Administrator

Administrator

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
እነእንትና…‘ኢሌክሽን’ ምናምን እንዴት ነው! እንዴት ነው… ወደዛኛው ግቢ አጥር ዘለላችሁ እንዴ! አምስተኛው እንትንማ መጦሪያዬ መጦሪያዬ ምናምን ማለት ስለበዛው ነገረ ሥራህ ትንሽ ግራ ገብቶን ስለነበር ነው፡፡
ይቺን ነገር ሳናወራት አልቀረንም…ፖለቲከኛው የምርጫ ንግግር እያደረገ ነው፡፡ እናላችሁ…ምን ይላል… “ወገኖቼ ለአገራችን ተዋግቻለሁ፡፡ አልጋዬ ጦር ሜዳ ነበር፣ ጣራዬም ሰማዩ ነበር፣ እያንዳንዱ ዱካዬ በደም እስኪቀልም ድረስ ያልዋልኩበት የጦር ሜዳ፣ ያላቋረጥኩት በረሀ የለም፡፡ ስለዚህ ምረጡኝ…” ይላል። ይህን ጊዜ ከህዝቡ መሀል አንዱ ምን ቢል ጥሩ ነው…
“ለአገርህ ከሚገባህ በላይ ሠርተሀል፡፡ እቤትህ ሂድና አረፍ በል፡፡ ተወዳዳሪህ ደግሞ ገብቶ ይሞክረው፣” ብሎት እርፍ፡፡
ከዚህ የሚገኘው ‘ሌሰን’…ቦተሊከኞች ለምርጫ ስትወዳደሩ ‘ሲቪያችሁን’ ከልክ በላይ አታርዝሙትማ። አሀ… “እቤትህ ሂድና አረፍ በል…” ትባላላችኋ! ቂ…ቂ…ቂ…
ስሙኝማ…መቼም ዘንድሮ ፊት ለፊት የምንሰማው፣ የምናየውና ዘወር ስንል ደግሞ ያለው ነገር አልገጥም ብሎን ተቸግረናል፡፡ ፈረንጅ…‘ኋት ዩ ሲ ኢዝ ኋት ዩ ጌት’ የሚላት ነገር አትሠራም፡፡
እንትናዬዎች…“አድናቂሽ ነኝ…” ምናምን ስትባሉ ስትሰሙ አብራችሁ ዘወር ስትሉ ሊባል የሚችለውንም እያሰባችሁ፡፡ “እኔ እኮ አድናቂሽ ነኝ ያልኳት እሷም ሴት ሆና በሚኒስከርት በመሄዷ ነው…” ምናምን ሊባል ይችላል፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
እንትናዬ ሸለል ብላ ወጥታለች፡፡ ዘንድሮ መቼም ሸለል ብሎ ለመውጣት የምትሞክር እንትናዬ መአት ነች፡፡ እናላችሁ…የሆነች እንትናዬ ሽልል ብላ ስትወጣ ምን ትባላለች መሰላችሁ… “አንቺ እንዴት ነው እንዲህ ያማረብሽ! እንዴ አንቺ እንዲህ ያብረቀርቅሽ የቤታችሁ የቅቤ ቅል እንዴት ሊሆን ነው!” አይነት ‘አድናቂሽ ነኝ’ ነገር ይቀርብላታል፡፡ እሷዬዋም ደስ ይላታል፡፡
እሷ ዘወር ስትል ምን ይባላል መሰላችሁ… “አገሩ ሁሉ በኮስሜቲክስ በሞላበት ምን አለ ትንሽ ለቅለቅ ብትል፡ “አላየሀትም እንዴ… ሥራ የበዛበት የዱቄት ወንፊት ትመስላለች እኮ፡፡”
እሱ ደግሞ ከአካሄዱ ጀምሮ… መንገዱን ተቆጣጥሮታል፡፡ “አንተ ምን አግኝተህ ነው…የእንግሊዝ ልዑላንን መሰልክ እኮ!” ምናምን ይሉታል፡፡ ይሄ እንግዲህ ዲፕሎማሲ ነው፡፡ ዘወር ሲል ምን ይባል መሰላችሁ… “እኔ እንደው ትከሻው ላይ ጃኬት ጣል ስላደረገ ነው እንጂ በልማት ምክንያት ይፍረስ የተባለ የማድቤት ግድግዳ ይመስላል…” ምናምን ይባላል፡፡
እናማ…‘ኋት ዩ ሲ ኢዝ ኋት ዩ ጌት’ ዘንድሮ አትሠራም፡፡
“አንተ! እንዴት ነው እንዲህ ትከሻ በትከሻ የሆንከው! የካምቦሎጆውን ሜዳ አከልክ እኮ?”
“ጂም እሠራለሁ፡፡”
“የሚገርም ነው፣ የሆነ እኮ በቀራጺ የተቀረጽክ ነው የምትመስለው…” ምናምን ‘አድናቂህ ነኝ’ አይነት ነገር ይባላል፡፡
ይህ እንግዲህ ‘ዲፕሎማሲ’ መሆኑ ነው፡፡
ዘወር ሲል አጅሬው ምን ይባላል መሰላችሁ… “ይሄን ሰውዬ ግን በደንብ አይተኸዋል? ውፍረቱ ግን የጤና አይመሰለኝም! እኛ እኮ ስንትና ስንት ዓመት ጂም የሠሩ ጓደኞች አሉን፡፡ እሱ በሁለት ወሩ የሆነውን እነሱ ምነው በሁለት ዓመታቸው አልሆኑ!”
እናማ…‘ኋት ዩ ሲ ኢዝ ኋት ዩ ጌት’ ዘንድሮ አትሠራም፡፡
ቦተሊከኛው ለረጅም ሰዓት ሲደሰኩር ይቆያል፡ ሲጨርስ አዳራሹ በጸጥታ ይዋጣል፡፡ የተናገረው ነገር የህዝቡን ስሜት በከፍተኛ ደረጃ እንደነካው እያሰላሰለ ትኩር ብሎ ሲያይ ምን ቢያይ ጥሩ ነው…ለካስ ሰዉ ሁሉ እንቅልፉን ይለጥጣል፡፡
ከዚህ የሚገኘው ‘ሌሰን’ ቦተሊከኞች ለረጅም ደቂቃዎች አውርተው ሲጨርሱ ጸጥታ ከሰፈነ ሰዉ በሀሳብ ተመስጦ ሳይሆን በእንቅልፍ ሰምጦ መሆኑን ልብ ይባልማ!
የሆነ ተናጋሪ ቀሺም ስለነበር አዳራሹ ውስጥ ማጉረምረም በዝቷል፡፡ እናማ...ድምጹን ከፍ አድርጎ ምን ይላል… “እባካችሁ ጆሯችሁን አውሱኝ…” ይላል። ይሄን ጊዜ ከተሰብሳቢዎቹ አንዱ ምን ቢለው ጥሩ ነው… “የእኔን ውሰድ፡ ቢያንስ ቢያንስ ያንተን ንግግር አልሰማም፡፡”
ተናግረናል…ዘንድሮ ‘ኋት ዩ ሲ ኢዝ ኋት ዩ ጌት’ አይሠራም፡፡
የንግግርን ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ… ሰውየው ለመናገር ሲሞክር ጫጫታው ያስቸግረዋል። ይሄን ጊዜ ይናደድና… “እዚህ አዳራሽ ውስጥ በአንድ ጊዜ አንድ ደደብ ቢናገር ደስ አይላችሁም!” ይላቸዋል፡፡ ከሰዉ መሀል አንዱ ምን ቢለው ጥሩ ነው… “መጀመሪያ አንተ ተናግረህ ጨርሳ!”  አሪፍ አይደል፡፡
ስሙኝማ… ሰዋችን በአደባባይ መናገር ጀምሯል፡፡ በፊት፣ በፊት ከአሥሩ አንዱ ሰው “አሁንስ መከራችንን በላን…በግራ በቀኝ አላስኖር አሉን እኮ…” ምናምን ሲል ዘጠኙ ሰው “ጎበዝ እንዳትበላ፣ ከተናግሮ አናጋሪ ይጠብቀን…” አይነት የጎሪጥ ይተያያል፡፡ ዘንድሮ አሥር ሰው ኖሮ አንዱ ሰው “አሁንስ መኖር አቃተን…” ሲል ስምንቱ “እነሱ ምን ቸገራቸው አትክልት ተራ አይሄዱ፣ እህል በረንዳ አይሄዱ…ወፍጮ ቤት አሻሮ ተሸክመው አይሄዱ…” ምናምን እያለ ይጨምርበታል፡፡
አስቸጋሪ ጊዜ ውስጥ ነን፡፡ በጣም አስቸጋሪ ጊዜ ውስጥ ነን! የምንስማማበት አንድ ርዕስ ቢኖር ‘የኑሮ መወደድ’ ነው፡፡ አንድ ፍርፍር ለሁለት የምንበላውም፣ አንድ ኪሎ ጥሬ ሥጋና ሁለት ስፔሻል ክትፎ ለብቻችን የምንበላውም እኩል… “ኑሮ አቃተኝ እያልን ነው፡፡”
የምግብ ነገር ከተነሳ አይቀር… ሰውየው ዶሮ አሮስቶ ያዛል፡ ዶሮዋ ስትመጣ ሲያያት ይጎመጅና ሲቀምሳት ምንም የዶሮ ጣእም የላትም፡፡ መቼም የሚወጣባት ገንዘብ ነውና እንደምንም ይጨርሳታል፡፡ ሂሳቡ ሲመጣለት ሁለት መቶ ሀያ ሁለት ብር ይሆናል፡፡ ምን አለፋችሁ…በንዴት ጣራ ይነካላችኋል፡፡
”ምንድነው ይሄ!”
”ሂሳቡ ነዋ፣ ጌታዬ፡፡”
“ሙሉውን የዶሮ እርባታ የሰጣችሁኝ መሰላችሁ እንዴ! ሁለት መቶ ሀያ ሁለት ብር! ዶሮዋ እኮ ቆዳና አጥንት ብቻ ነበረች...” ሲል አሳላፊው ምን ቢል ጥሩ ነው…
“ጌታዬ ላባዋንም ፈልገው ከነበረ ለምን አልነገሩንም!” ብሎት እርፍ፡፡
እናም አሪፍ መልክ ያላት ዶሮም ይሁን ሽፋኑ ዓይንና ቀልብ የሚስብ አብዛኛው ነገር እንዳሰቡት የማይገኝበት ዘመን ነው፡፡
እናማ…ዘንድሮ ‘ኋት ዩ ሲ ኢዝ ኋት ዩ ጌት’ ብሎ ነገር አይሠራም፡፡
ባል ሆዬ ገና ‘ፉከራውን ያልጨረሰ’ ሹሮ ወጥ ይቀርብለታል፡፡ “ዛሬ ገና ሹሮ ልትበላ ነው…” እያለ የመጀመሪያውን ጉርሻ ሲጎርስ… አለ አይደል… አንድያውን የሹሮ እህሉን ሳይከካ ቢያቀርቡለት ይመኛል፡፡
ብሽቅ ብሎ ምን ይላል… “ይሄን ወጥ የሠራው ማነው?”
ሚስትም ሥራዬ ተወደደልኝ ትልና ኮራ ብላ “እኔ ነኛ…ድሮስ ማን ሊሆን ነው…” ትላለች፡፡”
ባል ምን ቢል ጥሩ ነው… “በይ ቁጭ በዪና ራስሽ ብያት!”
ሚስቶች “በይ ቁጭ በዪና ራስሽ ብያት!” ከመባል ያድናችሁማ!
እናማ…መልክ ብቻ የሆነ ሹሮ ለሚቀርብላችሁ አባወራዎች ምክር ቢጤ… ሚስቶቻችሁን “ለወደፊቱ ጣት የሚያስቆረጥም ሹሮ የመሥራት ዓላማሽን ለማሳካት ትኩረት ሰጥተሽ ልትንቀሳቀሺ ይገባል…” በሏቸውማ፡፡ አሀ ልክ ነዋ…ራሳቸው ይኳኳሉ እንጂ ሹሮ ወጥን መኳኳል ምን የሚሉት ሙያ ነው!  ቂ…ቂ…ቂ…
እናማ…ዘንድሮ ‘ኋት ዩ ሲ ኢዝ ኋት ዩ ጌት’ ብሎ ነገር አይሠራም፡፡
ስሙኛማ…እግረ መንገዴን የሆነ ነገር ትዝ አለኝማ…እኛ ባሪያቶ ነው ምናምን የሚሏቸው ሰውዬ ተሰናበቱ አይደል! የምር እኮ… አንዳንዶቻችን ስንወርድባቸው የከረምነው…አለ አይደል…የስፖርት ጉዳይ ሳይሆን የሚስትና የርስት ጠብ ያለብን ነበር የሚመስለው፡፡
ስሙኝማ…አንድ ጊዜ “ግማሽ ሚሊዮን የሚሆን ብር እየዛቁ…” የሚባል ነገር ሰማሁ መሰለኝ! እንዲህ ተብሎ ነው እንዴ የሚታሰበው! ግራ ስለገባኝ ነው… እኚህ ሰውዬ የውጪ ዜጋ ናቸው፡፣ ደረጃቸው ምንም ይሁን ምን ዓለም አቀፍ አሰልጣኝ ናቸው…ደሞዛቸው አሥራ ስምንት ሺህ ዶላር ምናምን ‘ነች’፡፡ በኢንተርናሺናል አሰልጣኝነት ደግሞ ይቺ የመጨረሻዋ ቀሺም ክፍያ ትመስለኛለች፡፡ “...እየዛቁ…” የምትለዋ ግራገብታኝ ነው፡፡ ስፖርት ጋዜጠኞቻችንም እኮ “የስፖንሰር ገንዘብ እየዛቁ…” አይነት ነገር እየተባላችሁ ነው!  
የምር ግን እሳቸው ሰውዬ ላይ በሚዲያ የተወረደባቸውን ግማሹን ያህል ‘መከራ የሚያበሉን’ ባለወንበሮች ላይ የሚወረድባቸው ዘመን ይመጣ ይሆን!  አሀ…ልክ ነዋ! እኔማ አንዳንዴ ወገባችንን ይዘን ልክ ልካቸውን ስንነግራቸው… አለ አይደል… “እኚህ ሰውዬ የጀኔራል ደቦርሚዳ ዘመድ ናቸው እንዴ?” ልል ምንም አይቀረኝም ነበር፡፡
አዲሱን አሰልጣኝ ከዚህ ይሰውረውማ፡፡
እናማ…ላይ ላዩን እያያን ዘወር ሲባል የሚባለውን መርሳት አሪፍ አይደለም፡፡ ዘመኑ እንዲህ ነው፡፡
ዘንድሮ… ‘ኋት ዩ ሲ ኢዝ ኋት ዩ ጌት’ ብሎ ነገር አይሠራም፡፡
እናማ… ‘ከፊት ለፊት ተኳኩሎ፣ ከጀርባ ተከልሎ…’ ዘመንን ርዝመት ያሳጥርልንማ!
ደህና ሰንበቱልኝማ!

     የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኢትዮጵያ በእስር ላይ የሚገኙትን የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌን አያያዝና የወቅቱን አጠቃላይ ሁኔታቸውን በተመለከተ ምርመራ እያካሄደ መሆኑን ማስታወቁን ዘ ጋርዲያን ትናንት ዘገበ፡፡
የተመድ የግርፋትና ስቃይ መከላከል ልዩ ክፍል ባልደረባ የሆኑት ጁአን ሜንዴዝ ባለፈው ዓመት ሰኔ ወር ላይ በየመን አውሮፕላን ማረፊያ በቁጥጥር ስር ውለው ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ የተደረጉት አቶ አንዳርጋቸው፣በአሁኑ ወቅት ያሉበትን ሁኔታና አያያዛቸውን እየመረመሩ እንደሚገኙ ለእንግሊዝና ለኢትዮጵያ መንግስታት በጻፉት ደብዳቤ አሳውቀዋል ያለው ዘገባው፤ግለሰቡ እንቅልፍ እንዳያገኙ ተደርገዋል፣ ለብቻቸው ታስረዋል የሚሉ ክሶች እየቀረቡ እንደሚገኙም አስታውሷል፡፡
ተቀማጭነቱ በለንደን የሆነውና በመላ አለም የሞት ፍርድ የተጣለባቸውን እንግሊዛውያን ሁኔታ የሚያጠናው ሪፕራይቭ የተባለ ተቋም የአጣሪ ቡድን ዳይሬክተር ማያ ፎኣ በበኩላቸው፣ አቶ አንዳርጋቸው በህገወጥ በመንገድ መያዛቸውንና ለኢትዮጵያ ተላልፈው መሰጠታቸውን ጠቅሰው፣ ለአንድ አመት ያህል ባልታወቀ ቦታ ታስረው እንደሚገኙና ተመድም የአቶ አንዳርጋቸውን አያያዝ ለማጣራት መወሰኑ አግባብነት እንዳለው ተናግረዋል፡፡
የእንግሊዝ መንግስት ለጉዳዩ የበለጠ ትኩረት በመስጠት ጠንካራ እርምጃዎችን መውሰድ ይገባዋል ያሉት ዳይሬክተሯ፣ አቶ አንዳርጋቸው አለማቀፍ ህጎችን በሚጥስና አብዛኛዎቹን የፍትህ መርሆዎች ባላከበረ መልኩ በእስር ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው ግለሰቡ በአፋጣኝ ከእስር እንዲፈቱ ግፊት እንዲያደርግ ጠይቀዋል፡፡
የአቶ አንዳርጋቸው ጠበቃ የሆኑት ቤን ኩፐር በበኩላቸው፤ግለሰቡ በህገወጥ መንገድ በሌሉበት በተላለፈባቸው የሞት ቅጣት ያለአግባብ መታሰራቸውንና በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ ጠቅሰው፣ የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ቢሮም የተመድን የምርመራ ጅምር በመከተል ከእስር የሚለቀቁበትን ሁኔታ መፍጠር ይጠበቅበታል ብለዋል፡፡
በለንደን የሚኖሩት የአቶ አንዳርጋቸው ባለቤት የሚ ሃይለማርያም በበኩላቸው፤ ባለቤታቸው በቁጥጥር ስር ከዋሉበት ጊዜ አንስቶ አንድ ጊዜ ብቻ በስልክ እንዳነጋገሯቸውና የት ቦታ ታስረው እንደሚገኙ የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ተናግረዋል፡፡
በእንግሊዝ የኢትዮጵያ ኤምባሲ በበኩሉ፤ ግንቦት ሰባት በአገሪቱ ፓርላማ በአሸባሪነት የተመዘገበ ድርጅት መሆኑንና ዋና ጸሃፊው የነበሩት አቶ አንዳርጋቸውም በአገሪቱ ሽብርና ብጥብጥ እንዲፈጠር በማሴርና ሽብርተኞችን በኤርትራ ውስጥ በማሰልጠን፣ በፋይናንስ በማገዝና በማቀናጀት ስርአቱን ለመናድ በማቀድ ወንጀል ተከሰው ጥፋተኛ በመሆናቸው የሞት ፍርድ እንደተፈረደባቸው አስታውቋል፡፡ የእንግሊዙ ጠ/ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን በቅርቡ ለኢትዮጵያ አቻቸው ለጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በጻፉት ደብዳቤ፤ ግለሰቡ ከእስር እንዲፈቱ ቢጠይቁም አዎንታዊ ምላሽ አለማግኘታቸውን በቅርቡ መዘገባችን ይታወቃል፡፡

ተቃዋሚ ፓርቲዎች የገንዘብ አቅም ተፈታትኖናል አሉ


ለ5ኛው አገራዊ ምርጫ አዲስ አበባን ጨምሮ በክልል ከተሞች ከፍተኛ ወጪን የሚጠይቁ  ትላልቅ ቢልቦርዶችና ፖስተሮችን በብዛት በመጠቀም ከተፎካካሪዎቹ ልቆ የታየው ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ፤ በምርጫ ቅስቀሳ በኩል እንደ ዘንድሮም ተሳክቶልኝ አያውቅም ብሏል - ከዕቅዱ 98 በመቶው ውጤታማ እንደሆነ በመግለፅ። ተቃዋሚዎች በበኩላቸው፤ ጠንካራ ቅስቀሳ ማድረጋቸውን ጠቁመው የበጀት እጥረት ያሰቡትን ያህል እንዳይሰሩ እንደተፈታተናቸው ተናግረዋል፡፡
ምርጫ ቦርድ ለምርጫ ማስፈፀሚያ ብሎ ለኢህአዴግ ከ14ሚ. ብር በላይ፣ ለመድረክ 2.2 ሚ. ብር፣ ለኢዴፓ ወደ8 መቶ ሺ ብር፣ ለሰማያዊ ፓርቲ እንዲሁ ወደ 8 መቶ ሺ ብር ገደማ በጀት እንደመደበላቸው ይታወቃል፡፡  
ለተወካዮች ምክር ቤት 165 እጩዎችን በተለያዩ የሃገሪቱ ክልሎች ያቀረበው የኢትዮጵያውያን ዲሞክራቲክ ፓርቲ (ኢዴፓ)፤ ለምርጫው ወደ 1 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ በጀት ይዞ መነሳቱን ጠቁሞ አብዛኛውን ገንዘብ ለመኪና ላይ ቅስቀሳ፣ ለፖስተሮችና በራሪ ወረቀቶች እንዲሁም ባነሮች ዝግጅት ማዋሉን ገልጿል፡፡
የኢዴፓ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ወንደሰን ተሾመ፤ ፓርቲው እንግሊዝ ሀገር ከሚገኙ ደጋፊዎቹና አባላቱ የተሰበሰበውን 3 መቶ ሺህ ብር እንዲሁም ከምርጫ ቦርድ የተመደበለትን  8 መቶ ሺህ ብር ሙሉ በሙሉ ለምርጫው ማስፈፀሚያ እንደተጠቀመበት አስታውቀዋል፡፡
ኢዴፓ ከ1 ሚሊዮን ኮፒ በላይ በራሪ ወረቀቶች አሳትሞ መበተኑን የጠቆሙት አቶ ወንድወሰን፣ ለእጩ ተወዳዳሪዎች ለእያንዳንዳቸው 300 የሚደርሱ ፖስተሮች አዘጋጅቶ ማሠራጨቱን ገልፀዋል፡፡ ከፖስተሮችና በራሪ ወረቀቶች በተጨማሪ ባነሮችን አሠርቶ በተለያዩ አካባቢዎች ሰቅሎ እንደነበር የተናገሩት አቶ ወንደሰን፤ ባነሮቹ ባልታወቀ ሁኔታ ከቦታቸው መነሣታቸውንና አብዛኞቹ ፖስተሮችም ተቀዳደው መገኘታቸውን ገልፀዋል፡፡
ኢዴፓ የቢል ቦርድ ማስታወቂያ ለመጠቀም ቢያስብም በገንዘብ አቅም ማነስ መተግበር እንዳልቻለም ኃላፊው ይናገራሉ፡፡ “አንድ ቢልቦርድ ለማሰራት ከ70ሺህ ብር በላይ ያስፈልጋል፤ ፓርቲው ደግሞ ይህን የማድረግ አቅም አልነበረውም” ብለዋል አቶ ወንድወሰን፡፡
139 እጩዎችን ለፓርላማ ያቀረበው ሠማያዊ ፓርቲ በበኩሉ፤ ምርጫ ቦርድ ከሠጠው 800ሺህ ብር በተጨማሪ ወደ 1.2 ሚሊዮን ብር ገደማ በጀት ይዞ ቅስቀሳውን እንዳከናወነ ጠቁሟል፡፡ ከመኪና ላይ ቅስቀሳ ባሻገር ባነሮችን፣ ፖስተሮችንና በራሪ ወረቀቶችን እንዲሁም የተወሰኑ ቢልቦርዶችን በመትከል ቅስቀሳ ማድረጉንም የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ተናግረዋል፡፡
ፓርቲው በተለያዩ ቦታዎች ቢልቦርድ ለመስቀል ሞክሮ ችግር እንደገጠመው የገለፁት ኃላፊው፤ “ከክፍለ ከተማ ፍቃድ አምጡ” የሚሉ ምክንያቶች የታሰበውን ያህል ቢልቦርድ እንዳንሰቅል አድርጎናል ብለዋል፡፡ እንዲያም ሆኖ አዲስ ከተማና ኮተቤ ላይ ብቻ ወደ 10 የሚሆኑ ቢልቦርዶችን ለመትከል እንደቻሉ ሃላፊው ገልፀዋል፡፡
ፓርቲው ለአንድ እጩ እስከ 2ሺህ የሚደርሱ ፖስተሮችን ማሠራጨቱን የጠቆሙት አቶ ዮናታን፤ ወደ 1.5 ሚሊዮን በራሪ ወረቀቶች መበተናቸውንም ተናግረዋል፡፡ ፓርቲው ለድረ ገጽ የምረጡኝ ቅስቀሳም ከ10ሺህ ብር በላይ ማውጣቱን ሃላፊው ጠቁመዋል፡፡ ለ3 ተከታታይ ቀናት በ8 ተሽከርካሪዎች በአዲስ አበባ ሁሉም ክ/ከተሞች ቀኑን ሙሉ መቀስቀሱንና በክልል ከተሞችም በቂ የመኪና ላይ ቅስቀሳ ማድረጋቸውን አክለው ገልፀዋል፡፡
ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 270 እጩዎችን ያቀረበው መድረክ፤ ከምርጫ ቦርድ ከተሰጠው 2.2 ሚሊዮን ብር ውስጥ ወደ 700 ሺህ ብር ገደማ ለመኪና ላይ ቅስቀሳዎች ማዋሉን ጠቁሟል፡፡ የቀረውን ገንዘብ ለምርጫ ታዛቢዎች የውሎ አበል በነፍስ ወከፍ 50 ብር እንዲከፋፈል መደረጉን የመድረክ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጥላሁን እንዳሻው ገልፀዋል፡፡
“መድረክ ሊሰራ ካሰበው አንፃር የገንዘብ አቅሙ የጠብታ ያህል ነው” ያሉት ኃላፊው፤ የገንዘብ ችግሩን ለመቅረፍ እያንዳንዱ እጩ የራሱን ወጪ በግሉ መሸፈኑን ተናግረዋል፡፡
ፓርቲው በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ በራሪ ወረቀቶች ማሰራጨቱን የጠቆሙት ኃላፊው፤ በኦሮሚያ ክልል ብቻ በኦፌኮ አማካኝነት ወደ 5 ሚሊዮን በራሪ ወረቀቶች ተበትነዋል ብለዋል፡፡ በሌሎች ክልሎችም በሚሊዮን የሚቆጠሩ የቅስቀሳ በራሪ ወረቀቶች መሰራጨታቸውን ተናግረዋል፡፡
“መድረክ ያሰበውን ያህል ቅስቀሳ እንዳያደርግ የፋይናንስ እጥረት ተግዳሮት ሆኖበታል” ያሉት አቶ ጥላሁን፤ በዚህም ምክንያት ቢልቦርድ ማዘጋጀት አልተቻለም ብለዋል፡፡
501 እጩዎችን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያቀረበው ገዥው ፓርቲ ኢህአዴግ በበኩሉ፤ እስካሁን ለቅስቀሳ ስራ ያወጣው አጠቃላይ ወጪ በትክክል እንደማይታወቅ ጠቁሞ ፓርቲው ከምርጫ ቦርድ የተመደበለትን 14 ሚሊዮን ብር ገደማ፣ ከአባላት ከተሰበሰቡ መዋጮዎች ጋር በማጣመር ስኬታማ የቅስቀሳ ስራ መስራቱን አስታውቋል፡፡
በ2002 ምርጫ ከቅስቀሳ ዕቅዳችን 70 በመቶ ብቻ ነበር ያሳነካው ያሉት የኢህአዴግ ፅ/ቤት የህዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ኃላፊ አቶ ደስታ ተስፋው በዘንድሮ ምርጫ 98 በመቶ ውጤታማ ቅስቀሳ አድርገናል ብለዋል፡፡ ኢህአዴግ ቢልቦርዶችን፣ በየአካባቢው የሚደረጉ ህዝባዊ ስብሰባዎችን፣ ፖስተሮችን እንዲሁም፣ የመኪና ላይ ቅስቀሳዎችን በማከናወን ሁሉንም አማራጮች አሟጦ መጠቀሙንና ለህዝቡ በበቂ ሁኔታ ተደራሽ መሆኑን አቶ ደስታው አክለው ገልጸዋል፡፡ 

ምርጫ ቦርድ በህገወጦች ላይ የከፋ እርምጃ እወስዳለሁ ብሏል
ሞባይል ስልክ ይዞ መግባት አይፈቀድም

ነገ በሚካሄደው 5ኛው አገር አቀፍ ምርጫ ላይ በየምርጫ ጣቢያዎቹ ጥብቅ ፍተሻና ጥበቃ እንደሚደረግ የጠቆመው ምርጫ ቦርድ፤ ከህግና ሥርዓት ውጪ ሆነው በተገኙ ወገኖች ላይ ጥብቅ እርምጃ እንደሚወሰድ አስታወቀ፡፡ መራጮች ወደ ምርጫ ጣቢያዎች በሚሄዱበት ወቅት ከምርጫ ካርዳቸውና ከመታወቂያ ወረቀታቸው ሌላ ምንም አይነት ነገሮችን ይዘው መግባት እንደማይፈቀድላቸውም ተገልጿል፡፡
የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና ከትናንት በስቲያ በሒልተን ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት፤ ምርጫው ሠላማዊ በሆነ መንገድ እንዲካሄድ ለማድረግ የሚያስችል ቅድመ - ዝግጅት ተጠናቋል፡፡ መራጮች ወደ ምርጫ ጣቢያ ሲሄዱ ሞባይል ስልካቸውንም ሆነ ሌላ ምንም ዓይነት መሣሪያዎችን ይዘው መግባት አይፈቀድላቸውም፡፡
የምርጫው በሰላማዊ መንገድ መጠናቀቅ የቦርዱ ኃላፊነት መሆኑን ያስገነዘቡት ፕሮፌሰር መርጋ፤ ይህንን ሁኔታ ለማስጠበቅም ሠላማዊ የምርጫ ሂደትን ለማደፍረስ በሚንቀሳቀሱ ወገኖች ላይ ቦርዱ የሚወስደው እርምጃ የከፋ ይሆናል ብለዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ በቂ ዝግጅት ተደርጓል ሲሉ አስጠንቅቀዋል፡፡

አሁን የወጣቱ ልብና አዕምሮ ከአገር ውጭ ነው
ከፍተኛው የስደት መንስኤ የተሻለ ህይወት ፍለጋ ነው (ILO)
“በአገር ቤት ሰርቶ መለወጥ ይቻላል የሚለው ዲስኩር ለውጥ አያመጣም”
    አሊ ሃሰን፤ በቅርቡ በሜዲትራኒያን ባህር ህይወታቸውን ያጡት 8 የመርካቶ አባኮራን ሠፈር ልጆች አብሮ አደግ ነው፡፡ መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም “በሰላም ያግባችሁ” ብሎ የሸኛቸው አብሮ አደጐቹ ድንገት የሞታቸውን መርዶ ሲሰማ ክፉኛ ከመደንገጡ የተነሳ ማመን አቅቶት እንደነበር ይናገራል፡፡ “ቤተሰቦቻቸው በድህነት ያሳደጓቸው አብሮ አደጐቼ፣ ያልፍልናል ብለው ነው ህይወታቸው ያለፈው” የሚለው የ25 አመቱ አሊ፤ እነሱ ከወራት በፊት ወደ ሊቢያ ለመሻገር የሱዳን ቪዛ ሲሰጣቸው በቂ ገንዘብ በእጁ ላይ ባለመኖሩ ተነጥሏቸው እንደቀረና ገንዘብ ሲያገኝ እንደሚቀላቀላቸው ቃል ገብቶላቸው መለያየታቸውን ያስታውሳል፡፡ አሁን አሊ ወደ ሱዳን የሚያስገባውን የ2 ወር የቱሪስት ቪዛ ለማግኘት እየተሯሯጠ ሲሆን በቅርቡ ተጓዥ ነኝ ብሏል - ለአዲስ አድማስ፡፡ “ይህን ሁሉ ሞትና አሰቃቂ ነገር እየሠማህ እንዴት ትሄዳለህ?” በሚል ለቀረበለት
ጥያቄ ሲመልስ፤ “እነሱ እድላቸውን ሞክረው አልተሳካላቸውም፤ እኔም እድሌን ልሞክር” ነው ያለው፡፡ በሃገር ቤት ሠርቶ መለወጥ ይቻላል፤ አሹቅ በልተን በእናቶቻችን ጉያ ውስጥ መኖር ምናምን  የሚባለው ለኔ ትርጉም የለውም” የሚለው አሊ፤ እዚህ ሀገር ተቀምጬ እስከ መቼ ከእጅ ወደ አፍ የሆነ ኑሮ እመራለሁ ሲልም”  ይጠይቃል፡፡ ከሊስትሮ ጀምሮ አነስተኛ ሥራዎችን መስራቱን የሚናገረው ወጣቱ፤ ከ6 አመት በላይ የተለያዩ ተባራሪ የንግድ ስራዎችን ቢሰራም ከቤተሰብ ጥገኝነት መላቀቅ እንዳቃተው ይናገራል፡፡ ከእናቱና
ከሁለት እህቶቹ ጋር እንደሚኖር የጠቆመው አሊ፤ ከ3 አመት በፊት አባቱ መሞታቸውን ተከትሎ እህቶቹን የማስተማርና ወላጅ እናቱን የመጦር ሃላፊነት  እንደወደቀበት ይናገራል፡፡ ቤተሰቤ ፆም እንዳያድር ከጠዋቱ 12 ሰአት ጀምሮ እስከ ምሽት 2 ሰዓትና 3 ሰዓት ድረስ የተለያዩ ተባራሪ ስራዎችን ስሰራ ብውልም በቀን ከ60 እና 70 ብር በላይ ገቢ አላገኝም ይላል - ወጣቱ በምሬት። “በ70 ብር ምን ልታደርግበት ነው? ቁርስና ራትን እንተወውና ምሣ እንኳ ልብላ ቢባል ከ20 ብር በታች የሚሸጥ ምግብ የለም” የሚለው ወጣቱ፤ በቀን የሚያገኛትን 60 እና 70 ብር እንደምንም አብቃቅቶ ቤተሰቡን ከረሃብ እንደሚታደግ ነው የገለፀው፡፡ ግን በዚህ ሁኔታ እስከ መቼ እቀጥላለሁ በማለት ይጠይቃል፡፡ እናም ቀድሞ በጣሊያን አድርጐ እንግሊዝ ሃገር የገባ አብሮ አደጉ አሁን እስከ ሱዳን ሊያደርሰው የሚችል ገንዘብ እንደላከለትና በዚያም አስፈላጊውን የጉዞ ዝግጅት በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ተናግሯል፡፡ ባለፈው ሳምንት የ7ቱን አብሮ አደግ ጓደኞቻቸውን ሞት የተረዱት የአባኮራን ሰፈር ወጣቶች፤ ክፉኛ አዝነው የነበረ ቢሆንም አብዛኞቹ ግን ከአገር የመውጣት ከፍተኛ ጉጉት እንዳላቸው ገልፀውልናል፡፡ “እዚህ ሃገር 24 ሰዓት ቢሠራ ጠብ የሚል ነገር የለም” የሚሉት ወጣቶቹ፤ ከሃገር ከተወጣ ግን በተጨባጭ መለወጥ እንደሚቻል ከዚህ ቀደም የሄዱ ጓደኞቻቸውን በምሳሌነት እየጠቀሱ ያስረዳሉ፡፡ በሳሪስ አቦ አካባቢ በሊስትሮ ስራ የተሠማራው ጋዲሣ፤ ከትውልድ ሀገሩ አምቦ ወደ አዲስ አበባ የመጣው በመዲናይቱ ሰርቶ ለመለወጥ የሚል ዓላማ አንግቦ ሳይሆን ፓስፖርት ለማውጣት ነው፡፡ ፓስፖርቱን ከ4 ወራት በፊት ማውጣቱን የሚናገረው ወጣቱ፤ አሁን ደግሞ የሱዳን ቪዛ ለማግኘት
እየጣረ መሆኑን ይገልፃል፡፡ “በአይኤስ አሸባሪ ቡድን ስለታረዱትም ሆነ በሜዲትራኒያን ባህር ስለሰመጡት ሰዎች በሚገባ ሰምቻለሁ፤ መስቀል አደባባይ አይኤስን ለማውገዝ በተጠራው ሠልፍ ላይም ተሳትፌያለሁ፤ ግን ወደ አውሮፓ በየትኛውም መንገድ የመሄድ ሃሳቤን አልሰረዝኩም። ምክንያቱም እዚህ ጠብ የሚል ነገር የለም፤ ጓደኞቼ የደረሱበት ደረጃ መድረስ እፈልጋለሁ” ሲል ዓላማውን ገልጿል፡፡ ከቴክኒክና ሙያ በአውቶ ኤሌክትሪሲቲ በሠርተፍኬት መመረቁን የሚናገረው ጋዲሳ፤ እንግሊዝ ወይም ፈረንሳይ ቢገባ በተማረው ሙያ ስራ ሊያገኝ እንደሚችል ተስፋ ያደርጋል፡፡ ከሁለት አመት በፊት በጣሊያን አድርገው እንግሊዝ የገቡ ሁለት አብሮ አደጐቹ በተማሩበት የመካኒክ ዘርፍ በጋራዥ ውስጥ ተቀጥረው እየሠሩ መሆኑን እንደነገሩት የጠቀሰው ወጣቱ፤ ጓደኞቹ በሁለት አመት ጊዜ ውስጥም ለቤተሰቦቻቸው ገንዘብ መላክ እንደጀመሩ ይናገራል፡፡ የተወሰነ ለጉዞው ጉዳይ ማስፈፀሚያ የሚሆን ገንዘብም ለእርሱ እንደላኩለት ገልጿል፡፡ እናትና አባቱ ከሞቱ በኋላ ከሶስት ወንድሞቹ ጋር የተካፈላትን ውርስ ሸጦ ለጉዞው የሚያስፈልገውን ገንዘብ ለማሟላት ማሰቡንም ይናገራል፡፡ በጉዞህ ላይ አደጋ ቢያጋጥምህስ? በሚል ሲጠየቅ፤ “እሱ የእድል ጉዳይ ነው፤ እድሌን እሞክራለሁ” ባይ ነው፡፡ በሌላ በኩል በ2006 ዓ.ም ከሣኡዲ በተባረሩ ኢትዮጵያውያን ዙሪያ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ቀርፆ የሚንቀሳቀሰው የክርስቲያን ተራድኦ በጎ አድራጎት ድርጅት (CCRDA) ተመላሾቹ ስላሉበት ሁኔታ የሚገመግም የጥናት ሰነድ ሰሞኑን ይፋ ያደረገ ሲሆን ቀላል የማይባል ቁጥር ያላቸው የሣውዲ ተመላሾች ተመልሰው ከሃገር መሰደዳቸው ተጠቁሟል፡፡ በፕሮግራሙ ላይ ተጋባዥ ከነበሩ ጥቂት ተመላሾች መካከልም ሁለት ወጣቶች አሁን ያሉበትን ሁኔታ ለተሰብሳቢው ገልፀው ነበር፡፡ ሣውዲ አረቢያ በሰው ቤት ለሁለት አመት ተቀጥራ ትሠራ እንደነበር የገለፀችው በ20ዎቹ መጀመሪያ ላይ የምትገኘው ዘይነብ፤ ለሁለት አመት የሠራችበት ደሞዟን ተከልክላና ተባራ ጐዳና ወድቃ የነበረ ባዶ እጇን ወደ ሀገሯ እንደተመለሰችም ትናገራለች፡፡ በወር 700 ሪያል እንደሚከፈላት ተዋውላ ትሠራ እንደነበር የገለፀችው ዘይነብ፤ ሣውዲ ለሁለት አመታት የደከመችበት ወደ 16ሺህ ሪያል ገደማ ሣይከፈላት ባዶ እጇን ከተመለሰች በኋላ አንድ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት አስጠግቷት ለአንድ አመት እንደተንከባከባትና ከአንድ አመት በኋላ በምግብ ስራ ሙያ አሠልጥኗት ከ8 ሺህ ብር በላይ አውጥቶ የማብሰያ ማሽን ገዝቶ በመስጠት “በዚህ ስሪና ራስሽን ለውጪ” እንዳላት ተናግራለች፡፡ ይሁን እንጂ ዘይነብ ማሽኑን ታቅፎ ከመቀመጥ ውጪ ሥራ ልትሠራበትና ህይወቷን ልታሻሽልበት አልቻለችም፡፡ “መንግስት የመስሪያ ቦታ ሊሠጠኝ ፍቃደኛ ባለመሆኑና የንግድ መነሻ የሚሆን ገንዘብም ማግኘት ባለመቻሌ ዝም ብዬ ተቀምጬአለሁ” ብላለች፡፡ “በወጣትነቴ የሰው ጥገኛ ሆኜ መኖሬ ያሳስበኛል” ስትል የምታማርረው ዘይነብ፤ በሳውዲ ብዙ ግፍና መከራ የደረሰባት ቢሆንም አሁንም እድሉን ብታገኝ ወደዚያው አሊያም ወደ ሌላ ሀገር ከመሄድ ወደ ኋላ እንደማትል ገልፃለች፡፡ ሀገር ቤት ባለው ሁኔታ ተስፋ መቁረጧንም ወጣቷ በምሬት አስረድታለች፡፡
ሣውዲ እያለች ልጆቿን ጥሩ ትምህርት ቤት ታስተምር፣ ቤተሰቦቿንም በሚገባ ትረዳ እንደነበር ያወሳችው ሌላኛው ወጣት በበኩሏ፤ በአሁን ሰአት ከልጆቿ ጋር የቤተሰቦቿ ጥገኞች ለመሆን እንደተገደዱ ትገልፃለች፡፡
“በቴሌቪዥን ስጠየቅ በሃገር ቤት ሠርቶ መለወጥ ይቻላል ብዬ ነበር” ያለችው ወጣቷ፤ አሁን ግን ይሄን የማለት ድፍረት የለኝም ብላለች፡፡ መንግስት አደራጅቶና ብድር አመቻችቶ መለስተኛ የንግድ ስራ ከጓደኞቿ ጋር መጀመሯን እንዲሁም እዳቸውንም መክፈል መጀመራቸውን የጠቆመችው ወጣቷ፤ እዳቸውን እንኳ ሳይጨርሱ የ5ሺህ ብር ግብር እዳ አለባችሁ እንደተባሉ ተናግራለች፡፡ “በዚህ ሁኔታ እንዴት ነው ተመላሾች ሊቋቋሙና በሀገራቸው ሠርተው ሊለወጡ የሚችሉት?” ስትልም ትጠይቃለች፡፡በቤተሰቦቿ እጅ ላይ ተመልሣ መውደቋ ክፉኛ እንደሚያሳስባት የገለፀችው ወጣቷ፤ የቤተሰቦቿንም ሆነ የልጆቿን ህይወት ቀድሞ ወደነበረበት ለመመለስ የግዴታ ወደ ውጭ ወጥታ መስራት እንዳለባት ማመኗንና ለመሄድ አጋጣሚዎችን እየጠበቀች መሆኑን በምሬት ተናግራለች፡፡ በመድረኩ ላይ የታደሙት የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካይ በበኩላቸው፤ መንግስት ስደቱን እያባባሱ ነው በሚላቸው ህገ ወጥ ደላሎች ላይ እርምጃ እየወሰደ መሆኑን እንዲሁም ዜጐች በሀገራቸው ሰርተው የሚለወጡበትን ሁኔታ ለማመቻቸት ከወትሮው በተለየ እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ከመንግስት ጐን ሌሎች ባለድርሻ አካላትና ህብረተሰቡ መሣተፍ እንዳለበትም ተወካዩ አሳስበዋል፡፡ መንግሥታዊ ባልሆነ ድርጅት ውስጥ የማህበረሰብ ጥናት (ሶሺዮሎጂ) ባለሙያ በመሆን የሚሰሩት ዶ/ር ተካልኝ አባተ በበኩላቸው፤ አሁን ከመንግስት እየቀረቡ ያሉት ምክንያቶችና የመፍትሔ ሃሳቦች በቂም፤ አሣማኝም አይደሉም ይላሉ፡፡ “በሃገር ቤት ሠርቶ መለወጥ ይቻላል የሚለው የቀን ተቀን ዲስኩር አሠልቺ ከመሆን ያለፈ የግንዛቤ ለውጥ አያመጣም፣ መንግስት የፖሊሲ አማራጮቹን በሚገባ ማየትና መገምገም ይገባዋል” ብለዋል ምሁሩ፡፡ የማህበረሰብ ጥናት ባለሙያዎችን ጨምሮ የተለያዩ ምሁራን በጉዳዩ ላይ ጥልቀት ያለው ጥናትና ምርምር እንዲያደርጉም መንግስት መጋበዝ
እንዳለበት ዶ/ሩ ይመክራሉ፡፡ አለማቀፉ የሰራተኞች ድርጅት (ILO) ከግንቦት እስከ ሐምሌ 2014 ወደ አገራቸው በተመለሱ ስደተኞች ላይ ያደረገው ጥናት ውጤት እንደሚያመለክተው፤ ለስደታቸው መንስኤ ከሆኑ ምክንያቶች ከፍተኛውን ደረጃ የሚይዘው የተሻለ ህይወትን ፍለጋ የሚደረገው ስደት ነው፡፡ በህገወጥ ደላሎች ጉትጐታ አማካኝነት የሚደረገው ስደት እጅግ አነስተኛ ቁጥር ያለው መሆኑን አመልክቷል፡፡ እንደ ILO ሪፖርት፤ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ከስደት ተመላሾች ዳግም መሰደድ የሚፈልጉ ናቸው፡፡




Saturday, 16 May 2015 11:29

የፍቅር ጥግ

ትዳር የዕድሜ ጉዳይ ሳይሆን ትክክለኛውን ሰው የማግኘት ጉዳይ ነው፡፡
ሶፍያ ቡሽ
ሚስቴ የልቤ ጓደኛ ናት፤ ያለ እሷ መኖርን ላስበው አልችልም፡፡  
ማት ዳሞን
 ትዳር ግሩም ተቋም ነው፡፡ ግን ማነው በተቋም ውስጥ መኖር የሚሻው?
ግሮቶ ማርክስ
ሴት ባሏን ለመለወጥ የማትሞክርበት ብቸኛ ወቅት ቢኖር የጫጉላ ሽርሽር ነው፡፡
ኢቫን ኢሳር
ሴት ለምንድን ነው 10 ዓመት ባሏን ለመለወጥ ከለፋች በኋላ “ይሄ ያገባሁት ወንድ አይደለም” ብላ የምታማርረው?
ባርባራ ስትሪላንድ
የትዳር ችግሩ በእያንዳንዱ ምሽት ፍቅር ከሰሩ በኋላ መፍረሱ ነው፡፡ እናም በእያንዳንዱ ጥዋት ከቁርስ በፊት እንደገና መገንባት አለበት፡፡
ጋብሬል ግራሽያ ማርኪውዝ
ትዳር ገነትም ገሃነምም አይደለም፤ የንስሃ ቦታ ነው፡፡
አብርሃም ሊንከን  
ደስተኛ ያልሆነ ትዳርን የሚፈጥረው የፍቅር እጦት ሳይሆነ የጓደኝነት (ወዳጅነት) እጦት ነው፡፡
ፍሬድሪክ ኒቼ
ጥሩ ባል ጥሩ ሚስትን ይፈጥራል፡፡
ጆን ፍሎሪዮ
ፍቅረኛህ ከጋብቻ በኋላ እንዴት እንደምትይዝህ ለማወቅ ከፈለግህ ከትንሽ ወንድሟ ጋር ስታወራ አዳምጣት፡፡
ሳም ሊቨንሰን
የመጀመሪያውን ለፍቅር ብለህ ታገባለህ፡፡ ሁለተኛውን ለገንዘብ ብለህ፣ ሶስተኛውን ለጓደኝነት ስትል ታገባለህ፡፡
ጃኪ ኬኔዲ

በአገሪቱ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 በላይ ሰዎች ሞተዋል
      አገር ጥለው የተሰደዱ ዜጎች ከ500 ሺህ በላይ ደርሰዋል

    የቀድሞው የብሩንዲ የደህንነት ቢሮ ሃላፊ ሜጀር ጄኔራል ጎዲፍሮይድ ኒዮምባሬህ ባለፈው ረቡዕ በአገሪቱ መዲና ቡጁምቡራ ከሚገኝ የጦር ካምፕ በሬዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት፣ የፕሬዚደንት ኑኩሩንዚዛ አገዛዝ ማክተሙንና አገሪቱን የመምራቱን ሃላፊነት የሚረከብ ጊዜያዊ ብሄራዊ ኮሚቴ መቋቋሙን ያስታወቁ ሲሆን አገሪቱ በከፍተኛ ውጥረት ውስጥ ትገኛለች፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ከሌሎች አገራት መንግስታት ጋር በጉዳዩ ዙሪያ ለመምከር ወደ ታንዛኒያ መሄዳቸውን ተከትሎ፣ ጄኔራሉ በአገሪቱ መፈንቅለ መንግስት መካሄዱን ማስታወቃቸውንና በሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በቡጁምቡራ አደባባይ በመውጣት ደስታቸውን እንደገለጹ የዘገበው ቢቢሲ፤ አገዛዙን የሚቃወሙ ወታደሮችም በሁለት የጦር ታንኮች ታግዘው ወደ መዲናዋ ማዕከላዊ ክፍል ማምራታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ተቃውሞው የበለጠ ተጠናክሮ መቀጠሉንና ከትናንት በስቲያም በመንግስት ጦርና በተቃዋሚ ሃይሎች መካከል በቡጁምቡራ ግጭት እንደተከሰተ የጠቆመው ዘገባው፣ ስርዓቱ ይፍረስ የሚለውን የተቃዋሚዎች አቋም በመደገፍ ተቃውሞውን ከተቀላቀሉት የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስትር ጋር በተደረገ ድርድር መፈንቅለ መንግስቱ መቆሙን አንድ የአገሪቱ ጦር መሪ ማስታወቃቸውንም ገልጧል፡፡
ፕሬዚዳንት ንኩሩንዚዛ፤ መፈንቅለ መንግስት እንደታወጀባቸው ሲያውቁ ከታንዛኒያ ወደ ብሩንዲ ቢመለሱም፣ ሜጀር ጄኔራል ጎዲፍሮይድ ኒዮምባሬህ አውሮፕላን ማረፊያውና የአገሪቱ ድንበሮች እንዲዘጉ በማዘዛቸው፣ ፕሬዚዳንቱ ወደ አገራቸው መግባት እንዳልቻሉና ወደ ዳሬ ሰላም መመለሳቸውን ያስታወቀው የቢቢሲ ዘገባ፣ ፕሬዚዳንቱ በትዊተር ገጻቸው በኩል ከትናንት በስቲያ ባስተላለፉት መልዕክት የተቃውሞ እንቅስቃሴው በቁጥጥር ስር ውሏል፣ ህገመንግስታዊ ስርአቱም ከአፍራሽ ሃይሎች ተጠብቋል ብለዋል፡፡
የመንግስት ጦር የፕሬዚደንቱን ቤተ መንግስት፣ የብሄራዊ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ጣቢያውንና አውሮፕላን ማረፊያውን ጨምሮ በከተማዋ የሚገኙ ቁልፍ ቦታዎችን እንደተቆጣጠረ ቢያስታውቅም፣ የመፈንቅለ መንግስቱ መሪ ግን መዲናዋን ሙሉ በሙሉ በቁጥጥራችን ውስጥ አድርገናል ሲሉ አስተባብለዋል፡፡
የመፈንቅለ መንግስቱ ቃል አቀባይ ቬኖን ንዳባንዜ በበኩላቸው፤ “መንግስት ተቃውሞውን እንዲገቱ ያሰማራቸው ወታደሮችም ከጎናችን ቆመዋል፣ ድሉ የኛ ነው” ሲሉ ከትናንት በስቲያ ለአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ተናግረዋል፡፡
ከሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖች፣ ከሃይማኖት መሪዎችና ከፖለቲከኞች ጋር በመሆን በአገሪቱ የሽግግር መንግስት መቋቋም የሚችልበትን ሁኔታ እያመቻቹ እንደሚገኙም ሜጀር ጄኔራል ጎዲፍሮይድ ኒዮምባሬህ ተናግረዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ኑኩሩንዚዛ ህገ መንግስቱ ከሚፈቅድላቸው ውጭ ያለ አግባብ ለሶስተኛ ዙር በፕሬዚዳንትነት ለመወዳደር መዘጋጀታቸውን የተቃወሙ በርካታ የአገሪቱ ዜጎች አደባባይ ወጥተው ተቃውሟቸውን ከማሰማት ባለፈ፣ አገዛዙን ከስልጣን ለማውረድ መነሳታቸውን የገለጹት ጄኔራሉ፤ ጊዜያዊ ኮሚቴው ብሄራዊ አንድነትን መልሶ በመፍጠርና ምርጫው በፍትሃዊና ሰላማዊ ሁኔታ መካሄድ የሚችልበትን ሁኔታ ለማመቻቸት  እንደሚሰራ አስታውቀዋል፡፡
ከሁለት ሳምንታት በላይ በዘለቀው ተቃውሞ ከ20 በላይ ዜጎች ለሞት መዳረጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ አገር ጥለው የተሰደዱ ብሩንዲያውያን ዜጎች ቁጥርም ከ500 ሺህ በላይ መድረሱን አመልክቷል፡፡

ዝንጀሮዎችም እንኳን ከዛፍ ላይ ይወድቃሉ፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ሰባት ጊዜ ወድቀህ በስምንተኛው ተነስ፡፡
የጃፓናውያን አባባል
የበሰበሰ እንጨት አይቀረፅም፡፡
የቻይናውያን አባባል
አንዲት ውሸት ሺ እውነቶችን ታጠፋለች፡፡
የጋናውያን አባባል
አመድ መልሶ የሚበተነው ወደበተነው ሰው ፊት ነው፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል
ለመብላት የቸኮለ አፉን ይቃጠላል፡፡
የሉሃያ አባባል
ሙቅ ውሃ የሆነ ጊዜ ላይ ቀዝቃዛ እንደነበር አይዘነጋም፡፡
የአይቮሪኮስት አባባል
የልብን ‹ወሬ› ከፈለግህ ፊትን ጠይቀው፡፡
የጊኒያን አባባል
በአፉ አጥንት የያዘ ውሻ መጮህ አይችልም፡፡
የዛምብያውያን አባባል
ሆድ ከፊት ለመሰለፍ አይፈራም፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል
የመቃብርን ስቃይ የሚያውቀው የሞተ ሰው ብቻ ነው፡፡
የስዋሂሊ አባባል
አይጥ የቱንም ያህል ብትሰክር ድመት አልጋ ላይ መተኛት የለባትም፡፡
የካሜሩናውያን አባባል
ጨለማውን ከመራገም ሻማ ማብራት ይሻላል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ዛፍ በፍሬው ይታወቃል፡፡
የዙሉ አባባል
ትንሽም ኮከብ ብትሆን ጨለማን ትሰብራለች፡፡
የፊንላንዳውያን አባባል
ዕድል ስትጎበኝህ ሁሉም ሰው የምትኖርበትን ያውቀዋል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ጥሩ ምክር እንደሚመር መድኀኒት ነው፡፡
የቻይናውያን አባባል



 የኢራቅ መከላከያ ሚኒስትር አይሲስ በመባል የሚጠራው ጽንፈኛ አራጅ የሽብር ቡድን ምክትል መሪ የሆነው አቡአላ አልአፍሪ በህብረቱ ሀይሎች በተካሄደ የአየር ጥቃት ባለፈው ማክሰኞ መገደሉ ይፋ ተደርጓል፡፡  
በዩቲውብ የተለቀቀው አጭር የቪዲዮ ፊልም እንደሚያሳየው፤ አቡ አላ አልአፍሪ የተገደለው በኢራቅ የታል አፋር ከተማ በሚገኝ አንድ መስጊድ ውስጥ ነው፡፡ አብዱራህማን ሙስጠፋ አልቃዱሊ በሚል ተለዋጭ ስም የሚታወቀውና በ1957 ሞሱል ከተማ ውስጥ የተወለደው አቡ አላ አልአፍሪ የኢራቅ የአልቃኢዳ ቡድን ምክትል መሪና የሞሱል ከተማ ክንፍ ዋና አዛዥ በመሆን አገልግሏል፡፡
የፊዚክስ መምህር የነበረው አቡ አላ አልአፍሪ፤ የኢራቅ የአልቃኢዳ ምክትል መሪ በነበረበት ወቅት በኦሳማ ቢንላደን  ዘንድ ከፍ ያለ ሞገስ ማግኘት የቻለና ለአይሲስ ከፍተኛ መሪነት በዋናነነት የታጨ ሰው ነበር፡፡ የቱርክሜን ብሔረሰብ አባላት ከሆኑ የአይሲስ ከፍተኛ መሪዎች ግንባር ቀደም የሆነው አቡአላ አልአፍሪ የአይሲስ ዋነኛ መሪ መሆን ያልቻለውና የመሪነቱ ስልጣን ለአቡበከር አልባግዳዲ የተሰጠው አቡበከር አልባግዳዲ የዘር ሀረጉ ከነብዩ ሞሀመድ የዘር ሀረግ ስለሚመዘዝ ብቻ ነው፡፡
አቡአላ አልአፍሪ ከመገደሉ በፊት በተፈፀመበት የአየር ጥቃት ክፉኛ ቆስሎ አልጋ ላይ የዋለውን የአይሲስ መሪ አቡበከር አልባግዳዲን ተክቶ ቡድኑን ሲመራ ነበር ተብሏል፡፡
አሜሪካ በቁጥጥር ስር ለማዋል በጥብቅ ከምትፈልጋቸው ዋነኛ አሸባሪዎች ውስጥ አንዱ መሆኑን በመጥቀስ “ጠቁሞ ላስያዘው” የ7 ሚ. ዶላር ወሮታ እከፍላለሁ ስትል የነበረ ሲሆን የአቡአላ አልአፍሪን መገደልን ገና አምና የተቀበለችው አትመስልም፡፡ የዚህን ነብሰ በላ አሸባሪ መሞት ባይኔ በብረቱ አይቼ ካላረጋገጥኩ በቀር የሰውየው መገደል ዜና ከሆዴ አይገባም ብላለች፡፡

Saturday, 16 May 2015 11:06

የፀሐፍት ጥግ

ህክምና ህጋዊ ሚስቴ ናት፤ ስነፅሁፍ ውሽማዬ ናት፡፡ አንዳቸው ሲሰለቹኝ ከአንዳቸው ጋር ሌሊቱን አሳልፋለሁ፡፡
አንቶን ቼኮቭ
የሥነፅሁፍ ማሽቆልቆል የህዝብን ማሽቆልቆል ያመለክታል፡፡
ቮን ገተ
ግጥም የሥነ ፅሑፍ ዘውድ ነው፡፡
ሶመርሴት ሟም
ባህልን ለማጥፋት መፃሕፍትን ማቃጠል የለብህም፡፡ ሰዎች መፃሕፍት እንዳያነቡ ማድረግ ብቻ በቂ ነው፡፡
ሬይ ብራድበሪ
ህይወት ያለ ስነፅሁፍ ገሃነም ነው፡፡
ቻርለስ ቡከውስኪ
የምታነበው ሳይንስ ከሆነ አዳዲሶቹን ሥራዎች አንብብ፡፡ ሥነፅሑፍ ከሆነ ግን የጥንቶቹን አንብብ፡፡
ኢድዋርድ ጂ. ቡልዌር - ሊቶን
ሴቶች፤ ፍቅር ረዥም ልብወለድ እንዲሆን ይሻሉ፤ ወንዶች ደግሞ አጭር ልብወለድ፡፡
ዳፍኔ ዲ ማውሪየር
ቤተ መፃህፍት ውስጥ የሚጠፋ አንድ ሰዓት፣ በቤተ ሙከራ ውስጥ ከሚጠፋ አንድ ወር ጋ እኩል ነው፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
መፃሕፍት በሌሉበት መኖር አልችልም፡፡
ቶማስ ጄፈርሰን
መፃሕፍት በሁለት መደቦች ይከፈላሉ፡፡ የወቅቱ መፃህፍትና የምንጊዜም መጻህፍት በሚል፡፡
ጆን ሩስኪን
ንባብ ሙሉ ሰው፤ ጥሞና ጥልቅ ሰው፣ ንግግር ደግሞ ግልፅ ሰው ያደርጋሉ፡፡
ቤንጃሚን ፍራንክሊን
ማንበብ በራስ ጭንቅላት ከማሰብ ይልቅ በሰው ጭንቅላት ከማሰብ እኩል ነው፡፡
አርተር ስኮፊነር
በህይወት ውጣ ውረድ ውስጥ ብልሆች መፅናኛቸውን የሚያገኙት ከመፃሕፍት ነው፡፡
ቪክቶር ሁጎ
ሳላነብ ከምቀመጥ ይልቅ የጊዜ ሰሌዳ ወይም ካታሎግ ባነብ እመርጣለሁ፡፡
ሶመርሴት ሟም
መፃህፍትን ማንበብ ያለብህ እንደ መድኀኒት በትዕዛዝ እንጂ በማስታወቂያ አይደለም፡፡
ጆን ሩስኪን