Administrator

Administrator

የታሪክ ሊቅ የነበሩት ፕሮፌሰር ታደሰ ታምራት ከትላንትና በስቲያ አረፉ፡፡ ፕሮፌሰር ታደሰ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት፣ በተመራማሪነትና በተለያዩ የአመራር ኃላፊነቶች የሠሩ ምሁር ነበሩ፡፡ የመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያን ታሪክ ለአገርና ለዓለም ያበረከቱ ሲሆን፤ በተለይም ቤተ መንግሥትና ቤተ ክህነት በኢትዮጵያ (Church and State in Ethiopia, 1270-1527) የተሰኘው መጽሐፋቸው ዓለም አቀፍ እውቅና አስገኝቶላቸዋል፡፡

ፕሮፌሰር ታደሰ የረቀቀ የምርምር ችሎታቸውን በድኅረ ምረቃ ፕሮግራም ለተማሪዎቻቸው ለማስተላለፍ የበቁ ምሁር ሲሆኑ የምርምር ሥራዎቻቸው ዓለም አቀፍ እውቅናን አትርፈው፣ በካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ፣ በኖርዝዌስተርን ዩኒቨርሲቲ፣ በበክኔል ዩኒቨርሲቲና በኢሊኖይ ዩኒቨርሲቲ በጎብኚ ፕሮፌሰርነት ለማገልገል በቅተዋል፡፡

በተጨማሪም ፕሮፌሰር ታደሰ ከፍተኛ ግምት የሚሰጠውን የኮሌጅ ደ ፍራንስ የክብር ሜዳይና የድኅረ ምረቃ ትምህርት ያካሄዱበት ከነበረው “ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ለንደን” የአፍሪካና እስያ ጥናት ማዕከል የክብር ፌሎውነት ሽልማት አስገኝቶላቸዋል፡፡ ፕሮፌሰር ታደሰ ታምራት፤ ከምርምር መስኩ ባሻገር ለአያሌ ዓመታት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን በተለያዩ የአመራር ኃላፊነቶች ያገለገሉ ሲሆን እ.ኤ.አ. ከ1977-84 በኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ዳይሬክተር፤ ከ1986-92 የሶሻል ሳይንስ ኮሌጅ ዲን፤ ከ1995-99 በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ ዳይሬክተር ዋና ኤዲተር ፣ በኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ዳይሬክተር በመሆን ብቁ አመራር ከመስጠታቸውም በላይ 8ኛውን ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ጥናት ጉባኤ በማዘጋጀት የኢትዮጵያ ጥናት ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለስ ምንጊዜም የማይዘነጋ ውለታ ውለው ያለፉ ምሁር ናቸው፡፡

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት (ዩኤን) ባለፈው ሳምንት ከሮም ከተማ ለአለማችን ረሃብተኞች አንድ ምክርና የምስራች ወሬ አሰራጭቷል። የምስራች ወሬው፣ “እነ ጥንዚዛን በመመገብ ከረሃብ መገላገል ይቻላል” የሚል ነው። በደግነት የለገሰን ምክር ደግሞ፣ ከረሃብ ለመዳን “ነፍሳትን ብሉ” ይላል። ዩኤን ይህን “ምክርና የምስራች” በይፋ ለመላው አለም ያበሰረው፣ የአለም ምግብና እርሻ ድርጅት (ፋኦ) ባዘጋጀው ባለ 200 ገፅ ሰነድ አማካኝነት ነው። የሰነዱ ርዕስ እንዲህ ይላል፣ Edible insects፡ Future prospects for food and feed security። እነ ጉንዳን፣ የመጪው ዘመን የምግብ ዋስት ተስፋዎቻችን እንደሆኑ የሚሰብክ ሰነድ ነው። “ረሃብተኛ ሆኖ ለብዙ አመታት በተመፅዋችነት መቆየት፣ መጨረሻው ውርደት ሆነ? ‘ጥንዚዛ ብላ!’ የሚል የስላቅ ምላሽ የምንሰማበት ደረጃ ላይ ደረስን?” የሚል ጥያቄ የሚፈጠርባቸው የድሃ አገር ሰዎች መኖራቸው የማይቀር ነው። በእርግጥም፣ በርካታ አለማቀፍ የሚዲያ ተቋማት፣ ዜናውን የዘገቡት በስላቅ መንፈስ ነው።

“ዩኤን ለአለማችን ረሃብተኞች አንድ ምክር አለው - በራሪ ነፍሳትን መብላት…” በማለት ነው ያሁ-ኒውስ ዘገባውን የሚጀምረው። የአሶሼትድ ፕሬስ ዘገባም ተመሳሳይ ነው። “የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ ረሃብን፣ የአለም ሙቀትንና ብክለትን ለመዋጋት አዳዲስ መሳሪያዎችን ታጥቋል” በማለት የሚጀምረው የአሶሼትድ ፕሬስ ዜና፣ የዩኤን መሳሪያዎችን ለማየት ከፈለግን ሩቅ መሄድ እንደማይኖርብን ይገልፃል። አካበቢያችንን ብንቃኝ በቂ ነው። የዩኤን “ዘመናዊ” መሳሪያዎች፣ በሄድንበት ቦታ ሁሉ በዙሪያችን የሚያንዣብቡና አፍንጫችን ስር ሳይቀር “በረራ” የሚያዘወትሩ ናቸው። ይህንን የስላቅ አገላለፅ በማስቀደም አሶሼትድ ፕሬስ ዘገባውን ሲቀጥል… በዩኤን እምነት፣ የአለም ረሃብተኞች የወደፊት ተስፋ በራሪ ነፍሳትን መመገብ እንደሆነ ይገልጻል።

በዩኤን ስር፣ ለረሃብተኞች የእርዳታ እህል በማጓጓዝ የሚታወቀው ፋኦ፣ በራሪ ነፍሳት ለመብል የሚስማሙ መሆናቸውን ሲያስረዳ “በራሪ ነፍሳት በፕሮቲን የበለፀጉ ናቸው” ብሏል። እናም፣ ዩኤን እና ፋኦ፣ ረሃብን ለመከላከል ተስፋቸውን የጣሉት በበራሪ ነፍሳት ላይ ነው። ግን የነፍሳት ጥቅም፣ ከምግብነትም የላቀ እንደሆነ የገለፁት ዩኤንና ፋኦ፣ ለአካባቢ ጥበቃ ግሩም መፍትሄ ይሆንልናል ብለዋል። በሬና ላም፣ በግና ፍየል ብዙ ሳር እየበሉ አካባቢን ያራቁታሉ፤ የተለያዩ የጋዝ አይነቶችን እያመነጩ አካባቢን ይበክላሉ ይላል ዩኤን። ስለዚህ፣ አካባቢን የማያራቁቱና የማይበክሉ በራሪ ነፍሳት፣ ቀለባችሁ ይሁኑ በማለት ምክሩን ለግሷል። 1900 ያህል የነፍሳት ዝርያዎች ለምግብነት ተስማሚ መሆናቸውን ዩኤን ጠቅሶ፣ ጉንዳን፣ ጥንዚዛ፣ አንበጣ፣ ዝንብ፣ ምስጥ፣ አባጨጓሬ እንዲሁም ሌሎች በራሪና ተስፈንጣሪ ነፍሳትን በምሳሌነት ዘርዝሯል። የዩኤን እና የፋኦ መግለጫ፣ በረሃብተኞች ላይ የተሰነዘረ ስላቅ ይመስላል ብለው የሚቆጡ መኖራቸው አይቀርም።

ነገር ግን ብዙም አይገርምም። እድሜ ልክ እርዳታ እየጠበቀ የሚኖር ረሃብተኛ፣ ውሎ አድሮ “ከራበህ ጥንዚዛ ብላ!” የሚል ምላሽ ማግኘቱ የማይቀር ነው። ውርደት ሊመስል ይችላል። ከሁሉም የከፋ ውርደት ግን፣ ራስን ለመቻል አለመጣርና አለመቻል ነው። በሌላ በኩል ደግሞ፣ “ጥንዚዛና ዝንብ ተመገቡ” የሚለው ዘመቻ፣ በየጊዜው የሚያገረሽ የዩኤን እብደት ይመስላል። እናም፣ ለጊዜው ከተወራለት በኋላ፣ ወረቱ ሲያልቅ ተረስቶ ይቀራል ብለን እንገምት ይሆናል። ግን በዋዛ አይረሳም። ባለፉት 10 አመታት ለዘመቻው በጀት ሲመደብለት ቆይቷል። አሁንም ይመደብለታል። ለምን ቢባል… ዩኤንና ፋኦ ምላሽ አላቸው -ነፍሳትን የመመገብ ልምድ እንዲስፋፋና የህዝቡን ግንዛቤ ለማሳደግ (awareness raising) በጀት ይመድባሉ።

ሰነዶችን ለማዘጋጀትና ለማሰራጨት፣ በአባል አገራት የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ለማካሄድ፣ አዳዲስ ህጎችንም ለማዘጋጀት ገንዘብ ያወጣሉ። አነስተኛና ጥቃቅን ተቋማት፣ በራሪ ነፍሳትን የማርባት ሥራ እንዲጀምሩም ይደጉማሉ። ዩኤንና ፋኦ፣ ይሄን ሁሉ የሚያደርጉት፣ “ረሃብተኞችን ለመደገፍ” ነው። በሌላ አነጋገር፣ ዩኤንና ፋኦ፣ ብዙ ገንዘብና ሃብት ሳያባክኑበት በፊት፣ “የበራሪ ነፍሳት ፕሮጀክታቸውን” በአጭር ጊዜ እንደዘበት ይረሱታል ተብሎ አይጠበቅም።

ናሳ፣ ‘የምግብ ማተሚያ ማሽን” ለሚሰራ 125ሺ ዶላር ከፈለ ከሁለት ሳምንታት በፊት፣ በማተሚያ ማሽን የተሰራ የመጀመሪያው ሽጉጥ ጥቅም ላይ መዋሉን ተከትሎ፣ ምግብ “አትሞ” የሚያወጣ ማሽን ለመስራት የኮንትራት ውል ተፈረመ። አንጃን የተሰኘ የኢንጂነሪንግ ኩባንያ በስድስት ወራት ውስጥ ሰርቶ ለናሳ የሚያቀርበው 3D ማተሚያ ማሽን፣ “ፒዛ” አትሞ የሚያወጣ ነው። በጥንታዊው መንገድ ማሳ አርሶና እህል ፈጭቶ፣ እንስሳ አደልቦና ወጥ አብስሎ ምግብ ማዘጋጀት ሊቀር ነው? ወደ ማርስ ጠፈርተኞችን ለመላክ የአስር አመት ፕሮጀክት የጀመረው የአሜሪካ የጠፈር ምርምር ተቋም ናሳ፣ ጠፈርተኞቹ ሁለት አመት በሚፈጀው ጉዟቸው ላይ የምግብ ማተሚያ ማሽን እንዲኖራቸው ይፈልጋል።

አንጃን የተሰኘው ድርጅት በበኩሉ፣ የምግብ ማተሚያ ማሽን ለመፍጠርና ለመስራት የተነሳሳው፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ የአለማችን የምግብ እጥረት እየተባባሰ ይሄዳል በሚል ሃሳብ ነው። የአለም ህዝብ በየጊዜው እየጨመረ ነው። እህል እየፈጨንና እንስሳ እያረድን ብቻ የምንቀጥል ከሆነ፣ በቂ ምግብ አይገኝም ይላሉ የአንጃን ኩባንያ ባለሙያዎች። ስለዚህ ዘመናዊ የምግብ ምንጭና አዘገጃጀት ያስፈልጋል። ከተለያዩ ነገሮች ውስጥ፣ ለምግብነት ከማይውሉ የሳርና የአረም እፅዋት፣ ከጠጣርና ከፈሳሽ ነገሮች ጭምር፣ ፕሮቲኖችን፣ ካርቦሃይድሬቶችን፣ ቪታሚኖችንና ቅባቶችን አንጥሮ በማውጣት፤ በዱቄት መልክ ማዘጋጀት፣ የመጀመሪያው ስራ ይሆናል። ለፅሁፍ ማተሚያ ማሽን፣ ወረቀትና ቀለም እናዘጋጅ የለ? ለ3D የምግብ ማተሚያ ማሽን ደግሞ፣ የንጥረነገር ዱቄት ይዘጋጃል።

እነዚህን ዱቄቶች በመጠቀም ፒዛ አትሞ የሚያወጣ ማተሚያ ማሽን ሰርቶ ለናሳ ለማቅረብ የተፈራረመው አንጃን፣ ወደ ፊት ረሃብን ከአለማችን ማስወገድ የሚቻለው በምግብ ማተሚያ ማሽኖች አማካኝነት ነው ብሎ ያምናል። ኳርትዝ የተሰኘው የቴክኖሎጂ ዜና ተቋም እንደዘገበው፣ ከምግብ ማተሚያ ማሽን ሊገኝ የሚችል ሌላ ልዩ ጥቅም አለ። ሰዎች እንደየምርጫቸውና እንደጤንነት ሁኔታቸው፣ የንጥረ ነገር መጠናቸው በሂሳብ የተቀመረ የተለያዩ ምግቦችን በማዘጋጀት እንዲመገቡ ያስችላቸዋል። መቼም የሰው ልጅ አእምሮ፣ ነቅቶ ካሰበና ተግቶ ከሰራ፣ የማይፈጥረው መላ የለም - የዘንድሮው አዲስ መላ፣ 3D ማተሚያ ማሽን ነው። ግን፣ በዚህ ቴክኖሎጂ፣ ሽጉጥና ምግብ ተከታትለው መምጣታቸው አይገርምም? ለነገሩ፣ ሁለቱም (ሽጉጥና ምግብ) በቀጥታ ከህይወት ጋር የተሳሰሩ ናቸው።

“የሠራሁት ፊልም አንድ ተጨማሪ ተመልካች ካስከፋ ሥራዬን ሠርቻለሁ ማለት ነው!” ዉዲ አለን

 አንዳንድ ዕውነቶች ሲያረጁ ተረት ይመስላሉ፡፡ በአንድ አምባገነናዊ ሥርዓት ውስጥ አንድ ዕብድ ሰውዬ መንገድ ላይ በግልጽ በሚታይ ቦታ ላይ ቆሞ፤ “እዚህ አገር ስኳር የለም!” “እዚህ አገር ዘይት የለም!” “እዚህ አገር ዱቄት የለም!” እያለ እየጮኸ ይናገራል፤ አሉ፡፡ ከዚያም የመንግሥቱ የፀጥታ ሠራተኞች ይይዙና ወደ እሥር ቤት ይወስዱታል፡፡ አስፈላጊውን ጥያቄዎች ያደርጉለትና ወደ አንድ ክፍል ይወስዱታል፡፡ ከዚያም፤ “እሺ፤ ስኳር የለም አደለም ያልከው፤ ና ላሳይህ” ይለዋል የፀጥታ ሠራተኛው፡፡ ወስዶ የስኳር ዶንያ ጋ ያደርሰውና ማጅራቱን ይዞ ባፍ - ጢሙ ስኳሩ ላይ ይደፋዋል፡፡ ሰውዬውም ፊቱ ስኳር በስኳር ሆኖ ይነሳል፡፡ ቀጥሎ ወደ ሌላ ክፍል ይወስደውና፤ “እህ አጅሬ! ዱቄት የለም አደለ ያልከው?” ይላል የፀጥታ ኃላፊው፡፡

“አዎ!” ይላል እሥረኛው፡፡ “በል ና አሳይሃለሁ!” ይላል ኃላፊው፡፡ ይወስድና ያንን እሥረኛ፤ ዱቄት ጆንያ ውስጥ፤ ጭንቅላቱን ይዞ ባፍጢሙ ይደፋዋል፡፡ ከጆንያው ጭንቅላቱን ይዞ ሲያወጣው ያገር ዱቄት ቅሞ ይነሳል፡፡ ደሞ ሌላ ክፍል ወስዶ፤ “አጅሬ ዘይት የለም! አደለ ያልከው? ና ላሳይህ!” ወስዶ ጭንቅላቱን ይዞ ዘይት በርሜል ውስጥ ባፍ - ጢሙ ይደፍቀዋል፡፡ በመጨረሻ በል ውጣና ሂድ ይለዋል፡፡ እሥረኛው - ከእሥሩ ቅጽር ጊቢ ሲወጣ አንድ ዱሮ የሚያውው ሰው ያገኘውና፤ “እንዴ! አያ እገሌ ተለቀቅህ?” “አዎ!” “ምን አደረጉህ?” “ኧረ ተወኝ ምን ያላረጉኝ ነገር አለ! ብቻ እንኳን በርበሬ የሌለ፤ ጉድ ሆኜልህ ነበር!” ይለዋል፡፡ ቀጥሎ፤ “እዚህ አገር በርበሬ የለም! እዚህ አገር በርበሬ የለም!!” እያለ የመንገድ ላይ ጩኸቱን ቀጠለ፡፡

                                                      * * *

የተበደለ ህዝብ ጩኸቱን መቀጠሉን አይተውም፡፡ ያለውን አለኝ የሌለውን የለኝም ይል ዘንድ አንደበት ተሰጥቶታል፡፡ መብቱን ይረዳል፡፡ ነፃነቱን ያውቃል፡፡ ከተራቆተ ታረዝኩ፣ ፍትሕ ከጐደለው ተበደልኩ፣ ከተዘረፈ ተበዘበዝኩ ይል ዘንድ ልሣን አለው፡፡ እጀ - ሠባራ እንዳይሆን መሥራት፣ የታፈነ እንዳይሆን የመናገርና ሃሳቡን በነፃነት የመግለጽ መብቱን መጠቀም፣ የሚያየውን ጉድለት ማሳየት ይገባዋል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን የሚታዘበውን ሙስና ለአደባባይ ፀሐይ ማብቃት ይገባዋል፡፡ እርምጃ የሚወስደውን አካል በጥንቃቄ ማበረታታት ያሻል፡፡ በታሪክ እንዳየነው “ንጉሡ የወሰዱትን ገንዘብ እንዲመልሱ ቢጠየቁ አሻፈረኝ አሉ!” ተብሎ አይታለፍም - ስዊስ ያስቀመጡትን ገንዘብ መሆኑ ነው፡፡ ጆርጅ በናርድ ሾው የተባለው ታዋቂ የሒስና የምፀት ሰው፤ “ለማንኛውም ትንሽ ሴንሰርሺፕ ያስፈልጋልኮ” ተብሎ በባለሥልጣን ሲነገረው፤ “በትንሹ ማርገዝ የሚባል ነገር መኖሩን ካሳመንከኝ ትንሽ ሴንሰርሺፕ ያልከውን ነገር እቀበላለሁ!” ብሎ ነበረ፡፡ ይህን መንግሥታችን ልብ ይበል!! ዕውነቱን ነው የግፍ ትንሽ የለውም፡፡ የማያድግ በደልም የለም - ጊዜና ቦታ ካለ፡፡ ሰንሰለቱ ከታወቀ ስለቀለበቱ ማውራት ድካም ይሆን ይሆናል፡፡ ያላግባብ የሚሰጥ ፍርድም ሆነ ያላግባብ የተካበተ ገንዘብና ንብረት፤ ሁለቱም ለሀገርና ህዝብ በደል ናቸው፡፡ ፀሐፍት፤ “They shout at most against the vices they themselves are guality of” ይላሉ፡፡

ጅራፍ እራሱ ገርፎ እራሱ ይጮህ፤ እንደማለት ነው በዙር - አማርኛ፡፡ ትላንት ሙሰኞችን እናወድማለን ያሉ፣ ዛሬ ሙሰኛ ሆነው ሲገኙ ልንል የምንችለው አንድ ሁነኛ ቃል - “ጠርጥር!” ነው፡፡ ልባችን ሙስና አፋችን ፀረ - ሙስና ሲሆን፤ ጥርጣሬ ፎቁን ሲሰራ ማየት አይገርምም! “ማንኛው ይሆን ሀቀኛ?” “የቱ ይሆን ዕውነተኛ ንግግር?” ብሎ መጠራጠር ጥፋት አይሆንም፡፡ ሃሳብ አቅራቢም፣ ወሰኝም፣ አስፈፃሚም፤ የተወሰነ ሰው የሆነበት ሥርዓት ካለ ጤና አይኖርም፡፡ ፈረንጆች absolute power corrupts absolutely! የሚሉት ለዚህ ነው፡፡ “ፍፁም ሥልጣን ፍፁም ሙሰኛን ይወልዳል” እንደማለት ነው፡፡ ሁሉን ማዘዝ ከቻልኩ ማን አለኝ ከልካይ! ብሎ መደገግ አይቀሬ ነው፡፡ አደባባይ ላይ ተንፈራጥጦ የቆመህን ህንፃ ካላሳዩ እርካታ አይመጣም፡፡ “እቺ ምን ሰማይ ነች፣ በዐይን የምትታይ?” እንዳለው እብሪተኛ ንጉሥ ጣራ አልበቃ ይለናል፡፡ “ጣራው ጣር እንደሚሆንብን” እንዘነጋለን፡፡ የወደቁት ያጠፉት ጥፋት በእኛ አይደገምም እያልን እንፎክራለን፡፡ ያለነው ግን እዚያው ውቂያኖስ ውስጥ ነው፡፡

እንጠንቀቅ! የውቂያኖሱ ሥርዓተ ማዕበል አንድ ነውና፡፡ ማኪያቬሊ “ሰዎች የአስቸኳይ ጥቅምና ፍላጐታቸው ተገዢ ከመሆናቸው የተነሳ አታላይና አጭበርባሪ ሰው ከመጣ ለመታለልና ለመጭበርበር ዝግጁ ናቸው” ይለናል፡፡ አጋጣሚው የፈቀደላቸው እንዳታለሉ ይኖራሉ፡፡ ያልቀናቸውና የተነቃባቸው የእሥር ቤት ሰለባ ይሆናሉ፡፡ እንጂ ሥርዓቱ አልተለወጠም፡፡ ቁልፉ ጉዳይም ይሄው ነው፡፡ ሥርዓቱ በምን ይለወጥ? እስከመቼ፤ እንደወላይትኛው ተረት “አይጧ ከሌለች ጉድጓዱ ከየት መጣ?” እያልን ቁጭ ብለን እናያለን? የተጀመው መንገድ ከቀጠለ አይጧን ማጥመድም ሆነ፣ ጉድጓዱን መድፈን እንችላለን፡፡ “ወዳጅህን ከጐረቤት ታገኛለህ፡፡ ጠላትህን እናትህ ትወልድልሃለች” ይላል አበሻ፡፡ ከጉያችን ያለውን እንፈትሽ፡፡

የተቋጠረውን እየፈታን፣ የተዘጋ የሚመስለውን እየከፈትን፣ አደባባዩን ምሽግ ያደረገውን እየደረመስን፣ ወመቴን ከአለሌ፣ ጨውን ከአሞሌ፣ ቱሪስቱን ከፒስኮር፣ ህንዱን ከባኒያን፣ ጭልፊቱን ከአሞራው፣ የፖለቲካ ነጋዴውን ከሀቀኛ መንገደኛው፤ ለይተንና አበጥረን መጓዝ ለሀገርና ለህዝብ የሚመች አጓጓዝ ነው፡፡ ጐረቤትንም ልብ እንበል - ዓለም አላፊ ነው፣ መልክ ረጋፊ ነው! ያኔ፤ የተሳካ ሥራ ለመሥራታችን የራሳችን ልበ - ሙሉነት ማረጋገጫ ሲሰጠን፤ እንደፊልም ተዋናዩ ኮሜዲያን እንደዉዲ አለን፤ በምፀት፤ “የሠራሁት ፊልም አንድ ተጨማሪ ተመልካች ካስከፋ፣ ሥራዬን ሠርቻለሁ” ለማለት እንችላለን!!

ከሳምንት በኋላ በሚጀመረው ቢግ ብራዘር አፍሪካ ላይ ኢትዮጵያ እንደምትሳተፍ የታወቀ ሲሆን የውድድሩ አሸናፊ 300ሺ ዶላር ይሸለማል ተባለ፡፡ “ዘ ቼስ” በሚል ልዩ ስያሜ በሚደረገው የአፍሪካ ትልቁ የሪያሊቲ ሾው ውድድር ላይ ከ14 አገራት የተውጣጡ 28 ተሳታፊዎች ለ91 ቀናት አብረው ለመኖር ተዘጋጅተዋል፡፡ ባለፈው ዓመት ተሳታፊ ያልወከለችው ኢትዮጵያ ዘንድሮ በውድድሩ ውስጥ የገባች ሲሆን አንጎላ፤ ቦትስዋና፤ ጋና፤ ማላዊ፤ ናሚቢያ፤ ናይጄርያ፤ ኬንያ፤ ሴራሊዮን፤ ደቡብ አፍሪካ፤ ኡጋንዳ፤ ታንዛኒያ፤ ዛምቢያ እና ዚምባቡዌም ይሳተፋሉ፡፡

በቀን ለ24 ሰዓታት በሳምንት ለ7 ቀን በዲኤስቲቪ ሁለት ቻናሎች በቀጥታ በሚሰራጨው አብሮ የመኖር ውድድር ላይ እስከመጨረሻው ቀን በመቆየት የሚያሸንፈው ነዋሪ፤ የ300ሺ ዶላር ሽልማት ይጠብቀዋል፡፡ የቢግ ብራዘር አፍሪካ 8 ሙሉ ቀረፃ በደቡብ አፍሪካ የሚከናወን ሲሆን የሚሰራው እና የሚያዘጋጀው አፍሪካ ማጂክ ኢንተርቴይመንት ከደቡብ አፍሪካው ኩባንያ ኤንዴሞል ጋር በመተባበር ነው፡፡ ከሶስት ዓመት በፊት ኢትዮጵያዊው የአመራር ባለሙያ ያዕቆብ አቤሴሎም፤ በቢግ ብራዘር አፍሪካ ተሳትፎ 15ኛ ደረጃ ያገኘ ሲሆን ከሁለት ዓመት በፊት የህግ ባለሙያዋ ሃና መኩርያ እና የማርኬቲንግ ባለሙያው ዳንኤል ተሳትፈው በተለይ ሃና እስከመጨረሻው የውድድሩ ምእራፍ መጓዟ ይታወሳል፡፡

በመላው ዓለም ለእይታ ከበቃ ሁለት ሳምንት የሆነው “አይረን ማን 3” እስካሁን 980 ሚሊዮን ብር ገቢ በማስገባት ዘንድሮ ለእይታ ከበቁ ፊልሞች ብቸኛው ሊሆን በቃ፡፡ ፊልሙ ከምረቃው በኋላ በሁለት ሳምንት ጊዜ ውስጥ በመላው ዓለም በ40 አገራት ለእይታ በቅቶ ነው አንድ ቢሊዮን ዶላር ሊደርስ የተቃረበ ገቢ በማስገባት ሪከርድ ያስመዘገበው፡፡ በቻይና በመጀመርያ ቀኑ 21.5 ሚሊዮን ዶላር በማስገኘትም ሌላ ሪከርድ አስመዝግቧል፡፡ በአይማክስ የፊልም ፎርማት በመላው ዓለም 40 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ያስገባው ፊልሙ በዚህም ሌላ ክብረወሰን ይዟል፡፡ በሰሜን አሜሪካ ብቻ በ15 ቀን ውስጥ 295 ሚሊዮን ዶላር ማስገባትም ችሏል፡፡

በሌላ በኩል “አይረን ማን 3” ላይ በመሪ ተዋናይነት የሰራው ሮበርት ዳውኒ ጁኒዬር፤ የፊልሙን አራተኛ እና አምስተኛ ክፍሎች ለመስራት በ100 ሚሊዮን ዶላር ክፍያ መስማማቱ በሆሊውድ የተዋናዮች ክፍያ ታሪክ የመጀመርያው አድርጎታል፡፡ ሮበርት ዳውኒ፤ በሶስቱ የአይረን ማን ፊልሞች 50 ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝቷል፡፡ ተዋናዩ በአይረን ማን ፊልሞች ላይ ቶኒ ስታርክ የተባለ እና በጦር ኢንዱስትሪ ባለሙያነት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በሰራው ብረት ለበስ ወታደር፤ ዓለም አቀፍ ወንጀለኞችን በመወጋት የሚንቀሳቀስ ገፀባህርይን ይተውናል፡፡ በ“አይረን ማን 3” ላይ ከሮበርት ዳውኒ ጋር የሚሰሩት ሌሎች ምርጥ ተዋናዮች ጅዌኔትዝ ፓልትሮው፤ ዶን ቺድል፤ ጋሪ ፒርስ እና ሬቤካ ሆል ናቸው፡፡ የፊልም ኢንዱስትሪው ባለሙያዎች፤ በ200 ሚሊዮን ዶላር በጀት የተሰራው “አይረን ማን 3” ፤ በመላው ዓለም 1.15 ቢሊዮን ዶላር ገቢ በማስገባት ትርፋማ እንደሚሆን ተንብየዋል፡፡ የመጀመርያው “አየረን ማን” ፊልም፤ 585.2 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም “አየረን ማን 2” 623.9 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ያገኙ ሲሆን ሶስተኛው ከወጣ ከሁለት ሳምንት በኋላ የአየረን ማን ፊልሞች ገቢ 2.19 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል፡፡

በ“ፋስት ኤንድ ፊርዬስ” ተከታታይ ፊልሞች ዓለም አቀፍ ዝናን ያተረፈው ተዋናይ ቪን ዲዝል፤ የፌስቡክ ድረገፅን ተወዳጅ በማድረጌ ኩባንያው አንድ ቢሊዮን ዶላር ሊከፍለኝ ይገባል አለ፡፡ በፌስ ቡክ ድረገፅ 48 ሚሊዮን ወዳጆችን ያፈራው ተዋናዩ፤ የፌስቡክን ተወዳጅነት በመጨመር የሚስተካከለኝ የለም ሲል ለ“ኢንተርቴይመንት ዊክሊ” ተናግሯል፡፡ ከአራት ዓመት በፊት የፌስቡክ ድረገፁን እንደከፈተ አንድ ሚሊዮን የሚደርሱ ወዳጆችን በማፍራት ሊፎካከሩት የቻሉት የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ብቻ እንደነበሩ ያስታወሰው ቪን ዲዝል፤ ከአድናቂዎቹ ጋር በማህበራዊ ድረገፀ መነጋገር በመጀመሩ በተወዳጅነት በዓለም አንደኛ የፌስ ቡክ አድራሻ ይዞ መቆየቱን አብራርቷል፡፡ ተዋናዩ ባለፉት አራት ዓመታት በፌስቡክ ገፁ ከ11 በላይ የፎቶ አልበሞች እና 40 የቪድዮ ምስሎችን በማጋራት ወዳጆቹን ሲያስደስት ቆይቷል፡፡ በአክሽን ፊልሞቹ የሚታወቀው ቪን ዲዝል፤ በ19 ፊልሞች ላይ በመሪ ተዋናይነት፤ በረዳት ተዋናይነት፤ በአዘጋጅነት እና በተባባሪ አዘጋጅነት የሰራ ሲሆን በአጠቃላይ 2.8 ቢሊዮን ዶላር ገቢ አስገኝቷል፡፡

በኢትዮጵያ ብሔረሰቦች የሐዘን ሥርአት ላይ ያተኮረ የሥዕል አውደርእይ ዛሬ እንደሚቀርብ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአለ የሥነ ጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት የሚቀርበውን የአንድ ቀን የኢንስታሌሽን ሥእሎች የሚቀርቡበት አውደርእይ ያዘጋጁት ትምህርት ቤቱ እና ኑሮዋን ኖርዌይ ባደረገችው ኢትዮጵያዊት ሠዐሊ ማህሌት ኦግቤ ሀብቴ ከሌሎች ሠዐሊያን ጋር በመተባበር ነው፡፡ ዝግጅቱ በዳንስ እና ሌሎች ኪነጥበባዊ ግብአቶች ታጅቦ ዛሬ ከቀኑ 11 ሰዓት እንደሚቀርብ የዝግጅቱ ፕሮዳክሽን ማናጀር መሠረት ኃይሌ በተለይ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡

የኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድን 1500ኛ ዓመት ልደት የተመለከተ አውደጥናት ዛሬ እንደሚካሄድ በኢትዮጽያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምርያ ማህበረ ቅዱሳን አስታወቀ፡፡ ዛሬ ከጧቱ 2፡30 እስከ 11፡30 በግዮን ሆቴል በሚደረገው የአንድ ቀን አውደጥናት የቅዱስ ያሬድ ልደትና የምናኔ ሕይወት፣ ዜማና ድርሰት፣ የቅዱስ ያሬድ ድርሳናት ከነገረ መለኮት አንፃር፣ የቅዱስ ያሬድ ዜማ ተፅእኖ በባህላዊና ዘመናዊ ሙዚቃ የሚሉ ርእሶች ለውይይት ይቀርባሉ፡፡ ከዚህ በተያያዘም ነገ ከቀኑ 7 እስከ 11 ሰዓት የቅዱስ ያሬድ ልደትን የተመለከተ ሲምፖዚየም በኢትዮጵያ የስብሰባ ማእከል መዘጋጀቱን ማህበሩ አስታውቋል፡፡

የፋሽስት ኢጣሊያን ወረራ በመቃወም በ1928 ሐምሌ 22 ሰማእት የሆኑትን ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስን ተንተርሶ በደራሲ ፀሐይ መልአኩ የተፃፈው ረዥም ልቦለድ መጽሐፍ ምርቃት በአንድ ሳምንት ተራዘመ፡፡ ግንቦት 11 ቀን 2005 ዓ.ም ከጧቱ 2፡30 ትያትር ቤቱ ሊመረቅ የነበረው መጽሐፍ ምርቃት ወደ ግንቦት 18 ቀን ተላልፏል፡፡ ደራሲ ፀሐይ መልአኩ ካሁን ቀደም “ቋሳ”፣ “አንጉዝ”፣ “እመምኔት”፣ “ቢስ ራሄል”፣ እና “የንስሐ ሸንጎ” በተሰኙት የረዥም ልቦለድ መፃሕፍቷ እንዲሁም “የስሜት ትኩሳት” ቁጥር ፩ እና ፪ የግጥም መጻሕፍቷ ትታወቃለች፡