Administrator

Administrator

አቶ ሙሼ ሰሙ
(የቀድሞ የኢዴፓ ሊቀመንበር)

    አዲስ አድማስን በሶስት መሠረታዊ አቅጣጫዎች የማየው፡፡ አንደኛ ፈር ቀዳጅ ጋዜጣ ነው፡፡ በተለያዩ አምዶቹ የተለያዩ አጀንዳዎችን፡- ማህበራዊ፣ ስፖርት፣ ጤና፣ ኪነጥበብ፣ ፖለቲካና የመሳሰሉት ጉዳዮችን አካትቶ የሚወጣ ጋዜጣ ነው፡፡ በዚህ ደረጃ የተሟላ ገጽታ ይዘው መውጣት ከጀመሩ ጋዜጦች ቀዳሚው ነው፡፡ ብዙዎቹ ሲጀምሩ ዋነኛ ጉዳያቸው ፖለቲካ ብቻ ነበር፡፡ ቋሚ አምደኛ የሚባለው ነገርም ብዙ ጊዜ ከአዲስ አድማስ ጋር የመጣ ባህል ነው። ቋሚ አምደኛን ለረጅም ጊዜ ማሳተፍ በሌሎች ሀገሮች የተለመደ ነው፡፡ በ97 ዓ.ም ከተፈጠረው መንገራገጭ ውጪ አብዛኛውን ጊዜ ጋዜጣው በተቻለው መጠን ሚዛናዊና ምክንያታዊ ለመሆን ጥረት ሲያደርግ አያለሁ።
ሁለተኛው ፈር ቀዳጅ ነው የሚያስብለኝ በሌሎች ጋዜጦች ላይ የሚደርሰው ፈተና ሁሉ በዚህ ጋዜጣ ላይ አይደርስም የሚል እምነት የለኝም፡፡
የተለያዩ ተግዳሮቶች አሉበት፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያ ውስጥ ተግዳሮት የሚያጋጥመው ከመንግስት ብቻ አይደለም፡፡ በመንግስት ውስጥ የተቀመጡ ባለስልጣኖችም የተግዳሮት ምንጭ ናቸው። ያንን ሁሉ ተቋቁሞ ላለፉት 15 አመታት ሣይቋረጥና ሣያጓድል መውጣቱ በጣም ትልቅ ፈር ቀዳጅነት ነው ብዬ አምናለሁ።
ይሄ ደግሞ የምክንያታዊነት ውጤት ነው። ሽያጩ ጨመረ ቀነሰ ሳይባል የፖለቲካው ትኩሳትና መቀዛቀዝን ሳይከተል ወጥነትን ይዞ መሄዱ አንዱ ፈርቀዳጅነት ነው፡፡
ሌላው በህዝቡ ዘንድ ባለው ተቀባይነት በጣም ወጥቶ ወይም ወርዶ ያየሁበት ሁኔታም አልነበረም፡፡ ይሄ እንግዲህ ለአንድ ጋዜጣ በጣም ወሳኝ ነገር ነው፡፡ በቋሚነት አንባቢ ያለው፣ በትክክል ስነልቦናውን ተረድቶ መልዕክቱን ማስተላለፍ የቻለ ጋዜጣ ነው ብዬም አስባለሁ፡፡ ከነዚህ አኳያ አዲስ አድማስ ፈር ቀዳጅ ነው፡፡ የራሱን ደንበኞች መፍጠር የቻለም ጋዜጣ ነው፡፡
ወደፊት፣ ይሄን ተቀባይነቱን ተጠቅሞና አድማሱን አስፍቶ፣ ሌላውን ማህበረሰብ መድረስ የሚያስችል ውጥን ያስፈልገዋል ብዬ አስባለሁ፡፡ በፖለቲካ ጉዳይ ላይ ሠፋፊ ሃተታ የመፃፍ ጉዳይ ብዙም አይታይም፤ ለዚህ ትኩረት መስጠት አለበት፡፡ ሠፋ ያሉና ጥልቀት ያላቸው ፅሁፎች የሚያስተናግድበት ሁኔታ ሊታሰብ ይገባል፡፡ እንደ ተቋም፤ በእነዚህ 15 አመታት ግዙፍና ሠፊ መሆን መቻል ነበረበት፡፡ ያንን መፍጠር ያስፈልጋል። በቂ አቅም ሲፈጥር ተፅዕኖ መቋቋምና ስራውን በነፃነት መስራት ይችላል፡፡

    “ከወፍራም ቡና ጋር አብሮ የሚሄደው ነገር ምንድን ነው?” ብዬ ስጠይቃችሁ፤ ምን ቡና አለ?! ብላችሁ ወደ ወትሮው ምሬታችሁ እንድትገቡ አልፈልግም፡፡ ከወፍራም ቡና ጋር የሚሄደው ነገር ንባብ ነው፡፡ ጋዜጣ ወይንም መፅሔት አሊያም መፅሐፍ ከያዛችሁ ማለፊያ ነው፡፡ … ታዲያ ቡና እያጠጣ ጋዜጣ በራሱ ሂሳብ ገዝቶ አንብብልኝ የሚል ካፌ ከተገኘ ይኼ ሰው ባለውለተኛነቱ … ለቡና ጠጪ እና ለንባብ ፈላጊ ብቻ ሳይሆን … ከንባቡ ጀርባ ላሉት የጋዜጣና መፅሔት ፀሐፍት (የፃፉት እንዲነበብላቸው ለሚፈልጉ) እንዲሁም ለቡና ገበሬዎችና ቡና ነጋዴዎች (ያመረቱት እንዲጠጣላቸው ለሚመኙትም) ጭምር ነው፡፡ ቡናን ፉት እያሉ ንባብን ማጣጣም የሚችሉበትን ካፌ ገርጂ ያገኙታል፡፡
የመብራት ኃይል ካፌ ባለቤት አቶ ፀጋዬ ወንድሙ ራሳቸውን ያስተዋውቁንና ስለ ካፌያቸው ያወጉናል፡፡  

ፀጋዬ ወንድሙ እባላለሁ፡፡ የተወለድኩት እዚህ አዲስ አበባ ለገሀር አካባቢ ነው፡፡ በስፖርት ውስጥ በሩጫ እሳተፍ ነበር፡፡ ይሄ ደግሞ ወደ ውጭ የመሄድ አጋጣሚ ፈጠረልኝና ወደ ጣሊያን አመራሁ፡፡ ጣሊያን ለሁለት አመት ያህል ከቆየሁ በኋላ ወደ ካናዳ ተሻገርኩ፡፡ እዚያም ለ14 አመታት ኖርኩ፡፡ ካናዳ በነበረኝ ቆይታ በሩጫው ዘርፍ እወዳደር ነበር፡፡ በመጨረሻ ከ8 አመት በፊት ወደ ሀገር ቤት በመመለስ ካፌ ከፍቼ መስራት ጀመርኩ፡፡
ካናዳ ምን እየሰራህ ነበር የምትኖረው?
ያው መጀመሪያ በሩጫው ምክንያት ነው ከሀገር የወጣሁት፡፡ ካናዳ ከሄድኩኝ በኋላም አንድ ድርጅት ወክዬ እሮጥ ነበር፡፡ ነገር ግን የካናዳ የአየር ንብረት ትንሽ ስለከበደኝ በሩጫው መቀጠል አልቻልኩም፡፡ ስለዚህ እንደማንኛውም ሰው የተለያዩ የዕለት ተእለት  ስራዎችን እየሰራሁ ለ14 አመት ቆየሁ፡፡ የካናዳ ዜግነት ስላለኝ በፈለግሁት ጊዜ በመመለስ መኖር እችላለሁ። ነገር ግን ወደ አገሬ ስወጣ ለራሴም ገቢ የሚፈጥር፣ ህብረተሰቡንም የሚያግዝ ሥራ መስራት አለብኝ ብዬ ስለሆነ እየሰራሁ ነው፡፡
ከካናዳ መጥተህ እንዴት የካፌ ስራ ውስጥ ገባህ?
ከልጅነቴ ጀምሮ በተለያዩ ቢዝነሶች የመሰማራት እድሉ ነበረኝ፡፡ ሞተር ብስክሌት እና መኪና አለማምድ ነበር፡፡ መኪና ወደ ካፌ ቢዝነስ ልገባ የቻልኩት ግን  በካናዳ ባሳለፍኳቸው ጊዜያት ከጓደኞቼ ጋር እየተገናኘን የተለያዩ ነገሮችን የምንወያየው በካፌ ውስጥ ነበር። ካፌ ውስጥ ገብተን ጓደኞቻችንን በምንጠብቅበት ወቅት ታዲያ የእለቱን ጋዜጦችና መጽሔቶች ካፌው ያቀርባል ቴሌቪዥንም ይከፍታል፡፡ ወጣቶችም ይሁኑ አዛውንቶች ወደዚህ ካፌ ሲመጡ ከህትመት ውጤቶች ላይ መረጃዎችን እንዲያገኙ እፈልጋለሁ፡፡ ወጣቶች በተለይ አጓጉል ቦታ ጊዜያቸውን ከማሳለፍ እዚህ እያነበቡ፣ ቴሌቪዥን እየተመለከቱ የሚቆዩበት መንገድ ተመቻችቷል፡፡ ሥራ ፈላጊዎች ሳይጉላሉ ከጋዜጦች ላይ ክፍት የሥራ ቦታዎችን ያያሉ፡፡ እዚህ ክፍት የስራ ቦታ አይተን ስራ አገኘን የሚሉ ብዙ ደንበኞች ያጋጥሙኛል፤ ይሄ ያስደስተኛል፡፡
ከካፌ ሌላ ቢዝነስ አለህ?
በትራንስፖርት ዘርፍ ውስጥ እየሰራሁ ነው።  ገልባጭ መኪኖች አሉኝ፡፡ ከሚኒባስ ስራ ነው ወደ ገልባጭ የቀየርኩት፡፡
የየዕለቱን ጋዜጣ በማቅረብህ የካፌ ሥራህ አልተጐዳም? ደንበኞች ጋዜጣ ሲያነቡ ለረዥም ሰዓት መቀመጫ ይይዛሉ ብዬ ነው……
ለገንዘብ ብዬ የሠውን ፍላጐት መጫን ስለሌለብኝ ደንበኞቼ እንዲያነቡ ፈቅጃለሁ፡፡ መፍቀድ ብቻ አይደለም፤ የሚያነቡትንም እያቀረብኩ ነው፡፡ ያለምንም የሰአት ገደብ ማንበብ ይችላሉ፡፡ ይህንን ሳደርግ እኔም የማገኘው ጥቅም አለ፡፡ ሰው ጋዜጣ ለማንበብና ክፍት የስራ ቦታዎችን ለማየት ሲል ከተለያዩ ሰፈሮች ወደ እዚህ ካፌ ይመጣል፡፡ ጋዜጣውን ለማንበብ ሲቀመጥ ደግሞ ማዘዙ አይቀርም፡፡ ስለዚህ አንድ ደንበኛ የመሳቢያ መንገድ ነው ሊባል ይችላል፡፡ ጋዜጦችን ማቅረቤ ለቢዝነሱ የሚሰጠው ጥቅም አለ ማለት ነው…
በብዙ ካፌዎች ግን እንዲህ ያለ ነገር አልተለመደም። እንደውም “ጋዜጣ፣ መፅሐፍ ማንበብ ክልክል ነው” የሚሉ ማሳሰቢያዎች የሚለጥፉ ሁሉ ያጋጥማሉ፡፡
እንግዲህ ሁሉም ሰው የራሱ የሆነ ፍልስፍና፣ የራሱ የሆነ አተያይ ይኖረዋል፡፡ እነዚያ ሰዎች ለምን እንደዚያ እንዳደረጉ አላውቅም፡፡ እኔ ግን ባለኝ እውቀትና የአስተሳሰብ ደረጃ አንድ ሰው መረጃ ማግኘት አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ እየተከናወኑ ያሉ አዳዲስ ነገሮችን ሊያውቅና መረጃው ሊኖረው ይገባል የሚል አስተሳሰብ አለኝ፡፡ ስለዚህ ህብረተሰቡ ከሬዲዮና ከቴሌቪዥን ከሚያገኘው መረጃ ባሻገር ከተለያዩ ጋዜጦችና መጽሔቶች አዳዲስ መረጃዎችን እያገኘ፣ እግረ መንገዱን የማንበብ ባህልን እያዳበረ እንዲሂድ ባለኝ ፍላጐት ነው ይህንን ተግባር እያከናወንኩ ያለሁት፡፡
በካፌው ውስጥ ጋዜጦችና መጽሔቶች እንዲነበቡ በማድረግህ ምክንያት የገጠመህ ቅሬታ ወይ ትችት አለ?
በሁኔታው የሚደሰቱ እንዳሉ ሁሉ የሚከፉ ሊኖሩ የሚችሉበት አጋጣሚ አለ፡፡ እኔ ግን አምኜበት የማደርገው ስለሆነ “እገሌ ስለከፋው ማስነበቤን ላቁም” የምልበት ምክንያት አይኖረኝም፡፡ የሚደሰተውን እያስደሰትኩ መቀጠል ነው የኔ ሃላፊነት፡፡
ሰው አንድ ጋዜጣ ገዝቶ ሊያነብ ይችላል፤ ነገር ግን ሁሉንም የየዕለቱን ጋዜጣ ገዝቶ ሊያነብ አይችልም፡፡ ያንን ለማድረግ የኑሮውም ሁኔታ ላይፈቅድለት ይችላል፤ ስለዚህ እኔ ሁሉንም የየዕለቱን ጋዜጦች በማቅረብ የተለያዩ የመረጃ ምንጮች ለህብረተሰቡ በመፍጠር ከሌላው አለም ያገኘሁትን ተሞክሮ በአቅሜ ለዚህ ህብረተሰብ እያካፈልኩ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ነገር ግን ለምን ጋዜጣ ታስገባለህ ተብዬ የተጠየቅሁበት ጊዜ ሁሉ አለ፡፡ ሰው ቁጭ ብሎ ሲያነብ ችግር ለመፍጠር የተሰባሰበ ወይም ተቃውሞ ሊመስል ይችላል፡፡
በዚህም ምክንያት በተለያዩ አካላት ጋዜጣ እንዳላስነብብ ተነግሮኝ ነበር፡፡ ነገር ግን እኔ ጋዜጦችን ሳመጣ መርጬ እንደማላመጣና ሁሉንም አይነት ጋዜጦች እንደማመጣ፣ ዓላማዬም ህብረተሰቡ መረጃ እንዲያገኝና የማንበብ ባህል እንዲያዳብር መሆኑን፣ ይሄም ከውጭ አገር ያገኘሁት ተሞክሮ እንደሆነ አስረድቻቸዋለሁ፡፡  
ከህብረተሰቡ ምን አይነት ምላሽ ታገኛለህ?
ህብረተሰቡ በጣም ደስተኛ ነው፡፡ አንዳንድ ቦታ ሄጄ ባጋጣሚ ጋዜጣ ተከራይቼ በማነብበት ወቅት የተለያዩ ሰዎች የኪራዩን ሒሳብ የሚከፍሉበት ጊዜ አለ፡፡ እኔ በመልክ እንኳን የማላውቃቸው ሰዎች “አንተ ሁሌ በነፃ እያስነበብከን እኛ የአንድ ቀን የጋዜጣ ኪራይ ብንከፍል ምን አለበት” ይላሉ፡፡ በካፌ ውስጥ ቁጭ ብለው የሚያነቡ አዛውንቶች ሲመርቁኝ ህብረተሰቡ በዚህ ተግባሬ በጣም ደስተኛ እንደሆነ እገነዘባለሁ፡፡ አንዳንዴ እንደውም “እዚህ ስናነብ ባገኘነው ክፍት የስራ ቦታ አመለክተን ስራ አገኘን፤ ደስ ብሎናል ካልጋበዝኳችሁ “የሚሉ ደንበኞች ሁሉ ያጋጥሙናል፡፡ ስለዚህ በምንሰጠው አገልግሎት ህብረተሰቡ ደስተኛ ነው ብለን እናምናለን፡፡
አንዳንዶች የተሻለ ደሞዝ ያለው ሥራ ማግኘታቸውን ሲነግሩንም ደስ ይለናል፡፡ ለካ እንዲህ እያደረግን ነው ብለን እንድናስብ የሞራል ድጋፍ ይሆነናል፡፡
በአንተ ተሞክሮ በህብረተሰቡ ውስጥ የማንበብ ባህል አለ ብለህ ታስባለህ?
እኔ እንዳየሁት ከሆነ አቅሙ እስካለውና ሁኔታዎች ተመቻችተው እስከቀረቡለት ድረስ ህብረተሰቡ የማንበብ ፍላጐት አለው፡፡ ማታ ካፌውን በምንዘጋበት ሰአት መጥቶ 10 ደቂቃ ለንባብ ብሎ የሚያስፈቅድ ደንበኛ ሁሉ አለ፡፡ ይሄ ህብረተሰቡ የማንበብ ፍላጐት እንዳለው ያሳየኛል፡፡ ሌላው የመግዛት አቅሙ ባይኖረው እንኳን ተከራይቶ ሲያነብ ይስተዋላል፡፡ ከሰው ከሚሰማው ነገር ይልቅ አንብቦ ለመረዳት ያለው ፍላጐት ከፍተኛ ነው፡፡ ስለዚህ እንደኔ አስተያየት ህብረተሰቡ የማንበብ ፍላጐት አለው ነው የምለው፡፡ እንደዚያ ካልሆነማ፣ ለምን የተለያዩ ጋዜጦችንና መጽሔቶችን እየገዛሁ አስቀምጣለሁ? ሌላው ቀርቶ ስንዘጋ አንብቦ ያልጨረሰ ደንበኛ ካለ፣ ቤት ወስጄ ላንብብና ጠዋት ልመልስ የሚልበት አጋጣሚ ሁሉ አለ፡፡
ጋዜጣ ለምን ታስነብባለህ የሚል ጫና አሁንም ይደርስብሃል?
እኔ በግልፅ ተናግሬአለሁ፡፡ ምንም ዓይነት የፖለቲካ ዓላማ እንደሌለኝና ለሥራ የቆምኩ መሆኔን፣ ጋዜጣ አታስነብብም ከተባልኩ ካፌውንም እንደምዘጋ ገልጬአለሁ፡፡ እነሱም አንባቢው ጤነኛ እንደሆነና ምንም አይነት ችግር እንዳልተፈጠረ ሲያዩ ትተውኛል፡፡  አሁን ምንም አይነት ጫና የለብኝም፡፡ ይሄም የሆነው ሥራ የጀመርኩ ሰሞን ብቻ ነው፡፡
በልጅነትህ የማንበብ ልማድ ነበረህ?
ከልጅነቴ ጀምሮ የማንበብ ባህሉና ፍላጐቱ ነበረኝ ልልሽ አልችልም፡፡ የማንበብም ሆነ የማስነበብ ባህልን ያዳበርኩት ውጪ በነበርኩበት ጊዜ ነው፡፡ ለምሳሌ ካናዳ ስኖር የማስተውላቸው ነገሮች ነበሩ፡፡ በየካፌው የተለያዩ መጽሔቶች እና ጋዜጦች ተደርድረው ለደንበኞች ይቀርባሉ፡፡ እነሱ እያንዳንዱ እንቅስቃሴያቸው በመረጃ የተደገፈ ነው፡፡ ስለዚህ የንባብ ነገር ካናዳና ጣሊያን በነበረኝ ቆይታ ያዳበርኩት ባህል እንጂ ከልጅነቴ ጀምሮ የነበረ አይደለም፡፡
የየዕለቱ የጋዜጦች ወጪህ ስንት ነው?
በየቀኑ የሚወጡትን ሁሉንም አይነት ጋዜጦች አመጣለሁ፡፡ በቀን ለጋዜጣና ለመጽሔት እስከ 50 ብር አወጣለሁ፡፡ በሳምንት እስከ 350 ብር ገደማ ይሆናል። ለአንድ አስተናጋጅ በወር የምከፍለውን ደሞዝ ማለት ነው፡፡    

     በቅርቡ “ሉአላዊነትና ዲሞክራሲ በኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ ባወጡት መፅሐፍ የመጀመርያዎቹ አራት ምዕራፎች ላይ ራስዎንም ጭምር እየተቹ ፅፈዋል፡፡ የ1993 ክፍፍልና ከዚያ በኋላ ያለውን በሚተርከው ክፍል ላይ ግን ብዙ የተድበሰበሱ ጉዳዮች እንዳሉ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ….
እኔ ይሄን መጽሐፍ በሁለት አላማዎች ነው የፃፍኩት። አንዱ አላማ በኢትዮጵያ የሉአላዊነት ጉዳይ ከየት ተነስቶ የት እንደደረሰ ማስገንዘብ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ የኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ሂደት በ40 አመት ውስጥ ከየት ወዴት እንደደረሰ ለማሳየት ነው፡፡ ስለዚህ ሰዎች ይሄን ግንዛቤ እንዲይዙ ከራሴ ልምድና ከነበርኩበት ድርጅት አጠቃላይ እንቅስቃሴ በመነሳት የተቻለኝን ሁሉ አስቀምጫለሁ የሚል አስተያየት አለኝ፡፡
እኔ መጽሐፉ ከወጣ በኋላ ከደረሱኝ አስተያየቶች ከ90 በመቶ በላይ የሚሆኑት ነገሮችን በግልጽ ማስቀመጤን የሚጠቁ ሲሆን እንዲያውም አንዳንዱ ከሚጠበቀው በላይም ተገልጿል የሚል ነው፡፡ በህወሐቶች ዘንድ ደግሞ አላስፈላጊ የሆኑ ሚስጥሮች አውጥቷል ተብሎ እንደሚታሰብ ተገንዝቤአለሁ፡፡ እኔ ግን ህሊናዬና አቅሜ በሚፈቅደው የተቻለኝን ያህል እውነታውን ገልጨዋለሁ፡
በግልፅ አልተብራራም ከተባሉት መካከል በ1993 ክፍፍል ወቅት እርስዎን ጨምሮ አቶ ስዬ፣ አለም ሠገድ፣ አባይ ፀሐዬ… በአቶ መለስ ቦናፓርቲዝም ዙሪያ ያቀረባችሁት ጽሑፍ በሚገባ አልተጠቀሰም የሚለው ይገኝበታል፡፡ ምን አይነት ጽሑፎች ነበሩ የቀረቡት?
በኔ በኩል ስለ መለስ ቦናፓርቲዝም በመጽሐፉ ውስጥ በዝርዝር አስቀምጫቸዋለሁ፡፡ የመለስ አቋም፤ በኢትዮጵያ አመራር ውስጥ ቦናፓርቲዝም በግልፅ ተከስቷል የሚል ነበር፡፡ የቦናፓርቲዝም ዋናው ጉዳይ ደግሞ ሙስናና ፀረ ዲሞክራሲያዊነት ነው ብሏል፡፡ የኛ ጽሑፎች ከዚህ የተለዩ ናቸው፡፡
የቦናፓርቲዝም ንድፈ ሃሳብ መለስ ከአስቀመጠው የተለየ ትርጉም ነው ያለው፡፡ የቦናፓርቲዝም ዋናው ቁምነገር ሁለት ሃይሎች/መደቦች ለመጠፋፋት ከጅለው፣ ይሄን መጠፋፋት አስታርቆ የሚመጣ መካከለኛ መንግስት ማለት ነው፡፡ በመለስ አገላለጽ ግን ቦናፓርቲዝም ሙስናና ፀረ ዲሞክራሲ ስርአትን ለማንገስ የመጣ ስርአት ነው፡፡ ከዚያ በላይ በእኛ ፅሁፎች በስፋት የተገለፀው መለስ በወቅቱ የነበረውን የኢትዮጵያን ችግር በስፋት አላቀረበም የሚል ሃሳብ ነው፡፡ በወቅቱ ከነበረው ትልቅ ችግር ለመሸሽ የተዘጋጀ ጽሑፍ ነው የሚል አቋም ነው የያዝነው፡፡ ምክንያቱም የወቅቱ ትልቁ የኢትዮጵያ ችግር የሉአላዊነት መደፈር ነው፡፡ በተለይ በኤርትራ መንግስት የተቃጣብን ወረራ በልማታችን ላይ ያስከተለውን ችግር ሣይናገር፣ ሌላ ጉዳይ አንስቶ ከዋናው አጀንዳ አፈግፍጓል ብለን ነው በጽሑፋችን ያስቀመጥነው፡፡ ሉአላዊነት ሲባል የድንበር ጉዳይ ብቻ አይደለም፤ በሀገራችን፣ በህዝባችን፣ በመንግስታችን ላይ የተቃጣ መሆኑም ጭምር ነው። መለስና ጓደኞቹ ለውጭ ጫና ተንበርክከው፣ በወቅቱ ከእውነታው ሸሽተዋል የሚል ነው የጽሑፋችን ጭብጥ፡፡ እሱ ደግሞ ዋናው ጉዳይ የሙስናና የዲሞክራሲያዊነት ነው፤ የሉአላዊነት ጉዳይ ውጫዊ ጉዳይ ነው ብሎ ነው ያቀረበው፡፡ በአጠቃላይ አቶ መለስ ያቀረበው ጽሑፍ ከሉአላዊነት አጀንዳ የመሸሽ ነው፡፡
ከእናንተ ጋር አብረው አቶ መለስን ሲቃወሙ የነበሩት አቶ አባይ ፀሐዬ እንዴት ወደ አቶ መለስ ቡድን ተመለሱ?
ይሄን መመለስ ያለበት አባይ ራሱ ነው፡፡ እኔ እስከማውቀው ግን አቶ አባይ የመለስን አቋም ይቃወም ነበር፡፡ በተለያዩ ጊዜያት በተለይ ወረራውን በተመለከተ አቶ መለስ የወሰደው አቋም የተሣሣተ ነው በሚል ይቃወም ነበር፡፡ የእነ አቶ መለስ ቦናፓርቲዝም አስተሳሰብ ከሃገራችን ተጨባጭ ሁኔታ የወጣና ያፈነገጠ ጉዳይ ነው ብሎ አጥብቆ ተከራክሯል፡፡ እንግዲህ የክፍፍላችን ሁኔታ የተጠናቀቀው በፖለቲካዊ ውይይት አይደለም፡፡ አቶ መለስ የሠራዊቱንና የደህንነቱን ጣልቃ ገብነት ተጠቅሞ ነው ያሸነፈው እንጂ በውይይት አላሸነፈም፡፡ አስቀድሞ ሠዎችን በመግዛት በማስፈራራት ነው ያሸነፈው፡፡ አባይም ምናልባት ይሄን ጫና መቋቋም አቅቶት ይሆናል እንጂ እስከመጨረሻው ያለውን ሃቅ ያውቀዋል፡፡
እስከመጨረሻው የክፍፍሉ ሰአት ድምፅም ሠጥቷል፡፡ ከታገዱት 12 ሰዎች ውስጥም አንዱ እሱ ነበር፡፡ የመለስን አቋም እቀበላለሁ ብሎ መግባቱ የመለስን ጫና መቋቋም አቅቶት ሊሆን ይችላል፡፡ በወቅቱ ውስጥ ገብቶ መታገል ነው የሚያዋጣው ብሎ ነበር፤ ከገባ በኋላ ግን እንዳለው አልታገለም፡፡ የህወሓት ችግር እየባሰበት ሄደ እንጂ የለወጠው ነገር የለም፡፡ ዋናው መልስ መስጠት ያለበት እሱ ቢሆንም የኔ መላምት በአቋሙ መዝለቅ ያቃተው ጫና በዝቶበት ሊሆን ይችላል የሚል ነው፡፡
ግብርናን ኮሜርሻላይዝድ ለማድረግና ሜጋ ፕሮጀክቶችን በሀገሪቱ እንዴት መተግበር እንደሚቻል የሚያመላክት የስትራቴጂ እቅድ ነድፈው ለአቶ አዲሱ ለገሠ ሰጥተው ነበር፡፡ ከዚያ እቅድ ውስጥ ኢህአዴግ እስካሁን ተግባራዊ ያደረገው አለ?
ብዙም አይመስለኝም፡፡ ያኔ አቶ መለስ ሜጋ ፕሮጀክቶችን ይቃወም ነበር፡፡ እኛ ደግሞ ኢንዱስትሪው መምራት አለበት፣ ትላልቅ የመስኖ ስራዎች መተግበር አለባቸው፡፡ እርሻም መሠረቱን በሚለውጥ መንገድ መሄድ አለበት እንል ነበር፡፡ ከተሞችም በተጠና መንገድ ማደግ ነው ያለባቸው፡፡ ግብርና መር እያሉ እዚያው መንከባለል ኢትዮጵያ ውስጥ ለውጥ አያመጣም… የሚል አስተያየት ነበር ያቀረብኩት፡፡
በቅርቡ የ5 አመት እቅድ ብለው በነደፉት ላይ ኢንዱስትሪ መር እናደርጋለን ብለዋል፡፡ ሁኔታው አስገድዷቸው ሊሆን ይችላል፡፡ የሄዱበት መንገድ ለውጥ አለማምጣቱን ተረድተው ይሆናል፡፡ ሆኖም መሠረታዊ መዋቅራዊ ለውጥ እስካሁን ድረስ አልመጣም፡፡ ያኔ እነሱ የሚያዳምጥ ልቦና አልነበራቸውም፡፡ አሁንም የገቡበት ስትራቴጂ በተጠና መንገድ ስለመሆኑ ያሳብበኛል። የሆነ ሆኖ ያኔ የቀረቡት ሃሣቦች አሁንም አንዳንድ አሉ። እኔን ይበልጥ የሚያስገርመኝ ትግራይ ክልል ላይ እኛን ሲቃወሙን የነበረውን አሁን በእጥፍ እየተገበሩት መሆናቸው ነው፡፡ መለስ እኛን ለመምታት ሲል “ብክነት አለበት” ብሎ ያልተቀበላቸው የመስኖ ስራዎች፣ የመንገድ ስራዎች፣ የግድብ ስራ፣ የሪፈራል ሆስፒታል ስራ፣ የሠማዕታት ሃውልት ግንባታ… እነዚህን ሁሉ አሁን ትክክል ናቸው ብለው ተቀብለዋል፡፡ ይሄን ሲያደርጉ ደግሞ ያኔ ትክክል አይደሉም ላሉት ይቅርታ ሳይጠይቁ ነው፡፡ ለነገሩ እነሱ ከሠውም ወስደናል አይሉም፤ ይቅርታም አይጠይቁም፡፡ በኤርትራ ጉዳይ ብዙ ጥፋት ተሠርቶ ይቅርታ ያሉት ነገር የለም፡፡
ያኔ እናንተ “ሻዕቢያን ማንበርከክ…” ብላችሁ ያቀረባችሁት ሃሣብ ሊሳካ ይችል ነበር ይላሉ?
በነገራችን ላይ አቶ መለስ ወደፊት ገፍቶ የሻዕቢያን ሠራዊት ማንበርከክና መደምሰስ አይቻልም የሚል ሃሳብ ነው ያቀረቡት፡፡ ኋላ ላይ የመጡ መረጃዎች ግን ማንበርከክ ይቻል እንደነበርና… ያለቀለት ጉዳይ እንደነበረ ይጠቁማሉ የኤርትራ ባለስልጣናትም እየተናገሩት ነው። ለምሣሌ ሃይልይሮ የተባለውና አሁን በእስር ላይ የሚገኘው፤ ባለስልጣን፤ “በቃ ወያኔ አጥለቅልቆናል፤ በሚገባ አሸንፎናል” ብሎ ነበር፡፡ ሌላ አድሃኖም የሚባል የእነሱ አመራር፣ የሻዕቢያ ሠራዊት ከአሰብ ወደ ምጽዋ ማፈግፈግ ጀምሮ እንደነበር ጠቅሶ ከአስመራም ለማፈግፈግ ተቃርቦ ነበር ብሏል፡፡ ገፍተን ብንሄድ ኖሮ አሁን በአካባቢው የተፈጠረው ትርምስ ባልኖረ ነበር፡፡ ኢትዮጵያን ለ14 አመት ችግር ውስጥ ነው የከተታት የጉዳዩ እልባት አለማግኘት ነው፡፡ ሁሌም በተጠንቀቅ እንድትቆም ነው ያደረጋት፡፡ ከዚያም በላይ ሻዕቢያ የሚደግፋቸው ሃይሎች በኢትዮጵያ ውስጥ ትርምስ ለመፍጠር ሲሞክሩ እያስተዋልን ነው፡፡ ሻዕቢያን ማስወገድ ቢቻል ኖሮ ለኤርትራ ህዝብም ሆነ ለኢትዮጵያ በጐ ነገር በተፈጠረ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ረጅም እፎይታ ያገኝ ነበር፡፡
አሁን እርስዎ የሚከተሉት ርዕዮተ ዓለም ምንድን ነው?
እኔ በአጠቃላይ እውነተኛውን፣ መሠረቱን ሊብራል ያደረገ ዲሞክራሲን መከተል በሚለው ነው የማምነው። ሊበራል ውስጥ ብዙ አይነት ክፍሎች አሉ፡፡ በአሁን ወቅት በኢትዮጵያ ሶሻሊዝም ማርክሲዝምን ተግባራዊ ማድረግ አስቸጋሪ ነው፡፡ ማርክሲዝም ረሃብና ጭቆናን ለማስወገድ ጠቃሚ ነው፡፡ በደርግም በንጉሡ ስርአትም አሁንም ዲሞክራሲ በተግባር ስራ ላይ አልዋለም፡ ባለንበት እየረገጥን ነው፡፡ ዲሞክራሲ ያለ ነፃ የሲቪል ማህበረሰብ፣ ያለ ነፃ ፕሬስ አይታሰብም፡፡ ህብረተሰቡ በነፃነት ሣይንቀሳቀስ በየ5 አመቱ ምርጫ ማካሄድ ዲሞክራሲ አይደለም፡፡ መድብለ ፓርቲ በሌለበት ዲሞክራሲ የለም፡፡ በኢትዮጵያ እነዚህ ነገሮች እንኳ ብንተገብር ለውጥ ይመጣ ነበር፡፡ መጀመሪያ የዲሞክራሲ መሠረትን መገንባት ነበር የሚያስፈልገው፤ ከዚያ በኋላ ማርክሲስቱም፣ ሊበራሉም፣ ሌላውም የፈለገውን ሃሳብ ማራመድ ይችላል፡፡ እኔ አሁንም የፀና እምነቴ እውነተኛውን ዲሞክራሲ መተግበር በሚለው ስለሆነ የምታገለውም ለዚሁ ነው፡፡
ከ1993 የህወኃት ክፍፍል በኋላ ከድርጅቱ የወጣችሁ ፖለቲከኞች አንድ ላይ መሠባሰብ አልቻላችሁም፤ ሁላችሁም በየፊናችሁ ነው የተበታተናችሁት? አንዳንድ ወገኖች ከድርጅቱ የወጣችሁትግለሰብ ላይ ባላችሁ ጥላቻ እንደሆነ ይናገራሉ…
እኛ አቶ መለስን የተቃወምነው በሉአላዊነት ጉዳይ ነው፡፡ ከዚያ ጋር በተያያዘም በአብዮታዊ ዲሞክራሲ የተቃኘው ዲሞክራሲ ትክክል አይደለም የሚል ነበር። መለስም አቸንፌያለሁ ብሎ አንዳንዱን እስር ቤት ወርውሮታል፣ አንዳንዱን የቁም እስረኛ አድርጐታል፤ አንዳንዱን እንደገና ጫና ፈጥሮ እንዲመለስ አድርጐታል። ህወሐት የወጣን ሰዎች የጋራ ፕሮግራም አልነበረንም። በሁለቱ ጉዳዮች የጋራ መግባባት ነበረን እንጂ የጋራ ፕሮግራም አልነበረንም፡፡ መታወቅ ያለበት ግን አቋም ዋጋ ያስከፍላል፡፡ እኛ ህይወት የሚያስከፍል አቋም ነው ወሰድነው፡፡
ከክፍሉ በኋላ አቶ መለስ አለማቀፍ ሰብዕና ያላቸው ሰው ሆነዋል፣ “የምጡቅ አስተሳሰብ ባለቤት” እየተባሉ ተሞካሽተዋል፡፡ በተቃራኒው የእናንተ ቡድን ደግሞ “ራሱን አላደሰም” ተብሎ ይወቀሳል፡፡ አስተሳሰባችሁን አንጥራችሁ ማውጣት አልቻላችሁም ተብላችሁ ትወቀሳላችሁ…
እኔና በአረና ፓርቲ ውስጥ ያለን ግለሰቦች መሰረታዊ ለውጥ አድርገናል ብዬ አምናለሁ፡፡ ፕሮግራማችንን ማየት ይቻላል፡፡ አብዮታዊ ዲሞክራሲ ምናምን የሚል ማጭበርበር የሌለበት ፕሮግራም እንዲነደፍ አድርገናል። በባህር በር ጉዳይም ኢትዮጵያ የባህር በር ይገባታል ብለናል፣ መሬት የመንግስት መሆን የለበትም፣ የህዝብ ነው የሚል አቋም ወስደናል፡፡ በኢትዮጵያ አንድነት ዙሪያም መሰረታዊ አቋም በመውሰድ መገንጠል የሚባል ነገር መኖር የለበትም ብለናል፡፡ ኢህአዴግ ግን ባለበት አቋሙ ነው የፀናው፡፡ መለስ መች የአይዲኦሎጂ ለውጥ አመጣ? የተለየ አይዲኦሎጂ አምጥቶ ቢሆን ኖሮ እንደተባለው እኛ ባለንበት ቆመናል በሚል ተብለን ልንወቀስ እንችላለን፡፡ አንድ ነገር ግን ለውጥ መጥቷል፡፡ እኛ ስንቶቻቸው የነበሩ ነገሮችን አቶ መለስ በተግባር አውሎታል፡፡ የአለማቀፍ ድርጅቶችና ሃብታም ሃገሮችን ተላላኪነትን በስራ ላይ አውሎታል፡፡ መለስ ይኑርም አይኑርም ኢህአዴግ አለማቀፍ ተቀባይነት ያገኘው ወደ ሱማሌ ግባ ሲባል በመግባቱና የተላላኪነት ሚና በመወጣቱ ነው፡፡ እንዲህ ያለውን ሚና የሚወጣላቸውን አካል ደግሞ እነዚህ ሃገሮች ተክለ ሰውነቱን ይገነቡታል፡፡ ዲፕሎማሲ የጥቅም ጉዳይ ስለሆነ እነዚህ ሃገሮች የደገፋቸው ወይም የታዘዘላቸው መሪ ካገኙ ሰብዕናውን ይገነቡታል እንጂ አቶ መለስ ኢህአዴግ ይከተለው ከነበረው ርዕዮተ አለም የመጠቀ አስተሳሰብ ስለተከተለ አይመስለኝም፡፡
በመፅሀፉ ከትግሉ ጀምሮ እስከ ህወሐት ክፍፍል ድረስ ስህተት ያሏቸውን ጉዳዮች በግልፅ አስቀምጠዋል፤ እርስዎ እነዚያን ስህተቶች ተሸክመው እንዴት እስከ ክፍፍሉ ድረስ ዘለቁ? ለምን በወቅቱ እርምጃ አልወሰዱም?
በወቅቱ ድርጅቱ የሚገመግማቸው ስህተቶች ነበሩ። ይኖራሉም፡፡ ግን ሁልጊዜ በሂደት ይታረማሉ የሚል ሃሳብ ነበረኝ፡፡ መሰረታዊ ቢሆን እንኳ ተወያይተን የምናርማቸው ጉዳዮች ነው የሚሆኑት ብለን እናስብ ነበር፡፡ በክፍፍሉ ወቅት ግን እነዚያ ችግሮች መታረም አይችሉም ብለን አቋም ወሰድን፡፡ አንዳንድ ስህተቶች ደግሞ ከምንከተለው አብዮታዊ ዲሞክራሲ ርዕዮተ ዓለም ነበር የሚመነጩት፡፡ ያን ያየሁት ከወጣን በኋላ ነው፡፡ ስንከፋፈል እንኳ ሁለታችንም የነበረን ርዕዮተ ዓለም አብዮታዊ ዲሞክራሲ ነው፡፡ ከወጡት አሁንም አብዮታዊ ዲሞክራሲን የሚከተሉ ይኖሩ ይሆናል፡፡ እኔ ማርክሲዝምን በማምንበት ጊዜ፣ ዲሞክራሲ ለወዳጅ እንጂ ለጠላት መሰጠት የለበትም የሚል አቋም ነበረኝ። ግን ዲሞክራሲ ለሁሉም ዜጋ እኩል መድረስ ያለበት መሆኑን አምኛለሁ፡፡
በትግል ህይወትዎ አሁን ሲያስቡት የሚያስቆጭዎ ወይም የሚፀፅትዎ ነገር አለ?
በመታገሌ ፈፅሞ አልቆጭም፡፡ በተለይ ለ17 ዓመታት ያደረግሁት ትግል ሌሎች አላማዎች ባይሳኩም በኢትዮጵያ ዲሞክራሲን አፍኖ የቆየው፣ ዜጎችን በግፍ ይገድል የነበረ ስርአት በመወገዱ እንደ ትልቅ ገድል አድርጌ እወስደዋለሁ፡፡
ያም ሆኖ አንዳንድ አቋሞቼ ይፀፅቱኛል፡፡ ለምሳሌ በኤርትራ ላይ በትግሉ ወቅት የወሰድነው አቋም ይፀፅተኛል፡፡ የኢትዮጵያን ጥቅም ሳናስከብር ቅኝ ግዛት ነው ብለን ኤርትራ ነፃ እንድትወጣ መወሰናችንና የዚያ ውሳኔ አካል መሆኔ ይፀፅተኛል፡፡ ኤርትራ ነፃ መውጣቷ በእርግጥ የግድ ነበር፤ ነገር ግን ኢትዮጵያ ቅኝ ገዢ ስለሆነች የሚባለው ትልቅ ስህተት ነበር፤ ይሄ እስካሁን ድረስ ይፀፅተኛል፡፡ በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅትም በመካከላችን የነበረውን ልዩነት ከጦርነቱ ቀድመን ማሳወቅ ነበረብን ወይ የሚለውም ያሳስበኛል። ከዚያ ውጪ ግን በአይዲኦሎጂ በተፈጠሩት ስህተቶች የጊዜውን ፋሽን ተከትሎ የሚለዋወጥ በመሆኑ አልፀፀትም፤ እታረማለሁ እንጂ፡፡ ከሁሉም የሚፀፅተኝ ኢትዮጵያን የባህር በር የነሳው ውሳኔ ነው፡፡ በጦርነቱም ወቅት በእንዝላልነት ያን ያህል ዋጋ መከፈል ሳያስፈልገው መከፈሉ ያሳዝነኛል፡፡ ቀደም ብሎ መደራጀት ቢቻል ኖሮ፣ ያሁሉ ሞትና መፈናቀል ባልተከሰተ ነበር፡፡
የሚያስደስትዎ ወሳኔስ?
ብዙ ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ዋናው ግን ለመታገል መወሰኔ ያስደስተኛል፤ ችግሩ ሳይቀጥል በአንፃራዊነት ነፃ ሆኜ መኖሬም ትልቁ የሚያስደስተኝ ነገር ነው፡፡ አሁን አገሪቱ ውስጥ መሰረታዊ ችግሮች አሉ፡- የሙስና ችግር ስር የሰደደ ነው፣ ብልሹ አሰራሮችና የመልካም አስተዳደር ጉድለቶች አሉ፤ የሰብአዊ መብት ጥሰት ተበራክቷል፡፡ የ1997 ምርጫን ተከትሎ ከ190 በላይ ዜጎች ሲገደሉ የዚያ አካል አለመሆኔ ያስደስተኛል፡፡
ከአቶ መለስና ከአቶ ኃይለማርያም አመራር የትኛውን ይመርጣሉ?
በኢትዮጵያ ያለው ችግር የግለሰቦች አይደለም። በክፍፍሉ ከህውኃት የተለየነው ግለሰቦች መለስን አሸንፈን ስልጣን ብንይዝ ኖሮ እኛም አምባገነኖች እንሆን ነበር፡፡ ምናልባት በኤርትራና በሉአላዊነት ጉዳይ እንዲሁም በአንዳንድ ሃገራዊ ፖሊሲዎች ላይ የተሻለ ነገር የማምጣት እድል ሊኖረን ይችል ነበር፡፡ በተረፈ በአብዮታዊ ዲሞክራሲ ስለምንቀጥል አምባገነን ከመሆን የሚያግደን የለም፡፡ ይሄን ርዕዮተ ዓለም ተከትሎ የሄደ ሰው አምባገነን ነው የሚሆነው፡፡ መሰረቱ እዚያ ርዕዮተ ዓለም ውስጥ ነው ያለው፡፡ ርዕዮተ ዓለሙ ስልጣን አያከፋፍልም፣ በአንድ ሰው ላይ ነው የሚቆልለው፣ ተቃዋሚን አይፈቅድም፣ የሚቃወሙትን በጠላትነት ነው የሚያየው፡፡ ህዝቡ እንዳሻው እንዲንቀሳቀስ አይፈቅድም። ስለዚህ መለስም ይሁን ኃይለማርያም አምባገነን የሚያደርጋቸው የሚከተሉት ርዕዮተ ዓለም ነው፡፡
ኤፈርት በማን ሃብት ነው የተቋቋመው?
በህወሐት ሃብት ነው የተቋቋመው፡፡
የህወሐት የሃብት ምንጭ ምን ነበር?
በዚያን ወቅት ጠላት ከሚለው ደርግና፣ ከውጭ እርዳታ ያገኘው ሃብት ነበር፡፡ በንግድ በኩልም የተለያዩ መርከቦች ነበሩት፤ ይነግድ ነበር፡፡ መነሻ የሆነው ከዚህ የተገኘው ሃብት ነው፡፡ እኔ መነሳት ያለበት የሚመስለኝ፣ ሃብቱ ህዝብን እየጠቀመ ነው ወይ የሚለው ነው፡፡ ህዝቡስ ይሄን ሃብት መቆጣጠር ችሏል ወይ? የቦርዱ አባላትና ሊቀመንበሮች የፓርቲ አባላት ናቸው፡፡ በዚህ ሁኔታ ስሙ ነው ኢንዶውመንት እንጂ የህወሐት ተብሎ ነው የሚታሰበው፡፡
እንደ ሌላው ተቋም ብዙ ሃብት ቢይዝም ግልፅነትና ተጠያቂነት የለውም፡፡ ህዝቡ ወጪና ገቢውን አያውቅም፡፡ እንደ መርህ አንድ ጥያቄ ማንሳት ይቻላል። ኢንዶውመንት ማቋቋም ህጋዊ ነው፡፡ ፓርቲ ነጋዴ ሲሆንስ? ይሄ ጥያቄ ነው መነሳት ያለበት፡፡ በኤፈርት ዙሪያ የሙስና፣. የባለቤትነት ጉዳዮች ይነሳሉ፡፡ ምናልባት የሰጠው ጥቅም የምለው በሚከፈቱት ድርጅቶች ህዝቡ የስራ እድል ማግኘቱ ነው፡፡
የህወሐት 40ኛ ዓመት አከባበርን እንዴት አዩት?
ትግል መዘከር አለበት፡፡ ፀረ-ዲሞክራሲያዊ ስርአትን ለመጣል የተሰዉትን መዘከር አግባብነት አለው፤ አስፈላጊም ነው፡፡ እንኳን ለዚህ ትግል ህይወታቸውን ለሰጡት በግለሰብ ደረጃም ይዘከራል፡፡ ግን የሚከበርበት መንገድ አግባብ አይደለም፡፡ “ለምንድነው ለዚህ ፕሮግራም 10 ሚሊዮን ብር የሚወጣው?” የሚለው የግድ መነሳት አለበት፡፡
ህወሐት ከተመሰረተ 40 ዓመት፣ ስልጣን ከያዘ 23 ዓመት ሆኖታል፡፡ በአሉን ሲያከብሩ በነዚህ ዓመታት የተጓዙበትን አቅጣጫ መገምገም ነበረባቸው፡፡ ግን በተቃራኒው ህዝቡና ተቃዋሚዎች የሚያነሷቸውን ጥያቄዎች ለመደፍጠጥና ህዝቡን ወደ ኋላ ለመመለስ ሞክረዋል፡፡
ህውሐት ራሱም ወደ ፊት እንዳያይ ነው ያደረጉት፡፡ ህዝቡንም “ያሁኑን አታንሳ፤ ደደቢትን ተመልከት፤ የከፈልነውን መስዋዕትነት አስብ” ህወሐት በዚህ መልኩ ህዝቡን በስሜት ወደ ኋላ ጎትቶ በአሉን ማክበሩ ስህተት ይመስለኛል፡፡  

መግቢያ
ኢሕአዴግ፣ የዐፄውን ሥርዐት ርዝራዥና የደርግን አስከፊ ሥርዐት አፈራርሼ አገሪቱን በተሻለ የዴሞክራሲ ጎዳና እየመራኹ ነው በማለት ያለመታከት እያበሠረና እየወተወተ ይገኛል። ካለፈው ሥርዐት አላቅቄኣችኋለኹ የሚለው የራሱ እውነታ ቢኖረውም፣ በአንጻሩ ግን ኢሕአዴግ ራሱ የሚያበጅልን ዐዲስ ቀንበር መልክ አውጥቶ ዐደባባይ ወጥቶ መታየቱ አልቀረም፡፡ ያረጀውን አገዛዝ በዐዲስ አሠራር ከሚጭንብን ከዚኽ ዐይነቱ ቀንበር መላቀቅ የኢሕአዴግ ችግር ሳይኾን፣ የእኛ የአገሪቱ ዜጎች ችግር እና የቤት ሥራ መኾኑን መረዳት ይኖርብናል።
የዚኽ መጣጥፍ ቀዳሚ ዓላማ÷ ከኹለት ዐሥርት ዓመታት በላይ የቆየው የኢሕአዴግ አገዛዝ ከዴሞክራሲ፣ ከዜጎች ነጻነትና መብት አኳያ ምን ዐይነት መንገድ ይዞ እየኼደ እንደኾነና ኢሕአዴግ በጥቂቱም ቢኾን ከጀመረው የዴሞክራሲ መንገድ ስቶ የኋላ ኋላ ራሱን ወደ ኢ-ዴሞክራሲ አገዛዝ እንደምን እንደቀለበሰ በተወሰነ መልኩ ለማሳየት ነው። መጣጥፉ በሦስት ንኡሳን ርእሶች የተከፈለ ነው፡፡ በክፍል አንድ፣ የዴሞክራሲ እና የሊብራሊዝም ፅንሰ ሐሳቦችን ከአገራችን ኹኔታ ጋራ በማያያዝ የመንደርደሪያ ሐሳብ እሰጣለኹ። በክፍል ኹለት፣ በሰው ልጆች የቅርብ ታሪክ ውስጥ ዴሞክራሲ እና ነጻነት ለመጎናጸፍ ይበጃሉ የሚባሉት ተቋማት÷ ለምሳሌ፣ እንደ ፓርላማ፣ የፍትሕና የሚዲያ፣ የመድበለ ፓርቲና የምርጫ ሥርዐት እንዲኹም ሲቪል ማኅበራትን ኢሕአዴግ እንደምን መንፈሳቸውን ቀይሮ የራሱ የፖለቲካ መገልገያ እንዳደረጋቸው፤ የምርጫ ሥርዐቱን በምሳሌነት በማንሣት ሐተታና ትችቴን አቀርባለኹ። በክፍል ሦስት፣ በአገራችን የፖለቲካ ሕይወት ውስጥ የሚገኘውን አፍራሽ የኾነ የፍትሕ አቀራረብ በማሳየትና በመጨረሻም፣ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ዐጭር ማስታወሻ በማኖር መጣጥፉን እቋጫለኹ።      
፩. የዴሞክራሲ እና የሊበራሊዝም ነገር
እንደ ዕውቁ የሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ምሁር ሳሙኤል ፒ. ሃንቲንግተን እይታ፣ በቅርብ የሰው ልጅ የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ በተለያዩ ጊዜዎች ሦስት የዴሞክራሲ ሞገዶች ተከሥተዋል። ከፍጹማዊ አገዛዝ ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዐት የተደረጉትን ሽግግሮች ምሁሩ በሞገድ አምሳል ያቀርቧቸዋል። እንደእርሳቸው ትረካ፣ የመጀመሪያው ሞገድ ከፈረንሳይና ከአሜሪካ ዐብዮት በኋላ በ19ኛው ምእት መባቻ የተነሣው ሲኾን ተከታዩ ደግሞ ከኹለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ በብዙ አገሮች ውስጥ የታየው ነው፤ ሦስተኛው ደግሞ ከ1974 እስከ 1990 (እ. አ. አ.) ሠላሳ ያኽል አገሮች ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዐት የተሸጋገሩበት ነው፤ ምሁሩ ይህን የሽግግር ወቅት “ሦስተኛው የዴሞክራሲ ሞገድ” የሚል ስያሜ ሰጥተውታል።
ከሦስተኛው ሞገድ በኋላ ግን ሒደቱ የዴሞክራሲ ልምላሜን እያጠወለገ፣ በአንዳንድ አገሮች ውስጥ ወደ ኋላ ይቀለበስ ጀምሯል፡፡ ከእኒኽ አገሮች መካከል ኢትዮጵያ አንድዋ ናት። የአገሮቹ መንግሥታት ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዐት ግንባታ ገብተናል ብለው ሲያውጁ፣ ነጻነት እና የመብት ጥያቄዎች ቀዳሚ ቦታ ይይዛሉ ተብሎ ተገምቶ ነበር። ኾኖም ግን፣ እነዚህ መንግሥታት የዴሞክራሲን መዋቅር ሌጣውን ተቀበሉ እንጂ በባሕርያዊነት አብሮት የሚሔደውን የሊብራሊዝም ጎዳና ስላልተከተሉ፣ በአሉበት እየረገጡ ወደፊት መራመድ ተስኗቸዋል።
በዚህ ዙሪያ ወሳኝ ጥናቶችን ያደረጉ ሰዎች እንደሚናገሩት፣ የዴሞክራሲ እና የሊብራሊዝም ፖለቲካዊ መርሕ ከፍልስፍና አንጻር ሲታዩ አንድነትም ልዩነትም አላቸው። የሰው ልጅ ምሉዕ የኾነ ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊና ፍትሐዊ ነጻነት ይኖረው ዘንድ የዴሞክራሲ እና የሊብራሊዝም መስተጋብር የግድ ይላል። ዴሞክራሲ የሚለው ቃል በዋናነት ሕዝብን ከዓምባገነናዊ ኀይል የሚከላከል ጋሻ (Demo-protection) ሲኾን፣ ሊብራሊዝም ደግሞ የሕዝብ ሉዓላዊነት (Demo-power) ነው። ዐዲሶቹ “ዴሞክራሲያዊ” መንግሥታት በተወሰነ ደረጃ የዴሞክራሲን አንዳንድ ፈለጎች ለመከተል ባይቸገሩም፣ የሊብራል ጥሪዎችን ማድመጥ ግን በእጅጉ ተስኗቸዋል።
ምናልባት፣ በዴሞክራሲ እና በሊብራሊዝም መሀል እንዴት ወይም ምን ዓይነት ልዩነት ሊኖር ይችላል ብለው የሚጠይቁ ሰዎች ስለሚኖሩ በዚኽ ዙሪያ ጥቂት ብለን ማለፉ ተገቢ ነው። አንደኛ፣ ዴሞክራሲ የሚያተኩረው በሥልጣን ክፍፍል፣ በየጊዜው በሚደረጉ ምርጫዎች፣ በብዙኃን መገናኛ፣ በመድበለ ፓርቲ፣ በሲቪል ማኅበራት… ወዘተ ተቋማዊ አያያዝና አሠራር ላይ ነው። በአንጻሩ ሊብራሊዝም በሕግ የበላይነት፣ በመሠረታዊ የሰው ልጆች ነጻነትና መብት ላይ ያተኩራል።
ኹለተኛ፣ ዴሞክራሲ የመንግሥት ሥልጣን በሚያዝበት መዋቅር ላይ ሲያተኩር፣ ሊብራሊዝም ደግሞ የሥልጣን ወንዝ ከገደቡ ወጥቶ ዜጎችን እንዳያጥለቀልቅ ለመከላከል፣ በምን መንገድ እየተቀየሰና እየተገራ መሔድ እንዳለበትና እንደሚገባው ይደነግጋል። ይኸውም ዴሞክራሲ ተሳትፎ ላይ ሲያተኩር ሊብራሊዝም ደግሞ ተጠያቂነት ላይ ያተኩራል። በአንዲት አገር መልካም የነጻነትና የፍትሕ ሕይወት መንገድ ተይዟል የሚባለው፣ ዴሞክራሲ የሚጠይቀው ሕዝባዊ ተሳትፎና ሊብራሊዝም የሚሻው መንግሥታዊ ተጠያቂነት በአንድነት ተባብረው ሲገኙ ነው።
በፅንሰ ሐሳብ ደረጃ የዴሞክራሲ እና የሊበራሊዝም የአጽንዖት ልዩነት እንደተጠበቀ ኾኖ፣ ወደ ኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ኹኔታ ስንመጣ፣ ሥርዐቱ የኹለቱንም መሠረታዊ ጥሪዎች ማስተናገድ የተሣነው ኾኖ እናገኘዋለን። የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ከደርግ በኋላ፣ በተወሰነ መልኩ የዴሞክራሲ ጭላንጭል ቢያገኝም፣ ሕገ መንግሥቱ እንደሚደነግገው የሥልጣን ባለቤትነትን አልተጎናጸፈም። ይህን ለማለት የሚያስደፍረው፣ የአገራችንን ፖለቲካ ከሕዝባዊ ተሳትፎና ከመንግሥታዊ ተጠያቂነት አንጻር ስንመለከተው ትልቅ ጉድለት በመኖሩ ነው፡፡
(፩) ሕዝባዊ ተሳትፎ፦ ዜጎች በሕይወታቸው፣ በንብረታቸው፣ በማኅበረሰባዊ ኹኔታዎቻቸው ወሳኝ በኾኑ ጉዳዮች ላይ የምክክርና የውሳኔዎች አካል ባልኾኑበት ሥርዐትና አሠራር ውስጥ የዴሞክራሲ መሠረታዊ ጥሪ የኾነው ሕዝባዊ ተሳትፎ አልተወለደም ማለት ነው። ለኢሕአዴግ ግን ተሳትፎ ማለት (ሀ)አስቀድሞ የወሰነውን ነገር ሥልጠና በሚል ፈሊጥ ወደ ሕዝብ ማውረድ፣ (ለ)ባለድርሻ በሚል ፈሊጥ የራሱን ወኪሎች መርጦ ውሳኔዎች በተሳትፎ የተገኙ ማስመሰል ነው። ለሐቀኛ ተሳትፎ ግን የንግግር ነጻነት እና የመሰብሰብ ነጻነት ያስፈልጋል። መንግሥት እና ዜጎች በእኩል ደረጃ መወያየታቸው ቀርቶ፣ መንግሥት አቀባይ ሕዝብ ደግሞ ተቀባይ ኾነዋል።  
(፪) ተጠያቂነት፦ መረጃ ከመንግሥት ወደ ሕዝብ የማይወርድበት አገር ውስጥ የተጠያቂነትን ሥርዐት ማሟላት በእጅጉ አስቸጋሪ ይኾናል። ሥርዐቱን ለማሟላት ከመንግሥት ቁጥጥር ውጭ የኾነ ሚዲያ ይኖር ዘንድ ግድ ይላል። ዜጎች መረጃ የሚያገኙበት መንገድ እስከሌላቸው ድረስ መንግሥትን ተጠያቂ ሊያደርጉባቸው የሚችሉባቸው መንገዶች ኹሉ ይዘጋሉ።
አንዳንድ የፖለቲካ ምሁራን፣ ዴሞክራሲ ለማበብ ረዘም ያለ ጊዜ ይጠይቃል፤ በመኾኑም ኢሕአዴግን የበለጸገ ዴሞክራሲ አላመጣም ብሎ መተቸት አግባብነት የለውም፤ የሚል መከላከያ ያቀርባሉ። የአፍሪቃ ዴሞክራሲ ገና ለጋ በመኾኑ ለመቶዎች ዓመታት ከቆየው ምዕራባዊ ዴሞክራሲ ጋራ ሊነጻጸር አይገባም፤ ሲሉም ይሞግታሉ። ለዚኽ ዓይነቱ አስተያየት ተገቢ መልስ ሰጥተዋል ብለን የምናምነው የ20ኛው ምእት ትልቁ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር ጂዮቫኒ ሳርቶሪ (Giovanni Sartori) ናቸው። በእርሳቸው አመላለስ፣ ዴሞክራሲ የተለያዩ ክፍሎች ያሉት መዋቅር እንጂ አንድ ወጥ ባለመኾኑ፣ አንድ መንግሥት ቢያንስ የዜጎችን የንግግር፣ የመሰብሰብና ሐሳብን የመግለጽ ነጻነትን ለማክበር ምን ያኽል ጊዜ ያስፈልገዋል? ጋዜጠኛን ላለማሰር፣ የፖለቲካ ስብሰባዎችንና ሰላማዊ ሰልፎችን ላለመከልከል ሥርዐቱ ስንት ዘመን መቆየት ይኖርበታል?    
በእኔ በኩል በዴሞክራሲ ፍላጎትና በገዢዎች ፍላጎት መሀል የተዘረጋው ቅራኔ እንደተጠበቀ ኾኖ፣ ከዚህ ቀደም ለማሳየት እንደሞከርኹት፣ የአገራችን የዴሞክራሲ ሥርዐት ግንባታ ለችግር የተጋለጠበት አንዱ ምክንያት፣ አውሮጳውያን በዘመነ አብርሆ ለመቶ ዓመታት ያኽል እንደአደረጉት፣ በሊብራሊዝም ባህል ላይ የተመሠረተ የሐሳብና አመለካከትን የመግለጽ ነጻነት፣ የኅትመት ነጻነት፣ ሃይማኖታዊ መቻቻልና በጥቅሉ በመሠረታዊ የሰው ልጆች የነጻነት ጥያቄዎች ላይ አስቀድመን ብርቱ ሥራ ባለመሥራታችን ነው።
፪. ዐዲሶቹ የኢ-ዴሞክራሲያዊ ኀይሎች ሥርዐተ ተቋማት
በዚህ ርእስ ሥር በከፊል የማቀርበው ሐሳብ በዋናነት የተመረኮዘው፣ በቅርቡ የጀርመኑ የፖለቲካ ሳይንቲስት ፕሮፌሰር አንድሪያስ ሺድለር (Andreas Schedler) በ2009 (እ. አ. አ.) በዴሞክራሲ ስያሜ ስለሚንቀሳቀሱት ዐዲስ መንግሥታት በአጠኑት ጥናት ላይ ነው።
ቀደም ባለው ክፍል ለማሳየት እንደሞከርኹት፣ ፕሮፌሰር ሳሙኤል ፒ. ሃንቲንግተን “ሦስተኛው የዴሞክራሲ ሞገድ” ወደፊት መገስገሡን ትቶ፣ የቀኝ-ኋላ ዙር መንገድ መከተሉን መግለጻቸውን አውስቻለኹ። ሌሎች ጸሐፍትም፣ ከዚኹ የገለጻ መንፈስ ጋራ በሚሔድ መልኩ፣ ይህን ፕሮፌሰሩ ‘ቅልበሳ’ ያሉትን ፅንሰ ሐሳብ፣ አንዴ ‘ኢ-ሊብራል ዴሞክራሲ’፣ አንዳንዴ ‘ኦተሪቴሪያን ዴሞክራሲ’ የሚሉ ስያሜዎች እየሰጡ ለመግለጽ ሞክረዋል። ፅንሰ ሐሳቡ በተለያዩ ስያሜዎች ቢገለጽም፣ በዋና ጭብጣቸው፣ የሥርዐቶቹን ‘ኢ-ዴሞክራሲያዊ’ ባሕርይ የሚያሳዩ መኾኑ ላይ ግን ሙሉ ስምምነትና አንድነት አላቸው።የዴሞክራሲ ሞገድ ውስጥ የተፈጠሩት ዐዲስ ሥርዓቶች፣ በውጣኔአቸው የነጻነትና የመብት ፍንጣቂ ቢታይባቸውም፣ ከሰብአዊ ነጻነት አኳያ ሲመዘኑ ግን የተመናመነ የተሰፋ መንገድ ላይ እንዳሉ መረዳት አዳጋች አይኾንም።
“ፍጹማዊ የሥልጣን አገዛዝ” ወይም ደግሞ “የጭቆና አገዛዝ” በሚል ቀደም ብሎ የሚታወቀው ስያሜ በዐዲሶቹ ሥርዐቶች ዐውድ ውስጥ “ዴሞክራሲያዊ” የሚል ቅጽል ተለጥፎለት እናገኘዋለን። እዚኽ ላይ ማንሣት የሚገባን መሠረታዊ ጥያቄ፣ “ዴሞክራሲያዊ” የሚለው ቃል ከእኒኽ ሥርዓቶች ስያሜ ጋራ ለምን አብሮ ተያይዞ ይቀርባል? የሚል መኾን ይኖርበታል። ይህን ጥያቄ የምናነሣበት ዋነኛ ምክንያት በቀደመው ዓምባገነናዊ አገዛዝ (Dictatorship) እና በዛሬው ጠቅላይ አገዛዝ (Authoritarianism) መካከል መሠረታዊ ዝምድናና ልዩነት ይኖር እንደኾን መፈተሽ ስላለብን ነው።
ፍተሻው በቀጥታ ወደ አገራችን ተጨባጭ ኹኔታ ያመጣናል። ለመኾኑ፣ በደርግ ሥርዐትና በኢሕአዴግ ሥርዐት መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው? ደርግን “ዲክቴተርሺፕ”፣ ኢሕአዴግን ደግሞ “ኦተሪቴርያን” የምንላቸው ለምንድን ነው? የኹለቱ ሥርዐቶች ልዩነት ሲቀርብ፦ አንዱ ገዳይ፣ ጨፍጫፊ፣ አረመኔ ተደርጎ ይተነተናል፤ ሌላው ደግሞ፣ በወዳጆቹ ዘንድ፣ እንደ ነጻ አውጪ፣ የዴሞክራሲ አራማጅ ተደርጎ ሲቀርብ፣ በተቃዋሚዎቹ በኩል ደግሞ፣ እንደ ኢ-ዴሞክራሲያዊና ጎሰኛ ተደርገው እንደኾነ ዘወትር እንሰማለን። ኹለቱም አቀራረቦች ላይ ላዩን ሲታዩ በተወሰነ መልኩ እውነታ ቢኖራቸውም፣ በፅንሰ ሐሳብ ደረጃ ግን፣ የኹለቱን ሥርዐቶች መሠረታዊ ልዩነት በበቂ አይነግሩንም። በመኾኑም የቀድሞውንና የዐዲሱን መንግሥታዊ ሥርዐቶች ልዩነት በምንመረምርበት ጊዜ፣ ፕሮፌሰር ሺድለር የሚያቀርቡት ሐሳብ የበለጠ ጠቃሚ ኾኖ እናገኘዋለን።
ቀዳሚ የሚኾነው የኹለቱም ሥርዐቶች ተልእኮ ሥልጣንን ማካበት እና ሥልጣን ላይ መቆየት ነው። ከዚኽ አንጻር፣ ኹለቱም ሥርዐቶች ግባቸው አንድ ነው፡፡ ከግቡ ለመድረስ የሚጠቀሙባቸው መንገዶች ግን የተለያዩ ናቸው። እንደ ፕሮፌሰር ሺድለር አቀራረብ፣ የቀድሞዎቹ ዓምባገነኖች ሥልጣን ላይ ለመቆየት የሚጠቀሙባቸው ተቋማት ወትሮውንም በታሪክ ውስጥ የሰውን ልጅ ነጻነት በመፈታተን የሚታወቁትን፣ እንደ ‘የጦር ኀይል’፣ ‘ፖሊስ’፣ ‘ጸጥታ’፣ ‘ደኅንነት’፣ ‘ሲቪል ታጣቂዎች’ ናቸው። በሌላ በኩል፣ ዐዲስ የመጡት ዴሞክራሲያዊ ነን የሚሉት ሥርዐቶች ደግሞ የድሮውን የመጨቆኛ ተቋማት ትተው፣ የሰውን ነጻነትና መብት ያስከብራሉ የሚባሉትን የፍትሕ፣ የሕግ አውጪ፣ የምርጫ፣ የብዙኃን መገናኛ ተቋማትን ወዘተ… በጭቆና መሣሪያነት ይጠቀማሉ።
እዚህ ላይ ተገቢ የሚኾነው ጥያቄ፣ ለነጻነት የታሰቡ ተቋማት እንደምን ተቀልብሰው የመንግሥት መጠቀሚያ ለመኾን በቁ? የሚል ነው። በመኾኑም በዚህ ጉዳይ ላይ ትንሽ ገለጻ ከሰጠን በኋላ፣ የፍትሕ ተቋማትን፣ የብዙኃን መገናኛ ተቋማትንና የምርጫ ተቋማትን በምሳሌነት እናነሣለን።
ከኹሉ አስቀድሞ፣ ዐዲሱ ሥርዐት ሥልጣን በሚይዝበት ጊዜ የሚረከበው “ባዶ የፖለቲካ ተቋማዊ መሬት” (institutional tabularasa) አያገኝም። እንዲያውም ካለፈው ሥርዐት የቀጠሉ ርዝራዥ ተቋማት ተፎካካሪ ሊኾኑበት ስለሚችሉ የሚጠቅመውን ተቋም ዐቅፎና አስቀጥሎ አይበጀኝም የሚለውን ያፈርሰዋል።
በኹለተኛ ደረጃ፣ ዴሞክራሲን ሊያራምዱ ይችላሉ የሚባሉትን ዐዲስ ተቋማት ይገነባል፤ ኾኖም ግን፣ ተቋማቱ በመጀመሪያ እንደ ሥርዐት የቆሙበትን መንፈስ ሽሮ ሕይወት አልባ በማድረግ ለታይታ፣ በቅርፃቸው ብቻ እውናዊ እንዲመስሉ ያደርጋቸዋል። በዚኽም ሳይገታ በራሱ ቁጥጥር ሥር ከአዋላቸው በኋላ፣ ተቋማቱን እንደ ለማዳ እንስሳ እዚያው ሥርዐቱ ግቢ ውስጥ ይለቃቅቸዋል፤ ነገር ግን እነኚኽ የተሽመደመዱና ለአገዛዙ የተገሩ ተቋማት እንዲኹ ተቀላቢ ኾነው አይቀመጡም። ሥርዐቱ እስከአለ ድረስ ትጉሃን የጭነት ፈረስ ኾነው አገልግሎታቸውን ያበረክታሉ።
በሦስተኛ ደረጃ፣ ሥርዐቱ ሲጀምር ሕገ መንግሥት ተቀርፆ በአንድ በኩል ከአሐዳዊ ወደ ፌደራላዊ ሥርዓት ሽግግር መደረጉ ተገልጧል፤ በሌላ በኩል ከአንድ ወጥ የሥልጣን ዘርፍ ወደተለያየ የሥልጣን ዘርፍ ሔዶ የሥልጣን ክፍፍል እንዲኖር በሕገ መንግሥቱ በሕግ ተደንግጓል፡፡ አሁን ምን ደረጃ ላይ ደርሰናል ብለን በምንመለከትበት ጊዜ ግን የምናገኘው የሚከተለውን እውነታ ነው። ሕግ አስፈጻሚው ክፍል ወደ ጎን (Horizontal) እና ወደ ላይ (vertical) የሥልጣን ሽሚያ በማድረግ በአንድ በኩል ፌደራል ተቋሙ ላይ በሌላ በኩል የሕግ አውጪው እና የሕግ ተርጓሚው ላይ ትልቅ ጫና በማሳረፍ ሥልጣናቸውን በእጅጉ ገድቦታል። በመኾኑም፣ በእኒኽ ኹለት ዐሥርት ዓመታት ውስጥ፣ ሕግ አስፈጻሚው ተቋም ከሌሎቹ የመንግሥት ክፍሎች ኹሉ በበለጠ እየተጠናከረ እንዲኹም ሌሎቹን ተቋማት እያመነመነ ሔዷል።
ሀ) የፍትሕ ተቋማት፡-
በማንኛውም ሀገር ታሪክና በእኛም ነባራዊ ኹኔታ እንደምንረዳው፤ ያለሕግ ነጻነት የለም። እንዲኹም ሕግን ለመተግበር የፍትሕ ተቋማት ወሳኝ ድርሻ አላቸው። ኾኖም ግን የአንድን አገር ፍትሕ ለማስከበር የሕግ ተቋማት ራሳቸው በነጻነት እንዲንቀሳቀሱ የግድ ይላል። ይኸውም የራሳቸውን ልዕልና ያላስከበሩ ተቋማት የዜጎችን ነጻነት ያስከብራሉ ማለት ዘበት ስለኾነ ነው።
አንዳንድ ጸሐፍት እንደሚነግሩን፣ የጠቅላይነት ሥርዓቶች የፍትሕ ተቋማትን ልዕልናና አቋም ለመቦርቦርና ለማዳከም ሕጉን ለመጨቆኛ በሚኾን መልኩ ደጋግመው በማመቻቸት (Judicialization of repression) ሲተገብሩ ይስተዋላሉ። ይህን ለመተግበር ከሚከተሏቸው መንገዶች የተወሰኑትን እንደሚከተለው ማየት ይቻላል።
የፍትሕ ተቋማትን ሥልጣን መገደብ (disempowerment)፤
የፍትሕ ተቋማትን መገደብ በምንልበት ጊዜ፤ የተለያየ እመቃ ደረጃ ያለው ነው። በመጀመሪያ፣ የተሠየሙትን ዳኞች ሥልጣን መገደብና ማሳነስ ነው፤ በተጨማሪም ለመመርመር የሚችሉበትን ወሰን በእጅጉ ማጣበብና በመጨረሻም ዳኞች ሊኖራቸው የሚገባውን የውሳኔ ነጻነት (ዲስግሬሽን) ማሳጠር ማለት ነው።
ለመንግሥት “ይበጃሉ” የሚባሉ ሰዎችን መሠየም፤ በዚህ ረድፍ የሚታየው ኢ-ፍትሐዊ ጉዞ የሚጀመረው በዳኝነት ወንበር ላይ የሚሠየሙት ዳኞች እየተመረጡ የሥርዐቱ ወዳጆች እንዲኾኑ መደረጉ ነው። የሕዝብ አስተዳደር ጥናት ያጠኑ አንዳንድ ምሁራን እንደሚነግሩን፤ አንደኛው የመንግሥት ችሎታ፣ ለጥቅማጥቅም ቀልባቸውን ሊሰጡ የሚችሉትን ነቅሶ የማውጣት ስልት ነው። እነኚኽም ለጥቅማጥቅምና ድጎማ የተመቻቹ ሹመኞች (incentive compatibility) ናቸው። በጥቅም የማይደለሉትን ደግሞ ቀጥተኛውን መንገድ ተከትለው እንዳይሔዱ በማስፈራራት ሐሳብን የማስፈጸም ጫና (dissuasive punishment) እንዲደርስባቸው ይደረጋል። ከዚኽም በተጨማሪ የፍትሕ ሒደቱን ረጅምና ውሳኔውን ለመሻር በሚያመች መልኩ ከታች ወደ ላይ እንዲሔድ፤ እልባቱ በረጅም የአቤቱታና የውሳኔ መሻርያ ሰንሰለት እንዲፈጸም ይደረጋል።
የተበታተነ የፍትሕ ሥርዐት፤
ሕጉን ለመጨቆኛ በሚኾን መልኩ ማመቻቸት (Judicialization of repression) በአንድ ሀገር ያለ የፍትሕ ሥርዓት አንድ ወጥ የኾነ ቅርጽ እንዳይኖረው፣ መደበኛ ከኾነው የሕግ ተቋም ተፎካካሪና በሕግ አስፈጻሚው ቁጥጥር ሥር የኾነ መንታ ተቋም በመፍጠር የመደበኛውን ፍርድ ቤት ተግባር ወደ ተቀጽላው ተቋም ማሸጋገር ነው።
ለ) የሚዲያ ቁጥጥር፤
ሚዲያን በሚመለከት ተቀዳሚው የኦተሪተርያን መንግሥታት ዓላማ፤ ፖለቲካዊ መረጃዎችን የማምረቻ ኃይልን መቆጣጠርና በአገሩ ውስጥ ብቸኛ አምራች ኾኖ መቅረብ ነው። ዜጎች በተለይ የፖለቲካ መረጃን በአማራጭ እንዳያገኙና ተፎካካሪ የኾነ የፖለቲካ ምልከታ እንዳይኖር ፍጹማዊ ሥልጣንን የተጎናጸፉ መንግሥታት ከሚያደርጓቸው ዕቀባዎች መካከል የሚከተሉትን መጥቀስ ይቻላል።
የመገናኛ ምንጮች ብዝኃነት በመከልከሉ ዜጎች የመገናኛ አውታር ባለቤት የመኾን ዕድል የላቸውም። በመኾኑም በአገሪቱ የሚገኙት ሚዲያዎች በመንግሥት ሥር በመኾናቸው፤ የዝግጅቱን ይዘት ለመወሰን፣ ሕዝቡ ምን መስማት እንዳለበትና ምን መስማት እንደሌለበት በቁጥጥራቸው ሥር ማድረግ ይችላሉ። አንዳንድ የሚዲያ ተቋማት ለግለሰቦች በባለቤትነት የተሰጡ ቢኾንም የትኩረት አቅጣጫቸው ጠንከር ያሉ ፖለቲካዊ ጉዳዮችን በማንሣት ወይም ወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮችን በትኩረት በመዘገብ እንዲሠሩ ስለማይፈቅድ ብዙ ጊዜ በመዝናኛ፣ በስፖርታዊ ዘገባዎችና ይህን በመሳሰሉ ጉዳዮች ላይ የታጠሩ ፕሮግራሞችን በማስተላለፍ እንዲጠመዱ ያደርጓቸዋል። ይህ ዐይነቱ የመገናኛና ሚዲያ የትኩረት አቅጣጫ ለሥርዐቱ ብዙም አስጊ ባለመኾኑ ከጫና ለመገላገል የሚጠቅም መላ ኾኖ ሲያገለግል ይስተዋላል።
ሐ. የምርጫ ሥርዓት፡-
ወደ ዴሞክራሲ ጎዳና ገብተዋል የሚባሉት አገሮች ተቀዳሚ ሥራ የሠሩት በምርጫ ተቋማት ላይ ነው። መንግሥታት በአገራቸው ሕዝብ ፊትም ኾነ በዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ፊት በፍትሐዊ ምርጫ ሥርዐትና ሒደት ውስጥ ማለፋቸው የቅቡልነት መሠረታዊ ጥያቄ ኾኗል። የምርጫ አስፈላጊነት በዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ድንጋጌ ላይ እንኳን የሕግ ዕውቅና አግኝቶ ወቅታዊ እና እውነተኛ ምርጫ ማካሔድ የአገሮች ተቀዳሚ ሓላፊነት እንደኾነ ተቀምጧል።
በኢትዮጵያም በሕገ መንግሥቱ፣ እንደ አንድ የዴሞክራሲ ሽግግር ሒደት ውስጥ እንዳለ አገር፣ በየአምስት ዓመቱ አገሪቱን ለማስተዳደር ተፎካካሪ ፓርቲዎች በብሔራዊ ምርጫ ለመንግሥት ሥልጣን የሚወዳደሩበት ሥርዐት ተደንግጓል። ከዚኽም በመነሣት፤ የመጪው ግንቦት ወር 2007 ዓ.ም. ውድድር ብሔራዊ ምርጫ ነጻ፣ ፍትሐዊና የሕዝብ ተአማኒነት ባለው መልኩ እንዲካሔድ አቅጣጫ ተቀምጧል። የሕዝብ ተአማኒነት የሚለው እንደ መሥፈርት በዓለም አቀፍ ደረጃ የተቀመጠ ስላልሆነ ለጊዜው እንተወውና፣ “ነጻ” እና “ፍትሐዊ” በሚሉት ስያሜዎች ላይ እናተኩር። ከኹሉ አስቀድሞ፣ ቃላት በመስጠትና ቃላቱን በመደጋገም ብቻ እውንና ተጨባጭ ማድረግ ይቻላል ወይ? በአኹኑ ጊዜ ኢትዮጵያ ነጻና ፍትሐዊ ምርጫ ልትጎናጸፍ ትችላለች ወይ? ስለ ነጻና ፍትሕዊ ምርጫ በመጠኑ ከአብራራኹ በኋላ፣ የጥያቄዎቹን ምላሽ ለአንባቢ እተዋለኹ።  
“ነጻ” እና “ፍትሐዊ” የሚለው ቃል በመጀመሪያ ብቅ ያለው እ.ኤ.አ. በ1927 ዓ.ም. የአሜሪካን ካልቨን ኮሌጅ ልኡክ ኒኳራጓ ለምትባለው አገር “አሜሪካ ነጻና ፍትሐዊ ምርጫ እንድታካሂድ ቃል እሰጣለኹ፤” የሚል ንግግር ሲያደርግ ቃሉ የመጀመሪያ ዕውቅናውን አግኝቷል። ቀጥሎም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የ1956 ዓ.ም የቶጎ ላንድን የወደፊት ኹኔታ በሕዝበ ውሳኔ ለማረጋገጥ ባወጣው ሪፖርት ላይ ይኸው ቃል ተደግሟል። በሦስተኛ ደረጃ፤ በ1978 ዓ.ም. በተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት ውሳኔና ቁጥጥር የናሚቢያ ነጻነት፣ ነጻና ፍትሐዊ ምርጫ ከተካሔደ በኋላ ምክር ቤቱ የሒደቱን ፍትሐዊነትና ነጻ አካሔድ ለዓለም ሲያበሥር ቃላቱ ዓለም አቀፋዊ ተቀባይነት ለማግኘት በቅተዋል።
ኹለቱ ስያሜዎች አብዛኛውን ጊዜ በአንድነት ቢጠቀሱም፤ ይዘታቸውንና ትርጉማቸውን በተናጠል ለማየት እሞክራለኹ፡፡
(ሀ) የምርጫ ነጻ ሒደት ሲባል፡-
ከኹሉ አስቀድሞ ነጻ የሚለው ቃል ዜጎች የማይሸራረፍ የመምረጥ መብት እንዳላቸው የሚጠቁም ነው። የዜጎችን በነጻ የመምረጥ መብት ለመተግበር የሚከተሉት ኹኔታዎች መመቻቸት አለባቸው።
የመሰብሰብ እና የመመካከር ነጻነት፣
ማኅበራትን የማቋቋም መብት፣
የመንቀሳቀስ መብት፣
የመናገር መብት፣
የፖለቲካ ድባቡ ከዘለፋ፣ ከማስፈራራትና ከመዋከብ የጸዳ መኾን ይኖርበታል።
(ለ) ፍትሐዊ ምርጫ ስንል ደግሞ፡-
ተአማኒ በኾነ የምርጫ ቦርድ ሥር የድምፅ ቆጠራው መካሔዱ፣
ከምርጫው በፊትም ኾነ በኋላ በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል አለመግባባት ሲከሠት ፍትሐዊ የግጭት መፍትሔ የሚሰጥ ተቋም መኖሩ፣
ኹሉም የፖለቲካ ፓርቲዎችና ግለሰቦች ውድድር ውስጥ እንዲገቡ ያልተጨናነቀና እኩል ዕድል መስጠት፣
ኹሉንም ተፎካካሪ ፓርቲዎች የሚያስተናግድ እኩል የሚዲያ አቅርቦት ማመቻቸት፣
የውድድሩ ሜዳ ለኹሉም ፓርቲዎች የተስተካከለ እንዲኾን ማድረግ ሲቻል፣
በዋናነት የመንግሥትና የፓርቲ የምርጫ ወጪ የሚወጣበት ቋት ሲለይ ነው።
ከላይ የጠቀስናቸው አንዳንድ ነጥቦች እንደሚያሳዩት፣ ነጻና ፍትሓዊ ምርጫ የሚሟላው በአንድ ቀን የድምፅ መስጫ ኮሮጆ ውስጥ ካርድ በማስገባት ሳይኾን ሦስት የምርጫ ኺደትን ሲያካትት ነው። (ሀ) ከምርጫ በፊት ያለው የአገሪቱ የፖለቲካ ድባብና የመወዳደሪያው ሜዳ መስተካከል፤ (ለ) የምርጫው ቀን ውሎ እና ገለልተኛ አወዳዳሪ ተቋም፤ (ሐ) ከምርጫው ዕለት በኋላ በተወዳዳሪዎችና በድምፅ ሰጪዎች መካከል ጭቅጭቅ ቢነሣ ዳኝነትን የሚሰጥ ገለልተኛ ተቋም። ከላይ ላነሣነውም ጥያቄ ተገቢ ምላሽ ለማግኘት፣ አንባቢ፣ የጠቀስናቸውን መስፈርቶች ከአገራችን ነባራዊው ኹኔታ ጋራ በማነጻጸር የራሱን ፍርድ መስጠት ይችላል።  
(ይቀጥላል)

============================================================

 “ሁሉም የጋዜጣው ኮፒዎች አሉኝ”

በሙያዬ የፅንስና የማህፀን ሀኪም ነኝ፡፡ ለመፅሀፍና ለጋዜጣ ልዩ ፍቅር ስላለኝ ላለፉት በርካታ ዓመታት አያሌ መፅሀፍትን እንዲሁም ጋዜጦችን አንብቤአለሁ፡፡ ጋዜጣ ሳነብ አልመርጥም፡፡ በተለይ አዲስ አድማስን አንብቤ ለአዟሪው መልሼ አላውቅም፡፡ መጀመሪያውኑም አዲስ አድማስን ስገዛ ርዕስ እና የፊት ገፅ አልመለከትም፡፡ መግዛት ግዴታዬ እንደሆነ ነው የሚሰማኝ፡፡ ገና ብርቱካናማውን የጋዜጣውን ሎጐ ስመለከት የሆነ ደስ የሚል ነገር ይሰማኛል፡
አዲስ አድማስ ባለፉት 15 ዓመታት እጅግ በርካታ ቁም ነገሮችን፣ አስተማሪና አዝናኝ ጉዳዮችን ሲያስኮመኩመን ኖሯል፡፡ “የእኛ ሰው በአሜሪካ”፣ “እንጨዋወት”---የመሳሰሉት አምዶች አይረሱኝም፡፡ መስራቹን አቶ አሰፋ ጐሳዬን ነፍሱን በገነት ያኑራት እላለሁ፡፡ እሱ ካለፈም በኋላ የጋዜጣው ህልውና እንዲቀጥል ያደረጉትን ቤተሰቦቹን ማመስገን እወዳለሁ፡  ጋዜጣው ከመነሻው ጀምሮ ቢታይ፤ በዘርፉ ጥናትና ምርምር ለሚያደርጉ፣ ወደ ጋዜጣ አሳታሚነት ለሚገቡ፣ በጋዜጠኝነት በተለይ በህትመት ሚዲያ ላይ ትምህርት ለሚከታተሉ ሁሉ አይነተኛ ግብአት ነው ባይ ነኝ፡፡
የእኛም ማህበር (ኢሶግ) በጋዜጣው ላይ “ላንቺና ላንተ” የተሰኘ ቋሚ አምድ አለው፡ በዚህ ዓምድ በሚወጣ ፅሁፍ በርካቶችን ማስተማር ተችሏል፡፡ በአገራችን እንደ ልብ ጋዜጣ በማይገኝበትና እንደ ልብ መፃፍ በማይቻልበት ሁኔታ እንኳን አዲስ አድማስ ሁሉን ተቋቁሞ፣ ሁሉን እንዳመሉ ችሎ መረጃ ያቀብለናል፡፡ በውስጡ ደግሞ እንደ ገጣሚና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን፣ እንደነ አብደላ ዕዝራ፣ እንደነ ኤፍሬም እንዳለ እና መሰል ሳተና ብዕረኞች አሉት፡፡ ቀድሞም በርካታ ብርቱ ብርቱ ፀሐፊዎች ነበሩ፡ ያን ጊዜም አሁንም ጋዜጣውን አነበዋለሁ፡፡ ወንዱ ልጄ ሶፍትዌር ኢንጂነር ቢሆንም የእኔው ዓመል ተጋብቶበት፣ ቅዳሜ ቅዳሜ አዲስ አድማስን ብብቱ ስር ሸጉጦ መምጣት ከጀመረ ረዘም ያለ ጊዜ ሆኖታል፡፡ ታዲያ እሱ ገዛ ብዬ እኔ መግዛቴን አልተውም፡፡ በዚህ ምክንያት ከመጀመሪያው እትም አንስቶ  የአድማስ ኮፒ አለኝ፡፡
አዲስ አድማስ ጋዜጣን ተውሶ የማይመልስልኝ ጠላቴ ነው፡፡ ለስራ ብዙ ጊዜ ወደተለያዩ የአፍሪካና የአውሮፓ አገራት ስሄድ፣ ደንበኛዬ ጋዜጦቹን በጥንቃቄ ያስቀምጥልኛል፡፡ አሁን አሁን ደግሞ ከአገር ስወጣ ዌብሳይቱ ላይ ማንበብ መቻሌ ያስደስተኛል፡፡ ብቻ… በአዲስ አድማስ ደስተኛ ነኝ፡፡ ከአዲስ አድማስ ቀጥሎ የማንበብ ጥሜን የሚያረካልኝ የነበረውና እንደ ሃምሌ ፀሐይ ብልጭ ብሎ የጠፋው “አዲስ ነገር” የተባለ ጋዜጣ ነበር፡፡ ጋዜጣውም ተዘጋ፤ አዘጋጆቹም ኮበለሉ፡፡
ለዚህ ነው ከላይ እንደ ልብ መናገርና መፃፍ በማይቻልባት ኢትዮጵያ፤ ትችቱንም፣ ትዝብቱንም፣ ወቅታዊ ትኩሳቶችንም አለዝቦ በማቅረብና ማህበረሰቡን በማስተማር ሲተጋ 15 አመት መጓዙ አድማስን ያስመሰግነዋል የምለው፡ አሁንም በርካታ 15 ዓመቶችን ያክብር፡ አዘጋጆቹንም ፀሐፊዎቹንም ኢትዮጵያንም ፈጣሪ ይባርክ፡፡
(ስማቸው እንዲገለፅ ያልፈለጉ)

     በአብዛኛው ፓርቲዎች ለብቻቸው አየር ላይ የተንጠለጠሉ ናቸው፡፡ ከዜጎች ተጨባጭ ችግር ተነስተው መፍትሄ ለመፈለግ የመጡ አይደሉም፡፡ መሰረት የሌለው አመለካከታቸውን ዜጎች ላይ የሚጭኑ ናቸው፡፡ ለመመረጥ ብቻ ብሎ የፖለቲካ አስተሳሰብን ከህዝብ ቃርሞ መሄድ ትክክል አይደለም፡፡ እኔ ብመረጥ፤ በምን አገባኝ ስሜት መያዛችን፣ ምን ዋጋ አለው በሚል ተስፋ ቆራጭነት ቁጭ ማለታችን እንዲያበቃ የበኩሌን ድርሻ ለመወጣት እፈልጋለሁ፡፡”
(ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሣ፤ ለፓርላማ የግል ዕጩ ተወዳዳሪ በነበሩ ወቅት ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ ከሰጡት ቃለ - ምልልስ የተወሰደ፤
የካቲት 11 ቀን 1992 ዓ.ም)

“አዲስ አበባ መስተዳድር ካለ ቅድመ ዝግጅትና ካለ ውይይት ድንገት በነዋሪው ላይ የሚጭናቸው ህጎችና ሌሎች መሰናክሎች የንግድ እንቅስቃሴውን አዳክመዋል፡፡ መስተዳደሩ በሩን ለውይይት ዘግቶ ለእርምት እድል ነፍጓል፡፡
መስተዳደሩ ራሱን ከነዋሪው አርቋል፡፡ ለማገልገል ሳይሆን በነዋሪው ለመገልገል የፈለገ ይመስላል፡፡”
የቀድሞ የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት (አቶ ክቡር ገና፤ ምክር ቤቱ ባዘጋጀው “ምረጥ አዲስ አበባ” ዘመቻ ላይ  ከተናገሩት የተወሰደ፡፡
አዲስ አድማስ የካቲት 4 ቀን 1992 ዓ.ም)

“ከረጅም አመታት በኋላ ከሚወደኝ የሀገሬ ህዝብ ጋር ለመቀላቀል በመቻሌ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፡፡ ከዚህ የሙዚቃ ትርኢት የሚገኘው ገቢም በድርቅ ለተጎዱ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ የሚውል ይሆናል፡፡
ልዩ ፍቅር ከሚያሳየኝ የኢትዮጵያ ህዝብ ጎን ሆኜ በድርቅ ለተጎዱት ወገኖቼ መርጃ እንዲሆን ማናቸውንም የኪነ ጥበብ ሀብቴን ብሰጥ ለእኔ መታደል ነው፡፡ ዋስትናችንና ኃይላችን የኢትዮጵያ ህዝብ ፍቅር መሆኑን ከልብ አምናለሁ፡፡”
(አስቴር አወቀ፤ ጥር 27 ቀን 1992 ዓ.ም በአገሯ የመጀመሪያ ኮንሰርቷን ስታቀርብ
ለአዲስ አድማስ ከላከችው መልዕክት የተወሰደ)

“አሁን በስራ ላይ ያሉትን ህጎች የሚመለከቱ መሰረታዊ ጉዳዮች ውስጥ ሳንገባ የህጉ አፈፃፀም ሂደት እንዲቀላጠፍ በማድረጉ ስራ ላይ ብዙ መሻሻል የሚገባቸው ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህ ነገሮች ግን አክስዮን ገበያውን ከማቋቋም ሊገቱን አይችሉም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ከዚህ ቀደም በንጉሰ ነገስቱ ዘመን የአክስዮን ገበያ ነበር፡፡ አሁን ያለው የንግድ ህግም ያኔ የነበረው ነው፡፡ በመሆኑም የአክሲዮን ገበያው ሂደት ሙሉ በሙሉ ህጋዊ ነው፡፡ ህጋዊ እስከሆነ ድረስ በመንግስት በኩል ይኖራል ብለን የምንጠብቀው ጣልቃ ገብነት የለም፡፡ መንግስት በአንዳንድ መልኩ የገበያውን ሂደት የሚያቀላጥፉ ሁኔታዎችን ቢያመቻች ደስ ይለናል፡፡ ይህንንም ያደርጋል ብለን እንጠብቃለን፡፡ ከዚህ ውጪ ከመንግስት ጋር የሚያጋጨን ነገር የሚኖር አይመስለኝም፡፡”
(አቶ ኤርሚያስ አመልጋ፤  የአዲስ አድማስ ጋዜጣ የመጀመሪያ እትም ላይ ስለ አክስዮን ገበያ ታህሳስ 29 ቀን 1992 ዓ.ም ከተናገሩት የተወሰደ)

   በሙያዬ የፅንስና የማህፀን ሀኪም ነኝ፡፡ ለመፅሀፍና ለጋዜጣ ልዩ ፍቅር ስላለኝ ላለፉት በርካታ ዓመታት አያሌ መፅሀፍትን እንዲሁም ጋዜጦችን አንብቤአለሁ፡፡ ጋዜጣ ሳነብ አልመርጥም፡፡ በተለይ አዲስ አድማስን አንብቤ ለአዟሪው መልሼ አላውቅም፡፡ መጀመሪያውኑም አዲስ አድማስን ስገዛ ርዕስ እና የፊት ገፅ አልመለከትም፡፡ መግዛት ግዴታዬ እንደሆነ ነው የሚሰማኝ፡፡ ገና ብርቱካናማውን የጋዜጣውን ሎጐ ስመለከት የሆነ ደስ የሚል ነገር ይሰማኛል፡
አዲስ አድማስ ባለፉት 15 ዓመታት እጅግ በርካታ ቁም ነገሮችን፣ አስተማሪና አዝናኝ ጉዳዮችን ሲያስኮመኩመን ኖሯል፡፡ “የእኛ ሰው በአሜሪካ”፣ “እንጨዋወት”---የመሳሰሉት አምዶች አይረሱኝም፡፡ መስራቹን አቶ አሰፋ ጐሳዬን ነፍሱን በገነት ያኑራት እላለሁ፡፡ እሱ ካለፈም በኋላ የጋዜጣው ህልውና እንዲቀጥል ያደረጉትን ቤተሰቦቹን ማመስገን እወዳለሁ፡  ጋዜጣው ከመነሻው ጀምሮ ቢታይ፤ በዘርፉ ጥናትና ምርምር ለሚያደርጉ፣ ወደ ጋዜጣ አሳታሚነት ለሚገቡ፣ በጋዜጠኝነት በተለይ በህትመት ሚዲያ ላይ ትምህርት ለሚከታተሉ ሁሉ አይነተኛ ግብአት ነው ባይ ነኝ፡፡
የእኛም ማህበር (ኢሶግ) በጋዜጣው ላይ “ላንቺና ላንተ” የተሰኘ ቋሚ አምድ አለው፡ በዚህ ዓምድ በሚወጣ ፅሁፍ በርካቶችን ማስተማር ተችሏል፡፡ በአገራችን እንደ ልብ ጋዜጣ በማይገኝበትና እንደ ልብ መፃፍ በማይቻልበት ሁኔታ እንኳን አዲስ አድማስ ሁሉን ተቋቁሞ፣ ሁሉን እንዳመሉ ችሎ መረጃ ያቀብለናል፡፡ በውስጡ ደግሞ እንደ ገጣሚና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን፣ እንደነ አብደላ ዕዝራ፣ እንደነ ኤፍሬም እንዳለ እና መሰል ሳተና ብዕረኞች አሉት፡፡ ቀድሞም በርካታ ብርቱ ብርቱ ፀሐፊዎች ነበሩ፡ ያን ጊዜም አሁንም ጋዜጣውን አነበዋለሁ፡፡ ወንዱ ልጄ ሶፍትዌር ኢንጂነር ቢሆንም የእኔው ዓመል ተጋብቶበት፣ ቅዳሜ ቅዳሜ አዲስ አድማስን ብብቱ ስር ሸጉጦ መምጣት ከጀመረ ረዘም ያለ ጊዜ ሆኖታል፡፡ ታዲያ እሱ ገዛ ብዬ እኔ መግዛቴን አልተውም፡፡ በዚህ ምክንያት ከመጀመሪያው እትም አንስቶ  የአድማስ ኮፒ አለኝ፡፡
አዲስ አድማስ ጋዜጣን ተውሶ የማይመልስልኝ ጠላቴ ነው፡፡ ለስራ ብዙ ጊዜ ወደተለያዩ የአፍሪካና የአውሮፓ አገራት ስሄድ፣ ደንበኛዬ ጋዜጦቹን በጥንቃቄ ያስቀምጥልኛል፡፡ አሁን አሁን ደግሞ ከአገር ስወጣ ዌብሳይቱ ላይ ማንበብ መቻሌ ያስደስተኛል፡፡ ብቻ… በአዲስ አድማስ ደስተኛ ነኝ፡፡ ከአዲስ አድማስ ቀጥሎ የማንበብ ጥሜን የሚያረካልኝ የነበረውና እንደ ሃምሌ ፀሐይ ብልጭ ብሎ የጠፋው “አዲስ ነገር” የተባለ ጋዜጣ ነበር፡፡ ጋዜጣውም ተዘጋ፤ አዘጋጆቹም ኮበለሉ፡፡
ለዚህ ነው ከላይ እንደ ልብ መናገርና መፃፍ በማይቻልባት ኢትዮጵያ፤ ትችቱንም፣ ትዝብቱንም፣ ወቅታዊ ትኩሳቶችንም አለዝቦ በማቅረብና ማህበረሰቡን በማስተማር ሲተጋ 15 አመት መጓዙ አድማስን ያስመሰግነዋል የምለው፡ አሁንም በርካታ 15 ዓመቶችን ያክብር፡ አዘጋጆቹንም ፀሐፊዎቹንም ኢትዮጵያንም ፈጣሪ ይባርክ፡፡
(ስማቸው እንዲገለፅ ያልፈለጉ)

“አዲስ አድማስ መስዋዕትነት የከፈለ ጋዜጣ ነው”
ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም
(የአለማቀፍ የህግ ባለሙያና ፖለቲከኛ)
     አዲስ አድማስ እንደሌሎቹ ጋዜጦች በፕሬሱ እንቅስቃሴ ውስጥ መስዋዕትነት የከፈለ፣ ለእውነትና ለሃቅ የታገለ ጋዜጣ አድርጌ ነው የማየው፡፡ እርግጥ እንደ ሌሎቹ የመዘጋት እድል አልገጠመውም፡፡ እንደሚታወቀው አሁን በእስር ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሣለኝ ያዘጋጃቸው የነበሩ ጋዜጦች በሙሉ ተዘግተዋል፡፡
አዲስ አድማስ ጋዜጣም ምናልባት አስቸጋሪ በሆነ ሁኔታ ውስጥ በቀጭን ክር እየተራመደ ዘልቋል ብዬ አስባለሁ፡፡
ለወደፊትም እንደሚዘልቅ ተስፋ አደርጋለሁ። እስካሁን ድረስ ለመዝለቁም የአዘጋጆቹ ጥበብና ብልህነት ነው እንጂ አፈና ሳይደርስበት ቀርቶ አይደለም፡፡
ለወደፊትም ቢሆን አሁን በያዘው ጥበበኛ አካሄድ ቢቀጥል መልካም ነው፤ ባልሆነ መንገድ ሄዶ መዘጋቱ ለሀገርም ጉዳት ነው፡፡
በተቻለ መጠን የሚዘጋበት ደረጃ እንዳይደርስ በጥንቃቄና በአስተዋይነት ቢጓዝ የበለጠ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡ ይሄኛው ጥሩ መንገድ ይመስለኛል፡፡  


Tuesday, 03 March 2015 14:38

አዲስ አድማስ

የእርግዝናዬን ግዜ ሳስበው እጅግ ይዘገንነኛል፡፡ ልጄ አሁን ሁለተኛ አመቱን ይዞአል፡፡ በባለቤቴም በኩል ይሁን በእኔ በኩል ያሉ ቤተሰቦች አንድ ልጅ መደገም እንዳለበት     ሲነግሩኝ...በሁኔታው ባምንም ...ሳስበው ግን እጅግ ይመረኛል፡፡ ከክብደት ጀምሮ ገጽታዬ በሙሉ እንዲሁም የቆዳ ቀለሜ የእኔ አልነበረም፡፡ ጭራሽ ነበር የተበለሻሸሁት፡፡ እኔነቴ     ተመልሶ ይመጣል የሚል እምነት አልነበረኝም፡፡ አሁን ደግሞ ተመልሼ ባረግዝ ...ልክ አንደበፊቱ ልበላሽ ነው ብዬ በጣም እጨነቃለሁ፡፡ ለመሆኑ ሐኪሞቹ ምን ይላሉ?
ይህን ጥያቄ ያቀረበችው እናት በእድሜዋ ወደ ሀያ አምስት አመት ስትሆን የምትኖረውም በአዲስ አበባ ነው፡፡ ስሙዋ ደግሞ ቆንጂት ብርሀኔ ይባላል፡፡ ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት በዚህ ዙሪያ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
በእርግዝና ወቅት በእያንዳንዱ የእናቶች የሰውነት ክፍል የሚከሰቱ ለውጦች ይኖራሉ፡፡ የሰውነት anatomic የምንለው ለውጥ ብቻ ሳይሆን በውስጣቸው የሚሰሩት ነገሮች በሙሉ የሚለወጡበት ሁኔታ ነው የሚኖረው፡፡ ይህም physiologic changes of pregnancy  ወይንም ከእርግዝናጋር በተያየዘ የሚከሰት ጤናማ የሆነ ለውጥ ማለት ነው፡፡ ይህ ለውጥ እንግዲህ በተለያዩ ሴቶች ላይ የሚኖረው ሁኔታ ይለያይ እንጂ ሁሉም ሴቶች ላይ የማይቀር ለውጥ ነው፡፡ በእያንዳንዱ የሰውነታችን ስርአት ውስጥ የተለያዩ ለውጦች ይካሄዳሉ፡፡ በዚህ ወቅት የሚታዩት አካላዊ ለውጦች በዋናነት ከኪሎ መጨመር ጋር ተያይዘው የሚመጡ ለውጦች ናቸው፡፡  ክብደት ሲጨምር የትኞቹ ክፍሎች ናቸው የሚለወጡት ያልን እንደሆን ሰውነት ውስጥ ከሚከማቸው ፈሳሽ ጀምሮ የሚወፍሩ አካላት ይኖራሉ፡፡ ልጅ እና የእንግዴ ልጅ ሌላውን ክፍል ይይዛል፡፡ የማህፀን እድገት የራሱን የሆነ ክፍል ይይዛል፣ የሽርት ውሀ የራሱ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡ ሌሎች ሰውነት ውስጥ የሚከማቹ  ስብን ጨምሮ የሰውነት ቅርፅ ለውጥ እንዲመጣ የሚያደርጉ ናቸው፡፡ እነኚህ ለውጦች ከምን የተነሳ ነው የሚመጡት ብለን ያየን እንደሆነ በዋናነት በእርግዝና ወቅት የሚቀየሩት ወይንም የእናቶች ሰውነት ውስጥ የሚመነጨው የሆርሞን መጠን ነው፡፡ ይህ የሆርሞን መጠን መጀመሪያ እርግዝናው እንደተከሰተ የዘር ፍሬ ከሚመረትበት ወይንም እንቁላሏ ከወጣችበት ቦታ የሚቀረው ክፍል Corpus luteum  ከምንለው የሚወጣው ነው የመጀመሪያው የሆርሞን ለውጥ፡፡ በመቀጠልም የእንግዴ ልጅ የሚያመነጨው እጅግ በጣም ብዙ የሆነ የሆርሞን መጠን ይኖራል፡፡ እነኚህ ሆርሞኖች በእርግዝና ወቅት ለሚከሰቱ ለውጦች ወይንም physiologic changes of pregnancy
ለምንለው ምንጭ ናቸው፡፡ ሰውነት ውስጥ ፈሳሽ እንዲከማች፣ ስብ እንዲከማች፣ ልጅ እንዲያድግ የጠቀስኳቸው አካላት በሙሉ እድገት እንዲያሳዩ የሚያደርጉት እነኚህ ሆርሞኖች ናቸው፡፡ ስለዚህ የለውጡ ምንጭ ከእርግዝናው ጋር የተያያዘ ነው፡፡
ከክብደት መጨመር በተጨማሪም ቆዳ ላይ የሚከሰቱ ለውጦች ይኖራሉ፡፡ ፊት ላይ፣ በእናቶች ሆድ ላይ፣ በጡት ላይ፣ የቆዳ (መልክ) መቀየር አይነት ሁኔታዎች ሊኖሩ ይችላሉ እና በተለያየ ቦታ በቆዳ ላይ የሚከሰቱ ለውጦች ይኖራሉ፡፡ እነኚህ  በቆዳ ላይ የሚታዩት ለውጦችም ቢሆኑ ከሆርሞኖች የተነሳ የሚመጡ ናቸው፡፡ አንዳንዶቹ እናቶች በሁለቱም ጎናቸው ላይ የመጥቆር አይነት ሁኔታ ይኖራል፡፡ mealasma ወይንም colasma  ወይንም mask of pregnancy የሚሉት ነገር ነው፡፡ ይህም ኢስትሮጂን የሚባለው ሆርሞን ሰውነት ውስጥ ከመብዛቱ የተነሳ ቆዳ ላይ የሚከሰተው ለውጥ ነው ማለት ነው፡፡ የእናቶችን ሆድ ደግሞ ያየን እንደሆነ መሀል ላይ የመጥቆር ሁኔታ ይኖራል፡፡ ይህም ከዛ ጋር የተያያዘ ነው  linea nigra  ነው የምንለው፡፡ ሌሎች ደግሞ ሸንተረሮች ይኖራሉ ሆድ፣ ጡት፣ እግር አካባቢ፣ እነኚህም ምንድነው በዋናነት የእነዚህ ሆርሞኖች መኖርና ሰውነት ክብደት እየጨመረ ሲሄድ ስብ እየተከማቸ ሲሄድ ወይንም ፈሳሽ እየተከማቸ ሲሄድ የመለጠጥና ከስር ያለው ቆዳ ወይም dermis የምንለው ቆዳ መሰነጣጠቅ ከዛም የመዳን ሁኔታዎች ናቸው እነኚህን ለውጦች የሚፈጥሩት ማለት ነው፡፡
አንዳንድ ግዜ ጤናማ ባልሆነ ሁኔታ ፈሳሽ ሰውነት ውስጥ የሚከማችበት ወይንም ከቆዳ ስር የሚከማችበት edema የምንለው ነገር ማለት ነው በብዛት የሚከማችበት ሁኔታ ሊኖር ይችላል፡፡ ይህ ጤነኛ ባልሆነ ሁኔታ ብዙዎቹ እናቶች ከሰማኒያ % በላይ የሚሆኑት ላይ edema የምንለው ነገር ሊኖር ይችላል፡፡ ግን በጣም ከልክ ያለፈ አይደለም፡፡ ከልክ ያለፈ የሚሆነው ጤነኛ ባላሆነ ሁኔታ በአንዳንድ ከእርግዝና ጋር ሊመጡ በሚችሉ ችግሮች ለምሳሌ በደም ግፊት የተነሳ በጣም ብዙ ፈሳሽ ከቆዳ ስር ሊከማች ይችላል፣ ሆዳቸው ላይም ሊከማች ይችላል፣ እግራቸው ላይ ሊሆን ይችላል፣ እጃቸው ሊያብጥ ይችላል፣ ፊታቸው ሊያብጥ ይችላል፡፡ እነኚህ ጤነኛ ባልሆነ ሁኔታ የተከሰቱ ሁኔታዎች ናቸው ፡፡ ግን normally ጤነኛም ሆኖ የአንዱ ክብደት መጨመርና የሰውነት ቅርፅ መለዋወጥ ዋናው ምክንያት የዚህ የፈሳሽ መጠራቀምና የስብ ሰውነት ውስጥ መከማቸት ሁኔታዎች ናቸው፡፡ እንግዲህ እነኚህ ሰውነት ውስጥ ከእንግዴ ልጅ በብዛት በሚመነጩ ቅመሞች ወይንም ሆርሞኖች የተነሳ የሚከሰቱ ናቸው ማለት ነው፡፡
ጥ/ በእርግዝና ግዜ የሚወሰድ ቫይታሚን ለክብደት መጨመርና ለቆዳ መበለሻሸት ምክንያት ይሆናልን?
መ/ እንግዲህ በአጠቃላይ በእርግዝና ወቅት የእናቶችን አመጋገብ ወይንም የምግብ ሁኔታ ያየን እንደሆን በተመጣጠነ ሁኔታ እናቶች ምግብ ማግኘት አለባቸው፡፡ ምግብ ስንል በዋናነት macronutrient  እና micronutrient  ብለን ነው የምንከፍላቸው፡፡ macronutrient
በዋናነት የምንመገባቸው ለሰውነት ግንባታና ለሀይል የሚያገለግሉ ምግቦች ናቸው፡፡ ይህ እንግዲህ ካርቦሀይድሬት፣ ፋት እና ፕሮቲን እያልን የምንጠራቸው ዋናዎቹ ምግቦች ናቸው ማለት ነው፡፡ ከዛ በተጨማሪ  micronutrient  የምንላቸው ቫይታሚንና ሚንራሎች ለሰውነት አስፈላጊ የሆኑ ንጥረ ነገሮች ናቸው፡፡ እነኚህ በዋናነት ጉልበት የመስጠትና ሰውነት መገንባት ቀጥተኛ የሆነ ተሳትፎ ባይኖራቸውም ሰውነት ውስጥ የሚካሄዱት የተለያዩ አይነት ሂደቶች በእነኚህ ሚንራሎችና ቫይታሚኖች በመታገዝ ነው፡፡ እነኚህ ለእናቲቱ ብቻ ሳይሆን እያደገ ላለው ፅንስ የሁለቱም የmacronutrient  እና  micronutrient  ምግቦች ምንጭ እናቲቱ ጋር ሲኖር ነው ወደ ልጁ ሊሄድ የሚችለው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የተመጣጠነ ምግብ የሚመገቡ እናቶች እነኚህ አስፈላጊ የሆኑት ንጥረ ነገሮች ከምግብ ውስጥ በቀን የሚያስፈልገውን ያክል ያገኛሉ ተብሎ ይታሰባል፡፡ ግን በቀን የሚያስፈልገውን ቫይታሚንና ፕሮቲን የምንላቸውን ንጥረ ነገሮች ከምግብ ውስጥ ብቻ የማይገኝባቸው ወይንም በቂ የማይሆኑበት ሁኔታዎች አሉ፡፡ አንዱ ምንድነው ምግባችን እነዛን ሚንራሎች ወይንም ቫይታሚኖች በበቂ ሁኔታ ያልያዘ ሊሆን ይችላል፡፡ ቢይዝም እንኳን በእርግዝና ወቅት የበለጠ  እነዚህን ቫይታሚንና ሚንራል አይረንና ፎሊክ የምንላቸው ነገሮች አስፈላጊ ይሆናሉ፡፡ ስለዚህ እነኚህ አስፈላጊ ንጥረ ነገሮች ናቸው እንጂ ከሚፈጠሩት የሰውነት ለውጦች ጋር በምንም መንገድ የማይገናኙ ናቸው፡፡ ቫይታሚኖቹና ሚንራሎቹ በእርግዝና ወቅት አስፈላጊ የሆኑ ንጥረ ነገሮች ናቸው፡፡ አንዲት እናት በትክክል ማግኘት የሚገባት ንጥረነገር ነው፡፡
    በእርግዝና ወቅት ያለው የአመጋገብ ሁኔታን በተመለከተ አንዲት እናት እርጉዝ ካልሆነችው እናት የበለጠ ምግብ መመገብ አለባት፡፡ በእርግዝና ወቅት የሰውነቷ የካሎሪ ፍላጎት ይጨምራል፡፡ ይህ የሚሆነው ለምንድነው? አንዱ ለሰውነት ግንባታ ነው፣ ሁለተኛ ፅንሱ ጤናማ ሆኖ ለማደግ የሚያስፈልጉ ንጥረ ነገሮች የሚገኙት ከእናቲቱ በመሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ metabolic rate  የምንለው ነገር በእግዝና ወቅት ይጨምራል፡፡ ስለዚህ በእርግዝና ወቅት አንዲት እናት ቀድሞ ከምትመገበው የበለጠ መመገብ አለባት፡፡ የሰውነቷም ፍላጎት እያደገ ያለውም ፅንስ ይህንን ነው የሚፈልገው፡፡ ስለዚህ በምግብ ደረጃ ያየን እንደሆነ አንዲት እናት በእርግዝናዋ ወቅት ቢያንስ አንድ ተጨማሪ ምግብ መመገብ አለባት ተብሎ ነው የሚታሰበው፡፡ ይህ እንግዲህ ምንድነው አንዲት እናት በእርግዝናዋ ወቅት ወደ 300/ ኪሎ ካሎሪ ተጨማሪ ምግብ ትፈልጋለች ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የምግብ ፍላጎት መጨመሩ የመጀመሪያዎቹን ሶስት ወራት ይሄ የማቅለሽለሹ፣ የማስመለሱና ምግብ የማስጠላቱ ነገር ከመኖሩ በስተቀር በተለይ ሁለተኛው ግማሽ የእርግዝና ወቅት እነኝህ ፍላጎቶች እየጨመሩ የሚሄዱበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ስለዚህ ይሄ ጤናማ የሆነው በእርግዝና ወቅት የሚኖረው የምግብም ሆነ የካሎሪ ወይንም የጉልበት መጠን ፍላጎት የሚጨምርበት ወቅት ነው ማለት ነው፡፡ ይህ በእርግዝና ወቅት ሲሆን የምታጠባ እናት ደግሞ የምትፈልገው የምግብ ወይንም የጉልበት ወይንም የካሎሪ መጠን ከእርጉዝ ሴት በተሻለ ነው፡፡ ይህም አንዲት የምታጠባ እናት ወደ 500/ ኪሎ ካሎሪ ተጨማሪ ምግብ የምትፈለፍግበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ስለዚህ ይህ በምግብ ሲሰላ ድሮ ከምትመገበው ሁለት ተጨማሪ ምግብ መመገብ አለባት፡፡ ስለዚህ ይሄ ለውጥ ከቫይታሚኖቹ የተነሳ አይደለም፡፡ በእርግጥ ቫይታሚኖች ሰውነታችን ውስጥ እያንዳንዱን metabolism የምንለውን ነገር የማመቻቸት ወይም facilitate የማድረግ ጠቀሜታ ነው ያላቸው፡፡
እያንዳንዱ ሰው የሚያመጣው ለውጥ ሊለያይ ይችላል፡፡ ግን በሰውነት ውስጥ የሚፈጠሩት ሆርሞኖች ለእነኚህ ልዩነቶች ወይም ለእነኚህ ለውጦች ዋናዎቹ ምክንያቶች ናቸው፡፡ ለምን አንዳንድ እርጉዝ ሴቶች ይህን ቀለም ያዙ? ለምን ሌሎቹ ይህን አልያዙም? ለሚለው ይህ በተለያዩ ምክንያቶች ሊሆን ይችላል፡፡ ለምሳሌ በአንፃራዊነት የእነኚህ ሆርሞኖች መጠን ምን ያክል ነው? በተጓዳኝ በእርግዝና ወቅት የሚመነጩ ሌሎች ነገሮች ይኖራሉ ወይ? አንዲት እናት ቆዳዋ ለፀሀይ ብርሀን ያለው sensitivity  ምን ያህል ነው? የሚሉት ነገሮች ይኖራሉ፡፡ melanosite  የምንላቸው ወይም የቆዳ ቀለምን ሊያመነጩ የሚችሉ ህዋሶች ምላሻቸው ምንድነው? ይህ በተለያዩ ምክንያቶች ሊለያይ ይችላል፡፡ ለምሳሌ እንዳንድ እናቶች ፊታቸው ላይ የመጥቆር ሁኔታ ይኖራል አንዳንዶቹ ምንም አይነት ለውጥ አይኖራቸውም፡፡ በእርግዝና ብቻም ሳይሆን አንዳንድ የወሊድ መቆጣጠሪያ መድኒት የሚወስዱ እናቶች ፊታቸው ላይ የመጥቆር ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል ፡፡ አንዳንዶቹ ላይ ምንም ላይፈጠር ይችላል፡፡ ይህ የሚያሳየው በዋናነት ሆርሞኖቹ ተፅእኖ ቢኖራቸውም ሆርሞኖቹ ብቻቸውን ሳይሆን ሌሎች ተጓዳኝ ወይም ያንን ነገር ሊገልፁ የሚችሉ ከ genetic ከመሳሰሉት environmental factors
ሊሆን ይችላል፡፡ የለውጦቹ ዋና ምንጮች ሆርሞኖቹ ቢሆኑም ለውጡ ግን እንደየ ሰዉ ሊለያይ ይችላል፡፡




በሀገራችን ያለው የሙያ ማህበራት ቁጥር ከጊዜ ወደ ግዜ እየጨመረ መጥቷል፡፡ እነዚህ የሙያ ማህበራት ከአባላቱ ባሻገር ለሙያ ዘርፉ ብሎም ለሀገር እድገት የሚጫወቱት ሚና እጅግ ከፍተኛ ነው፡፡ በህክምናው ዘርፍ ከተቋቋሙ የሙያ ማህበራት መካከል የኢትዮፕያ ፅንስና ማህፀን ሀኪሞች ማህበር አንዱ ነው፡፡ ማህበሩ ባለፈው ሳምንት ሀያ ሶስተኛ መደበኛ ጉባኤውን ደረጃውን የጠበቀ የማህፀንና ፅንስ ህክምና ስልጠናን ማሳደግ በሚል መሪ ቃል በጅማ ዩንቨርሲቲ አካሂዷል፡፡
ዶክተር ደረጄ ንጉሴ የማህበሩ ፕሬዝዳንት ናቸው። የዚህ አመት ጉባኤ ደረጃውን የጠበቀ የማህፀንና ፅንስ ህክምና ስልጠናን ማሳደግ የሚለው መሪ ቃል የተመረጠበትን ምክንያት ሲናገሩ፡-
“የዚህን አመት ጉባኤ ደረጃውን የጠበቀ የማህፀንና ፅንስ ህክምና ስልጠናን ማሳደግ በሚል አካሂደናል። ይህን መሪ ቃል የመረጥንበት ዋናው ምክንያት የያዝነው አመትየምእተ አመቱ     የልማትግቦች ማብቂያ እንደመሆኑ በጤናውም ዘርፍ እየተሰራ ያለውን ስራ ለማስቀጠል የባለሙያውን አቅም መገንባት አስፈላጊ ነው ብለን ስለምናምን ነው፡፡
የምእተአመቱ ግብ ከተጠናቀቀ በኋላ የሚኖረው የጤና አገልግሎት በተሳካ ሁኔታ እንዲካሄድ ደረጃቸውን     የጠበቁ ባለሙያዎች ማፍራት አስፈላጊ ስለሆነ ከዚህ ጋር በተያያዘ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ምክክር ለማድረግ ይህን መሪ ቃል መርጠን የዚህን አመት ስብሰባ አካሂደናል ነው፡፡
ለሶስት ቀናት በተካሄደው ጉባኤ ላይ አስራ ሁለት ያህል ጥናታዊ ፀሁፎች የቀረቡ ሲሆን ፅሁፎቹ በተለያዩ የስነተዋልዶ ጤና ችግሮች እንዲሁም ከማህፀንና ፅንስ ጋር ተያያዥ በሆኑ ጉዳዮች ላይ በገራችን ያለውን ሁኔታ መሰረት በማድረግ የተሰሩ ናቸው፡፡ እያንዳንዱ ፅሁፎች ከቀረቡ በኋላም አባላቱና ለሌሎች የስብሰባው ተሳታፊዎች ተወያይተውበታል፡፡   
በጉባኤው ላይ የክብር እንግዳ ነበሩት በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የሰው ሀብት ልማት አስተዳደር ዳይሪክተር የሆኑት ዶክተር ወንድምአገኝ እምቢ አለ፣፣ ‘’Ministry of  Health’s plans and issues in light of scaling up quality Obstetrics and Gynecology training’’ በሚል እርእስ ደረጃውን የጠበቀ የማህፀንና ፅንስ ህክምና ስልጠናን ለማሳደግ በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በኩል የተያዘውን እቅድ ለተሰብሳቢዎች አቅርበዋል፡፡
ማህበሩ ከጤና ጥበቃ ጋር በመተባበር በእናቶች ጤና ላይ በተለይ በእርግዝናና በወሊድ ግዜ የሚከሰትን የእናቶች ሞት ለመቀነስ በትብብር እየሰራ እንደሆነና እንዲህ አይነት የሙያ ማህበራት በጤናው ዘርፍ የሚጫወቱት ሚና እጅግ ከፍተኛ በመሆኑ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከማህበሩ ጋር ያለውን ግንኙነት ከምንግዜውም በላይ አጠንክሮ እንደሚሰራ ዶ/ር ወንድማገኝ ገልፀዋል። ከጽንስና ማህጠን ሐኪሞች ማህር ጋር ባለው የስራ ግንኙነትም የሚከተሰለውን ተናግረዋል።
“የኢትዮጵያ ፅንስና ማህፀን ሀኪሞች ማህበር ከተመሰረተበት ከፈረንጆቹ 1992/ አመተ ምህረት ጀምሮ የእናቶችና ህፃናትን ሞት ለመቀነስ እየሰራ ያለ ማህበር ነው፡፡ ከጤና ጥበቃም ጋር በመተባበር የሚሰራቸው የተለያዩ ትልልቅ ፕሮጀክቶች አሉ፡፡ በቅርቡም የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በጤናው ዘርፍ ከእርግዝናና ከወሊድ ጋር በተያያዘ ለእናቶች ሞት ትልቅ ምክንያት የሆነውን የክህሎት ችግር ለመቅረፍ የድንገተኛ የፅንስ ህክምና ባለሙያዎችን እያሰለጠንን ነው፡፡ ይህን ስልጠና ከጀመርን አምስት አመት ቢሆንም በበቂ ሁኔታ እየተተገበረ አይደለም። ስለዚህ ይህን ስልጠና በሀገር አቀፍ ደረጃ ተደራሽ ለማድረግ ከእነዚህ ባለሙያዎች ጋር በትትብር እየሰራን ነው፡፡”



የያዝነው የፈረንጆቹ 2015 የምእተ አመቱ የልማት ግቦች ወይም millennium development goals ማብቂያ አመት እንደ መሆኑ በጤናው ዘርፍ እስከአሁን የታዩት እመርታዎች ምን ይመስላሉ ተብሎ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ዶ/ር ወንድማገኝ ምላሽ ሲሰጡም፡-
የምእተ አመቱን የልማት ግቦችን በማሳካት እረገድ የጤናው ዘርፍ ትልቅ እመርታ አሳይቷል ማለት ያቻላል። የዛሬ ሁለት አመት የህፃናትን ሞት በመቀነስ ኢትዮጵያ በአለም አቀፍ ደረጃ እውቅና ተሰጥቷታል፡፡ የእናቶችን ሞት በተመለከተም ለውጡ በጣም ትልቅ ነው፡፡ ሆኖም ግን አሁንም እየተሰሩ ያሉ ስራዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ ለእናቶች ሞት ትልቁ ምክንያት የሆነው የግንዛቤ እጥረት ነው፡፡ ይህንን በተመለከተ የጤና አገልግሎቱ ተጠናክሮ እያንዳንዷ እናት አገልግሎቱን ፈላጊ እንድትሆንና በጤና ተቋም እንድትወልድ ማድረግ በጤና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎች እየተሰራ ያለ ስራ ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ከዛሬ አምስት አመት በፊት 6% የነበረው በጤና ተቋም የሚወልዱ እናቶች ቁጥር አሁን ወደ 20% አድጓል፡፡ ስለዚህ በበቂ ሁኔታም ባይሆን የምእተ አመቱን ግብ ማሳካት ችለናል።” ብለዋል፡፡ በጉባኤው ከነበሩ ክንውኖች መካከል የደም ልገሳ ፕሮግራም አንዱ ነበር፡፡ የስብሰባው ተሳታፊዎች በበጎፈቃደኝነት ደም ለግሰዋል፡፡ የደም ልገሳ ፕሮግራሙ ባለሙያዎቹ ከህክምና ስራቸው በተጓዳኝ ለህብረተሱ አለኝታ መሆናቸውን ለማሳየት ታስቦ የተዘጋጀ እንደሆነ የማህበሩ ፕሬዝዳንት ዶክተር ደረጀ ይገልፃሉ፡፡
“ይህ የደም ልገሳ ፕሮግራም የተዘጋጀው ባለሙያዎች ከህክምና ስራው ባሻግር ለህብረተሰቡ አለኝታ መሆናቸውን ለማሳየት ሲባል ነው፡፡ ህብረተሰቡም ይህንን በማየት የደምን አስፈላጊነት ተረድቶ ህይወትን ለማዳን ሲባል ደም መስጠት እንዳለበት ለማስተማር ታስቦ የተዘጋጀ ነው፡፡”
ዶክተር ሙኸዲን አብዶ የማህፀንና ፅንስ ሀክምና እስፔሻሊስትና የማህበሩ የቦርድ አባል ናቸው፡፡ የህክምና ባለሙያዎች በእንዲህ አይነቱ የደም ልገሳ ፕሮችራሞች ላይ መሳተፋቸው ለሌላው የህብረተሰብ ክፍል የሚሰጠው የተለየ ትርጉም እንዳለ ይገልፃሉ?፡፡
“ባለሙያ እንደዚህ አይነት የደም ልገሳ ፕሮግራም ላይ መሳተፍ ተገቢ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ምክንያቱም ከእኛ ከባለሙያዎች የበለጠ የደም እጦት የሚያደርሰውን ጉዳት የሚያውቅ የለም፡፡ ለእናቶች ሞት ምክንያት ከሆኑት ነገሮች መካከል የደም መፈሰስ ትልቁን ድርሻ ይይዛል፡፡ ስለዚህ በተለይ እንደኛ የማህፀንና ፅንስ ህክምና ላይ ያሉ ባለሙያዎች በደም መፍሰስ ምክንያት የሚሞቱ እናቶችን ቁጥር ለመቀነስ ደም መለገስ ከምንም በላይ አስደሳችና ሊዘወተር የሚገባው ነው፡፡”
በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል የማህፀንና ፅንስ ሀኪም የሆኑት ዶክተር ባላካቸው ንጋቱም የዶክተር ሙኸዲንን ሀሳብ ይጋራሉ፡፡“እንደሚታወቀው የማህፀንና ፅንስ ሀኪሞች በአብዛኛው ከደም ጋር የተያያዘ ስራ ላይ ነው ያለነው። እናቶች በተለያየ ምክንያት ደም ይፈሳቸዋል ለዚህም ከየደም ባንኩ ብዙ ደም እንጠይቃለን፡፡ የምንጠይቀውን ደም እራሳችንም በተወሰነ መልኩ አስተዋፅኦ ማድረግ እንዳለብን ሁልግዜም አስብ ነበር፡፡ ስለዚህ ዛሬ እድሉን አግኝቼ ደም በመስጠቴ እጅግ ደስተኛ ነኝ፡፡ ከምንሰጠው የህክምና አገልግሎች በተጨማሪም ማህበራዊ ግዴታችን ነው ብዬ አስባለሁ ተምሳሌትነቱም ለማህበራችን አባላት ብቻ ሳይሆን ሌላውም የህብረተሰብ ክፍል ነው፡፡”