Administrator

Administrator

Monday, 20 April 2015 15:38

የጥረት ፍሬ

ወ/ሮ ውድነሽ መልከ መልካምና የደስደስ ያላት፤ ሳቂታና ተጫዋች ናት። በልጅነቷ ገበያ ላይ ከተዋወቀችዉ ጓደኛዋ ጋር ትዳር መስርታ አንድ ልጅ አፍርተዋል። ከእለታት በአንዱ ቀን ጨለማ ለብርሃን ስፍራዉን ሲለቅ ተነስታ ለባለቤቷ ቁርስ ታዘጋጃለች። ባለቤቷ ደግሞ ቀን ለሚሰራቸዉ ስራዎች የሚያስፈልጉትን ነገሮች ካዘጋጀች በኋላ ቁርሳቸዉን በፍቅር አብረዉ ተመገቡ። ከቁርስ በኋላ ባለቤቷ ሲለባብስ ይንን ልበስ፣ ይህንን ቀይር፤ እዚህ ጋር አስተካክል እያለች ካቆነጃጀችዉ በኋላ የግራ እጆቿን ጣቶች የቀኝ እጆቹ ጣቶች ውስጥ አሰካክታ ከቤት ይዛው ወጣችና እሱ ወደ መኪናው ሲሄድ ቆም ብላ እጆቿን ከእጆቹ በቀስታ አላቀቀች። መኪና ውስጥ ገብቶ ሲያስነሳ ሰራተኛዋን ጠርታ የግቢዉን በር እንድትከፍትለት ነገረቻት። ሰራተኛዋ በሩን ከፍታ ወደነሱ ስትመለከት ወ/ሮ ውድነሽ ጠጋ ብላ ባለቤቷ የለመደዉን የስንብት ሰላምታ ለማግኘት ዝቅ ባደረገዉ መስታወት በኩል ሳም አድርጋዉ በፍቅር ተሰናበተችዉ። ይህን የተመለከተችዉ ሰራተኛዋ በቀኝ እጇ አፏን እንደመሸፈን ብላ በማፈር መንፈስ ወደ መሬት አቀረቀረች።  ባለቤቷ አቶ ወርቅነህ ግቢውን ለቆ ሲወጣ ወ/ሮ ውድነሽ በሩን ዘግታ ከሰራተኛዋ ጋር ወደ ቤት ተመለሱ።
ሰራተኛዋ የተለመደውን አልጋ የማንጠፍ፣ ቤት የማጽዳት፣ እቃ የማጣጠብ ስራዋን ጨርሳ ወደሚቀጥለዉ ምግብ የማብሰል ስራዋ ልትሄድ ስትዘጋጅ ስትመለከታት የነበረችዉ ወ/ሮ ውድነሽ አንዳች ነገር ልቧን ደቃትና “ፈለጉሽ ነይ እሰኪ!” ብላ ወደራሷ ጠራቻት። ሰራተኛዋ ስራዎቹን የምትሰራዉ በግዴለሽነት ነዉ። በህይወቷ ለማሳካት የምትፈልገዉ ምንም አይነት ህልም የላትም። ያላትን መልካም አጋጣሚዎች ሁሉ ሳትጠቀምባቸው ታባክናለች። ገና ከገጠር ወደ ከተማ ስትመጣ  በአንዳንድ ጓደኞቿ እና አጉል ተስፋ በሚሰጡ ሰዎች ተገፋፍታ ትምህርቷን ቤተሰቧ ጋር ሆና በአግባቡ ትምህርቷን እየተማረች ካለችበት አቋርጣ የመጣችዉ። አሁን ደግሞ ያቋረጠችዉን ትምህርቷን ማታ ማታ እንድትቀጥል ወ/ሮ ውድነሽ ከስራ ነጻ በማድረግ ሁኔታዎችን ብታመቻችላትና ብትገፋፋትም ፈቃደኛ አልሆነችም። የምትሰራበትን ገንዘብ እንኳን አጠራቅማ እራሷን ለመለወጥ አትጥርም። ‘የማይረቡ ነገሮችን’ በመግዛት አበካክና ትጨርሳለች። እናም ወ/ሮ ውድነሽ ሁሌ ትመክራታለች፤ እሷ ግን መስማት እንጂ ወደተግባር ስትለውጥ አትታይም። በዚያን እለት ግን ትምህርት እንዲሆናት ብላ የራሷን የልጅነት ልፋት ኮስተር ባለ መንፈስ እንደተሞክሮ አካፈለቻት።
“ይኸዉልሽ ፈለጉሽ፣ ነገ የተሻለ ህይወት ለመኖር ዛሬን መጣጣር ያስፈልግሻል። እኔ ከወላጆቼ የወረስኩት ገንዘብና እውቀት አልነበረም። ስለዚህም ገና ትንሽ ልጅ እያለሁ ኑሮዬን የተሻለ ለማድረግ በሰፈር ውስጥ ድንች፣ ቃሪያ፣ ሽንኩርት፣ጎመን…የመሳሰሉትን እየቸረቸርኩ ለራሴ የሚያስፈልጉኝን አንዳንድ ነገሮች እገዛ ነበር። በዚያ ሂደት ከጊዜ በኋላ ትንሽ ብር ማጠራቀም ቻልኩኝ። ያጠራቀምኩትን ብር ይዤ የቻለልኝን ያክል እቃ ገዝቼ እያዞርኩ ሱቅ በደረቴ መስራት ጀመርኩኝ። ስራዉን እየሰራሁ የበለጠ ገንዘብም እያገኘሁ እያለ አንድ ቀን …” እንዳለች ትካዜ ውስጥ ገባችና ንግግሯን አቋረጠች።
“እንዴ እትዬ ምነው ቆዘሙሳ?” አለቻት ሰራተኛዋ።
ለሴኮንዶች ጸጥ ካለች በኋላ “አይ ምንም አይደለም” ብላ ጨዋታዋን ቀጠለች። “እ…በእለቱ የእግረኛ መንገድ ዘግተን እንዳንሸጥ ፖሊስ ሲያባርረን ለማምለጥ የመኪና መንገድ እያቋረጥኩ ስሮጥ ከባድ የመኪና አደጋ ደረሰብኝ። በዘመድ አዝማድ ድጋፍ ጭምር ህክምና ባገኝም ከልጅነቴ ጀምሮ ከግራ እጄ ጋር ጉዳት የነበረበት የቀኝ እግሬ ከአገልግሎት ውጪ ሆነ” ብላ እምባ እየተናነቃት በአውራ ጣቷ እና በአመልካች ጣቷ ሁለት ዓይኖቿን ከድና ይዛ ወደታች አቀረቀረች።
“አይዞት እትዬ፤ እግዚአብሄር ይማሮት” አለቻት ሰራተኛዋ በሀዘኔታ።
“አዎ ምሮኛል!” ብላ ቀና አለችና ጨዋታዋን ቀጠለች ወ/ሮ ውድነሽ። “ታዲያ ያን ጊዜ ተስፋዬ ጨልሞ ምን ማድረግ እንዳለብኝ ባላወኩበት ጊዜ የአማራ ክልል የሴቶች ጉዳይ ቢሮ ከባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ጋር በመተባበር ፍላጎት ላላቸዉ ሴቶች መጠነኛ ብድርና የመስሪያ ቦታ እንደሚያመቻቹ ሰማሁ። በዚያ ሁኔታ ውስጥ ሆኜ ጉዳዩን ማጣራትና መከታተል ያዝኩኝ። በመጨረሻም በአካል ጉዳተኝነት ቅድሚያ እድሉን በማግኘቴ ተስፋዬ አንሰራርቶ  መደብ ይዤ እጉልት የንግድ ስረዬን መስራት ጀመርኩኝ። ከዚያ ጊዜ በኋላ የሚያጋጥሙኝን ፈተናዎች ሁሉ በጽናት በማለፍ ይኸዉ ለዚህ በቅቻለሁ። አንቺም ነገ ኑሮሽን ለመቀየር ዛሬ መጣጣር አለብሽ” ብላ አጠንክራ ነገረቻት።
“እሺ እትዬ፤ እጥራለሁ!” አለች ሰራተኛዋ።
እናትና አባት ወደ ባህር ዳር የመጡት የእድሜያቸውን እኩሌታ ካሳለፉበት የደቡብ ጎንደር ገጠራማ አካባቢ ሲሆን ወ/ሮ ውድነሽ ግን የተወለደችዉ ባህረ ዳር ነው። ከመጻፍና ማንበብ ያለፈ ምንም ትምህርት አልተማሩም። በሚያባትል የኑሮ ውጣውረድ ተጠምደዉ እላይ እታች ዱብዱብ ሲሉ የኖሩ ናቸው። አባቷ የቀን ስራና ያገኙትን ተባራሪ ስራ በመስራት ህይወትን ሲመሩ የኖሩ ሲሆን እናቷ ደግሞ የሰው ቤት በተመላላሽ ሰራተኝነት እና በሰፈር ውስጥ ልብስ በማጠብ በሚያገኟት ገቢ ኑሯቸዉን ሲደጉሙ የኖሩ ናቸው።
ወ/ሮ ውድነሽ ታዲያ በልጅነቷ ወደ ትምህርት ቤት እንድትገባ ከወላጆቿ ሁኔታዎችን የማመቻቸትም ሆነ የመገፋፋት እድል አልገጠማትም። ‘ከጓደኞቼ አልቀርም’ እያለች በማልቀስ  እና ብሶ ሲመጣም ‘ከጓደኖቿ በታች አታድርጓት’ እያስባለች በጎረቤቶቻቸው በማስነገር የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቷን አጠናቃለች። ከቤት ሳትወጣ የቤት ውስጥ ስራ ብቻ እንድትሰራ ነበር የቤተሰቦቿ ፍላጎት። ‘ሴት ልጅ በማጀት ውላ የቤት ዉስጥ ስራ ብቻ ስትሰራ ተፈላጊነቷ ይጨምራል፤ ከቤት ወጥታ አደባባይ ከዋለች ግን እሷ አለሌ ናት እየተባለች ተፈላጊነቷ ይቀንስና ቆማ ትቀራለች’ የሚለው ለዘመናት በህብረተሰቡ ውስጥ ሰርጾ የቆየ አባባል በወ/ሮ ውድነሽ ቤተሰቦችም ዘንድ የጸና ነበር። ከዚህ ሌላ ደግሞ አካል ጉዳተኛ በመሆኗ ብዙ የእድሜ እኩዮቿ ይርቋት ስለነበርና የአካባቢዉ ሰዎችም በተለየ ሁኔታ ያይዋት ስለነበር ‘የተረገመ ዘር አለባቸዉ’ ብሎ ህብረተሰቡ እንዳያገላቸዉ በመስጋትም ጭምር ነበር ከቤት እንዳትወጣ ጥረት ያደርጉ የነበረዉ። ሌላው ቀርቶ እንግዳ ወደ ቤታቸዉ ሲመጣ እንኳን ፊት ለፊት እንዳትታይ ወደጓዳ እንድትገባ ያደርጓት ነበር።
ሰራተኛዋን ለመምከር ካደረገችዉ ጥረት በኋላ ያለፈዉ መጥፎ ትዝታ መንፈሷን ስለረበሸዉ ወ/ሮ ውድነሽ ትንሽ እረፍት ለማግኘት ባለ አንድ ፎቅ የሆነው ቤታቸው አናት ላይ ወዳለዉ ክፍት ቦታ ወጥታ አረፍ አለች። ባለችበት ሆና ግቢዉን በዓይኗ መቃኘት ጀመረች። ግቢያቸዉ በጣም ሰፊና የተዋበ ነው። በልዩ ልዩ አበባ እና በተፈጥሮ ሳር ፈርጅ ፈርጅ ባለው መልኩ የተሸፈነ ነው። እጸዋቱ ለዓይን ከመማረካቸዉ ባሻገር ግቢውን ነፋሻማ አድርገዉታል። ከውሻ ቤት ጀምሮ በግቢዉ ውስጥ ያሉ ክፍሎች በንጽህና የተያዙ ናቸዉ።  
በዓይኗ ግቢዉን እየቃኘች ሆዷ ውስጥ የሆነ ስሜት ተሰማት። ወዲያዉ በኋላ ባለቤቷ አቶ ወርቅነህ ትዝ ላት እና ለራሷ ፈገግ አለች። አንድ ቀን ከዋለበት የንግድ ስራዉ ሲመጣ ወ/ሮ ወድነሽን አልጋ ላይ አገኛት። በቀስታ ወደ እሷ ካመራ በኋላ፤
“የኔ ውድ፤ ስላም ዋልሽ?” ብሎ በፍቅር ሳም አደረጋት።
“ደህና ነኝ” አለችዉ በደንብ እየነቃች።
ወደታች ወረድ ብሎ ሆዷን ዳበስ እያደረገ “እንዴት ነው ይህ ጎረምሳ?” አላት።
ሳቅ እንደማለት ብላ “ጎረምሳ መሆኑን እንዴት አወቅክ? ጎረመሲት ናት!” አለችዉ እና ሁለቱም ተያይተዉ ተሳሳቁ።
ወ/ሮ ውድነሽ ድርስ ናት። ካረገዘችበት ጊዜ ጀምሮ የምታሳያቸዉ በየጊዜዉ ስሜቶቿ ይቀያየራሉ። እርግዝናዉ ከአካል ጉዳተኝነቷም ጋር ተዳምሮ ጫና እንዳይፈጥርባት አቶ ወርቅነህ አጥብቆ ከጎኗ በመሆን የምትፈልገዉን ሁሉ አቅሙ በፈቀደዉ መጠን በማሟላትና በመንከባከብ የድረሻዉን ይወጣል።
በዚያች ቅጽበት በሃሳብ ሰረገላ እየጋለበች ከባለቤቷ ጋር ያሳለፈቻቸውን መልካም ጊዜ በዓይነ ህሊናዋ መቃኘት ጀመረች።
ሁለቱም አብረዉ ብዙ ጊዜ በእግር ጉዞ የደርጉ ነበር። ከእለታት በአንዱ ቀን አመሻሽ ላይ የእግር መንገድ ለማድረግ ተያይዘዉ ወጡ። በእለቱ የእግር ጉዞውን ለማድረግ የወሰኑት ለቤታቸዉ ቅርብ ወደሆነው ጣና ሃይቅ ዳርቻ በመሆኑ ወደዚያዉ ተጓዙ። የሃይቁ ዳርቻ ሸክላማ ድንጋይ የተነጠፈ በመሆኑ ለአግር ጉዞ በጣም ተመችቷቸዋል። ከመንገዱ በቀኝ በኩል ሃይቁን ተንተርሰዉ በተሰሩ የሃይቅ ዳርቻ መዝናኛዎችና ለምለም እጸዋት አይናቸዉ ተማርኳል። ወደ ግራ ዞር ሲሉ ደግሞ  ሃይቁና ሰማዩ የተገናኙበት የሚመስል ቦታ ላይ በግማሽ የጠለቀችው ፀሐይ በቀረዉ አካሏ በምትለቀዉ ፍም እሳት በሚመስለዉ ብርሃኗ የውሃው ገጽ ላይ የተለየ ማራኪ ሁኔታን ፈጥራላቸዋለች። በስፍራዉ በሚታየዉ ነገር በሙሉ መንፈሳቸዉ ታድሷል። ለእግር ጉዞዉ ከተነጠፈዉ ሸክላማ ድንጋይ መጨረሻ ሲደርሱ ከመመለሳቸው በፊት ሀይቁ ዳር አረፍ ብለው የዱሯቸዉን ማውጋት ጀመሩ።
አረፍ ብለዉ ትንሽ እንደቆዩ  “ፍቅሬ! ጉልት ሰፈርን ታሰታውሰዋለህ?” ብላ ጠየቀችዉ ወ/ሮ ውድነሽ።   


“እሱማ እንዴት ይረሳል የኔ ፍቅር። ለዛሬዉ ማንነታችን መሰረቱ እሱ አይደል?” አላት በፈገግታ በተሞላ ፊት አይን አይኗን እያየ።
“እሰኪ ከዚያ የማትረሳዉን ነገር ንገረኝ!” አለችዉ የጉንጩን ጺም እየደባበሰችና አይኑን በቆረጣ እያየች እያየች።
“እ…እዛማ የሚፈራረቅብን ፀሃይና ዝናቡ፣ እቃ አልሸጥ ሲለን ሌላ እቃ ማምጣት ሲያቅተንና በጣም ስንቸገር፣…ከሁሉም በላይ የማልረሳዉ ደግሞ ከንግድ ቢሮ ነዉ የመጣነዉ ያሉ ግለሰቦች የንግድ ፈቃድ ሳይኖራችሁ መስራት አትችሉም ብለዉ መደባችን ፈራርሶ ከቦታችን ተፈናቅለን የተንገላታነዉ ነዉ” አላት።
“ኡ…ያን ጊዜማ አታንሳዉ!” አለችዉ ወ/ሮ ውድነሽ እጆቹን ጥብቅ አድርጋ እየያዘችና ትኩር ብላ እየተመለከተችዉ።
“አይዞሽ ውዴ! አሁንኮ አልፏል” አላት ዘና ባለ መንፈስ።
ቀጠል አደረገችና “ያኔ እኮ እኔ ተስፋ ቆርጬ በህይወቴ ወደኋላ የተመለሰኩበት ጊዜ ነበር” አለችው አዘኔታ በተሞላበት ድምጸት።
ወደራሱ እቅፍ እያደረገ “አዎ! ግን ያው የተለያዩ አካላት…” ሲል ሳታሰጨርሰዉ ቀበል ብላ፤
“እሱማ ነዉ።  በሴቶች ዙሪያ የሚሰሩ የተለያዩ አካላት ተቀናጅተዉ የመስሪያ ቦታችን ከበፊቱ በተሻለ መልኩ መጠለያም እንዲሰራለት፣ ለመንቀሳቀሻ ብድር እንዲመቻችልን እንዲሁም የንግድ ስራችንን እንዴት መስራትና ውጤታማ መሆን እንደምንችል ስልጠና እንድናገኝ ድጋፍ ካደረጉልን በኋላ እኮ ነዉ ወደራሴ ተመልሼ እንደገና በወኔ መንቀሳቀስ የጀመርኩት” አለችዉ።
“ከዚያ በኋላ እኮ በቃ እንደ ጥይት ተተኮስሽ” አላት ፈገግ እያለ።
“ታዲያስ! ከዚያማ ብርታት አግኝቼ ወደኋላ ላልመለስና በህይወቴ ውደፊት ብቻ ለመጓዘዝ አመረርኩኝ” ብላ እንደ መቀለድ አለችና ሳም አደረገችዉ።
ወዲያው ዞር ብሎ ተመለከተና፤ “ጨለማ እየመጣ ነዉ፤ ሰው ሁሉ ሄዶ ጭር ብሏል። እንነሳ” ብሏት እነሱም ወደ ቤታቸዉ ጉዞ ቀጠሉ። በመንገድ ላይ እሷ በግራ እጇ እሱ ደግሞ በቀኝ እጁ አንዱ የሌላኛው ወገብ ላይ በማሳረፍ ተቃቅፈዉ ነበር የሚጓዙት። ወደ ቤታቸዉ አቅራቢያ ሲደርሱ ወ/ሮ ውድነሸ ድንገት “ያዝ!” ብላ ክራንቿን ለአቶ ወርቅነህ ሰጠችው። “እንዴ ኧረ እንዳትወድቂ!” ብሎ ጮኸባት። “አይዞህ አታስብ ሌላ ምረኩዝ አለኝ። የጉልት ንግዴ በተቃወሰበት ጊዜ እንድጠነክር በማበረታታት፣ የገበያ አማራጮችን በማፈላለግ፣ የተሻለ ገቢ እንድናገኝ እና ከጉልት ወደ መደበኛ ሱቅ በመሸጋገር የንግድ ስራችን እዚህ ደረጃ እንዲደርሰ ከጎኔ ሆኖ ያበረታታኝና መቻሌን ይመሰክርልኝ የነበረ ምረኩዝ አለኝ።” አለችዉ ጭንቅላቷን በራስ መተማመን መንፈስ ወደላይ እና ወደታች እያንቀሳቀሰች።
“ምን እያልሸሀ ነዉ? ማንን ነዉ?” ብሎ ጠየቃት በአግራሞት መንፈስ እያያት።
ሳቅ እያለች በአመልካች ጣቷ ወደሱ ጠቆመች። እሱም እየሳቀ ወደራሱ አሰጠግቶ እቅፍ አደረጋት እና “ ይህንን እኮ በማድረጌ አንቺ ብቻ ሳትሆኚ እኔም ነኝ የተጠቀምኩት” አላት።
“እሱስ ልክ ነህ። መቼም ሁሉም ወንዶች እንዲህ የሚያስቡበት ጊዜ መምጣቱ አይርም” አለችዉ።
ሁለታቸዉም ተያይተዉ ተሳሳቁ። በወ/ሮ ውድነሽ በዚህ ትዝታ ውስጥ እያለች፤
“እትዬ!” የሚል ድምጽ አባነናት።
“ወይ” አለች በሃሳብ በነጎደችበት ሰረገላ ወደገሃዱ ዓለም እየተመለሰች።
ሰራተኛዋ ነበረች ምሳ እያቀራረበች የተጣራችው።
ወ/ሮ ውድነሽ በጣም ጠንካራ፣ በተስፋ የተሞላች እና ፈተና እንኳን ሲገጥማት ከጨለማ ዛሬ በስተጀርባ ብርሃን የሆነ ነገ እንዳለ የምታስብ ናት። በችግር ውስጥ ሆና ጥቃቅን መልካም አጋጣሚዎችን በመጠቀም ባገኘችው ቀዳዳ ሾልካ በመውጣት በህይወት መንገድ ላይ ጉዞዋን የምትቀጥል ሴት ናት። እንኳንስ ሴትነት አካል ጉዳተኝነት ለስኬት እንቅፋት ያልሆነባት ብርቱ የሆነች ሴት ናት። በመሆኑም የተለያዩ ሸቀጣ ሸቀጦችን ያከፋፍሉበት ከነበረዉ ሱቅ በማሻሻል ያለቀላቸዉ የቆዳ ምርቶችን ለአገልግሎት ዝግጁ በማድረግ ‘በኢትዮጵያ የተሰራ’ የሚል ጽሁፍ እያተሙበት ወደ ውጭ መላክ ደረጃ ላይ ደርሰዋል። ምርቶቻቸዉ የበረካታ አገራት ገበያን ሰብረዉ መግባት የቻሉ ናችው። ድርጅታቸውን እሷ በስራ አስኪያጅነት ባለቤቷ ደግሞ በምክትል ስራ አስኪያጅነት ይመሩታል። አሁን ግን እሷ ሁለተኛ ልጃቸውን እርጉዝ በመሆኗ ወልዳ እስክትነሳ ባለቤቷ እሷን ተክቶ ድርጅቱን ይመራል።
ዛሬ ላይ ወ/ሮ ውድነሽ ህይወቷ ተቀይሯል። እንደዚህ አይነት ኑሮ እኖራለሁ ብላ አስባም አታውቅም። ስታስበዉ ለራሷም በጣም ትገረማለች። እሷ የሚገጥማትን ፈተናና ጫና በማለፍ ለበለጠ ውጤት መትጋት ላይ ነበር ሁል ጊዜም ትኩረቷ። ጥረቷም ፍሬ አፍርቶ አሁን ላይ ከራሷና ከቤተሰቧ አልፋ በድርጅታቸዉ ውስጥ ለበርካታ ሰዎች የስራ እድል መፍጠር ችላለች።ሴቶች ሁሉ እንደሷ ጠነክረው በመስራት ከራሳቸውና ከቤተሰባቸዉ አልፈዉ ለሃገራቸው እድገት አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ አጥብቃ ትሻለች። በዘር፣ በጎሳ፣ በሃይማኖት፣ በቀለም እና በጾታ ሳትለያይ የሰውን ልጅ ሁሉ በምትችለዉ አቅም መርዳት ትፈልጋለች። በርካቶችንም ባገኘችው አጋጣሚ በገንዘብና በሃሳብ በመደገፍ በህይወታቸዉ አንድ እርምጃ ወደፊት እንዲጓዙ ምክንያት ሆናላቸዋለች። ለዚህ ስኬቷ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት የተደረገላትን ድጋፍ እንደ ምክንያት ብትጠቅሰውም የአማራ ክልል ነጋዴ ሴቶች ማህበር ሚና ግን የጎላ እንደሆነ ትገልጻለች ወ/ሮ ውድነሽ። በዋናነትም በማደራጀት፣ ስልጠና በመስጠት፣ የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ በማድረግ እና የገበያ ትስስር እንዲፈጠርላቸዉ በማድረግ ለርካታ ሴቶች ለውጤት መብቃት ማህበሩ የተጫወተዉ ሚና አሌ የማይባል መሆኑን በመጥቀስ ሁሌም ታመሰግናለች። ኧረ እንዲያዉም አንዳንዴ የአማራ ክልል ነጋዴ ሴቶች ማህበርን ‘የህይወት ጉዞ ማርሽ አስቀያሪ’ ትለዋለች። ብዙ ሴቶች የጥረታቸዉን ፍሬ እንዲበሉ ከጐኗቸዉ በመሆን ደግፏቸዋልና።


በደቡብ አፍሪካ፣ በየመን፣ በጣሊያን
        ከምስራቅና ከምዕራብ አቅጣጫዎች የምንሰማው መረጃና ዘገባ፣ ከደቡብም ከሰሜንም የምናየው የፎቶና የቪዲዮ መረጃ፣ የግርግርና የትርምስ ወሬ ሆኗል። ቀደም ሲል በሳዑዲ አረቢያና በደቡብ ሱዳን፣ ዘንድሮ ደግሞ በተለይ ሰሞኑን በደቡብ አፍሪካ፣ በየመን፣ እንዲሁም ከሊቢያ ወደ ጣሊያን በሚያሻግረው የሜዲትራኒያን ባሕር ላይ የተከሰቱ ቀውሶችን ተመልክታችኋል። በደቡብ አፍሪካ ማክሰኞ እለት በተቀሰቀሰው የጅምላ ዘረኛ ጥቃት፣ ኢትዮጵያዊያን ሰለባ ሆነዋል። የጅምላ ጥቃቱ፤ በአስር ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ፣ ከተለያዩ የአፍሪካ አገራት የመጡ ወደ 3 ሚሊዮን ስደተኞችን ለአደጋ አጋልጧል። በዚሁ ሳምንት፣ በጦርነት በታመሰችው ሊቢያ በኩል አስር ሺ ስደተኞች ወደ አውሮፓ ለመግባት ሲሞክሩ፣ አንድ ጀልባ ተገልብጣ ከአራት መቶ በላይ ስደተኞች ሞተዋል። ይህም ብቻ አይደለም። የጎሳ ግጭትና ሃይማኖታዊ ጦርነት ባመሳቀላት የመን ውስጥ የሚገኙ በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን፣ መግቢያ መውጪያ አጥተዋል።
እንደ ድሮ ቢሆን፣ በሌሎች አገራት የሚፈጠሩ ቀውሶችና ግጭቶች፣ በቀጥታ ሕይወታችንን የመንካት ቅርበት ይኖራቸዋል ብለን ስለማንገምት ያን ያህልም ባላስጨነቁን ነበር። በአፍሪካ የሰሜንና የደቡብ ጠረፎች፣ በአረብና በአውሮፓ አገራት ድንበሮች ላይ የሚፈጠሩ ችግሮች፣ ከሕይወታችን ጋር የቅርብ ግንኙነት ይኖራቸዋል ብለን ካላሰብን ለምን ያስጨንቀናል? በዚያ ላይ፣ እንደ ድሮ ቢሆን፣ ስለ ቀውሶቹ በዝርዝር የምናውቅበት ሰፊ እድል ባላገኘን! አንድ ደቂቃ ከማትሞላ የዜና ቁራጭና ከተባራሪ ወሬ ያለፈ መረጃ አናገኝም ነበር።
ዛሬ ግን እንደድሮ አይደለም። እስከተጠቀምንበት ድረስ፣ የመረጃ ባዕድ ወይም የአፈና ሰለባ የማንሆንበት እድል ተፈጥሯል - የሳተላይት ዲሽና ኢንተርኔት በመሳሰሉ የሳይንስና የቴክኖሎጂ ውጤቶች። የቢዝነስ ድርጅቶች ደግሞ፣ ቴክኖሎጂውን ወደ ምርትና ወደ ንግድ አሳድገው፣ ለአለም አዳርሰውታል። የየትኛውም ሃይማኖትና እምነት ተከታይ አልያም የየትኛውም አገርና ብሔር ብሔረሰብ ተወላጅ ብንሆን ለውጥ የለውም። አፕል እና ሳምሰንግ የመሳሰሉ የሞባይል ቀፎ አምራች ኩባንያዎች፤ እንዲሁም ጉግል፣ ፌስቡክ እና ዩቱብ የመሳሰሉ የቢዝነስ ኩባንያዎች፤ ቴክኖሎጂው እጃችን ውስጥ እንዲገባ አድርገዋል። ቴክኖሎጂውን የመጠቀም ምርጫና ብቃት፣ የግል ምርጫችን እንዲሆን ሰፊ እድል ከፍተውልናል። አይገርምም? በጥቂት ዓመታት ውስጥ የመጣ ተዓምረኛ ለውጥ ነው። ምን ለማለት ፈልጌ ነው?
አንደኛ፤ በጭፍን እምነት፣ በጭፍን “ባህል” እና በጭፍን ፕሮፖጋንዳ ምትክ፤ ለአእምሮ ክብር የሚሰጥ ሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና የመረጃ ነፃነት ሲስፋፋ.... ሁለተኛ፤ በመንግስት ገናና የኢኮኖሚ ቁጥጥር፣ በድጎማና በጥገኝነት ፋንታ፤ ለብልፅግና ክብር የሚሰጥ ቢዝነስ፣ ንግድና ትርፋማነት ሲያድግ... ሦስተኛ፤ በጅምላ ፍረጃ፣ በቡድናዊነትና በብሔረተኝነት (በዘረኝነት) ምትክ የእያንዳንዱ ሰው ማንነት እንደየግለሰቡ ብቃት፣ ባህርይና ሰብእና የመመዘን ፍትሃዊነትና የእኔነት ክብር ሲስፋፋ፣ የሰው ልጅ ድንቅ ተዓምሮችን ይሰራል። እነዚህ ሦስቱ ነጥቦች (ሳይንስ፣ ካፒታሊዝም እና የግል ማንነት) መሰረታዊዎቹ የስልጣኔ እሴቶች መሆናቸውን ልብ በሉ።
ለነገሩ፤ በየአቅጣጫው የምናየው የኢትዮጵያዊያን ስደትም፤ ከእነዚሁ ሦስት የስልጣኔ እሴቶች ጋር የተቆራኘ ነው። የዚህን ወይም የዚያን ሃይማኖት እምነትንና ቀኖና ፈልገው አይደለም የሚሰደዱት። የአገር ወይም የብሔር ብሔረሰብ ጥንታዊ ባህልን፣ ቋንቋንና የጅምላ ማንነትን ፍለጋ አይደለም የሚሰደዱት። ለመንግስት ቁጥጥር ለመገዛት፣ አልያም የመንግስት ጥገኛ ሆነው ድጎማ ለመቀበል ጓጉተው፣ ወይም የሃብት ልዩነት የሌለበት አለም ናፍቋቸው አይደለም የሚሰደዱት። በተቃራኒው፤ ለሃይማኖትና ለእምነት ልዩነት ቦታ ባለመስጠት ነው የሚሰደዱት። የጥንታዊ ባህልና የተወላጅነት ልዩነቶችን ወደ ጎን በማለት ነው የሚሰደዱት። ለመንግስት ድጎማና ለሃብት ክፍፍል ቦታ ባለመስጠትም ነው የሚሰደዱት።
ይልቅስ፣ በሃይማኖት ላይ ሳይሆን በአእምሯቸው ላይ ተማምነው፣ በተወላጅነት ላይ ሳይሆን በግል ብቃታቸው ላይ ተማምነው፣ በመንግስት ድጎማ ሳይሆን በራሳቸው ጥረት ሃብት አፍርተው ሕይወታቸውን ለማሻሻል ነው የሚሰደዱት - የመበልፀግ መልካም ምኞታቸውን እውን ለማድረግ። በአጭሩ፤ ሦስቱ የስልጣኔ እሴቶችን የተላበሱ ናቸው። ነገር ግን፣ የስልጣኔ ፊታውራሪዎች ናቸው ማለት አይደለም። በጭራሽ። እንደአብዛኛው ሰው ሁሉ፣ ስደተኞችም በአብዛኛው ከስልጣኔ እሴቶች ጋር፣ ፀረ ስልጣኔ አዝማሚያዎችንም አዋህደው የያዙ ናቸው። እንዴት በሉ።
ዘመኑ የስልጣኔ ዘመን አይደለም። ከስልጣኔ እሴቶች በተቃራኒ፣ ሦስት የስልጣኔ እንቅፋቶች በዓለም ዙሪያ ያንሰራሩ የመጡበት ዘመን ላይ ነው የምንገኘው - የጭፍን እምነት ስብከትን የሚያራግብ የሃይማኖት አክራሪነት፣ የሃብት ክፍፍል ዲስኩር የሚዘወተርበት የመንግስት ገናናነት፣ ጥንታዊ ባህልን በማምለክ የሚለፈፍበት ዘረኝነት፣ እንደ አሸን ሲፈሉ የምናየው ለምን ሆነና! በእነዚህ ሦስት ፀረስልጣኔ አቅጣጮች ምክንያት የሚከሰቱ ቀውሶችን ነው በአለም ዙሪያ የምናየው - (የአውሮፓ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ቀውስ፣ የመካከለኛው ምስራቅ ሃይማኖታዊ ሽብርና ጦርነት፣ የአፍሪካ የዘረኝነትና የጎሳ ትርምስ)። ኢትዮጵያውያን ስደተኞችም በየቦታው ሰለባ እየሆኑ ነው።  
ለነገሩ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየባሰበት ቢመጣም፣ አምናም ተመሳሳይ ነገሮችን እንዳየን የምንረሳው አይመስለኝም። “የአገርን ሃብት ትቀራመታላችሁ፤ የስራ እድልን ታጣብባላችሁ፤ ሃይማኖትን የሚቃረን ባህርይ ታስፋፋላችሁ” በሚል፣ ከመቶ ሺ በላይ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ከሳዑዲ ዓረቢያ ሲባረሩ አይተናል። በጥንታዊ የባህል ልዩነትና በጎሳ ተወላጅነት የተቧደኑ የደቡብ ሱዳን ታጣቂ ጎራዎች ከፈጠሩት ጦርነት ጋር በተያያዘም፣ “መጤዎች የአገራችንን ወይም የጎሳችንን ሃብት ይመዘብራሉ” በሚል በርካታ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ለአደጋ መጋለጣቸውን እናስታውሳለን። ዘንድሮም ተመሳሳይ ነው።
ከላይ እስከ ታች በጦርነት እየነደደች ባለችው የመን ውስጥ፤ በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ተስፋቸው ምን ሊሆን እንደሚችል አስቡት። እንደ ሌላው ዓለም በኢኮኖሚ የተቃወሰችው የመን፣ አንደኛውን ለይቶላት በጎሳ ግጭትና እና በሃይማኖታዊ ጦርነት ስትታመስ ይሄውና ዓመት ሊሆናት ነው። እንዲያም ሆኖ፣ በዓመት ውስጥ ከ60ሺ በላይ ኢትዮጵያዊያን ባህር አቋርጠው የመን ገብተዋል። የአገሪቱ ጦርነት ከመርገብ ይልቅ እየተባባሰ ከመምጣቱም በተጨማሪ፣ ውስጥ ውስጡን ሺዓ እና ሱኒ በሚል ሲፎካከሩ የቆዩት የኢራንና የሳዑዲ ዓረቢያ ጎራዎች አሁን በይፋ ገብተውበታል። ኢራን የጦር መርከቦችን ስታሰማራ፣ ሳዑዲ በበኩሏ በጦር አውሮፕላኖች የድብደባ ዘመቻ ስታካሂድ ሰንብታለች። እንዲያም ሆኖ፣ የዩኤን መረጃ እንደሚያመለክተው በመጋቢት ወር ብቻ ከ3ሺ በላይ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የመን ገብተዋል። ያሳዝናል፤ ግራ ያጋባል። ግን አዲስ ክስተት ካለመሆኑም በተጨማሪ፤ እልባትና መፍትሄ የሚገኝለት አይመስልም።
በደቡብ አፍሪካ፣ የኢትዮጵያዊያን ስደተኞችን ሕይወት የቀጠፈው የሰሞኑ ዘረኛ ጥቃትም፣ ድንገተኛ አዲስ ክስተት አይደለም። ለአመታት ሲንተከተኩ በዘለቁ ፀረ ስደተኛ ስሜቶች፣ በተለይ ደግሞ ከጥቅምት ወር ጀምሮ በየአካባቢው ሲቆሰቆሱ በቆዩ ጥቃቶች ምክንያት የተጨነቁ በርካታ የረድኤት ድርጅቶች፣ “ይሄ ነገር አደገኛ ነው” እያሉ ለማስጠንቀቅና ለመምከር ሲሞክሩ ከርመዋል። አንዳንዶቹም፣ “የተወሰኑ ስደተኞች ወንጀል ስለፈፀሙ፣ ስደተኞችን በጅምላ አትጥሉ። እያንዳንዱን ስደተኛ በግል ተግባሩ እንዳኘው። በርካታ ስደተኞች በራሳቸው የግል ጥረት ሃብት በማፍራትና ሃብት በመፍጠር ለአገሪቱ ኢኮኖሚ ጠቃሚ አስተዋፅኦ ያበረክታሉ” በማለት መከራከሪያ ለማቅረብና ለማሳመን ተጣጥረዋል። በተጨባጭ መረጃ የተደገፈ ጥናታዊ ፊልም፣ ዘገባ እና መግለጫ በማሰራጨት የጥላቻ ስሜቶችንና የጅምላ ፍረጃን ለማርገብ ደፋ ቀና ብለዋል። ምን ያደርጋል? ብዙዎቹ ሰሚ አላገኙም። ሰሚ ያገኙትም፣ የሚያምናቸው አላገኙም። ጥረታቸውና ሙከራቸው፣ ከመነሻው ከንቱ እንደሆነ አላወቁም። ድንገት ተነስተው፤ “ስለ ተጨባጭ መረጃ፣ ስለ ሃብት ፈጠራ፣ ስለ ግል ማንነት” የሚያወሩት ነገር ውጤት አላስገኘም። ለምን ቢባል፤ አብዛኞቹ የረድኤት ድርጅቶችን ተመልከቷቸው።
ከፊሎቹ የእርዳታ ድርጅቶች፣ የምዕራባዊያንን የሳይንስና የስልጣኔ እመርታን የሚያወግዙ የሃይማኖት ሰባኪዎች ናቸው። በአንድ በኩል ጭፍን እምነትን እየሰበኩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ “እባካችሁ ለተጨባጭ መረጃ ክብር በመስጠት ከጭፍን ስሜታዊነት መታቀብ ያስፈልጋል” ቢናገሩ ማን ይሰማቸዋል? ከንቱ ንግግር ነው።
ከፊሎቹ የእርዳታ ድርጅቶች ደግሞ፣ በ“ሃብት ፈጠራ” ላይ ሳይሆን በ“ሃብት ክፍፍል” ላይ የተመሰረተ ሶሻሊስታዊ የኢኮኖሚ አስተሳሰብ በማንገብ የምዕራባዊያንን የካፒታሊዝም ዝንባሌ የሚያጥላሉ ናቸው።
“የሆነ የአገር ሃብት አለ። ዋናው ቁምነገር፣ ያንን ሃብት የማከፋፈል ጥያቄ ነው” ብለው ያምናሉ። ሃብት ማፍራትንና ሃብት መፍጠርን እንደቁምነገር ስለማይቆጥሩትም ነው፤ ብዙዎቹ የረድኤት ድርጅቶች ባለሃብቶችንና የቢዝነስ ድርጅቶችን ሲያወግዙ የምንሰማው። “የሆኑ ሰዎች የሚበለፅጉት፣ ሃብት ስለሚያፈሩ ሳይሆን፣ ከአገር ሃብት ውስጥ ከድርሻቸው የበለጠ ሸምጥጠው ስለሚወስዱ ነው” ብለው ያምናሉ። እንደዚህ አይነት እምነት የያዘ ሰው ስደተኞችን መጥላቱ የግድ ነው። ስደተኞችን ባየ ቁጥር፤ “የአገርን ሃብት የሚሸመጥጡ ተጨማሪ እጆች መጡብኝ፤ ድርሻዬን ይቀራመቱብኛል” ብሎ መስጋቱ አይቀርማ። እና፣ እለት በእለት “ስለ ሃብት ክፍፍል” የሚደሰኩሩ የእርዳታ ድርጅቶች፣ ድንገት ተነስተው፣ “ስደተኞች ሃብት ያፈራሉ” የሚል አንድ ጥናታዊ ፊልም ቢሰሩ ቅንጣት ለውጥ አያመጣም።
የባህል ጥበቃን የሚሰብኩ ሌሎቹ የእርዳታ ድርጅቶችም እንዲሁ፣ የምዕራባዊያንን ዝንባሌ ያወግዛሉ - በባህል ወራሪነት ወይም በባህል የለሽነት እየወነጀሉ። “የሰው ማንነት የሚወሰነው በአገሩ ወይም በብሄረሰቡ ባህል ነው” እያሉ ዘወትር የጅምላ ማንነትን የሚሰብኩት እነዚሁ የረድኤት ድርጅቶች፤ ድንገት አንድ ቀን ተነስተው “ከሌላ አገር የመጡ ስደተኞችን አትጥሉ፤ በጅምላ አትፈርጁ” የሚል ቁራጭ መግለጫ ቢያሰራጩ፣ ኢምንት ለውጥ አያመጡም።
ታዲያ፣ ቀውሱ፣ ግጭቱ፣ አደጋው በየአመቱ እየተደጋገመና እየተባባሰ መምጣቱ፣ ከዚያም አልፎ መፍትሄ አልባ መምሰሉ ይገርማል?

“ዕጣው ያልደረሰኝ… ለበጐ ነው”

    የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባለፈው መጋቢት አጋማሽ ላይ 30ሺ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለከተማዋ ነዋሪዎች በዕጣ ማስረከቡን አብስሮናል፡፡ እውነትም የአፍሪካ መዲና የሆነችውና ከ4 ሚሊዮን ህዝብ በላይ ይኖርባታል ተብሎ የሚገመትባት አዲስ አበባ፤ ፈርጀ ብዙ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች እየተካሄደባት የምትገኝ ከተማ ናት፡፡ የከተማው አስተዳደር ከአስር ዓመት በፊት የጀመረው የኮንዶሚኒየም የመኖሪያ ቤቶች ግንባታ አሁን 10ኛ ዙር ላይ ሲሆን 136ሺ ቤቶችም ለነዋሪዎች ተላልፈዋል ተብሏል፡፡
የኮንዶሚኒየም ቤቶች ግንባታ በመሰረቱ የድሃውን ህብረተሰብ የመኖሪያ ቤት ችግር ይቀርፋል በሚል ዓላማ የተወጠነ ፕሮጀክት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በተጨባጭ ግን በሀገሪቱ በፈጣን ሁኔታ እየገሰገሰ ባለው የኢኮኖሚ ዕድገት ምክንያት ፍላጎትና አቅርቦቱን ማጣጣም ባለመቻሉ፣ የመኖሪያ ቤቶቹን እየተጠቀመ ያለው ድሃው የህብረተሰብ ክፍል ሳይሆን መካከለኛ ገቢና ከዚያ በላይ የተሻለ ገቢ የሚያገኘው የህብረተሰብ ክፍል ነው። ለዚህ መቼም ሳይንሳዊ ትንተና የሚያስፈልገው አይመስለኝም። በየኮንዶሚኒየሙ የተሰቀሉ የቴሌቪዥን ሳህኖች፤ በየፎቁ ስር ተጨናንቀው የቆሙ መኪናዎችና የኮንዶሚኒየም ቤቶች ከፍተኛ የኪራይ ዋጋ በቂ ምስክሮች ናቸው፡፡
ቤቶቹን ድሆች እጣው ደርሷቸው ያከራዩት… ወይም ባለእድሉ ነዋሪ ራሱ ይኑርበት ዜጎች ወጥተው የሚገቡበት ታዛ መገኘቱ በራሱ እሰየው ያስብላል፡፡
ነገር ግን ከ1997 ዓ.ም ጀምሮ እጣ ወጥቶላቸው መኖሪያ ቤታቸውን በአቅም ማነስ ምክንያት መረከብ ያልቻሉ ዜጎች ቁጥር እየተበራከተ መምጣትና እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የቁጠባ ባህልን ማዳበር እንዲችል ለማበረታታት የከተማ ቤቶች ልማት ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በደረሱት ስምምነት መሰረት፣ ባንኩ ለኮንዶሚኒየም ቤቶች መገንቢያ የሚሆን 1ቢሊዮን ብር ለአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ጽ/ቤት በብድር መልክ እንዲሰጥ መወሰናቸው ይታወሳል፡፡
መንግስት በጥናት ደረስኩበት ባለው መሰረት፤ በተጨባጭ የመኖሪያ ቤት ችግር ያለበት ድሃው የህብረተሰብ ክፍል እጣው በወጣለት ወቅት የሚጠየቀውን ቅድሚያ ክፍያ ማሟላት አለመቻሉን ታሳቢ በማድረግ፣ የ1997 ዓ.ም ተመዝጋቢዎችን ዳግም በመጥራት እንዲሁም አዲስ ተመዝጋቢዎችን አካቶ በሰኔ ወር 2005 ዓ.ም ላይ ባካሄደው ምዝገባ፣ ከ900ሺ በላይ ቤት ፈላጊ የከተማዋ ነዋሪዎችን እንደ አቅማቸው በ10/90፤ በ20/80 እና በ40/60 መርሀ ግብር ከፋፍሎ ወደ ቁጠባ ማስገባቱ ይታወቃል፡፡
ይሄን ተከትሎም 135 ሺህ የሚደርሱ የ1997 ዓ.ም ተመዝጋቢዎች፣ የእድሉ ቅድሚያ ተጠቃሚ እንዲሆኑ አድርጓል፡፡ ከ21 ወራት ቁጠባና ቆይታ በኋላም ባለፈው መጋቢት 13 ቀን 2007 ዓ.ም ቢያንስ ለ16 ወራት የቆጠቡ ነዋሪዎች በእጣው ተካትተው፣ 35ሺ የሚደርሱ የከተማዋ ነዋሪዎችን የቤት ባለ እድል ማድረጉን አስታውቋል፡፡ መቼም እጣው ደርሶት ያልተደሰተ፤ ያልፈነደቀ ያለመኖሩን ያህል፣ 16 ወራት መቆጠብ ባለመቻሉ ከእጣው የተገለለና ቆጥቦ እንኳን ቢሆን እጣው ያልወጣለትና ያላዘነ ሰው ይኖራል ብዬ አልገምትም፡፡ ሆኖም ግን ይህ ደስታና ሁካታ በብርሃን ፍጥነት ወደ ሀዘንና ተስፋ ማጣት ሲቀየር፣ በአንጻሩ እጣው ያልወጣለት ደግሞ “እሰየው ለበጎ ነው… እጣው የዘለለኝ” ሲል ከሳምንት ያልበለጠ ጊዜ ብቻ ነው የወሰደበት፡፡
ለምን ይሆን አትሉም?
ምክንያቱማ የቤቶች ልማት ፕሮጀክት ጽ/ቤት ስለቤቶቹ ማስተላለፍ በበተነው ብሮሸር ላይ የተቀመጠው የቤቶቹ ሂሳብ አከፋፈል መመሪያ፣ የከተማ ልማት ሚኒስቴር በወቅቱ ተፈፃሚ ይሆናል ብሎ ቃል ከገባበት መመሪያ ጋር ተጻራሪ ሆኖ በመገኘቱ ነው፡፡ የከተማ ልማት ሚኒስትሩ በወቅቱ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ መንግስት ዜጎችን የመኖሪያ ቤት እንዲኖራቸው ለማድረግ በ1997 ዓ.ም የጀመረው የኮንዶሚኒየም ቤቶች ግንባታ በሚፈለገው ፍጥነት እየተጓዘ አለመሆኑ አንድ ጉዳይ ሆኖ፣ እጣው የወጣላቸው ባለእድለኞች ግን ቤቱን እንዲረከቡ ጥሪ በሚደረግበት ሰዓት አብዛኛው የህብረተሰብ ክፍል በይበልጥም ድሃው ለቅድምያ ክፍያ የሚሆን ገንዘብ ማግኘት ከባድ ፈተና እንደሆነበት መንግስት መረዳቱን ጠቁመው አዲስ የተዘረጋው በየወሩ የመቆጠብ አሰራር ወርሃዊ ቁጠባውን እንዲያከናውንና እጣው በወጣለት ጊዜም ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መኖሪያ ቤቱን እንዲረከብ በማድረግ የአስተማማኝ ኑሮ ዋስትና እንዲያገኝ ያግዛል በማለት መናገራቸው አይዘነጋም፡፡
ሚኒስትሩ ይህን ቃል ሲናገሩ፤ እያንዳንዱ ቤት ፈላጊ የእድሉ ተጠቃሚ እንዲሆን ቢያንስ በየወሩ እንዲቆጥብ የተተመነበትን ሂሳብ በአግባቡ ከቆጠበ፣ እጣው በደረሰው ወቅት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ቤቱን ተረክቦ ኑሮውን ይጀምራል ማለታቸው እንደሆነ የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ ይገነዘባል፡፡ ነገር ግን ለ10ኛ ዙር ባለ እድለኞች የቀረበላቸው መመሪያ ግን ዱብ እዳ ነገር ነው፡፡ የቤቶች ልማት ፕሮጀክት በቅርቡ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ አሁን የተገነቡት ቤቶች ዋጋ የልደታ መልሶ ማልማት ፕሮጀክት ግንባታ ሲካሄድ የተፈጠረውን የዋጋ ልዩነት ታሳቢ በማድረግ፣ ከዚህ ቀደም ቤቶቹን ለመገንባት ይፈጃል የተባለው ተመን የ20 በመቶ የጭማሪ ማሻሻያ እንደተደረገበት አስታውቋል፡፡ ልብ በሉ! እንግዲህ ቤቶቹን የሚገነባው አካል በተፈጠረበት የዋጋ ንረት መሰረት የ20 በመቶ ጭማሪ ሲያደርግ የከተማው ነዋሪውም ከሚያገኘው ገቢ ላይ በንጽጽር የዚያኑ ያህል የዋጋ ንረት ይገጥመዋል ማለት ነው፡፡
ሆኖም የቤቶች ልማት ፕሮጀክት ከሁለት ዓመት በፊት ሚኒስትሩ የተናገሩትንና ተግባራዊ ይሆናል ብለው ቃል የገቡትን ውሳኔ ወደ ጐን በመተው፣ ስለ እድለኞች የመኖሪያ ቤት ርክክብ በሚያስረዳው መመሪያ ላይ በቀረበው የዋጋ ትመና መሰረት፤ ለ10/90 ቤቶች በካሬ ሜትር 1ሺ 910 ብር፤ ለ20/80 ስቱዲዮ 2ሺ 483 ብር፤ ለ20/80 ባለ አንድ መኝታ ቤት 3ሺ 438 ብር፤ ለ20/80 ባለ ሁለት መኝታ ቤት 4ሺ 394 ብር እና ለ20/80 ባለ ሶስት መኝታ ቤት 4ሺ 776 ብር መጨመሩ ታውቋል፡፡ ከዚህ ሌላ የ10/90 ባለዕድለኞች 10 በመቶ ቅድሚያ ክፍያ መክፈል ሲጠበቅባቸው፤ የ20/80 የጋራ መኖሪያ ቤት ባለእድለኞች ደግሞ የ20 በመቶ ቅድሚያ ክፍያ መክፈል ይኖርባቸዋል ይላል፡፡ እንደ ቤቶቹ አይነትና ስፋት እያንዳንዱ ባለ እድለኛ ቅድሚያ ክፍያ እንዲከፍል የቀረበለት ተመንና ከሁለት ወር የእፎይታ ጊዜያት በኋላ በ15 ዓመት ተከፍሎ የሚጠናቀቅ የወርሃዊ ክፍያ ተመን ጭንቅላት አስይዞ የሚያስጮህ፤ የሚያስበረግግ ምናልባትም እንደ እብድ በየጎዳናው ላይ ለብቻ እያወሩ እንዲጓዙ የሚያደርግ ነው፡፡ ለዚህ ነው አንዳንዱ ነዋሪ እጣው “እንኳንም አልደረሰኝ!!” ያለው፡፡
እንደ ማሳያ ለማቅረብ ያህል፣ ባለ ሁለት መኝታ ቤት የደረሰው ባለ እድለኛ አለ እንበል፡፡ አፍ ሞልቶ በእርግጠኝነት ይኖራል ማለት አስቸጋሪ ስለሚሆን ብቻ ዝም ብለን አለ እንበል፡፡ ታዲያ ይህ ሰው ለባለሁለት መኝታ ቤት የሚከፍለው ጠቅላላ ክፍያ ብር 317068 ይሆናል፡፡ በመመሪያው መሰረት፣ 20 ከመቶ ቅድሚያ ክፍያ መክፈል ስላለበት 21 ወራት እንኳን ቆጥቧል ቢባል (560 ብር x 21 ወራት = 11,760 ብር) ይመጣል ማለት ነው፡፡ ይህ ባለ እድለኛ 51,653 ብር ገደማ ለቅድሚያ ክፍያ አቅርቦ ከንግድ ባንክ ጋር መዋዋል ይጠበቅበታል፡፡ አሁን ይሄ ብር ከየት ይመጣል? ኧረ በምን ስሌት ይሆን ከሁለት ወር የእፎይታ ጊዜ በኋላ በየወሩ 2,700 ብር ከፍሎ በ15 ዓመት ውስጥ እዳውን የሚያጠናቅቀው? ምግብ አይበላም? የትራንስፖርት ወጪ የለበትም? ለልጆች የትምህርት ቤት ክፍያ አይከፍልም? እንደው በደፈናው ቤቱ ይድረሰው እንጂ ከባሌም ከቦሌም ብሎ ይክፈል በሚል የኢኮኖሚክስ መርህን በሚጥስ ስሌት ተዘጋጅቶ የቀረበ መመሪያ ነው የሚመስለው፡፡ ይሄ በእውነቱ “መንግስት አበደ እንዴ?” ያሰኛል፡፡ ግን መንግስት ቢያብድ ምን ይሆን የሚደረገው? መንግስት የኑሮውን ሁኔታና ክብደት መረዳት ይከብደው ይሆን እንዴ? የተማረ ኢኮኖሚስት ጠፍቶ ነው ወይስ የፖለቲካ ደባና ሴራ እየተካሄደ ነው? ለነገሩ ይህቺ ከተማ ለድሆች ፊቷን ካዞረች ሰነባብታለች፡፡
አንዳንዱ ሰው እኮ በአምላክ ተዓምር ካልሆነ በቀር፣ ልጆቹን እንዴት እያሳደገ እንደሆነ ማሰብ ሁሉ ይከብዳል፡፡ በዘመናዊ የሽፍን መኪና የምትመላለሱ የፖለቲካ አመራሮቻችን፤ መንግስት በአነስተኛ ክፍያ ቤት እየሰጣችሁ የምትኖሩ ባለስልጣኖቻችን፤ ልጆቻችሁን የተሻለ ት/ቤት የምታስተምሩ አለቆቻችን… እስኪ ለአንድ ወር እንኳን የእኛን የድሃዎቹን የአኗኗር ዘይቤ ኑና ተቋደሱ!!
መንግስትና አገሪቷን እየመራ ያለው ኢህአዴግ፣ በምርጫ ዋዜማ በእርግጥም ይህን አይነት የፖለቲካ ኪሳራ የሚያከናንብ ድርጊት አምኖበት ይሆን የፈጸመውን? እስኪ እውነት እንነጋገር ከተባለ መንግስት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለቤቶች መስሪያ የተበደረውን 1 ቢሊዮን ብር ለማስመለስ ዋስትና ማቅረብ ይሳነዋል? የትኛውስ ኢትዮጵያዊ ነው የባንክ እዳውን መከፈል ሳይችል ቤቱ ውስጥ መኖር የሚችለው? እውነት ንግድ ባንክ እዳቸውን ያልከፈሉ ዜጎችን መኖሪያ ቤት በሃራጅ ሸጦ ብሩን ማስመለስ ያቅተዋል?
ኢህአዴግ ትላልቅ ሃገራዊ ፕሮጀክቶችን እየመራ፣ እነዚህን ጥቃቅን የሆኑ፣ ነገር ግን ህዝብን የሚያማርሩ ስህተቶችን እንዴት ይፈጽማል?  በአፋጣኝ መፍትሄ የሚሻ ጉዳይ ነው፡፡ የሰለጠኑ አገራት አመራሮች እኮ ስህተት ተፈጽሞ ሲገኝ በይፋ ህዝባቸውን ይቅርታ ጠይቀው የእርምት እርምጃ ይወስዳሉ፡፡ እኔማ አንዳንዴ መንግስትንና ህዝብን የማቃቃር ተልእኮ ያነገቡ ጸረ ሰላም፤ ጸረ ዲሞክራሲና ፀረ ልማት ሀይሎች በመዋቅሩ ውስጥ እንዳይኖሩ እሰጋለሁ፡፡ ኢህአዴግ ሆይ፤ አሁንም የእርምት እርምጃ ለመውሰድ ጊዜው አልረፈደም። ኧረ ጎበዝ ልብ እንበል!

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ኢጣሊያዊ የማፊያ መሪ (የዘራፊ፣ የመንታፊና ገዳይ ቡድን መሪ) መሞቻው ጊዜ ደርሶ ኖሮ የልጅ ልጁን ጠራው፡፡ ከዚያም፤
“የልጅ ልጄ ያስጠራሁህ ለዋዛ አይደለም፡፡ በደንብ አዳምጠኝ”
“እሺ አያቴ፡፡ ምን ልትለኝ ፈልገሃል?”
“እንግዲህ መሞቻዬ ተቃርቧል”
“አያቴ፣ ለምን እንዲህ ትላለህ?”
 “በጣም ደህና እኮ ነህ?” ምንም የህመም ምልክት እንኳ አይታይብህም
“አይመስለኝም፡፡ ድምፄ ከመክሰሙ በፊት ብታዳምጠኝ መልካም ነው፡፡”
“እሺ አያቴ አዳምጥሃለሁ”
“አየህ እኔ ምን ጊዜም እንድታስታውሰኝ ስለምፈልግ አንድ ስጦታ ልሰጥህ እፈልጋለሁ”
“አያቴ ምንም ስጦታ ባትሰጠኝም አልረሳህም”
“በጭራሽ፡፡ የሰንሰል ቅጠልም ቢሆን ሰው ለሰው ስጦታ የሚሰጠው እንዲያስታውሰው ይጠቅመዋል፡፡ ስለዚህ ኮልት 45 ሽጉጤን እሰጥሃለሁ፡፡ ዘራፊ፣ መንታፊና የገዳይ ቡድን አባል የሆንኩትን አያትህን ምን ጊዜም የምታስታውሰኝ በዚህ ሽጉጥ ይሆናል” አለ፡፡
ይሄኔ የልጅ ልጁ፤
“ግን አያቴ፣ እኔ ሽጉጥ፣ ጠመንጃ፣ ጦር ጋሻ አልወድም፡፡ ምን ያደርግልኛል? እኔ የማፊያ ቡድን አባል አልሆንም፡፡  ይልቅስ ዕውነት የምትወደኝ ከሆን ሮሌክስ ሰዓትህን ትተህልኝ ሂድ፡፡ ውድ ሰዓትህ ሁልጊዜ አንተን የስታውሰኛል፡፡”
አያትዬው ድምፁ እየተንተባተበና እየተጎተተ መጣ፣
“የልጅ .. ል…ጄ…. በደ…ምብ አድምጠኝ የ… ቤታ…ችንን… ን.ግ.ድ.የምትመራው አንድ…ቀን አን…ተ  ነ.ህ… ከዚያ ቆንጆ ..ሚ..ስ..ት…ታገባ…ለህ፡፡ ብዙ … ገንዘብ ..  ይኖ.. ርሃል፡፡ ትልቅ ቪላ.. ቤ..ት ይኖር…ሃል፡፡ ምናል…ባ…ት..ም.. አንድ ሁለት ባምቢኖ (ልጆች) ይኖሩሃል፡፡
… እና ከዕለ… ታት አንድ ቀን … ሥ…ራ ውለህ ወደ ቤት … ስትመጣ ሚስትህ … ከሌላ ወንድ ጋር ተኝታ ልታገኛት ትችላለህ…  ያን ጊዜ ምን ታደርጋለህ? … የእኔን ሮሌክስ ሰዓት እያሳየህ “በቃችሁ ሰዓቱ ደርሷል!” ትላቸዋለህ?
ይልቅ መሳሪያዬን ተረከብ!” አለውና ድምፁ መሰማት አቆመ፡፡
*            *           *
ሁሉም ጉዳይ የየራሱ ማስፈፀሚያ አለው፡፡ የሀገራችን አንዳች የሚያህል ችግር አባትና ልጅ፣ ትውልድና ትውልዱ አለመጣጣሙ ነው፡፡ የአንዱ ፍላጎት ከሌላው ፍላጎት ጋር አለመመጋገቡ ነው፡፡ ለማንኛውም እያንዳንዱ ትውልድ የየራሱን ጣዕም ማበጀቱ እጅግ ወሳኝ ነገር ነው፡፡ የየራሱ ጣዕም የሌለው ትውልድ ለአገር አይበጅም፡፡ ስፖርት የሚያዘወትር፤ ትግል የሚወድ፣ አለ፡፡ ባንፃሩ ማጭበርበርን እንደኑሮ ዘዴ የለመደ፣ በመፈክር አገር እገዛለሁ ብሎ የሚያስብ፤ እርስ በርስ መጠላለፍን እንደፖለቲካ ካባ የደረበ ወዘተ ብዙ ዓይነት ትውልድ አይተናል፡፡
ሁሉም እኔ ልክ ነኝ ስለሚል ተው አይሆንም ማለት አዳጋች ነው፡፡ አቋሙ ታሪክ እስኪሆን በትዕግስት እንድንጠብቅ እንገደዳለን፡፡
ሌላው ችግራችን ስም-ልጠፋ ነው - በክፋት፡፡ (Branding) በዚህ ጉዳይ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ያለንን መስማት ጥሩ ነው፡-
“አንድ ተረት ልንገርህ፡፡ አንዲት እናት ልጇ አይናፋር ኖሮባት ከጓዳ አልወጣ አለ፡፡ “ወጣ በል!”  ተብሎ ከጓደኞቹ ጋር መቀላቀል ቢፈልግም አልቻለም፡፡ ግን የልጆቹን ሁሉ ስም አጥንቷል፡፡ እዚያ አካባቢ የሚነገረውን ስለሚሰማ ሁሉን ያውቃል፡፡ እቤት ይገባና ለእናቱ “በደሻ እንዲህ ሲል አፍንጮ እንዲህ ብሎ መለሰለት … ቀዮ ግን …” እያለ ይነግራታል፡፡ እናቱ ስትመልስለት “ያንተስ ስም ማነው?” ስትለው “እኔማ … እኔማ ስም የለኝም” አላት፡፡ “እንግዲያው ሂድ… ሂድ መንገዱን አቋርጥ፡፡ ልክ ስታቋርጥ ስም ያወጡልሃል፡፡ ያኔ ትነግረኛለህ፡፡” አለችው፤ ይባላል፡፡
መንገዱን ማቋረጥ የሀሳብ ትግል ይሆናል፡፡ የአቋም መለወጥ ሊሆን ይችላል። የሀሳብ ልዩነትን ግልፅ ሆኖ ማሳየት ሊሆን ይችላል፡፡ በማንኛውም የትኛውንም አዲስ መንገድ አቋርጠን እንሂድ ብንል አዲስ ስም እንደሚወጣልን ጥርጥር የለውም፡፡ ያየናቸው መንግስታት ሁሉ ለጠላቶቻቸው ስም ሳያወጡ አልኖሩም፡፡ ንፁሃን ዜጎችን ጭምር ስም ያወጡላቸዋል፡፡ ይሄ ደግ ዜጋ መንግስትን እንዳያምንና እንዲጠራጠር ያደርገዋል፡፡ ጥርጣሬ ካለ ዕድገት የለም፡፡ ልማት የለም፡፡ ወደፊት መራመድ የለም! ስለዚህ ለትንሽ ለትልቁ መንገድ አቋራጭ፤ ስም ማውጣቱን ትተን ለምን ከቤቱ ወጥቶ መንገድ አቋረጠ? ብለን መጠየቅ ያባት ነው!
ለውጥ ባየን ቁጥር ግትር ብለን አልቀበልም ማለት ጅልነት ነው፡፡ ለውጥ ባየን ቁጥር አብረን ዘራፍ ማለትም ጅልነት ነው፡፡ እኔ ምን አገባኝ ብሎ በምንግዴ መጓዝና መንግሥት ተለወጠ  አልተለወጠ፣ አይሞቀኝ አይበርደኝ ማለት የባሰ ጅልነት ነው! እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው ማለት እንደማያዋጣን ከልብ አውቀን ከተጓዝን አያሌ ነገሮችን ወደቀናው ነገ እንዲያመሩ ለማድረግ እንችላለን፡፡ ለዳግማይ ትንሣዔም እንበቃለን! መልካም በዓል!




አሸባሪው ቡድን ‘አይኤስአይኤስ’ ስደተኛ ኢትዮጵያዊያንን ገደለ
የሟች ቤተሰቦች ሐዘን ተቀምጠዋል - በኢንተርኔት ፎቶና ቪዲዮ አይተው


በሊቢያ የአሸባሪው ቡድን ‘አይኤስአይኤስ’ ታጣቂዎች፣ ’30 ኢትዮጵያዊያን ክርስትያኖችን ገድለናል’ ብለው በቪዲዮ የተቀረፀ አሰቃቂ የጭካኔ ግድያ ያሰራጩት በሳምንቱ መጨረሻ ላይ ነው። በደቡብ አፍሪካ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ላይ በደረሰው ዘረኛ ጥቃት ማግስት፣ በሊቢያ ሲቪል ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ላይ የተፈፀመው የአሸባሪ ቡድን ዘግናኝ ግድያ፤ የኢትዮጵያውያን ሐዘንና ቁጭት አክብዶታል።
በኢንተርኔት የተሰራጨው ቪዲዮና ፎቶ፣ የሟቾቹን ማንነት ወዲያውኑ ለማወቅና ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውን ለማረጋገጥ ለብዙዎች አስቸጋሪ ቢሆንም፣ ለቤተሰቦች ግን አጠራጣሪ አልነበረም። ወላጆችና ቤተሰብ፣ ወንድምና እህት፣ ጎረቤትና ወዳጆች ሁሉ ውስጥን በሚያደማ ቅፅበታዊ ሐዘን ነው የተመቱት።  
በአዲስ አበባ የኢያሱ ይኩኖአምላክ እና የባልቻ በለጠ ቤተሰቦች ድንገተኛ መርዶ የደረሳቸው እሁድ እለት ነው። በሰላሳዎቹ ዕድሜ ላይ የነበሩት ኢያሱና ባልቻ በአንድ ሰፈር ውስጥ ያደጉ ጎረቤታሞች ናቸው - በቀድሞው ወረዳ 21 ቀበሌ 25፤ በአሁኑ ወረዳ 10። የሟቾቹ ቤተሰቦች መኖሪያ ቤት አጠገብ ለአጠገብ ስለሆነ ለቅሶውም አንድ ላይ ነው፡፡
ኢያሱና ባልቻ የዛሬ ሁለት ወር ገደማ ወደ ሊቢያ የሄዱት አንድ ላይ እንደሆነ የገለፀልን የኢያሱ ወንድም፤ የሊቢያውን የግድያ ወሬ የሰማው እሁድ ዕለት ነው - ስልክ ተደውሎ። የደወለለት ሰው፣ “የናንተ ሰፈር ልጆች ሊታረዱ ሲሉ የሚያሳይ ፎቶ በፌስቡክ ተለጥፏል” ብሎ ሲነግረው፤ በደንጋጤ “እነማን ናቸው?” ብሎ ጠየቀ። “የወንድሜን ስም ጨምሮ ነገረኝ፤ የወንድሜን ስም አያውቅም ነበር” ይላል የኢያሱ ወንድም።
“የኔ ፌስቡክ ስለማይሰራ ጓደኛዬ ጋር ሄጄ አየሁ። በደንብ ስላልታየኝ እንደገና ከምሽቱ አራት ሰአት ስንከፍት ወንድሜን ተንበርክኮ አየሁት። ባልቻን ደግሞ ቀይ ቱታ ካደረጉት መሀል ለየሁት፡፡ ለእናቴ ከመንገሬ በፊት ለሩቅ ዘመዶች ለመናገር እያሰብኩ እያለ እነሱ ቀድመው ሰምተው ለቅሶ ላይ አገኘኋቸው” ብሏል የኢያሱ ወንድም።
ኢያሱ ኳታር ሰርቶ የተወሰነ ገንዘብ ይዞ ስለመጣ የባልቻንም ወጪ ሸፍኖለት ነው አብረው የሄዱት። ከኢትዮጵያ ወጥተው በሱዳን ጉዞ የጀመሩት ከሁለት ወር በፊት ነው። “ሱዳን እያሉ በስልክ እንገናኝ ነበር። ገንዘብ ሲያስፈልጋቸው እልክላቸው ነበር” የሚለው የኢያሱ ወንድም፤ “ወደ ሊቢያ ከተሻገሩ በኋላ ግን ስልክ ቁጥር እሰጥሃለሁ ቢለኝም አንገናኝም ነበር” ብሏል።  
 

 ሶስት ኢትዮጵያውያን በጥቃቱ ህይወታቸው አልፏል
- ብዙዎች ንብረታቸውን ተዘርፈዋል፣ በእሳት ተለብልበዋል
“ስደተኞችን በጉያችን ይዘን የምናባብልበት ጊዜ ማብቃት አለበት!” - የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ልጅ
“ስደተኞች ጓዛቸውን ጠቅልለው ወደመጡበት መመለስ አለባቸው!” - የዙሉ ንጉስ ዝዌሊቲኒ  
    ከሶስት ሳምንታት በፊት...
እትብታችን በተቀበረባት አፈር ላይ የሌሎች አገራት ዜጎች ተደላድለው ተቀመጡ፣ የዕለት እንጀራችንን ነጠቁ፣ ሃብት አፈሩ በሚል ሰበብ የተበሳጩ ደቡብ አፍሪካውያን ጎበዛዝት፣ በቁጣ ነድደው ወደ አደባባይ ወጡ። ቆንጨራቸውን ይዘው፣ ከላይ እስከ ታች ታጥቀው፣ ደም ሊያፈስሱ ተንደረደሩ፡፡
ለአመታት ጊዜ እየጠበቀ ሲፈነዳ የቆየውና ከወራት በፊት በሶዌቶ ዳግም የተቀሰቀሰው የጥላቻ መንፈስ ያደረባቸው እነዚህ ደቡብ አፍሪካውያን፣ በኢስፒንጎና ቻትስዎርዝ ከተሞች የሚገኙ የውጭ ዜጎችን ሱቆችና ግሮሰሪዎች በእሳት አነደዱ፡፡ ከእሳት የተረፉትም ዘረፉ፡፡
ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ፤ ጥፋቱን ለማስቆም የፓርላማ አባላትንና ሚኒስትሮችን የያዘ ግብረ ሃይል አቋቁመው እየሰሩ እንደሚገኙ ቢያስታውቁም፤ ይህ ነው የሚባል ለውጥ አልታየም፡፡ የአገሪቱ ፖሊስ ይህንን የጥፋት እሳት ለመግታት ደፋ ቀና ሲል ቢሰነብትም አልተሳካለትም፡፡ ቁጣና ጥፋቱ በያቅጣጫው መሰራጨቱን ቀጠለ፡፡ ወደ ክዋማኩታ... ወደ ኡምላዚ... ወደ ሌሎች የደቡብ አፍሪካ ከተሞች ተዛመተ፡፡ አገሬው ስደተኛውን እያሳደደ ማጥቃቱን ገፋበት፡፡ ሰርቼ ሰው እሆናለሁ ያሉ በሺዎች የሚቆጠሩ የሌሎች አፍሪካ አገራት ስደተኞች፣ ከጥፋቱ ለማምለጥ በየአቅጣጫው ተበተኑ፡፡ ላባቸውን አፍሰው ያፈሩትን ሃብትና ንብረት ታግለው ለማዳን የደፈሩ ጥቂቶችም፣ ከሞት ጋር ተፋጠጡ፡፡
የአገሪቱ ፖሊስ ግን፣ ራሳቸውን ከጥቃት ለመከላከል በቡድን የተንቀሳቀሱትን እነዚሁ ስደተኞች ሊያግዛቸው አልፈለገም፡፡ ይልቁንም ባለፈው ረቡዕ በአስለቃሽ ጭስ በተናቸው፡፡
ባለፈው ሳምንት አርብ፣ ምሽት ላይ...
የውጭ አገራት ስደተኞችን ለማጥቃት የወጡት ደቡብ አፍሪካውያን፣ ፊታቸውን ከደርባን በስተ ደቡብ ወደምትገኘው ኡማልዚ ከተማ አዞሩ፡፡ በከተማዋ የሚገኙ የስደተኞች ሱቆችን በእሳት አቀጣጠሉ፡፡ በሱቆቻቸው ውስጥ እያሉ በድንገተኛው የእሳት ወላፈን ከተለበለቡት የውጭ አገራት ስደተኞች መካከል፣ ሁለቱ ወንድማማች ኢትዮጵያውያን ነበሩ፡፡ አንደኛው በደረሰበት ቃጠሎ ለሞት ተዳርጓል፡፡
የያዝነው ሳምንትም በደቡብ አፍሪካ ለሚገኙ ስደተኞች የመከራ ሆኖ ቀጥሏል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ ምሽት...
ይባስ ብሎም የአገሪቱ መሪ ጃኮብ ዙማ ወንድ ልጅ፣ የውጭ አገራት ዜጎችን በጉያችን ይዘን የምናባብልበት ጊዜ ማብቃት አለበት ሲል አፍ አውጥቶ በመናገር ጥፋቱን የባሰ የሚያቀጣጥል ድርጊት ፈጸመ፡፡ የፕሬዚዳንቱ ልጅ ይሄን ባለባት ምሽት፣ አገሬው ለባሰ ጥፋት ታጥቆ ተነሳ፡፡ የደቡብ አፍሪካዋ የወደብ ከተማ ደርባን ጎዳናዎች፣ ስደተኞችን ለማጥፋት ቆርጠው በተነሱ፣ እሳትና ስለት በታጠቁ ዜጎች ተጥለቀለቁ፡፡ በከተማዋ ጥፋት ሆነ፡፡
በርካቶች ራሳቸውን ከሞት ለማዳን ድቅድቁን ጨለማ እየሰነጠቁ፣ እግራቸው የመራቸውን አቅጣጫ ተከትለው ሮጡ፡፡ አሶሼትድ ፕሬስ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፤ ከሁለት ሺህ በላይ ስደተኞች በፖሊስ ጊዚያዊ መጠለያ ካምፖች፣ በስታዲየሞችና በተለያዩ የመንግስት ተቋማት ተጠለሉ፡፡
በዚህ የጥፋት ዘመቻ፣ ሰሞኑን ብቻ የ14 አመት ዕድሜ ያለውን ብላቴና ጨምሮ ሁለት የውጭ አገራት ዜጎችና 3 ደቡብ አፍሪካውያን ለህልፈተ ህይወት ተዳርገዋል፡፡ ፖሊስም በዚህ የጥፋት ዘመቻ ተካፍለዋል ያላቸውን 74 ያህል ሰዎች በቁጥጥር ውስጥ ማዋሉን አስታውቋል፡፡
በደቡብ አፍሪካ የኢትዮጵውያን ኮሚኒቲ መሪ ኤፍሬም መስቀሌን ጠቅሶ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ባለፈው ማክሰኞ እንደዘገበው፣ ባለፈው አርብ ሱቁ በእሳት የጋየበትን ግለሰብ ጨምሮ 3 ኢትዮጵያውያን በጥቃቱ ህይወታቸው አልፏል፡፡
ይህንን የዘረኝነትና የጥፋት ዘመቻ ለመቃወም ያለመና 10 ሺህ ያህል ሰዎች የተሳተፉበት ሰልፍ በደርባን ከተማ ተካሂዷል። ማላዊ ባለፈው ረቡዕ በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ዜጎቿን ለማውጣት መዘጋጀቷን ስትገልጽ፣ ሞዛምቢክም በበኩሏ፤ ከደቡብ አፍሪካ በሚያዋስናት ድንበር አካባቢ የስደተኞች መሸጋገሪያ ካምፕ ማዘጋጀቷን አስታውቃለች፡፡
እ.ኤ.አ በ2008 ሶዌቶ ውስጥ በተቀሰቀሰ ተመሳሳይ ጥቃት፣ ከ62 በላይ የሌሎች አገራት ዜጎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ከሰሞኑ የተከሰተውን ጥፋት ያቀጣጠለው ዝዌሊቲኒ የተባሉ የዙሉ ንጉስ የተናገሩት ንግግር ነው እንደተባለ ጠቁሟል፡፡
እኒሁ ተሰሚነት ያላቸው ንጉስ ባለፈው ወር ስደተኞች ወደየአገራቸው መመለስ አለባቸው ብለው ተናግረዋል በሚል ወቀሳ እየቀረበባቸው እንደሆነ ዘገባው ገልጾ፣ ይሄም ሆኖ ንጉሱ ግን እንዲህ ብለው አለመናገራቸውን በመግለጽ፣ ወቀሳውን ማጣጣላቸውን አክሎ አስታውቋል።
በተለይም ኢትዮጵያውያንና ሶማሊያውያንን ታላሚ አድርጎ የተጀመረው የዘረኝነት ጥቃት፣ አሁን ወደ ሁሉም የአፍሪካ አገራት ስደተኞች መስፋፋቱን የዘገበው ቪኦኤ፤ አገሬው የስደተኞቹን ንብረት በመዝረፍና በእሳት በማጋየት እንዲሁም በጭካኔ በመደብደብ ተግባሩ እንደገፋበት አመልክቷል፡፡
የደቡብ አፍሪካ መንግስት ጥቃቱን ያወገዘ ሲሆን ባለፈው ማክሰኞ የተለያዩ ሚኒስትሮች ንግግር አድርገዋል፡፡ የአገሪቱ ፖሊስ ሚኒስትር ናቲ ንህሌኮ፣ጥቃቱ አፍሪካውያን የራስ ላይ ጥላቻቸውን ያንጸባረቁበት መንገድ ነው ማለታቸውን News24.ዘግቧል፡፡
“አንዳንዶቻችን የውጭ ዜጎች ጥላቻ ነው ብለን ለማሰብ ተቸግረናል፡፡ የተወሰነ የፖለቲካ ችግርን የሚወክልም ይመስለኛል፡፡ የአውስትራሊያ ዜጎች በመንገድ ላይ ሲሳደዱ አታዬም፤ እንግሊዞች መንገድ ላይ ሲሳደዱ አታዩም፡፡” ብለዋል የፖሊስ ሃላፊው፡፡
እሳቸው እንዲህ ይበሉ እንጂ ፓኪስታኖችና ባንግላዲሾች ጥቃት እንደተፈጸመባቸው የሚያመለክቱ ዘገባዎች አሉ፡፡
የመከላከያ ሚኒስትሩ ኖሲቪዌ ማፒሳ-ንኳኩላ በበኩላቸው፤ “የውጭ ዜጎች በመሆናቸው ብቻ ንጹሃን ላይ ጥቃት ከሚፈጽሙ ወገኖች ጋር ደቡብ አፍሪካውያን መተባበር የለባቸውም” ብለዋል፡፡

ኤምባሲው በጥቃቱ ማዘኑን ገልጿል
“ኢትዮጵያውያን ለደቡብ አፍሪካ ህዝብ ሲያደርጉ የነበረውን ድጋፍ አሁን መጠቀሚያ ሊያደርጉት አይገባም”  -  (የፕሬዚዳንቱ ልጅ)
“ከደቡብ አፍሪካ አመራሮች ጋር እየተገናኘን ችግሩን ለመፍታት እየሰራን ነው”  - (ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም፤ የውጭ ጉዳይ ሚ/ር)

ሰሞኑን በደቡብ አፍሪካ በሚገኙ ኢትዮጵያውያን ላይ እየተወሰደ ያለው የጥቃት እርምጃ ተባብሶ የቀጠለ ሲሆን በርካታ ኢትዮጵያውን ስደተኞች የጥቃቱ ሰለባ እየሆኑ መምጣታቸውን ምንጮች ጠቆሙ፡፡ ድርጊቱን የሚቃወሙ ሰላማዊ ሰልፎች እየተካሄዱ ሲሆን ጥቃቱ አሁንም እልባት አለማግኘቱንና ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ስደተኞች በከፍተኛ ስጋት ላይ እንደሆኑ እነዚሁ ምንጮች ገልፀዋል፡፡
እስከአሁን የሶስት ኢትዮጵያውያንን ህይወት የቀጠፈውና የብዙዎችን ሰርቶ የመኖር ተስፋ ያጨለመው የሰሞኑ የደቡብ አፍሪካ ጥቃት፣ አድማሱን እያሰፋና እየተባባሰ ሄዷል የሚሉት ኢትዮጵያውያኑ፤ ጥቃቱ እንዳይፈፀም የሚያደርግና ስጋታችንን የሚቀንስ ምንም አይነት እርምጃ በአገሪቱ መንግሥትም እየተወሰደ አይደለም ብለዋል፡፡ የአገራችን መንግስት ለጉዳዩ የሰጠው ትኩረት አነስተኛ ነው ሲሉ ወቅሰዋል፡፡
የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ ልጅ ኤድዋርድ ዙማ፤ ጥቃቱን አስመልክቶ በሰጠው ቃለ ምልልስ፤ እርምጃው አግባብ መሆኑን ጠቁሞ ጥቃቱ መወሰድ ያለበት በአፍሪካውያን ላይ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ያለምንም ህጋዊ ሰነድ በደቡብ አፍሪካ እየኖሩ ባሉ የውጪ ዜጎች ላይ ጭምር ነው። እነሱን በማባበል ጊዜ ማጥፋት አያስፈልግም፡፡ ቀደም ሲል ስለአደረጉልን ድጋፍ እናመሰግናለን፡፡ ያንን ድጋፋቸውን ግን ለአሁን መጠቀሚያ ማድረግ አይችሉም” ብሏል፡፡
“በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ የውጪ አገር ዜጎች በሙሉ ወደሚመለከተው የመንግስት አካል ሄደው መመዝገብ አለባቸው፤ ምን እናውቃለን… ISISን ወይም አልሻባብን እየረዱ ሊሆኑ ይችላሉ” ሲልም የፕሬዚዳንቱ ልጅ ተናግሯል፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ በበኩላቸው፤ በስደተኞቹ ላይ የተፈፀመውን ጥቃቅ አውግዘው “በችግራችን ወቅት ነፃነታችንን እንድናገኝ የእርዳታ እጃቸውን ዘረጉልን እንጂ አላሳደዱንም፤ ይህንንም ማስታወስ ይገባናል” ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም፣ የደቡብ አፍሪካውን ጥቃት አስመልክተው ሲናገሩ፤ በደቡብ አፍሪካ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሙሉ ጊዜውን ለጉዳዩ ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው ከአገሪቱ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትርና ከሌሎች የደቡብ አፍሪካ አመራሮች ጋር ተገናኝተው ችግሩን ለመቅረፍ እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ “ሚኒስትሯ በሁኔታው በጣም እንዳዘኑና እንዳፈሩበት ነግረውናል” ያሉት ዶ/ር ቴዎድሮስ፤ ኢትዮጵያ ለደቡብ አፍሪካውያን ቤታቸው ነች፤ በነፃነት ትግላችን ወቅት ያደረጋችሁልንን ድጋፍ አንረሳውም፤ የተቻለንን ሁሉ እናደርጋለን” ብለውናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡
እንደ ኢትዮጵያውያኑ ሁሉ ዜጎቻቸው የሰሞኑ ጥቃት ኢላማ የሆኑባቸው የዚምባቢዌና ማላዊ መንግስታት፣ በአገሪቱ እየተካሄደ ያለውን ጥቃት በማውገዝ ድርጊቱ እንዲቆም የሚጠይቅ ደብዳቤ ለአገሪቱ ኤምባሲ አስገብተዋል፡፡ በማላዊም በዚህ ጉዳይ የተሰባሰበ ቡድን የማላዊ ዜጎች የደቡብ አፍሪካ ምርቶችን ከመግዛት እንዲቆጠቡና በደቡብ አፍሪካ አየር መንገድ እንዳይጠቀሙ ጠይቋል፡፡  
በሌላ በኩለ፤በኢትዮጵያ የደቡብ አፍሪካ ኢምባሲ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ፣ የአገሪቱ ፖሊስ ዜጎቹንና የውጭ አገራት ዜጎችን ደህንነት ለመጠበቅና ጥቃትና ዝርፊያ የሚፈጽሙ ህገወጦችን በቁጥጥር ስር ለማዋል እየሰራ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡ የአገሪቱ መንግስት በውጭ አገራት ዜጎች ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት ለማስቆምና ጸጥታን ለማስፈን የተቀናጀ ርብርብ እያደረገ እንደሚገኝም ጠቁሟል፡፡ ይህም ሆኖ ከችግሩ ስፋት አንጻር የበለጠ የተቀናጀና ዘላቂነት ያለው ስራ መስራት የሚገባ መሆኑ ስለታመነበት አዲስ አቅጣጫ እየተቀየሰ መሆኑንም ገልጧል፡፡
ደቡብ አፍሪካውያን በታሪክ አጋጣሚ ከአገራቸው ወጥተው በኢትዮጵያና በሌሎች የአፍሪካ አገራት ይኖሩ እንደነበር ያስታወሰው መግለጫው፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ለደቡብ አፍሪካ የነጻነትና የአመራር ንቅናቄዎች ያደረገውን ድጋፍ ዛሬም በክብር እናስታውሰዋለን ብሏል፡፡
የሁለቱ አገራት ታሪካዊ ትስስር ለወደፊትም ይቀጥላል፤ ለአፍሪካ ልማት እውን መሆን የጀመርነው የጋራ ጥረትም ተጠናክሮ ይቀጥላል ያለው ኢምባሲው፣ በጥቃቱ ህይወታቸውን ላጡ ዜጎች ቤተሰቦች የተሰማውን ሃዘን ገልጾ፣ የቆሰሉትም በቶሎ እንዲያገግሙ ያለውን መልካም ምኞት ገልጧል፡፡

የአለም ባንክ ቡድን አባል የሆነው ኢንተርናሽናል ፋይናንስ ኮርፖሬሽን (IFC) ተቀማጭነቱ በኢትዮጵያ ለሆነው አፍሪፍሎራ ግሩፕ የተባለ የአበባ አምራች ኩባንያ ማስፋፊያ የሚውል የ90 ሚሊዮን ፓውንድ (2ቢ.880ሚ. ብር ገደማ) የገንዘብ ብድር ሊሰጥ መሆኑን አስታወቀ፡፡
ከ9ሺህ በላይ ሰራተኞች ያሉት አፍሪፍሎራ ከአለም ባንክ በሚያገኘው የገንዘብ ብድር የአበባ ምርቱን 60 በመቶ ለማሳደግ፣ ውሃን መልሶ ለመጠቀም የሚያስችል ቴክኖሎጂ ለመገንባት፣ የፈጠረውን የስራ ዕድል ከ50 በመቶ በላይ ለማሳደግና ሌሎች የማስፋፊያ ስራዎችን ለማከናወን እንደሚያውለው ተቋሙ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
አፍሪፍሎራ በአበባ ምርት ዘርፍ የስራ ዕድል በመፍጠር በኢትዮጵያ ቀዳሚው እንደሆነ የጠቆመው የኢንተርናሽናል ፋይናንስ ኮርፖሬሽን መግለጫ፣ በቀጣይም አለማቀፍ የአካባቢና የማህበራዊ ዘላቂነት መስፈርቶችን ባሟላ መልኩ ምርቱን ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝ ጠቁሟል፡፡
በዝዋይ አካባቢ በሚገኘው የኩባንያው ዋና እርሻ እስከ 40 ሺህ የሚደርሱ ሰዎችን በቀጥታ፣ ከ100 ሺህ በላይ የሚሆኑትን ደግሞ በተዘዋዋሪ ተጠቃሚ እያደረገ  ሲሆን ትምህርት ቤቶችን፣ ሆስፒታልና ስቴዲየም በመገንባት ማህበራዊ ሃላፊነቱን እየተወጣ እንደሚገኝም አስታውቋል፡፡
ኢንተርናሽናል ፋይናንስ ኮርፖሬሽን ባለፈው የፈረንጆች የበጀት አመት ከሰሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገራት ለሚከናወኑ የግብርና ቢዝነስ ፕሮጀክቶች 686 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉንም መግለጫው አክሎ አስታውቋል፡፡

ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማት ተዘጋጅቷል
ዕጣ የደረሰው በዱባይ የንግድ ትርኢት ይሳተፋል

ታላቱ ሩጫ በኢትዮጵያ ከኢስት አፍሪካ ቦትሊንግ ኩባንያ (ኮካኮላ) ጋር በመተባበር ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ ሲያካሂድ የነበረውን የኮካኮላ የጎዳና ላይ ውድድር በ “ዳሳኒ የጎዳና ሩጫ” መተካቱን አስታወቀ፡፡ በቅርቡ በሚካሄድ የጐዳና ሩጫ ላይ ላሸነፉ ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማት ተዘጋጅቷል ተብሏል፡፡
የሩጫው አዘጋጆች ከትናንት በስቲያ በሰጡት መግለጫ፤ ዳሳኒ ውሃ ዓለም አቀፍ የጥራት ደረጃ ያለው የኮካኮላ ምርት መሆኑን ጠቅሰው፣ ውድድሩ ከስም ለውጥ በስተቀር አራት ዓመት ሲካሄድ ከቆየው ውድድር ጋር ተመሳሳይ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
ከዚህ ቀደም ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ 15ሺህ ተሳታፊዎች የተሳተፉበት ትልቅ የጐዳና ላይ ውድድር ማካሄዱን ጠቅሰው ዘንድሮ በሁለቱም ፆታ በሚካሄደው ውድድር 18ሺ ያህል ራጮች ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡
በመጪው ሰኔ 7 በዳያስፖራ አደባባይ ለሚካሄደው ውድድር ሰኞ ሚያዝያ 12 ቀን ምዝገባ እንደሚጀመር ጠቅሰው ሩጫውም 7.5 ኪ.ሜ ለጤና ሯጮች፣ 15 ኪ.ሜ ደግሞ ለአትሌቶች እንደሚሸፍን የተገለፀ ሲሆን አሸናፊዎች እስካሁን በኢትዮጵያ ታሪክ ለሯጮች ተሰጥቶ የማያውቅ የገንዘብና የቁሳቁስ ሽልማት እንደሚሸለሙ አስታውቀዋል፡፡
በወንድና በሴት ምድብ ተከፍሎ በሚካሄደው ውድድር፤ ከ1ኛ እስከ 10ኛ ለሚወጡ ተወዳዳሪዎች 285 ሺህ ብር የተዘጋጀ ሲሆን በሁለቱም ፆታ 1ኛ የሚወጣ 60ሺ ብር፣ 2ኛ 30 ሺህ ብር፣ 3ኛ 20,500 ብር እንደሚሸለም ታውቋል፡፡ በውድድሩ ለሚሳተፉ ተወዳዳሪዎች በ2008 በዱባይ በሚካሄደው የንግድ ትርዒት ለመሳተፍ የሚያስችል የዕጣ ዕድሎች የተዘጋጁ ሲሆን ዕጣው የደረሰው ተወዳዳሪ የደርሶ መልስ ቲኬትና የሁለት ቀን ወጪ እንደሚሸፈንለት ተጠቁሟል፡፡ የላፕቶፕና የሞባይል ቀፎ ዕጣ ዕድሎችም እንደተዘጋጁ ታውቋል፡፡

ሲኒማ ቤቱ ህገወጥ የንግድ አሰራርን ይከተላል ተብሏል

የንግድ ውድድርና የሸማቾች ጥበቃ ባለስልጣን አቃቤ ህግ፤ በሴባስቶፖል ኢንተርቴይንመንት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ላይ ክስ መሰረተ። ክሱ የተመሰረተውና የታየው ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ረፋድ ላይ በባለስልጣኑ አስተዳደር ችሎት ሲሆን የባለስልጣኑ አቃቤ ህግ ሴባስቶፖል በፈጸመው ፀረ ውድድር  የንግድ አሰራር ምክንያት ክሱ እንደተመሰረተበት በክስ ቻርጁ አመልክቷል፡፡
ሴባስቶፖል ክስ የተመሰረተበት ኤግዚቢሽን ማዕከል በሚገኘው ሲኒማ ቤቱ አዳዲስ ፊልሞችን ለማሳየት የሚመጡ ፕሮዲዩሰሮችን ፊልሞቻቸው የሚታዩት ኢዮሃ ሲኒማ ላለማሳየት የሚስማሙ ከሆነ ብቻ እንደሆነ በመግለፅና በፊልም ፕሮዲዩሰሮች ላይ ጫና በማሳደር ተገቢ ያልሆነ የንግድ አሰራር እያካሄደ በመሆኑ ነው ይላል የክስ ቻርጁ፡፡
የሴባስቶፖል ኢንተርቴይንመንት ድርጊት በአቅራቢያው የሚገኘው ኢዮሃ ሲኒማ በገበያው የፊልም አቅርቦት እንዳያገኝና ተወዳዳሪ ሆኖ እንዳይቀጥል ብሎም ከገበያ እንዲወጣ የሚያደርግ ፀረ-ውድድር የንግድ አሰራር እንደሆነ በክስ ቻርጁ ያተተው የባለስልጣኑ አቃቤ ህግ፤ ድርጊቱም የፌደራል የንግድ ውድድርና የሸማቾችን አሰራር መብት አዋጅን የሚቃረን በመሆኑ ይህን የሚያደርግበት ምክንያት ምን እንደሆነ ተከሳሹ ድርጅት መልስ ይዞ ለሚያዚያ 8 እንዲቀርብ ቀጠሮ የሰጠ ቢሆንም በዕለቱ የሴባስቶፖል ሲኒማ ባለቤት አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ “ጊዜው አጥሮኛል” በሚል ምክንያት መልሱን ይዞ አልቀረበም፡፡ በእለቱ ተሰይሞ የነበረው የባለስልጣኑ አስተዳደር ችሎት፤ ተከሳሹ ድርጅት መልሱን ይዞ እንዲቀርብ ለሰኔ 1 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
የኢዮሃ ሲኒማ ባለቤትና ዋና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ አዩ ዓለሙ፤ ሴባስቶፖል ባደረሰባቸው ጫና ላለፉት ሁለት ዓመታት በፊልም እጥረት ከፍተኛ ኪሳራ እንደደረሰባቸው ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል። “እስከዛሬም ሲኒማ ቤቱን ያልዘጋነው በአንዳንድ ደፋርና የመጣው ይምጣ ብለው ፊልማቸውን ኢዮሃ በሚያስገቡ ፕሮዲዩሰሮች ብርታት ነው” ያሉት ሥራ አስኪያጇ ጉዳዩ እዚህ ደረጃ ላይ እንዳይደርስ ላለፉት ሁለት ዓመታት ቢታገሱም እንዳልተሳካ ገልፀዋል፡፡
የሴባስቶፖል ሲኒማ ባለቤት አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመን ለማነጋገር በተደጋጋሚ ብንደውልም ስልኩ ባለመነሳቱ ሃሳባቸውን ለማካተት አልቻልንም፡፡