Administrator

Administrator

         ብሩክ ኢትዮጵያ በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል በሃላባ ልዩ ወረዳ በ1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባቸውን የሃላባ ቁሊቶ ከተማና አካባቢው የጋማ እንስሳት ደህንነት ጥበቃና ስልጠና ማዕከልና የጋማ እንስሳት ውሃ ማጠጫ ገንዳዎችን አስመረቀ፡፡
በርካታ የጋማ እንስሳት በሚስተናገዱበት በሃላባ ከተማ ዋና የገበያ ስፍራ ላይ የተገነባው ማዕከል፤ ከእንስሳት እንክብካቤ ጋር የተያያዘ ስልጠና ከመስጠት ባለፈ፣ እንስሳቱ ተገቢውን መኖና ውሃ እያገኙ በምቹ ሁኔታ የሚቆዩበት ሲሆን እንስሳቱን ከስርቆት በመከላከልና ከሚደርስባቸው ስቃይ በማዳን ረገድ ጠቀሜታው የጎላ እንደሆነ ተነግሯል፡፡
በልዩ ወረዳው ለሚገኙ የመንግስት ክሊኒኮችና የእንስሳት ህክምና መስጫ ማእከላት የአቅም ግንባታ ድጋፎችን የሚያደርገው ብሩክ ኢትዮጵያ የአካባቢውን የጋማ ከብቶች የጤና እንክብካቤ ለማሳደግ ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በቁሳቁስ፣ በመድሃኒትና በህክምና መሳሪያዎች ማሟላቱን የድርጅቱ ሃላፊ አቶ ጥበቡ ደበበ ተናግረዋል፡፡
ህክምናውን ለማሻሻል የእንስሳት ሀኪሞችንና የህብረተሰብ የእንስሳት ጤና ሰራተኞችን አቅም በስልጠና በዘላቂነት ከማጎልበትና ለህብረተሰቡ ግንዛቤ በማስጨበጥ የተሻሉ የጋማ ከብት አያያዝ ልማዶችን ከማዳበር ባሻገር፣ በልዩ ወረዳዋ በሚገኙ ክሊኒኮችና የጤና ኬላዎች አስተማማኝ የጋማ እንስሳት መድሃኒት አቅርቦት እንዲኖር ለማስቻል በ370 ሺህ ብር የመድሃኒትና የክትባት ተዘዋዋሪ በጀት አሰራር ቀይሶ እንደሚሰራም ገልጸዋል፡፡
በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የሃላባ ልዩ ወረዳ የመንግስት ተወካይ፤ አቶ መሐመድ ኑር ሳኒያ በወረዳው ያሉት ከ39 ሺህ በላይ የጋማ ከብቶች ለህብረተሰቡ ከፍተኛ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ ጠቁመው፣ ይሄም ሆኖ ግን የጋማ እንስሳትን ጤንነትና ደህንነት ከማስጠበቅ አንጻር ችግሮች እንደነበሩ ገልጸዋል፡፡ “ብሩክ ኢትዮጵያ” በልዩ ወረዳው እያከናወናቸው የሚገኙ ስራዎች የአካባቢውን የጋማ ከብቶች ደህንነት ለማስጠበቅ ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርጉም ተናግረዋል፡፡
“ብሩክ ኢትዮጵያ” የተቀናጀ የጋማ ከብት ደህንነት ትብብር ፕሮግራም በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል ጉራጌ፣ ሃዲያ፣ ወላይታና ጋሞ ጎፋ ዞኖች እንዲሁም ከአማራ መልሶ ማቋቋምና ልማት ድርጅት ጋር በመተባበር በሰሜን ጎንደር ዞን ፕሮጀክቶችን ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡


ባለፉት 15 ዓመታት በዓለም የማራቶን ውድድሮች መድረክ  የምስራቅ አፍሪካ አገራት ከፍተኛ የበላይነት ሲያሳዩ ቆይተዋል፡፡ ከ5 ዓመታት ወዲህ ግን በተለይ የኬንያ ወንድ አትሌቶች ከኢትዮጵያውያኑ ከፍተኛ ብልጫ እያገኙ ናቸው፡፡ በአንፃሩ በማራቶን ከኬንያ አቻዎቻቸው በመፎካከር እየተሳካላቸው  የሚገኙት የኢትዮጵያ ሴት አትሌቶች ሆነዋል፡፡ የዓለም ማራቶን ሜጀር ሲሬዬስ አካል በሆኑ ትልልቅ ማራቶኖችና ሌሎች ውድድሮች እንዲሁም፤ በዓለም የማራቶን ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ ሰንጠረዦች በአጠቃላይ ኬንያውያን በሁለቱም ፆታዎች  በውድድር ዘመኑ ከኢትዮጵያውያን የተሻለ ስኬት ነበራቸው፡፡ በተለይ በወንዶች ምድብ በማራቶን ውጤት የኬንያ አትሌቶች ከኢትዮጵያውያን ተቀናቃኞቻቸው ጋር ያላቸው ልዩነት እየሰፋ መጥቷል፡፡
በተያያዘ ነገ የኒውዮርክ ማራቶን በታሪኩ ለ44ኛ ጊዜ ሲደረግ በሁለቱም ፆታዎች ፉክክሩ በምስራቅ አፍሪካ አገራት አትሌቶች እንደሚወሰን ቢጠበቅም የተሻለውን ግምት ኬንያውያን ወስደዋል፡፡ የኒውዮርክ ማራቶን እስከ 51 ሺ ተሳታፊዎች ፤ እስከ 2 ሚሊዮን ተመልካቾች የሚያጅቡት ትልቅ ውድድር ነው፡፡ ከኢትዮጵያውያን ማራቶኒስቶች መካከል በኒውዮርክ ማራቶን በወንዶች ምድብ በ2010 እኤአ ላይ አሸናፊ የነበረው ገብሬ ገብረማርያም እና በሴቶች ምድብ ደግሞ ለሁለት ጊዜያት ያሸነፈችው ፍሬህይወት ዳዶ ይሳተፋሉ፡፡ በሌላ በኩል የ2013/14 የዓለም 6 ማራቶኖች ሜጀር ሲሪዬስ “ማራቶን ሊግ” የደረጃ ሰንጠረዥ በመሪነት አጠናቅው 1 ሚሊዮን ዶላር ሽልማትንየ ሚካፈሉት አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች ኬንያውያን ናቸው፡፡ የማራቶን ሊጉ ነገ በሚካሄደው የኒውዮርክ ማራቶን ሲያበቃ ሲሆን በተለይ በወንዶች ምድብ አሸናፊውን የሚለይ ነጥብ ሊመዘገብበት ይችላል፡፡ የዓለም ማራቶን ሪከርድ ዘንድሮ ያስመዘገበው ኬንያዊ ዴኒስ ኪሜቶ የማራቶን ሊጉን እየመራ ቢሆንም ፤ የማራቶን ሪከርዱ የተሰበረበት የተሰበረበት ዊልሰን ኪፕሳንግ በነገው የኒውዮርክ ማራቶንን ካሸነፈ የማራቶን ሊጉን በአንደኛነት በመጨረስ 500ሺ ዶላር የመሸለም እድል ይኖረዋል፡፡
ለነገሩ ከወር በፊት ከተካሄደው የቺካጎ ማራቶን በኋላ በ2013/14 የውድድር ዘመን የማራቶን ሊግ ፉክክር  በሁለቱም ፆታዎች ኬንያውያን ማሸነፋቸው የተረጋገጠ ይመስላል፡፡  በተለይ በሴቶች ምድብ የቺካጎ ማራቶንን ያሸነፈችው ኬንያዊቷ ሪታ ጄፕቶ በውድድር ዘመኑ የማራቶን ሊግ አሸናፊነቷን ያረጋገጠችው ከኒውዮርክ ማራቶን በፊት ነው፡፡  ኬንያዊቷ ሪታ ጄፕቶ በሴቶች ምድብ የማራቶን ሊጉን 100 ነጥብ በመምራቷ የ500ሺ ዶላር ሽልማት ትወስዳለች፡፡
በ2014 የዓለም ማራቶኖች በወንዶች ኬንያ፣ በሴቶች ኢትዮጵያ
በ2014 እኤአ ላይ ኢትዮጵያውያን ሴት አትሌቶች በርካታ የማራቶን ውድድሮችን አሸንፈዋል፡፡  ትልቁ ድል የተመዘገበው የዓመቱን ማራቶን ፈጣን ሰዓት ባስመዘገበችው እና የበርሊን ማራቶንንን ባሸነፈችው አትሌት ትርፌ ፀጋዬ ነው፡፡ የትርፌ ፀጋዬ የዓመቱ ፈጣን የማራቶን ሰዓት 2 ሰዓት ከ20 ደቂቃዎች ከ18 ሰከንዶች ሲሆን በበርሊን ማራቶን አሸናፊነቷ ያስመዘገበችው ነው፡፡ ይሁንና በለንደን ፤ በቺካጎ፤ በቦስተን እና በፓሪስ ማራቶኖች የኬንያ ሴት አትሌቶች የበላይነት ማሳየታቸው በማራቶን ሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ከፍ አድርጓቸዋል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ  ሴት አትሌቶች በማራቶን ሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ በየጣልቃው ኬንያውያንን ለመፎካከር የበቁት በማራቶን ሊግ ውድድሮች ባይሆንም በሌሎች በርካታ ማራቶኖች ከወንዶቹ ኢትዮጵያውያን በተሻለ ብዛት አሸፊና በመሆናቸው ነው፡፡  ኢትዮጵያውያኑ  ሴት አትሌቶች በበርሊን ማራቶን ተከታትለው መግባታቸው አንፀባራቂው ስኬተ ነው፡፡ በሌሎች በዓለም ዙርያ በተካሄዱ ውድድሮችም በተመሳሳይ ሁኔታ ብልጫ ለማሳየት አሸንፈዋል፡፡ ከእነሱም መካከል ማሬ ዲባባ የሻይናሜን ማራቶንን በቻይና፤ ትርፌ ፀጋዬ በየነ የቶኪዮ ማራቶንን በጃፓን ፤ ፍሬህይወት ዳዶ  የፕራግ ማራቶንን፤ ትእግስት ቱፋ የኦታዋ ማራቶንን በካናዳ ፤ ሙሉ ሰበቃ የዱባይ እና የዳጋኖ ማራቶኖችን በማከለኛው ምስራቅ እና በቻይና፤ አበበች አፈወርቅ የሂውስተን ማራቶንን በአሜሪካ፤ ማርታ ለማ  የሙምባይ ማራቶንን በህንድ፤ መስታወት ቱፋ የዶንግ ያንግ ማራቶንን በደቡብ ኮርያ እንዲሁም አማኔ ጎበና የሎስ አንጀለስ ማራቶንን በአሜሪካ ማሸነፋቸው ከሴት ማራቶኒስቶች አስደናቂ ስኬት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያዊ ወንድ ማራቶኒስቶች በአንፃሩ በ2014 ብቻ ሳይሆን ባለፉት አምስት አመታት ውጤታቸው ከኬንያውያኑ በጣም አየራቀ እና እየወረደ መጥቷል፡፡ በዓመቱ ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ ኢትዮጵያ ወንድ ማራቶኒስቶች በበላይነት በቅርብ ጊዜ የሚመለስ አይሆንም፡፡ እነዚህን ደረጃዎች የያዟቸው ኬንያውያን ናቸው፡፡ ከ6 የማራቶን ሊግ ውድድሮች አንዱንም ኢትዮጵያዊ አትሌት ሊያሸንፍ ያልቻለበት የውድድር ዘመንም ነበር፡፡
በኦል አትሌቲክስ ድረገፅ የ2014 ከፍተኛ ውጤት በማስላት በወጣ የደረጃ ሰንጠረዥ መሰረት በወንዶች ማራቶን አንደኛ ደረጃ የያዘችው በ3994 ነጥብ ኬንያ ናት፡፡ ኢትዮጵያ በ3901 ነጥብ፤ ጃፓን በ3618 ነጥብ ፖላንድ በ3523 ነጥብ እንዲሁም ኤርትራ በ3509 ነጥብ እስከ አምስት ያለውን ደረጃ አከታትለው ይወስዳሉ፡፡ በሴቶችም ኬንያ በ934 ነጥብ መሪ ናት፡፡ ኢትዮጵያ በ3910 ነጥብ ትከተላታለች፡፡ ጃፓን በ3629 አሜሪካ በ3576 እንዲሁም ጣሊያን በ3503 እስከ አምስት ያለውን ደረጃ ይወስዳሉ፡፡ በዚሁ ድረገፅ በቀረቡ አሃዛዊ መረጃዎች ለመንገዘብ የሚቻለው በዓመቱ ምርጥ የማራቶን ብቃት እና ፈጣን ሰዓት ሁለቱንም የመሪነት ስፍራዎች የተቆናጠጡት ኬንያውያን ናቸው፡፡ ሪታ ጄፔቶ እና ዴኒስ ኪሜቶ 1340 እና 1456 ነጥብ እንደየቅደም ተከተላቸው በማስመዝገብ ነው፡፡ በዚሁ ደረጃ በሴቶች ምድብ እስከ 20ኛ ባለው እርከን ኢትዮጵያውያን ቢያንስ ከስምንት በላይ ናቸው፡፡ በወንዶች ግን ያሉት ከ3 አይበልጡም፡፡
የኬንያ ወንድ አትሌቶች የበላይነት በርግጥም ከፓሪስ፤ ከበርሊን  እና ከቦስተን ማራቶኖች በኋላ ከወር በፊት በተደረገው የቺካጎ ማራቶንም በግልፅ ታይቷል፡፡  የቺካጎ ማራቶንን ያሸነፈው በረጅም ርቀት የትራክ ውድድሮች የቀነኒሳ ተፎካካሪ ሆኖ የቆየው ኬንያዊ ኤሊውድ ኪፕቾጌ ነበር፡፡ ኪፕቾጌ ወደ ማራቶን ፊቱን ካዞረ ወዲህ አራት ጊዜ ተወዳድሮ ለ3 ጊዜ በአንደኛነት መጨረሱ አስደንቋል፡፡ በቺካጎ ማራቶን ሲያሸንፍ ያስመዘገበው ሰዓት ደግሞ  2 ሰዓት ከ04 ደቂቃዎች ከ15 ሰከንዶች ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ሳሚ ኪርሞ በ2 ሰዓት 04 ከ18 እንዲሁም በሶስተኛ ደረጃ ዲክሰን ቺምቦ በ2 ሰዓት 04 25 በሆነ ጊዜ የጨረሱ ሌሎቹ የኬንያ አትሌቶች ናቸው፡፡ በወንዶች እስከ 10ኛ ባለው ደረጃ አንድ ኢትዮጵያዊ ብቻ ሲመዘገብ 7 ኬንያውያን ነበሩ፡፡ ያ ኢትዮጵያዊ ደግሞ ሁለተኛ የማራቶን ውድድር ለመሮጥ የበቃው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ በቺካጎ ማራቶን ላይ ቀነኒሳ በ4ኛ ደረጃ ውድድሩን ያጠናቀቀ ሲሆን ሰዓቱ 2 ሰዓት ከ05 ደቂቃዎች ከ51 ሰከንዶች ነው፡፡ ቀነኒሳ በውድድሩ 2 ሰዓት ከ5 ደቂቃዎችን ርቀቱን ለመሸፈን በቻለበት ብቃት እንደረካ በወቅቱ ተናግሮ ነበር፡፡  የግሉን ፈጣን ሰዓት ለማስመዝገብ ከጅምሩ ማቀዱ አልቀረም ነበር፡፡ እንደውም ሌትስራን ድረገፅ እንደዘገበው ያቀደው ጊዜ  2 ሰዓት ከ3 ደቂቃዎች ከ13 ሰከንዶች ነው፡፡ በእርግጥ ከቀነኒሳ በፊት የነበሩት ታላቅ የረጅም ርቀት ሯጮች በመጀመርያ ሁለት የማራቶን ውድድራቸው ፖል ቴርጋት በ2 ሰዓት ከ08 ደቂቃዎች ሃይሌ ደግሞ 2 ሰዓት ከ06 ደቂቃዎች ነበር ያስመዘገቡት፡፡ እንደ ጆስ ሄርማንስ አስተያየት ቀነኒሳ በቀለ በቺካጎ ማራቶን በውድድሩ አይነት ለሁለተኛ ጊዜ የተሳተፈው ልምድ ለማዳበር እና ማራቶንን ለመማር ነው፡፡
የቺካጎ ማራቶን ከመካሄዱ በፊት ማራቶንን በ2 ሰዓት እና ከ2 ሰዓት በታች ይገባል ተብሎ የተጠየቀው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ የሰው ልጅ ያን ያህል መፍጠን አይችልም በሚል መልስ ሰጥቷል፡፡‹‹ ምናልባት ወደፊት ማን ያውቃል ሳይንቲስቶች ልዩ የሰው ልጆች ካልፈጠሩ በቀር…›› ነው ያለው ቀነኒሳ፡፡ የአትሌቱ ማናጀር የሆኑት የ64 ዓመቱ ሆላንዳዊ ጆስ ሄርማንስ ግን በተቃራኒው በሰጡት አስተያየት‹‹ ቀስ በቀስ ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች እንደሚገባ አስባለሁ… ምናልባትም ከ20 ዓመታት በኋላ›› ብለዋል፡፡ ለጆስ ሄርማንስ ለዚህ ብቃት ዋና እጩ የተደረገው ራሱ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ በማራቶን ስልጠናው እና ልምምዱ ላይ ስርነቀል መሻሻሎች እንደሚያስፈልጉ ጎን ለጎን አስረድተዋል፡፡‹‹ ብዙ ለውጦች ያስፈልጋሉ፡፡ በልምምድ፤ በህክምና ድጋፍ እና በጤንነት አጠባበቅ፤ በፊስዮቴራፒ ያሉትን ሁኔታዎች ማሻሻል ይገባል፡፡ በቀለ በጣም ተፈጥሯዊ ብቃት የታደለ አትሌት ነው፡፡ መልቲ ቫይታሚን ወስዶ እንኳን አያውቅም›› በማለት ጆስ ሄርማንስ በአትሌቱ ላይ ስላላቸው ተስፋ መናገራቸውን ሌትስራን ድረገፅ ዘግቦታል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ለቺካጎ ማራቶን ባደረገው ዝግጅት ለውጦች ማድረጉ ግድ ነበር፡፡ የመጀመርያ ማራቶኑን በፓሪስ ከመሮጡ በፊት የሰራው ልምምድ ምንም እንኳን በውድድሩ በምንጊዜም የማራቶን ፈጣን ሰዓት 6ኛ ደረጃ አስመዝግቦ ቢያሸንፍም በወቅቱ 27ኛው ኪሎሜትር ላይ ለገጠመው የጉዳት ስሜት ምክንያቱ የልምምድ ስርዓቱ ነበር፡፡ ለፓሪስ ማራቶን ሲዘጋጅ በሳምንት ከ180 እስከ 200 ኪሎሜትሮችን ሮጦ ነበር፡፡ ለቺካጎ ማራቶን የተዘጋጀው ግን ከ160 እስከ 180 ኪሎሜትሮችን ነው፡፡የዓለም የማራቶን ሪከርድ በኬንያዊ አትሌት ሲሰበር የዘንድሮው ለሶስተኛ ጊዜ ሲሆን በዴኒስ ኪሜቶ የተያዘው 2 ሰዓት ከ02 ደቂቃዎች ከ57 ሰከንዶችን በሚቀጥሉት 15 ዓመታት በ177 ሰከንዶች በማሻሻል በሰው ልጅ ብቃት ማራቶንን 1 ሰዓት ከ59 ደቂቃዎች መግባት እንደሚቻል ሳይንቲስቶች ይገልፃሉ፡፡ ከምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ይህን በማሳካት ደግሞ ኬንያውያን ወንድ አትሌቶች ከኢትዮጵያውያን እጅግ በላቀ ሁኔታ ግምት አግኝተዋል፡፡
ቺካጎ ላይ በሴቶች ምድብ  ያሸነፈችው ኬንያዊቷ ሪታ ጄፒቶ ስትሆን ርቀቱን በ2 ሰዓት ከ24 ደቂቃዎች ከ35 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ በመሸፈን ነበር፡፡ ይሁንና የኢትዮጵያ ሴት አትሌቶች በውድድር ዘመኑ እንዳሳዩት ስኬት በቺካጎም ዋና ተፎካካሪዎች ነበሩ፡፡ ቺካጎ ላይ ኢትዮጵያዊቷ ማሬ ዲባባ በ2 ሰዓት ከ25 ደቂቃዎች ከ37 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ርቀቱን በመሸፈን ሁለተኛ ደረጃን ስታገኝ፤ 3 የወጣችው የኬንያዋ ፍሎረንስ ኪፕላጋት ናት፡፡ በሴቶች ሌሎቹ ኢትዮጵያውያን በ2 ሰዓት ከ27 ደቂቃዎች ከ02 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ብርሃኔ ዲባባ አራተኛ እንዲሁም ገለቴ ቡርቃ በ2 ሰዓት ከ34 ደቂቃዎች ከ17 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ስምንተኛ መውጣታቸው ይጠቀሳል፡፡

በ8 የማራቶን ሊጎች በወንዶች ኬንያ  7 ኢትዮጵያ 1፤ በሴቶች ኬንያ 3 ኢትዮጵያ 1
ማራቶን ሊግ “ዎርልድ ማራቶን ሜጀር ሲሪዬስ”  በሚል ስያሜ ዘንድሮ የተካሄደው ለስምንተኛ ጊዜ ነው፡፡ በማራቶን ሊግ ላይ በስድስት ትልልቅ ማራቶኖች  በሚመዘገብ ውጤት መሰረት 1ኛ ሆኖ መጨረስ በሁለቱም ፆታዎች በነፍስ ወከፍ የ500ሺ  ዶላር ሽልማት ይገኝበታል፡፡ ማራቶን ሊጉ ዘንድሮ የተጀመረው   በቶኪዮ ማራቶን ሲሆን የመጨረሻው ውድድር ነገ በኒውዮርክ ማራቶን ይሆናል፡፡
የዘንድሮ ማራቶን ሊግ በኒውዮርክ ማራቶን ከመጠናቀቁ በፊት በተለይ በሴቶች ምድብ በአንደኛነት በመጨረስ 500ሺ ዶላር እንዳሸነፈች ያረጋገጠችው ኬንያዊቷ ሪታ ጂፔቶ ሆናለች፡፡ ሪታ ጄፕቶ በ2013 እኤአ የቺካጎ እና የቦስተን ማራቶኖችን ለማሸነፍ የበቃች ሲሆን በ2014 እኤአ ደግሞ መልሷ በሁለቱም ማራቶን ውድድሮች በተከታታይ ዓመት በማሸነፍ በማራቶን ሊጉ 100 ነጥብ አስመዝግባለች፡፡ በ213 በዓለም ሻምፒዮና 1ኛ፤ በለንደን ማራቶን ሁለተኛ እንዲሁም በ2014 በለንደን ማራቶን ያሸነፈችው ኤድና ኪፕላጋት በ65 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ አግኝታለች፡፡ በ2013 እኤአ ላይ በቦስተን ማራቶን 3ኛ ደረጃ የነበራት እና በ2014 እኤአ የቶኪዮ እና የበርሊን ማራቶኖችን ያሸነፈችው ትርፌ ፀጋዬ በ51 ነጥብ 3ኛ ደረጃ በማግኘት በውድድር ዘመኑ በማራቶን ሊግ በኢትዮጵያዊ የተመዘገበውን ከፍተኛ ውጤት አግኝታለች፡፡
በሌላ በኩል በማራቶን ሊጉ የወንዶች ምድብ በነጥብ ብልጫ በአንደኛነት በመጨረስ የ500ሺ ዶላር ተሸላሚ የሚሆን አትሌት የሚታወቀው ነገ  በሚደረገው የኒውዮርክ ማራቶን ሊሆን ይችላል፡፡ በዚህም የኬንያውያን አትሌቶች እድል የሰፋ ነው፡፡ ሊጉን በአንደኛነት የሚመራው ከሳምንታት በፊት በበርሊን ማራቶን አዲስ የዓለም ክብረወሰን በማስመዝገብ ያሸነፈው እና በ2013 እኤአ ላይ በቶኪዮ እና ቺካጎ ማራቶን ላይ ያሸነፈው ዴኒስ ኪሜቶ በ75 ነጥብ ነው፡፡ በ2ኛ ደረጃ በ65 ነጥብ ይከተል የነበረው በ2013 በዓለም ሻምፒዮና አራተኛ ደረጃ በለንደን ማራቶን አንደኛ እና በኒውዮርክ ማራቶን 2ኛ ደረጃ እንዲሁም በ2014 በለንደን 3ኛ በቺካጎ አራተኛ ደረጃ ያስመዘገበው ኢትዮጵያዊ ፀጋዬ ከበደ ነው፡፡ በማራቶን ሊጉ የዴኒስ ኬሚቶን ደረጃ በመቀናቀን ከኒውዮርክ ማራቶን ውጤት በኋላ ለማሸነፍ እድል የሚኖረው የቀድሞ የማራቶን ክብረወሰን ባለቤት ዊልሰን ኪፕሳንግ ብቻ ይሆናል፡፡
በማራቶን ሊጉ ለአትሌቶች እስከ አምስተኛ ደረጃ በሚመዘገብ ውጤት  ነጥብ የሚያስገኙ ዓለም አቀፍ 6 ማራቶኖች  በቶኪዮ፤ በቦስተን፤ በለንደን፤ በበርሊን፤ በቺካጎ እና በኒውዮርክ የሚካሄዱት ናቸው፡፡ የኦሎምፒክ እና የዓለም ሻምፒዮና የማራቶን ውድድሮችም በሚካሄዱባቸው የውድድር ዘመናትም ነጥብ ይገኝባቸዋል፡፡ አንድ የማራቶን ሊግ የውድድር ዘመን በ2 የውድድር ዓመታት ውስጥ የሚወሰን ሲሆን በእዚህ ጊዜ ውስጥ የሊጉ አካል የሆኑ ቢያንስ 12 ማራቶኖች አሉ፡፡ በእነዚህ ውድድሮች ቢበዛ በ4 ማራቶኖች በመሳተፍ ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡ አትሌቶች በደረጃ ሰንጠረዡ በአንደኝነት በመጨረስ 500ሺ ዶላር በየፆታ መደቡ ለመሸለም  ሰፊ እድል ይኖራቸዋል፡፡ በማራቶን ሊግ  ውድድሮች ለአንደኛ ደረጃ 25 ነጥብ ፤ ለሁለተኛ ደረጃ 15 ነጥብ ፤ ለሶስተኛ ደረጃ 10 ነጥብ ፤ ለአራተኛ ደረጃ 5 ነጥብ  እንዲሁም ለአምስተኛ ደረጃ 1 ነጥብ ይሰጣል፡፡ ከ2006 በእኤአ ወዲህ  በተካሄዱት 7 የማራቶን ሊግ የውድድር ዘመናት ኬንያውያን በከፍተኛ ብልጫ ኢትዮጵያውያን እየራቁ መሄዳቸው ይስተዋላል፡፡ የዎርልድ ማራቶንስ ሜጀር ሲሪዬስ ወይንም የማራቶን ሊግ ከተጀመረ ወዲህ 129 ውድድሮች ተደርገው ማሸነፍ ከቻሉ 102 የአፍሪካ አትሌቶች 93 የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ናቸው፡፡ የአንበሳው ድርሻ ደግሞ የኬንያውያን ነው፡፡ከቺካጎ ማራቶን በኋላ በዓለም የማራቶን ሊግ ውስጥ በሚካሄዱ 6 የማራቶን ውድድሮች ከ1989 እኤአ ወዲህ የምስራቅ አፍሪካ በተለይ  የኬንያ እና የኢትዮጵያ አትሌቶች  በወንዶች 72.6 በመቶ በሴቶች 90 በመቶ አሸናፊዎች ናቸው፡፡
ከ1990 ወዲህ በሁለቱም ፆታዎች በቶኪዮ ማራቶን ኬንያ 9 ኢትዮጵያ 1 ፤ በቦስተን ማራቶን ኬንያ 14 ኢትዮጵያ 4፤ በለንደን ማራቶን ኬንያ 12 ኢትዮጵያ 3 ፤ በበርሊን ማራቶን ኬንያ 13 ኢትዮጵያ 4 ፤ በቺካጎ ማራቶን ኬንያ 12 ኢትዮጵያ 2፤  እንዲሁም ከነገው ውድድር በፊት በኒውዮርክ ማራቶን ኬንያ 10 ኢትዮጵያ 2 አሸናፊዎች አስመዝግበዋል፡፡
ባለፉት ስምንት የማራቶን ሊግ የውድድር ዘመናት የደረጃ ሰንጠረዡን በአንደኛነት በመጨረስ  የተሳካላቸው በወንዶች 7 ጊዜ የኬንያ አንድ ጊ. የኢትዮጵያ እንዲሁም በሴቶች ሶስት ጊዜ የኬንያ፤ እያንዳንዳቸው ሁለት ጊዜ የጀርመን እና የራሽያ እንዲሁም አንድ ጊዜ የኢትዮጵያ አትሌቶች በነፍስ ወከፍ የ500ሺ ዶላር ሽልማት አግኝተዋል፡፡ የማራቶን ሊጉን በማሸነፍ የተሳካላቸው ሁለት የኢትዮጵያ አትሌቶች ናቸው፡፡ በወንዶች ምድብ ባለፈው ዓመት በ75 ነጥብ የሊጉን ፉክክር በአንደኛነት በመጨረስ ያሸነፈው ፀጋዬ ከበደ ፤ እንዲሁም በሴቶች በ2006 እና 2007 ላይ በመጀመርያው የማራቶን ሊግ በ80 ነጥብ ያሸነፈችው ጌጤ ዋሚ ናቸው፡፡

Monday, 03 November 2014 07:56

ኢቦላ በአሃዝ ሲገለፅ

የዓለም ጤና ድርጅት በቅርቡ ያወጣው ሪፖርት እንደሚያመለክተው፤ የኢቦላ በሽታ ስርጭት በአስደንጋጭ ሁኔታ እየጨመረ ነው፡፡ የድርጅቱ ሪፖርት ቀጣዮቹን መረጃዎች ይፋ አድርጓል፡፡
8.033       እስከ አሁን በኢቦላ ቫይረስ የተያዙ ሰዎች
3865     በኢቦላ በሽታ ምክንያት ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች
233    በኢቦላ በሽታ ህይወታቸውን ያጡ የጤና ባለሙያዎች
400     በበሽታው የተያዙ የጤና ባለሙያዎች
21    በኢቦላ ቫይረስ የተጠቃ ሰው የበሽታውን ምልክቶች የሚያሳይባቸው ቀናት
        ***        
የየአገራቱ የጤና በጀት
በአሜሪካ የነፍስ ወከፍ አመታዊ የጤና በጀት     $ 8895
በላይቤሪያ     “    “    “    $ 65
በሴራሊዮን     “    “    “$ 96
በጊኒ        “    “    $ 32
በኢትዮጵያ     “    “    $ 18        
የዓለም ጤና ድርጅት ሌሎች መረጃዎች
በኤችአይቪ በየሳምንቱ - 4795 ሰዎች ይሞታሉ
በተቅማጥ    በየሳምንቱ -2828   ሰዎች ይሞታሉ
በኢቦላ     በየሳምንቱ -10ሺ ሰዎች ይሞታሉ ተብሎ ይታሰባል፡፡   

        በኢትዮጵያ ከ104 ሺ በላይ ኤርትራውያን ስደተኞች ይገኛሉ
         የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርት፣ በየዕለቱ ከ200 በላይ ኤርትራውያን ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ እንደሚገቡ መግለጹን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡
በኤርትራ መንግስት አስተዳደር የተማረሩ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ የአገሪቱ ዜጎች አገራቸውን ጥለው መሰደዳቸውን ያስታወሰው የተመድ ሪፖርት፣ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን አደገኛ ድንበር እያቋረጡ በህገወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ስደተኞች ቁጥር ካለፈው መስከረም ወር አንስቶ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ነው ብሏል፡፡ ባለፉት ሁለት ወራት ብቻ ከ3ሺህ 500 በላይ ኤርትራውያን ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ መግባታቸውን የገለጸው የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ሪፖርት፣ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ኤርትራውያን ስደተኞች ቁጥር ከ104 ሺህ በላይ መድረሱን አስታውቋል፡፡
የስደተኞችን ቁጥር እንዲጨምር ያደረገው ምክንያት በሪፖርቱ እንዳልተገለጸ የጠቆመው ዘገባው፤ይሄም ሆኖ ግን አንዳንድ የመብት ተሟጋች ቡድኖች ኤርትራውያን በአገሪቱ መንግስት የሚደርስባቸው ጭቆና እየከፋ መምጣቱ ለስደቱ መባባስ በምክንያትነት እንደሚያስቀምጡት ገልጧል፡፡

  • በ“ክልሉ ባለፉት ሶስት አመታት ብቻ 5ሺህ ያህል ሰዎች ታስረዋል”
  • የእንግሊዝ ጋዜጦች ኢትዮጵያ በየአመቱ የሚሰጣትን ከ9 ቢ. ብር በላይ እርዳታ ተቃውመውታል
  • የኢትዮጵያ መንግስት የእነአምነስቲን ሪፖርት መሰረተ ቢስ ነው ይላል

        በኦሮሚያ ክልል ባለፉት ሶስት አመታት 5ሺህ ያህል ሰዎች ኦነግን ትደግፋላችሁ፣ መንግስትን ትቃወማላችሁ በሚል ጥርጣሬ  ክስ ሳይመሰረትባቸው እንደታሰሩና በርካቶችም ለስቃይና ለሞት እንደተዳረጉ “አምነስቲ” የገለጸ ሲሆን የእንግሊዝ ጋዜጦች በየአመቱ፣ ለኢትዮጵያ የሚሰጠውን ከ9 ቢሊዮን ብር በላይ እርዳታ ተቃውመውታል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ አምነስቲ ኢንተርናሽናልና ሌሎች የሰብዓዊ መብት ተቋማት የሚያወጡት ሪፖርት፤ የውጭ ሃይል ጣልቃገብነትን የሚያራምድ መሰረተ ቢስ ውንጀላ ነው ይላል፡፡
አምነስቲ ኢንተርናሽናል ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርት፤ የኢትዮጵያ መንግስት በኦሮሞ ተወላጆች ላይ የሚፈጽመው በደል እየከፋ መምጣቱንና ሰላማዊ ተቃውሞ ባደረጉ ዜጎች፣ በተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አባላትና በተማሪዎች እንዲሁም በክልሉ በሚኖሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ላይ በጥርጣሬ ላይ የተመሰረተ እስር፣ ስቃይና ግድያ እንደሚፈጸም ገልጿል፡፡
በክልሉ በርካቶች ለእስር የተዳረጉት ሌሎች ሰዎች መንግስትን እንዲቃወሙ አነሳስታችኋል በሚል እንደሆነ የጠቆመው ሪፖርቱ፤ የተጠርጣሪዎች ቤተሰቦችም ጥቃት እንደሚደርስባቸው አስታውቋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ የጦር ካምፖች ውስጥ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ታስረው እንደሚገኙና አብዛኞቹም ከጠበቆችና ከቤተሰቦቻቸው ጋር እናዳይገናኙ እንደተከለከሉ ሪፖርቱ አብራርቷል፡፡
አለማቀፋዊና ክልላዊ የሰብዓዊ መብት ተቋማት በአፋጣኝ በጉዳዩ ጣልቃ ሊገቡና በክልሉ የሚፈጸሙ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ገለልተኛ የሆነ ምርመራና ማጣራት ሊደረግባቸው ይገባል ብሏል አምነስቲ፡፡
በተያያዘ ዜና የእንግሊዝ መንግስት ከፍተኛ እርዳታ ከሚሰጣቸው አገራት ኢትዮጵያ በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ትናንት የዘገበው ቴሌግራፍ፣ ባለፈው አመት ብቻ ከ329 ሚሊዮን ፓውንድ በላይ እርዳታ መቀበሏን ጠቅሶ የጸጥታ ሃይሎች ዜጎችን ለሚያሰቃዩባት ኢትዮጵያ እርዳታ መሰጠቱን ተቃውሟል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በየአመቱ ከእንግሊዝ የሚያገኘውን ከ9 ቢሊዮን ብር በላይ እርዳታ ለልማት ማዋል ሲገባው ዜጎችን ለመጨቆን እያዋለው ይገኛል ያለው ጋዜጣው፣ ድርጊቱን አውግዞታል፡፡ ዴይሊ ሜይልም በተመሳሳይ ሁኔታ እንግሊዝ ባለፉት ሶስት አመታት ብቻ ለኢትዮጵያ 1 ቢሊዮን ፓውንድ በእርዳታ መስጠቷን አስታውሶ፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ባወጣው ሪፖርት በሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በመንግስት ሃይሎች ለእስራት፣ ለሞትና ለስቃይ እየተዳረጉ እንደሚገኙ ማስታወቁን ገልጧል፡፡

በኦሮሚያ ክልል የሚገኙትን የአዳማና ሞጆ አካባቢዎች የሚሸፍን የዲጂታል ቶፖግራፊ ካርታ እየተሰራ መሆኑን የኢትዮጵያ ካርታ ስራዎች ኤጀንሲ አስታወቀ፡፡
ኤጀንሲው ጃይካ ከተባለው ዓለም አቀፍ ተራድኦ ድርጅት ጋር በትብብር የሚሰራው ዲጂታል ቶፖግራፊ ካርታ፣ በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ አዲሱ ካርታ ኤጀንሲውን ወደ ዲጂታል የአሰራር ዘዴ እንደሚያሸጋግረው ተጠቁሟል፡፡ የአዳማና ሞጆ አካባቢዎች ለፕሮጀክቱ ስራ የተመረጡት ትላልቅ ፕሮጀክቶችና ሰፋፊ የልማት ስራዎች የሚከናወኑባቸው ስፍራዎች በመሆናቸውና ለአዲስ አበባ ከተማ ያላቸው ቅርበት ስራውን በወቅቱ ለማጠናቀቅ ይረዳል በሚል እንደሆነ ታውቋል፡፡

እስከ 16 አመት የሚደርስ እስር ሊፈረድበት ይችላል

የ21 አመቱ ትውልደ ኢትዮጵያዊ ወጣት ሮቤል ፊሊጶስ፤ የአሜሪካ ፖሊስ ባለፈው ሚያዝያ ወር በቦስተን ማራቶን ውድድር ላይ በተከሰተው የቦንብ ጥቃት ዙሪያ በሚያደርገው ምርመራ ሃሰተኛ መረጃ ሰጥቷል፤ ምርመራውን ሆን ብሎ አስተጓጉሏል በሚሉ ሁለት ክሶች ባለፈው ማክሰኞ በቦስተን ፌደራል ፍርድ ቤት ቀርቦ ጥፋተኛ መባሉ ተዘገበ።
ፍንዳታው ከደረሰ ከሶስት ቀናት በኋላ፣ የቦንብ ጥቃቱ ፈጻሚ ነው ተብሎ በሚጠረጠረው ዞካር ሳርኔይ የተባለ ግለሰብ ክፍል ውስጥ የነበሩ ማስረጃዎችን አሽሽተዋል ከተባሉ ሶስት ሰዎች ጋር እንደነበር የተጠረጠረውና የግለሰቡ ጓደኛ የሆነው ወጣት ሮቤል ፊሊጶስ፣ በመጭው ጥር ወር መጨረሻ በቀረቡበት ክሶች በእያንዳንዳቸው እስከ ስምንት አመት የሚደርስ የእስራት ቅጣት ሊጣልበት እንደሚችል ተነግሯል፡፡
ሮቤል በወቅቱ አደንዛዥ ዕጽ ተጠቅሞ ስለነበር፣ በክፍሉ ውስጥ ስለተፈጠረው ነገር ማስታወስ ባለመቻሉ እንጂ ሆን ብሎ አልዋሸም ያሉት የሮቤል ጠበቆች፣ ይግባኝ እንደሚጠይቁ ተናግረዋል፡፡
ሶስት ሰዎችን ለሞት፣ ከ260 በላይ ሰዎችንም ለመቁሰል አደጋ የዳረገውን የቦንብ ጥቃት ፈጽሟል ተብሎ የተጠረጠረው ዞካር ሳርኔይ፣ በመጪው ጥር ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ የጠቆመው ዘገባው፤ ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘ እስከ ሞት የሚደርስ  ቅጣት ሊጣልበት እንደሚችል ታውቋል፡፡

የፖለቲካ ሳይንስ ምሁሩና የኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ “በውጭ ያሉ ኢትዮጵያውያንን የፖለቲካ እንቅስቃሴ” በተመለከተ አሜሪካ ውስጥ ላለፉት ስድስት ወራት ጥናት ሲያደርጉ ቆይተው በቅርቡ ወደ አገራቸው ተመልሰዋል፡፡ በአሜሪካ ስለነበራቸው ቆይታ፣ ስለ ጥናታቸው፣ እንዲሁም በሃገሪቱ ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳዮች ዙሪያ ከአዲስ አድማስ ከፍተኛ ሪፖርተር አለማየሁ አንበሴ ጋር ያደረጉት ቃለ-ምልልስ እንዲህ ቀርቧል፡፡

ላለፉት ስድስት ወራት አሜሪካ ቆይተው ነው የመጡት፡፡ የጉዞዎ አላማ ምን ነበር?
“ናሽናል ኢንዶውመንት ፎር ዲሞክራሲ” በተባለ የአሜሪካ ተቋም ውስጥ ጥናት ሳደርግ ነው የቆየሁት፡፡ ዲሞክራሲ እና የኢትዮጵያ ዳያስፖራን በተመለከተ በተለይ በኢትዮጵያ ውስጥ በሚደረገው ዲሞክራሲያዊ ትግል ውስጥ ያላቸውን ሚና ማየት ነበር የጥናቱ ዓላማ፡፡ የአሜሪካ ዋና ከተማ ዲሲ ውስጥ የኢትዮጵያ ሁለተኛ ዋና ከተማ በሚመስል ደረጃ ነው ኢትዮጵያውያኖች ያሉት፡፡ እዚያ አካባቢ ፖለቲካው ያገባናል ብለው የሚንቀሳቀሱትን አግኝቻለሁ፡፡ እንደ ሲያትል፣ ሳንዲያጎ፣ ላስቬጋስ፣ ሳንፍራንሲስኮ፣ ሚኒሶታ፣ ዳላስ፣ ፊላደልፊያ በመሳሰሉት የአሜሪካ ከተሞች ተዛዙሬም ኢትዮጵያውያንን አነጋግሬያለሁ፡፡ በዚያውም ለፓርቲያችን ድጋፍ ለማሰባሰብ ሞክሬያለሁ፡፡ ከሞላ ጎደል በውጭ ያለው ዳያስፖራ በሀገሩ ፖለቲካ ላይ እንዴት ነው? የሚለውን ነው ያየሁት፡፡ በ“ኢሳት” እና በ“ቪኦኤ” እንዲሁም በ“ኦሮሞ ሚዲያ ኔትዎርክ” ላይ የኢትዮጵያን ፖለቲካ በተመለከተ በስፋት ቃለምልልሶችንና ክርክሮችን ለማድረግ ሞክሬያለሁ፡፡ መጨረሻ ላይም አሜሪካውያንና ኢትዮጵያውያን በተገኙበት መድረክ ላይ የጥናት ውጤቱን አቅርቤአለሁ፡፡
መሰረታዊ ችግሮቻችንን ለመፍታት ከኢትዮጵያ መንግስት፣ በውጭው ዓለም ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ከዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ምን ይጠበቃል በሚሉት ሶስት መሰረታዊ ነገሮች ላይ ነው አስተያየት ለማቅረብ የሞከርኩት፡፡
በወቅቱ ፕሬዚዳንት ኦባማ፣ የአፍሪካ አምባገነን መሪዎችን ሰብስቦ ሲያነጋግር፣ እኔ ጥናት ያቀረብኩበት ዲሞክራቶች የሚመሩት ናሽናል ዲሞክራቲክ ኢንስቲቲዩት፣ እንዲሁም ዊልሰን ሴንተርና ፍሪደም ሴንተር የሚባሉ ተቋማት በጋራ የአፍሪካ ሲቪል ማህበረሰብ አባላትን ሰብስበው ነበር፡፡ በጣም ሰፊ ስብሰባ ነው፡፡ በመድረኩ ላይም ስለ አፍሪካ መሰረታዊ ችግሮች ማለትም ስለ ምርጫ፣ ስለ ፍትህ፣ ስለ ሰብአዊ መብት አከባበር… ሃሳቦች ተንፀባርቀው ውይይት ተደርጓል፡፡ በዚህ ስብሰባ ላይም በተናጋሪነት ተሳትፌያለሁ፡፡ እንግዲህ እነዚህን ስራዎች ስሰራ ነው የቆየሁት፡፡
በዳያስፖራው ላይ ባካሄዱት ጥናት ምን ውጤት አገኙ?
ምንም ጥያቄ የለውም፤ ከዳያስፖራው ጋር በሁለት ነገሮች ላይ መግባባት ያስፈልገናል፡፡ እንደሚታወቀው ያለ ዳያስፖራው ድጋፍ መንቀሳቀስ ይከብዳል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ አሁን ባለው የፖለቲካ ምህዳር፣ ከሃገር ውስጥ የፋይናንስ ድጋፍ ማግኘት የሚቻልበት ደረጃ ላይ አይደለንም፡፡ የዳያስፖራው ድጋፍ ያስፈልገናል፡፡ ዳያስፖራው ግን ድጋፉን ሲሰጠን ውሃ ልኩን ካላወቀ፣ ሃገር ውስጥ የሚደረገው ትግል መልኩን ሊስት ይችላል፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገውን ሰላማዊና ህጋዊ ትግል፣ ዳያስፖራው በውጪ ደረጃና ሚዛን ካየው እንዲሁም እንደዚያ ተንቀሳቀሱ ካለ፣ አገር ውስጥ በዚያ ደረጃ መንቀሳቀስ ስለማይቻል፣ ብዙ ተስፋ የመቁረጥ ዝንባሌ ይከሰታል፡፡ ይሄንንም በጥናቴ ተመልክቻለሁ፡፡ ሌላው ደግሞ ዳያስፖራው በሚሰጠው ድጋፍ መጠን በሚፈልገው አቅጣጫ ግፋበት የማለት ዝንባሌ ይታያል፤ እሱም ያስቸግራል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን አስቸጋሪው ዳያስፖራው በተለይ በብሄር የመከፋፈሉ ነገር ነው፡፡ በብሄር ብሄረሰቦች ጥያቄ ዙርያ ዳያስፖራው ሃገር ውስጥ ካለነው በበለጠ ተከፋፍሏል፡፡   ምን ዓይነት ዲሞክራሲያዊ ለውጥ መምጣት አለበት በሚለው ላይ ሀገር ውስጥ ያሉት ተቃዋሚዎችም ሆኑ ዳያስፖራው ስምምነት ላይ ካልደረሱ፣ ለዲሞክራሲ የሚደረገውን ትግል ወደፊት ለመግፋት ይቸግራል፡፡ በዳያስፖራው እና በሃገር ውስጥ ባለው ተቃዋሚ መካከል ኢትዮጵያ እንዴት ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ትሂድ በሚለው ላይ መግባባት መፍጠር ያሻል፡፡
ዳያስፖራው በፖለቲካ ብቻ ሳይሆን በሃይማኖትም ጭምር እስከ መከፋፈል ደርሷል በማለት የሚተቹ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ በጥናትዎ ምን ታዘቡ?
ከሃይማኖት ይልቅ በፖለቲካው ውስጥ ያለው ክፍፍል፣ በተለይ በብሄረሰቦች ጥያቄ ዙርያ ሁለት ፅንፍ አለ፡፡ መሃል መንገድ ላይ የሚሰባሰቡ ኃይሎች ተፈጥረው፣ የኢትዮጵያን ዕጣ ፈንታ ሊወስን የሚችል ዲሞክራሲያዊ ትግልን መልክ ማስያዝ እስካልቻሉ ድረስ ያለማጋነን የሁለት ፅንፎች እስረኛ እንሆናለን፡፡ አንዱ ኢትዮጵያ የሚባል ነገር አልሰማም ይላል፤ ሌላው ደግሞ የኢትዮጵያዊነት ሰርተፍኬት ሰጪም ከልካይም እኛ ነን ባይ ነው፡፡ ያ ደግሞ አገር ውስጥም ይንፀባረቃል፡፡ እነዚህ ነገሮች መልክ እንዳይዙ ያደረጉት የገዥው ፓርቲ ቀጥታም ሆነ ስውር እጆች ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ በሃገር ደረጃ ያለባት ፈተናም ይሄን የማለፍ እና ያለማለፍ ነው፡፡
ይሄ የዳያስፖራው ሁኔታ ሀገር ውስጥ ባሉ ተቃዋሚዎች ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ ምንድን ነው?
በዚህ ምክንያት በአጠቃላይ ትግሉ ተጎድቷል፡፡ ክርር ወዳለው መስመር የመሰባሰብ ችግር አለ፡፡ አብዛኛው ሰውም በዚህ ሃይል ስር ነው፡፡ ይህ ደግሞ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ሃገር ውስጥ ባለው ትግል ላይ ተፅዕኖ አለው፡፡ ለዚህ ደግሞ ተጠያቂው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ የፖለቲካ ምህዳሩን ባጠበበ ቁጥር ወደዚህ መሰሉ እንቅስቃሴ ብዙዎች መግባታቸው አይቀርም፡፡ ብሄረሰቦች እየተቻቻሉ፣ የተሻለች ዲሞክራቲክ ኢትዮጵያን እንዳይፈጥሩ ያደረገው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ የገዥውን ፓርቲ አቅጣጫ መለወጥ ካልቻልን የትም አንደርስም፡፡ የፖለቲካ ምህዳሩን የማስተካከል ኃላፊነት በግድም ሆነ በውድ የገዥው ፓርቲ ነው፡፡ በዳያስፖራው አካባቢ ላለው የከረረ ፖለቲካ ምንጩ ምንድን ነው? የሚለውን መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ዋናው ምንጭ የፖለቲካ ምህዳሩ መጥበቡ፣ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ የሚካሄድበት መድረክ መፈጠር ያለመቻሉ፣ ነፃ ሃሳብ የሚንሸራሸርበት ሚዲያ አለመኖሩ፣ በቀላል ቋንቋ ገዥው ፓርቲ “ስልጣን ወይም ሞት?” በሚለው አቋሙ መቀጠሉ ነው ይሄን የፈጠረው፡፡ ትግሉን ወደ ውጪ ያስወጣው እኮ ራሱ ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ ጋዜጠኞችን፣ ፖለቲከኞችን የሚያሳድደውና ሰው ወደ ውጭ እንዲያይ የሚያደርገው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ አገር ውስጥ ያለው ነገር ቢስተካከል የኢትዮጵያ ፖለቲካን ትግል ይዞ አሜሪካ ወይም አውስትራሊያ አሊያም ሌላ ሃገር የሚሄድበት ምክንያት የለም፡፡ ይሄ አካሄድ ደግሞ ገዥውን ፓርቲም ቢሆን እየጠቀመው አይደለም፡፡ በዋናነት የኢትዮጵያ ፖለቲካ እንዲሰደድ ያደረገው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ ገዥው ፓርቲ የኢትዮጵያ ፖለቲካ እንዳይሰደድ ከፈለገ፣ እዚህ ያለውን የፖለቲካ ምህዳር መክፈትና ማስፋት አለበት፡፡
በአብዛኛው በዳያስፖራው አካባቢ የሚደረገው ትግል እየሰፋ የሚሄድበትና በዚያው መጠን ፖለቲካው የሚከርበት ምክንያት ምንድን ነው? የሚለውን ብዙ ሰው እየረሳ ነው፡፡ እዚህ ያለው የፖለቲካ ምህዳር ስለጠበበ፣ ስለማያሰራ፣ ወጣቶችን፣ ጋዜጠኞችን፣ ፖለቲከኞችን ስለሚያሳድድ ውጪ እየሄዱ እየተደራጁ፤ ውጪም ብቻ ሳይሆን ጫካም እየሄዱ እየተደራጁ፣ ባገኙት መንገድ ትግሉን መቀጠል ስለሚፈልጉ ነው፡፡
የዳያስፖራው ትግል ሃገር ውስጥ ባለው ስርአት ላይ ተጨባጭ ተፅዕኖ የመፍጠርና ለውጥ የማምጣት አቅም አለው ብለው ያስባሉ?
ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚደረገው ትግል ካልራቀ ምንም ጥርጥር የለውም፤ ተጨባጭ የሆነ ለውጥ ማምጣት የሚችልበት እድል አለው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገውን ትግል በሃብት ሊረዳ ይችላል፡፡ በእውቀት፣ በዲፕሎማሲና በብዙ መንገድ ሊረዳ ይችላል፡፡ የኢትዮጵያ ባለስልጣናትም ጭምር አሁን የሚደረገውን የዳያስፖራውን ትግል እንደቀላል እያዩት አይደለም፡፡ ዳያስፖራው እኮ ምናልባትም የእነሱም የመጪው ጊዜ መኖሪያ ሊሆን ይችላል፡፡ ብዙ የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት፣ ብዙ ወጪ እያወጡ ዳያስፖራ ውስጥ ኑሮአቸውን ለመመስረት እየሞከሩ ነው፡፡ የደርግ ባለስልጣናት ዛሬ ኑሮአቸው ዳያስፖራ ውስጥ ነው፡፡ ባለስልጣናት በሚሄዱበት ሃገር ምን እየገጠማቸው እንደሆነ እያየን ነው፡፡ እኛን በሃገራችን መኖር እንዳንችል አድርጋችሁ እናንተ እዚህ መቀመጥ አትችሉም እየተባሉ ነው፡፡ እነ ጁነዲን ሳዶ እኮ እየተደበቁ ነው የሚኖሩት፡፡ ሃገር ውስጥ ለሰሩት ወንጀል ምናልባት በህግ ልንጠየቅበት እንችላለን እያሉ ይጨነቃሉ፡፡ በሃገሪቱ ኢኮኖሚ ላይም የዳያስፖራው ሚና ቀላል አይደለም፡፡ በዓመት 4.5 ቢሊዮን ብር ወደ ሃገር ውስጥ ይልካሉ፡፡
በቅርቡ በአሜሪካ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ከባንዲራ ጋር በተያያዘ ስለተፈጠረው ሁኔታ ምን ይላሉ?
የባንዲራው ጉዳይ ውስጥ ብዙ መግባት አልፈልግም፡፡ ኢህአዴግም ቢሆን ከማንም በላይ የባንዲራ ጠባቂ ነኝ ሊል የሚችል ድርጅት አይደለም፡፡ በተለይ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ስለባንዲራ ምን ይሉ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ኢህአዴግ ያን ያል  የባንዲራ አስከባሪ መሆን አይችልም፡፡ ዋናው ነገር ኤምባሲዎች አካባቢ እንደዚያ ያለ ነገር ገፍቶ ከቀጠለ በአጠቃላይ ጥሩ ምልክት አይደለም፡፡ የሃገሪቱ ያለመቻቻል ፖለቲካ እዚያ ድረስ ሄዶ ሁላችንንም በማያስከብር መልኩ እየተንፀባረቀ ነው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ መንግስት የፖለቲካ ምህዳርን በመዝጋትና በማፈን ብዙ ነገሮችን አደርጋለሁ የሚለውን ደጋግሞ ቢያስብበትና ጩኸቱንም ቢሆን እዚሁ ሃገር ቤት ብንጯጯህ ይሻላል፡፡
ዳያስፖራው በተቻለው ሁሉ አሜሪካ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ተፅዕኖ እንድታሳርፍ ሲጥር መቆየቱ ይታወቃል፡፡ ከዚህ በተቃራኒው በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ከፕሬዚዳንት ኦባማ ጋር ያደረጉትን ውይይት ተከትሎ በሰጡት መግለጫ፤ “ወዳጅነታችን ተጠናክሯል፣ ውጤታማ ውይይትም አድርገናል” ብለዋል፡፡ በዚህ ዙሪያ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው?
የአሜሪካ መንግስት ባለስልጣናት ፍቅራቸውና ሌላ ነገራቸው ብዙም አያሳስበኝም፡፡ እኔ የሚያሳስበኝ የቤት ስራችንን መስራትና አለመስራታችን ነው፡፡ እኔ ፖለቲካል ሣይንስ በተለይም የውጪ ፖሊሲ ላይ አስተምራለሁ፤ እናም “አሜሪካኖች ቋሚ ጥቅም እንጂ ቋሚ ፍቅር የላቸውም፡፡” ለምሣሌ የግብጽ መንግስት ገና መናጋት ሲጀምር “በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ወዳጃችን ነው” እያሉ ሲቀባጥሩ ነበር፡፡ ኋላ ላይ ግን ኦባማ “ሠላማዊ ተቃዋሚን መግደል ወንጀል ነው” ብሎ ተናገረ፡፡ ከዚያ በኋላ ጨዋታው ተቀየረ፡፡ ስለዚህ ዋናው ነገር ኢትዮጵያውያን በጋራ ትግሉን ማጠናከራቸው ነው፡፡ ያ ከሆነ የአሜሪካ መንግስት ትግሉን የማይደግፍበት ምንም ምክንያት የለም፡፡ አሁን ሁለቱን መንግስታት ያወዳጀው የሽብር ጉዳይ ነው፡፡ ይሄ በግልጽ ይታወቃል፡፡ በፀረ-ሽብር ጨዋታ ውስጥ ተጠላልፈው ገብተው እያደረጉ ያለው ነገር ግልጽ ነው፡፡ ነገር ግን ዋናው እኔን የሚያስጨንቀኝ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ሃይሎች፣ የኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ሃይሎችና የኢትዮጵያ ሕዝብ የራሱን የቤት ስራ እየሰራ ነው? ለራሱ መብት፣ ክብርና ነፃነት እየታገለ ነው ወይ? የሚለው ጉዳይ ነው፡፡
ካነሱት አይቀር አሁን ያለውን የተቃዋሚ ሃይሎች ፖለቲካ፣ የህዝቡን ፍላጐት እና የገዥው ፓርቲን ሁኔታ እንዴት ይገመግሙታል?
 ሁሉም ፓርቲ የአቅሙን ያህል እየሰራ ነው፡፡ የመከፋፈል ፖለቲካው ግን አሁንም ቀጥሏል፡፡ ብዙ ፓርቲዎች የ97ቱን የመሠለ እንቅስቃሴ መፍጠር አልቻሉም፡፡ ያን ጊዜ ቢያንስ ሁለት ስብስቦች መፍጠር ተችሎ ነበር፤ አሁን ግን ሙከራዎች ቢኖሩም ወደፊት የሚያስኬድ አይመስልም፤ ክፍፍሉ አሁንም አለ፡፡ ነገር ግን ነፃና ፍትሃዊ የሚባለው አይነት የምርጫ ስርአት ከተዘረጋ ምንም ጥርጥር የለውም፣ ኢህአዴግ በአንድ ወር እንቅስቃሴ ይሸነፋል፡፡ ይሄን በሰሞኑ የመምህራን ስልጠና ላይም ተናግሬዋለሁ፡፡ ኢህአዴግን ለማሸነፍ ቀላል ነው፡፡ ዋናው ጉዳይ ኢህአዴግ በአንድ በኩል ተቃዋሚዎች ተዳክመዋል ይላል፤ መቼም ሰይጣን አይደለም ተቃዋሚዎችን የሚያዳክመው፤ ኢህአዴግ ራሱ ነው፡፡ አሞሌና ዱላ ይዞ የሚዞረው ኢህአዴግ ነው፡፡ በአሞሌ ያልወደቀ በዱላ ይወድቃል፡፡ ኢህአዴግ አሞሌና ዱላ ይዞ መዞር ካቆመ፣ እሱን ማሸነፍ ትልቅ ነገር አይደለም፡፡ ይልቁንስ ከዚያ በኋላ ሃገር ለመምራት ተቻችሎ፣ ተግባብቶ የጋራ የፖለቲካ አጀንዳ ቀርፆ ለመንቀሳቀስ ይቻላል ወይ የሚለው ነው እኔን የሚያሳስበኝ፡፡
ኢህአዴግን ለማሸነፍ ያስቸግራል የሚል ግምት ግን የለኝም፡፡ ዋናው ኢህአዴግ የራሱን ዳኛ ይዞ ወደ ጨዋታ ሜዳ አለመግባቱ ነው፡፡ አሁን ዳኛም ተጫዋችም ነው፡፡ ሁልጊዜ ዳኛም ተጫዋችም ሆኜ እቀጥላለሁ ካለ ግን ምናልባትም እኛም ኢህአዴግም የማንፈልገው ነገር ኢትዮጵያ ውስጥ ሊፈጠር ይችላል፡፡
በአንድ በኩል ምርጫ ቦርድ ገለልተኛ አይደለም የሚል ትችት ከተቃዋሚዎች ሲሰነዘር ይደመጣል፡፡ እነዚያው ፓርቲዎች ግን ባላመኑበት ምርጫ ሲሳተፉ እንመለከታለን፡፡ ቦርዱ ገለልተኛ አይደለም ካሉ በኋላ በምርጫው መሳተፍ ተገቢ ነው ይላሉ?
ሁለት ነገር ነው ያለው፡፡ ተቃዋሚ ስንል ህዝብ ተቃዋሚ ናቸው ብሎ የሚያምንባቸውን ነው እንጂ ኢህአዴግ የሚቀልባቸውን ማለት አይደለም፡፡ እነዚህ ፓርቲዎች ይህ አይነቱ አዙሪት እንዲያበቃ በጋራ “አንሳተፍም” የሚል አቋም መያዝ አለባቸው፡፡ ብዙ ጊዜ እንዲህ ያለ ሃሳብ ማግኘት ያስቸግራል፡፡ አንዱ ትልቁ ችግር ይሄ ነው፡፡ ለምሣሌ በ2002 ምርጫ መድረክ አካባቢ የተሠባሰብነው ወደ ምርጫ ያለመግባት ሃሳብ ነበረን፤ ነገር ግን መኢአድ የስነምግባር ደንቡን በመፈረሙ፣ የተቃዋሚዎችን የጋራ አቋም ስላላገኘን፣ ጨዋታው ከሚበላሽብንና የፖለቲካ ትርፍ ቢገኝ ብለን ገባንበት እንጂ ውጤት ያመጣል ብለን አይደለም፡፡ የ97 ምርጫን ካየን፣ ህብረት በጨዋታው ሜዳ ላይ ተደራድሯል፡፡ የሚፈለገውን በአንድነት ገፍተን ባናገኝም የተወሰኑ ጥቃቅን ነገሮች ተሻሽለዋል፡፡
የሚዲያ አጠቃቀምን ማንሳት እንችላለን፡፡ በወቅቱ ኢህአዴግ የቆመበት መሬት እስኪከዳው ድረስ የገፋነው በሱ ነው፡፡ የ2002 ምርጫ ላይ ግን መግባቱ ጥቅም አልነበረውም፡፡ አሁንም የተቃዋሚዎች ሙሉ አቋምና ውሣኔ እስካልተገኘ ድረስ አንዱ ገብቶ ሌላው ሲቀር አስቸጋሪ ነው፡፡ አንዳንዴ መቀመጫም ባናገኝ የፖለቲካ ጥቅም ለማግኘት የምንገባበት አጋጣሚም አለ፡፡ ሌላው ሁለት ምርጫ ላይ ያልተሳተፈ ይሰረዛል የሚል ህግ አለ፤ ያንን በመፍራትም ይገባል፡፡
አሁንስ የ8 ወር እድሜ ለቀረው የ2007 ብሔራዊ ምርጫ የተቃዋሚዎች ዝግጅት ከኢህአዴግ አንፃር እንዴት ይታያል?
ተቃዋሚዎች ዝግጅት ይኖራቸዋል፤ ነገር ግን ዋናው ጉዳይ የፖለቲካ ምህዳሩ እስካልሰፋ የትም አይደረስም፡፡ የ2007 ምርጫን ከአሁኑ ገምግም ከተባልኩ፣ ምናልባት ኢህአዴግ የተወሰኑ የመቀመጫ ፍርፋሪዎችን ለተቃዋሚዎች ለቆ እንደገና አሸነፍኩ ሊል ይችላል፡፡ ያ ማሸነፍ ለኢትዮጵያም፣ ለኢህአዴግም ለሁሉም የሚጠቅም አይመስለኝም፡፡ ምንጊዜም ህዝብን ተስፋ አታሳጣ፤ ህዝብን ተስፋ ካስቆረጥከው ተስፋ የቆረጠ ስራ ውስጥ ሊገባ ይችላል፡፡ አሁንም ሃገር ውስጥም ሆነ ውጪ ብዙ ነገሮች ጤናማ አይደሉም፡፡
ቀደም ብለው እንደነገሩኝ፤ በአሜሪካ ቆይታዎ ኢሣት ቴሌቪዥን ላይ ሰፊ ቃለ ምልልስና አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ደግሞ ጣቢያውን የ“አሸባሪዎች” ልሣን ነው በማለት የፖለቲካ ድርጅቶች ከጣቢያው ጋር ያላቸውን ግንኙነት እንዲገቱ አስጠንቅቋል፡፡ ከዚህ አንፃር ጉዳዩ ስጋት ውስጥ አልከተትዎትም?
“ኢሣት” እንግዲህ የኢህአዴግ ወዳጅ ሃገር በሚባለው አሜሪካ በነፃ ተመዝግቦ የሚንቀሳቀስ ጣቢያ ነው፡፡ ድጋፍ ከማህበረሰቡ እያሰባሰበ ነው የሚሠራው፡፡ እዚያ ጣቢያ ላይ መረራ የራሱን አስተያየት ነው የሰጠው እንጂ የኢሣትን ፕሮፓጋንዳ አይደለም ያንፀበረቀው፡፡
በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ነው አስተያየቴን የሰጠሁት፡፡ ኢሣት ጠመንጃ የለውም፣ የትጥቅ ትግልም እያካሄደ አይደለም፡፡
 ስለዚህ እኔ እንደ ከባድ ነገር አላየውም፡፡ በነገራችን ላይ የኢህአዴግ ባለስልጣናትም አልፎ አልፎ አስተያየት ይሰጣሉ፡፡ የኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቪዥንን ባያፍን እኮ “ኢሣት” ጋ የምሄድበት የተለየ ምክንያት የለኝም፡፡ የውጪ ሚዲያ ጋ እንዳንሄድ ከፈለገ፣ የሀገር ውስጡን ይስጠን፡፡ መረራ “ኢሣት”ን ባይጠቀም ሌሎች ብዙ ሺህ ምሁራን ይጠቀሙበታል፡፡ እንደሚታወቀው የኛ ፓርቲ የሽብር ፕሮጀክት የለውም፤ በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ ነው የሚታገለው፡፡ “ኢሳት” ላይ የምናገረው ሃገር ውስጥ ባለው ቴሌቪዥን ጣቢያ እንድናገር እድል ቢሰጠኝ የምናገረውን ነው፡፡ እኔ ውጪም ሆነ ውስጥ ቋንቋዬ አንድ ነው፡፡

(ዘልኤ አይቤ ጋዬ - ዎሬ አይቤ ቁፌ) የወላይታ ተረት

ከላፎንቴን ታሪኮች አንዱ እንዲህ ይለናል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን የሰማይ ቁጣ በእንስሳት ላይ እየመጣ ነው ስለተባለ የዱር እንስሳት ተሰብስበው ማ አጠፋ? ማ አጠፋ? በመባል ጥፋተኛውን አጋልጠው ለመስጠት አውጫጪኝ ይቀመጣሉ፡፡ እንስሳት ሁሉ ለረሀብ ተጋልጠው የእርስ በርስ ፍቅራቸው ሁሉ ሞቷል፡፡ ሁሉ ተኮራፍፏል፡፡ ተኩላ ከተኩላ እርግብ ከእርግብ እንኳ አይነጋገሩም! ከመጣው መዓት ለመዳን ሁላችሁም ሀሳብ ስጡ ተባለ፡-
አንበሳ ወንበሩን ያዘና በሊቀመንበርነት፡-     
“ወዳጆቼ ሆይ! የሰማይ ቁጣ ጥፋተኞች ላይ መውረዱ ደንብ ነው፤ አንቃወመውም፡፡ ነገር ግን ሁሉ ኃጢያት እኩል አይደለምና የበለጠና የከፋ ኃጢያት የሰራውን መለየት ይኖርብናል! ያ ጥፋተኛ ቅጣቱን ሲቀበል ለእኛ ስርየት፣ መዳኛ ይሆንልናል! ህሊናችንን ሳናጭበረብር ዕውነቱን እንናገር፡፡ እኔ በበኩሌ  ጥቂት ያስቀየሙኝን በጎች በልቻለሁ - አንዳንዴም እረኞቻቸውንም የቀመስኩበት ጊዜ ነበረ፡፡ ወድጄ አይደለም ስላስቀየሙኝ ነው፡፡ ይህ ጥፋት ነው ካላችሁ ሞት ይፈረድብኝ፡፡ ብቻ ዋናው ነገር ሌሎቻችሁም ኃጢያት ኃጢያታችሁን ተናዘዙ፡፡ ድርሻ ድርሻችሁን ውሰዱ፡፡ ከዚያ የከፋ ጥፋት የሰራውን እንለያለን፡፡ (It is only fair that all should do their best
to single out the guiltiest)”
ከዚያ ቀበሮ ተነሳና
“ንጉሥ ሆይ! ለእንደ ርሶ ያለ የተከበረ የዱር አራዊት ጌታ፤ በግ መብላት በጭራሽ ሀጢያት ሊሆን አይችልም፡፡ እነዚህን ባለጌና ልክስክስ በጎች መብላት ፈፅሞ ሊያስጠይቅ አይገባም፡፡ እረኞችም ቢሆኑ በእኛ ላይ ሲዶልቱ የሚኖሩ ናቸውና የእጃቸውን ነው ያገኙት” ብሎ ተቀመጠ፡፡ ጭብጨባው ቀጠለ፡፡
ቀጥሎ ማንም በነብር፣ በድብና በመሳሰሉት ክቡር እም ክቡራን ይቅርታ - የለሽ ወንጀል ላይ ምንም ሀሳብ ሳያነሳ ጭራሽ እንዲህ ያለ የተቀደሰ ተግባር የፈፀመ ከዚህ የለም፤ እየተባለ ውዳሴው ተዥጎደጎደ፡፡
በመጨረሻ አህያ ተነሳች፡-
“አንድ ቀን አንድ ሰፊ የሣር መስክ ሳቋርጥ ረሀብ አንጀቴን ቢመዠርጠኝ የምላሴን ያህል ቅንጣት ሳር ግጬ አልፌያለሁ፡፡ ያንን ሳር የመጋጥ መብት እንደሌለኝ በእርግጥ አውቃለሁ” አለች፡፡
ሁሉም እጃቸውን እያወጡ በአህያ ላይ የእርግማን መርግ ይጭኑባት፣ ይወርዱባት ጀመር፡፡ አንድ የተማረ፣ ብዙ ያነበበ የሚባል ተኩላም ተነስቶ፤
“ከዚህ በላይ በዓለም ላይ ኃጢያት ተሰርቶ አያውቅም፡፡ የኃጢያቶች ሁሉ ኃጢያት የሰው ሣር መጋጥ ነው! የሁላችንንም ኃጢያት ልትሸከም የሚገባት ይህቺ አህያ ናት! ቁጣውም እሷ ላይ መውረድ አለበት፡፡ የተንኮል ሁሉ ደራሲ እሷ ናት! ፎ! የሰው ሳር እንዴት ይጋጣል?! ስለዚህ ሞት ነው የሚገባት! ሆኖም አንድ ሀቅ ልጨምር ብሎ በግጥም ቀጠለ፡፡
“ሀብታም ሆንክ ደሀ፣
ክክቡር ነህ የተባልክ ወይ ከንቱ ቁጥር
ሁልህ ይደርስሃል የተራህ ሥፍር
ችሎት ይቀባሃል፣ ወይ ነጭ ወይ ጥቁር!”
                                              *         *         *
ፍሬድሪክ ኒች “ከመጥፎ ሥራ ጋር አብሮ ከመኖር ከመጥፎ ህሊና ጋር አብሮ መኖር ይከብዳል” ይላል፡፡ በሌላው ላይ በጅምላ ስምምነት፣ በመንገኝነት መፍረድ ትልቅ ኃጢያት ነው፡፡ ውሎ አድሮ እንቅልፍ መንሳቱ አይቀሬ ነው፡፡ ከህሊና ጋር በእፎይታ ማደር፣ ያለ አንዳች ወንጀለኝነት ስሜት አንገትን ቀና አድርቶ ለመሄድ መቻል ታላቅ ጸጋ ነው፡፡ የራስን አሳር የሚያህል የተቆለለ ወንጀል አድበስብሶ አንዲትን ቀጭን ሽፋን አጋኖ በሌላው ላይ መደፍደፍ አገር ገዳይ ነው! ህዝብ አሰቃይ ነው፡፡
“በክፉ ሰዓት የእናት ልጅ አይታመንም!” ይላል አበሻ ሲተርት፡፡ በክፉ ሰዓት የማ ባህሪ መቼ እንደሚቀየር አይታወቅም፡፡ በክፉ ሰዓት የትኛው ወዳጅ ተገልብጦ ጠላት እንደሚሆን አይታወቅም፡፡ ብዙ የፌሽታ ጊዜ ጓደኞች ጊዜ ከምበል ሲል አብረው ይከነበላሉ! ዕበላ - ባዮች፣ አቋም - የለሾች፣ አድር-ባዮች፣ አሥጊና አጥፊዎች ናቸው የሚባለው ለዚህ ነው፡፡ ስለሆነም ለህዝብም ለአገርም አይበጂም!
በጥንታዊት ቻይና የዌይ ግዛተ - መንግስት አንድ ለንጉሱ ታማኝ ሚሱ ሳይ የሚባል ባለሟል ነበር፡፡ የግዛቱ ህግ “የንጉሱን ሰረገላ በሚስጥር የነዳ ሰው እግሩ ቆረጣል” ይላል፡፡ ያ ታማኝ ሰው እናቱ ትታመምና ልትሞት ታጣጥራለች፡፡ ሊደርስላት የንጉሡን ሰረገላ ምንም አይሉኝም ብሎ እየነዳ ሄደ፡፡ ንጉሡ ይሄን ሲሰሙ “አይሱ ሳይ! እጅግ ኃላፊነት የሚሰማው ሰው ነው፡፡ ለእንቱ ሲል እግሮቹን እንደሚያጣ ረሳ!” አሉ፡፡ ታማኝ ሰዎች ታማኝነታቸው የት ድረስ መብት እንደሚሰጣቸው የረሱ‘ለት ራሳቸውን ያጣሉ ነው ትምርተ - ታሪኩ (Lesson/Moral of the story እንዲሉ ፈረንጆች፡፡)
የሀገራችን ፕሮጀክት ቀራጮች፣ ንድፈ - ሀሳብ አንጓቾች (theoreticians) አማካሪዎች፣ ስትራቴጂስቶች፣ ቀዳሽ ዳሳሾች በእርግጥ ከልባቸው ለህዝብና ለአገር ተቆርቁረው ነው ወይ ሥራውን የሚሰሩት ብሎ መፈተሸ የአባት ነው! ማ በተዘዋዋሪ ወገንተኛ ነው? ማ ልታይ ልታይ እያለ ከሙሰኞች ጋር የተሰለፈ ነው? ማ አፍአዊ፣ ማ ልባዊ ነው? ማ አጉራሽ አልባሽነትን እንደትራንስፎርሜሽን እያስቆጠረ ነው? ውስጣችንን እንፈትሽ፡፡ አንደበተ - ርቱዑን ከበቀቀኑ እንለይ፡፡
ፖለቲካችን፣ ኢኮኖሚያችን፣ ማህበራዊ ግንኙነታችን በአስመሳይ ሰዎች ሲታጠር ህይወታችን ጉድፍ የተሞላ፣ በደል የበዛው፣ ዕድገታችን ሀሳዊ፣ ፍቅራችን ነውር ያጎደፈው፣ ተስፋችን ጨለግላጋ፣ የጋራ ቤታችን የተራቆተ እንደሚሆን ገሀድ ነው፡፡ ምን እየዘራን ምን እያጨድን እንደሆነ በቅጡ ልብ እንበል፡፡ “ንግድ ምንድንነው? ትንባሆ፤ ትርፉ ምንድን ነው? - ሳል” የሚለውን የወላይትኛ ተረት አበክረን እናስምርበት!

ጥቃቱ ከአይሲስ ጋር ሊያያዝ ይችላል እየተባለ ነው
ባለፈው ረቡዕ ማለዳ በካናዳ ርዕሰ መዲና ኦትዋ በሚገኘው የአገሪቱ የጦርነት መታሰቢያ አደባባይና በፓርላማ ውስጥ በተከሰተውና ሁለት ሰዎችን ለህልፈት በዳረገው የተኩስ ጥቃት ዙሪያ የተጀመረው ምርመራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ሲ ኤን ኤን ዘገበ፡፡
ሚካኤል ዜሃፍ ቢቤው የተባለ የታጠቀ ግለሰብ፣  የአገሪቱን የጦርነት መታሰቢያ አደባባይ በመጠበቅ ላይ በነበሩ ሁለት ወታደሮች ላይ ተኩስ በመክፈት አንደኛውን የገደለ ሲሆን፣ ከሌሎች የጸጥታ ሃይሎች ጋር በተደረገው የተኩስ ልውውጥ ሌሎች ሶስት ወታደሮችን ካቆሰለ በኋላ የግለሰቡ ህይወት ማለፉን ዘገባው ገልጧል፡፡
ጥቃቱ በተፈጸመበት ወቅት በአገሪቱ ፓርላማ ተገኝተው ለምክር ቤቱ አባላት ንግግር እያደረጉ የነበሩት የካናዳው ጠቅላይ ሚኒስትር ስቴፈን ሃርፐር ጉዳዩን በተመለከተ ረቡዕ ምሽት በሰጡት መግለጫ፣ አገሪቱ በመሰል ጥቃቶችና ነውጦች እንደማትሸበር ገልጸው፣ ጥቃቱ ካናዳ ከአጋሮቿ ጋር በመሆን ጽንፈኝነትን ለመዋጋት የያዘችውን አቋም የበለጠ እንድታጠናክር የሚያደርግ ነው፤ ጽንፈኞች እንደፈለጉ የሚፈነጩበት ምቹ ቦታ አያገኙም ብለዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥቃቱን የፈጸመው ሚካኤል ዜሃፍ ቢቤው የተባለ ግለሰብ መሆኑን ከመግለጽ ባለፈ ማንነቱንም ሆነ ድርጊቱን ለመፈጸም ያነሳሳውን ምክንያትና አላማውን በተመለከተ ተጨማሪ መረጃ ያልሰጡ ሲሆን፣ ስለአሸባሪው ተጨማሪ መረጃ ለማግኘትና ሌሎች ተባባሪዎች እንዳሉት ለማጣራት የተጀመረው ምርመራ በጥቂት ቀናት ውስጥ ውጤት ያስገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል፡፡በወሩ መጀመሪያ ላይም የካናዳ መንግስት በኢራቅ የሚገኙ የአይሲስ ታጣቂዎችን ለማጥቃት በሚደረገው ዘመቻ ላይ ለመሳተፍ እቅድ እንዳለው ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው ሰኞ አንድ የአገሪቱ ወታደር አሸባሪ ተብሎ በተጠረጠረ ግለሰብ ሞንትሪያል ውስጥ በመኪና ተገጭቶ መገደሉን ተከትሎም፣ አገሪቱ ያለባትን የሽብር ስጋት መጠን ከዝቅተኛ ወደ መካከለኛ ደረጃ ከፍ ማድረጓን አስታውሷል፡፡
ካናዳ አይሲስ የተባለውን ጽንፈኛ ቡድን ለመዋጋት በተጀመረው አለማቀፍ እንቅስቃሴ እንደምትሳተፍ በይፋ ማስታወቋንና በቡድኑ ላይ ለሚደረገው የአየር ድብደባ ላይ የሚሳተፉ ስድስት ተዋጊ ጀቶችን ለመላክ መወሰኗን ተከትሎ ጥቃቱ መከሰቱ፣ ጉዳዩ ከአይሲስ ጋር ተያያዥ ሊሆን ይችላል የሚል ጥርጣሬ መፍጠሩን ዘገባው አስታውቋል፡፡አይሲስ ካናዳውያንን ለሽብር ጥቃት እየመለመለ እንደሆነ በቅርቡ ማስታወቁን ያስታወሰው ዘገባው፤ የአገሪቱ መንግስት ባለፈው ነሃሴ ወር ላይ ባወጣው ሪፖርትም፣ 130 ያህል ካናዳውያንም ወደሌሎች አገራት በመሄድ ከአሸባሪ ቡድኖች ጋር መቀላቀላቸውንና ከእነዚህ ውስጥም 30 የሚሆኑት በሶርያ በሚካሄደው ጦርነት ላይ እየተሳተፉ ይገኛሉ ተብሎ እንደሚገመት ማስታወቁን ገልጧል፡፡
በአገሪቱ መሰል የሽብር ጥቃቶች በጂሃዲስቶች ሊሰነዘሩ እንደሚችሉ ይገመት እንደነበር የጠቆመው ሲ ኤን ኤን፤ አሜሪካም መረጃ አግኝቻለሁ በማለት በቅርቡ በካናዳ በሚገኘው ኤምባሲዋና ቆንስላዋ ላይ ያለውን የደህንነት ሁኔታ በጥብቅ መከታተል መጀመሯን አስታውሷል፡፡አይሲስም ሆነ ሌሎች ቡድኖች ለጥቃቱ ሃላፊነት አለመውሰዳቸውን የገለጸው ዘገባው፣ የአገሪቱ የደህንነት መስሪያ ቤትም አይሲስ ወይም ሌሎች የሽብር ቡድኖች ከጥቃቱ ጋር በቀጥታ እንደሚያያዙ የሰጠው መግለጫ በይፋ ባያስታውቅም፣ በጉዳዩ ላይ ጥብቅ ምርመራ እያደረገ እንደሚገኝ ገልጿል፡፡ቢቢሲ በበኩሉ፤ በካናዳ የተለያዩ የጽንፈኛ ቡድኖች አባላትና ግለሰቦች አክራሪነትን መስበክ ከጀመሩ መቆየታቸውን በመጥቀስ፣ በአገር ውስጥና በውጭ አገራት ብጥብጦችን መፍጠር እንደሚገባ ብዙዎችን ማሳመን መቻላቸውን ዘግቧል፡፡ የአገሪቱ ፖሊስ 90 ተጠርጣሪዎችን ያሳተፉና ከሽብርተኝነት ጋር የተያያዙ 63 የብሄራዊ ደህንነት ጉዳዮችን በመመርመር ላይ እንደሚገኝ ባለፈው ሳምንት ማስታወቁንም አስታውሷል፡፡