት፡፡ “በማወቅ ጉጉትሽ ምክንያት ሞት አፋፍ ደርሰሽ ተመለስሽ” አላት፡፡ ዕውቀት ስር መጠለል ሽተሽ ግንኙነታችንን ገሥሠሽ አጠፋሽ! ቃልኪዳንሽን ሰበርሽ! ሆኖም በፍቅር ዓለም ምንም ነገር ለዘለዓለም አይጠፋም፡፡
ባልና ሚስቱ በዚህ ዕምነት ተይዘው/ተጠርንፈው ወደ ዚዑስ ሄዱ፡፡ ፍቅራቸው ከእንግዲህ እንዳይጠፋ ለመኑ፡፡ ዚዑስ ከብዙ ክርክርና ሙግት በኋላ የአፍሮዳይትን ምክር አገኘ፡፡ ከዚያን ቀን ወዲህ ሳይክ (የአንጎላችን አላዋቂ (unconscious) ግን አመክኖአዊ ወገን) እና ኢሮስ (ፍቅር) በደስታና በተድላ ለዘለዓለም ኖሩ!”
በዚህ ታሪክ መሰረት፤ “ይህንን የማይቀበሉና አስማታዊና ሚስጥራዊ ለሆነው የሰው - ልጅ ግንኙነት ማብራሪያ ለማግኘት የሚሹ ሁሉ፤ እንደሳይክ የህይወትን ምርጥ ክፍል ያጣሉ!” የሚባለው ለዚህ ነው፡፡
ሳይክ፤ በሆዷ እንዲህ አለች፡-
“አንድ ቀን ቤተ መንግሥት ውስጥ እነቃለሁ! የምፈልገው አንድ ነገር፤ ጊዜ ብቻ ነው!”
*          *          *
በዓለማዊው ህይወታችን ሳያዩ ማመን ከባድ ነው፡፡ ባሌ እባብ ሊሆን ይችላል ብሎ መኖርም ከባድ ነው! እርግጥ፤ “አንድ ቀን ቤተ መንግሥት ውስጥ እነቃለሁ” ብሎ ማሰብ ይቻላል፡፡ ግን ድካም አለበት፡፡ በቀስት ተጭሮ እንደመንቃት ቀላል አይደለም፡፡ ቃልኪዳንን መጠበቁን ይጠይቃል፡፡ ለማወቅ ጉጉት ለከት ማበጀትም ይፈታተናል፡፡ በልጦ መገኘትን ጠንቅቆ መቻል እንደው ያለጥረት የሚገኝ፣ ክብሪት እንደመጫርም የቀለለ፣ የዘፈቀደ ነገር አይደለም፡፡ በሀገራችን ተፎካካሪን በልጦ መገኘት እጅግ አዳጋች፣ የቋጥኛማ ተራራ ያህል የማይዘለቅ ችግር ሆኖ ከቆየ ሰነባብቷል፡፡ አንድ ፀሃፊ እንዳለው፤ “እያንዳንዱ ሰው ትንሽ ትንሽ ዘውድ በኪሱ ይዞ ስለሚዞር “ውይይቱም፣ ድርድሩም፣ ፉክክሩም ሌላውን በማጥፋት ወይም በመጥለፍ ላይ የተመሰረተ ይሆንና ጤናማ ጉዞ አይሆንም፡፡ ጥንትም እንደዚያው ነበር፤ አሁንም ቅኝቱን አልቀየረም፡፡ በዚህ ቅኝት ላይ የመከፋፈል ዜማ ሲጨመርበት ለባላንጣ ሲሳይ የመሆን አባዜ ይከተላል፡፡ ማ ለምን ይህን አደረገ? ምን እየተጠቀመብኝ ነው? ብሎ ማሰብ ያባት ነው!
ተፈጥሮውን ማሳየት የሚበጀው / የሚያዋጣው አንዳንዴ ብቻ ነው፡፡ ከተቻለ ቃናውን ዝቅ ማድረግ መማር አለብህ… ስትጀምር ብዙ ሳትጮህ መጀመር ነው፤ አዋጪው፡፡ የውድድር ዘዴ! “ከጥበብ ሁሉ ከባዱ ደደብነትህን መቼ እንደምትጠቀምበት ማወቅ ነው!” ይላሉ አዋቂ ፀሀፍት፡፡ ብዙ ከመንጫጫት፣ ሰብሰብ ብሎ የማሰብ፣ የማስተዋል ክህሎት ሊኖር ይገባል፡፡ ከተመክሮ ሁሉ ጥንቃቄን የሚፈልግ ተመክሮ የትግል ተመክሮ ነው፡፡ አምስት ዓመት ሙሉ ጊዜ ኖሮ በቂ ዝግጅት ማጣት አንድም ንዝህላልነት፣ አንድም አቅለ-ቢስ መሆን ነው ከማለት በስተቀር ምን ትርጓሜ ይኖረዋል? ራስን ለክፍፍል ማጋለጥ፣ የራስን ችግር ራስ አለመፍታት፣ የተፎካካሪን ስልትና ስትራቴጂ አለማስላት፣ የህዝብንና የሀገርን ፍላጐት አለማስቀደም፣ የመንገዶችን ኮረኮንችና ሊሾነት አለመለየት አባዜዎች ሁሌ እንደተፈታተኑን አሉ፡፡ ጠንካራነትን ብቻ ሳይሆን ደካማነትንም መገንዘብ ብልህነት ነው፡፡
”ደካማ ከሆንክ በማታሸንፈው ጦርነት ውስጥ ለክብርህ ብለህ አትዋጋ፡፡ ይልቁንም ማፈግፈግን እወቅ፡፡ ማፈግፈግ ጊዜ መግዛት ነው፡፡ ማገገሚያ ነው፡፡ ቁስልህን ማከሚያና ባላንጣህን ማዳከሚያ ነው፡፡ ቁልፉ ነገር ማፈግፈግን የኅይል ማፍሪያ መሳሪያ ማድረጉ ነው!”
ጉዞን በረዥሙ ማቀድ ሌላው የብልህነት ስልት ነው፡፡ “ዛሬ ካልተሳካ ሞቼ እገኛለሁ” ማለት ቢያንስ የዋህነት ነው! አጓጉል ፍዘትም ስስ ብልት መስጠት ነው፡፡ ፖለቲካ ማመዛዘንን፣ ጊዜ-መግዛትንና ፍጥነትን መሰረት የሚያደርግ “ሸቃባ ሚዛን” ነው ይባላል፡፡ ይሄን ልብ ማለት ግድ ነው፡፡ “ታሪክ ባሸናፊዎች የሚፃፍ ተረት ነው!” የሚባለውንም አለመርሳት ነው፡፡
ታዲያ ፀጋዬ ገ/መድህን በሼክስፒሩ ሐምሌት እንደሚለን፡-
“…ፈጥነህ ጠብ ውስጥ አትስጠም
አንዴ ከገባህበት ግን እጅህ ከባላንጣህ ይቅደም”
የሚለውን ሳንዘነጋ ነው፡፡ ሁሉም መስዋእትነት ይጠይቃል፡፡ መስዋእትነት እንደ ዴሞክራሲ ሁሉ ገጠመኝ አይደለም፡፡ ቀድመው መሰረትና እሳቤ የሚያበጁለት ነው፡፡
“አንተኛም ካላችሁ እንገንድሰው
መኝታ እንደሆነ ቀርቷል ካንድ ሰው!” እያልን የምናላዝንበትም ከቶ አይደለም፡፡ ሂደት ነው፡፡ መቀጠል አለበት፡፡ ዝምታ እንኳ መስዋእትነት የሚጠይቅበት ጊዜ አለ፡፡ ትግል በጥበብ የተሞላ መንገድ ነው! ካልበሰሉ በድፍረት ብቻ የሚወጡት የወጣት ስሜታዊነት ዘመቻ መሆኑ ቀርቷል፡፡ እንደ ፋሽን በወረት የሚያሸበርቁበት የገና ዛፍም አይደለም፡፡ ከጀመሩ በኋላ “ፉርሽ ባትሉኝ!” የሚባልበት ጨዋታም አይደለም! “ሰይ ብል ባንከረባብት” እያሉ ያሹትን የሚያጭዱበት ቁማርም መሆን የለበትም! “አርፋ ስጠኝ”፣ “አቫንስ ስጠኝ” እያሉ የሚጠባበቁበት አይደለም፡፡ ትግል መሰረቱ የፖለቲካ ክህሎት ነው፡፡ ያልተነገረ ያልተሰማ ነገር የለም፡፡ ከአንጃ እስከ ዋና መስመር፣ ከቀኝና ግራ መንገደኛ እስከ አምስተኛ-ረድፈኛ፣ ከውጪ ወራሪ እስከ ውስጥ ቦርቧሪ፣ ከአናርኪስት እስከ ዘውድ-ናፋቂ፣ ከገንጣይ-አስገንጣይ እስከ በታኝ-ከፋፋይ፣ ከጠባብ እስከ ትምክህተኛ፣ ከአኢወማ እስከ ሊግ፣ ከአንጋፋው ፎረም እስከ ብላቴናው ፎረም…” ስርዝ የኔ ድልዝ ያንተ፣ እመጫት የሷ፣ ሆያ-ሆዬ የሰፊው ህዝብ ስንባባል በኖርንበት አገር ትግል “ሁለት አንድ ዐይናዎች ተጋብተው ሁለት ዐይን ያለው ልጅ ወለዱ፡፡ ምነው ቢሉ፣ አንዱን ከእናቱ አንዱን ከአባቱ!” ብለው የሚገላገሉት አይደለም!? “ዋና የማይችል ባህር አይግባ፤ ትግል የማይችል ልፊያ አይውደድ” የሚባለው ተወዶ አይደለም፡፡ እሙናዊውን ዓለም እናጢን! ሁሌ ልጅ አንሁት - ልብ-እንግዛ!!


መንግስት መሰረተቢስ ውንጀላ ነው በሚል ያጣጥለዋል
የኢትዮጵያ መንግስት በአገሪቱ የግል ሚዲያ ላይ የሚያደርገው የተራቀቀ ጫና፣ ሚዲያዎቹ በመጪው ግንቦት ወር የሚካሄደውን ምርጫ በተመለከተ በሚሰሩት ዘገባ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ ምህዳሩን እያጠበበባቸው ነው ሲል ሂዩማን ራይትስ ዎች ገለጸ፡፡
መንግስት የግሉን ሚዲያ እንደ አንድ የታመነ የመረጃና የትንተና ምንጭ ሳይሆን እንደ ስጋት በመቁጠር የተጠና ጫና ያደርስበታል ያሉት የሂውማን ራይት ዎች የአፍሪካ ምክትል ዳይሬክተር ሌስሊ ሌፍኮው ሚዲያው በመጪው ምርጫ ቁልፍ ሚና መጫወት ቢኖርበትም፣ በአንጻሩ ግን በርካታ የአገሪቱ ጋዜጠኞች ምርጫን በተመለከተ በሚያቀርቡት ዘገባ ለእስር እንዳረጋለን የሚል ስጋት እንዳደረባቸው ገልጸዋል፡፡
መንግስት በአገሪቱ የግል ሚዲያ ላይ የሚያደርገው ጫና እየተባባሰ በመምጣቱ ባለፈው አመት ብቻ ስድስት የግል የህትመት ውጤቶች ተዘግተዋል፤ በ22 ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮችና አሳታሚዎች ላይ የወንጀል ክስ ተመስርቶባቸዋል፤ ከ30 በላይ ጋዜጠኞችም እስራትን በመፍራት አገራቸውን ጥለው ተሰደዋል ብሏል ሂዩማን ራይትስ ዎች ከትናንት በስቲያ ባወጣው ሪፖርት፡፡
“ጋዜጠኝነት ወንጀል አይደለም፣ የመገናኛ ብዙሃን ነጻነት ጥሰት በኢትዮጵያ” የሚል ርዕስ ያለው  ሪፖርቱ፣ የኢትዮጵያ መንግስት ላለፉት አራት አመታት ነጻ ዘገባን የሚያቀጭጩ ተግባራትን ሲፈጽም እንደቆየ ጠቅሶ፣ በእነዚህ አመታትም ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብታቸውን በመጠቀማቸው 19 ጋዜጠኞች መታሰራቸውንና 60 ያህሉም መሰደዳቸውን ገልጿል፡፡
ሂውማን ራይትስ ዎች በስደትና በአገራቸው የሚገኙ ከ70 በላይ ጋዜጠኞችን አነጋግሬ ያዘጋጀሁት ነው ባለው በዚህ ሪፖርቱ፣ በአገሪቱ አብዛኞቹ የህትመትና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች በመንግስት ቁጥጥር ስር እንደሚገኙ ጠቁሞ፣ ጥቂት የግል የህትመት ውጤቶችም እንዳይዘጉ በመስጋት ፖለቲካዊ ጉዳዮችን ሲዘግቡ በአብዛኛው በራሳቸው ላይ ሳንሱር እንደሚያደርጉ ጠቁሟል፡፡መንግስት በበኩሉ፤ ሂዩማን ራይትስ ዎች የሚያወጣቸው የነፃነትና መብት ጥሰትን የተመለከተ ሪፖርቶች መሰረተ ቢስ እንደሆነ በመግለፅ በተደጋጋሚ ማጣጣሉ ይታወቃል፡፡

           በኢትዮጵያ ተግባራዊ በመደረግ ላይ የሚገኙት የታክስ ፖሊሲዎችና ህጎች ከወቅታዊ አለማቀፍና አገራዊ ሁኔታዎች ጋር ተገናዝበው መሻሻል እንደሚገባቸው የፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ (የማህበራዊ ጥናት መድረክ) ጥናት  አመለከተ፡፡በመድረኩ አዘጋጅነት “የኢትዮጵያ የታክስ ፖሊሲና ህጐች ቅኝት” በሚል ርዕስ መድረኩ ያቀረበው ጥናታዊ ፅሁፍ እንደጠቆመው፤ የአገሪቱ የገቢ ግብርና የቫት ህጎች ከአስር አመት በላይ ያስቆጠሩ ቢሆኑም ጉልህ የማሻሻያ ለውጥ አልተደረገባቸውም፡፡ ከወር ደሞዝ ታክስ የማይከፈልበት 150 ብር ወይም ከአመት ገቢ 1800 ብር እንዲሆን ከአመታት በፊት የወጣው ህግ ከብር የመግዛት አቅም መሸርሸርና ከዋጋ ንረት ጋር ተያይዞ ከመጡ ለውጦች ጋር ተገናዝቦ አልተሻሻለም፡፡ አላግባብ ከፍተኛ የታክስ ክፍያ የተጣለባቸው ድርጅቶች ጉዳያቸው እንዲመረመር አቤቱታ ማቅረብ ከፈለጉ፣ በቅድሚያ ግማሽ ያህሉን ክፍያ እንዲፈፅሙ እንደሚገደዱና ለአቤቱታቸው ምላሽ ለማግኘት ረጅም ጊዜ እንደሚንገላቱ የጠቆመው ጥናቱ፤ ብዙውን ጊዜም የሚያገኙት ውሳኔ ፍትሀዊ  እንዳልሆነ ይነገራል ብሏል፡፡ የታክስ ኦዲትን አስመልክቶም የታክስ ኦዲት የሚደረገው ከ4 እና ከ5 አመት በኋላ ስለሆነ የተጠራቀመ የታክስ እዳ እንዲከፍሉ የሚወሰንባቸው ድርጅቶች ከፍተኛ ወለድም ጭምር እንደሚጫንባቸው ጥናቱ ገልጿል፡፡የንግድ ድርጅቶች የ‹‹ሀ›› ምድብ፣ የ‹‹ለ›› ምድብ በሚል የሚፈረጁበት አመታዊ የሽያጭ ገቢ  በዋጋ ንረት ሳቢያ የብር የመግዛት አቅም ተሸርሽሮ ሽያጫቸው ላይ ጭማሪ ቢያሳይም ህጉ ግን እንዳልተሻሻለም በጥናቱ ተጠቅሷል፡፡የ‹‹ሐ›› ምድብ ተብለው በሚፈረጁትና አመታዊ ሽያጫቸው እስከ 100 ሺህ ብር  በሆኑ ድርጅቶች ላይ የሚደረገው የታክስ ክፍያ አወሳሰንም ውስብስብና በግምት ላይ የተመሰረተ ነው ብሏል፡፡
ብዛት ያላቸው መመሪያዎች በስራ ላይ መዋላቸው በታክስ ከፋዩና አንዳንድ ጊዜም በግብር ሰብሳቢ መስሪያ ቤቱ ባለሙያዎች ግራ አጋቢ እንደሚሆኑ ያመለከተው ጥናቱ፤ በተለያዩ የግብር መሰብሰቢያ ቢሮዎች ወጥ የሆነ መረጃ ያለመኖር እንዲሁም  ባለሙያዎችም መረጃዎቹን የሚረዱበት አግባብ ወጥ አለመሆኑ እንዲሁም በህጉ ላይ የተቀመጠውና በተግባር የሚታየው የተለያዩ መሆናቸው እንደችግር ተጠቅሰዋል፡፡ጥናቱ በታክስ ፖሊሲና ህጎች ዙሪያ መሻሻል ያለባቸውን ነገሮች ያስቀመጠ ሲሆን በአጠቃላይ ግን በአገር ውስጥና በአለም አቀፍ ደረጃ ያሉ ለውጦችን ግምት ውስጥ ማስገባት እንደሚኖርበት ተጠቁሟል፡፡
 “ፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ” (የማህበራዊ ጥናት መድረክ) በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ጥናትና ምርምር እንዲሁም ሕዝባዊ ውይይቶችን የሚያካሂድ መንግስታዊ ያልሆነ አገር በቀል ድርጅት ነው፡፡

ተደጋጋሚ የቅጥር ማስታወቂያ ባወጣም ሠራተኛ ማግኘት አልቻልኩም ብሏል
በአመራር ደረጃ ላይ ያሉ ሠራተኞች የአመለካከትና የአቅም ችግር እንዳለባቸውም ገልጿል

   የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በያዝነው አመት ካጋጠሙት ችግሮች ሁሉ እጅግ የከፋው በርካታ ሠራተኞች በየጊዜው ከሥራ መልቀቃቸው መሆኑንን በመጠቆም ይህም በሚፈልገው መጠን ለመሥራት እንዳይችል እንቅፋት እንደሆነበት ተገለፀ፡፡ የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል፤ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከትናንት በስቲያ ባቀረቡት የስድስት ወራት እቅድ አፈፃፀም ሪፖርት ላይ እንደገለፁት፤ በበጀት ዓመቱ የተለያዩ ችግሮች የገጠሙአቸው ቢሆንም በጐላ መልኩ የሚጠቀሰው ግን በርካታ ሠራተኞች በየጊዜው መልቀቃቸው እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ ከሥራቸው በለቀቁ ሠራተኞች ምትክ ለመቅጠርና ክፍት የሥራ ቦታዎች ለማሟላት የቅጥር ማስታወቂያ በተደጋጋሚ ቢወጣም በሚፈለገው መጠንና ጊዜ የሰው ኃይል ከገበያው ለማግኘት አለመቻሉን ገልፀዋል፡፡ ችግሩን ለመቅረፍ ከፍተኛ ጥረት በመደረግ ላይ መሆኑን የገለፁት ሚኒስትሩ፤ ተደጋጋሚ የሥራ ማስታወቂያዎችን ማውጣትና ያሉት ሰራተኞች በተቻለ መጠን ስራዎችን በማካካስ እንዲሰሩ ማድረግ እየተወሰዱ ካሉት እርምጃዎች ተጠቃሽ እንደሆኑም ገልፀዋል፡፡ የሥራ ተቋራጮች
በውላችን መሰረት የግንባታውን ሥራ በተቀመጠው ጊዜ ያለማስኬድ ችግር አለባቸው ያሉት ሚኒስትሩ፤ የስራ ተቋራጮቹ በገቡት ውል መሰረት ስራዎቹን እንዲያከናውኑ ኃላፊነት እንዳለባቸው የማስገንዘብ ስራ እየሰሩ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡ ሚኒስቴር መ/ቤቱ በዋናነት ከኮንስትራክሽን ፕሮጀክቶች አፈፃፀም መጓተት ጋር በተያያዘ የተመደበለትን በጀት በተሟላ መልኩ መጠቀም አለመቻሉን ሚኒስትሩ በሪፖርታቸው ላይ ገልፀዋል፡፡