Administrator

Administrator

ቫይረሱ በትንፋሽ መተላለፍ ሊጀምር እንደሚችል ተሰግቷል

በምዕራብ አፍሪካ አገራት ተከስቶ ከ22 ሺህ በላይ ሰዎችን ያጠቃውና ወደ 9 ሺህ የሚደርሱትንም ለህልፈት የዳረገው የኢቦላ ቫይረስ፣ ባህሪውን እየለወጠ እንደሚገኝና ለውጡ ቫይረሱን ከሰው ወደ ሰው በቀላሉ መዛመት እንደሚያስችለው ለማወቅ  ጥናት እየተካሄደ  መሆኑን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የፈረንሳዩን ፓስተር ኢንስቲቲዩት ተመራማሪዎች ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ቫይረሱ የቀድሞ ባህሪውን እየለወጠ እንደሚገኝ የተረጋገጠ ሲሆን ተመራማሪዎቹ የቫይረሱ የባህሪ ለውጥ የከፋ አደጋ የሚያስከትል መሆኑን ለማወቅ  በጊኒ፣ በቫይረሱ በተጠቁ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የደም ናሙና ላይ ምርምር እያደረጉ ይገኛሉ፡፡
የተመራማሪ ቡድኑ አባል የሆኑት ዶክተር አናቫይ ሳኩንታቢ እንዳሉት፤ የኢቦላ ቫይረስ በሚገርም ሁኔታ የተፈጥሮ ባህሪውን እየቀየረ እንደሚገኝ በጥናታቸው አረጋግጠዋል፡፡ ቫይረሶች በጊዜ ሂደት የተፈጥሮ ባህሪያቸውን መቀየራቸው የተለመደ ክስተት ነው ያሉት ዶክተሩ፣ ኢቦላም እንደ ኤች አይቪ ኤድስና ኢንፍሉዌንዛ ቫይረሶች ሁሉ በከፍተኛ ሁኔታ የባህሪ ለውጥ የማካሄድ ተፈጥሯዊ ባህሪ እንዳለው ተናግረዋል፡፡ ይህም ቫይረሱ ከሁኔታዎች ጋር የመላመድ አቅሙን ከፍ እንደሚያደርገውና የበለጠ ሊስፋፋ ይችላል የሚል ስጋት እንደፈጠረ አክለው ገልጸዋል፡፡
ቫይረሱ በርካታ ሰዎችን እያጠቃና የባህሪ ለውጡን እየቀጠለ ከሄደ፣ በትንፋሽ የመተላለፍ ዕድል ሊኖረው ይችላል የሚል ስጋት መኖሩን የተናገሩት ተመራማሪዎቹ፣ ይህም ሆኖ ግን ለጊዜው ቫይረሱ በትንፋሽ እየተላለፈ እንደሚገኝ የሚያረጋግጥ ምንም አይነት ተጨባጭ ማስረጃ አለመኖሩን ገልጸዋል፡፡
በተያያዘ ዜና የአለም ባንክ ፕሬዚደንት ጂም ያንግ ኪም፤ አለማችን በቀጣይ ሊከሰቱ ለሚችሉ ኢቦላን የመሳሰሉ ገዳይ በሽታዎች ይህ ነው የሚባል ዝግጅት አለማድረጓንና ይህም ከፍተኛ ጥፋት ሊያስከትል እንደሚችል አስታወቁ፡፡
መንግስታት፣ የእርዳታ ድርጅቶች፣ አለማቀፍ ተቋማትና ኩባንያዎች ወደፊት ሊከሰቱ የሚችሉ የገዳይ በሽታዎች ወረርሽኞችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር እጅ ለእጅ ተያይዘው መስራት ይገባቸዋል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ በምዕራብ አፍሪካ አገራት ከፍተኛ ጥፋት ካደረሰው የኢቦላ ወረርሽኝ በመማር አለም ከወዲሁ ዝግጅት ማድረግ ይጠበቅባታል ብለዋል፡፡

የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው አውሮፕላኖችንና መንገደኞችን በማስተናገድ በአለማችን ከሚገኙ አውሮፕላን ማረፊያዎች የመጀመሪያውን ደረጃ መያዙን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡
በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2014 ዓ.ም 70 ነጥብ 47 ሚሊዮን መንገደኞችን ያስተናገደው የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ፣ ከዚህ በፊት በርካታ መንገደኞችን በማስተናገድ ቀዳሚነቱን ይዞ የቆየውን የለንደኑን ሄትሮው አውሮፕላን ማረፊያ በመብለጥ በአንደኝነት መቀመጡን ዘገባው አስታውቋል፡፡
የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ስራ አስኪያጅ ሼህ አህመድ ቢን ሰኢድ አል መክቱም እንደገለጹት፣ በርካታ አለማቀፍ በረራዎችን በማስተናገድ የሚታወቀው አውሮፕላን ማረፊያው የሚያስተናግዳቸውን መንገደኞቹን ቁጥር ባለፉት አምስት አመታት በኣማካይ በሁለት ዲጂት እያሳደገ መጥቷል፡፡
አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው ዱባይን የአለማቀፍ የአየር በረራ ማዕከል የማድረግ ግቡን ወደ ማሳካት እየተቃረበ ነው ያሉት ስራ አስኪያጁ፣ በተያዘው የፈረንጆች አመትም የመንገደኞቹን ብዛት በከፍተኛ ሁኔታ ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
የአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ፖል ግሪቭስ በበኩላቸው፣ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው አዲስ የበረራ ማስተናገጃ በመክፈት፣ አመታዊ የመንገደኞች ማሰተናገድ አቅሙን በያዝነው የፈረንጆች አመት 90 ሚሊዮን ለማድረስ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡
ከዚህ ቀደም በርካታ መንገደኞችን በማስተናገድ በቀዳሚነት ይጠቀስ የነበረው የለንደኑን ሄትሮው አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ በ2014 ያስተናገዳቸው መንገደኞች ቁጥር 68.1 ሚሊዮን እንደነበር ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡

የአፍሪካ ህብረት የአህጉሪቱን ርዕሰ መዲናዎች በመንገድ፣ በባቡርና በአየር በረራ ማስተሳሰር ያስችላል የተባለ ትልቅ ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ ከቻይና መንግስት ጋር የትራንስፖርት የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረመ፡፡
ከቻይና ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዚያንግ ሚንግ ጋር የመግባቢያ ስምምነቱን የተፈራረሙት የህብረቱ ሊቀመንበር ንኮሳዛ ድላሚኒ ዙማ፣ ባለፈው ማክሰኞ በአዲስ አበባ የተፈረመውን ስምምነት ህብረቱ እስካሁን ከአጋሮች ጋር ከተፈራረማቸው ስምምነቶች ሁሉ ጉልህ ስፍራ የሚሰጠው ነው ብለውታል፡፡
ዚያንግ ሚንግ በበኩላቸው፤ የመግባቢያ ስምምነቱ የምዕተ አመቱ ትልቅ ሰነድ ነው፣ በአየር በረራ መስክ የተፈረመው ስምምነትም በአፍሪካ ህብረት እና በቻይና መካከል ያለውን ትብብር ወደ አዲስ መስክ ያሰፋ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከአንደኛው የአፍሪካ ክፍል ወደ ሌላኛው ለመጓዝ የተሻለ አማራጭ ተደርጎ የሚወሰደው የአውሮፓን የበረራ መስመር የተከተለ አካሄድ ነው ያሉት ሚንግ፣ አህጉሪቱ ሰፊ እንደመሆኗ በአውሮፓ የበረራ መስመሮች ላይ ጥገኛ ያልሆነና አገራቱን በቀላሉ የሚያስተሳስር የራሷ የትራንስፖርት አውታር ሊኖራት ይገባል ሲሉ መናገራቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

አሜሪካ በኩባ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ እንዳትገባ ያስጠነቀቁት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ራኡል ካስትሮ፤ መሰል ጣልቃ ገብነቶች በሁለቱ አገራት መካከል እንደገና የተጀመረውን ግንኙነት ትርጉም አልባ ያደርጉታል ሲሉ  መናገራቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡ ከ40 አመታት በኋላ ኩባን በመጎብኘት የመጀመሪያው የአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ረዳት ጸሃፊ ሮቤርታ ጃኮብሰን ባለፈው ሳምንት አገሪቱን መጎብኘታቸውን ተከትሎ ፕሬዚዳንት ራኡል ካስትሮ የአሜሪካ አካሄድ በኩባ ላይ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጫና ለመፍጠር ማሰቧን ያመላክታል  ብለዋል፡፡
አሜሪካ ይህንን አካሄዷን የማታስተካክል ከሆነ በሁለቱ አገራት መካከል እንደገና የተጀመረው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ትርጉም ያጣል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ አሜሪካ በውስጥ ጉዳያችን ጣልቃ ለመግባት የምታደርገውን ማንኛውም አይነት ሙከራ አገራቸው በዝምታ እንደማታልፈው አስጠንቅቀዋል፡፡
አሜሪካ በኩባ ውስጣዊ የፖለቲካ ተቃውሞን ለማቀጣጠል እያሴረች ነው ያሉት ራኡል ካስትሮ፣ ይሄም ሆኖ ግን ከዚህ የጣልቃ ገብነት ተግባሯ መታቀብ በምትችልበት ሁኔታ ዙሪያ ከአሜሪካ ጋር ለመምከር ፈቃደኛ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ አገራቸው በኩባ ላይ የጣለችውንና ለአስርት አመታት የዘለቀውን የኢኮኖሚ ማዕቀብ እንድታነሳ ጫና እንዲያሳድሩ ጥሪ ያቀረቡት ራኡል ካስትሮ፣ ኩባንያዎቿ በኩባ የቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ ላይ እንዲሰማሩ የፈቀደችው አሜሪካ፣ በሌሎች የኢኮኖሚ መስኮች ላይም እንደምትሰራ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል፡፡

   ቴለር ኤንድ ሰንስ የተባለው የእንግሊዝ ኩባንያ፣ የአገሪቱን ኩባንያዎች የመመዝገብ ስልጣን በተሰጠው ካምፓኒስ ሃውስ የተሰኘ የመንግስት ተቋም ላይ፣ ስሜን ሲመዘግብ የአንዲት ፊደል ግድፈት በመፈጸም ለተለያዩ ቀውሶች ዳርጎኛል ሲል በመሰረተው ክስ የ9 ሚሊዮን ፓውንድ ካሳ እንዲከፈለው ፍርድ ቤት እንደበየነ ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ፍርዱ የተላለፈበት የመንግስት አካል በአገሪቱ በኪሳራ ላይ የሚገኙ ተስፋ ቢስ ኩባንያዎችን በሚመዘግብበት ሰነድ ላይ፣ ከስድስት አመታት በፊት በማንችስተር የሚገኝን ቴለር ኤንድ ሰን የተባለ የከሰረ ኩባንያ ለመመዝገብ ፈልጎ፣ በስህተት የአንዲት ፊደል ግድፈት በመፈጸም ቴለር ኤንድ ሰንስ ብሎ በመመዝገቡና መረጃውን ለህዝብ ይፋ በማድረጉ ነው የኩባንያው ሃላፊዎች ክስ የመሰረቱበት፡፡
ኩባንያው ስሙ ተዛብቶ መመዝገቡንና በኪሳራ ላይ እንደሚገኝ የሚያሳየው መረጃ ለህዝብ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ 250 ሰራተኞቹ ስራ መልቀቃቸውን፣ የብድር አቅራቢ ተቋማትና 3ሺህ ያህል አቅራቢዎችም ከኩባንያው ጋር የነበራቸውን የስራ ግንኙነት ማቋረጣቸውን የኩባንያው ጠበቆች ተናግረዋል፡፡
በምህንድስና ስራ ላይ የተሰማራውና ከ100 አመታት ጀምሮ ወታደራዊ መሳሪያዎችን በማምረት የሚታወቀው  ቴለር ኤንድ ሰንስ ኩባንያ የቀድሞ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ፍሊፕ ዴቪሰን ሰብሪ፣ ከስድስት አመታት በኋላ የፊደል ግድፈቱ መከሰቱን ሰምተው ከሁለት ወራት በፊት ከኩባንያው አመራሮች ጋር ስብሰባ ማድረጋቸውንና ክሱን መመስረታቸውን ተናግረዋል፡፡
በእንግሊዙ ሮያል ኮርት ኦፍ ጀስቲስ ፍርድ ቤት ካሳ እንዲከፍል የተወሰነበት የመንግስት ተቋም በበኩሉ፣ የፊደል ግድፈቱን መፈጸሙን ቢያምንም፣ በኩባንያው ላይ ለፈጠረው ስህተት ይሄን ያህል ገንዘብ በካሳ እንዲከፍል የተጣለበትን ቅጣት ተቃውሟል፡፡

ፕሬዚዳንቱና 160 ባለስልጣናት ጥቁር መኪና ትተው ነጭ ሊሙዚን መጠቀም ጀምረዋል

 በመካከለኛው እስያ የምትገኘው ቱርክሜኒስታን፣ የአገሪቱ ዜጎች ከአሁን በኋላ ጥቁር ቀለም ያላቸው መኪኖችን ወደ ግዛቷ እንዳያስገቡ መከልከሏን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የቱርክሜኒስታን የጉምሩክ ባለስልጣናት፣ የአገሪቱ ዜጎች ጥቁር ቀለም ያላቸውን መኪኖች ከውጭ አገራት ገዝተው እንዳያስገቡ የሚከለክል ህግ ከሰሞኑ ይፋ ማድረጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለስልጣናቱ ክልከላውን በምን ምክንያት ተግባራዊ እንዳደረጉት ግልጽ አለማድረጋቸውን አስታውቋል፡፡
ባለስልጣናቱ ከውጭ አገራት መኪና ገዝተው የሚያስገቡ ኩባንያዎችን፣ ከጥቁር መኪኖች ይልቅ ነጭ ቀለም ያላቸውን መኪኖች እንዲያስገቡ እያግባቡ መሆኑን የጠቀሰው ዘገባው፣ ነጭ ቀለም የመልካም ዕድል ተምሳሌት እንደሆነ መግለጻቸውንም ጠቁሟል፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጉርባንጉላይ በርዲሞሃመዶቭ፤ ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ ጥቁር መኪና መጠቀም ማቆማቸውንና ህዝብ በሚሰበሰብባቸው ስፍራዎችም ነጫጭ ሊሙዚኖችን መጠቀም መጀመራቸውን ያስታወሰው ቢቢሲ፣ እሳቸውን ተከትለውም 160 ያህል የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት በነጭ ሊሙዚን መዘዋወር እንደጀመሩ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት የቅንጦት መኪና እንዳይገባ የሚከለክል፣ የተለየ ታርጋ ቁጥር መለጠፍና እይታን የሚጋርድ ሽፋን የተለጠፈባቸውን መኪኖች ማሽከርከር የሚያግድ እንዲሁም ሌሎች ከመኪኖች ጋር የተያያዙ ጥብቅ ህጎችን ማውጣቱንና ተግባራዊ በማድረግ ላይ እንደሚገኝም ዘገባው ያመለክታል፡፡

አንድ አፍሪካዊ የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ለብዙ ዓመታት በምዕራብ አገራት ትምህርቱን ሲከታተልና ሲያስተምር ቆይቶ ወደ ትውልድ ቀዬው ይመለሳል፡፡
የትውልድ መንደሩ እንደደረሰም አንድ የመንደር ልጅ ሃይቅ ዳር ቆሞ ይመለከታል፡፡ ልጁ ሰዎችን በታንኳ እያሳፈረ የዕለት ጉርሱን የሚቃርም ነው፡፡ ፕሮፌሰሩ ጀልባው ላይ ተሳፍሮ አፍታ እንኳን ሳይቆይ ልጁን በጥያቄ ያጣድፈው ገባ፡፡
ፕሮፌሰር ፡- ፍልስፍና አንብበሃል?
ልጁ ፡- አላነበብኩም
ፕሮፌሰር ፡- ከንቱ ነህ!
ፕሮፌሰር - ሥነ ልቦናስ አንብበሃል?
ልጁ፡- በፍጹም!
ፕሮፌሰር፡- ውዳቂ ነህ!
ፕሮፌሰር ፡- እሺ ታሪክስ?
ልጁ፡- አላነበብኩም
ፕሮፌሰር፡- ለምንም የማትሆን አልባሌ ሰው ነህ!
ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ አደገኛ ማዕበል ተነሳና ጀልባዋን እንደ ጉድ ይንጣት ጀመር፡፡
ፕሮፌሰሩ በታላቅ ፍርሃት እየራደ ልጁ እንዲረዳው ይጮህ ገባ፡፡ ልጁ ፕሮፌሰሩን በትዝብት እያየው፤ “ፕሮፌሰር፤ ዋና አልተማሩም?” ሲል ጠየቀው፡፡ (አሁን ከንቱው ማነው? በሚል ቅላፄ)

Saturday, 31 January 2015 12:48

ዝብርቅርቅ ጥያቄ

….. (እኔ ላንቺ ማሬ)
አበባ ሞልቶልኝ - ዕድሜዬን ቀጥፌ
ቄጤማ እያለ - እኔኑ አንጥፌ
ወፎች ስላልበቁኝ - ጥርሶቼን አርግፌ .....
እኔ ቀልጬልሽ -
ሜዳ ላይ ፈስሼ - ለፍቅሬ ሳበራ
በገዛ መብራቴ -
ልብሽ ሌላ ‘ያየ - ለግብዣ ከጠራ .....”
.
አይጣልብሽ አንቺው - ያ’ይምሮዬ ነገር
አንቺን እያሰብኩኝ - ትዝ የሚለኝ ሀገር
አሁን የኔን ነገር - ምን ይሉታል ማሬ?
ምን ያገናኝሻል - እስቲ አንቺን ካ’ገሬ?
“…..(እኔማ ላ’ገሬ - )
.
“ሀገሬ ተራራሽ” - እያልኩኝ ዘፍኜ
ያ ቀዳዳነቷን - በአፌ ደፍኜ
እየፆምኩ ስጸልይ - ለሀገሩ ጌታ
ሁሌ እያሰርኩኝ - ሁል ጊዜ ስፈታ ..... ”
.
ግድ የለሽም በቃ -
የምር አብጃለሁ - ሙች ለይቶልኛል
እንዴት “ሀገር” ሳስብ -
እግዜር ከነግርማው - ይደቀንብኛል?
.
“ ….(እግዜር ደ’ሞ እኔን - )
ደካማዋ ነፍሴ - ከእቅፉ ርቃ
ነገር ሲጋጭባት - ሺህ ጊዜ ጠይቃ
እሱ እንደሩቅ ሰው - ዝም - ጭጭ - በቃ
ይህን ጊዜ ነፍሴ - በሃሳቧ ደርቃ ....”
.
ገላጋይ እንቅልፌ - አፋፍሶኝ ይነጉዳል
ያ ባካኙ ልቤም - እንቅልፉን ይወዳል!
.
ማሬ
እኔና እግዜሩ - አንቺና ሀገሬ
ጥያቄዎች ነን - በልቤ ‘ስከዛሬ
ስላ’ንዳችን ሳስብ -
ሌላው ብቅ እያለ - እዛው ላይ ነኝ ዞሬ!!

    ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አይጥ ሁሌ እንደጉድ የሚጠላው ድመት ነበር አሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ህይወቱ ይረበሻል፡፡ መንፈሱ እረፍት ያጣል፡
አንድ ቀን ድንገተኛ አውሎ ንፋስ መጣ - በሀገሩ!
የትም መሄጃ ያጣው አይጥ፣ ለድመቶች ጥቃት ተጋለጠ፡፡
አይጥ እንግዲህ ወደ ከተማው ታዋቂ ጠንቋይ ሄደ፡፡ ችግሩንም አዋየው፡፡
ታላቁ ጠንቋይ ሁኔታውን በመገንዘብ፤ አይጡን ከአይጥነት ይልቅ ድመት ቢሆን ይሻለዋል፤ በሚል እሳቤ ወደ ድመት ለወጠው፡፡
ሆኖም አይጡ ወደ ድመት መለወጡ፣ ብዙ አልለወጠውም! የእንስሳት ባህሪ ሆኖበት ውሻን ክፉኛ መፍራት ጀመረ!
ይሄን ያስተዋለው አዋቂ ድመቱን ወደ ውሻ ለወጠው፡፡
ቀጠለና ያ ከድመትነት ወደ ውሻነት የተለወጠው እንስሳ፤ አሁን ደግሞ ነብርን መፍራት ተማረ!
ያ ታጋሽ አዋቂም፤ አስቦ አስተውሎ የድመቱን የመጨረሻ ደረጃ በመገንዘብና ትዕግሥት የበዛው በመሆኑ ነብር ላድርገው ብሎ ወሰነና ነብር አደረገው!
ያም ሆኖ ያ ነብር አዳኝ ቢመጣብኝስ? ብሎ ሥጋት በሥጋት ሆነ!
ይህንን ሁሉ ዕድል ሰጥቼው ካልተለወጠ የራሱ ጉዳይ ነው አለ፡፡ ከዚያም መልሶ ወደ አይጥነቱ መመለስ ዋናው ጉዳይ ነው! አለ!
ከዚያም አይጡ ወደ አይጥነት መመለሱ ግድ ሆነና ዛሬ አምነን ወደተቀበልነው አይጥ ተመለሰ!!
*   *   *
ማንነትን በማናቸውም አጋጣሚና አስገዳጅ ሁኔታ መለወጥ፣ የመርገምት ሁሉ መርገምት ነው! የትኛውንም ዓይነት ፍጡር እንሁን ብለን መከራን እናሳልፍ ብንል፤ ከተፈጥሮአችን ውጪ የረባ ፍሬ አናገኝም ወይም ልዩ ፍሬ አናተርፍም፡፡
አንድ ግብ ጋ ለመድረስ የግድ ሁለት የፍሬ ምንትነት መኖር የለበትም፤ በዚህም ሆነ በዚያ ዘመን፤ በዚህም ሆነ በዚያ ቦታና ወቅት ልናገኝ የምንችለውን ነገር በዛሬ ሽኩቻ አናክሽፈው! ከህብረት ውጩ መከፋፈል ፋይዳ የለውም፡፡
ሙግታችንና ክርክራችን ተሰብስቦ ሲታሰብ ጥቅሙ “በግልፅም መረጃ” መንፈስ ታላቅ ነው ሊባል ቢችልም፤ “ለማን እየጠቀመ ነው?” የሚባለውን አንድምታ አለማሰብ ከንቱ ቦታ ይጥለናል! የፓርቲዎች ሁሉ ውክቢያና “ጫጫታ” ስለምን በአሁኑ ወቅት ሆነ? ብሎ መጠየቅ የአባት ነው፡፡ ስለማንስ ጥቅም? “ምርጫ አያስፈልግም!” ከሚል አስተሳሰብ እስከ “ምርጫ ከተሳተፍን ግልፅ አቋም፣ ግልፅ ማንነት፣ ግልፅ ውክልና ሊኖረን ይገባል!” እስከሚለው ድረስ መወያየት አለብን ማለት አገራዊ ጥያቄ ነው! ስንተዋወቅ - አንተናነቅ ድረስ ማሰብ ቢቻል ግን መልካም ነው!
የምረጡና ካርድ ውሰዱ ውትወታ ስሜት፣ የወጣት እንቅስቃሴ (በድሮው አባባል የአኢወማ ግዳጅ)፣ የሴቶች ጥያቄ፣ ድህነት ቅነሳና ልማት… ወዘተ፡፡ የእስከ ዛሬው እያንዳንዱ መንግስት ተደጋጋሚ (Replica) ነገሮች ቢመስሉም፣ ዲሞክራሲ ሂደት እንጂ ቁርጥ ክፍያ ስላልሆነ “ባመጣህበት ውሰደው” የሚለው የነጋዴ ቋንቋ የግሎባላይዜሽን አንዱ ገፅታ ነው እንለዋለን!
መተቸትንና መተቻቸትን ለማይቀበል ሥርዓት፤ ይሄን ተቀበል፣ ይሄንን አትሻ ለማለት ብዙ እንግልት እንዳለበት፣ ስለ ዲሞክራሲ ብለህ ይሄን እሻ፣ ይሄን አትሻ ብሎ አጉል እሰጣ ገባ ውስጥ መግባት ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ ስለዲሞክራሲ፣ ስለፍትህ፣ ስለሰብዓዊነና ህዝባዊ መብት፣ ስለሙስና አደጋ ለማውራት የተገፋው፣ የተበደለውና መብት አጣሁ የሚለው ወገን ተናጋሪ፣ ካልሆነና ብሶቱን ካላስረዳ፣ በገዢው ፓርቲስ፣ በተቃዋሚስ ወገን ማን አቤት ይላል? “ሁሉም ፈረስ ላይ ከወጣ ማን ገደል ያሳያል?” የሚለው ተረት ቁምነገሩ ይሄው ነው ጎበዝ!


        ባለፈው ሚያዚያ የታሰሩት ሦስት ጋዜጠኞችና ስድስት የዞን ዘጠኝ ጦማሪዎች ላይ አቃቤ ህግ ያቀረበው የሽብር ክስ እንዲቀጥል ሰሞኑን በፍ/ቤት መፈቀዱ እንዳሳሰበው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የገለፀ ሲሆን፤ የክሱ ሂደት በግንቦቱ ምርጫ ተአማኒነትና ዲሞክራሲያዊነት ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ያሳድራል ሲል ነቀፈ፡፡ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሐሙስ እለት ባወጣው መግለጫ፤ በኢትዮጵያ የፀረ ሽብር ህጉ ላይ ቀጥተኛ ትችት ባይሰነዝርም፤ የህጉ አተገባበር ግን በህገመንግስት የተረጋገጡ የፕሬስ እና የሐሳብ ነፃነቶችን የሚቃረን እንደሆነ ጠቁሟል፡፡ ከዘጠኙ ጋዜጠኞችና የኢንተርኔት ፀሐፊዎች በተጨማሪ፣ ካሁን ቀደም ሌሎች ጋዜጠኞች፣ የፖለቲካ አንቀሳቃሾችና የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችም በፀረ ሽብር ህጉ እንዲከሰሱ መደረጋቸውን የሚኒስቴሩ መግለጫ አስታውሷል፡፡
ይህም፤ የህጉ አተገባበር፣ በህገ መንግስቱ የተረጋገጡ የፕሬስና የሃሳብ ነጻነቶች ላይ ጉልህ ጥያቄዎችን አስነስቷል ብሏል፡፡
የፕሬስ፣ የሃሳብ ነጻነቶች የአንድ ዲሞክራሲያዊ ማህበረሰብ መሰረታዊ ባህሪያት ናቸው ያለው መግለጫው፤ የኢትዮጵያ መንግስት ለእነዚህ ነጻነቶች መከበርና ለዲሞክራሲ ግንባታ ቁርጠኝነት እንዲያሳይ ጥሪ አቅርቧል፡፡
የዘጠኙ ጋዜጠኞችና የኢንተርኔት ፀሐፊዎች የፍርድ ሂደት ፍትሃዊነትና ግልፅነት የተላበሰ፣ እንዲሁም ከአገሪቱ ህገ መንግስቱና ከአለማቀፍ የሰብዓዊ መብት ስምምነቶች ጋር በማይጣረስ መልኩ እንዲካሄድም ሚኒስቴሩ በመግለጫው ጠይቋል፡፡ የፍርድ ሂደቱ ከፖለቲካዊ ተጽዕኖ የጸዳና ለህዝብ እይታ ክፍት እንዲሆን ማድረግ ይገባል ብሏል - መግለጫው፡፡