Administrator

Administrator

ብዙ ወጣቶች በምርጫ ድምጽ እንዲሰጡት ለማድረግ ነው
የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን አባል የሆኑበት ወግ አጥባቂው ትሮይ ፓርቲ በቅርቡ በሚከናወነው ምርጫ ብዙ ድምጽ ለማግኘት በፌስቡክ ለሚያደርገው ቅስቀሳ በአመት ከ1 ሚሊዮን ፓውንድ በላይ ገንዘብ ወጪ እንደሚያደርግ ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ፓርቲው ባለፈው አመት መስከረም ላይ ብቻ የፌስቡክ ተጠቃሚዎች እንዲወዱት ለማድረግ የከፈለውን 25 ሺህ ፓውንድ ጨምሮ፣ በወሩ በድምሩ 123ሺህ የእንግሊዝ ፓውንድ ለፌስቡክ ኩባንያ ገቢ ማድረጉን የጠቆመው ዘገባው፤ ባለፈው ህዳር ወር ፖለቲካዊ ይዘት ላለው ሌላ ድረገጽ 115 ሺህ ፓውንድ መክፈሉን አስታውቋል፡፡
ለፌስቡክ ይህንን ያህል ወጪ ማውጣቱን እንደ ትልቅ ኢንቨስትመንት እንደሚቆጥረው የገለጸው ትሮይ ፓርቲ፤ ገንዘቡን የሚያወጣው ቁጥራቸው የበዛ ወጣቶች በምርጫ ድምጻቸውን እንዲሰጡት በማሰብ እንደሆነ ቢገልጽም፣ የሚሳካለት አይመስልም ብሏል ዘገባው፡፡
በፌስቡክ ተጠቃሚዎች ዘንድ ተወዳጅነትን በማትረፍ ረገድ፣ ብሪቴን ፈርስት የተባለው ፓርቲ ትሮይን በእጥፍ ያህል እንደሚበልጠው የጠቀሰው ዘገባው፣  ብሪቴን ፈርስት 650 ሺህ፣ ትሮይ ደግሞ 340 ሺህ ያህል የፌስቡክ ወዳጆች እንዳሏቸው ጨምሮ ገልጧል፡፡




*ውሳኔው ጨረቃ የማን ናት
በሚለው ጥያቄ ላይ ተጽዕኖ አለው ተብሏል

የአሜሪካ መንግስት፤ አገራት፣ የግል የህዋ ምርምር ተቋማትና ኩባንያዎች በጨረቃ ላይ የሚያከናውኗቸውን የንግድ ስራዎች በተመለከተ ቁጥጥር ማድረግ ሊጀምር እንደሆነ ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
አሜሪካ ቁጥጥር ማድረግ እንደምትጀምር ማስታወቋ፣ ጨረቃ የማን ናት፣ የተለያዩ ቁሳቁሶችን ወደ ጨረቃ መላክ የሚችሉትስ እነማን ናቸው የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ የተጀመሩ ጥረቶችን አንድ እርምጃ ያራመደ ነው ተብሏል፡፡
የአገሪቱን ኩባንያዎች ጨምሮ በመስኩ የተሰማሩ የመላው አለም ኩባንያዎች መንኮራኩሮችን ወደ ጨረቃ መላክና የተለያዩ ስራዎችን ማከናወን የሚችሉት ከአሜሪካ ፈቃድ ሲያገኙ ብቻ ነው ያለው ዘገባው፤ ፍቃዱን የሚሰጠውም የአገሪቱ የፌዴራል አቪየሽን ባለስልጣን እንደሚሆን ጠቁሟል፡፡
ባለስልጣኑ ያወጣው የቁጥጥር መመሪያ ኩባንያዎችና ተቋማት ወደ ጨረቃ ለሚያደርጉት ጉዞ ፈቃድ ከመስጠት በተጨማሪ፣ በጨረቃ ላይ የሚኖራቸውን ክልል የሚወስን ነው፡፡
አሜሪካ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸደቀውንና ጨረቃ እና ሌሎች የህዋው አለም ቦታዎች በማንኛውም መንግስት ባለቤትነት ስር አይሆኑም የሚለውን ህግ እንደተቀበለች ያስታወሰው ዘገባው፣ ህጉ የግል ኩባንያዎች በጨረቃ ላይ እንዳያስቀምጡ ባይከለክልም፣ አሜሪካ ግን ይሄን አካሄድ ለመቆጣጠር መነሳቷን አስረድቷል፡፡

በ189 ዜጎች ላይም የሞት ቅጣት ጥላለች

   የቀድሞውን የግብጽ ፕሬዚዳንት ሆስኒ ሙባረክ በአመጽ ከስልጣን ለማውረድ ከአራት አመታት በፊት በተቀሰቀሰው አመጽ ተሳትፈዋል የተባሉ 230 የአገሪቱ አብዮተኞች ባለፈው ረዕቡ በካይሮ የእድሜ ልክ እስራት እንደተፈረደባቸው  ቢቢሲ ዘገበ፡፡
እ.ኤ.አ በ2011 ታህሳስ ወር ላይ በካይሮው ታህሪር አደባባይ በተካሄደው አመጽ ከአገሪቱ የጸጥታ ሃይሎች ጋር ተጋጭተዋል፣ የተለያዩ የመንግስት ህንጻዎችንና ተቋማትን በእሳት አቃጥለዋል የተባሉት እነዚሁ ተከሳሾች፣ ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው የቅጣት ውሳኔው እንደተላለፈባቸው ዘገባው ጠቁሟል፡፡ ተከሳሾቹ ከእስራቱ በተጨማሪ በድምሩ 2ነጥብ 2 ሚሊዮን ዶላር በቅጣት መልክ እንዲከፍሉ በፍርድ ቤቱ ተውስኖባቸዋል፡፡
ቅጣቱ ከተላለፈባቸው ግለሰቦች መካከል በችሎቱ ተገኝቶ የፍርድ ውሳኔውን ያደመጠው ብቸኛ ተከሳሽ፣ አመጹን በማቀጣጠልና በመምራት ጉልህ ሚና እንደተጫወተ የሚነገርለት የ26 ዓመቱ አህመድ ዱማ፤ ዳኛው ክሱን በሚያነቡበት ወቅት በማጨብጨብና ጮክ ብሎ በመናገር፣ ተቃውሞውን ለማሰማት ሞክሯል ተብሏል፡፡
የተከሳሾቹ ጠበቆች በበኩላቸው፤ ፍርድ ቤቱ ያስተላለፈውን ውሳኔ የተቃወሙ ሲሆን ዳኛው በተከሳሾቹና በጠበቆቻቸው ላይ ተጽዕኖ ሲፈጥሩ ነበር፣ የፍርድ ሂደቱ በአግባቡ አልተከናወነም፣ ውሳኔውም በአገሪቱ ታሪክ አስደንጋጭና የማይጠበቅ ነው ብለዋል፡፡
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፍርድ ቤቱን ውሳኔ የተቃወመ ሲሆን፣ የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይም በአገሪቱ የሚታየው የጅምላ እስራትና ቅጣት ከዲሞክራሲያዊ መርሆዎች ጋር የሚጋጭ ነው ብለዋል፡፡ የአውሮፓ ህብረት በበኩ፤ ግብጽ አለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ግዴታዎችን ስትጥስ ቆይታለች፤ የግብጽ ባለስልጣናት ይህንን ግዴታ ማክበርና ፍትሃዊ የፍርድ ውሳኔ እንዲሰጥ ማድረግ ይገባቸዋል ብሏል፡፡
ውሳኔውን ያስተላለፉት ዳኛ ባለፈው ሰኞም የእስላማዊ ቡድን አባላት ናቸው ተብለው በተጠረጠሩ 183 ግለሰቦች ላይ ባለፈው ሰኞ የሞት ፍርድ መበየናቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ አለማቀፍ የሰብዓዊ መብት  ተሟጋች ተቋማት ፍርዱን መቃወማቸውን እንደገለጹ አመልክቷል፡፡

ወላጆቻቸውን በኤችአይቪ ኤድስ ባጡ ህፃናት የተዘጋጁ የጥበብ ውጤቶች የሚታዩበት “ተስፋ ኪነጥበብና ሙዚቃ ጋር” የተሰኘ የኪነ ጥበብ ኤግዚቢሽን ነገ በ ‹አለ› ዲዛይንና የስነ ጥበብ ት/ቤት ግቢ ውስጥ ይከፈታል፡፡
የእስራኤል ኤምባሲ ከእስራኤሉ ሃዳስ ዩኒቨርሲቲ ኤንግልሃርድ፣ ከነፃ የጥበብ መንደር የአርቲስቶች ቡድንና ከአርቲስት ፎር ቻሪቲ ጋር በመተባበር ያሰለጠናቸው ወላጆቻቸውን በኤች አይቪ ኤድስ ያጡ ህፃናት ከመቶዎች በላይ ልዩ ልዩ የጥበብ ስራዎቻቸውን በኤግዚሽኑ ላይ እንደሚያቀርቡ ተገልጿል፡፡
“ተስፋ ከጥበብና ሙዚቃ ጋር የሚል ስያሜ በተሰጠው በዚህ ዝግጅት ላይ ህፃናቱ በተለያየ አይነት አቀራረብና አሳሳል የሳሏቸውን ስዕሎች እንደሚያቀርቡና ኤግዚቢሽኑም ለአንድ ሳምንት ለህዝብ ክፍት እንደሚሆን ኤምባሲው የላከልን መረጃ ያመለክታል፡፡  

  • አቶ ልደቱ ከ15 ዓመት በፊት የትጥቅ ትግል አስበው ነበር
  • ኢህአዴግ እያዳከመን ነው ማለት፣ የራስን ድክመት መናገር ነው
  • ህብረት መፍጠር የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን አልጠቀመም    

የፖለቲካ ተሳትፎ ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ በተለይ ከ97 ምርጫ በኋላ በተፈጠሩ አሉባልታዎች ዙሪያ የሚያጠነጥን “ቴአትረ ቦለቲካ፤ አሉባልታና የአገራችን የፖለቲካ ገመና” በሚል ርዕስ አዲስ መጽሐፍ ያወጡት የቀድሞው የኢዴፓ ፕሬዚዳንት አቶ ልደቱ አያሌው፤ በመፅሐፋቸው ጭብጥና በአጠቃላይ በአገሪቱ ፖለቲካ ዙሪያ ከጋዜጠኛ ኤልሳቤት ዕቁባይ ጋር አውግተዋል፡፡

ከፖለቲካው ብዙ ርቀዋል -- አሁን ምን እየሰሩ ነው?
በፖለቲካው ያለኝ ሚና ቢቀንስም አልራቅሁም። አሁን የስራ አስፈፃሚ አባል ስላልሆንኩ የእለት ተእለት ስራ ውስጥ የለሁም፡፡ በዚህ ምክንያት ከመገናኛ ብዙኃን ጋር አልገናኝም፡፡ የኢዴፓ የላዕላይ ምክር ቤት አባል ነኝ፡፡ በፓርቲው ውስጥ ባለኝ የኃላፊነት መጠን መስራት ያለብኝን እየሰራሁ ነው፡፡ በሚዲያ ስለማልቀርብ ከፖለቲካው መራቅ ብቻ ሳይሆን የተውኩ ሁሉ የሚመስላቸው አሉ፤ እውነታው ግን ያ አይደለም፡፡ በእርግጥ ሙሉ ጊዜዬን ለፖለቲካው ስለማላውል ሌሎች ስራዎችን እሰራለሁ፡፡
“ቴአትረ ቦለቲካ” የተሰኘው አዲሱ መፅሃፍህ በዋናነት በአሉባልታ ጉዳይ ላይ የሚያጠነጥን ነው--
እዚህ መፅሀፍ ላይ ማስቀመጥ የፈለግሁት በአብዛኛው ሂደት ውስጥ የነበረውን ነገር ነው፤ አልፎ አልፎ የራሴን ጉዳይ ባስቀምጥም፡፡ ብዙ ጊዜ “ፖለቲካል ኮሬክትነስ” የምንለው ነገር አለ፡፡ ጉዳዩ እሱ አይደለም፤ ያለፍኩበትን ሂደት በነበረበት ሁኔታ አስቀምጬ፣ ሰዎች ሌላ ጊዜ እንደ እኔ ፖለቲካ ውስጥ ሲገቡ ሊያጋጥማቸው የሚችለውን ፈተና አስቀድመው እንዲያውቁት ነው፡፡ ሳያውቁት ገብተው በኋላ ላይ ችግር ከሚገጥማቸው… ምናልባትም ወደ ተስፋ መቁረጥ ከሚገቡ፣ ራሳቸውን አዘጋጅተው መቋቋም እንዲችሉ ለማድረግ ትንሽ አስተዋፅኦ ሊያበረክት ይችላል ብዬ ነው የፃፍኩት። መፅሀፉ ላይ እንደገለጽኩት፤ መጀመሪያ ላይ አሉባልታ ብዙም አያስጨንቀኝም ነበር፤ “የሆነው ሆኗል፤ ያመንኩበትን አድርጌያለሁ፤ ሌላው ሰው የፈለገውን ቢል የኔ ችግር አይደለም፤ ነገሩ እየታወቀ ሲመጣ ሰዎች ሁኔታውንም እኔንም ይረዱኛል” የሚል አስተሳሰብ ስለነበረኝ፣ በጣም ጠንካራ በሆነ ሁኔታ ነው ተቋቁሜው የሄድኩት። ነገር ግን አንድ ቦታ ላይ ከዚያ አስተሳሰብ የተለየ፣ ምናልባትም ሰው መሆኔን በደንብ የሚነግረኝ ስሜት ተፈጠረ፡፡
ይህ በህይወቴ ላይ ትልቅ ትምህርት ሰጥቶኛል። ሁላችንም ሰዎች እስከሆንን ድረስ የሚወጣ የሚወርድ፣ የሚፈራረቅ ስሜት አለን፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሳታውቂው በውስጥሽ የተከማቸ ነገር እንደዚያ አይነት ሁኔታ ሲያገኝ ሊወጣ የሚችልበት እድል ሰፊ ነው፡፡ ይህንን ማስቀመጡ ተገቢ ነው በሚል እንጂ ያለፈ ነገር ነው፡፡  በዚህ ስሜት ውስጥ ማለፍ ምን ማለት ነው የሚለውን ለመረዳት እድል የሰጠኝ አጋጣሚ ነው፡፡ በፖለቲካ ትግሉ ያለኝን ተሳትፎ እንዳቆም ወይም እንዳለዝብ አሊያም ወደ ተስፋ መቁረጥ እንድሄድ ያደረገ ነገር አይደለም፡፡ በትግሉ እቀጥላለሁ፡፡ በእርግጥ የእድሜም ጉዳይ አለ፤ ለአዲሱ ትውልድ ቦታ መልቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ግን ይህን ምክንያት አድርጎ ከትግል መራቅ ተገቢ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ፖለቲካ ፈቅጄ፣ ወድጄ፣ አምኜ የገባሁበት ስለሆነ፣ ያሳለፍኩት ሂደት በጣም ከባድ ቢሆንም ወደፊትም የምርቀው ነገር አይደለም፡፡
በኢትዮጵያ ፖለቲካ አሉባልታን በመኮትኮት ተሰሚነት እንዲያገኝ ያደረጉት ራሳቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎችና የመገናኛ ብዙኃን ናቸው የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎስ በዚህ ይስማማሉ?
ለእኔ አንዱ ለሌላው ያቀበለው ባህል አይመስለኝም፡፡ ችግሩ ሁሉም ላይ የነበረና ያለ በመሆኑ ተመጋጋቢ ነው፡፡ ሁላችንም የዚህ ህብረተሰብ ውጤቶች ነን፡፡ በእኔ እምነት አሉባልታ የፖለቲካ ድርጅቶቹ ወይም የፕሬሱ ብቻ አይደለም፤ በአጠቃላይ እንደ ህብረተሰብ ያለብን ችግር ነው፡፡ አንድ ግለሰብ ወይም ቡድን  የአሉባልታ ሰለባ ቢሆን ወይም አንድ ግለሰብ ወይም ቡድን የአሉባልታ አራማጅ ቢሆን የጉዳቱ መጠን ብዙ ላይሆን ይችላል፡፡ ግን ህብረተሰብን ለማስተማር፣ የህብረተሰብን አስተሳሰብ ለመቅረፅ የተቋቋመ መገናኛ ብዙኃን የአሉባልታ ሰለባ ሲሆን ጉዳቱ ከፍተኛ ነው፡፡ ለዚህ ነው የፕሬሱን ጉዳይ ልዩ ትኩረት በመስጠት በመጽሃፌ የጠቃቀስኩት። በጋዜጣ የተፃፈ፣ በራዲዮ ወይም በቴሌቪዥን የተነገረ ነገር ሁሉ እውነት መስሎ የሚታየው የህብረተሰብ ክፍል አለ፡፡ በአፍሽ ስትነግሪው ውሸት የሚመስለው ነገር፣ በመገናኛ ብዙኃን ሲገለጽ፣ እውነት የሚመስለው ቀላል የማይባል የህብረተሰብ ክፍል አለ፡፡ ችግሩ ፕሬሱ ውስጥ አለ፣ ፓርቲዎቹ ውስጥ አለ፣ ህብረተሰቡ ውስጥ አለ፡፡ አሉባልታውን የማቀባበሉ ሚና፣ ከአንዱ ወደ አንዱ ይሄዳል፡፡ ነገር ግን የመገናኛ ብዙኃን ከዚህ ካልፀዱ፣ አንድ አገር ትልቅ አደጋ ውስጥ ነው ማለት ነው፡፡
 በአገሪቱ ያለውን ፕሬስ እንዴት ያዩታል?
እንግዲህ ሁሉ ነገር እኛ አገር ላይ ገና ነው፡፡ ያለን የፖለቲካ ባህል በጣም ኋላቀር ነው፡፡ በዚህ ኋላቀር ባህል ውስጥ ሆነን ሚዲያው ለብቻው ተለይቶ፣ ከችግር ነፃ ሆኖ ሊያድግ አይችልም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለ ሚዲያ ከችግር የፀዳ ሆኖ እንዲወጣ አልጠብቅም፡፡ ቁጥሩ አነሰም በዛም በሚጠበቀው ደረጃ ላይ አይደለም፡፡ ይህን ስል ሁሉም ፕሬሶች ተመሳሳይ ድክመትና ችግር ነበረባቸው ማለት አይደለም፡፡ በአንፃራዊነት የተሻለ የሚሰሩ ነበሩ፤አሁንም አሉ፡፡  
የኢትዮጵያ ፖለቲካ ወደ ተሻለ ደረጃ እንዳይሸጋገር፣ የፖለቲካ ባህላችን እንዳያድግ በማድረግ ረገድ መገናኛ ብዙኃን፣ በተለይ ነፃው ፕሬስ የራሱ አሉታዊ ተፅዕኖ ነበረው፡፡ አንዳንድ ጊዜ የፕሬሱ ሚና መረጃ ማቀበልና መቀበል ብቻ አልነበረም፤አጀንዳ ቀርፆ ለፖለቲካ ሀይሎች የማቀበልም ሚና ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡
አሁን የፕሬስ ውጤቶችን  ያነባሉ?
አልፎ አልፎ አነባለሁ፡፡ ግን አንዳንድ ጊዜ ጓደኞቼ ወይም በፖለቲካ ፓርቲ ዙሪያ ያሉ ሰዎች እንዲህ አይነት ፅሁፍ ወጥቷል አንብብ ቢሉኝ እመርጣለሁ፡፡ እንደ በፊቱ ሰፊ ጊዜ ወስጄ አላነብም፡፡ መፅሀፌ ላይ እንደገለፅኩት፣ እኔን ጨምሮ አብዛኞቻችን፣የፖለቲካ አስተሳሰባችን የተቀረፀው ኢህአዴግ እንደገባ በነበሩት የግል ፕሬሶች ነው፡፡ ያኔ ሁሉንም ትክክል ነው ብሎ የመውሰድ አዝማሚያ ነበረኝ፤  ትክክል እንዳልሆነ የተማርኩት በሂደት ነው፡፡
 በፖለቲካ እንቅስቃሴው ውስጥ “ይህ እንዴት ሊሆን ቻለ?” ያስባልዎት የተለየ ክስተት ምንድነው?
አሉባልታ በዚህ መጠን ችግርና ተፅዕኖ ይፈጥራል ብዬ አስቤ አላውቅም፡፡ የተወሩብኝ ነገሮች እውነት እንዳልሆኑ እየታወቀና እየታየ እንኳን አልቆመም  ነበር፡፡ የተወራው ነገር ውሸት ለመሆኑ አንደኛ ምስክር ቅንጅት ውስጥ የነበሩ ሰዎች ናቸው። አንዳቸውም ግን ምንም አላሉም፡፡ ህብረተሰቡም ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል አለማለቱ ይገርመኝና ያስደነግጠኝ ነበር። አሉባልታ አገር እንደሚያፈርስ ሩዋንዳ ላይ አይተናል፡፡ አሉባልታ አሁንም  በአገር ደረጃ የሚያሳስበኝ ነገር ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ወደ ፖለቲካ ሲገቡ የሚያስቡት ችግር የመታሰር፣ ከስራ የመባረር ወይ የሞት ጉዳይ ነው፤አሉባልታን እንደ ችግር ብዙም አይቆጥሩትም፡፡ እኔ 22 አመት በትግሉ አሳልፌያለሁ፤ እንደ አሉባልታ በትግሉ ውስጥ ከባድ ነገር የለም፡፡ ትግሉንም በከፍተኛ ሁኔታ የጎዳው አሉባልታ ነው፡፡    
ኢዴፓ የፓርቲዎች ህብረት፣ ውህደት---- የመሳሰሉ ስብስቦችን ለምንድን ነው ላለመቀላቀል የወሰነው?
በማንኛውም ጉዳይ በተናጠል ከመሄድ መተባባር ይሻላል የሚል አስተሳሰብ አለ፡፡ ችግሩ ምንድን ነው-- ይሄ አስተሳሰብ በተለይ ወደ ፖለቲካ ስንመጣ፣ሊሰራ እንደማይችል፣ ከጥቅሙ ጉዳቱ ሊያመዝን እንደሚችል ጥያቄ ማንሳት አይፈለግም። በዚህ ጉዳይ ላይ ጥያቄ ወይም ትችት ማቅረብም ከፍተኛ የፖለቲካ ስህተት ተደርጎ ነው የሚታየው። መተባበር ጥሩ ሀሳብ ነው፣ ግን በተጨባጭ ጉዳዩን እንለካው ከተባለ በተቃዋሚው ውስጥ የህብረት ጥያቄ፣ ትግሉን የጠቀመ ሳይሆን በጣም የጎዳ ነው ብዬ አስባለሁ፤ ባይኖር ይሻል ነበር፡፡ የህብረት ጥያቄ ባይኖር ኖሮ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ እስከ አሁን ሁለት ወይ ሶስት ጠንካራ ፓርቲዎች ተፈጥረው እናይ ነበር። የህብረት ጥያቄ ትግሉን ለማጠናከር ከፈየደው በላይ በህብረት ስም አንዳንድ ግለሰቦች የራሳቸውን የፖለቲካ ተሰሚነት ወይም ተቀባይነት ለማግኘት የሚጠቀሙበት አጀንዳ ሆኖ ነው የኖረው፡፡ ህብረቱ ወይ የሚፈለግበትን አላሳካ ወይ በተናጠል የሚታገሉ ፓርቲዎች ራሳቸውን አጠናክረው እንዲያወጡ እድል አልሰጠም፡፡ እንዲያውም አንድ ጠንካራ እንቅስቃሴ ለማድረግ የሚችል ፓርቲ ሲፈጠር፣ ጠንካራ እንቅስቃሴ ማድረግ ያልቻሉት ነባር ፓርቲዎች፣ የዚያን ፓርቲ እንቅስቃሴ ማፈን የሚችሉበት ስልት ነው የታየው፡፡ ጉዳዩ መዘጋት የሌለበት ቢሆንም በደንብ መጤን ያለበት ነው፡፡ የእንተባበር ጥያቄ የድክመት መሸፈኛ ነው፡፡ ጠንካራ ህብረት ለመፍጠር መጀመሪያ ጠንካራ ፓርቲዎች መኖር አለባቸው፡፡ የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው በሚል አንድ ላይ መቆም የሚለው አስተሳሰብም የተሳሳተ ነው፡፡ ለመተባበር የሚፈልጉ ቢያንስ መሰረታዊ ነገሮች ላይ መስማማት አለባቸው፡፡ ውህደት መፍጠር በራሱ ግብ አይደለም፡፡
ተቃዋሚዎች እርስበርሳቸው፣ እንዲሁም ከገዢው ፓርቲ ጋር ያላቸውን ውዝግብ እንዴት ያዩታል?
በኔ እምነት ትግሉን በጣም የሚያዳክመው በራሱ በተቃዋሚው ጎራ ያለው ችግር ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ  ስልጣኑን መልቀቅ አይፈልግም፣ ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥሩ አመለካከት የለውም፤ስለዚህ የተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዲዳከሙ የቻለውን ሁሉ ያደርጋል፡፡ እንደዚህ አይነት ባህርይ ያለው ገዢ ፓርቲ እንዳለ እናውቃለን፡፡ የኛ ጥንካሬ የሚለካው ይህንን ተፅዕኖ ተቋቁመን በመውጣት ነው፡፡ ልንፈትነው እንዳንችል ያደረገን የውስጥ ችግራችን ነው፡፡ ክፋቱ ግን አብዛኛው ተቃዋሚ ይህንን አያምንም፤ ሁልጊዜ በውስጡ ያለውን ችግር ውጫዊ አድርጎ ነው የሚያቀርበው፡፡ ከምንሰራው ድርጅታዊ ስራ ይልቅ ትኩረት የምንሰጠው ለፕሮፓጋንዳ ነው፡፡ ራሳችንን የመገምገም ባህርይ የለንም፣ ኢ-ዲሞክራሲያዊ አሰራር ነው የምንከተለው፡፡ ገዢው ፓርቲ ለኢትዮጵያ ህዝብ ዲሞክራሲን አላመጣም እንጂ ራሱን በደንብ የሚገመግምበት ዲሞክራሲያዊ አሰራር አለው፡፡ ኢህአዴግ እያዳከመን ነው ሲባል ዞሮ ዞሮ የራስን ድክመት መናገር ነው፡፡ ችግሩ ከውጫዊው ይልቅ ውስጣዊ ነው፡፡ ራሳችንን እንገምግም ስትይ፣ ለኢህአዴግ ጥቅም እየሰራሽ እንደሆነ ይቆጠራል፡፡
በዘንድሮ ምርጫ ይወዳደራሉ?
ፓርቲዬ ይወዳደራል፣እኔ አልወዳደርም፡፡
 ከግንቦቱ አገራዊ ምርጫ ምን ይጠብቃሉ?
ተቃዋሚው ያለበትን ሁኔታና የኢህአዴግን አካሄድ ሳየው፣ ካለፈው ምርጫ የተለየ ውጤት ይመጣል ብዬ አላስብም፡፡ ኢህአዴግ ሙሉ በሙሉ ምርጫውን በራሱ ቁጥጥር ስር አድሮጎ እንደቀጠለ ነው፣ ተቃዋሚው ጎራም ካለፉት ስህተቶቹና ችግሮቹ ተምሮ ራሱን አጠናክሮ የተሻለ ውጤት ለመያዝ የሚያደርገው ነገር ብዙም የለም፡፡ ድፍረት አይሁንብኝና ተቃዋሚው ጎራ ያለችውን አንድ መቀመጫ አስጠብቆ ይቀጥላል ወይ የሚለው ያሳስበኛል፡፡ ሂደቱ መቀጠል ስላለበት ተሳትፎ ማድረጉ አስፈላጊ ቢሆንም በዚህ ምርጫ የኢትዮጵያን ዲሞክራሲ አንድ የተሻለ ደረጃ ላይ የሚያደርስ ውጤት አልጠብቅም፡፡ ይህ የግል ግምቴ ነው፣ ውጤቱን እናያለን፡፡
በመጀመሪያዎቹ የትግል አመታት በጎጃምና ወሎ አዋሳኝ ቦታ ላይ ተጀምሯል የተባለ የትጥቅ ትግል ለማየት ወደ ገጠር ሄደው እንደነበር በመጽሃፉ ገልጸዋል፡፡ የትጥቅ ትግል ለመጀመር አስበው ነበር?
ብዙ ሰዎች ባለፈ ታሪካቸውና አስተሳሰባቸው ያፍሩ ይሆናል፤ እኔ በግልፅ ነው ያስቀመጥኩት። በወቅቱ ያን አይነት የፖለቲካ አስተሳሰብ እንዲኖረኝ የቀረፀኝ ሁኔታ ነበር፡፡
ትግሉን በተቀላቀልኩ የመጀመሪያዎቹ ሶስት ወይም አራት አመታት የነበረኝ አስተሳሰብ በጣም አውዳሚ ነበር፡፡ በስልት ደረጃ በስልጣን ላይ ያለው መንግስት በማንኛውም መንገድ መወገድ አለበት ብዬ ነበር የማምነው፡፡ ይህን መንግስት ከስልጣን ለማውረድ ማንኛውንም መስዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ ነበርኩ፡፡
የወጣቶች ካውንስል አባል በነበርኩበት ወቅት ራስን አቃጥሎ በስርአቱ ላይ ያለውን ብሶት በማሳየት፣ ህዝቡን ማነሳሳት ይቻላል የሚል እምነት ነበረኝ፡፡
ከነፍሰገዳይ ጋር የትጥቅ ትግል አለ በሚል የሄድኩትም በዚያ ምክንያት ነበር፡፡ አሁን ላይ ሳየው ስህተት ቢሆንም ተምሬበት ያለፍኩበት ነው፤ እኔ ይህን ያደረግሁት ከአስራ አምስት አመት በፊት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ሰላሳ እና አርባ አመት አሳልፈው፣እኔ ከዛሬ 15 አመት በፊት የነበረኝ ዓይነት አስተሳሰብ ያላቸው ሰዎች አሉ፡፡ ይህ በጣም የሚያስገርም ነው፡፡  

የተረት - አባት የሆነው ኤዞፕ እንዲህ ይለናል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን ተኩላዎች ተመካከሩና መልዕክተኞች ወደ በጐች ላኩ፡፡
የተኩላዎቹ ልዑካን እበጐች መንደር ደረሱ፡፡ በጐች ተኩሎች መጡብን ብለው ተሸሸጉ፡፡ አድፍጠው ጋጣቸው ውስጥ አድብተው ተቀመጡ፡፡ ተኩሎቹ ግን ረጋ ብለው፣ አደብ ገዝተው፤ “በጐች አትደናገጡ” “እንደምና ዋላችሁ” አሉ፡፡
“ድርድር ነው የመጣነው” አሉ ተኩሎቹ፡፡ በጐቹ ቀስ በቀስ ከተደበቁበት ወጡ፡፡
“እኛ በድርድር እናምናለን፡፡
እህስ? ምን እግር ጥሏችሁ መጣችሁ? ምን የድርድር ሃሳብ ይዛችሁ መጣችሁ?” አሉ በጐች፡፡
“አንድ የቸገረ ነገር ገጥሞን ነበርና ልናዋያችሁ ፈልገን ነው”
“ምንድነው? ከተመካከርን የማይፈታ ምንም ነገር አይኖርም፡፡ ዋናው ተቀራርቦ መነጋገር ነው ንገሩን፡፡”
ተኩሎችም፤
“እግዚአብሔር ይስጥልን፡፡ የቸገረን ነገር ምን መሰላችሁ? ይኸው ከተፈጠርን ጀምሮ ከውሾች ጋር ነጋ - ጠባ እንታገላለን፡፡ የችግራችን መነሻም መድረሻም ውሾች ናቸው፡፡ እርኩስ ውሾች እኛን ባዩ ቁጥር ይጮሃሉ፡፡ ይተነኩሱናል፡፡ ሠፈር ይረበሻል! ለእኛ ለእናንተ ወዳጅነትና ሰላም ዋናዎቹ እንቅፋቶች ውሾች ናቸው፡፡”
በጐችም፤
“ታዲያ ምን እናድርግ? ምን ዘዴ ብንፈጥር እንቅፋቶቹን ማስወገድ እንችላለን?”
ተኩሎችም፤
“እናንተ እሺ ካላችሁማ ዘዴ አይጠፋም ነበር”
“እኮ ዘዴ ካለ ነገሩና?”
“ለጌታችሁ ንገሩ፡፡ ውሾች እንዳልተመቿችሁ፣ ሰላምም እንደነሷችሁ አስረዱ፡፡ ይባረሩልን በሉ!”
“ይሄማ ቀላል ነው፡፡ እንነግረዋለን፡፡”
በዚህ ተስማሙና ተኩሎቹ ሄዱ፡፡
በጐቹ፤ ውሾቹ እንዲባረሩ ለጌታቸው አመለከቱ፡፡ ጌታቸውም ስንት ዘመን ቤት - ደጁን ይጠብቁ የነበሩትን ውሾች ከቤት አስወጥቶ አባረራቸው፡፡
ከዚያን ቀን በኋላ፣ የዋሆቹ በጐች የዘመናት ጠባቂዎቻቸውን አጡ፡፡ ተንኮለኞቹ ተኩሎች እየተዝናኑና በጐቹን አንድ በአንድ እየለቀሙ፤ በሏቸው፡፡
*   *   *
የድርድርን ትርጉም አለማወቅ እርግማን ነው፡፡ ከማን ጋር ነው የምደራደረው? ተደራዳሪዬስ ሊደራደረኝ ያሰበው ምን አስቦ ነው? ጠላቴ እንኳ ቢሆን ድርድሩ ያዋጣኛል ወይ? ከቅርብ ጊዜ ግቤ አንፃር ምን እጠቀማለሁ? ከዘለቄታ ግቤ አንፃርስ ምን እጠቀማለሁ? ትላንትና ምን ዓይነት ግንኙነት ነበረኝ፡፡ ዛሬስ? ዛሬን በዛሬው ክስተት መዳኘት እንዴት እችላለሁ? ብሎ ማሰብ የአባት ነው፡፡
በሁለኛው የዓለም ጦርነት ወቅት የአሜሪካው ጄኔራል ማካርተር በፊሊፒንስ የአሜሪካ ጦር አዛዥ ተደርጐ ሲሾም አንድ ረዳት መኰንን አንድ መጽሐፍ ይሰጠዋል፡፡ መጽሐፉ ከዚህ ቀደም የነበሩት አዛዦች የዋሉባቸውን ጦርነቶች ዝርዝር የያዘ ነው፡፡ ማካርተር “የዚህ መጽሐፍ ስንት ቅጂ አለ?” ብሎ ጠየቀው፡፡ ረዳቱም “ስድስት አሉ” አለው፡፡ ጄኔራሉም “መልካም፡፡ በል ስድስቱንም መጽሐፍት ሰብስበህ አቃጥልልኝ፡፡ እኔ የትላንትና ውሎዎች ባሪያ መሆን አልፈልግም፡፡ ችግር ሲከሰት እዛው ወዲያውኑ መፍትሔ እሰጠዋለሁ፡፡ መጽሐፍቱን በሙሉ አቃጥልና ሁኔታዎች በተከሰቱ ሰዓት እንደ ሁኔታው ግዳጅህን ፈጽሞ” አለው፡፡ ታሪክ የራሱ ዋጋ ቢኖረውም ያንን እንደ ተመክሮ መውሰድ ተገቢም፣ ደንብም ነው፡፡ በትላንት ለመመካት ከሆነ ግን የግብዝ አመድ - አፋሽ መሆን ነው!
“ነበርን ማለት ግን ከንቱ ነው፣ ተው ነው መጀነኑ በቅቶን
ጉራ መንዛት መዘባነን፣ የሚያዛልቅ ዘዴ ባይሆን!” ይለናል ኦቴሎ የሼክስፒሩ፤
በፀጋዬ ገ/መድህን ብዕር ልሣን! ስለታሪክ፣ ስለትላንት ማውራት ሳይሆን ዛሬን ማሸነፍ ነው የፖለቲካ ፋይዳው! ይሄን ያወቁ ላቁ! ይሄን የናቁ ወደቁ! እንደማለት ነው፡፡
ከ1966 ጀምሮ የተከሰቱ የሀገራችን የፖለቲካ ፓርቲዎች አበሳዎች፤ እከሌ ከእከሌ ሳይባል በትንሹ አሥር መሠረታዊ ጉዳዮች ላይ የተንተራሱ ይመስላሉ፡፡ ከአበሳዎቹ፤ አንደኛው/ በትንሽ በትልቁ መከፋፈል፣ ያለመስዋዕትነት ድል መመኘት፣ ውሎ አድሮ ጧት የማሉበትን ማታ መካድ፡፡ “ዕምነት ሲታመም፣ ሺ ወረቀት መፈራረም” ነው፡፡ 2ኛው/ ለባላንጣቸው ሠርጐ - ገብነት መጋለጥ ነው፡፡ 3ኛው/ እርስ በርስ አለመከባበር፣ አለመተሳሰብ 4ኛው/ የመስመር ጥራት አለመኖር ርዕዮተ - ዓለማዊ ብስለት ማጣት  5ኛው/ በትንሽ ድል መወጣጠርና በትንሽ ሽንፈት መፍረክረክ 6ኛው/ ተጋጣሚን መናቅና ወሬን/አሉባልታን እንደ አቋም ወሱድ 7ኛ/ የጊዜን ፋይዳ በትክክል መረዳት፣ ባልፈውስ? አለማለትና የኃይል ሚዛን የማን ነው አለማለት፣ ከተፈፀመም አለመመዘን፣ ይሄ ዓላማ ባይሳካ ምን ሁለተኛ ዘዴ ቀይሻለሁ? ብሎ አለመዘጋጀት፡፡
8ኛው/ ባለፈው ያረግነው የት አደረሰን? ታሪኩ ተተንትኖ ተገምግሞ ሳያልቅ በነዚያው ተዋንያን ተውኔቱ መቀጠሉ 9ኛው/ እምቢ አላረጅም ማለት ነው፡፡ አዲሱ ያሸንፈኛል አለማለት The new is invincible የሚለውን መርሳት “ካፈርኩ አይመልሰኝ” ማለት፡፡ 10ኛው/ እኔ ባልሆንስ መፍትሔው? ሌላ ቢኖርስ ከኔ የተሻለ አለ ብሎ ፈጽሞ አለማሰብ…
ከነዚህ ሁሉ ይሰውረን፡፡ እነዚህን ሁሉ ከልብ ከመረመርን ፓርቲዎቹ ሁሉ የቆሙት በአንድ ወይም በጥቂት ቡድን ሐብለ ሠረሠር (Spinal cord) ዙሪያ ነው፡፡ ይሄ እንግዲህ የሚሆነው፤
“ከተኳሾቹም - አሉ በልዩ
ማህል - አገዳ የሚለያዩ”
በምንልበት አገር ነው፡፡ ከፖለቲካ ንቃተ - ባህሉ (ትምክህቱ ጥበቱ፣ ዕምነቱ፣ የፖለቲካ ጥንቆላው፣ ሟርቱ ወዘተ) ባለበት አገር ልማድን አለመመርመር ጦሱ ብዙ ነው፡፡ አጠቃላይ የፖለቲካ ተመክሮአችን ገና አልተፈተሸም፡፡ “ዳሩ ሲነካ መሀከሉ ዳር ይሆናል” ይላል ያበሻ አባባል፡፡ ዞሮ ዞሮ ግን ግንዱ ሲመታ ቅርንጫፉና ቅጠሉ መርገፉ አይቀሬ ነው፡፡ ቻይናዎቹ “ዛፉ ሲወድቅ ዝንጀሮዎቹ ይበተናሉ” የሚሉን መሠረታዊ ነገር የሚሆነው ለዚህ ነው! “ቁልቋል የወደቀው ቅርንጫፍ ስላበዛ ነው” የሚለውም የትግሪኛ ተረት አዙረን ስናየው እንደቻይናዎቹ ነው!!

         ውህደት ለመፈፀም ተደጋጋሚ ድርድሮችን ሲያካሂዱና ስምምነት ሲፈፀሙ የቆዩት አንድነት ፓርቲ እና መኢአድ፣ የውህደት ጅምራቸው ካለመሳካቱም በተጨማሪ በየፊናቸው ለሁለት ለሁለት ተከፍለው ሲወዛገቡ ነው የከረሙት፡፡ በመጨረሻም የምርጫ ቦርድ፣ ከመኢአድ ፓርቲ በአቶ አበባው መሃሪ ለሚመራ ቡድን፣ ከአንድነት ፓርቲ ደግሞ በአቶ ትዕግስቱ አወሉ ለሚመራው ቡድን እውቅና ሰጥቻለሁ ብሏል፡፡ እውቅና ያልተሰጠው በአቶ በላይ የሚመራው የአንድነት ቡድን ብዙም ሳይቆይ፣ ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ተቀላቅሏል፡፡

እገዳው ለ15 አመታት ተግባራዊ ሆኖ ቆይቷል
    የአሜሪካ ፌዴራል አቪየሽን ባለስልጣን የአገሪቱ አውሮፕላኖች በተወሰኑ የኢትዮጵያ የድንበር ካባቢዎች የአየር ክልል ውስጥ እንዳይበሩ የጣለችውንና ለ15 አመታት ተግባራዊ ሆኖ የቆየውን እገዳ ማንሳቱን አስታወቀ፡፡ባለስልጣኑ የበረራ እገዳውን የጣለው የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት በተቀሰቀሰበት ወቅት እንደነበር
አስታውሶ፣ እገዳው በተጣለባቸው አካባቢዎች የደህንነትና የጸጥታ ሁኔታ እየተሻሻለ መምጣቱንና የአደጋ ስጋት የሌለበት መሆኑን በጥናት በማረጋገጡ እገዳውን ማንሳቱን ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረገው መረጃ አስታውቋል፡፡በወቅቱ በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የተከሰተውን የድንበር ግጭት በድርድር ለመፍታት የተጀመረው ጥረት መስተጓጎሉን ተከትሎ፣ በአካባቢው የነበረው አጠቃላይ ሁኔታ ለአደጋ የሚያጋልጥ ነው በሚል የበረራ እገዳው እ.ኤ.አ በ2000 ግንቦት ወር መጣሉን የጠቀሰው የባለስልጣኑ መረጃ፣ እገዳው መነሳቱ በሚመለከታቸው የመንግስት አካላት መጽደቁን ተከትሎ፣ የአሜሪካ አውሮፕላኖች በየትኛውም የኢትዮጵያ የአየር ክልል ውስጥ መንቀሳቀስ እንደሚችሉ አስታውቋል፡፡

  • ሰሞኑን 35 ስደተኞች የያዘ ጀልባ የመን ሳይደርስ ሰጥሟል
  • በዓመት 200 ገደማ ኢትዮጵያውያን በበረሃ እና በባህር ጉዞ ላይ ሞተዋል
  • “በህጋዊ ምዝገባ የስራ ጉዞ መታገዱ ህገወጥ ስደትን አባብሷል”

       በህጋዊ ምዝገባ ወደ አረብ አገራት የሚደረግ ጉዞ ከታገደ ወዲህ፣ በየመን በኩል እየተሰደዱ ለአደጋ የሚጋለጡ ኢትዮጵያዊያን መበራከታቸውንና ባለፉት ስድስት ወራት 47ሺ ያህል ስደተኞች የመን እንደገቡ RMMS ሰሞኑን ገለፁ፡፡ የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን እና ሌሎች አለማቀፍ ድርጅቶች በጋራ ያቋቋሙት ይሄው ተቋም እንደሚለው፣ ዘንድሮ የስደተኞቹ ቁጥር ከአምናው በእጥፍ ይበልጣል፡፡ ባለፉት አስራ ሁለት ወራት ውስጥ 250 ስደተኞች የመን ለመግባት ሲሞክሩ፣ በባህርና በበረሃ ጉዞ ላይ መሞታቸውን ተቋሙ ጠቅሶ ከስደተኞቹ መካከል ሰማኒያ በመቶ ያህሉ ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውን ገልጿል፡፡ ሰሞኑን በባህር ጉዞ ላይ በተፈጠረ አደጋ አንድ ጀልባ መስመጡን የዘገበው ኤኤፍፒ፤ ጀልባዋ 35 ስደተኞችን አሳፍራ ነበር ብሏል፡፡ ከጉዞ አደጋ በተጨማሪ ስደተኞቹ የመን ከገቡ በኋላም ግማሽ ያህሉ በወሮበላ ቡድኖች እንደሚታገዱ የገለፀው RMMS፤ ከእገታ ለመለቀቅ ከቤተሰብ ገንዘብ እንዲያስልኩ ይገደዳሉ ብሏል፡፡ ለስደት የሚገፋፉ ዋና ዋና ምክንያቶችን ለማወቅ በሺ በሚቆጠሩ ስደተኞችና በትውልድ አካባቢዎቻቸው ላይ ጥናት ያካሄደው ይሄው ተቋም፤ በኢትዮጵያ ዋናዎቹ መንስኤዎች የኑሮ ችግር እንዲሁም ህይወትን የሚያሻሽል ነገር ፍለጋ ናቸው ብሏል፡፡ የፖለቲካ ችግርም የተወሰነ ጫና እንደሚፈጥር ተቋሙ ጠቅሶ፣ የደላሎች ድርሻ ግን ብዙዎች እንደሚያስቡት አይደለም፤ ከመቶ ስደተኞች መካከል በደላላ ግፊት ለስደት የሚነሳሱት ከሁለት ወይም ከሦስት አይበልጡም ብሏል፡፡
ብዙ ወጣቶች ወደ ስደት የሚያቀኑት አደጋ ሊያጋጥማቸው እንደሚችል ባለማወቃቸው ነው ለማለት እንደሚያስቸግር ተቋሙ ሲያስረዳ፤ በአመት ውስጥ ወደ የመን ከገቡት ኢትዮጵያዊያን መካከል ሩብ ያህሉ ከሳዑዲ አረቢያ ወደ አገራቸው የተባረሩና ካሁን በፊት ስደትን የሞከሩ ናቸው ብሏል፡፡ ከቅርብ ወራት ወዲህ የስደተኞቹ ቁጥር የተባባሰበት ሌላው ምክንያት፣ በህጋዊ ምዝገባ ወደ ሳዑዲ አረቢያና ወደ ኩዌት ሲደረግ የነበረው የስራ ጉዞ በመንግስት መታገዱ ነው ብሏል - የተቋሙ ጥናት፡፡ በሌላ በኩል ሶማሊያ ውስጥ ከድህነት በተጨማሪ የሰላም እጦት ወጣቶችን ለስደት እንደሚገፋፋ ተቋሙ ገልፆ፤ በኤርትራ ደግሞ ከኑሮ ችግር ሌላ ዋነኛው ግፊት የመንግስት ከፍተኛ የፖለቲካ አፈና ነው ብሏል፡፡ በሊቢያና በግብጽ በኩል ወደ አውሮፓ ለመግባት ከሚሞክሩ ስደተኞች መካከል ከሶሪያዊያን በመቀጠል በቀዳሚነት የሚጠቀሱት ኤርትራዊያን መሆናቸውን የጠቀሰው ይሄው ተቋም፤ ባለፉት አራት ወራት 15ሺ ኤርትራዊያን ወደ ኢትዮጵያ እንደተሰደዱ ገልጿል፡፡ ስደት የተባባሰው በድህነትና በአፈና ምክንያት አይደለም በማለት የኤርትራ መንግስት ሲያስተባብል፤ ወጣቶች እንዲሰደዱ በማድረግ አገሪቱን ኦና ለማድረግ አለማቀፍ ሴራ እየተካሄደብኝ ነው ብሏል፡፡

 

ውህደት ለመፈፀም ተደጋጋሚ ድርድሮችን ሲያካሂዱና ስምምነት ሲፈፀሙ የቆዩት አንድነት ፓርቲ እና መኢአድ፣ የውህደት ጅምራቸው ካለመሳካቱም በተጨማሪ በየፊናቸው ለሁለት ለሁለት ተከፍለው ሲወዛገቡ ነው የከረሙት፡፡ በመጨረሻም የምርጫ ቦርድ፣ ከመኢአድ ፓርቲ በአቶ አበባው መሃሪ ለሚመራ ቡድን፣ ከአንድነት ፓርቲ ደግሞ በአቶ ትዕግስቱ አወሉ ለሚመራው ቡድን እውቅና ሰጥቻለሁ ብሏል፡፡ እውቅና ያልተሰጠው በአቶ በላይ የሚመራው የአንድነት ቡድን ብዙም ሳይቆይ፣ ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ተቀላቅሏል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ መሪዎች ቀደም ሲል አንድነት ፓርቲ ውስጥ እንደነበሩና በክፍፍል ምክንያት ወጥተው ፓርቲ እንዳቋቋሙ የሚታወስ ሲሆን የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤ በፓርቲዎች ክፍፍል እና በወቅታዊ የፖለቲካ ውዝግቦች ዙሪያ ለጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ የሰጡትን አስተያየት አቅርበናል፡፡

የምርጫ ሰሞን የፓርቲዎች ክፍፍል
በየምርጫው የፓርቲዎች ግጭትና ክፍፍል የተለመደ ቢሆንም የዘንድሮው ይለያል፡፡ በመንግስት አቋም ተወስዶበት የተሰራ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ በራሱ ስራና ብቃት መመረጥ እንደማይችል አውቋል፡፡ ስለዚህ ህዝቡን አማራጭ ማሳጣት ይፈልጋል፡፡ በተቃዋሚ ፓርቲዎች ውስጥ ያሉ ጥቃቅን ስህተቶችን በማጉላት እንዲሁም ሬዲዮ ፋናን፣ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥንንና ምርጫ ቦርድን  በመጠቀም፣  “የተቃውሞው ጎራ እርባና ቢስ ነው፤ ብትወደኝም ባትወደኝም ከእኔ ጋር ትኖራለህ” በሚል ህዝቡ ላይ ጫና ለማሳደር የመጫን ስራ ሆን ብሎ እየሰራ ይገኛል፡፡ ለዚህም  ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በአንድነት ላይ የወሰደውን ውሳኔና የሰጠውን መግለጫ ማየት ይቻል፡፡ “የእነ ትዕግስቱ ቡድን ለእኛ ስለሚታዘዝና በእኛ ሃሳብ ስለሚስማማ እንጂ የራሱ ድክመት አለበት” በማለት አንድነትን ለእነሱ አፅድቆላቸዋል፡፡ ሌላው በእኛ በሰማያዊ ፓርቲ ላይ ቦርዱ
የጀመረው ዘመቻ ነው፡፡ ይቅርታ እንድንጠይቅ ደብዳቤ ፅፎብን ነበር፡፡ እንደ ጥፋት ያቀረባቸው
ነገሮች ግን እዚህ ግባ የማይባሉና ጥፋት ያልሆኑ ነገሮች ናቸው፡፡ ለምሳሌ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ትብብር ለምን ሰራችሁ፣ ያልተመቸንን ስብሰባ ትተን መውጣት መብራታችን ሆኖ ሳለ እንዴት ረግጣችሁ ትወጣላችሁ በሚል ነው የመጨረሻ የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ  የፃፈልን፡፡ ሬዲዮ ፋናንና ኢትዮጵያ ቴሌቪዥንን ብንመለከት፣ እንደሌሎቹ ፓርቲዎች እኛ ላይ ፕሮፓጋንዳ ለመስራት ጠሩኝ፡፡ አክብሬ ሄድኩኝ፤ እዚያው ሬዲዮ ፋና ስቱዲዮ ውስጥ ለሁለት ሰዓት ከተቀረፅኩኝ በኋላ መጨረሻ ላይ ፊልሙ ተበላሽቷል አይተላለፍም አሉኝ፡፡ እኛ የቀረፅነው ስላለ እንስጣችሁ አልናቸው፤ አልፈለጉም፡፡ በተጨማሪም ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ተመሳሳይ ጥያቄ ይዞ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት አቶ ዮናታንን ለአንድ ሰዓት ተኩል ያህል አነጋገራቸው፤ ግን በቴሌቪዥን አልተሰራጨም፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ለእነሱ ፕሮፓጋንዳ የሚመች መልስ ስላልሰጠን ነው፡፡ ይህን ሁሉ ስመለከተው መንግስት ሆን ብሎ ፓርቲዎችን ጥላሸት ለመቀባት ለህዝብ ለማሳየት እየተደረገ ያለ ጥረት መሆኑን እገነዘባለሁ፡፡“አንድነት” ለሁለት ስለመሰንጠቁእኔ በበኩሌ አንድነት ለሁለት ተሰነጠቀ ለማለት እቸገራለሁ፡፡ ምክንያቱም ቅር ተሰኘን የሚሉ ጥቂት ሰዎች ሄደው ለምርጫ ቦርድ ቅሬታ አቀረቡ፡፡ ከስራ አስፈፃሚው እስከ ታች ያለው የፓርቲው መዋቅር ግን በእነ አቶ በላይ ፍቃዱ የሚመራ ነው፡፡ የፓርቲው የብሔራዊ ም/ቤት አፈጉባኤ፣
ምክትል አፈጉባኤ፣ የአዲስ አበባ ምክር ቤት ሰብሳቢ፣ የአዲስ አበባ ወጣቶች ኃላፊ…  ከእኛ ጋር ቀላቀሉት ናቸው፡፡ ሌላው አንድነት የት አለ? ከእኛ ጋር ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የፓርቲው ትልቁን የኃላፊነት ቦታ የያዙት ስለሆኑ እኔ አንድነት ተሰነጠቀ አልልም፤ ከኛ ጋር ተዋሃደ እንጂ አልተሰነጠቀም፡፡ በአሁኑ ሰዓት እዚህ እየመጡ እየተመዘገቡ ነው በክልልም ለምርጫው እጩ እስከማቅረብ እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ፡፡ እስካሁን ከእኛ ጋር የተቀላቀሉትን ብዛት በቁጥር ለመግለፅ እቸገራለሁ፡፡ በአጠቃላይ በአቶ በላይ ፈቃዱ ሲመሩ የነበሩት እውነተኛዎቹ የአንድነት አባላት ከነመዋቅራቸው ወደ እኛ መጥተዋል፡፡ “አንድነት ሰማያዊ ሴራ ፈረሰ” ስለመባሉበብዕር ስም ተፅፎ የወጣው፤ ዘገባ ሃሰት ነው፡፡ ምክንያቱም በእስር ላይ ያሉትን እነ ሃብታሙ አያሌውን ሁልጊዜ እናገኛቸዋለን፡፡ እንደውም ወደፊት አብረን ስለምንሰራበት ሁኔታ በየጊዜው እንወያያለን፡፡ ከሃብታሙም ሆነ ከየሺዋስ ጋር ጓደኛሞች ነን፡፡ የአንድነት ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ወደ ሰማያዊ ፓርቲ በመግባታቸው ኢህአዴግ በደረሰበት ድንጋጤ ሆን ብሎ የሚያስወራው ነው፡፡ እዚያ ዘገባ ላይ ከተፃፈው አንድ ምሳሌ ልንገርሽ፡፡ በበላይ ፍቃዱ የሚመራው ቡድን በዶ/ር ያዕቆብ ሸምጋይነት ከሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ጋር በተናጠል ሲደራደር ቆይቷል ተብሎ ተፅፏል፡፡ ይሄ አይን ያወጣ ውሸት ነው፡፡ እኔና በላይ ፍቃዱ ከጓደኝነታችን የተነሳ ለመገናኘት ሽማግሌ
አያስፈልገንም፤ ሁልጊዜም ቢሆን እየተገናኘን በአገራችን ወቅታዊ በጎና መጥፎ ጉዳዮች ላይ ሌት
ተቀን የምንነጋገር የምንከራከር ነን፡፡ እኔና ዶ/ር ያዕቆብ አንድ ላይ ሆነን ሻይ ጠጥተን እንደማናውቅ ላረጋግጥልሽ እወዳለሁ፡፡ ይሄ ሁሉ የሚመራብን ወሬ  የኢህአዴግን ድንጋጤ የሚያሳይ ነው፡፡
እንደ ክፍፍሉ ውህደቱ መፍጠኑአሁን ጥቃቅንና አነስተኛ የፕሮግራም ልዩነቶችን እያነሳን ጊዜ የምናባክንበት ወቅት ላይ አይደለንም፡፡ በመሰረቱ አንድነትና ሰማያዊ በአብዛኛው ፕሮግራሞቻቸው ላይ ልዩነት የላቸውም፡፡ ስለዚህ ዋና ዋናዎቹ ላይ ከተስማማን በጥቂትና ጥቃቅን የፕሮግራም ልዩነቶች ላይ በሂደት በውይይትና በክርክር የምንስማማባቸው ይሆናሉ፡፡ አብረን ለመስራት የሚከለክሉን ስላልሆኑ ይሄ
አያስጨንቀንም፤ በአሁኑ ሰዓት እንደ ቁምነገር የምናነሳው አይደለም፡፡ የአንድነት አባላት በሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ የሚኖራቸው የአመራር ቦታቀደም ብዬ እንደተናገርኩት ወደኛ የመጡት የአንድነት ሰዎች በትልልቅ የአመራር ቦታ ላይ የነበሩ ናቸው፡፡ በፓርቲው ስልጣንና ሹመት ውስጥ ብቻ ሳይሆን አሁን አዲስ አበባ ላይ በምናቀርባቸው እጩዎች ላይ ጥሩ ጥሩ ተፎካካሪዎችን ማቅረብ ይችላሉ፡፡ የመመረጥ መብታቸው እስከ ከፍተኛ አመራር ድረስ ክፍት ስለሆነ መብታቸው ነው፡፡ ይህንን ጉዳይ በተደጋጋሚ ተነጋግረንበታል፡፡ አሁን ከተቀላቀሉን ውስጥ ብዙዎቹ ጥሩ ጥሩ የአመራር ብቃት ያላቸው ስለሆኑ ለፓርቲያችን ያስፈልጉናል፡፡ በፓርቲው ወሳኝ ወሳኝ ቦታ ላይ ገብተው የመስራት መብት አላቸው፡፡ በቀሪው አንድ ሳምንት ውስጥ በእጩነት እንዲገቡም እናደርጋለን፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሁሌም “ፓርቲዎች ትከፋፈላላችሁ፤ አትግባቡም” እንባለለን፡፡ ይሄ ቁጭት በውስጣችን እያለና ገዢው ፓርቲ ሆን ብሎ “ተጣልተዋል፤ ተከፋፍለዋል” የሚለውን ስራዬ ብሎ በተቆጣጠራቸው ሚዲያዎች እያናፈሰ ባለበት አስቸጋሪ ሰዓት ፓርቲያችንን የሚያግዝና የሚያጎለብተን ኃይል ሲመጣ እንዴት አንደሰትም፡፡ ከዛ በተረፈ በሁለቱም ፓርቲዎች በኩል ያለን ሰዎች የምንተዋወቅና የምንግባባ ስለነበርን እንደ አዲስ አንተያይም፤ አብረን ለመስራት ሁሉንም ነገር ያቀልልናል፡፡ለምርጫ ስላቀረቧቸው እጩዎች ብዛት እስካሁን ፓርቲያችን በአገር አቀፍ ደረጃ ወደ 400 የሚጠጉ እጩዎችን አስመዝግበናል፡፡ አሁን ደግሞ እጩ የማስመዝገቡ ሂደት ለአንድ ሳምንት ተራዝሟል፡፡ በዚህ በቀረን አንድ ሳምንት አዲስ ከተቀላቀሉን ሰዎች ውስጥ የምናስመዘግባቸው ይኖራሉ፡፡ በአጠቃላይ የእጩዎቻችን ቁጥር ወደ 500 ከፍ ሳይል እንደማይቀር እገምታለሁ፡፡ መጀመሪያ ላይ ልናስመዘግብ ያቀድነው የእጩዎች ብዛት 300 ነበር፡፡ በምርጫ ዘመቻ የፓርቲዎች ስህተትና ትኩረትምርጫው እየቀረበ እንደመሆኑ መጠን በውስብስብና አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነው የምንገኘው፡፡ በትናንሽ ጉዳዮችና በእርስ በርስ ፉክክር ላይ ከማተኮር ይልቅ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ትልቁን የአገራቸውን ምስል እንዲያዩ እመክራለሁ፡፡ ልዩነትም ቅራኔም ቢኖር መቻቻልና ቅራኔን በጥበብ
በመያዝ ለውጤት ወደሚያበቃ ትግል ተጠናክረን መግባት አለብን፡፡ ዛሬ የምንሰራው ስህተት ልብ ሰብርና ህዝቡን ተስፋ የሚያሳጣ እንዳይሆን በመጠንቀቅ በጥበብ መጓዝና ለምንታገልለት ህዝብ የተስፋ ብርሃን መፈንጠቅ ይኖርብናል፡፡ ፓርቲዎች የገዢውን ፓርቲ ከፋፋይ ሴራ በማወቅ፣ ከፍተኛ
ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ጥሪ አቀርባለሁ፡፡