Administrator

Administrator

አርቲስት ደበበ እሸቱ ብቸኛው የህይወት ዘመን ተሸላሚ እጩ ሆኗል
በመጪው የካቲት የሚያካሂደውና በኢትዮ ፊልምስ ባለቤትነት የሚመራው የጉማ ፊልም ሽልማት ምርጥ አምስቶች ከትናንት በስቲያ በሃርመኒ ሆቴል ይፋ ሆኑ፡፡ በህይወት ዘመን ተሸላሚነት አርቲስት ደበበ እሸቱ ብቸኛ እጩ መሆኑም ተገልጿል፡፡ በዕለቱ በ17 ዘርፎች በዳኞችና በተመልካች የተመረጡ አምስት አምስት እጩዎች የታወቁ ሲሆን ዘርፎቹም በምርጥ የተማሪ አጭር ፊልም፣ በምርጥ ድምፅ፣ በምርጥ ሙዚቃ፣ በምርጥ ስኮር፣ በምርጥ ሜክአፕ፣ በምርጥ የፊልም ጽሑፍ፣ በምርጥ ቅንብር፣ በምርጥ ሲኒማቶግራፊ፣ በምርጥ ተስፋ የተጣለባት ህፃን ተዋናይት፣ በምርጥ ተስፋ የተጣለበት ህፃን ተዋናይ፣ በምርጥ ረዳት ሴት ተዋናዮች፣ በምርጥ ረዳት ወንድ ተዋናይ፣ በምርጥ ሴት ተዋናይት፣ በምርጥ ወንድ ተዋናይ፣ በምርጥ የተመልካች ምርጫ፣ በምርጥ ዳይሬክተርና በምርጥ ፊልም ጐራ በሚል ተከፋፍለዋል፡፡ መቶ ዳኞች በተሳተፉበት በዚህ ምርጫ ምርጥ አምስቶቹ የታወቁ ሲሆን በቀጣይ ከአንድ እስከ ሦስት የሚወጡት ተለይተው፣ የካቲት 16 ቀን 2007 ዓ.ም ደማቅ የሽልማት ስነ ስርዓት እንደሚካሄድ የኢትዮ ፊልም መስራችና ስራ አስኪያጅ ዮናስ ብርሃነ መዋ ለጋዜጠኞች ተናግሯል፡፡ ፕሮግራሙን ሙሉ በሙሉ ስፖንሰር ያደረገው በደሌ ቢራ ነው፡፡

በታሪካዊቷ ደሴ ከተማ መሀል በሚገኘው ደሴ ህንጻ ላይ ደረጃውን የጠበቀ ዘመናዊ ሲኒማ ቤት መከፈቱ ተገለፀ፡፡ “
ዙም ሲኒማ” ቤት 265 ምቹ መቀመጫዎች ያሉት ሲሆን ኤች.ዲ ዘመናዊ ፕሮጀክተርና ዘመኑ የደረሰባቸው የድምፅ ቴክኖሎጂዎች ተገጥሞለታል፡፡
ሲኒማ ቤቱን በባለቤትነት የሚያስተዳድረው የጂታብ ኢንተርቴይመንት ሥራ አስኪያጅ አቶ ታዲዮስ ጌታቸው፤ “ደሴ ካላት ረጅም ዕድሜና የከተማው ነዋሪ ለኪነጥበብ ካለው ጥልቅ ፍቅር አንፃር ደሴ እስካሁን እንዲህ ያለ ዘመናዊ ሲኒማ ቤት ሳታገኝ መቆየቷ የሚያስቆጭ” ነው ብለዋል፡፡
ዳራሹ ከሲኒማ በተጨማሪ እንደ ቴአትር፣ ስታንድአፕ ኮሜዲና  ሰርከስ ለመሳሰሉ ጥበባዊ ትርዒቶች ምቹ በመሆኑ በዘርፍ የተሰማሩ ባለሙያዎች ቢመጡ አብሮ ለመስራት ዝግጁ ነን ብለዋል - አቶ ታዲዮስ፡፡ አስራ አንድ በአምስት (11x5) ሜትር ስፋት ያለው ዘመናዊ ስክሪን የተዘረጋለት አዲሱ ሲኒማ ቤት፤ ከጥር 16 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ በይፋ ስራ የሚጀምር ሲሆን የፊልም ፕሮዱዩሰሮች በሲኒማ ቤቱ ፊልማቸውን እንዲያሳዩ ጥሪ ቀርቧል፡፡   

   ከእለታት አንድ ቀን ከባድ የበረዶ ዘመን መጣና እፅዋትና እንስሳትን በቅዝቃዜ ጨረሰ፡፡ በየእለቱ ሞቶ የሚያድረው ነብስ እጅግ እየረከተ መጣ፡፡ ይሄኔ የባህር አሳዎች መመካከር ጀመሩ፡፡ ከነዚህ አሳዎች መካከልም በጣም እሾካማ የሆኑ አሳዎች አሉ፡፡
አንደኛው አሳ፤ ለሌኛው አሳ፡-
“እስከመቼ ድረስ ዝም ብለን ተቀምጠን በበረዶ ቅዝቃዜ እናልቃለን? ለምን ቢያንስ ተጠጋግተን፣ ተቃቅፈን አንተኛም?” ይለዋል፡፡
ሁለተኛው አሳም፤
“ተቃቅፈንና ተጠጋግተን መተኛቱ ለምን ይጠቅመናል?” ሲል ይጠይቀዋል?
አንደኛው አሳ፤
“በበረዶ ባህር ውስጥ ተራርቀንና ተለያይተን ከሚቀዘቅዘን ተጠጋግተን ብናድር አንዳችን ለአንዳችን ሙቀት እንሰጣለን፡፡ ስለዚህም እርስ በርስ እንክብካቤ የመደራረግ እድል እንፈጥራለን” አለው፡፡ በዚህ ሃሳብ ተስማሙ፡፡ አጠገብ ላጠገብ ሆነው ተኙ፡፡ ሆኖም አንድ ችግር ገጠማቸው፡፡
ሲጠጋጉ ሁሉም እሾሃማ ቆዳ ስለሆነ ያላቸው ያንዱ ቆዳ የሌላኛውን እየወጋው፣ እንደቆንጥር እየጠቀጠቀው ፈፅሞ ለመተኛት አዳገታቸው፡፡ ቢለያዩ ቅዝቃዜው ሊገላቸው ሆነ፡፡ ቢቀራረቡ እሾክ ለሾክ ሆኑና ሊወጋጉ ሆነ፡፡ ምርጫቸው ከሁለቱ አንዱን ማድረግ ሆነ፡- ወይ ተለያይቶ በበረዶው ቅዝቃዜ ማለቅ፤ ወይም ደግሞ እንደምንም እሾክ ለእሾክ ተቻችሎ የጐድን ውጋቱን ችሎ ማደር፡፡
በሁለተኛው ምርጫ ተስማሙ፡፡ ብዙ ሳይገላበጡ፣ ሙቀት እየተለዋወጡ ክፉውን የበረዶ ጊዜ ማለፍ! ጐረቤት ለጐረቤቱ የጐን ውጋት እንዳይሆን መጠንቀቅ፡፡ ውጋቱ ቢኖርም ቁስል ቢፈጠርም ታግሶ፣ ችሎ ማደርን መልመድ! በዚህ ዘዴ ህያው ሙቀት እየተሰጣጡ ያንን ዘመን ተሻገሩ፤ ይባላል!
ገልቱ የራሷ ወጥ ይጣፍጣታል!
ቀጥቃጭ ሲያረጅ ዱልዱም ይቀጠቅጣል
በሀገራችን የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች አንዱ ያንዱን ችግር ችሎ፣ አንዱ ያንዱን ቁስል አክሞ መከራን በትእግስት አልፎ፣ ቢቻልም እሾኩን ነቅሎ፤ ህያው ሙቀት ፈጥሮ አገር ማዳን ባለመቻሉ፤ ብዙ እድልና አጋጣሚ አምልጧል፡፡ ጥቃቅን ችግሮችን በወቅቱ ለማለፍ ባለመቻሉ የመፈረካከስ፣ የመሰነጣጠቅ ከናካቴውም የመበታተን አደጋ ደርቷል፡፡ የእኔ ትልቅ ነኝ …እኔ ትልቅ ነኝ ፍትጊያ ለብዙ መከራ ዳርጓል፡፡ የእኔ ልዋጥ እኔ ልዋጥ ሽኩቻ (Big Fish - Small Fish Theory እንዲሉ ፈረንጆች) ለብዙ አበሳ አጋልጧል፡፡ አገርና ህዝብን ማስቀደምና የጋራ ቤት የሚሰራበትን ወቅት ለየግል ፍልሚያ በመጠቀም አያሌ የአዝመራ ጊዜዎች ባክነዋል፡፡ ልብ ማለት ያለብን ከትላንት የእርስ በርስ አለመግባባት፣ ከትላንት እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ ትርምስ ማን ተጠቀመ? የሚለውን ነው፡፡ ዛሬም ከትላንት ለመማር አልረፈደም፡፡ አንድን ወቅት የዓለም ፍፃሜ አድርጐ መፈረጅ ወደ ተስፋ-መቁረጥ ነው የሚያመራው፡፡ ይልቁንም ሁሉን ነገር በትላንት በዛሬና በነገ ሰንሰለት ላይ እንዳለ ክስተት እያዩ፣ በትእግስትና በፅናት መጓዝን ለማወቅ ታላቅ ጥበብ ነው፡፡ አገር “በእድገት ላይ ነን ተብሎ ሊፃፍባት አይችልም፡፡ ወይም እንደ ንግድ በአዲስ መልስ ሥራ ጀምረናል” አይባልባትም፡፡ ዲሞክራሲ የተከለከለች የበለስ ፍሬ የማትሆነው ሁሉን ነገር እንደ ሂደት እያያያዝን ካየን ነው፡፡ ፍፁም የሆነ ዲሞክራሲ እንዳለመኖሩ፤ በተናፅሮ የምናገኘውን ዲሞክራሲ ለመጨበጥም ብዙ ድካም ይጠይቃል - በድሮው ቋንቋ ያለመስዋዕትነት ድል የለም - እንደ ማለት ነው፡፡ ከማማረር መማር ነው ነገሩ!” ጥርስ ነጭ ይሁን አይሁን፤ ግን ይጠንክር” ይላሉ አበው፡፡ አንድም፤ “በካፊያው ምን አስሮጣችሁና ገና ዝናቡ አለ አይደለም ወይ” የሚለውን ልብ ብሎ ማሰብ ነው፡፡
ዲሞክራሲን፤ ፍትሐዊነትን፣ መልካም አስተዳደርን፣ እውነተኛ ምርጫን፣ እኩልነትትን፣ ዲፕሎማሲን፣ ለማግኘት አያሌ አመታትን አሳልፈናል፡፡ እንደ አፍ እንደማይቀልም፣ አውቀናል፡፡ ተገንዝበናል፡፡ አንድም የራሳችንን የሽኩቻ ባህላዊ አሽክላ በቀላሉ ለመላቀቅ ባለመቻል፤ አንድም ደሞ ከውጪ የሚመጣብንን ጫና ለመመከት ባለመታደል፣ ጠንክረን ዳር የመድረስ ነገር የህልም ሩጫ ሲሆንብን ከርሟል፡፡ ዊንስተን ቸርችል፤ “እውነት በጣም እፁብ በመሆኗ በውሸት የክብር ዘቦች መጠበቅ ይኖርባታል” ያለውን እንኳ ለመፈፀም መቻቻል አልሆነልንም፡፡ ድህነትን ለመዋጋት ያላግባብ የመበልፀግን አባዜ አስቀድሞ ማሸነፍ ያስፈልጋል፡፡ ወዲህ እየለፈፉ ወዲህ እየዘረፉ አይሆንም፡፡ ከልብ የማናደርገውን ነገር በአዋጅ ብንናገረው ግማሽ-ጐፈሬ ግማሽ-ልጭት ሆኖ ነው የሚቀረው፡፡ ሕግ ለሁሉም እኩል የሚሰራባት አገር ታስፈልገናለች! “ድካማችን ሁሉ የእንቧይ ካብ፣ የእንቧይ ካብ” የማንልባት አገር ታስፈልገናለች! ሟርት የማይበዛባት አገር ታስፈልገናለች! በአንድ ሰሞን ዘመቻ ብቻ አገር ይለወጣል ከሚል አስተሳሰብ የፀዳች አገር ታስፈልገናለች! ጅራፍ ራሱ ገርፎ እራሱ ሲጮህ የማናይባት አገር ታስፈልገናለች! ራሱ ሰርቆ አፋልጉኝ ይላል እንደተባለው አይን-አውጣ፣ ሌባ እያየን ዝም የማንልባት አገር ታስፈልገናለች! ባንድ በኩል የራሳችንን ድምፅ ብቻ መልሰን ለማዳመጥ ዝግጁ ከሆን፣ በሌላ በኩል እኔ ያልኩትን ብቻ አዳምጡ ካልን፤ የትላንትናን ዜማ ብቻ የምንደግም ከሆነ፤ “ገልቱ የራሷ ወጥ ይጣፍጣታል”፤ “ቀጥቃጭ ሲያረጅም ዱልዱም ይቀጠቅጣል” የሚሉትን ተረቶች ስናሰላስል መክረማችን ነው!

ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ ምሽት ብዙዎች በጉስቶ ሬስቶራንት የተደረደሩ የኮካ ኮላ ምርቶችን አተኩረው ሲመለከቱ ያስተዋለ ግር ሊሰኝ ይችላል፡፡ ነገሩ ወዲህ ነው፡፡ ሁሉም በኮካ ጠርሙሶች ላይ የሚፈልገው የራሱን ስም ነበር፡፡ ምክንያቱም ኮካ ኮላ የተለመዱ የኢትዮጵያውያን ስሞች የታተመባቸው ምርቶች ማቅረቡን ይፋ ያደረገበት ምሽት ነው፡፡
በእርግጥ ታዳሚው ሁሉ (ጋዜጠኞች፣ አርቲስቶችና ታዋቂ ሰዎች ተገኝተው ነበር) የየራሱን ስም አግኝቷል ማለት አይደለም፡፡ የተወሰኑ የተለመዱ ስሞች ተመርጠው ነው የታተሙት፡፡ ለዚህ ነው ብዙዎች በእልህ ስማቸውን ሲፈልጉ ያመሹት፡፡ የተወሰኑት ፈልገው አግኝተዋል፡፡ ያላገኙትም ግን መፅናኛ አላጡም፡፡
የሚስት ወይም የባል፣ የፍቅረኛ አሊያም የልጆች ወይም የዘመድ ወዳጅ ስሞች ያሉባቸው የኮካ መጠጦችን አግኝተዋል፡፡
እኔ ራሴ ስሜ ያለበት ኮካ ማግኘት ካልቻሉት መካከል አንዱ ነበርኩ፡፡ ሆኖም የባለቤቴ፣ የእናቴና የቅርብ ወዳጄ ስሞች ያሉባቸው ሦስት የኮካ ኮላ ምርቶችን በማግኘቴ ፈንድቄአለሁ፡፡ የበለጠ የፈነደቅሁት ደግሞ ኮካውን ለባለ ስሞቹ ሳጋራቸው ነው፡፡ኮካ የጀመረው አዲሱ የገበያ ትውውቅ ዘመቻም “Share A Coke” የሚል ነው፡፡ የኮካ ኮላ ኢትዮጵያ ብራንድ ማናጀር አቶ ምስክር ሙሉጌታ እንደተናገሩት፤ 200 የወጣቶችና 200 የአዋቂ ኢትዮጵያውያን ስሞችን በመለየት የአዋቂዎቹ ስሞች 1.5 ሊትር በሚይዘው “ከበር ቻቻ” ላይ የታተሙ ሲሆን የቀሩት 200  ስሞች ደግሞ 0.5 ሊትር በሚይዘው “ሽር-ሽር” የኮካ ጠርሙሶች ላይ ታትመዋል፡፡
በኮካ ምርት ላይ ከታተሙት ታዋቂ ስሞች መካከል “ሳባ”፣ “አበበ”፣ “ሃያት”፣ “ቦንቱ”፣ “ዊንታ”… ወዘተ የሚሉ ይገኙባቸዋል፡፡ የግለሰብ ስሞች የሰፈሩባቸው የኮካ ምርቶች በአገር አቀፍ ደረጃ በገበያ ላይ የዋሉ ሲሆን በዋና ዋና ማከፋፈያዎች፣ በሱቆች፣ በሆቴሎችና ሬስቶራንቶች ለሽያጭ እንደቀረቡ ተገልጿል፡፡
የኮካ ኮላ የገበያ ትውውቅ ዘመቻ በአህጉር ደረጃ (በመካከለኛው፣ በምስራቅ፣ በምዕራብና ደቡብ አፍሪካ) በመካሄድ ላይ ሲሆን ይሄም በገበያው ላይ በጐ ተፅእኖ እንደሚፈጥርና የኮካን “ደስታን የማጋራት” ዓለም አቀፋዊ እቅድ እንደሚያጠናክርለት ይጠበቃል ብሏል - ኩባንያው በመግለጫው፡፡ ኩባንያው እንደ ፌስ ቡክ ወይም ትዊተር ያሉ የማህበራዊ ሚዲያዎችን እንዲሁም ሌሎች አሳታፊ የማስታወቂያ መድረኮችን በመጠቀም፣ ደንበኞች የመረጧቸው ስሞች እንዲታተምላቸው ማዘዝ ብቻ ሳይሆን ኮካን የመጋራት አይረሴ የደስታ ቅፅበቶች ላይ ያተኮሩ መልእክቶችን፣ ፎቶዎችን ወይም ቪዲዮዎችን እንዲጋሩ የሚያስችል መሆኑ ታውቋል፡፡


* ጥናቱ ለ15 ዓመታት በአራት አገራት ላይ የተካሄደ ነው
*  ያለ ዕድሜ ጋብቻ ላይ ያልተጠበቀ ውጤት ተገኝቷል
* በህፃንነት የተጎዱ ልጆች ላይ የመሻሻል ሁኔታ ታይቷል
* የትምህርት ጥራት ጉዳይ አሳሳቢ መሆኑን ጥናቱ ያመለክታል

   በኦክስፎርድ ዩኒቨርስቲ በአራት የተለያዩ አገራት ለ15 ዓመታት የተካሄደው ልጆች ላይ ያተኮረ የ“ያንግ ላይቭስ” ጥናት ኢትዮጵያንም ያካትታል፡፡ በጥናቱ ላይ የተሳተፈው የፓንክረስት የምርምር ተቋም ዳይሬክተር ዶ/ር አሉላ ፓንክረስት በፕሮጀክቱ ዙሪያ የሰጡንን ማብራሪያ እንደሚከተለው ተጠናቅሮ ቀርቧል፡፡
የ“ያንግ ላይቭስ” ፕሮጀክት
“ያንግ ላይቭስ” የተሰኘው የጥናት ፕሮጀክት በኢትዮጵያ፣ ፔሩ፣ ቬትናምና ህንድ ላይ ለ15 ዓመታት የተካሄደ ሲሆን በልጆች ላይ ያተኮረ ነው፡፡ በየአገሩ በጥናቱ ውስጥ የተካተቱት እ.ኤ.አ በ2000 ዓ.ም የተወለዱና በአሁኑ ወቅት 14 አመት የሞላቸው ልጆች ናቸው፡፡ በእያንዳንዱ አገር ሶስት ሺህ ልጆች ላይ ነው የምናተኩረው፡፡ ሁለት ሺዎቹ በ2000 ዓ.ም የተወለዱ፣ አንድ ሺዎቹ ደግሞ ለማነፃፀሪያ እድሜያቸው ከፍ ያለ አሁን አስራ ዘጠኝ አመታቸው ላይ የሚገኙ ልጆች ናቸው፡፡  ሁለት ሺዎቹን ከተወለዱ ጀምሮ እየተከታተልናቸው ሲሆን እስከ አሁን ድረስ  በልጆቹና በወላጆቻቸው ላይ አራት ዙር ጥናቶች  ተካሂደዋል፡፡
በኢትዮጵያ ጥናት የተካተቱት ክልሎች አዲስ አበባ፣ ትግራይ፣ አማራ፣ ኦሮሚያና ደቡብ ክልሎች ሲሆኑ ከተማ ገጠር፣ ሀብታም ቤተሰብ ድሀ ቤተሰብ፣ ሴት ወንድ የሚሉ ስብጥሮችን ባካተተ መልኩ የተካሄደ ነው፡፡  ጥናቱ ድሀ ተኮር በመሆኑ የምግብ ዋስትና ችግር ባለባቸው  በሀያ የተለያዩ ቦታዎች ላይ የተሰራ ነው ፡፡
የጥናቱ ትኩረት
ጥናቱ አመጋገብና ጤና ፣ ትምህርት፣ የልጆች እድገትና የወደፊት አላማቸው ላይ ያተኩራል፡፡ ጥናቱን  የሚያሰራው የኢትዮጵያ የልማት ጥናት ድርጅት ሲሆን  የኮሙኒኬሽን ስራችን ደግሞ ከህፃናት አድን ድርጅት ጋር ነው፡፡ አሁን  በአራተኛው ዙር ጥናት ውጤትና ከአንድ እስከ አራት ዙር በተካሄዱት ጥናቶች ለውጦቹ ምንድን ናቸው የሚለው ላይ አተኩረን እየሰራን ነው፡፡    
ለጥናቱ የተመረጡ አገራት መመዘኛ
ጥናቱ የሚካሄደው በኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ነው፡፡ በተለያየ የአለም ክፍልና በተለያየ የእድገት ደረጃ ላይ የሚገኙ አገራት በሚል መመዘኛ ነው የተመረጡት፡፡ ኢትዮጵያ ድሀ አገር እንዲሁም  ለጠንካራ እድገትና ለልማት ጥሩ የመንግስት አቋም ያለበት በሚሉ መስፈርቶች ነው የተመረጠችው፡፡ ክልሎቹ የተመረጡበት መስፈርት ደግሞ ጥናቱ የረጅም አመታት ጥናት እንደመሆኑ መጠን ትልቁ ስጋታችን የምንከታተላቸው ልጆች ከአካባቢው እንዳይጠፉ የሚል ነበር፡፡ አርብቶ አደር አካባቢዎች ምናልባት ልጆችን ለመከታተል ያስቸግራል ከሚል አንፃር ነው በጥናቱ ያልተከታተሉት፡፡ ነገር ግን  ተጨማሪ ጥናቶችም ይኖሩናል፡፡ በህፃናት አድን ድርጅት ድጋፍ ለማነፃፀር እንዲያግዘን ትምህርት ቤት ላይ ትኩረት ያደረገ ጥናት በሶማሌና አፋር ክልል ላይ አድርገናል፡፡
ወላጅ ያጡ ልጆች የጉልበት ብዝበዛ፣ በከተማ እድገት ምክንያት ልጆችና ቤተሰቦቻቸው ከአካባቢያቸው ሲፈናቀሉ እንዲሁም ከኮንዶሚኒየም ቤት አሰራር ጋር የተገናኘ ጥናት አካሂደናል፡፡ በቅርቡም አንድ የጀመርነው ወደ አዋቂነት ሽግግርና ቤተሰብ እንዴት እንደሚመሰርቱ፣ እንዴት እንደሚያገቡ፣ እድሜ፣ ወሊድ እና የመሳሰሉት ላይ ያተኮረ ጥናት አለ፡፡
ሌላ የምንጀምረው ጥናት ደግሞ የመዋዕለ ህፃናትና ቅድመ ትምህርት ፕሮግራሞች ላይ ይሆናል፡፡ በጥናቱ ያገኘነው አንድ ነገር ምንድን ነው… የአንደኛ ክፍል ትምህርታቸውን ከመጀመራቸው በፊት በቄስ ትምህርትም ይሁን በመዋዕለ ህፃናት ተምረው ያለፉ ልጆች፣ ሲያድጉ ያንን እድል ካገኙት ጋር ሲነፃፀሩ የተሻለ ውጤት እንደሚያመጡ ነው፡፡ በማንበብ፣ በሂሳብና በማሰላሰል ችሎታቸው የተሻሉ ሆነው ተገኝተዋል፡፡ ይህ የመዋዕለ ህፃናት ደግሞ በመንግስት ብዙ ትኩረት ስላልተሰጠውና ትኩረት የሚሻ ጉዳይ በመሆኑ ይበልጥ ልናጠናው ሀሳብ አለን፡፡ ሌላው የጥናት ትኩረታችን ልጆች ላይ የሚደርስ ጥቃት ነው፡፡
የጥናቱ ውጤቶች
ጥናቱ ከሚያተኩርባቸው አንዱ አመጋገብ ላይ ነው፡፡ ሌላው ትምህርት፣ ሶስተኛው የልጆች እድገት ላይ ነው፡፡ አመጋገብን ስናይ ብዙ ለውጦች ያሉ ቢሆንም አሁንም የአመጋገብ እጥረት ችግር ላይ የወደቁ ልጆች እንዳሉ የጥናት ውጤቱ ያሳያል፡፡ ተስፋ የሚሰጡ ነገሮችም አሉ፡፡  እስከ አሁን አንድ ህፃን ከተፀነሰበት ጊዜ ጀምሮ ያሉት አንድ ሺህ ቀናት ለህፃኑ እድገት ወሳኝ እንደሆኑ ይታመን ነበር፡፡ በነዚህ አንድ ሺህ ቀናት ውስጥ ህፃናት ጥሩ ምግብ ካላገኙ በዕድገት ሂደታቸው የአእምሮና አካላዊ ጉዳት እንደሚያጋጥማቸውና ተስፋ አይኖራቸውም የሚል አስተሳሰብ ነበር፡፡ በጥናት ውጤቱ ግን እኛም ያልጠበቅነው ነገር ነው ያገኘነው፡፡ በልጅነታቸው ከተጎዱት ውስጥ የተወሰኑት በጣም ደህና ሆነው ነው ያደጉት፡፡ ቁመታቸው፣ የትምህርት ደረጃቸው ጨምሮ በብዙ ነገር ጥሩ ሁኔታ ላይ ናቸው፡፡ ከዚህም በመነሳት አንዳንዶቹ በህፃንነታቸው ተጎድተው ለምን ደህና ሆኑ? አንዳንዶቹ ለምን መጥፎ ሁኔታ ላይ ሆኑ? ለውጡን ያመጣው ምንድነው? በሚሉት ላይ አተኩረን ማጥናት እንፈልጋለን፡፡ የምግብ ዋስትና ችግር ትንሽ ተሻሽሎ ነው ያገኘነው፡፡ ልጆቹ የሚመገቧቸው ምግቦች  ስብጥርም ተሻሽሏል፡፡ የንፅህና ጉዳይም ላይ መሻሻሎች አሉ፡፡ ስጋት ሆኖ ያገኘነው የመጠጥ ውሀ ላይ ነው፡፡ የመጠጥ ውሀ ሁኔታ የባሰ ሆኖ ተገኝቷል፡፡
ትምህርት ላይ ጥሩ ተብሎ የሚጠቀሰው ሽፋን ነው፡፡ የገጠርና የከተማ ልዩነት እንዳለ ቢሆንም  የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ተማሪዎች ቁጥር በጣም ከፍ ብሏል፡፡ ከዚያም ሌላ የሴቶች ተማሪዎች ቁጥር ይበዛል፡፡ በትምህርት ላይ ያገኘነው አሳሳቢ ነገር የጥራት ጉዳይ ነው፡፡ ቅድም እንዳልኩሽ የሁለት እድሜ ክልል ነው የምናነፃፅረው፡፡ ይህን ስናደርግ የማንበብና የሂሳብ ችሎታ የመቀነስ አዝማሚያ አሳይቷል፤ በተለይ በገጠር፡፡ ይህ አሳስቦናል፡፡ በተለይ የሂሳቡ ውጤት መቀነሱ ጠለቅ ያለ ጥናት ያስፈልገዋል፡፡ ችግሩ ከትምህርት ቤቶች፣ ከመምህራን ችሎታና ፍላጎት ፣ ከተማሪዎች መብዛት፣ ከልጆች የስራ ጫና… የመሳሰሉት አንፃር መታየት ይኖርበታል፡፡  እዚህ ላይ መጠናት ያለበት ነገር የተማሩ እናቶች ያሏቸው ህፃናት የተሻሉ ሆነው መገኘታቸው ነው፡፡ ሌላው ያለ እድሜ ጋብቻ ላይ ያገኘነው ውጤት ያልጠበቅነው ነው፡፡ በጥናቱ ከተካተቱ ሌሎች አገራት ጋር ሲነፃፀር የኢትዮጵያ ዝቅ ያለ ነው፡፡
የአገራቱ ንፅፅር
አራቱን አገራት ስናነፃፅር፣ እኛ የጠበቅነው ያለ እድሜ ጋብቻ ላይ ኢትዮጵያ ከፍተኛውን ቁጥር ትይዛለች ብለን ነበር፡፡ ውጤቱ ግን በተቃራኒ ነው የሆነው፡፡ ህንድ ከፍተኛውን ቁጥር ይዛለች፡፡
በህንድ አስራ ዘጠኝ አመት ከደረሱ ሴቶች 34 በመቶው አግብተዋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን አስራ ሶስት በመቶ ብቻ ናቸው ያገቡት፡፡ ከአራቱ አገራት የቀነሰ ቁጥር ነው የተገኘው፡፡ልጆች በመውለድ ደግሞ አንደኛ ፔሩ ናት፤ ምክንያቱም ሳያገቡም ይወልዳሉ፡፡ ውጤቱ በደረጃ ሲቀመጥ፤ ፔሩ፣ ህንድ ፣ ቬትናምና ኢትዮጵያ ናቸው፡፡ ይህ እጅግ ተስፋ የሚሰጥ ግኝት ነው፡፡ የትምህርት ጥራት ላይ ኢትዮጵያና ህንድ የሚያሳስባቸው አገሮች ሆነው ተገኝተዋል፡፡ የፔሩ ልጆች በተለይ በሂሳብ በጣም የላቁ ናቸው፡፡ የጥራት ችግሩ በህንድና ኢትዮጵያ ተመሳሳይ ሲሆን በሌሎቹ አገራት ሲሻሻል ሁለቱ ላይ ለምን ዝቅ አለ የሚለው ገና ጥናት የሚፈልግ ነው፡፡ ግን አገሮቹ የጀመሩበት ሁኔታ ግምት ውስጥ ሲገባ ኢትዮጵያ ማዳረስ ላይ ጥሩ ውጤት አምጥታለች፡፡
ለዚህ ደግሞ ብዙ ስራ መሰራቱ ይታወቃል፡፡ ትምህርት ቤት መገንባት፣ መምህራንን ማሰልጠን፣ በአፍ መፍቻ ቋንቋ መማር፣ የመፃፊያ ፊደሎች ለውጥ… ግምት ውስጥ ሲገባ ጥራትን እንደሚነካ የሚጠበቅ ነው፡፡ በአመጋገብና በጤና ረገድ ኢትዮጵያ ችግር የነበረባትና ያለባት አገር ናት፡፡ ግን ሌሎቹም አገሮች ውስጥ ደሀው አካባቢ ችግሮች አሉ፡፡ በጣም የሚገርመው በአራቱም አገሮች በህፃንነት የተጎዱ ልጆች ላይ የመሻሻል ሁኔታ ታይቷል፡፡ ይህ አለምአቀፍ ክስተት ሲሆን ኢትዮጵያም ላይ ተመሳሳይ ውጤት ተገኝቷል፡፡

አቶ አንዳርጋቸው ባለፈው ወር ከባለቤታቸው ጋር በስልክ ተነጋግረዋል

የእንግሊዝ የፓርላማ አባላትን የያዘ የልኡካን ቡድን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ከእስር ማስፈታት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ለመደራደር በቀጣዩ ወር ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመጣ ዘ ኢንዲፔንደንት ትናንት ዘገበ፡፡
ሁሉንም የእንግሊዝ የፖለቲካ ፓርቲዎች በአባልነት የያዘው የፓርላማ አባላት የሰብዓዊ መብቶች ቡድን ምክትል ሊቀመንበር ጀርሚ ኮርባይን የሚመሩት የልኡካን ቡድኑ፣ ከሚመለከታቸው የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት ጋር በመምከር የሞት ፍርዱ ተፈጻሚ እንዳይሆንና ግለሰቡ ከእስር እንዲፈቱ ለማስቻል እንደሚሰሩ ዘገባው አመልክቷል፡፡አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንግሊዛዊ ዜግነት ያላቸው እንደመሆኑ የእንግሊዝ መንግስት ጉዳዩን አጽንኦት ሰጥቶ መከታተልና ግለሰቡን ከሞት ማዳን ይጠበቅበታል ያሉት ኮርባይን፤ ቡድኑ አቶ አንዳርጋቸው ግልጽ ባልሆነና ተቀባይነት በሌለው የህግ አካሄድ ለእስር ተዳርገዋል ብሎ እንደሚያምን ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ አቶ እንዳርጋቸው የአሸባሪ ቡድን አባል ቢሆኑም በእስር ላይ ተገቢው እንክብካቤ እየተደረገላቸው መሆኑን በተደጋጋሚ መግለፁ ይታወሳል፡፡
የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ቢሮ ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ መንግስት ባለፈው ነሃሴና ታህሳስ ወር ላይ ከተደረጉት ሁለት የመንግስት ተወካዮች ጉብኝቶች ውጭ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ለመጎብኘት እንዳንችል አግዶናል ብለዋል፡፡
የእንግሊዝ መንግስት የአቶ አንዳርጋቸው ጉዳይ በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያሳስበው ገልጸው፣ በግለሰቡ ላይ የተጣለው የሞት ፍርድ ተፈጻሚ እንዳይሆን በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጫና ማድረጉን እንደቀጠለበትም አስረድተዋል፡፡በለንደን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ የኢትዮጵያን መንግስት ለማፍረስ የሚሰራ አሸባሪ ቡድን አባል ናቸው፣ በእስር ላይ ሆነውም ተገቢው እንክብካቤ እየተደረገላቸው ነው፤ እስረኞችን ማሰቃየት ኢሰብአዊ ድርጊት እንደመሆኑ በዛሬዋ ኢትዮጵያ ውስጥ ተግባራዊ የሚደረግ  አይደለም ሲሉ መናገራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ አምነስቲ ኢንተርናሽናል በቅርቡ ይፋ ያደረገው ሪፖርት ግን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች አባላት ከቅርብ አመታት ወዲህ በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች የሚፈጸምባቸው ስቃይ እያየለ መምጣቱን የሚያመላክት መሆኑን አክሎ ገልጿል፡፡አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፤ ባለፈው ወር እንግሊዝ አገር ወደምትገኘው ባለቤታቸው ስልክ ደውለው መገናኘታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በአብዛኛው ስለልጆቻቸው ጉዳይ እንዳወሩ፣ ደህንነታቸውን እንደገለጹላቸው፣ እንዲሁም ለልጆቼ የማይሆን ተስፋ መስጠት አልፈልግም ማለታቸውን ባለቤታቸው እንደተናገሩ አመልክቷል፡፡



ጉዳት የደረሰባቸው ወገኖች ለጉዳቱ መባባስ የእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከያና መቆጣጠሪያን ተጠያቂ አድርገዋል
“ቃጠሎው ከጃዝ አምባ አልተነሳም” የጃዝ አምባ ዋና ሥራ አስኪያጅ
እሣቱ ከጣይቱ ኪችን አለመነሳቱን አረጋግጣለሁ - አቶ አያሌው ታደሰ የጣይቱ ሆቴል ሥራ አስኪያጅ
አጋጣሚው ምትክ የማላገኝላቸውን ነገሮች ያጣሁበት ክፉ አጋጣሚ ነው - የፊልም ፕሮዳክሽን ባለቤት

ባለፈው እሁድ ማለዳ ላይ በተነሳ የእሳት ቃጠሎ ከባድ ጉዳት የደረሰበት ታሪካዊው የእቴጌ ጣይቱ ሆቴል እሣት መነሻ እያወዛገበ ነው፡፡ ፖሊስ እሳቱ የተነሳው በጃዝ አምባ አዳራሽ ውስጥ በተዘረጉ የኤሌክትሪክ መስመሮች መጠላለፍ ምክንያት የተከሰተ እንደሆነ ቢገለፅም እሳቱ ከጃዝ አምባ አለመነሳቱን የጃዝ አምባ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ኤርምያስ ፋንቱ ገልፀዋል፡፡የጃዝ አምባ የኤሌክትሪክ ሲስተም አዲስና ደረጃውን የጠበቀ በመሆኑ ለእንዲህ አይነት አደጋ የሚጋለጥበት ምንም ምክንያት እንደሌለና ላለፉት አራት ዓመታት ምንም ዓይነት ችግር አጋጥሞ እንደማያውቅ የተናገሩት አቶ ኤርሚያስ፤ ፖሊስ እሳቱ የተነሳው ከጃዝ አምባ ነው ማለቱ እንዳሳዘናቸው ተናግረዋል፡፡ “ከሙዚቃ መሳሪያ ጋር በተገናኘ እሳቱ ተነስቷል እንዳይባል እንኳን እሁድ ጠዋት የጃዝ አምባ ሰራተኛ የሆነው ልጅ ገብቶ መድረኩን ለቴአትር ዝግጁ ለማድረግ ሁሉንም የሙዚቃ መሳሪያ አነሳስቶ ነበር” ብለዋል፡፡ ሌላው እሳቱ ከጃዝ አምባ እንዳልተነሳ እርግጠኛ የሆኑበትን ምክንያት አቶ ኤርሚያስ ሲናገሩ፤ የህብረት ባንክና የጃዝ አምባ ሲስተም አንድ መሆኑን ጠቁመው፣ እሳቱ ተነስቶ ከጀርባ በኩል ጭስ ሲታይ ሰዎች ከኤቲኤም ማሽን ብር እያወጡ እንደነበር አስታውሰው፣ እሳቱ ከጃዝ አምባ ቢነሳ ኖሮ ኤቲኤም ማሽኑ አይሰራም ነበር  ሲሉ እሳቱ ከጃዝ አምባ ተነሳ መባሉን እንደማይቀበሉት ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ በ2003 ዓ.ም በታዋቂዎቹ ሙዚቀኞች አበጋዝ ክብረወርቅ፣ ሄኖክ ተመስገን፣ ግሩም መዝሙር፣ ዮናስ ጎርፌና ሳሙኤል ገዛኸኝ የተቋቋመው ጃዝ አምባ፤ በቃጠሎው ከ3 ሚሊዮን ብር በላይ ውድመት ደርሶብኛል ብሏል፡፡ የጃዝ አምባው ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ኤርሚያስ ፋንቱ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ በአደጋው የተለያዩ እጅግ ውድ ዋጋ የሚያወጡ ዘመናዊ የሙዚቃ መሳሪያዎቻቸው ሙሉ በሙሉ መውደማቸውን ገልፀው እሳቱ ገና በጀመረባቸው ደቂቃዎች ጉዳዩን ለእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች ብናሳውቅም አፋጣኝ ምላሽ ልናገኝ አልቻልንም ብለዋል፡፡ “እሳት አደጋዎች ዘግይተው መድረሳቸው ሳያንስ ከስፍራው ከደረሱም በኋላም አደጋውን ለመከላከል ያሳዩት ቸልተኝነት ጉዳቱ እንዲባባስ አድርጎታል ብለዋል፡፡
እነመርሃዊ ስጦታ፣ ጋሽ ባህታ፣ ግርማ ነጋሽና መሰል አንጋፋ የሙዚቃ ሰዎች ወደ ሙዚቃ እንዲመለሱና ሞራላቸው እንዲጠገን በማድረጉ በኩል ጃዝ አምባ ትልቅ አስተዋፅኦ እንደነበረው የተናገሩት አቶ ኤርሚያስ፤ ቃጠሎው በእነዚህ ሰዎችም ላይ ጉዳት ያደረሰ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ጃዝ አምባውን ወደ ቀድሞው ሥራው ለመመለስ በኮንሰርትም ሆነ በሌላ መንገድ ገቢ ለማሰባሰብ ቃል መገባቱንና ብዙ ተዘግቶ ይቆያል የሚል እምነት እንደሌላቸውም ተናግረዋል፡፡ የአዲስ ተስፋ ኮሙኒኬሽንና ኢንተርቴይመንት ሥራ አስኪያጅ አቶ አዲስ ተስፋ በበኩላቸው፤ በቃጠሎው ምትክ የሚያገኙላቸውን ውድ ነገሮች ማጣታቸውን ጠቁመው፣ “ይህ በህይወቴ ብዙ ነገሬን ያጣሁበት ክፉ አጋጣሚ ነው” ብለዋል፡፡ በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስቴር አቶ መለስ ዜናዊ ሞት ጊዜ አርቲስቶች የሰሩትን ስራ በኃላፊነት ተረክበው ሲሰሩ እንደነበር የተናገሩት አቶ አዲስ፤ ሥራው ያለ ቀሪ ሙሉ በሙሉ መውደሙን ገልፀዋል፡፡ በቀርቡ ሠርተው ያጠናቀቁት “በቅኝትሽ” የተሰኘ አዲስ ፊልምን ጨምሮ የሠርግ ስነስርዓታቸውን ሲፈፅሙ የተቀረፁ የቪዲዮና የፎቶግራፍ ቅጂም ያለምንም ምትክ ወድሞብኛል ብለዋል፡፡ በገንዘብ ልተካቸው የማልችላቸው በርካታ ዘጋቢ ፊልሞችና ምትክ የማላገኝላቸው ንብረቶች ሙሉ በሙሉ ወድመውብኛል ሲሉም ሁኔታውን በሃዘን ገልፀዋል፡የእሣትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከያና መቆጣጠሪያ ባለስልጣን የኮሙኒኬሽን ኦፊሰር አቶ ንጋቱ ማሞ፤ በቃጠሎው ወቅት በፍጥነት ከቦታው አለመድረሳቸውንና ከደረሱም በኋላ እሣቱን ለማጥፋት ቸልተኝነት ማሣየታቸውን አስመልክቶ የቀረበባቸውን ቅሬታ፤ የሥራውን ባህርይ ካላማወቅና ከግንዛቤ ማነስ የተሰጠ አስተያየት ነው ሲሉ አጣጥለውታል፡፡
የእሣት አደጋው ጥሪ በተደረገልን በሁለት ደቂቃ ውስጥ ከሥፍራው ደርሰናል ያሉት ኦፊሰሩ፤ የሆቴሉ እድሜ፣ ርዝማኔና የተሠራበት ቁሳቁስ በፍጥነት ተቀጣጣይ መሆን አደጋውን አባብሶታል ብለዋል፡፡
ሠራተኞቹ ከሥፍራው እንደደረሱ ምንም አይነት ቸልተኝነት አላሣዩም ያሉት አቶ ንጋቱ፤ እሣት እንደ ሻማ እፍ ተብሎ የማይጠፋ በመሆኑና ህዝብ የማይረዳቸው ብዙ ቴክኒካል ነገሮች በመኖራቸው እነሱ እስከሚስተካከሉ ድረስ ደቂቃዎች ማለፋቸው አይቀሬ ነው ብለዋል፡፡  

ያጨሰ 1 ሺህ ብር፣ ያስጨሰ 3 ሺህ ብር ይቀጣል

የመቐለ ከተማ አስተዳደር በመዝናኛ ስፍራዎች፣ በትምህርት ቤቶች፣ በሆስፒታሎችና በመሳሰሉት ህዝብ የሚሰበሰብባቸው ስፍራዎች ሲጋራ እንዳይጨስ የሚከለክል ህግ ተግባራዊ ማድረጉ ተገለፀ፡፡በመዝናኛ ስፍራዎች ሲጋራ ሲያጨሱ የተገኙ ግለሰቦች ከ1 ሺህ ብር በላይ፣ ሲጋራ እንዲጨስ የፈቀዱ የመዝናኛ ስፍራዎች ባለቤቶች ደግሞ ከ3ሺህ ብር በላይ ቅጣት እንደሚጣልባቸው የጠቆመው የአዣንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገባ፣ በአገር አቀፍ ደረጃ ተግባራዊ ሊደረግ የታቀደውን ይህን ህግ በስራ ላይ በማዋል መቐለ የመጀመሪያዋ ከተማ መሆኗንም አስታውቋል፡፡ህጉ ከዚህ በተጨማሪም በስታዲየሞችና ሃይማኖታዊ ዝግጅቶች በሚከናወኑባቸው ስፍራዎች ሲጋራ እንዳይጨስ እንደሚከለክል ታውቋል፡፡በወጣትነት የእድሜ ክልል ውስጥ ከሚገኙ ኢትዮጵያውያን አንድ አስረኛ ያህሉ የሲጋራ ሱስ ተጠቂ እንደሆኑ የአለም የጤና ድርጅት መረጃ ይጠቁማል፡፡የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቅርቡ ህዝብ በሚሰበሰብባቸው ስፍራዎች ሲጋራ እንዳይጨስ የሚከለክልና በሲጋራ ሽያጭ ላይ ገደብ የሚጥል  አዋጅ ማጽደቁ ይታወሳል፡፡

በሲሚንቶ ገበያ የታየው ለውጥ በቢራ እየተደገመ ነው

   ከነባር የሲማንቶ አምራቾች ላይ ግዙፉ የደርባ ሚድሮክ ፋብሪካ ከዚያም የድሬዳዋው ናሽናል ሲሚንቶ ሲታከልበት እንደታየው በቢራ አምራቾች የተጧጧፈ ውድድርም በአጭር ጊዜ አስደናቂ የዋጋና የአቅርቦት ልዩነት እየታየ ነው፡፡ የዋጋ ንረት በተለመደበት አገር ደንበኞችን የመማረክ ብርቱ ፉክክርና ከፍተኛ የዋጋ ቅናሽ ከመታየቱም በተጨማሪ፤ ዘንድሮ ውድድሩን የሚያጠናክሩ አዳዲስ ግዙፍ ፋብሪካዎች ስራ የሚጀምሩበት ዓመት ሆኗል፡፡
ሰሞኑን ሄኒከን ካስመረቀው ፋብሪካ ብዙም ሳይቆይ፣ በጥቂት ሳምንታትና ወራት ሃበሻ ቢራና  ሌላ ግዙፍ የዳሽን ቢራ ፋብሪካ ገበያውን ይቀላቀላሉ፡፡
በቢዝነስ ውስጥ የመንግስት ድርሻና ጣልቃ ገብነት በቀነሰ ቁጥር፣ የምርቶች ዋጋና የአገልግሎት ጥራት እንደሚሻሻል እንደ ዶ/ር እሌኒ ገብረመድህን የመሳሰሉ ምሁራን በበርካታ አመታት ጥናትና ምርምር ያረጋገጡ ቢሆንም የነፃ ገበያ ውድድር ትሩፋት ያለጥናትና ምርምር በገሃድ ከታየባቸው መስኮች አንዱ የሲሚንቶ ገበያ ነው፡፡ አነስተኛ የግንባታ ስራ የጀመሩ ዜጐች በሲሚንቶ የዋጋ ውድነት፣ ትልልቅ ፕሮጀክት የጀመሩ ኢንቨስተሮች ደግሞ ለባለ አስር ፎቅ ህንፃ የሚበቃ ሲሚንቶ ሲጠይቁ የአንድ ፎቅ ብቻ እየተፈቀላቸው፣ ለዚያውም ተራ እስኪደርሳቸው ግማሽ አመት እየዘገየ፣ የዋጋው ውድነት ታክሎበት ለዓመታት ከፍተኛ እንቅፋት ሆኖ እንደቆየ ይታወቃል፡፡ አንዳንድ አነስተኛ የሲሚንቶ ፋብሪካ ኢንቨስትመንቶችና የነባሮቹ የማስፋፊያ ውጥኖች ላይ ግዙፉ የደርባ ሚድሮክ ሲሚንቶ ማምረት ሲጀምር ግን የቀድሞው የምርት እጥረትና የዋጋ ንረት ተረት ሆነ፡፡ የሲሚንቶ ዋጋ በግማሽ ቀነሰ፡፡ የድሬዳዋው ናሽናል ሲሚንቶ መጠናቀቁና ወደፊትም የናይጄሪያው ናሽናል ሲሚንቶ መጠናቀቁና ወደፊትም የናይጄሪያው ባለሃብት ፕሮጀክት እየተስፋፋ መሆኑ ደግሞ፤ የሲሚንቶ ችግር በነፃ የገበያ ውድድር ለዘለቄታው እንደሚቀየር ይጠቁማል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ መንግስት ከቢራ ቢዝነስ እየወጣ በመጣ ቁጥር፣ የምርትና የአገልግሎት ማሻሻያዎች  እየታዩ መምጣታቸው የሚታወቅ ሲሆን የነፃ ገበያ ፉክክሩና ትሩፋቶቹ ጐልተው የታዩት ከአዲስ አመት መግቢያ ጀምሮ ነው፡፡ በአዲሱ ዓመት ዋዜማ ሄኒከን፤ ዋልያ ቢራ ምርቱን በ10 ብር ሲያቀርብ ነው፤ አይቀሬው የነፃ ገበያ ትሩፋት በራሱ ጊዜ መዛመት የቀጠለው፡፡ ሌሎቹም ግንባታው እያጠናቀቁ ነው - ለዚያውም በየፊናቸው ሪኮርድ የሚሰብሩ ግዙፍ ፋብሪካዎችን፡፡ እዚህም ጋ ኒያላ፣ ዘመን የመሳሰሉ ምርቶችን ከማስተዋወቅ ጋር፣ ደንበኞችን ለመማረክ የዋጋ፣ የአገልግሎት ፉክክር አጧጥፈዋል፡፡ ቢጂአይ  በ11 ብር የሚሸጠውን አንድ ጃንቦ ብርጭቆ ድራፍት “ሃፒ ሃወር” በማለት ማክሰኞ፣ ሐሙስና ቅዳሜ በ8 ብር መሸጥ ጀመረ፡፡ ዲያጆ በፊናው፤ በዘጠኝ ብር ይሸጥ የነበረውን አንድ ጃንቦ ሜታ ድራፍት በ8 ብር እንደሚሸጥ ካስታወቀ በኋላ፤ በቅርቡ “ዘመን” በማለት የሰየመውን የቢራ ምርት በ10 ብር መሸጥ ጀምሯል፡፡ ቢጂአይ በበኩሉ፤ ከሰሞኑ  ሁለት ጠርሙስ ጊዮርጊስ ቢራ ለሚጠጣ ደንበኛ አንድ ጠርሙስ መመረቅ ጀምሯል፡ ደንበኞችን ለመማረክ የሚደረገው የዋና የአገልግሎት ፉክክር በዚህ አይቆምም፡፡ በቅርቡ ወደ ገበያ ለመግባት የተቃረቡ አዳዲስ ቢራ ፋብሪካዎች ከደጃችን እየደረሱ ነው፡፡ ሃበሻ ቢራ በቅርብ ሳምንታት ወደ ገበያ እንደሚገባ የገለፀ ሲሆን፣ ዳሽን ቢራ በደብረ ብርሃን የማስፋፊያ ግንባታውን አጠናቆ በመጋቢት ወር በቀን 3 ሚሊዮን ጠርሙስ ቢራ የሚያመርት ግዙፍ ፋብሪካ ያስመርቃል፡፡ ራያ ቢራም ግንባታውን ጨርሶ ወደ ገበያ ለመግባት እየተንደረደረ ነው፡፡ እነዚህ ሁሉ አዳዲስ ቢራ ፋብሪካዎች ምርቶቻቸውን ወደ ገበያ ሲያስገቡ ፉክክሩ ይበልጥ እንደሚጦፍ መገመት ይቻላል፡፡ የሄኒከን እና የዳሽን ቢራን ዘገባ በገጽ 11 መልከቱ፡፡

በመቶ ከሚቆጠሩ አገራት ከአስር ሺ በላይ ተሳታፊዎችን በማስተናገድ በአዲስ አበባ ከተካሄዱ አለማቀፍ ጉባኤዎች መካከል አንዱ ይሆናል የተባለው 3ኛው “ፋይናንስ ለልማት” የተሰኘ ዓለም አቀፍ ኮንፍረንስ በሰኔ ወር ለማካሄድ የኢትዮጵያ ባለስልጣናትና የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ዋና አማካሪዎች እየተዘጋጁ ነው፡፡
የተለያዩ ሀገራት መሪዎችና ሚኒስትሮች፤ እንዲሁም የቢዝነስ ሰዎችን ጨምሮ 10 ሺ ተሳታፊዎች በኮንፈረንሱ ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የተናገሩት የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም፤ ኮንፍረንሱ የእዳ ቅነሳና ስረዛ ላይ የሚያተኩር ይሆናል ብለዋል፡፡ ከፍተኛ እዳ የተከማቸባቸው የአፍሪካና የሌሎች ድሃ አገሮች መንግስታት ባለፉት አስር አመታት የእዳ ስረዛ እንደተረገላቸው የሚታወስ ሲሆን፤ ከቅርብ አመታት ወዲህ እንደገና እዳ ውስጥ እየገቡ መምጣታቸው ይታወቃል፡፡ በእዳ ብዛት ሌሎች የአፍሪካ መንግስታት በርካታ ቢሆኑም፤ በኢትዮጵያ መንግስት ስር የሚገኙ ድርጅቶች በብድር የተከማቸባቸው እዳ በጥቂት አመታት ውስጥ ከእጥፍ በላይ ጨምሯል፡፡
ከ14 ቢሊዮን ዶላር በላይ (ወደ 300 ቢሊዮን ብር ገደማ) የውጭ እዳ፣ እንዲሁም የዚያን ያህል 300 ቢሊዮን ብር የአገር ውስጥ የባንክ እዳ እንዳለባቸው ከመንግስት ተቋማት የተገኙ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡
በሰኔ ወር የሚካሄደው አለማቀፍ ጉባኤ ለድሃ አገራት የእዳ ቅነሳና ስረዛ በሚደረግበት ሁኔታ ላይ የሚወያይ ቢሆን፤ ከዚሁ ጐን ለጐን የድሃ አገር መንግስታት ራሳቸውን የሚችሉበት ጉዳይም ይነሳል ተብሏል፡፡ ጉባኤው የአገር ውስጥና ፋይናንስ መፍጠሪያ ዘዴዎችን በማስፋፋት ላይ ትኩረትን ያደርጋል ብለዋል፡፡ የሀገር ውስጥ አለማቀፍ ፋይናንስን እንዴት ማንቀሳቀስ ይቻላል በሚለው ጥያቄ ላይም  ይመከራል ተብሏል፡፡  
ሚኒስትሩ ሐሙስ ጥር 7 ቀን ከአሜሪካ ከመጡ የፕሬዚዳንት ኦባማ ከፍተኛ አማካሪዎች ጋር የተወያዩ ሲሆን፤ የሰኔው ጉባኤ ውጤታማ እንዲሆን ድጋፋቸውን ለመስጠት መምጣታቸውን ከኦባማ ዋና አማካሪዎች መካከል ከፍተኛ ተሰሚነት ያላቸው ጆን ፓዴስታ ተናግረዋል፡፡
 ዶ/ር ቴዎድሮስ አዳኖም በበኩላቸው፤ የኦባማ ዋና አማካሪዎች እዚህ መምጣታቸው ለጉዳዩ ምን ያህል ትኩረት እንደሰጡት የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡ በገንዘብ ሚኒስትሩ ሶፍያ አህመድ የሚመራ የበላይ ኮሚቴ የጉባኤውን ዝግጅት እያከናወነ ሲሆን፤ የመጀመሪያው አለማቀፍ የፋይናንስ ለልማት በ2002 ዓ.ም በሞንትሪያል ሁለተኛው አለማቀፍ “ፋይናንስ ለልማት” ደግሞ በ2008 ዓ.ም በዶሀ መካሄዱን ሚኒስትሩ ገልፀዋል፡፡