Administrator

Administrator

የጥናት ጽሁፎችን አደባባይ ለማውጣት ትኩረት ተሰጥቷል

 የኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር ከተቋቋመ ከ30 ዓመት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በነሐሴ ወር 1982 ዓ.ም ለንባብ የበቃችው “ብሌን” የሥነፅሁፍ መፅሔት ፤ ከ15 ዓመት የህትመት መቋረጥ በኋላ ሰሞኑን ታትማ ዳግም ለአንባብያን ቀረበች፡፡
የደራስያን ማህበር 50ኛ ዓመት ክብረበዓልን ምክንያት በማድረግ በሰኔ 2003 ዓ.ም የ“ብሌን” መፅሔት ልዩ ዕትም (ቁ.7) ለንባብ መብቃቱ ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ መደበኛው የመፅሄቷ ዕትም ለዓመታት ሳይታተም ቀርቷል፡፡ ከማህበሩ የ30 ዓመት ጉዞ በኋላ መጽሄቷ ብቅ ስትል ለኢትዮጵያ ሥነፅሁፍ ዕድገት እንደ አንድ ብስራት ቆጥረን ነበር ያሉት የአሁኗ የ“ብሌን” ዕትም አርታኢዎች፤ መፅሔቷ “ቅፅ 1፣ ቁጥር 1” መባሏ ቢያንስ ሁለት ወይም ከዚያ በላይ ዕትም በየዓመቱ ይታተማል የሚል ተስፋን የሚያመላክት ቢሆንም በማህበሩ የ24 ዓመት ታሪክ ውስጥ ከ7 የበለጠ የ“ብሌን” እትም ሊታተም አልቻለም ብለዋል፡፡
ለመፅሄቷ መቋረጥ ተጠያቂው ሁላችንም ነን በማለትም አርታኢዎቹ ኋላፊነቱን ለሁሉም አከፋፍለዋል፡፡ “… በመጀመሪያ ደረጃ የኢደማን አመራር ይዘው የነበሩትን ሁሉ የሚመለከት ቢሆንም የችግሩ አድማስ ግን ሁላችንንም የሚያካትትና ሁላችንንም በተለያየ የኃላፊነት ደረጃ የሚያስጠይቅ ነው፡፡” ሲሉም አስረድተዋል፡፡
አዲሱ የደራስያን ማህበር ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙሴ ያዕቆብ መፅሄቷ ላይ ባሰፈሩት መልዕክት፤ የጠንካራ ተሳታፊዎች እጦት፣ የህትመት በጀትና የደጋፊ ወገን እጥረት መፅሄቷ ወቅቷን ጠብቃ እንዳትወጣ ዋነኛ ተግዳሮቶቿ እንደነበሩ ጠቁመዋል፡፡
በአሁኑ የመፅሔቷ ዕትም ትኩረት የተደረገው በምርምር አምባው ተወስነው የነበሩ የጥናት ውጤቶችን ወደ “ብሌን” መድረክ በማምጣት አደባባይ ማውጣት ላይ ሲሆን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከተደረጉ ጥናቶች ውስጥ ሶስቱ (የስንቅነሽ አጣለ፣ የቴዎድሮስ ገብሬና የአራጌ ይመር) ተመርጠው እንደቀረቡ ተገልጿል፡፡
“የዚህ ዓይነቱ ሙከራ ወደፊት ተጠናክሮ እንዲቀጥልና ብሌን በምርምርና በፈጠራ፣ በሂስና በንድፈ ሃሳብ መካከል ድልድይ ሆና እንድታገለግል ምኞታችን ነው” ብለዋል፤ አርታኢዎቹ፡፡
በ108 ገፆች የተቀነበበችው “ብሌን” መፅሄት፤ ከጥናትና ምርምር ፅሁፎች በተጨማሪ አጭር ልቦለድና ግጥሞችን ያካተተች ሲሆን በ50 ብር ለገበያ ቀርባለች፡፡ መፅሄቷ በዓመት ሁለት ጊዜ እየታተመች ለአንባቢያን እንደምትደርስም ለማወቅ ተችሏል፡፡

Saturday, 14 February 2015 15:22

ጋሽ ስብሃት - የዛሬ 29 ዓመት

ታዬ፡-     አንዳንዶቹ የበዓሉ ግርማ ገጸ ባሕርያት ጋብቻን በሚመለከት … በተለይ በኪነት ዓለም ውስጥ ስሜት ያላቸውና የሚሳተፉቱ … ጋብቻን በጥርጣሬ ዓይን ነው የሚያዩት።  ለምን? ጋብቻን ከኪነት ስራቸው ጋር እንደሚፎካከር፣ እና እንደልቡ ለመሆን እንደማይችል ደራሲው… ለምን? ላገባት ሴት ጊዜውን መስጠት አለበትና ያ ደግሞ የፈጠራ ጊዜውን እንደሚሻማ አድርገው የሚናገሩ፣ የሚሰማቸው ገጸ ባህሪያት አሉ፡፡ እንዲህ ዓይነት ስሜት አንተ የለህም?
ስብሐት፡- እኔ እንደሱ አይሰማኝም፡፡ ግን ይገባኛል የነሱ ስሜት፤ በደንብ ይገባኛል … ምክንያቱም እውነት ነው፡፡ ሚስት የኪነትን ጊዜ፣ ሀሳብ፣ “ኢነርጂ”፣ ሁሉን ትሻማለች ሳይሆን ትጋራለች ብንል ነው ጥሩ፡፡
ታዬ፡-     ለምን?
ስብሐት፡- ሽምያ መነጣጠቅ ነው፡፡ መጋራት ግን የሷ ተራ ሲሆን ለሷ ጊዜህን ትሰጣለህ፡፡ የኪነት ተራ ሲሆን ለኪነት ጊዜህን ትሰጣለህ፡፡ እሷም ከተዋደድን ይሄ ይገባታል፡፡
ታዬ፡-     ስለዚህ የፈጠራ ስራውን ጋብቻ ሊያስተጓጉልበት አይችልማ?
ስብሐት፡- የፍቅር ጋብቻ ከሆነ አይችልም ነው የምለው፡፡ እንዲያውም ሴትዬዋ ብዙ ልታግዘው ትችላለች፤ ብዙ ልታበረታታው ትችላለች፡፤ ጉልበት ልትሆነው ትችላለች … ድክመት ሳይሆን፡፡
ታዬ፡-     ከበዓሉ ጋር ስለ ሥነ ጽሑፍ በምትወያዩበት ጊዜ ብዙ ልዩነት የታየበት ነጥብ አለ እስካሁን ድረስ? ለምሳሌ በዚህ ነገር ላይ እኔ አልስማማም የተባባላችሁበት አለ… ስለ ሥነ ጽሑፍ ባላችሁ አመላከከት?
ስብሀት፡- አዎ፡፡
ታዬ፡-     ምን ምንን በሚመስል ነገር?
ስብሐት፡- ቅድም ያልኩህ ነው … መነሻው ጥያቄ ሌላ ሆኖ ነው እንጂ፡፡ እሱ መጻፍ ስለምትችል ሳንሱር እንዲያልፍ እያሰብክ መጻፍ አለብህ … እና ማሳተም አለብህ፤ ልትነበብ ካልሆነ ለምን ትለፋለህ ያለኝ፡፡ እኔ ደግሞ ለሳንሱር ብዬ ከጻፍኩማ ምኑን ጻፍኩት? ለራሴ … እና በደንብ የሚሰማኝን ለመጻፍ፣ ለማውጣት ካልሆነ ምኑን ጻፍኩት ነው እንግዲህ ልዩነታችን፡፡
ታዬ፡-     ስለዚህ አንተ በምትደርስበት ጊዜ መጀመሪያ የምታተኩረው አድማጭህ ላይ ሳይሆን ራስህ …?
ስብሐት፡- አድማጩ ላይ ነው! አንባቢዬ ላይ ነው! ግን አንባቢዬ ሳንሱር አይደለም፤ ሰው ነው፡፡ እንጂ እንዲያውም አንባቢዬ ላይ ነው በጣም የማተኩረው፡፡ ተግባባን?
ታዬ፡-     አዎን፤ ገባኝ፡፡ ባንተ አስተያየት ደራሲው በሚጽፍበት ጊዜ ይሄ ሳንሱር ያልፋል፤ ይሄ ሳንሱር አያልፍም የሚለው ነጥብ አጻጻፉን ሊወስነው፣ ወይ ሊለውጠው አይገባም ነው?
ስብሐት፡- ልክ! እኔ ስጽፍ ይሄ ለአንባቢዬ ግልጽ አይሆንም፤ ይሄ ግልጽ ይሆናል … ስለዚህ እንደዚህ እያልኩ ነው፡፡ አንባቢ ነው ሀሳቤ ውስጥ ያለው፤ ሳንሱር የለም፡፡
ታዬ፡-     ስለ አንባቢ ካነሳን አልቀረ ምን ዓይነት አንባቢዎች ናቸው በአእምሮህ ውስጥ የሚጉላሉት… በምትደርስበት ጊዜ አንድን የሆነ ድርሰት፣ ልቦለድ? ለምሳሌ ወይ በመደብ፣ ወይ በትምህርት፣ ወይ በጾታ እንደዚህ ታስባቸዋለህ አድማጮችህን? … በዚህ ዓይነት አታያቸውም?
ስብሐት፡- እኔ የማስበው አንባቢዬ ከኔ እኩል ሊያስብ ይችላል፤ ከኔ እኩል ሊሰማው ይችላል፡፡ ስለዚህ እኔ ቃላቱን፣ አባባሉን አጥቼበት ካልሆነ በስተቀር አንባቢዬ አይስተኝም፡፡ ምክንያቱም እኔ ውስጥ ያለ ሁሉ አንባቢዬ ውስጥም አለ፡፡ ያው የሰው ነገር ስለሆነ የምጽፈው … ስለ ምኞት፣. ስለ ኩም ማለት፣ ስለ መውደድ፣ ስለ መጥላት፣ ስለ ተስፋ፣ እንደዚህ፣ እንደዚህ ስለሆነ ምንም ለአንባቢ የማይገባ ነገር አይኖርም፡፡ በቃ እኩያ ነን እኔና አንባቢዬ ማለት ነው፡፡ ስለዚህም ነው ምናልባት እኔ ላስተምር አይደለም የምጽፈው፤ ተረት ልነግር ነው እንጂ፡፡
ታዬ፡-     በዚህስ ነጥብ ላይ አትለያዩም? ለምሳሌ እሱ የስነ ጽሑፍ ሚና ህብረተሰብን ማስተማር …
ስብሐት፡- ነው ይላል እሱ፡፡
ታዬ፡-     ይላል? በዚህ ነጥብ ላይ ግን አትስማሙም?
ስብሐት፡- አንስማማም፡፡
ታዬ፡-     ለማስታረቅም አልሞከራችሁም? ያው እንደተለያየ ነው ያለው ሀሳባችሁ?
ስብሐት፡ አዎ! እርቅ ምን ያደርጋል? በዚህ በኩል እኮ ሲለያዩ ነው ጥሩ፡፡ እሱም የራሱን መንገድ ይይዛል፤ እኔም የራሴን፡፡ ሁለታችንም በየበኩላችን አስተዋጽዖ እናደርጋለን ማለት ነው፡፡
ታዬ፡- እንደዚያም ሆኖ ግን፣ ይህም የሀሳብ ልዩነት ኖሮ ትግባባላችሁ?
ስብሐት፡- በጣም!
(ከላይ የቀረበው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በትርፍ ጊዜ የሥነፅሁፍ ተባባሪ ፕሮፌሰርና የኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር የሥነፅሁፍ መፅሔት “ብሌን” ዋና አዘጋጅ ታዬ አሰፋ፤ የዛሬ 29 ዓመት የለንደን ዩኒቨርሲቲ ተማሪ ሳሉ ስለአማርኛ ልቦለዶች የትረካ ስልት ለሚያደርጉት ጥናት ከደራሲ ስብሃት ገ/እግዚአብሔር ጋር ያደረጉት ቃለምልልስ ሲሆን ሰሞኑን ከወጣው “ብሌን” መፅሔት የቀነጨበ ነው።)
ቅጽ 8፣ ቁ.፤  (ታህሣሥ 2007)

የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ደጋፊዎቻቸው ገንዘብ አዋጥተው በስማቸው በመሰረቱት ቤተ መቅደስ ውስጥ ባቆሙላቸው ጣኦት አማካይነት እየተመለኩ እንደሆነ የዘገበው ሮይተርስ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በበኩላቸው የደጋፊዎቻቸው ድርጊት እንዳስደነገጣቸውና አፈንጋጭ እንደሆነ መናገራቸውን አስታወቀ፡፡
በመቶዎች የሚቆጠሩት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ደጋፊዎች፣ ራጅኮት በተባለችው የህንድ ምዕራባዊ ከተማ በሰሩት ቤተ መቅደስ ውስጥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቁጭ ብለው የሚያሳይ ጣኦት አቁመው እያመለኩ እንደሚገኙ ተዘግቧል፡፡
“ነገሩ በጣም አስደንጋጭ ነው፡፡ ግለሰቦቹ የሰሩት ስራ ለዘመናት ከዘለቀው ታላቁ የህንድ ባህል ጋርም የሚጋጭ ነው፡፡ ባህላችን እንዲህ አይነት ቤተ መቅደሶችን እንድንሰራ አላስተማረንም” በማለት ድርጊቱን አውግዘውታል፤ጠቅላይ ሚኒስትሩ፡፡
በጠቅላይ ሚኒስትሩ ምላሽ የተከፉት የተወሰኑ የቤተ መቅደሱ ፕሮጀክት አስፈጻሚ አባላት በበኩላቸው፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጣኦት በአንድ የሂንዱ ፈጣሪ ሃውልት ለመተካት አቅደዋል፡፡
“ጠቅላይ ሚኒስትራችንን እንወዳቸዋለን፤ እናመልካቸዋለን፡፡ ምክንያቱም እሳቸው እስከዛሬ ከነበሩት መሪዎቻችን ሁሉ የተለዩ ትልቅ ሰው ናቸው!” ብለዋል፤ለቤተ መቅደሱ ግንባታ የዋለውን መሬት በነጻ ያበረከቱት ፓሬሽ ራዋል የተባሉ ህንዳዊ ባለጠጋ፡፡

Saturday, 14 February 2015 15:01

የኔ ወፍ

ቀኑ የኔን ሃሳብ
ውስጤን ከገለፀ
አንቺነትሽ በኔ
ገብቶ እንደሰረፀ
ሃሳቤን ልንገርሽ
የልቤን ስጦታ
አበባ ያንስሻል
‹ወይን› አይሰጠኝ ደስታ
ተመልከቺ ፍቅሩን
ያንቺን ልዩ ቦታ
ወስደሽ ከጣቴ ላይ
የደሜን ጠብታ፡፡

ትዝታ
ድምፅሽ ሲቀያየር
ሆነሽ አጠገቤ
ፍስስ የሚልብኝ
ቆራጥ ያልኩት ልቤ
ያልሆንኩትን ሆኖ
እኔነ ጠፍቶ
እያሰብኩኝ አንቺን
መናፈቄ በዝቶ
ሲቀያየርብኝ
መውደድና መጥላት
መከልከል መለገስ
መጨከን መራራት
ሲለዋወጥብኝ
ፈሪነት ደግነት
ታዝቤዋለሁኝ
ሲሰማኝ ውብ ደስታ
ትርጉሙ ፍቅርሽ ነው
ሰናይ ነው ትዝታ፡፡
(ከእስክንድር ለማ ክብረት
“የኔ ወፍ” የግጥም መድበል የተወሰደ፤
የካቲት 2007 ዓ.ም)

የዳንስ ውድድር፣ ኮሜዲ፣ የፍቅር ዜማዎች፣ እራትና ወይን ጠጅ
የሆቴሎቹ የመዝናኛ ክፍያ ከ600 ብር - 5ሺ ብር ይደርሳል

   በዛሬው ዕለት በመላው ዓለም የሚከበረውን የፍቅረኞች ቀን (Valentine’s day) ምክንያት በማድረግ አዲስ አበባን ጨምሮ በሃዋሳ ቢሾፍቱና ላንጋኖ የሚገኙ ትልልቅ ሆቴሎች ለፍቅረኞች ምሽት ሽርጉድ እያሉ ሲሆን ለለያዩ መዝናኛዎች ከ600 ብር እስከ 5ሺ ብር ይጠይቃሉ፡፡ የቀይ አልባሳት ገበያ መድራቱንም ነጋዴዎች ገልፀዋል፡፡
አትሌት ኃይሌ ገ/ሥላሴ ጐዳና ላይ የሚገኘው ንግስተ ሳባ ሆቴል ዛሬ ማታ ልዩ የፍቅረኞች ምሽት ያዘጋጀ ሲሆን የተለያዩ የፍቅር ዜማዎችና ግጥሞች ይቀርቡበታል ተብሏል፡፡ አርቲስት አስቴር በዳኔ የንግስተ ሳባን የፍቅር ታሪክ በአጭር ድራማና መነባንብ መልክ ለታዳሚዎች ታቀርባለች፡፡ ንግስተ ሳባ ሆቴል ከአብርሃም ግዛው ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት ጋር በመተባበር ባዘጋጁት በዚህ ልዩ የፍቅር ምሽት፤ በጥንዶች መካከል የሳልሳ፣ የትዊስትና ዋልዝ ዳንሶች ውድድር የሚካሄድ ሲሆን ለሶስት አሸናፊ ጥንዶች ለእያንዳንዳቸው አምስት ሺ ብር የሚያወጣ የእራት፣ የአልጋና የቁርስ ግብዣ ይደረግላቸዋል፤ ብሏል - ጋዜጠኛና ፕሮሞተር አብርሃም ግዛው በምሽቱ ዝግጅት የኮሜዲ ስራዎች የሚቀርቡ ሲሆን ፕሮግራሙን ታዋቂ አርቲስቶች ይታደሙታል ተብሏል፡፡
በማማስኪችን እንዲሁ የፍቅረኞች ምሽት የተዘጋጀ ሲሆን አንጋፋው ድምፃዊ አለማየሁ እሸቴ በስራዎቹ ታዳሚውን ያዝናናል ተብሏል፡፡ መግቢያ 50 ብር እንደሆነም ታውቋል፡፡ በቫራይቲ ሬስቶራንት የፍቅረኞች ምሽት ዛሬ 11፡30 የሚጀምር ሲሆን ልዩ የእራት ፕሮግራም፣ የዲጄ ሙዚቃ፣ ለጥንዶች የሚበረከት ሰርፕራይዝ ስጦታና ሌሎች ፕሮግራሞች መዘጋጀታቸው ተጠቁሟል፡፡
ኔክሰስ ሆቴል፤ ልዩ የቡፌ እራት ከልዩ ልዩ የወይን ጠጆች ጋር ያሰናዳ ሲሆን የቫዮሊንና የፒያኖ ሙዚቃ ይቀርባል፡፡ ሰርፕራይዝ ስጦታም ይኖራል ተብሏል፡፡ የብራይት ካፌ የፍቅረኞች ምሽት ፕሮግራም የሚጀምረው ዛሬ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ሲሆን ከ10 በላይ ድምፃዊያን በአኩስቲክ ባንድ ታጅበው ሥራዎቻቸውን ያቀርባሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ሳልሳ ዳንስ፣ ስታንዳፕ ኮሜዲና ሌሎች አዝናኝ ዝግጅቶች እንደሚኖሩ ታውቋል፡፡ ታዋቂው የፊልም ተዋናይ ግሩም ኤርሚያስና እውቁ የሙዚቃ አቀናባሪ ቴዎድሮስ መኮንን (ቴዲ ማክ) በክብር እንግድነት እንደሚገኙም ተጠቁሟል፡፡ በሳሮ ማሪያ ሆቴል ደግሞ ለፍቅረኞች ልዩ የእራት ፕሮግራም፣ ሰርፕራይዝ ስጦታዎችና ሌሎች ዝግጅቶች እንዳሉ ታውቋል፡፡
ሰሜን ማዘጋጃ አካባቢ የሚገኘውና ባለፈው አመት የተከፈተው ሳሬም ኢንተርናሽናል ሆቴል፤  ልዩ የፍቅረኞች ምሽት ያዘጋጀ ሲሆን የጥንዶች መግቢያ 600 ብር ነው፡፡  ሆቴል ሲዮናትም ልዩ የፍቅረኞች ምሽት ማዘጋጀቱን ጠቁሟል፡፡ ልዩ ልዩ የፍቅር ሙዚቃዎች በዲጄ የሚቀርቡ ሲሆን፤ የጥንዶች መግቢያ 900 ብር ነው ተብሏል፡፡ ከነአንካሬ ዛሬ ምሽት ከ12 ሰዓት ጀምሮ ነው በሩን ለፍቅረኞች ክፍት የሚያደርገው፡፡ ልዩ የብፌ እራት እንዲሁም የዲጄ ሙዚቃም አሰናድቷል፡፡
ሃዋሳ የሚገኘው ኬራውድ ሆቴል፤ ፕሮግራሙን ከዋዜማው ምሽት የጀመረ ሲሆን የዲጄ ሙዚቃ፣ ልዩ የወይን ጠጅ እንዲሁም ልዩ እራት በማሰናዳት ፍቅረኞች ዕለቱን መቼም  እንዳይዘነጉት ለማድረግ እየታተረ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡ የአዲስ አበባው ዩጐቪያ ክለብ በበኩሉ የምሽቱን ታዳሚዎች የሚያዝናናው ከተወዳጁ ድምፃዊ አብነት አጐናፍር ጋር እንደሆነ ገልጿል፡፡ ጥንዶች ይሄ የደመቀ የፍቅረኞች ምሽት እንዳያመልጣቸው የግብዣ ጥሪውን አቅርቧል፡፡
የቢሾፍቱው ፒራሚድ ሪዞርት፤ የጥንዶች ውድድርና የፍቅር ፊልሞችን ለታዳሚዎቹ ያዘጋጀ ሲሆን ልዩ እራት ከልዩ የወይን ጠጅ ጋር ማሰናዳቱንም ጠቁሟል፡፡ ሀርመኒ ሆቴልም እንዲሁ ሚካኤል ለማን ከኤክስፕረስ ባንድ ጋር አቀናጅቶ ምሽቱን ለፍቅረኞች ውብና አስደሳች ለማድረግ መዘጋጀቱን ጠቁሟል፡፡ በተጨማሪም ልዩ እራት ከወይን ጋር፣ የኮሜዲ ምሽትና የፍቅረኞች ስጦታ አዘጋጅቻለሁ ብሏል፡፡ በሃርመኒ ሆቴል ምሽቱን ለማሳለፍ ላቀዱ ጥንዶች 1800 ብር፣ ብቻውን ለመጣ 900 ብር ይከፍላሉ፡፡
በደብረዘይት የሚገኘው አሻም አፍሪካ ሪዞርት፤ ለምሽቱ ልዩ ራት ከዋይን ጋርና የዲጄ ሙዚቃ ያዘጋጀ ሲሆን በሪዞርቱ የፍቅረኞች ምሽትን ለመታደም የሚሹ ጥንዶች 219 ዶላር ወይም 4423 ብር ያስፈልጋቸዋል፡፡ ቦሌ የሚገኘው ፍሬንድሺፕ ሆቴልም የፍቅረኞችን ቀን አይረሴ ለማድረግ ዛሬ ከምሽቱ 12 ሰዓት ጀምሮ በሩን ለእንግዶቹ ክፍት እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡ የተለያዩ የፍቅር ዜማዎች፣ ሰርፕራይዝ ስጦታዎችና ሌሎች…ፕሮግራሞችም እንደሚኖሩ ገልጿል፡፡
ሳሚ ካፌና ሬስቶራንትም እንዲሁ ልዩ የፍቅረኞች ምሽት ማዘጋጀቱን ገልጿል፡፡ አኩስቲክ ባንድ ምሽቱን እንደሚያደምቀውና ዳዊት ፍሬውም ክላርኔት እንደሚጫወት ተጠቁሟል፡፡
ውሃ ልማት አካባቢ የሚገኘው ባለ አምስት ኮከቡ ካፒታል ሆቴል፤  ምሽቱን ለየት ለማድረግ የቀይ ምንጣፍ ልዩ የፍቅረኞች ምሽት ያዘጋጀ ሲሆን የሰባት ጥንዶች የዋልዝ ዳንስ ውድድርና ሙዚቃ አሰናድቷል፡፡ የፍቅረኞች ምሽቱን በሆቴሉ ለመታደም የሚሹ ጥንዶች 1800 ብር፣ ለብቸኛ ታዳሚ ደግሞ 1200 ብር እንደሚያስከፍል የገለፀው ሆቴሉ፤ እዚያው ተዝንተው፣ አድረውና ቁርስ አድርገው መውጣት ለሚፈልጉ 4500 ብር ይበቃቸዋል ተብሏል፡፡
ላንጋኖ ሪዞርት የፍቅረኞች ቀን ልዩ ዝግጅቱን የጀመረው ከትላንት በስቲያ ሲሆን ዛሬ  የአዝማሪ ሙዚቃ፣ የጀልባ ሽርሽር እንዲሁም ልዩ ልዩ ምግብና ወይኖችን መዘጋጀታቸውንና ጥንዶች 3600 ብር፣ ብቸኛ 1900 ብር እንደሚከፍል ተጠቁሟል፡፡ አፍሮ ዳይት ሆቴልም ልዩ የፍቅረኞች ምሽት እንዳዘጋጀ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የፍቅረኞች ቀንን አምነውበት ለሚያከብሩት ብዙ አማራጮች የተዘጋጁ ይመስላል፡፡ ነገር ግን ቫለንታይን የውጭ ባህል ነው በሚል የሚቃወሙትም አሉ፡፡
በ20ዎቹ መጨረሻ ዕድሜው ላይ የሚገኘው እስክንድር፤ የፍቅረኞች ቀን በአገራችን መከበሩን ከእነአካቴው አይቀበለውም፡፡ “ፍቅር በአደባባይ ልታይ ልታይ የሚባልበት ሳይሆን የልብ ትስስር ጉዳይ ነው” ያለው ወጣቱ፤ ቫለንታይን የአገራችን ባህል ስላልሆነ አልቀበለውም ባይ ነው፡፡ ቀይ መልበስና ሌሎቹም ነገሮች የእኛ አለመሆናቸውን ይናገራል፡፡ እንዲያም ሆኖ ፍቅረኛው ደሞ በቫለንታይንስ ዴይ ቀያይ ልብሶች ገዝቶ በስጦታ እንዲያበረክትላት ትፈልግ ነበር፡፡ ነገሩን ፈጽሞ ባላምንበትም ፍቅረኛዬን በጣም ስለምወዳት የማልፈልገውን አደረግሁ ብሏል፡፡  “ፍቅረኛዬ እንዳይከፋት ብዬ ቢያንስ ከውስጥ የሚውል ቀይ ፓንትና ጡት ማስያዣ ገዝቼ በስጦታ አበርክቼላታለሁ፡፡ ዋጋው ግን በጣም ውድ ነው” ሲል በመገረም ገልጿል፡፡
የ31 ዓመቱ አሳየኸኝ፤ ፍቅረኛው ለቫለንታይን እንዲገዛላት የጠየቀችው ስጦታ ዋጋው ናላውን እንዳዞረው ይናገራል፡፡ ባለፈው ዓመትም በከፍተኛ ዋጋ ምክንያት ከፍቅረኛዬ ጋር ተጋጭተን፣ ለሰባት ቀናት ተዘጋግተን ነበር ያለው አሳየኸኝ፤ “ዘንድሮም መጋጨታችን አይቀሬ ነው” ሲል የፍቅረኞች ቀን ስጋት እንደሆነበት ገልጿል፡፡
እየሰራሁ ገቢ ባገኝም እየከፈልኩ እማራለሁ፣ ወንድሜንም አስተምራለሁ የሚለው ወጣቱ፤ እንዲህ ያሉ ወጪች በእጅጉ ይጎዱኛል ብሏል፡፡ በሌላ በኩል በአሜሪካ የዘንድሮው ቫለንታይን ቀን ለስጦታ የሚወጣው አጠቃላይ 18.9 ቢ.ዶላር ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅና ይሄም በከፍተኛነት ወጪ ሪከርድ እንደሚሰብር ተገምቷል፡፡ ከዚህ ውስጥ 4.8 ቢ. ዶላር ያህሉ ለጌጣጌጥ ስጦታዎች እንደሚወጣ ሰሞኑን ይፋ የተደረጉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በቫለንታይን ቀን ከረሜላዎች፣ ፖስት ካርዶችና  አበቦች በስጦታነት ይበረከታሉ - የአልማዝ ቀለበትና ሌሎች ጌጣጌጦች ሳይረሱ ማለት ነው፡፡
በአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ስማቸውን መግለፅ ያልፈለጉ አንድ የስራ ኃላፊ ስለ ቫለንታይን ቀን አስተያየታቸውን ሲናገሩ፤ “ጉዳዩ ከፍቅር ጋር የተያያዘ በመሆኑ ቀኑ ቢከበር አይከፋኝም፤ አንዳንድ ነጋዴዎች ግን አጋጣሚውን በመጠቀም ትርፍ ለማግበስበስ የሚያደርጉት ሩጫ አያስደስተኝም” ብለዋል፡፡ ሴቶችም ቢሆኑ በዚህ ቀን ፍቅረኞቻቸውን ለአላስፈላጊ ወጭ በመዳረግ ማማረር የለባቸውም ሲሉ ይመክራሉ፡፡ “ውድ ስጦታ እንዲሰጣቸው ማስገደድ ፍቅርን ከማጠንከር ይልቅ ስለሚያሻክረው ጥንቃቄ ያሻል” ብለዋል፡፡ ሁሉም አምኖበት የሚያደርገው ከሆነ፣ አበባ፣ ቀይ ልብሶች የሚሸጡና የሆቴል አገልግሎት የሚሰጡ አጋጣሚውን በጤናማ መንገድ ገቢ ቢያገኙበት ክፋት እንደሌለው ጠቁመው፤ በዓሉ ወግና ስርዓት በጠበቀ መልኩ ቢከበር መልካም እንደሆነ አክለው ገልፀዋል፡፡

Saturday, 14 February 2015 14:48

የቫለንታይን ስጦታ)

የሻማ ብርሃን፣ የጨረቃ ብርሃን፣ የክዋክብት ብርሃን
      ከሁሉ ይበልጥ የሚፈካው ግን  የፍቅር
     ብርሃን፡፡
                ግሪይ ሊቪንግስቶን
ያንሾካሾክልኝ በጆሮዬ ሳይሆን በልቤ በኩል ነው፤ የሳምከውም ከንፈሬን ሳይሆን ነፍሴን ነው፡፡
ጁዲ ጋርላን
ልብ ምን ያህል እንደሚይዝ ማንም ለክቶት አያውቅም፤ ገጣሚዎችም ጭምር፡፡
ዜልዳ ፊትዝጌራልድ
ስለ አንተ ባሰብኩ ቁጥር ዘለላ አበባ ባገኝ፣ ዕድሜ ልኬን በመናፈሻዬ ውስጥ እጓዝ ነበር።
ክላውዲያ ጋንዲ
የማፈቅርሽ ውብ በመሆንሽ ነው ወይስ ውብ የሆነሽው ስለማፈቅርሽ ነው?
ኦስካር ሐመርስቴይን ሁለተኛ
ነፍሴ መድረስ በሚችልበት ጥልቀት፣ ስፋትና ቁመት  አፈቅርሃለሁ፡፡
ኤሊዛቤት ባሬት ብራውኒንግ
ከልቤ የምሻው ፍቅርን ብቻ ነው፤ አልፎ አልፎ ጥቂት ቸኮሌት ግን አይጎዳም፡፡
ሉሲ ቫን ፔልት
ህይወት አጭር ቢሆንም  ፍቅር  ረዥም ነው፡፡
አልፍሬድ ሎርድ ቴኒሰን
ቫለንታይንን የሚያህል ታላቅ ቅዱስ እንደሌለ አረጋግጣለሁ፡፡
ኦግዴን ናሽ
የመፈቀር ጸጋ አግኝቶ ማን የደኸየ አለ?
ኦስካር ዋይልድ
ነፍስና ነፍስ የሚገናኙት በፍቅረኞች ከናፍር ላይ ነው፡፡
ፔርሲ ባይሼ ሼሊ
ፍቅር በዳበሰው ጊዜ ሁሉም ገጣሚ ይሆናል።
ፕሌቶ

የተከበሩ ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ በጥርስ ህክምናው ዘርፍ የተሠማሩ ባለሀብት ሲሆኑ በ2002 ምርጫ ተወዳድረው በማሸነፍ በፓርላማ ብቸኛ የግል እጩ ሆነዋል፡፡ ዶ/ር አሸብር በፓን አፍሪካ ፓርላማ ውስጥ በም/ፕሬዚዳንትነት እያገለገሉም ይገኛሉ፡፡ በግንቦቱ ምርጫ ዙሪያ ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር የሚከተለውን ቆይታ አድርገዋል፡፡

በግንቦቱ ምርጫ በእጩነት ይወዳደራሉ?
በምርጫው ለመወዳደር ጓደኞቼ ፊርማ አሰባስበውልኝ ለቦርዱ አስገብተናል፡፡ ሙሉ ለሙሉ ተወዳዳሪነቴን የማረጋግጠው የእጩነት ደብተሬን ስወስድ ነው፡፡ ከእኔ  የሚጠበቀውን ሁሉ   አድርጌያለሁ፡፡
የት ነው የሚወዳደሩት?
በከፋ ዞን፣ ቦንጋ ዲንቦ ጓታ ምርጫ ጣቢያ ነው የምወዳደረው፡፡
የግል ተወዳዳሪ የመሆን ጥቅሞችና ፈተናዎች ምንድን ናቸው?
አብዛኛው ጊዜ ፓርቲዎች ሚዲያ ተጠቅመው ራሳቸውን የማስተዋወቅ እድል አላቸው። ቴሌቪዥን፣ ራዲዮ ይጠቀማሉ፤ ለምርጫው ከመንግስት በጀት ያገኛሉ፡፡ ለግል ተወዳዳሪዎች ግን እነዚህ ሁሉ የሉም፡፡ እኛ የግል ተወዳዳሪዎች በራሳችን ወጪ መቀስቀስ፣ በራሳችን የቅስቀሳ አውታር መጠቀም ስለሚጠበቅብን ብዙ ፈተና ውስጥ ነው ያለነው፡፡ አንድ ግለሰብ ለመወዳደር ሲፈልግ፣ በዚህ ደረጃ ራሱን ማዘጋጀት አለበት፡፡
ጥቅሞቹስ?
ራሱ ኢህአዴግን ብትወስድ አባላቱ ከ10 ሚሊዮን አይበልጡም፡፡ ከህዝቡ 70 እና 80 በመቶው የፓርቲ አባል አይደለም ማለት ነው። ስለዚህ ህዝቡ እኛን በቀላሉ መረዳት ይችላል፡፡ ከየትኛውም ፓርቲ ገለልተኛ መሆን ለአስተያየትም ለፍርድም ይጠቅማል፡፡ ብዙ ሰው ወደ ፓርቲ አይጠጋም፤ለዚህም ምክንያቱ ገለልተኛ መሆን ስለሚፈልግ ነው፡፡
የግል ተወዳዳሪ መሆን ትልቅ ጥቅም አለው፡፡ ግለሰቡ ራሱ በራሱ ነው ወሳኝ የሚሆነው፡፡ የፓርቲ ዲሲፒሊን ተብሎ የሚገዛበት ነገር አይኖርም፡፡ የምታስበውን ያመንከውን ትናገራለህ፤ታደርጋለህ። የፓርቲ ፕሮግራም ነው በሚል ያላመንክበትን በብዙኃኑ ተገዝተህ እንድታምን አይሆንም፡፡ ራስን ብቻ ነው የሚኮነው፡፡ ህዝቡም ራሱን ሆኖ የሚቀርብ  ይፈልጋል፡፡
 የተቃዋሚ ፓርቲዎችን እንቅስቃሴ እንዴት ያዩታል? በምርጫው ውጤት ያገኛሉ ብለው ይገምታሉ?
በኢትዮጵያ የምርጫ ታሪክ ህዝቡ ያገባኛል፣ የራሴ ጉዳይ ነው በሚል በስፋት ወጥቶ ድምፅ የሰጠው በምርጫ 97 ነው፡፡ ያኔ ህዝብ ለውጥ ማየት አለብኝ፣ ብሎ በተለይ የአዲስ አበባ ነዋሪ ለተቃዋሚዎች ሙሉ ድምፅ ሰጥቶ አሸንፈው ነበር። ሆኖም አስተዳደሩን አለመረከባቸው ዛሬ ገዥው ፓርቲ አብላጫውን ስልጣን እንዲቆጣጠር አስተዋፅኦ አበርክቷል፡፡ አዲስ አበባ ማለት ከአንድ አገር በላይ ነው፡፡ የአፍሪካ መዲና፣ የዓለም ተቋማት መቀመጫ ነው፡፡ አዲስ አበባን መያዝ ማለት ተፅዕኖው ከፍተኛ ነው፡፡ ያንን ይዘው ቢሆን ኖሮ ኢህአዴግ ዛሬ አውራ ፓርቲ አይሆንም  ነበር፡፡ አዲስ አበባ መሪ ስታጣ ህዝቡ፣ “ለካ ሊያስተዳድሩኝ አይችሉም” አለ፡፡ ገዥውም ፓርቲ ግለ ሂስ አድረገና ህዝቡም ተቀበለው፡፡ ከዚያ በኋላ ገዢው ፓርቲ ልማትን፣ መልካም አስተዳደርን በማስፈን ለመመረጥ ጥረት እያደረገ ነው፡፡ እውነቱን ለመናገር የኛ ተቃዋሚዎች መኖራቸውን የምንሰማው፣ አሁን ለመመረጥ ሲሯሯጡ ነው፡፡ ይሄ በቂ አይደለም፡፡ በአንድና ሁለት ወር ውስጥ ምን አቅርበው ሊመረጡ ነው? ይሄ ለህዝቡም ፈተና ነው የሚሆነው፡፡ ውጤቱን እንግዲህ ሲደርስ እናየዋለን፡፡
እርስዎስ  በምርጫው አሸንፈው ለሁለተኛ ጊዜ ፓርላማ የሚገቡ ይመስልዎታል?
ፓርላማ እንደምገባ አልጠራጠርም፡፡ ተመልሼ እመረጣለሁ የሚል እምነት አለኝ፡፡ እኔ ከራሴ ህዝብ ጋር ነው የቆየሁትም፡፡ በፊት ሳያውቀኝ የመረጠኝ አሁን መልዕክተኛወ ሆኜ የላከኝን ፈፃሚ መሆኔን ከመቼውም በበለጠ ያውቃል፡፡ ስለዚህ እመረጣለሁ ብዬ በእርግጠኝነት  መናገር እችላለሁ፡፡ በእርግጥ የምወዳደረው ከኢህአዴግም ከተቃዋሚዎችም ጋር ነው፡፡ እኔ ከዚህ በፊት ም/ቤት ስገባ ኢህአዴግን እንደማልቃወም፣ ገብቼም የኢህአዴግ ደጋፊ እንደምሆን ቃል ገብቼ ነው የተመረጥኩት፡፡ በእርግጥም አንድም ቀን ኢህአዴግን ተቃውሜ አላውቅም፡፡ በዚህ የተነሳ የገዥው ፓርቲ አባል ከእኔ ጋር ይወዳደራል ብዬ አልጠበቅሁም  ነበር፡፡ እኔ እኮ የአባሉን ያህል ስሰራ ነው የቆየሁት፤ ሃገርን ወክዬ በፓን አፍሪካ ፓርላማ የተቀመጥኩ ሰው ነኛ። ይሄ የፓን አፍሪካ ፓርላማ ቦታችንን ማስጠበቅ የምንችለውም እኔ በኢትዮጵያ ፓርላማ ውስጥ ስኖር ብቻ ነው፡፡ ኢህአዴግ ይሄንንም ከግምት ውስጥ የሚያስገባ መስሎኝ ነበር፡፡
 አሁን ስማቸውን የማልጠቅሳቸው ኃላፊ፣ ከኔ ጋር እንደማይወዳደሩ ሲናገሩ ነበር፡፡ አሁን ግን ወደ መወዳደሩ የገቡ ይመስለኛል፡፡ እኔ እንደገና ተመርጬ ፓርላማ ብገባም ኢህአዴግን አልቃወምም፡፡ በእኔ እምነት ኢህአዴግ ለሃገሪቱም ለህዝቡም ጥሩ ስራዎች ሰርቷል፡፡ ከዚህ አንጻር የእኔ ፓርላማ መግባት ድሮም አልረበሸውም፣ አሁንም የሚረብሸው አይመስለኝም፡፡ በፓን አፍሪካ ፓርላማ ኢትዮጵያ ያላትን ቦታ ለማስጠበቅ ያስችለኛል ብዬ ስለማስብ ነው ወደዚህ ምርጫ የገባሁት፡፡
ኢህአዴግን የማይቃወሙና በፖሊሲው የሚስማሙ ከሆነ ለምን አባል አይሆኑም?
ይሄን እኔን ከመጠየቅ ኢህአዴግን መጠየቅ ይቀላል፡፡ “ለምን ዶ/ር አሸብርን አባል አታደርገውም?”ተብሎ ቢጠየቅ፣ኢህአዴግ የራሱን መልስ ሊሰጥ ይችላል፡፡ እኔ ግን ኢህአዴግን ተቃውሜም አላውቅ፣ልቃወምም አልችልም፡፡ በእኔ እምነት ኢህአዴግ የምወዳደርበትን አካባቢ ቢተውልኝ የሚጐዳው ነገር አይኖርም፡፡ አሁን ከሚተነበየው አንጻር፣ኢህአዴግ በሰፊው ሊያሸንፍ እንደሚችል ይታወቃል፡፡ ከዚህ በፊትም ኢህአዴጎች ለእነ አቶ በትሩ አደም ለቀውላቸው የተመረጡበት ሁኔታ ነበር፡፡ እነዚህ ሰዎች ምን ሠርተው የዚህ አይነት እውቅና እንዳገኙ ባላውቅም፣ እኔ እንደ አንድ ዜጋ ራሴን ሳስብ ግን የሚጠበቅብኝን ሰርቻለሁ። እውቅና መስጠት የዚያኛው ወገን ጉዳይ ነው፡፡ “ለምን አባል አልሆንክም?” ለሚለው፣ እነሱ ምን ዓይነት ሰው አባል እንደሚያደርጉ መጠየቁ የሚቀል ይመስለኛል፡፡
እርስዎ አባል የመሆን ፍላጎት አለዎት?
መጀመሪያ መታወቅ ያለበት የእነሱ ፍላጎት ነው። ማንን አባል እንደሚያደርጉ ከእነሱ ማወቅ ይቀላል። እኔ በበኩሌ፣ የፓርቲ አባል ባልሆን ለራሴም ለሌላውም እጠቅማለሁ ብዬ አስባለሁ፡፡ ብትሆንም የሚጎዳ ነገር የለውም፡፡

“...ትዳር ከያዝኩኝ ከአስራ ሁለት አመት በሁዋላ ነበር ያረገዝኩት፡፡ እርግዝናው ከመከሰቱ

አስቀድሞ በእኔም ይሁን በባለቤቴ ቤተሰቦች ዘንድ የተመሳሰለ ቅሬታን አስተናግጃለሁ፡፡ በጣም የሚያሳዝን ነበር፡፡ የእሱም ቤተሰቦች እኔን መሐን ሲሉ ...የእኔም ቤተሰቦች እሱን መሐን ሲሉ ...እጅግ የሚያስጨንቅ ሁኔታ ነበር ሁለታችንንም የገጠመን፡፡ እኔ እንዲያውም ቢቸግረኝ... ባለቤቴን ...በቃ ልጅ አስወልደህ አምጣ...የሚል ፈቃድ ሰጥቼዋለሁ፡፡ እሱ ግን በምንም ምክንያት አንቺን ትቼ ሌላ ጋ አልሄድም በማለቱ ኑሮአችን በቤተሰብ ውጥረት ሲሰቃይ ቆይቶአል፡፡ በሁዋላ ግን ሕክምናው ...ጸበሉ ...የተቻለው ሁሉ ተደርጎ ሳይሳካ ከቆየ በሁዋላ እርግዝናው ሳይታሰብ ተከሰተ፡፡ እኔ እንዲያውም ሕመም ይሆናል እንጂ መቼም እርግዝና አይደለም ብዬ አስቤ ነበር፡፡ ሐኪሞቹ ግን ሕመም አይደለም ...እርግዝና ነው... በማለታቸው ተደሰትን፡፡ ምን ያረጋል... ደስታው ደስታ እንደሆነ ቢዘልቅ ጥሩ ነበር፡፡ ነገር ግን አልሆነም፡፡ በማህጸኔ ውስጥ ኢንፌክሽን በመኖሩ ምክንያት ጽንሱ መቀጠል ስላልቻለ እና እኔም በጣም ስለታመምኩ እርግዝናው እንዲቋረጥ ተደረገ፡፡ ከምንጊዜውም በላይ እጅግ በጣም ነበር ያዘንኩት፡፡ ከዚያም በሁዋላ ማርገዝ አልቻልኩም፡፡         ትእግስት ሺፈራው ከኮተቤየትእግስት ደብዳቤ የደረሰን በፖስታ ነበር፡፡ እኛም ገጠመኙን ይዘን ወደሕክምና ባለሙያ ነበር ያመራነው፡፡ ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ በጳውሎስ ሆስፒታል የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻ ሊስት በማህጸን ኢንፌክሽንና እርግዝና ዙሪያ ለዚህ እትም ማብራሪያ እንዲሰጡ  ተጋብዘዋል፡፡ ዶ/ር ታደሰ እንደሚሉት ኢንፌክሽን ሲባል መገለጫው ብዙ ነው፡፡  በሽታን ሊያመጡ የሚችሉ ተሀዋስያን መገኘት የሌለባቸው ቦታ ላይ ከተገኙ ኢንፌክሽን ወይንም መመረዝ ይከሰታል፡፡ የማህጸን ኢንፌክሽንን ለይተን ስናይ ደግሞ በተለምዶ ብዙ አይነት ሲሆን ምንጩ ባክቴሪያ፣ ፈንገስ፣ ቫይረስ ወይንም ሌሎች ፓራሳይትስ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ኢንፌክሽኑ ያጠቃውስ የትኛውን
የማህጸን ክፍል ነው የሚለውን መለየትም ያስፈልጋል፡፡ ኢንፌክሽኑ በታችኛው የማህጸን ክፍል ውስጥ የሚገኝ ከሆነ ብዙውን ጊዜ ቀላል የሆነ ኢንፌክሽን ነው፡፡ ቀላል ሲባልም ...ለአጭር ጊዜ የሚቆይ ምልክታቸውም በፍጥነት የሚታይ ነው፡፡  በታችኛው የማህጸን ክፍል የሚከሰተው ኢንፌክሽን በአብዛኛውም በግብረስጋ ግንኙነት ጊዜ የሚተላለፍ እንደ ጨብጥ (ጎኖሪያ) የመሳሰሉት ስለሆኑ ምልክታቸው በታየ ጊዜ ሕክምናው ስለሚሰጥ በቀላሉ ሊድኑ የሚችሉ ናቸው፡፡ ስለዚህም ከእርግዝና ጋር በተያያዘ ምንም ችግር አያስከትሉም፡፡/ር ታደሰ እንደሚሉት የታችኛው የማህጸን ክፍል በኢንፌክሽን ተያዘ ሲባል ብዙ ጊዜ ኢንፌክሽኑ ወደላይኛው የማህጸን ክፍልም የመዛመት እድል ይኖረዋል፡፡ በዋናው ማህጸን ክፍል ወይንም በዘር መተላለፊያው እንዲሁም በዘር ፍሬ መፈጠሪያው አካባቢ ወይንም ዙሪያውን ያሉትን የሰውነት ክፍሎች የተዛመተው ኢንፌክሽን ጉዳት ሊያስከትል የሚችልበት ሁኔታ ያጋጥማል፡፡
ከእርግዝና ጋር በተያያዘ ችግር የሚፈጠረው ኢንፌክሽኑ ወደላይኛው የማህጸን ክፍል ከገባ በሁዋላ፡-
የማህጸን የውስጥ ክፍል የመቁሰል እና ጠባሳ ምልክት ሊያሳይ ይችላል፡፡የዘር መተላለፊያ ቱቦው ሊቆስልና ሊዘጋ ይችላል፡፡የዘር ፍሬ የሚመረትበት አካባቢ መግል የመቋጠርና የመያያዝ ሁኔታ ሊኖረው ይችላል፡፡
ከላይ የተዘረዘሩት ሁኔታዎች እርግዝና እንዳይከሰት ማድረግ ወይንም እርግዝናው ቢከሰትም እንዳይቀጥል ምክንያት የመሆን አለበለዚያም ከማህጸን ውጭ እርግዝና እንዲከሰት የማድረግ አቅም አላቸው፡፡ ይህም የረጅም ጊዜ ጠንቅ ተብሎ ይገለጻል፡፡ ኢንፌክሽኑ ከእርግዝና ጋር በተያያዘ ጉዳት ያስከትላል ሲባል በሰውነት ክፍል ውስጥ ስለተገኘ ብቻ ሳይሆን ለመራቢያ የሚያገለግሉ የሰውነት ክፍሎች ላይ በሚያደርሱት ጉዳት ነው፡፡ የመራቢያ አካላቱ ጉዳት ደረሰባቸው ሲባልም የሰውነት የመከላከል አቅም እነዚህን በሽታ አምጪ ሕዋሳት ለማጥፋት ሲል የሚያደርገው ጦርነት  ውጤት ነው፡፡ ለምሳሌም የዘር ማስተላለፊያ ቲዩብ ቆስሎ ቢገኝ  ምክንያቱ ሰውነታችን እነዚያን እየተባዙ ያሉ ጀርሞች ለማጥፋት በሚያደርገው ቁጣ የተነሳ ነው፡፡ ስለዚህም በዋናነት ከኢንፌክሽኑ በላ ችግር የሚሆነው ሰውነት ተሐዋስያኑን ለማጥፋት ሲል በሚወስደው ተፈጥሮአዊ እርምጃ ሰውነት ላይ የሚደርሰው ጉዳት ነው፡፡ ኢንፌክሽን ሲከሰት ጉዳት እስኪያደርስ ድረስ የተወሰነ ጊዜ ስለሚወስድ በዚህ መሀል እርግዝና ሊከሰት ይችላል፡፡ በማህጸን የታችኛው ክፍል የሚታይ ችግር ከሆነ በቀላሉ ሊታከም የሚችል ሲሆን በላይኛው የማህጸን ክፍልም ቢሆን ምልክት ሲታይ እርግዝናውም ቢኖር ሕክምናው ይሰጣል፡፡ በእርግዝና ጊዜ ማህጸን ይዘጋል... ስለሆነም ምልክቶቹን እንዴት ማየት ይቻላል?  ለሚለው ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ እንደሚሉት የተጎዳው ክፍል የታችኛው የማህጸን ክፍል ከሆነ የፈሳሽ መኖር የደም መፍሰስ የመሳሰሉት ምልክቶች ሊታዩ ይችላል፡፡ ኢንፌክሽኑ የደረሰው በላይኛው የማህጸን ክፍል ላይ ከሆነ ደግሞ ከፈሳሽ ይልቅ ሌሎች ምልክቶች ይታያሉ፡፡ ለምሳሌም ትኩሳት፣ በሆድ አካባቢ ከበድ ያለ ህመም (በምርመራ ወቅት በትንሽ እንኩዋን ሲነካ ከፍተኛ ሕመም የመሰማት ሁኔታ) ይከሰታል፡፡ ከዚህም ባለፈ የላቦራቶሪ ምርመራ የመሳሰሉት ተደርገው በማህጸን ውስጥ
ኢንፌክሽን ካለ ጽንሱ እያለም ቢሆን ሕክምና ይደረጋል፡፡ በእርግጥ ሕክምናው ጠንከር ያለና
ክትትል የሚያስፈልገው ስለሚሆን ሆስፒታል እስከመተኛት የሚያደርስ ሊሆን ይችላል፡፡ የጽንሱ ሁኔታ እናትየው ሕክምናውን እየወሰደች እድገቱን ሊቀጥል ይችላል... አለበለዚይም ሕመሙ ከፍተኛ ከሆነ ሊያጨናግፈውም ይችላል፡፡ ኢንፌክሽን መኖሩ ብቻ ጽንሱን የሚያቋርጠው ሳይሆን ሙሉ በሙሉ ሰውነትዋን ከመረዘው ምናልባት የሚኖር አጋጣሚ ነው፡፡ በግብረስጋ ግንኙነት ጊዜ የሚተላለፉት እንደ ጨብጥ፣ ቂጥኝ የመሳሰሉት ኢንፌክሽኖች በእርግዝና ወቅት ሊከሰቱ ወይንም ከእርግዝናም በፊት ሊከሰቱ የሚችሉ ናቸው፡፡ እንደዚህ ያሉት ኢንፌክሽኖች እርግዝናው እንዲወርድ ምክንያት ሊሆኑ ሲችሉ ከዚህም ባለፈ ወደ ጽንሱ የመተላለፍ አቅም አላቸው፡፡ ጽንስ ሆድ ውስጥ የመቀጨጭ፣ጽንስ ሆድ ውስጥ የመጥፋት ወይንም ያለቀኑ መወለድ ወይንም... እነዚህ ሁሉ ሳይከሰቱ ቀርተው ልጅ የኢንፌክሽኑ ተጎጂ ሆኖ ሊወለድ ስለሚችል እናትየውን ቶሎ በማከም ልጁንም ማዳን ይቻላል፡፡ባለሙያው እንደሚገልጹት እርጉዝ ሴቶች እንደተገኘ ወይንም በቀላሉ መድሀኒትን አይጠቀሙም ቢባልም በአንዳንድ ምክንያቶች ግን የተለየ ሕክምና ይሰጣል፡፡ ነገር ግን በጽንስ ላይ ችግር የሚያስከትሉ ...ፈጽሞ በእርግዝና ወቅት የማይወሰዱ ተብለው የተለዩ መድሀኒቶች አሉ፡፡ንስ ላይ ምናልባት ችግር ሊያስከትሉ ይችላሉ፡፡ ግን የመድሀኒቱ ጠቀሜታ ከጉዳቱ ሊያመዝን ይችላል ተብሎ የሚሰጡ አሉ፡፡ ጽንስ ላይ ችግር ያምጣ አያምጣ አይታወቅም፡፡ ግን የመድሀኒቱ ጠቀሜታ ለእናትየውም ይሁን ለጽንሱ ጠቀሜታ አለው የሚባሉ መድሀኒቶች አሉ፡፡ ፈጽሞ በጽንስ ላይ ምንም ችግር አያመጡም የሚባሉ የመድሀኒት አይነቶች አሉ፡፡
ስለዚህ እነዚህ መድሀኒቶች በውል ተለይተው የሚታወቁ ሲሆን እንደሌላው መድሀኒት ዝም ተብሎ በቀላሉ የሚወሰድ ሳይሆን በሐኪሞች ልዩ ትእዛዝ በከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሰጡ ናቸው፡፡ በአብዛኛው ያለው ግንዛቤ ከማህጸን ፈሳሽ ከታየ እንደ ኢንፌክሽን የመቁጠር ዝንባሌ ያለው ነው፡፡ ነገር ግን በተለይም በእርግዝና ወቅት በማህጸን አካባቢ ብዙ ለውጥ ያለ ሲሆን ከነዚህም አንዱ የፈሳሽ መብዛት ነው፡፡ አንዳንድ እርጉዝ ሴቶች አልፎ አልፎ ሞዴስ እስከመጠቀም የሚደርሱበት ሁኔታም ይስተዋላል፡፡ ነገር ግን ፈሳሽ ከኢንፌክሽን የመጣ ነው የምንለው መቼ ነው የሚለውን መለየት ያስፈልጋል፡፡ በእርግጥ መብዛቱ አንዱ ምልክት ቢሆንም ብቻውን ግን ኢንፌክሽን ነው አያሰኘውም፡፡ ከዛ ባለፈ ግን የማሳከክ ወይንም የማቃጠል ስሜት ካለው ወይንም መልኩ ከሌላ ጊዜ የተቀየረ ሲሆን ...ወዘተ ኢንፌክሽን መሆኑን ሊያረጋግጥ ይችላል፡፡ ስለዚህም ሕክምናውን በጊዜው ማድረግ ተገቢ ነው ይላሉ ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ፡፡ በስተመጨረሻም ዶ/ር ታደሰ በተለይም በእርግዝና ወቅት ከሚኖረው የአካል ገጽታ ጋር በተያያዘ የገለጹትን እናስነብባችሁ፡፡ “...አንዲት እናት ከማርገዝዋ በፊት እና በእርግዝና ላይ እያለች የሚያመሳስላት ነገር     ቢኖር ስምዋ ብቻ ነው፡፡” ለምን? የሚለውን ጥያቄ መልስ በቀጣዩ እትም እናስነብባችሁዋለን፡፡ ይቀጥላል

ከዕለታት አንድ ቀን ዕመት ጦጢት ዘር ልትዘራ ወደ እርሻ ቦታ ትሄዳለች፡፡ ከዚያም በሰፊው እርሻ

ላይ በመት በመት ስትዘራ ትታያለች፡፡
በእርሻው ዳር የሚያልፈው ሰው ሁሉ ጥያቄ ይጠይቃል፡፡
ጦጢት ምን ዘራሽ?“ ይላታል አንዱ፡፡
“ዘንጋዳ” ትላለች ጦጢት፤ ኩራቷ ፊቷ ላይ እየተነበበ፡፡
“ጦጢት ምን ዘራሽ?” ይላታል ሁለተኛው፡፡
“ስንዴ!” ትላለች ጦጢት፡፡
“ጦጢት ምን ዘራሽ?” ይላታል ሌላው፡፡
“ጤፍ!” ትላለች፡፡
“ጦጢት ምን ዘራሽ?” ደሞ ሌላው፡፡
“አተር!” ትላለች፡፡
አንዳቸውም ከእጁዋ የሚወጣውን ዘር አለማየታቸው እየገረማት ነው መልስ የምትሰጠው፡፡ የመጨረሻው ሰው መጣና፣ “እሜት ጦጢት፣ ምን ዘራሽ?” አላት
“ባቄላ!” አለችው፡፡
“እንዲያው ባቄላ እዚህ መሬት ላይ ይበቅል ይመስል … ምን ይበጅሻል?
“ማምሻውን ሁኔታውን እዩ?” ብላ መለሰች፡፡ ጦጢት ስትዘራ ስትታይ ዋለችና ወደ ማታ ወደ እርሻው ተመልሳ መጣች፡፡ ከዚያም ቀን ስትዘራ የዋለችውን ዘር እንደገና ከእርሻው እያወጣች ስልቻዋ ውስጥ ትከት ጀመር፡፡ ቀን ስትዘራ ያዩዋት ሰዎች ከገበያ ሲመለሱ የምታደርገውን አይተው በመገረም፤ “እመት ጦጢት፤ ብልጥ የነበርሺው ሴትዮ አሁንስ ተጃጃልሽ መሰል! ደሞ ምን ልሁን ብለሽ ነው

የዘራሽውን መልሰሽ የምትለቅሚው?”
ጦጢትም፤
“ወዳጆቼ! ያለንበት ዘመን አያስተማምንም! የያዙትን ይዞ ወደ ቤት ክትት ነው የሚሻለው፡፡ ንብረትን በእጅ ይዞ ማደርን የመሰለ ነገር የለም!!” ብላ መለሰች፡፡
*                  *               *
በማናቸውም የህይወታችን መንገድ ጥርጣሬን ይዘን ከተጓዝን ዕቅዳችን በቅጡ አይሳካም፡፡ የምናደርገው ነገር ሁሉ ልባዊ አይሆንምና ውሽልሽል አጥር ነው የምናጥረው፡፡ ውሽልሽል አጥር ለአደጋ የተጋለጠ ነው፤ እንደጦጢት የምንዘራውን እየደበቅን መጓዝ፣ አልፈን ተርፈንም የዘራነውን መልሰን መልቀምና ይዘን ማደር ግዴታ እስኪሆን ድረስ ኑሮአችን ያልተረጋጋ ይሆናል፡፡ ያልተረጋጋ ዲሞክራሲ፣ ያልተረጋጋ  ፖለቲካን ነው የሚወልደው፡፡ ያልተረጋጋ ፖለቲካ ያልተረጋጋ ኢኮኖሚን ነው ይዞ እሚያዘግመው፡፡ የዚህ ባለቤት የሚሆነው ያልተረጋጋ ህዝብ ነው፡፡ ህዝብ ሲጠራጠር ደግ አይደለም፡፤ ይሄን ልብ ብሎ ማስተዋል ይጠይቃል፡፡ ሼክስፒር እንደሚነግረን፣
“ግን እንደዚሁ እንደህንፃ፣ ላዩ በሰም አንፀባርቆ
አካባቢው በጌጥ ደምቆ
መሰረቱ ግን በግድፈት፣ በአገም ጠቀም ተደባብቆ
በመሀንዲስ ጥበብ ጉድለት፣ ወይ ባጉል መራቀቅ ዘፍቆ
ከስህተቱም ከጥራቱም፣ ተቻችሎ አለ ተጣብቆ፡፡
እንግዲህ  ሐምሌት ምናልባት፣ ዛሬ እወድሻለሁ ሲል
በፍቅሩ የልብ ጥራት፣ አይገኝ ይሆናል እክል
ግን የልደቱን ደረጃ፣ ስታስቢው ደሙን ቅጅ
ፍቃዱ የሱ እንዳልሆነ፣ አስተውይ የእናቴ ልጅ፡፡”
ሌላው አስጊና አትጊ ነገር እርስ በርስ መጠራጠር ነው፡፡ መሪዎች ካልተማመኑ ተመሪዎች ተግባብተው መራመድ ይቸግራቸዋል፡፡ ተግባብተው የማይራመዱ ሰዎች ወንዝ ለወንዝ ሲማማሉ ነው የሚኖሩት፡፡
“ዕምነት ሲታመምሺ ወረቀት መፈራረም” ይለዋል ጸጋዬ ገ/መድህን፡፡ ቢሮክራሲያችን፣ ፓርቲዎቻችንም፣
አመራሮቻችንም ከአበሻ የጥርጣሬ ድርና ማግ ነው ተሰሩት፡፡ ዛሬ የተባለው ነገ የሚሻረው ለዚህ ነው፡፡
እኔ ከሁሉ በላይ ነኝ የሚል አስተሳሰብ አጥፊ ነው፡፡ የበላይነትን በተሻለ ሥራ ካላሳየን ከፉከራ አያልፍም፡፡
“የተሻልን ነን እያልን
ያልተሻለ ነገር ከሰራን
መሻላችን ምኑ ላይ ነው፣ ትላንት ላይ ከተጋደምን”እንደሚለው ነው ገጣሚው፡፡
ህዝብ መንግስትን አምኖ በራሱ ተነሳሽነት ካልተንቀሳቀሰ፣ ዲሞክራሲው ጤነኛ ነወይ? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ የምስራቅ አውሮፓ መንግስታት ብትንትናቸው እስኪወጣ ድረስ 98 በመቶ ምርጫውን አሸንፈናል ይሉ እንደነበር አለመርሳት ብልህነት ነው፡፡ ያልመረጠው ለምን እንዳልተመረጠ ብቻ ሳይሆን የመረጠው ለምን እንደሆነ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ ቀስቅሰን፣ አስገድደን ወይ አታለን መመረጥ ጭብጨባን እንጂ ልባዊ ድጋፍን አያስገኝም፡፡ በእርግጥ የፖለቲካ ጸሀፍት፤ “ገባው አልገባው አይደለም የፖለቲካ ሚስጥሩ፡፡ ተቀበለ አልተቀበለ  ነው እንጂ” ይላሉ፡፡ ሆኖም ጊዜያዊ ነው፡፡ እንደሚታወቀው እንኳን ፖለቲካው ታሪክም አሸናፊዎች የሚፅፉት ተረት ነው፤ ይሏል፡፡ ስለዚህም ኢ-ተዓማኒ ሪፖርት በተነገረ ቁጥር፣ ሙገሳና የአፍ ሙካሽን የተንተራሰ ሲሆን “እሰይ እሰይ! እልል በይ ጉሜ!” ማለት ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ በማንኛውም የለውጥ ንፋስ ውስጥ ጊዜን፣ ወዳጅንና ባላንጣን ማሰብ ዓይነተኛ ብልህነት ነው፡፡ ጊዜው እንጂ ሁኔታው አይደለም ጥፋተኛው፡፡ “ሳህን ቢጠፋ አብረን በላን” እንደሚባለው የትግሪኛ ተረት፤ “የሰሜን ብርድ ከማትወድደው ጋር ያስተቃቅፋል” የሚለው ተረት ዋና ጉዳይ ነው!

  • የመን እንደ ሶማሊያ መታመሷ፣ ለኤርትራ መንግስት አመቺ ይሆናል

የኤርትራ መንግስት አካባቢውን እየበጠበጠ ስለሆነ በጋራ እንመክተዋለን ያሉት የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትርና የጅቡቲ ፕሬዚዳንት፤ በኤርትራ መንግስት ላይ የተጣለው አለማቀፍ ማዕቀብ እንዲቀጥል
የጠየቁ ሲሆን፤ የኤርትራው ፕሬዚደንት በበኩላቸው ውንጀላውን አስተባበሉ፡፡ሰሞኑን  በጅቡቲ የሶስት ቀናት ጉብኝት ያደረጉት ጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሳለኝ እና የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ኢስማኤል ኦማር ጊሌ፤ የኤርትራ መንግስት ለአካባቢው አገራት ፀጥታ ስጋት ስለሆነ ኢትዮጵያና ጅቡቲ በጋራ እየሰሩ ነው ብለዋል፡፡ የኤርትራ መንግስት የጅቡቲን ጨምሮ የአካባቢውን አገራት ፀጥታ እያወከ ነው ያሉት ፕሬዚደንት ኦማር ጊሌ፤ ኤርትራ ላይ የየተጣለው ማዕቀብ እንዲቀጥል ከጠ/ሚ ኃይለማርያም ጋር መስማማታቸውን ገልፀዋል፡፡ ኢትዮጵያና ጅቡቲ ድንበራቸውን በጋራ ለመጠበቅ ዝግጁ መሆናቸውን የገለፁት ጠ/ሚ ኃይለማርያም በበኩላቸው፤ የኤርትራ መንግስት አካባቢውን ከመበጥበጥ ስላልተቆጠበ ስድስት አመት ያስቆጠረው አለማቀፍ ማዕቀብ እንዲቀጥልና ተመጣጣኝ እርምጃ እንዲወሰድበት ንጠይቃለን ብለዋል፡፡ በአፍሪካ ህብረት፣ ከዚያም በተባበሩት መንግስታት የፀጥታ ምክር ቤት አማካኝነት ኤርትራ ላይ ማዕቀብ የተጣለው፣ የሶማሊያ አሸባሪዎችን በመደገፍና በማስታጠቅ አካባቢውን ይበጠብጣል በሚል ምክንያት እንደሆነ ይታወሳል፡፡ የኤርትራ መንግስት የሶማሊያ አሸባሪዎችን እንዲሁም በየአገሩ አማፂ ቡድኖችን ያስታጥቃል በሚል ከፍተኛ ስጋት ያደረባቸው አገራት በተለይም ኢትዮጵያና ጅቡቲ ከየመን ጋር ትብብር በመፍጠር ጫና ለማሳደር ሲጥሩ የነበረ ሲሆን፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የየመን ቀውስ እየተባባሰ መንግስት አልባ መሆኗ ለሁለቱ አገራት ይበልጥ አሳሳቢ ሆኖባቸዋል። ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ በበኩላቸው፤ ከኢትዮጵያ የሚሰነዘረውን ውንጀላ በማስተባበል፤ በኤርትራ ላይ የተጣለው ማዕቀብ እየላላ ስለመጣና ማዕቀቡ ይነሳል የሚል ስጋት ስላደረባቸው ነው ውንጀላውን የሚደጋግሙት ብለዋል፡፡ የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባሰራጨው ተመሳሳይ ምላሽ፣ ኢትዮጵያ የድንበር ዳኝነትን
ባለማክበር አካባቢውን ትበጠብጣለች በማለት የወነጀለ ሲሆን፤ ከጅቡቲ ጋር በኳታር ሸምጋይነት ድርድር ከተጀመረ በኋላ የጅቡቲ መንግስት ከኢትዮጵያ ጋር ማበሩ አሳዝኖናል ብሏል፡፡ የኤርትራ መንግስት የሶማሊያ አሸባሪዎችን በማስታጠቅ፣ የጎረቤት አገራትን ፀጥታ ያውካል  በሚል በቀረበ ክስ፣ በ2001 የፀጥታው ምክር ቤት ኤርትራ ላይ ማዕቀብ ሲጥል፤ ከቻይና እና ከራሺያ የተአቅቦ ድምፅ በስተቀር የምክር ቤቱን ይሁንታ በማግኘት ያለፈ ውሳኔ እንደሆነ ይታወሳል፡፡ በወቅቱ ኢትዮጵያ የተለያዩ ሰነዶችን በማስረጃነት ያቀረበች ሲሆን የኤርትራ መንግስት ጐረቤት አገራትን የሚበጠብጠው በመከላከያ ሚኒስትሩ ጀነራል ኤፍሬም ስብሀት አስተባባሪነት እንደሆነና፤ የአየር ሀይል እና የባህር ሀይል አዛዞችን ጨምሮ 12 ጀነራሎች የእንቅስቃሴው መሪዎች እንደሆኑ በሰነዶቹ ተዘርዝሯል፡፡ የኤርትራ የባህር ሀይል ዋና አዛዥ ሜ/ጀ ሁመድ ካሪካሬ፣  ባለፈው አመት የሞቱት  ሜ/ጀ ገብረ እግዚአብሄር አንደማርያም፣ ሜ/ጀ ሀይለ ሳሙኤል፣ የኤርትራ ብሄራዊ ደህንነት አዛዥ ብ/ጄ አብርሀ ካሳ የኢትዮጵያ እና የጅቡቲን ፀረ ሰላም ሀይሎች በማስተባበር ያሰማራሉ ተብለው በስም ተጠቅሰው ነበር፡፡