Administrator

Administrator

“የዝምታ ጩኸት” በተሰኘው የመጀመሪያ የግጥም መድበሏ የምትታወቀው የትዕግስት ዓለምነህ ሁለተኛ ስራ “ዕልልታና ሙሾ” የግጥም መድበል የፊታችን ሰኞ በብሔራዊ ቴአትር ከ11፡30 ጀምሮ ይመረቃል፡፡ በመድበሉ ውስጥ በተካተቱት ግጥሞች ፍቅር፣ ሀገር፣ አንድነት፣ ወቅታዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች የተዳሰሱ ሲሆን ለዛ ያለው የቃላት አጠቃቀሟም አስደሳች ነው ተብሏል፡፡ ገጣሚዋ በትምህርት አለም ያፈራቻቸው ድግሪዎች ከስነ - ፅሁፍ ጋር ባይዛመዱም ባላት ተሰጥኦ በርካታ ጠንካራ ግጥሞችን ለአንባብያን ማቅረቧ ተጠቁሟል፡፡  በምርቃት ፕሮግራሙ ላይ ወጣትና አንጋፋ ገጣሚያን በመሶብ የባህል ባንድ ታጅበው የስነ ጽሑፍ ስራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡና ሌሎች በባህላዊ ለዛ የተቃኙ ዝግጅቶችም እንደሚኖሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡ “ዕልልታና ሙሾ” በ120 ገፆች የተቀነበበ መድበል ሲሆን ዋጋው 40 ብር ነው ተብሏል፡፡  

ጥሬ ስጋን ጨምሮ በአገሪቱ የሚገኙ የባህል ምግብና መጠጦችን በስፋት የሚያስተዋውቅ “በጥቅምት አንድ አጥንት” የተሰኘ የምግብና የመጠጥ ፌስቲቫል ዛሬ በኤግዚቢሽን ማዕከል  ይከፈታል፡፡
 ሴንቸሪ ፕሮሞሽን ሰርቪስ፤ ከቢጂ አይ ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ያዘጋጀውና ዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ የሚካሄደው ይኸው የምግብና የመጠጥ ፌስቲቫል፤ የአገሪቱን የባህል ምግቦችና መጠጦች በማስተዋወቅ ለቱሪዝም ኢንዱስትሪው ዕድገት የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ የፕሮግራሙ አዘጋጆች ገልፀዋል፡፡ ፌስቲቫሉ እስከ ነገ ጥቅምት 14 ቀን 2008 ዓ.ም ድረስ ይቆያል፡፡

     በርካታ የስፌት መኪኖች በሰልፍ ተደርድረዋል፡ አንዱ እጅግ ዘመናዊ መሳሪያ ሰፊ ቦታ ይዞ እየተሽከረከረ እንዴት ደረጃ በደረጃ እንደሚሰራ ያሳያል፡፡ ገሚሱ አርማ፣ መለያና የንግድ ምልክት ይጠልፋል፡፡ የልብስ ታጎች የሚሰሩም ሞልተዋል፡ ብዙ ኢንዱስትሪዎች የተለያየ ቀለም ያላቸው ድውሮች አቅርበዋል፡፡ የሚያመርቷቸውን የሸሚዝ ኮሌታዎች ብቻ ዓይነት በዓይነት የደረደሩም ብዙ ናቸው፡፡ ከውስጥና ከላይ የሚለበሱ ከጥበብ የተሰሩ የህፃናት፣ የሴቶችና አዋቂ ልብሶች፣ የተለያየ ዓይነትና መጠን ያላቸው የህፃናትና የአዋቂ ካልሲዎች፣ ፒጃማዎች፣ የበጋና የክረምት ልብሶች፣ ሙሉ ልብሶች፣ ኮቶች፣ ጂንሶች፣ … የደረደሩ ሞልተዋል፡፡ የተለያየ ዓይነትና ዲዛይን ያላቸው የሴት ቆዳ ቦርሳዎች፣ የወንድና የሴት ጫማዎች፣ ከጥጥ የተሰሩ ሻርፖች፣ በቀለም የደመቁ የአፍሪካውያን ልብሶችና ጨርቆች፣ ጌጣ ጌጦች፣ የተለያዩ የማሳጅና የስፓ ፎጣዎች፣ ምንጣፎች፣ መጋረጃዎች… ትናንት በተጠናቀቀውና በሚሊኒየም አዳራሽ በተካሄደው
“ኦሪጅን አፍሪካ - 2015 ኤግዚቢሽን” ከቀረቡ በርካታ የጥጥ ምርቶች ውስጥ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ካለፈው ረቡዕ እስከ ትናንት በቆየው ኦሪጅን አፍሪካ ኤግዚቢሽን፤ የአፍሪካ ታዋቂ የጥጥ፣ የጨርቃጨርቅ፣ የልብስ፣ የቤት ማስዋቢያ ጨርቆችና የቴክኖሎጂ ኢንዱስትሪዎች ምርቶቻቸውን ለዕይታ ያቀረቡ ሲሆን ከ180 በላይ ዓለም አቀፍ አምራቾችና ኤክስፖርተሮች ምርቶቻቸውን በኤግዚቢሽኑ አቅርበው አስተዋውቀዋል፡፡
ኤግዚቢሽኑን ያዘጋጁት ኦሪጅን አፍሪካ፤ ከኢትዮጵያ ጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩትና ከኢትዮጵያ ጨርቃጨርቅ አልባሳት አምራቾች ማኅበር ጋር በመተባበር ሲሆን አላማውም የአፍሪካን የጥጥ ምርት በማቅረብ ዓለም አቀፍ ኤክስፖርተሮች ጥራቱን አይተው እንዲገዙ፣ የገበያ ትስስር እንዲፈጥሩ፣ አፍሪካውያኑ ዓለም አቀፍ አምራቾች ይዘዋቸው የመጡትን ዘመናዊ መሳሪያዎች በማየት፣ ዓለም በዘርፉየደረሰበትን ደረጃ መገንዘብ ያስችላቸዋል፡፡ በኦሪጅን አፍሪካ 2015 ኤግዚቢሽን የተሳተፉት አገሮች ከአፍሪካ ኢትዮጵያን ጨምሮ 12፣ ከኤስያ 7 እንዲሁም ከአውሮፓ 7 ሲሆኑ ከአፍሪካ ኬንያ፣ ታንዛኒያ፣ ዩጋንዳ፣ ሩዋንዳ፣ ዛምቢያ፣ ማዳጋስካር፣ ሱዳን፣ ሌሴቶ፣ ግብፅና ደቡብ አፍሪካ፣ ከኤስያ፣ ጃፓን፣ ቻይና፣ ሕንድ፣ ሲንጋፖር፣ ስሪላንካ፣ ታይላንድ፣ የተባበሩት ዐረብ ኢመሬትስ፣ እንዲሁም ከአውሮፓ እስራኤል፣ ቱርክ፣ እንግሊዝ፣ ጀርመን፣ ኢጣሊያ፣ ስዊዘርላንድና አሜሪካ ተሳትፈዋል፡፡ ዓለም አቀፍ አምራቾችና ኤክስፖርተሮቹ በኤግዚቢሽኑ የተሳተፉት ምርቶቻቸውንና መሳሪያዎቻቸውን በማሳየት አብራቸው የሚሰራ ሸሪክ ወይም ወኪል ፍለጋ ነው፡፡ አፍሪካውያኑ ደግም የምርቶቻቸውን ጥራት በማሳየት የሚገዛ ወይም በስምምነት ተቀብሎ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚያከፋፍል ደንበኛ ለማግኘት ነው፡፡ ከኤግዚቢሽኑ ጎን
ለጎን ሴሚናሮችም ተካሂዷል፡፡ በመጀመሪያው ዕለት “ኤክስፓንዲንግ ፋውንዴሽን ፎር ኮተን ፕሮዳክሽን ኢን አፍሪካ” በሚል ርዕስ በአክሱም አዳራሽ ፅሑፍ ቀርቦ ውይይት ተካሂዶበታል፡፡ በላሊበላ አዳራሽ ደግሞ “ኦፖርቹኒቲስ ኤንድ ቻሌንጅስ ቱ አጉዋ ኤክስቴንሽን - ዘ ኔክስት ቴን ይርስ በሚል ርዕስ ጽሑፍ ቀርቧል፡፡ ሐሙስ ዕለት ጧት “ኢመርጂንግ ማርኬት ኢንቨስትመንት ኦፖርቹኒቲስ ኢን አፍሪካ፤ ሪኳየርመንትስ ኦፍ ኢሮፕያን ካምፓኒስ ሶርሲንግ ፍሮም አፍሪክ ማኑፋክቸረርስ”፣ … በሚልና በሌሎች በርካታ ርዕሶች ላይ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡

          በኃይሉ ዘላለም የበደሌ ከተማ ነዋሪ ሲሆን በተለያዩ የፈጠራ ሥራዎቹ ይታወቃል፡፡ የ20 ዓመቱ በኃይሉ ከሰራቸው የፈጠራ ውጤቶች አንዱ፣ ከፊት የሚገጠም የባጃጅ የኋላ መመልከቻ መስተዋት (ስኮፒዮ) ሲሆን እንደ ሀይገር ባስ የጎንና የኋላ መመልከቻ መስተዋት (ቀንድ አውጣ) ቅርፅ አለው፡፡ አንዳንድ የከተማዋ ባጃጆች ተሽከርካሪያቸው ላይ ገጥመውት ወደውታል፡፡ “የፋብሪካው ስኮፒዮ ትንሽ ስለሆነ እይታውም ትንሽ ነው፡፡ ይኼኛው ትልቅ ስለሆነ ሰፊ እይታ ይሰጣል፤ ውበትም አለው” ብለዋል፤አሽከርካሪዎቹ፡፡  ወጣቱ በር ለሌላቸው የከተማዋ ባጃጆች በር ሰርቶላቸዋል፡፡ በጉዞ ወቅት ተሳፋሪ ሊወድቅ ስለሚችል መዝጊያ እንዲኖራቸው በትራፊኮች ታዝዟል፡፡ በኃይሉ ደግሞ መዝጊያዎቹን በጥሩ ዲዛይን ሰርቶ እየገጠመላቸው እንደሆነ የባጃጅ አሽከርካሪዎች ተናግረዋል፡፡ የኋላ ፓራውልት የተገጠመላቸው ባጃጆችም አሉ፡፡  በኃይሉ በባትሪ ድንጋይ የሚሰራ የስካቫተር ናሙናም ሰርቶ አሳይቷል፡፡ ሆኖም ድጋፍ የሚያደርግለት በማጣቱ አሁን ትቶታል፡፡ ቀደም ሲልም የተለያዩ የሄሊኮፕተር፣ የመኪና ሞዴሎች፣ … ሰርቷል፡፡ ወደፊት፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የሌለችውንና በፊልም ሲያያት በጣም ደስ የምትለውን ላምበርጊኒ የተባለች የጣሊያን የቅንጦት መኪና(sportear) እና አሮጌውን ሞዴል ሄሊኮፕተር መስራት ምኞቱ ነው፡፡ ፈጠራዎቹን የሚሰራው ከወዳደቁ ቁሶች ነው፡፡   

በአፍሪካ ከ25ሺ በላይ ሆቴሎች በዌብሳይቱ ተካተዋል
ከአገር አገር የሚዘዋወሩ መንገደኞችና ቱሪስቶች በተለያዩ የዓለም አገራት በሚገኙ ሆቴሎች ውስጥ ቀድመው የመኝታ ክፍል ለመያዝ የሚችሉበት ዌብሳይት ሥራ ጀመረ፡፡ JOVAGO.Com በሚል መጠሪያ የሚታወቀው ይኸው ዌብሳይት፤ከአንድ እስከ አምስት ኮከቦች ባላቸው ሆቴሎች ላይ የሚሰራ ሲሆን መንገደኞች በሚያርፉባቸው አገራት ሁሉ አቅማቸው በሚፈቅደው መጠን የመኝታ ክፍል ለመያዝ የሚያስችላቸው መሆኑን የድርጅቱ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ሚስተር አሌክሳንደር በርተንሾው ከትናንት በስቲያ በካፒታል ሆቴል ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ላይ ተናግረዋል፡፡ ዌብሳይቱ በአገር ውስጥ ለሚካሄዱ ጉዞዎችም አገልግሎት
እንደሚሰጥ ተገልጿል፡፡ 

    በጠዋት ቡና የመጠጣት ሱስ ያባቸው ሰዎች፤ የለመዱትን ካጡ የደም ፍሰት ሂደታቸውና በአንጎላቸው ውስጥ የሚካሄደው ኤሌክትሪካል ሲስተም እንደሚዛባ አንድ ጥናት አመለከተ፡፡
ሁልጊዜ ጠዋት ጠዋት ቡና የመጠጣት ሱስ ያለባቸው ሰዎች፤ በቡና ውስጥ የሚገኘው ካፌይን በህብለ-ሰረሰራቸው (Spinal cord) ውስጥ የሚገኙትን የደም ቅዳ ቧንቧዎች ያጠባቸዋል፡፡ ይህ መስመር ደሞ ወደ አንጎላችን የሚተላለፍበት ሲሆን የደም ቅዳ ቧንቧዎቹ በመጥበባቸው ምክንያትም ደም ወደ አንጎላችን የሚደርሰው በዝግታ ይሆናል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ካፊይኑ የአንጎልን የኤሌክትሪክ ሲስተም በማዛበት በተጠንቀቅ እንዲቆም ያደርገዋል፡፡ በዚህ ምክንያትም ሰውነታችን ተመጣጣኝ ያልሆኑ ንጥረነገሮችን ይለቃል፡፡ ይህም ወደ አንጎልዎ የሚፈሰውን ደም ይጨምረዋል፡፡ በዚህ ሳቢያም ድንገተኛ የአንጎል ውስጥ ደም መፍሰስ (ስትሮክ) ሊያጋጥምዎ ይችላል፡፡  

   የደቡብ ኮርያ ብሄራዊ የስለላ አገልግሎት ተቋም፣ ሰሜን ኮርያ አራተኛውን የኒዩክሌር ሙከራ ለማድረግ እየተዘጋጀች እንደሆነ የሚያረጋግጥ መረጃ እንዳገኘ ሊ ቾኤል የተባሉት የአገሪቱ ከፍተኛ የህግ ጉዳዮች ባለስልጣን መናገራቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡የደቡብ ኮርያ ብሄራዊ የስለላ አገልግሎት ተቋም፣ ኒዮንግዮን በተባለው የሰሜን ከርያ ዋነኛ የኒዮክሌር ጣቢያ ላይ ባደረጋቸው የክትትል እንቅስቃሴዎች፣ አገሪቱ የኒዩክሌር ሙከራ ለማድረግ እየተዘጋጀች እንደሆነ አረጋግጧል ብለዋል  ባለስልጣኑ፡፡ሰሜን ኮርያ የደቡብ ኮርያ የኒዩክሌር ሙከራውን ለማድረግ ብትዘጋጅም በቅርቡ ተግባራዊ እንደማታደርገው ባለስልጣኑ ቢናገሩም፣ የስለላ ተቋሙ የህዝብ ጉዳዮች ሃላፊ ግን የተባለው ነገር እውነት ስለመሆኑ ማረጋገጫ ከመስጠት
እንደተቆጠቡ ዘገባው ገልጧል፡፡ሰሜን ኮርያ ሁሉንም የአቶሚክ ነዳጅ ማምረቻ ማዕከላቷን ደረጃ እንዳሳደገችና እንደገና ስራ እንዳስጀመረች ባለፈው ወር ላይ ማስታወቋን ያስታወሰው ዘገባው፣ ይህም አገሪቱ ለአራተኛ ጊዜ የኒዩክሌር ሙከራ ለማድረግ ትችላለች የሚል ጥርጣሬ መፍጠሩን አስረድቷል፡፡ሰሜን ኮርያ የኒዩክሌር ፕሮግራሟን እንድታቋርጥና በምላሹም የተጣሉባት ማዕቀቦች እንዲቀነሱላት ማድረግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ እንምከር በሚል፣ ባለፈው ሳምንት አሜሪካና ደቡብ ኮርያ በጋራ ያቀረቡላትን ሃሳብ ውድቅ እንዳደረገችውም ዘገባው አስታውሷል፡፡ሰሜን ኮርያ እ.ኤ. በ2006፣ በ2009 እና በ2013 ሶስት የኒዩክሌር ሙከራ ማድረጓንና በዚህም ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት የኢኮኖሚና የንግድ ማዕቀቦችን እንዳስጣሉባት ዘገባው
አክሎ ገልጧል፡፡

- በ4 ተከታታይ ምርጫዎች ያልተሸነፈው ገዢው ፓርቲ፣ ዘንድሮ ከባድ ፈተና ገጥሞቷል
- ነገ የሚካሄደው የኮንጎ ብራዛቪል ህዝበ ውሳኔ ከወዲሁ የ4 ሰዎችን ህይወት ቀጥፏል
   ነገ ሊከናወን የታቀደውና በአገሪቱ የምርጫ ታሪክ ከፍተኛ ውጥረት የታየበት እንደሆነ የተነገረለት ምስተኛው የታንዛኒያ ምርጫ፤ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ስጋት የፈጠረ ሲሆን የገዢው ፓርቲና የተቃዋሚ ፓርቲዎች ደጋፊዎች ጎዳና ላይ ወጥተው በተጠንቀቅ እንደሚገኙ አልጀዚራ ዘገበ፡፡የአገሪቱ ፖሊስ በተቀናቃኝ የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ደጋፊዎች መካከል ግጭት እንዳይፈጠር በመካከላቸው ገብቶ በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፣ ምንም እንኳን የአገሪቱ መንግስት ታጣቂዎችን የመለመሉ ፓርቲዎች ግጭትና ብጥብጥ እንዳያስነሱ በተደጋጋሚ ቢያሳስብም፣ ብዙዎች ግን ከዚህ በፊት እንደተከሰተው ሁሉ በነገው ምርጫም ግጥትና ጥቃት ይፈጸማል ብለው እንደሰጉ ገልጧል፡፡ታንዛኒያ የመጀመሪያውን የብዙሃን ፓርቲ ምርጫ እ.ኤ.አ በ1992 እንዳካሄደች ያስታወሰው ዘገባው፣
ከዚያ በኋላ በተካሄዱት አራት ምርጫዎች በአሸናፊነቱ የዘለቀው ቻማ ቻማ ማፒንዱዚ የተባለውና አሁንም ድረስ በስልጣን ላይ ያለው ፓርቲ እንደሆነ ጠቁሟል፡፡ገዢው ፓርቲ በዚህ አመት የታንዛኒያ አራት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥምረት ከሆነው ኡካዋ የተባለ ተቀናቃኙ በተለየ ሁኔታ ጠንካራ ፉክክር እንደገጠመው የጠቆመው ዘገባው፣ የጥምረቱ አባላት ከሆኑት ተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል ሁለቱ በአገሪቱ በትልቅነታቸው ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን የያዙ ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ ፈተናው ከባድ ሊሆንበት እንደሚችል ገልጧል፡
በሌላ በኩል የኮንጎ ብራዛቪል ፕሬዚዳንታዊ የስልጣን ዘመንና የእድሜ ገደብ ህጎች ይሻሻሉ ወይስ
አይሻሻሉ የሚለውን ለመወሰን በነገው ዕለት ህዝበ ውሳኔ እንደሚካሄድ የዘገበው ቢቢሲ፣ ህዝበ ውሳኔው በስልጣን ላይ ያሉትን ፕሬዚዳንት ዴኒስ ሳሶ ንጉኤሶን ህጉ ከሚፈቅድላቸው ውጪ በምርጫ ተሳትፈው በስልጣን ላይ እንዲቆዩ ለማድረግ የታቀደ ህገወጥ ተግባር ነው በሚል ጉዳዩን ተቃውመው በመዲናዋ ብራዛቪል ባለፈው ማክሰኞ ሰልፍ በወጡ ተቃዋሚዎች ላይ ፖሊስ በወሰደው የተኩስ እርምጃ አራት ሰዎች መሞታቸውን ገልጧል፡፡በአገሪቱ የአጭር የጽሁፍ መልዕክትና የኢንተርኔት አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ መቋረጡንና ህዝበ ውሳኔው እስከሚካሄድ ድረስ ህዝባዊ ስብሰባ ማድረግ መከልከሉን የጠቆመው ዘገባው፣ አብዛኛዎቹ የመዲናዋ ሱቆች ተዘግተው እንደሰነበቱና ህዝቡም  ግጭት ይከሰታል በሚል ስጋት በየቤቱ እንደተከከተ አስረድቷል፡፡ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል በበኩሉ፤የፕሬዚዳንታዊ የስልጣን ዘመንና የዕድሜ ገደብ በማሻሻል፣ ግልጽነት ያለው ምርጫ ለማካሄድ የሚያስችል ገለልተኛ የምርጫ ኮሚሽን በሌለበት ሁኔታ ምርጫን ማካሄድ በኮንጎ ብራዛቪል የከፋ አደጋና ቀውስ ሊያስከትል ይችላል ሲል ስጠንቅቋል፡፡የአገሪቱ መንግስት በቅርቡ በፖለቲካ ታጋዮች ላይ ህገወጥ እስር መፈጸሙ ያሳስበኛል ያለው
ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል፣ መንግስት ህገመንግስቱን በህገወጥ መንገድ ለማሻሻል እደረገ ያለው
እንቅስቃሴ ለአገሪቱ ብቻም ሳይሆን ለአካባቢው ሰላም ጭምር አደጋ መሆኑን አበክሮ
አስጠንቅቋል፡፡  

ማስጠንቀቂያ የደረሰው ተጠቃሚ፣
ፈጣን እርምጃ መውሰድ አለበት
ታዋቂው የማህበራዊ ድረ-ገጽ ፌስቡክ፣ በአገራት መንግስታት የሚደገፉ የድረገጽ የስለላ ጥቃቶች ለሚሰነዘሩባቸው ተጠቃሚዎቹ መረጃ በመስጠት፣ ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ የሚያስጠነቅቅበትን አዲስ አሰራር ተግባራዊ ሊያደርግ መሆኑን ኒውስ የተባለ ድረ ገጽ ዘገበ፡፡ፌስቡክ አንድ ተጠቃሚው በመንግስታት የሚደገፍ የስለላ ጥቃት እየተፈጸመበት እንደሚገኝ የሚያመለክቱ ተጨባጭ ማስረጃዎችን ሲያገኝ፣ ‘Please Secure Your Accounts Now’ የሚል ርዕስ ያለውና የፌስቡክና የሌሎች አካውንቶቹ የጥቃት ሰለባ ሳይሆኑ እንዳልቀሩ የሚገልጽ የማስጠንቀቂያ መልዕክት በአፋጣኝ ለተጠቃሚው እንደሚልክ አስታውቋል፡፡ተጠቃሚው መልዕክቱ እንደደረሰው የይለፍ ቃሉን ከመቀየር ባለፈ፣ የሚጠቀምበትን ሞባይል
ወይም የኮምፒውተር ሲስተም በአዲስ መልኩ መስራት ወይም መቀየር ይጠበቅበታል  ሲልም አስጠንቅቋል፡፡አዲሱ የማስጠንቀቂያ አሰራር ከለላ ለሚያስፈልጋቸው ሰዎች ድጋፍ እንደሚያደርግ
የጠቆመው ፌስቡክ፣ በማህበራዊ ድረገጹ ተጠቃሚዎች ላይ የሚቃጡ ጥቃቶችን የመከላከልና የመለየት አቅሙን በማሳደጉ እንደሚገፋበትም ጠቁሟል፡፡ በመንግስታት ከሚደገፉ ከፍተኛ የድረገጽ ጥቃቶች መካከል፣ ባለፈው አመት የሰሜን ኮርያ መንግስት ሶኒ ኢንተርቴንመንት በተባለው ታዋቂ ኩባንያ ላይ የሰነዘረው ጥቃት ቀዳሚውን ስፍራ እንደሚይዝም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

Saturday, 24 October 2015 08:35

.....ዛሬም መገለል አልቀረም

    በዚህ እትም ወደ ጅግጅጋ እና ሐረር ተጉዘን ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ በመሰራት ላይ ያለውን እንቅስቃሴና በአጠቃላይም የወላዶችን ሁኔታ ለንባብ ብለናል፡፡
በጅግጅጋ በአንድ የግል የህክምና ተቋም ውስጥ ወላዶችን ለማየት ገባን፡፡ በአንድ ክፍል አንዲት እርጉዝ ሴት በመተኛ አልጋዎች መካከል ምንጣፍ ተነጥፎላት ተኝታለች፡፡ ዙሪያዋን ቤተሰቦችዋ ከብበዋታል፡፡ እርጉዝዋ ሴት ያለችው በቤትዋ ነው ቢባል ይሻላል፡፡ ሁሉም በየፊናቸው ያወራሉ፡፡ አንድዋ ሴት የእርጉዝዋን ወገብ አንድዋ ሴት ደግሞ እግርዋን ሌላዋ ደግሞ እጅዋን ይዘው ያሻሻሉ፡፡ እርጉዝዋ ሴት ምጡ ሲመጣ እያማጠች...ምጡ ተወት ሲያደርጋት ደግሞ የእነሱን ንግግር እያደመጠች ትስቃለች፡፡ ታስጎበኘን የነበረችውን ነርስ ሁኔታውን ስንጠይቃት የሚከተለውን መልስ ነበር የሰጠችን፡፡
ጥ/    ሲ/ር ፋጡማ እነዚህ ቤተሰቦች በሆስፒታል ውስጥ ምጥ ከያዛት ሴት ጋር ምን     ያደርጋሉ?
መ/    የምታምጠው ሴት የምጡዋ ደረጃ ገና ስለሆነ ቤተሰቦችዋ ከብበዋት ምጡን እንድትረሳ     ያጫውቱአታል፡፡ ሆድዋም እንዳይባባ ዘመዶችዋ አብረዋት እንደሆኑ የምታውቅበት     መንገድ
ነው፡፡ የመውለጃ ሰአትዋ ሲደርስ ግን ከመሀከላቸው ወስደን እንድትወልድ እናደርጋለን፡፡
ጥ/ ጅግጅጋ ከተማ ውስጥ የወላዶች ሁኔታ ምን ይመስላል?
መ/ እንግዲህ እዚህ ክሊኒክ ላይ ብዙ ወላዶች ይመጣሉ ቢያንስ በቀን አንድ ስድስት እና ሰባት          ሰው ይወልዳል በወር ደግሞ እስከ 90 ሰው ይወልዳል፡፡
ጥ/ እናቶች ለእርግዝና ክትትል ወደ እናንተ ሲመጡ ቫይረሱ በደማቸው የመገኘቱ ሁኔታ ምን       ይመስላል?
መ፡ ሁሉም እናቶች መጀመሪያ ሲመጡ የምክር አገልግሎት ተሰጥቷቸው ምርመራ እንዲያደርጉ ይደረጋል፡፡ እና ሁሉም እናቶች ፍቃደኞች ናቸው፡፡ አሁን ዘጠነኛ ወር     ላይ ሁለት እናቶችን አግኝተናል አስረኛ ወር ላይ ደግሞ ሶስት እናቶችን አግኝተናል፡፡     ከዛ በኋላ ምንም አላገኘንም፡፡
ሁሉም ማለትም ቫይረሱ በደማቸው  የሚገኝ እናቶች       መድሀኒቱን ጀምረዋል፡፡ ወደፈለጉበት አካባቢ እሪፈር ተፅፎላቸው     በሄዱበትም  መድሀኒቱን ጀምረዋል፡፡ ብዙ ግዜ ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ የሚገኙ እርጉዝ     ሴቶች     አያጋጥሙም፡፡ ግን አሁን በአምስት ወይም በስድስት ወር ግዜ ስናይ ነው... ሁለት ወይም ሶስት የምናገኘው ፡፡
ጥ/ ልጆቻቸውን በሚመለከትስ እንዴት ነው ክትትል የሚያደርጉት?
መ/ ምንም ችግር የለባቸውም፡፡ እንደውም ከእራሳቸው የበለጠ ልጆቻቸው ላይ ነው ትኩረት     የሚያደርጉት፡፡ መድሀኒቱን ስናስጀምራቸው በደንብ የምክር አገልግሎት ስለምንሰጣቸው እራሳቸው የበለጠ ወደ ልጁ ነው የሚያደሉት ልጁን በደንብ ተከታትለው መድሀኒቱን እንዲወስድ ያደርጋሉ፡
ጥ/ እናቶች ከወሊድ ጋር በተያያዘ ከሚደርሱ ችግሮች ምን ያህል ተላቀዋል?
መ አሁን ያለምንም ችግር እያዋለድናቸው ነው፡፡ በተለይም ስልጠና የወሰድን አዋላጅ     ነርሶች     የሀኪሙ እገዛ እንኳን ሳያስፈልገን ብዙ ስራዎችን እንሰራለን፡፡ እኔ ለምሳሌ...የደም     ግፊታቸው ከፍተኛ የሆኑ ፣ የደም መፍሰስ ያጋጠማቸው እናቶችን ሁሉ     በሚገባ     አዋልዳለሁ፡፡ ምክንያቱም በስልጠናው ላይ እንደዚህ አይነት ችግሮች ሲገጥሙ     ምን መደረግ እንዳለበት ተምሬያለሁ፡፡ ከፍተኛ እና ከአቅም በላይ በሆነ ችግር ከሌላ ቦታ     የሚመጡ እናቶች ካልሆኑ በስተቀር በወሊድ ምክንያት እኛ ጋር የምትሞት እናት የለችም፡፡
በሐረር ጠቅላላ ሆስፒታል አንዲት እርጉዝ ሴት አንድ የአራት አመት ልጅ በእጅዋ ይዛ ከወዲያ ወዲህ ይንቀሳቀሳሉ፡፡ መልኩዋ ብስል ቀይ ነው፡፡ ቁመናዋ እረዘም ያለ እና መልከ ቀና ነች፡፡
መ/    እኔ ወደእዚህ ሆስፒታል የመጣሁት ፀረ ኤችአይቪ (ኤአርቲ) ልወስድ ነው፡፡ የኤች     አይቪ ቫይረስ በደሜ ውስጥ ስላለ ዛሬም ብቻ ሳይሆን በፕሮግራም እየመጣሁ መድሀኒትም እወስዳለሁ ከሐኪም ጋርም እመካከራለሁ፡፡
ጥ/ ባለቤትሽስ?
መ/ ባለቤቴ እዚህ የለም ድሬድዋ ነው ግን እሱ ከቫይረሱ ነፃ ነው
ጥ/ ቫይረሱ በደምሽ ውስጥ መኖሩን ያወቅሽው መቼ ነው?
መ/ ከባለቤቴ ጋር ተገናኝተን ትዳር ከመመስረታችን በፊት መመርመር አለብን ተባብለን     ስንመረመር ነው ያወኩት፡፡
ጥ/ የመጀመሪያውን  ልጅ ስታረግዢ እና ስትወልጂ ምንድነው ያደረግሽው?
መ/ ያን ግዜ ትንሽ ችላ ብዬ ነበር ማለት መድሀኒት ጀምሬ ነበር ግን በጥንቃቄ ጉድለት     ምክንያት የተወሰነ ነገር ተበላሽቶብኛል
ጥ/ ምንድነው የተበላሸው?
መ/ ከወለድኩ ከስድስት ሳምንት በኋላ ለምርመራ መመለስ ነበረብኝ፡፡ ጡት መስጠቱንም     ከስድስት ወር በኋላ ማቆም ነበረብኝ፡፡ ግን በቃ ቤተሰቦች ስለሁኔታው ምንም አያውቁም     ነበር እና የዛን ግዜ ብቻዬን ነበርኩ፡፡ ለቤተሰብ የማሳወቅ ፍላጐቱም አልነበረኝም በቃ     እራሴ ባደረኩት ነገር ክፍተት ተፈጠረ፡፡
ጥ/ የኤችአይቪ ቫይረስ በልጁ ደም ውስጥ አለ?
መ/ አዎን፡፡ አለ፡፡
ጥ/ አሁን የደረስሽ እርጉዝ ነሽ፡፡ እና ካለፈው ስህተትሽ ምን ተምረሻል?
መ/ አሁን በጣም ጥንቃቄ እያደረኩ ያለፈውን ስህተት ላለመድገም እየጣርኩ ነው፡፡ እርግዝናው     ከተጀመረ ጀምሮ ክትትል እያደረኩኝ ነው፡፡ ከከተማ ወጣ ብዬ ወደ ጉርሱም ከተማ ነው     የምኖረው እና እዛ አካባቢ እንደዚህ አይነት ነገሮች በግልፅ አይነገሩም፡፡ እኔም ለዚህ ነው     ለቤተሰቦቼ ያላሳወኩት፡፡
ጥ/ በፊት ምን ነበር የምትሰሪው?
መ/ በአጠቃላይ በፊት ላይ የነበረው ህይወቴ ጥሩ አልነበረም፡፡ በቃ መዝናናት ነው መጣጣት ነ    ው እና ለሕይወቴ የማደርገው ጥንቃቄ አልነበረም ፡፡ ብቻ ጥሩ የህይወት መንገድ ላይ     አልነበርኩም፡፡ አሁን ነው ተረጋግቼ መኖር የጀመርኩት እና እንደዛ ባልሆን ኖሮ ለዚህ     እንደማልዳረግ ስለማስብ አሁን ነው የሚቆጨኝ፡፡ አሁን ግን ያለፈውን ግዜ በመርሳት የወደፊት ህይወቴን እያስተካከልኩ ነው፡፡ በፊት በጣም እታመም ነበር አሁን መድሀኒቱን መውሰድ ከጀመርኩ በኋላ ግን በጣም ጤነኛ ነኝ ብየ አስባለሁ፡፡ ምንም በሽታም አያጠቃኝም ለእራሴ በጣም እጠነቀቃለሁ፡፡
ጥ/ ልጁ መድሀኒቱን ስትሰጪው ምን ይላል?
መ፡ ለምንድነው ሁልግዜ መድሀኒት የምትሰጪኝ ይለኛል፡፡ እናቴም ለምንድነው ይህን መድሀኒት ከአመት አመት የምትሰጪው ትለኛለች፡፡ ሆዱን ስለሚያመው ወይም በተደጋጋሚ ተቅማጥ ስለሚይዘው ነው እላታለሁ እንጂ እውነቱን አልነግራትም፡፡     
ምክንያቱም ከነገርኩት ጥሩ ስሜት ላይሰማት ይችላል ፡፡ የማግለል ነገርም ሊመጣ ይችላል ብዬ ስለማሰብ እንዲሸሹኝ ስላልፈለግሁ ነው፡፡ ዛሬም መገለል አልቀረም፡፡ ልጁም ወደፊት እንዴት አድርጌ መድሀኒት እንደምሰጠው ገና ከአሁኑ እየጨነቀኝ ነው፡፡ እድሜ ሲጨምር ሊያስቸግረን ይችላል ብዬ አስባለሁ፡፡ እንግዲህ ከእግዚአብሔር ጋር ሐኪም     የሚነግረኝን መመሪያ ተቀብዬ እታገላለሁ፡፡
ጥ/ እንዴት ነው የወደፊት ህይወትሽን መምራት የምታስቢው?
መ/ ያው አንደኛውን ብሰሳትም ለሁለተኛው የበለጠ ጥንቃቄ አድርጌ እንደማንኛውም ጤነኛ     ሰው የደስታ ህይወት ለመኖር አስባለሁ፡፡ ከኤችአይቪም የበለጠ ብዙ በሽታዎች እንዳሉ     ሳይ ደህና እንደሆንኩ እና አንድ ቀን እግዚያብሄር ምህረቱን እንደሚሰጠኝ አስባለሁ ፡፡     ቫይረሱ በደማችን የሚገኝ ሰዎች ሳናስበው በተፈጠረ ስህተት እንደዚህ አይነት ችግሮችን     ብንፈጥርም እንደውም አሁን መድሀኒቱን በትክክል በመጠቀም እራሳችንን መጠበቅ     ግዴታ አለብን፡፡  የእግዚያብሄር ምህረት ሲታከልበት ደግሞ ምናልባት መድሀኒት     ሊገኝ ይችላል እና እራሳቸውን  የሚደብቁም ካሉ ለእራሳቸው ጥንቃቄ ማድረግ     አለባቸው፡፡ መድሀኒቱን መውሰድ ምንም የሚያመጣው     ችግር የለም ፡፡...ይሄ ያከሳል     ወይም ያሳብጣል የሚሉት ነገር በሙሉ ውሸት ነው፡፡     መድሀኒቱ በአግባቡ ምግብን     መመገብን ብቻ ነው የሚፈልገው ፡፡
ስለዚህ የተገኝውን ነገር ቤት ያፈራውን እየተመገቡ     እና ከአጓጉል ሱሶች ተላቆ እንደማንኛውም ጤነኛ ሰው መኖር እንደሚቻል የእኔ ሁኔታ     በቂ ምስክር ነው፡፡