Administrator

Administrator

“ቱሪዝም አሁንም ገና ጨቅላ ነው”
የአገሪቱን ቱሪዝም ምቅር ቤት የሚመሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው
አስጐብኚ ምንም ነገር አላውቅም ማለት የለበትም
ባለፈው የጥምቀት በዓል ሰሞን በጎንደር ከተከናወኑት ጉዳዮች አንዱ የጎንደር እህት ከተማ በሆነችው የፈረንሳይዋ ቬንሰን ከተማ ሁለገብ እድሳት ተደርጎለት የተጠናቀቀውን የ“ራስ ግንብ”ን ማስመረቅ ነበር፡፡
ግንቡ ራስ ሚካኤል ስሁልን ጨምሮ በርካታ የጎንደር ነገስታት ራሶች መኖርያ ስለነበር ነው፡፡ “ራስ ግንብ” የተባለው፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ ለ20 ዓመታት የፋሲል አብያተ-መንግስትን በማስጎብኘት እውቅናና አድናቆትን ካተረፉት
የቱሪዝም ከፍተኛ ኤክስፐርት አቶ ጌትነት ይግዛው ንጉሴ ጋር በጐንደር የቱሪዝም እንቅስቃሴ፣ በታሪካዊ ቅርሶች እድሳት፣
በአስጎብኝነት ህይወታቸው፣ እንዲሁም
በቱሪዝም ኢንዱስትሪና ተያያዥ
ጉዳዮች ዙርያ
ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡  

ወደ ፌደራል ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከመምጣትዎ በፊት የአፄ ፋሲል አብያተ መንግስትን ለ20 ዓመታት እንዳስጎበኙ ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ ስለዚህ ጉዳይ ያጫውቱኝ …
ዌል! ይሄ ረጅም ጊዜ ነው፡፡ ለ 21 ዓመታት የቱሪስት ጋይድ ነበርኩ፤ የጎንደር አካባቢ ሲኒየር ጋይድ ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ ከዛ በኋላ የጎንደር ዓለም አቀፍ ቅርስ አስተዳደር (የአብያተ መንግስታት አስተዳደር) ማናጀር ሆንኩኝ፡፡ የዩኔስኮም ተጠሪ (ፎካል ፐርሰን) ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ የጎንደር ቅርሶች በዓለም አቀፍ ደረጃ የተመዘገቡ በመሆናቸው፣ አሁን እኔ ስራዬን ወደ ፌደራል ባህልና ቱሪዝም በመቀየር የዛሬ አንድ ዓመት ከአምስት ወር አካባቢ ጀምሮ የቱሪዝም ከፍተኛ ኤክስፐርት ሆኜ እየሰራሁ ነው፡፡
ጎንደርን ለመጎብኘት እጅግ በርካታ ቱሪስቶች ይመጣሉ፤ አንዱ ሲሄድ ሌላው እየተተካ በቀን ለብዙ ጎብኚዎች ገለፃ ማድረግ ይኖርብዎታል፡፡ አድካሚነቱ ምን ያህል ነበር?
የማስጎብኘት ሥራ የዲፕሎማሲ ስራ እንደመሆኑ የአገርን ታሪክ፣ የአገርና ህዝብን ባህል፣ የአገርን ኢኮኖሚና ፖለቲካ እያገናዘቡ፣ ህዝብንና አገርን ማዕከል በማድረግ ገለፃ የሚደረግበት ነው፡፡ እንዳልሽው የተለያየ ዓይነት ቱሪስት ነው የሚመጣው፤ ከአገር ውስጥም ከውጭም ማለቴ ነው፡፡ እጅግ በርካት የሆኑ ሰዎችን አግኝቻለሁ። ለምሳሌ የአገር መሪዎች፣ በርካታ የጥናትና ምርምር ስራ የሚሰሩ ባለሙያዎች፣ ለመዝናናትና አዲስ ተመክሮ ለመቅሰም የሚጓዙና መሰል ሰዎችን አግኝቻለሁ፡፡ ምክንያቱም ሁለት አስርት ዓመታት ቀላል አይደሉም፡፡ እንደውም ዝም ብዬ ሳስበው የያኔው ስራዬ አሁን ካለሁበት ስራ አንፃር ሲታይ እጅግ ውስብስብ ነበር፡፡ ምክንያቱም በቱሪዝም ህግ መሰረት አንድ አስጎብኚ “አላውቅም” አይልም፡፡ ስለዚህ የምትጠየቂውን ሁሉ መመለስ ይጠበቅብሻል፡፡ ስትመልሺ ታዲያ ታሪክሽን እንዳታዛቢ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ አለብሽ፡፡ ምክንያቱም አሁን በዓለማችን ውስጥ ከፍተኛ የታሪክ ሽሚያ አለ፡፡ ሃይማኖትን፣ ዘርንና ቀለምን ሳታይ ለሁሉም እኩል መስተንግዶ መስጠት ግዴታሽ ነዉ። ከዚህ አንፃር ሳየው በጣም የተወሳሰበና አድካሚ ነበር፤ ሆኖም ኃላፊነቴን በአግባቡ ተወጥቻለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡
የትምህርት ዝግጅትዎ ከቱሪዝም ሙያ ጋር የተያያዘ ነው?
የትምህርት ዝግጅቴ ከቱሪዝምና ከቅርስ አስተዳደር የወጣ አይደለም፡፡ ከሰርተፍኬት ጀምሮ እስከ ማስተርስ ዲግሪ የሰራሁት ከቱሪዝምና ከቅርስ አስተዳደር እስከ ሄሪቴጅ ማኔጅመንት ድረስ ነው። ለምሳሌ ማስተርሴን የሰራሁት በቱሪዝምና ሄሪቴጅ ማኔጅመንት፣ የመጀመሪያ ዲግሪዬ በቱሪዝም ማኔጅመንት፣ ዲፕሎማዬ በእንግሊዝ አገር ከሚገኝ ካምብሪጅ ኮሌጅ በቱሪዝም እና ትራቭል ኤጀንት ማኔጅመንት ሲሆን ሰርተፍኬቴን ያገኘሁት ደግሞ በአገራችን በቱሪዝም ዘርፍ ፈር ቀዳጅ ከሆነው CTTI ቱሪስት ጋይድ በተባለ ዘርፍ ነው፡፡ እንደምታይው ከቱሪዝም አልወጣሁም ማለት ይቻላል፡፡
አንዳንድ ጎብኚዎች በተለይም ከአውሮፓ እና ከሌሎች አህጉራት የሚመጡት የግንቦቹን አሰራር ረቂቅነት ሲመለከቱ እጃችን አለበት በማለት እንደሚሟገቱ ሰምቻለሁ፡፡ እነዚህን ዓይነት ፈታኝ ጥያቄዎች እንዴት ነበር የሚጋፈጧቸው?  
የዓለም ስልጣኔ መጀመሪያ የአፍሪካ አህጉር እንደሆነ በማስረዳት እጀምራለሁ፡፡ ምክንያቱም አገራችን የሰው ዘር መገኛ ሆና በዓለም ከታወቀችበት ጊዜ ጀምሮ እስካሁን በሌላ ዓለም ቀደምት የሰው ዘር ቅሪት አልተገኘም፡፡ ስልጣኔ የሚነሳው ደግሞ ከሰው ልጅ መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ሰው የኑሮ ጫናዎቹን ለማቃለል ደፋ ቀና ሲልና ለችግሮቹ መፍትሄ ሲፈልግ ነው ስልጣኔ እና ፈጠራ አብሮ የሚመጣው፡፡ የመጀመሪያው መልሴ ከላይ የገለፅኩት ነው፡፡ አውሮፓውያን የስልጣኔ ምንጭ አውሮፓ ናት ካሉ፣ ያ በእነሱ መልክ ነው የሚሆነው። አሜሪካኖችም እንዲያ ሲሉ በእነሱ መልክና እሳቤ ነው፡፡ ለምን ካልሽኝ … የዛሬ 400 ዓመት የተመሰረተች አገር፣ ከሶስት ሺህ ዓመት በላይ ታሪክ ካላት አገር ጋር እኩል መሆን አትችልም፡፡ የሰው ልጅ እስካለ የኪነ-ህንፃም ሆነ ሌላም ስልጣኔ ይኖራል፡፡ ይህን ሳስረዳቸው የዚያ ጥበብና ስልጣኔ ባለቤት እንደሆንን ያምናሉ፤ የመንፈስ ቅናት አድሮባቸው ካልካዱ በስተቀር ማለቴ ነው፡፡
ከኪነ-ህንፃ ጋር በተያያዘ በተለይ የውጭ ጎብኚዎች ምን ይላሉ? እንዴት ነው ስሜታቸው? ይገርምሻል! አግራሞታቸው ሰፊ ነው፡፡ ጥቁር ህዝብ ቤተ-መንግስት ውስጥ የሚኖርባት የአፍሪካ አገር መሆኗ ይገርማቸዋል፡፡ በእነሱ እምነት ቤተ-መንግስት ውስጥ የሚኖረው አውሮፓዊ ብቻ ነው፤ የታላቋ ብሪታኒያ ነገስታቶች፣ የፈረንሳይ ነገስታቶች ብቻ ይመስሏቸዋል፡፡ ይታይሽ … ከ16ኛው ክ/ዘመን መጀመሪያ አንስቶ እስከ 17ኛው ክ/ዘመን፣ በጎንደርና አካባቢዋ ከፍተኛ ቤተ-መንግስታት ተሰርተው ነበር፤ ስልጣኔውም ነበር፡፡ እንደሚታየው ግንባታው ከኖራ ጋር ተቀላቅሎ ዝም ብሎ የተሰራ ሳይሆን የኪነ-ህንፃ ልዩነቱን ጠብቆ በጥልቅ ፈጠራ የተገነባ ነው እና የኪነ-ህንፃ ጥበብ ያረፈባቸው፣ ገላጭ የሆኑ ህብረ-ህንፃዎች ናቸው፡፡ ይህን በአግራሞትና በመደመም ነው የሚመለከቱት፡፡ ከዚህ አንፃር የሚያነሱት ዘርፈ ብዙ ጥያቄዎች ማባሪያ የላቸውም፡፡
ከ400 ዓመት በላይ እድሜ ያላቸው የፋሲል አብያተ መንግስታት ግንባታዎችን ከአሁኑ ዘመን የኪነ-ጥበብ ህንፃ ጋር ማነፃፀር ይቻላል? እርስዎ ያነፃፅሩ ቢባሉ እንዴት ይገልፁታል?
እንግዲህ ውርስ ሊኖር ይችላል፤ የእውቀትና የቴክኖሎጂ ውርስ ማለቴ ነው፡፡ ነገር ግን ሙሉ በሙሉ ውርስ ይኖራል ብሎ መናገር ይከብዳል፡፡ የጎንደርን ኪነ-ህንፃዎች አንቺ ቅድም እንደገለፅሽው የውጭ ዜጎች ናቸው የገነቡት ይላሉ፤ እኔ በፍፁም በዚህ አልስማማም፡፡ የኪነ-ህንፃ ጥበብ ልክ እንደ ሙዚቃ የአለም ቋንቋ ነው፡፡ አንዲት አገር የራሷ ወጥ የሆነ የኪነ-ጥበብ ህንፃ የላትም፡፡ በምን ምክንያት ካልሽ … በእኛ በሰዎች ምክንያት፡፡ ሰው የተለያየ የህይወት ውህደት አለው፤ ይዘዋወራል፡፡ ሲዘዋወር አካባቢውን ይመስላል፤ ከአካባቢው የሚወስደውም ጥበብ ይኖራል፡፡
ያ ሰው ከሄደበት አካባቢ የወረሰውን ጥበብ፣ ሌላ ቀን የራሱ አድርጎ ይተረጉመዋል፤ ነገር ግን የነበረበት አካባቢ ተፅዕኖ ያርፍበታል፡፡ በዚህ የተነሳ ኪነ-ህንፃ የዓለም ቋንቋ ነው ይሉታል፡፡ እዚህ አካባቢ የፖርቹጋል፣ የህንድ፣ የአርመንና የሞሪሽየስ ዜጎች ነበሩ፡፡ በእርግጥ ከጎንደር በፊት የተሰሩ የአክሱም፣ የላሊበላና የየሀ ህንፃዎች አሉ፡፡ ሰዎች እስካሉ ድረስ እንኳን ጥበብ ዘርም ይቀያየራሉ፤ ከዚህ አንፃር የጎንደር ኪነ-ህንፃዎች የእነዚህ አገር ሰዎች ተፅዕኖዎች አለበት ይባላል፡፡
ከስድስቱ የፋሲል አብያተ መንግስታት አንዱ፣ በህንዳዊ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ እንደተሰራ ይነገራል። እውነት ነው?
እርግጥ አብዱልከሪም የሚባል ህንዳዊ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ በአፄ ፋሲለደስ ዘመን ነበር፡፡ እንደሚታወቀው አፄ ፋሲል አባታቸው አፄ ሱስንዮስ የካቶሊክን እምነት ለማስፋፋት ጥረት ያደርጉ ስለነበር በ1622 (ቅድመ ክርስቶስ ልደት) በርካታ ህዝብ አልቋል፡፡ አፄ ፋሲል ይህን አልተቀበሉም ነበር፡፡ የንግስና ዙፋኑን ሲይዙ 7 ሺህ ገደማ የካቶሊክ ሚሽነሪዎችን ከኢትዮጵያ አስወጥተዋል፡፡ የዛን ጊዜ ታዲያ ኢትዮጵያ ቢያንስ ለ200 ዓመት በሯን ለአውሮፓውያን  ዘግታ ነበር፤ ይህ “የጨለማ ዘመን” እያሉ የሚጠሩት ነው፡፡ ስለዚህ አብዱልከሪም የተባለው ህንዳዊ ሰውዬ ምንም እንኳ ሙስሊም ቢሆንም በኪነ-ህንፃ ጥበብ የተካነ ስለነበር፤ ከአባ ገ/እግዚያብሔር ጋር በመሆን የንጉስ አፄ ፋሲልን ቤተ መንግስት እንዲሰራ ተደርጓል፡፡ በዚህ ምክንያት የህንዶች ኪነ-ህንፃ ተፅዕኖ አለበት፡፡
እስቲ ወደ እርስዎ የአስጎብኚነት ጊዜ እንመለስ። ዝነኛ አስጎብኚ እንደነበሩና እንደነ ሲኤንኤን፣ ቢቢሲ እና መሰል ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ዘጋቢ ፊልም ለመስራት ሲመጡ፣ በሰከንድ 120 ዶላር ለእርሶ እየከፈሉ በሙያዎ ያገለግሏቸው እንደነበር ሰምቻለሁ፡፡ እውነት ነው? እስቲ ያጫውቱኝ…
ይህ እንግዲህ በፈረንጆቹ 1991 ዓ.ም አካባቢ ነው፡፡ ያኔ “ፍሮም ፖል ቱ ፖል” የተሰኘ ፊልም ተሰርቶ ነበር፡፡ የዛን ጊዜ አብሬ ሰርቻለሁ፤ ክፍያው በሰከንድ ሳይሆን በሰዓት ነበር፡፡ በሰዓት 150 ዶላር! ለእኛ አገር ትልቅ ይመስላል እንጂ ለእነሱ በጣም ዝቅተኛ ክፍያ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ገና ከለንደን ከመነሳታቸው ከአንድ ወር በፊት ነው አፈላልገው ያገኙኝ፡፡ ከዚያም ያንን ፊልም ሰርተናል፡፡ ከቢቢሲ በኋላ ከሌሎችም የፊልም ቡድኖች ጋር ብዙ ስራዎችን ሰርተናል፡፡ ለምሳሌ ከጀርመንና ከጣሊያን፣ የፊልም ቡድኖች ጋር ሰርቻለሁ፡፡ ከፍተኛ የህይወት ልምድም አግኝቼበታለሁ፡፡
በጎንደር ከተማ የመንግስት ሰራተኛ ሆነው መኪና የነበረዎት ብቸኛው ሰው እንደነበሩም ሰምቻለሁ …
(ሳ…ቅ!) በአንዳንድ አጋጣሚ በግልሽ ቢዝነስ ስትሰሪ ገንዘብ ታገኛለሽ፡፡ ስለዚህ መኪና መግዛት ቻልኩ፡፡ የዛን ጊዜ መኪና እንደአሁኑ ውድ አልነበረም፤ እኔ በገዛሁበት ወቅት 50ሺ ነበር ዋጋው። የዛሬ 12 ዓመት አካባቢ ማለት ነው፡፡ እርግጥ ያኔ ብሩ በደንብ ዋጋ ነበረው፡፡ ስለዚህ በዚያን ወቅት መኪና መግዛት ያን ያህል የሚያስደንቅ ነገር አልነበረም፡፡
የበፊቷ መኪና ተቀየረች ወይስ…
አልተቀየረችም ራሷ ናት፤ አዲስ አበባ ነው አሁን ያለችው፡፡
ስለ አገራችን ቱሪዝም ስታስብ የሚቆጭህ ነገር ምንድን ነው?
አሁን የሚቆጨኝ ነገር የለም! እኔ ቱሪዝምን በአስተሳሰብ ደረጃ ተረድቼ ስሰራ በነበረበት ወቅት ብዙ ሰው ገና አልተረዳውም ነበር፡፡ ቱሪዝምን የምቾት፣ የቅንጦትና የመዝናናት አድርገው የሚያዩት ወገኖች ነበሩ፡፡ ቱሪዝም ግን እንደዛ አይደለም፡፡ ቱሪዝም የስራ እድል ፈጣሪ ነው፤ ዳቦ ነው፤ ሰላም ነው፤ ሁሉም ነገር ማለት ነው፡፡ አገርሽ ውስጥ ያለውን የባህልና የታሪክ ቦታዎች የምትሸጭበትና የስራ እድል የሚፈጥር ኢንዱስትሪም ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ የዚያን ጊዜ ሰዎች ቱሪዝምን የተረዱበት አስተሳሰብ ትክክል አልነበረም፡፡ እናም ሰው መቼ በትክክል እንደሚገባው፣ ገብቶትም መቼ ወደ ቢዝነስ እንደሚቀይረውና ተጠቃሚ የሚሆንበትን ቀን እናፍቅ ነበር፡፡ በአሁኑ ሰዓት ግን ሁሉም ሰው ስለቱሪዝም ያወራል፡፡ ስለ ገፅታ ግንባታው፣ ስለ ስራ ፈጣሪነቱና ስለተያያዥ ጉዳዮች ሰው ሲናገር ስሰማ በጣም እደሰታለሁ፤
ምክንያቱም ማንም ሳይረዳሽ ብቻሽን ስለቱሪዝም የምታወሪበት ጊዜ አልፎ አሁን አጋር ስታገኚና ሰው ሲገባው በጣም ያስደስትሻል፡፡
በወሬ ብቻ ነው ወይስ በተግባርም ነው?
አገሪቱ በዚህ ቅኝት ውስጥ እየገባች ነው ብሎ መናገር ይቻላል፡፡ ምክንያቱም ወደ ኢንዱስትሪው እንሸጋገራለን የሚል እቅድ ላይ ነው ያለነው፡፡ ወደ ኢንዱስትሪ ዘመን ሲገባ የበለጠ የሚያይለው የአገልግሎቱ ዘርፍ ነው፡፡ አሁን አገራችን ወደዚያ እየሄደች ነው፡፡ የቱሪስቱ ፍሰት እየጨመረ ነው። የበላይ አመራሮችና ውሳኔ ሰጪ አካላትም ስለቱሪዝም እያቀነቀኑ ነው፡፡ የትራንስፎርሜሽን ኤጀንሲ ተቋቁሟል፡፡ ከዚያ ባሻገር የአገሪቱን የቱሪዝም ምክር ቤት የሚመሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው፡፡ ይህን ስታይ አገሪቱ ወደ ቅኝቱ ገብታለች ማለት እችላለሁ፡፡ እና ቁጭት የለኝም፤ እንዲያውም በጣም ደስታ ነኝ፡፡
ጎንደር ባሏት ታሪካዊ መስህቦች የሚገባትን ያህል ተጠቅማለች ይላሉ?
እዚህ ላይ ነው ወሬ የምናቆመው! ከተማዋ ያላትን ሀብት በአግባቡ አልምታ፣ የህብረተሰቡን ግንዛቤ አሁን ካለው የበለጠ አስፍታ፣ ህዝቡን ቀጥተኛ ተጠቃሚ አድርጋ የማስኬድ ስራ ገና ይቀራታል፡፡ ቱሪዝም ኢትዮጵያ ውስጥ የ30 እና የ40 ዓመት እድሜ ነው ያለው፡፡ ቅርስ አጠባበቅም እንደዚሁ! ምክንያቱም ቱሪዝም ካልሽ የምትሸጪው ቅርስ ስለሆነ፡፡ ኢትዮጵያ እኮ ከ80 በላይ ብሄር ብሄረሰቦች፣ ከ35ሺህ በላይ ገዳማትና ቤተክርስቲያናት፣ ከ25 በላይ ከፍታቸው ከ4ሺህ ሜ በላይ የሆኑ ተራሮች፣ በምስራቅ አፍሪካ ትልቁ የስምጥ ሸለቆ ስክራች መነሻና ሌሎች አገሮችን የሚያቋርጥ ስምጥ ሸለቆ እንዲሁም አሁንም በአይን የሚታይና አክቲቭ የሆነ እሳተ ጎመራ ያላት ናት። ይህም ሆኖ ቱሪዝም አሁንም በአገራችን ጨቅላ ነው፡፡ ይህንን ወደ ጥቅም ለመለወጥ እኔም፣ አንቺም ሌላውም በየሞያው የቤት ስራ አለበት፡፡ አለቀ፡፡
አሁን ቆመን የምንነጋገርበት ቦታ በእነ ፋሲለደስ ዘመን ራሶችና ተመሳሳይ ስልጣን የነበራቸው ሰዎች የሚኖሩበት “ራስ ግንብ” ነው፡፡ ዛሬ እዚህ ቦታ የተገናኘነውም የጎንደር እህት ከተማ በሆነችው የፈረንሳይ ቬንሰን ከተማ እድሳት ተደርጎለት የምርቃት ስነ-ስርዓቱ በመሆኑ ነው፡፡ በእድሳቱ የተነሳ “ራስ ግንብ” ብቻ ሳይሆን ሌሎችም አብያተ መንግስታት ምንነታቸውን እና የቀድሞ መስህብነታቸውን ያጣሉ የሚል ስጋት አለ፡፡ ይህ እንዳይሆን ምን ምን ቅድመ ጥንቃቄዎች ይደረጋሉ?
አሪፍ ጥያቄ ነው! አገራችን እንደምታውቂው የገንዘብ እጥረት አለባት፡፡ ይህንን ነገር ለመሸፈን ከተሞች አንዳንድ ሁነቶችን ማዘጋጀት አለባቸው፡፡ የገንዘብ ሁኔታ እንዲጎለብት የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመፍጠርና ስምምነቶችን በማድረግ፣ ከእነዚያ የአውሮፓ ከተሞች ተሞክሮዎችን ይወስዳሉ፤ በገንዘብም ይደጎማሉ፡፡ የጎንደር የቬንሰን ታሪክም ይሄ ነው፡፡
ይህን ፕሮጀክት የጀመሩት እርስዎ ነዎት ይባላል?   
ትክክል ነው! ፕሮጀክቱን የጀመርኩት እኔ ነኝ፡፡ ፕሮጀክቱን ቢያንስ ለስድስትና ለሰባት ወር ብቻዬን ነው የሰራሁት፤ ማንም ሰው አያውቅም ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ነው በግልፅ ወደ ከንቲባ ጽ/ቤትና ወደ ከተማ አስተዳደሩ ያሸጋገርነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ጎንደር የቬንስን እህት ከተማ እንደመሆኗ፣ የእነሱም ከተማ ስለሆነች ይህን ራስ ግንብ ማደስ እንደሚፈልጉና የሙዚየም፣ የሀንድክራፍትና የቱሪዝም ልማነት እንዲሆን ገንዘቡን አቀረቡ፡፡ የግንቡ ፕሮጀክት አራት ምዕራፍ ነው ያለው፡፡
አንዱ ሙዚየም ልማት ነው፡፡ ሁለተኛው የሀንድክራፍት ልማት ሲሆን ሶስተኛው ቱሪዝም ልማት ነው፡፡ አራተኛው ደግሞ ግንቡን መጠገን ነው፡፡ አሁን የተሰራው የፕሮጀክቱ አራተኛ መዕራፍ ነው፡፡ የግንቡ ጥገና አልቆ ዛሬ ሊመረቅ እስፍራው ተገኝተናል፡፡
ይህ ግንብ ሲጠገን፣ የዩኔስኮ ንብረት የዓለም ህዝብ ንብረት በመሆኑ፣ ሶስት ነገሮች መጠበቅ አለባቸው፡፡
አንደኛው ኦተንትሲቲ (የዱሮ ይዞታውን የጠበቀ መሆን አለበት)፣ ይህ ማለት ለእድሳቱ የምንጠቀመው እንጨት፣ ድንጋይና ሌሎች ቁሳቁሶችም ጭምር የዱሮ መሆን አለባቸው ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው ድሮ ከነበረው ከባቢ ጋር ቅንጅት (integrity) ያለው መሆን አለበት።
ከኢትዮጵያ ኪነ-ህንፃ ሁኔታ ጋር የተስማማና የተቀናጀ መሆን አለበት፡፡ በሶስተኛ ደረጃ “ሲንክሮናይዜሽን” የሚባል ነገር አለ፡፡ ይሄ ማለት አዲስ እንጨት ለእድሳቱ ካስገባሽ አዲስ ለመሆኑ ምልክት ማስቀመጥ አለብሽ፡፡ እነዚህ ሶስት መሰረታዊ ጥንቃቄዎች ተሟልተው ሲታደሱ ቅርሱ የቀደመ ምንነቱን አያጣም፡፡ ይህ ራስ ግንብም በዚህ መሰረት ነው የታደሰው፡፡
እርስዎ ሃገርዎን እንደሚያስጎበኙት ውጭ አገራትን የመጎብኘት ዕድል ገጥመዎታል? እስቲ ስለሌሎች አገራት አስጎብኚዎች ይንገሩኝ…
ለጉብኝት የሄድኩባቸው የውጭ አገሮች ብዙ ላይሆኑ ይችላሉ፤ ነገር ግን በሌላም ስራ የሄድኩባቸው ብዙ ቦታዎች አሉ፡፡ ከአፍሪካ ብንጀምር ሱዳን፣ ኬንያ፣ ዚምባብዌ… ወደ አውሮፓ ስንመጣ ትምህርቴን አልጨረስኩም እንጂ የመጀመሪያ ስኮላርሺፕ ያገኘሁት ቡልጋሪያ ነበር። ምስራቅ አውሮፓን ብትወስጂ ሀንጋሪ፣ ራሺያ እና ሌሎችንም አውቃለሁ፡፡ ከምዕራብ አውሮፓ ፈረንሳይን አይቻለሁ፡፡ ሁለት ጊዜ የመሄድ እድል ገጥሞኛል፡፡ ህንድ ሄጃለሁ፡፡
እንግሊዝም እንዲሁ። የማስጎብኘት ሁኔታው እንደየአገሩ ይለያያል፡፡ በሄድኩባቸው ቦታዎች ሁሉ ጉብኝት አድርጌያለሁ፤ ለቬንሰንም ጉዳይ ፈረንሳይ ሄጃለሁ፣ በአስጎብኚም ጎብኝቻለሁ፡፡ አስጎብኚ ለመሆን የታሪክ ሰው መሆን ያስፈልጋል ብለው ያምናሉ?
የታሪክ ሰው መሆን ያን ያህል ላያስፈልግ ይችላል፡፡ ቢሆንም ግን ጥሩ ነው፡፡ ዋናው ልብ ልንል የሚገባው አስጎብኚ ሁሉም ነገር ማለት ነው፡፡ ቀደም ሲል እንዳልኩት አስጎብኚ ምንም ነገር “አላውቅም” ማለት የለበትም፡፡
ፖለቲከኛ፣ የባዮሎጂ ሰው፣ የጂኦሎጂ ሰው፣ አርኪዎሎጂስት፣ የታሪክ ሰው፣ …ሁሉንም መሆን አለበት፡፡
ዘርፈ-ብዙ እውቀት ያስፈልገዋል፡፡

የጥብቅና ሞያን በፈቃደኝነት ላይ በተመሰረተ የሲቪክ ማኅበር ማስተዳደር አይቻልም
የሌሎች አገራት የሕግ ባለሞያዎች ወይም የጠበቃ ማኅበራት የሚሰሩት እንዴት ነው?
የህግ ባለሙያ ድርጅቶች (ፈርሞች)  ስላላቸው ፋይዳ ያብራራሉ
በቅርቡ የአገር አቀፍ የፍትህ ዘርፍ የፍትህና መልካም አስተዳደር መድረክ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በተገኙበት ተካሂዶ ነበር፡፡
በመድረኩ ላይ በተለይ ከጠበቆች የሥነምግባር ችግሮች ጋር በተገናኘ በተነሱ ጉዳዮች ዙርያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ ከጠበቆች ማህበር ፕሬዚደንት አቶ ወንድምአገኘሁ ገብረስላሴ ጋር ሰፊ ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡


የአገር አቀፍ የፍትሕ ዘርፍ የፍትሕና መልካም አስተዳደር መድረክ ጉባዔ እንዴት ነበር?
 ጥሩ ነበር፡፡ በፍትሕ ሥርአቱ ላይ የሚታዩ በርካታ ችግሮች ተነስተዋል፡፡ መፍትሔም ሊሆኑ ይችላሉ የተባሉ ኃሳቦች ቀርበዋል፡፡ ችግሮቹንም ለማቃለል እቅድም ተዘጋጅቷል፡፡ የታሰቡት ነገሮች በሙሉ እንኳን ባይሆኑ በአብዛኛው ሥራ ላይ ከዋሉ መልካም መሻሻሎች ሊታዩ ይችላሉ ብዬ እገምታለሁ፡፡
 ከተነሱት ችግሮች አንዱ የሕግ ባለሞያዎች ወይም ጠበቆች በፍትሕ አሰጣጥ ረገድ መደገፍና መርዳት ሲገባቸው ፍትሕ እንዲጨናገፍ ያደርጋሉ፣ ጉቦ ያቀባብላሉ፣ ከጥብቅና ሥነምግባር ውጭ ይሰራሉ የሚል ነው፡፡ በዚህ ወቀሳ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው?
 በስብሰባው ላይ ከፍተኛ ትኩረት ተሰቶት ከነበረው መሰረተ ሃሳብ አንዱ ሁልጊዜ ውጫዊ ምክንያቶች ላይ ብቻ ከምናተኩር የራሳችንን የውስጣችንን ሁኔታ እንመርምርና ለችግሮቻችን መፍትሔ እንስጥ የሚል ነው፡፡ በዚህም ላይ ተመስርቶ በዳኝነት ሥርዓቱ ላይ የሚታዩ ችግሮች፣ በአቃቤ ሕግ መሥሪያ ቤት ላይ የሚታዩ ችግሮች፣ በፖሊስ እና በሌሎችም ተዛማጅነት ባላቸው ተቋማት ላይ የሚታዩ በጣም በርካታ ችግሮች ተነስተዋል። እንደውም ለጉባኤው የቀረበው ሪፖርት በዋናነት ያተኮረው ችግሮች ላይ ብቻ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ይህ እንግዲህ ቀደም ሲል ከሚታዩት ሪፖርቶች ጋር ሲነፃፀር በጣም የተለየ ነው፡፡ በአብዛኛው በየቤታችን የምናነሳቸው ችግሮች በሪፖርቱ ውስጥ ተካተዋል። ችግሮቹ በዚህ አይነት መልክ ተነቅሰው ከወጡ ደግሞ ፈቃደኝነትና ቅንነት ታክሎበት መፍትሔ ሊያገኙ ይችላሉ የሚል ተስፋ ይሰጣል። ከዚህ አኳያ ሲታይ የሕግ ባለሞያዎች በተለይም ደግሞ ጠበቆችን በተመለከተ የቀረበው ሪፖርት፣ በሌሎቹ የፍትሕ ሥርዓት አካላት ላይ ከሚታየው ችግር የተለየ እንዳልሆነ ማየት ይቻላል፡፡ ጉቦ ሰጭ አለጉቦ ተቀባይ አይኖርም፡፡ ፈረንጆቹ እንደሚሉት ታንጎ ለመደነስ ሁለት ደናሾች ያስፈልጋሉ፡፡ ስለዚህ ችግሩ በሁሉም ቤት ያለ ነው ማለት ነው፡፡ እኛም ብንሆን የምንሰማቸው ስሞታዎች አሉ፡፡ እንዲያውም ብዙ ጥሩ ችሎታና ሥነምግባር ያላቸው ጠበቆች፣ ከሚያዩትና ከሚሰሙት ችግር ለመሸሽ ከሥራው የመራቅ ሁኔታ ሁሉ ይታያል፡፡ ከዚህ በፊት ቅር ያሰኘን የነበረው ወቀሳ “ጠበቆች ሲባሉ በአብዛኛው ችግር አለባቸው” የሚል አንድምታ ያለው አገላለፅ ይቀርብ ስለነበር ነው፡፡ የችግሩም ምክንያቶች ጠበቆች ብቻ እንደሆኑ በሚመስል ሁኔታ ነበረ የሚገለጸው፡፡ በዚህኛው ጉባኤ ላይ ግን አጥፊዎች ቢኖሩም ብዙዎቹ ጠበቆች  የሞያ ስነምግባራቸውን አክብረው እንደሚሰሩ፣ እንደውም ከእነዚህ ጠበቆች ጋር በመሆን ችግሩን ተጋፍጠን እናስተካክለዋለን የሚል መንፈስ የተንፀባረቀበት በመሆኑ ከቀደሙት ጊዜያት በጣም የተሻለና የተለየ ነው፡፡ እኔም ከጠበቅሁት በላይ አስደስቶኛል፡፡
 ጥብቅና ሞያ እንደመሆኑ መጠን የሞያውን ስነምግባር ሳያከብሩ መገኘትን እንዴት ያዩታል?
 እውነት ነው፤ ጥብቅና በጣም ረጅም ዕድሜ ያለው ሞያ ነው፡፡ እንደውም እስከቅርብ ዘመን ድረስ እንደ ሞያ ይቆጠር የነበረው የሕግ ሞያና ሕክምና ነበር፡፡ እነዚህ ሞያዎች የእድሜያቸውን ርዝመት ያህል በጣም በርካታ የሞያ ደንብ፣ ስነምግባርና ዲሲፕሊን ያላቸው ናቸው፡፡ ሞያ እንዲባሉ ካበቃቸውም ነገር አንዱ የሞያ ሥነምግባርና ዲሲፕሊን ያላቸው መሆናቸውም ጭምር ነው፡፡ ከዚህ አኳያ ሲታይ አንዳንድ የሞያው አባላት ጉድለት ሲታይባቸው ማሳዘኑ አይቀርም፡፡ የስነምግባርና ዲስፕሊን ጉድለቶች በሞያው ክብርና ግርማ ሞገስ ላይ የራሳቸውን ጥላ ማጥላታቸው አይቀርም፡፡ ታዲያ በዚህ ሁኔታ ጉዳቱ አመዝኖ የሚታየው ችግሩን በፈጠሩት ሰዎች ላይ ሳይሆን በአጠቃላይ በሞያው እና ስርአት ጠብቀውና አክብረው በሚሰሩ ባለሞያዎች ላይ ነው፡፡ የዚህ አይነት ችግር እየተስፋፋ ሲሄድ፣ የሚጎዳው ችግር ፈጣሪውን ሳይሆን መልካም ስነምግባር ያለውን ባለሞያ፣ የፍትሕ ሥርዓቱንና አገርን በአጠቃላይ በመሆኑ አሳሳቢ ችግር መሆኑ አይካድም፡፡ እንደግለስብ እንዲሁም እንደ የሕግ ባለሞያዎች ማኅበር መሪነቴ በጣም ያሳስበኛል፡፡ ያሳዝነኛልም። ሆኖም ግን ሁላችንም ሰዎች በመሆናችን የተለያየ አስተሳሰብ፣ እምነትና አመለካከት ሊኖረን ይችላል። በዚህም የተነሳ ምንም ጊዜ ቢሆን ከመስመር ወጣ የሚሉ ሰዎች መኖራቸው አይቀርም፡፡ የሕግ ሞያ ከዚህ ሙሉ በሙሉ ንጹህ ይሆናል ብሎ መጠበቅም አይቻልም፡፡ አልፎ አልፎ ደግሞ ሆን ተብለው ሳይሆን በአጋጣሚ የሚፈጠሩ የሥነምግባር ጉድለቶችም ይኖራሉ፡፡ ዋናው ነገር ችግሮች ለምን ይፈጠራሉ ወይም መፈጠር አልነበረባቸውም ብሎ ማማረር ብቻ ሳይሆን ችግሮች እንዳይፈጠሩ የሚረዳ፣ ችግሮች በተለያየ ሁኔታ ከተፈጠሩም በኋላ አግባብ ባለው ሁኔታ የእርምት እርምጃ የሚወስድ ተቋማዊ ስርአት ማደራጀትና በአግባቡ እንዲሰራ ማድረግ ነው፡፡ ይህ የሆነ እንደሆነ የስነምግባርም ሆነ ሌሎች ችግሮች እንደሁኔታው አፋጣኝ፣ አግባብ ያለውና ፍትሐዊ የሆነ መፍትሄ ያገኛሉ፡፡ ይሄን እውን ለማድረግ መሥራት አለብን ብዬ አምናለሁ፡፡  
እስካሁን  ይህን ችግር ለማቃለል ወይም ለማስወገድ ምን የሠራችሁት ሥራ አለ?
 ጥሩ ጥያቄ ነው፡፡ ይህንን ጥያቄ ለመመለስ ግን ትንሽ የማኅበራችንን ባሕርይ ማየት የሚያስፈልግ ይመስለኛል፡፡ ምናልባት እንደምታውቀው፣ ማኅበራችን የተቋቋመው በ1957 ዓ.ም ሲሆን ሲቋቋም የነበረው ዓላማ የመረዳጃ ዕድር መልክ የያዘ ነበር፡፡ ቀስ በቀስ እና ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ  ዓላማውን በማሻሻል የጠበቆች ማኅበር ሲባል ቆይቶ አሁን ደግሞ የሕግ ባለሞያዎች ማኅበር ለመሆን በቅቷል፡፡ በ2002 ዓ.ም ተሻሽሎ የፀደቀው የማኅበሩ ዓላማዎች፣ የፍትሕ አስተዳደር በተቀላጠፈ ሁኔታ እንዲካሄድ መርዳት፣ የፍትሕ ስርአቱ እንዲሻሻል ማገዝ፣ የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን መርዳት፣ የሕግ ሳይንስ (jurisprudence) እንዲዳብር መርዳት፣ የሙያ ሥነምግባር ደረጃውን የጠበቀ እንዲሆን መጣር፣ አቅም ለሌላቸው ሰዎች ነፃ የሕግ አገልግሎት መስጠት፣የሕብረተሰቡ የሕግ ንቃተ ህሊና እንዲድግ መስራት፣ በአባላት መካከል መቀራረብና መተባበር እንዲዳብር ማድረግ የሚሉት ወዘተ.. ሲሆኑ፣ ማንኛውም የሕግ ባለሞያ የሆነ ሰው አባል መሆን ይችላል፡፡ ማለትም ማኅበሩ የፈቃደኝነት ማኅበር ነው፡፡ ጠበቃም፣ ዓቃቤ ሕግም፣ የሕግ ት/ቤት መምሕራን፣ በመንግሥት መሥሪያ ቤት ውስጥ የሚሰሩ የሕግ ባለሙያዎችም ወዘተ. አባላት ሊሆኑ ይችላሉ። የፈቃደኝነት ማኅበር በመሆኑም ሊሰራ የሚችለው አባላቱን በማስተባበርና መልካም ሥነምግባርን መከተል እንዳለባቸው፣ የሞያው ክብርና ሞገስ እንዲያድግ የድርሻቸውን እንዲወጡ በመምከርና በማሳሰብ ነው፡፡ ይህ ደግሞ የውይይትና የሥልጠና ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት፣ማሳሰቢያዎችን ከመስጠት ያለፈ አይደለም፡፡ የስነምግባር ጉድለት የሚፈጽሙ የሕግ ባለሞያዎችን ወይም አባላቱን የሚያርምምበት ወይም የዲሲፕሊን ቅጣት የሚጥልበት ኃይልና ስልጣን የለውም፡፡ በርግጥ አባላት በውሳኔያቸው ማኅበሩ ዲሲፕሊን እንዲቆጣጠርና ጥሰት በሚፈጽሙ አባላት ላይ የቅጣት ውሳኔ እንዲያሳልፉ መስማማት ይችላሉ። ይህ ግን ሊሆን የሚችለው በአባላቱ ላይ ብቻ ሲሆን አባላቱም ቢሆኑ በዚህ ውሳኔ እስካልተስማሙ ድረስ ማኅበሩን ለቀው መውጣት ይችላሉ፡፡ ስለዚህ ማኅበሩ የራሱ የሆነ ምንም አይነት አስገዳጅ ሥልጣንና ኃይል የለውም። ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ሊያደርግ የሚችለው አባላቱ በበጎ ፈቃዳቸው የሞያው ሥነምግባር ተገዢዎች እንዲሆኑ ማበረታትና መምከር ነው። ይህንን ደግሞ አቅም በፈቀደ መጠን በማድረግ ላይ እንገኛለን፡፡ ሲጠቃለል፣ የኛ ማኅበር በአባላት የተቋቋመ የሲቪክ ማኅበር ነው፡፡ ከዚህ የተለየ ሥራ መስራት አይቸልም፡፡  የሌሎች አገር የሕግ ባለሞያ ወይም የጠበቃ ማኅበራት ግን ሰፋ ያለ ኃይልና ሥልጣን አላቸው፡፡
 እንዴት ነው የሌሎች አገራት የሕግ ባለሞያዎች ወይም የጠበቃ ማኅበራት የሚሰሩት?
የሌሎች አገራትን በተመለከተ የተለያዩ ልምዶች መጥቀስ ይቻላል፡፡ መሰረታዊው ነጥብ ግን የጠበቆች ማኅበራት ሦስት ዋና ዋና ተግባራትን ያከናውናሉ፡፡ 1. ሞያውን የማስተዳደር፣ ማለትም ፈቃድ መስጠት፣ የዲሲፕሊን ደንቦችን የማስከበርና የማስፈጸም፣ የሕግ ትምሕርት የሚሰጥበትን ደረጃ መወሰን፣ ለጠበቆች ተከታታይ የሕግ ሞያ ስልጠና መስጠት፣ ከዳኝነት አካሉና ከሕግ አስፈፃሚው አካል ጋር የጥብቅና ሞያንና ሥራን በተመለከተ ተፈፃሚ በሚሆኑ ደንቦች፣ ሥነሥርአቶች፣ የሥነምግባር ደንቦች እና በመሳሰሉት ጉዳዮች ላይ በጋራ መሥራት እና የመሳሰሉትን ሥራዎች ማከናወን፤ 2. የሕዝብ አገልግሎት ሥራዎችን መስራት፣ ማለትም፣ ከፓርላማ ጋር በመተባበር የሚሰሩ ተግባራትን ለምሳሌ በሕግ ረቂቆች ላይ በሚደረግ ዝግጅት፣ ውይይት መሳተፍ፣ አስተያየቶችን አዘጋጅቶ ማቅረብ፣ ነፃ የሕግ አገልግሎት መስጠት፣ ለሕግ የበላይነትና የፍትሕ ሥርዓቱ እንዲጠናከር መስራት፣ 3. ሞያውን መወከል፣ ይህ የሞያ ማኅበር ወይም የዩኒየን ተግባራትን የሚመለከት ሲሆን፣ ሞያውን በመንግሥትና በተለያዩ ወገኖች ዘንድ መወከል፣ ከሌሎች የሞያና ሲቪክ ማኅበራት ጋር መስራት፣ ሕግን፣ የሞያ ስነምግባርን በጠበቀ መልኩ ለአባላት መብትና ጥቅም መቆምን ይጨምራል። በብዙ ሀገራት የሞያ ማኅበራቱ መጀመሪያ በፈቃደኝነት ላይ ተመስርተው ከተቋቋሙ በኋላ ቀስ በቀስ በሕግ የተቋቋሙበት ሁኔታ ነው ያለው፣ ለምሳሌ በአሜሪካ ማኅበራቱ ሦስቱንም ተግባራት ያከናውናሉ፡፡ እንደ እንግሊዝ ባሉ ሀገራት ደግሞ የሞያ ማኅበራቱ በረጅም ጊዜ እየዳበረ የመጣ በኮመን ሎው ላይ የተመሰረተ ሦስቱንም ሥራዎች የመሥራት ሥልጣን አላቸው፡፡ የእንግሊዞቹ እንደውም ከአራት መቶና እና አምስት መቶ አመት በላይ እድሜ ያላቸው ናቸው፡፡ በፈረንሳይ ደግሞ አደረጃጀታቸው ከፍርድ ቤቶች ጋር የተያያዘ ሲሆን ሞያውን የማስተዳደር፣ ፈቃድ የመስጠት፣ የዲሲፕሊን አርምጃ የመውሰድና የሕዝብ አገልግሎት ሥራዎችን የመሥራት ስልጣን አላቸው፡፡ በህንድም የዚሁ አይነት አሰራር ነው ያለው፡፡ የብራዚል የጠበቆች ማኅበር ከ750,000 በላይ አባላት ያሉት ሲሆን የጥብቅና ሞያውን የማስተዳደር፣ ሞያውን የመወክል እና የሕዝብ አገልግሎት ተግባራትን ያከናውናል። እዚሁ አቅራቢያችን የሚገኙት የኬንያ፣ የኡጋንዳ፣ የታንዛንያ የጠበቆች ማኅበራትም በሕግ እንዲቋቋሙ ተደርገው ሞያውን በተለያየ ደረጃ የማስተዳደር፣ የመወከል እና የሕዝብ አገልግሎት ተግባራትን ያከናውናሉ፡፡ በነዚህ ማኅበራት ውስጥ አባል መሆን ግዴታ ነው፡፡ በአንዳንዶቹ ሀገራት ቀድሞ ነገር በማኅበራቱ መመዘኛ መሰረት ትምሕርት ወስዶ፣ ፈተናውን አልፎ ጠበቃ መሆን ይችላል ያልተባለ ባለሞያ፣ በማናቸውም ፍርድ ቤት ቆሞ ሊከራከር አይችልም። ስለዚህ ፈቃዱን ካገኘ በኋላም የስነምግባር ጉድለት ፈጽሞ ቢገኝ የሚቀጣው በማኅበሩ ነው፡፡ ቅጣቱም የጥብቅና ፈቃድ እስከመሰረዝ ሊደርስ ይችላል፡፡ ስለዚህ የጠበቆች ማኅበራቱ በቂ አቅምና ኃይል አላቸው፡፡ አባላቶቻቸውን ያስተምራሉ፣ ይመክራሉ፣ ይገስፃሉ፣ ይቀጣሉ፡፡  በነዚህ ደረጃዎች የማይታረም አባል ከማኅበሩ ይባረራል፤ የጥብቅና ሥራ እንዳይሰራ ይደረጋል፡፡  
ወደኛ አገር ስንመለስ ታዲያ ማኅበሮቻችን በጣም የተወሰነ ተግባር ያላቸው ሲሆኑ ሞያውን የማስተዳደር ምንም አይነት ሥልጣን ስለሌላቸው፣ የስነምግባር ጥሰቶችን የመከታተልና የማረም ሥራዎችን አይሰሩም፡፡ የዚህ አይነት አቅም የሌላቸው ማኅበራት ከኛ ሌላ በሌሎች ሀገሮች ለመኖራቸው ብዙም መረጃ የለኝም፡፡ ቢኖሩም ደግሞ መኮረጅም ካለብን የተሻለ አሰራርና ጥቅም የሚሰጡትን ልምዶች ከሀገራችን ሁኔታና ፍላጎት ጋር አጣጥመን መሆን ይኖርበታል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ስለዚህ ለሀገራችን የጥብቅና ሞያ አስተዳደር በርካታ መሻሻሎች ያስፈልጉታል፡፡
የአባላት የስነምግባር ጉዳይ አይመለከተንም እያሉ ነው?
አይመለከተንም ሳይሆን፣ ሥልጣን በሕግ የተሰጠው የጠበቆች ማኅበር ስለሌለ፣ የማኅበሮቻችን አባልነት በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ስለሆነ፣ በዚህም ምክንያት ብዙ አባላት በማናቸውም ማኅበር ውስጥ አባል ስላልሆኑ፣ አባል የሆኑትም በማናቸውም ጊዜ ለቀው መውጣት ስለሚችሉና ይህ ከማኅበር የመውጣት እርምጃቸውም የጥብቅና ፈቃዳቸውን ስለማይነካ፣ ማለትም ከማኅበሩ ወጥተውም የጥብቅና ሥራቸውን መቀጠል ስለሚችሉ አስገዳጅ የሆነ ስነምግባር የማስከበር ሥራ መሥራት እንችልም ለማለት ነው እንጂ አያገባንም ለማለት አይደለም። ስለሚያገባንማ የሲቪክ ማኅበር ብንሆንም በየጊዜው በስነምግባር ሕጉና በተያያዙ መልካም የስነምግባር ደንቦች ስልጠና እንሰጣለን፣ ውይይቶች እናዘጋጃለን፡፡ ባለፈው አመት ለምሳሌ ከጠበቆች ሥነምግባር ጋር በተያያዘ ሁለትፕሮግራሞች አዘጋጅተን የነበረ ሲሆን በዚህ አመት በእቅዳችን ውስጥ የተያዙ ሁለት ስልጠናዎች አሉ፡፡ ዋናው ለማለት የፈለግሁት ምንድነው፣ የጥብቅና ሞያን በፈቃደኝነት ላይ በተመሰረተ የሲቪክ ማኅበር ማስተዳደር አይቻልም፡፡ ቋሚ የሆነ ዘለቄታ ያለው አደረጃጀት ወይም ተቋም ያስፈልገዋል፡፡  
 የጠበቆች ማኅበር አለ አይደለ?
 የጠበቆች ማኅበር አለ፡፡ ሆኖም ግን በጠበቆች ማኅበርም ዘንድ ያለው ችግር እላይ ከገለጽኩት የተለየ አይደለም፡፡ የጠበቆች ማኅበርም ቢሆን የፈቃደኝነት ማኅበር ነው፡፡ በርግጥ የጠበቆች ማኅበር በፍትሕ ሚኒስቴር ውስጥ ባለው የጠበቆች የዲሲፕሊን ኮሚቴ አባል ቢሆንም በአጠቃላይ የጠበቆችን ስነምግባር በተመለከተ እንደ አባል ኮሚቴው ውስጥ ከመሳተፍ በቀር የማስፈጸም ኃይሉ የሕግ ባለሞያዎች ማኅበር ካለበት ችግር የተለየ አይመስለኝም፡፡  
በዚህ ችግር ዙርያ መፍትሔ ለማምጣት ለምን በትብብር አትሰሩም?
 በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ ሃሳብ እየተለዋወጥን ነው፡፡ በሁለቱም ማኅበራት አመራር በኩል በጋራ ተረዳድቶ መሥራት ጥቅም እንዳለው መተማመን ላይ ተደርሷል፡፡ አብረን እንዳንሰራም የሚያግደን ነገርም የለም፡፡ ለወደፊቱ በጋራ የምንሰራቸው በርካታ ነገሮች ስላሉ እየተመካከርን ውጤት ያለው ሥራ ልንሰራ እንደምችል አምናለሁኝ፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ በሰፊው መነጋገር እንችላለን፡፡  
ዘላቂ መፍትሔው ምንድነው ይላሉ?
 እንደኔ እንደኔ፣ መፍትሔው በሕግ የተቋቋመ ሞያውን ማስተዳደር የሚችል፣ ሁሉም ጠበቃ በየደረጃው የግዴታ አባል የሚሆንበት የጠበቆች ማኅበር ማቋቋም ቢቻል አብዛኛው ችግር የሚቀረፍ ይመስለኛል፡፡ ምናልባት እንዳደጉት ሀገሮች ሁሉንም ሥልጣን ማኅበሩ እንዲኖረው ማድረግ አይቻል ይሆናል ግን በተወሰነ ደረጃ ሞያውን የማስተዳደር ሥልጣን የግድ ማኅበራት ያስፈልጋቸዋል፡፡ ማኅበራት ያልኩበት ምክንያት በፌደራል፣ በክልል እና በአዲስ አበባ እንዲሁም በሌሎች ፌደራል ከተሞች ደረጃ ሞያውን በተወሰነም ደረጃ ቢሆን ማስተዳደር የሚችሉ፣ በየደረጃው ሞያውን የሚወክሉ፣የሕዝብ አገልግሎት የሚያከናውኑ ማኅበራት ስለሚያስፈልጉ ነው፡፡ በየደረጃው ካልሆነ አሁንም በአባላትና በማኅበሩ መካከል መራራቅ፣ ማለትም የቦታም፣ በፌደራል ስትራክቸሩ መሰረት  የአሰራርም፣ የግንኙነትም ወይም የእንቅስቃሴና የተሳትፎ ወዘተ…ይጨምራል፣ ዞሮ ዞሮ ውጤታማ የሆነ ክትትልና አርምት ማድረግ አይቻልም፡፡ በአጠቃላይ ግን ቅርጹን የማጥናትና የአሰራር ደረጃውን በጥሩ ጥናት ላይ ተመስርቶ መምረጡ እንደተጠበቀ ሆኖ ይህ መንገድ ይሰራል ብዬ የማምንበት ምክንያት በሌሎች ሀገሮች ተሞክሮ ውጤት ያመጣ እንዲያውም በአብዛኛው ሀገራት የሚሰራበት በመሆኑ ሲሆን ሌላው ደግሞ ጠበቃው በሥራ አጋጣሚ ስለሚገናኝ፣ ስለሚተዋወቅ፣ በቅርብ አብሮ ስለሚኖር ሞያውንና ሥነምግባሩን በቅርብ መነጋገር መወያየት፣ ማረም አስፈላጊም ሲሆን በማኅበሩ በኩል እርምጃ መውሰድ ስለሚችል፣ በሌላ በኩል ደግሞ የሞያው ስነምግባር መሻሻልና ተፈፃሚ ሲሆን ክብርና ሞገስ የሚሰጠው ለሞያውና ለባለሞያው ስለሆነና ይህ ደግሞ በቀጥታ የባለሞያው ዋና ጥቅም በመሆኑ ለውጥ ያመጣል ብዬ አምናለሁ፡፡ ማኅበራቱን ከበላይ ሆኖ የሚያስተባብር ደግሞ ባር ካውንስል ማቋቋም ይቻላል፡፡ ይህ በብዙ አገራት የሚሰራበት ነው። ይህ ከሆነ በኋላ አሁን ያሉት ማኅበራት አባላቱ እስከፈለጉ ድረስ ሲቪክ ማኅበራት ሆነው መቀጠል የማይችሉበት ምክንያት አይኖርም፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የጠበቆች ድርጅት ወይም የጠበቆች ፈርም ቢቋቋም፣ በጥብቅና ሞያው ጥራትና ደረጃ እንዲሁም በሥንምግባር ጥበቃ በኩል ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል ብዬ አምናለሁ፡፡
የጠበቆች ድርጅት ሲሉ ምን ማለትዎ ነው? ያሏቸውን ጥቅሞችስ ሊያመጣ የሚችለው እንዴት ነው? ትንሽ ቢያብራሩልን?
 በኛ አገር ጠበቆች የጥብቅና አገልግሎታቸውን የሚሰጡት በተናጠል ወይም በግል ነው፡፡ ጠበቆች እንደ ሥራ አንድ ላይ ተሰባስበው ሞያዊ አገልግሎት የሚሰጡበት ሁኔታ የለም፡፡ እንደሚታወቀው ሕግ ደግሞ በጣም ሰፊ ዘርፎች አሉት፡፡ ሕግ የማይነካው ምንም አይነት ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት የለም፡፡ ያለማጋነን ማናቸውም እንቅስቃሴ በሕግ የሚገዛ ነው፡፡ ስለዚህም የንግድ ሕግ፣ የኮንስትራክሽን፣ የትራንስፖርት፣ የተፈጥሮ ሀብት፣ የአካባቢ ጥበቃ፣ የቤተሰብ፣ የአሰሪና ሰራተኛ፣ የወንጀል፣ የባሕር፣ የውጭ ንግድ፣የመሬት፣የባንክ፣የኢንሹራንስ፣የታክስ፣የኢንቨስትመንት ወዘተ… እያለ ማናቸውንም እንቅስቃሴ የሚመሩ ሕጎች አሉ፡፡ በዚህ ሁሉ የሕግ ዘርፍ ደግሞ አንድ የሕግ ባለሞያ በቂ አውቀትና ልምድ ኖሮት የተሟላ አገልግሎት ለመስጠት ይቸገራል፡፡ በአንፃሩ ደግሞ በተለያየ የሕግ ዘርፍ ከፍ ያለ አውቀትና ልምድ ያላቸው ሰዎች ተሰባሰበው መሥራት ቢችሉ፣ በተሰባሰቡት ባለሞያዎች መካከል የሥራ ክፍፍል ይደረጋል፡፡ እያንዳንዱ ባለሞያ የተሻለ አውቀትና ልምድ ባለው መስክ የሚመጡ ሥራዎችን ይሰራል፣ በየዲፓርትመንት ይደራጃል፤ሥራውን ያከናውናል። ባለሞያዎቹ ባጋጠሙዋቸው የሕግ ጥያቄዎች ላይ ይመካከራሉ፤ ኃሳብ ይለዋወጣሉ፣ የተነሳውን የሕግ ጥያቄ እንዴት አድርገው መፍታት እንዳለባቸው መክረው ዘክረው ይወስናሉ፡፡ ይህ እንግዲህ ጥራት ያለው ሥራ እንዲሰሩ ይረዳቸዋል፡፡ ባለሞያዎቹም በሙሉ ልብ ሥራቸውን ያከናውናሉ፤ ተገልጋዩም ከፍተኛ ደረጃና ጥራት ያለው ምክር ያገኛል፣ ፍርድ ቤትም ሲወከል በደንብ በተዘጋጀ አቤቱታና ክርክር ይወከላል፡፡ ይህ በራሱ አንድ ትልቅ ችግር ይቀርፋል፡፡ ባለሞያዎች በስራ ብዛትና መደራረብ ብዙም በማያውቁት የሕግ መስክ እንዳይዳክሩ በማድረጉ ቅልጥፍናና ጥራት ያመጣላቸዋል። ከዚህ ጋር ተያይዞ ከሚፈጠር የሥነምግባር ጉድለትም ይጠብቃቸዋል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ባለሞያዎቹ በቡድን  መልክ ስለሚሰሩ የእውቀትና የልምድ ጉድለትን እያሟሉ እንደሚሄዱ ሁሉ፣ የሚታዩ የሥነምግባር ጉድለት አዝማሚያዎችንም እያረሟቸው ይጓዛሉ፡፡ በሦስተኛ ደረጃ ደግሞ ፈርሙ ወይም የባለሞያዎቹ ድርጅት የተሻለ ሥራ ማግኘት የሚችለው በሥራው ደረጃና ጥራት እንዲሁም በሥነምግባር ጥንካሬው ስለሚሆን ለራሱ ለድርጅቱ ወይም ለፈርሙ ሕልውና ሲል የሥነምግባር ጉድለቶችን እንዲያርም ይገደዳል። በዚህም ጠበቆች የተሻለ አገልግሎት የሚሰጡ፣ ከፍተኛ የሥነምግባር ብቃት ያላቸው እንዲሆኑ ይረዳል፡፡
ስለዚህ በአገራችን የጠበቆች ድርጅቶች ወይም ፈርሞች እንዲቋቋሙ የሚያስችል ሕግ ቢወጣ ቀደም ብዬ እንደጠቀሱት በርካታ ችግሮችን በመፍታት ለፍትሕ ሥርአቱ መጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል የሚል እምነት አለኝ፡፡
 እስከዛሬ በዚህ ረገድ ምንም ሥራ አልተሰራም ማለት ነው?
ምንም አልተሰራም ማለት አይቻልም። ከጥቂት አመታት በፊት ፍትሕ ሚኒስቴር በጠበቆች ድርጅት ላይ ረቂቅ አዘጋጅቶ በሰፊው እንድንወያይበት አድርጎ ነበር፡፡ እኛም ይጠቅማሉ ያልናቸውን አስተያየቶች ሰጥተናል፡፡ ይህ ከሆነ አንድ ሁለት አመት የሆነው መሰለኝ፡፡ ከዚያ ወዲህ ረቂቁ ምን ላይ እንደደረሰ አልፎ አልፎ ስንጠይቅ ማስተካከያዎች እየተደረጉበት እንደሆነ ተነግሮናል። በቀደም በተካሄደው የሀገር አቀፍ የፍትሕ ዘርፍ የፍትሕና መልካም አስተዳደር መድረክ ላይም በጉዳዩ ላይ አስተያየት የሰጡ ከፍተኛ የፍትሕ ሚኒስቴር ኃላፊ፣ ሥራው እየተጠናቀቀ መሆኑን እና ብዙዎቹ ያነሳናቸው ነጥቦች በተሻሻለው ረቂቅ ውስጥ የተካተቱ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ እኛም በተሰጠው አስተያየት ከፍተኛ ተስፋ አድሮብናል፡፡  
እዚህ ላይ አንድ መጨመር የምፈልገው ነገር የጠበቆች ጅርጅት ወይም ፈርም መቋቋም ቀደም ሲል ከገለጽኩት በተጨማሪ በቀጥታ ከውጭ በሚመጣው ኢንቨስትመንት ወይም direct foreign  investment ላይም ከፍተኛ ተጽእኖ አለው፡፡ ወደ ሀገራችን የሚመጡት ኢንቨስተሮች በብዙ መልኩ የሕግ ባለሞያዎች በሚሰጡዋቸው ምክር ላይ እምነት በመጣል ውሳኔዎችን ይሰጣሉ። በአብዛኛው የዓለም ሀገራትም ለሕግ አማካሪህ፣ ለሀኪምህና ለንስሃ አባትህ የሚደበቅ ነገር የለም የሚባለው መርህ በከፍተኛ ደረጃ የሰረፀ በመሆኑ የኢንቨስትመንት ውሳኔያቸው በሚያገኙት የሕግ ምክር ላይ በከፍተኛ ደረጃ የተመሰረተ ነው። ጉዳያቸው ወደ ፍርድ ቤት ሲሄድም በሙሉ እምነት ጉዳያቸው ተገቢውን ትኩረት ተሰጥቶት ክርክሩ እንዲቀርብ እና ክትትልም እንዲደረግበት ለሚያምኑት ባለሞያ መስጠት ይፈልጋሉ፡፡ በማናቸውም ሁኔታ የሰጡት እምነት እንዳይፋለስ እንዳይደናቀፍ ይፈልጋሉ፡፡ ያ ባለሞያ ግን አንድ ብቻ ሆኖ የሚሰራ በመሆኑ ደስተኞች አይደሉም። የሕግ አማካሪያቸው ወይም ጠበቃቸው አንድና  ብቻውን የሚሰራ መሆኑ ስጋታቸውን በጣም ከፍ ያደርገዋል፡፡ የሕግ ባለሞያው ወይም ጠበቃው አንድ ችግር አጋጥሞት ፍርድ ቤት መቅረብ ባይችልስ? ቢታመምሰ? ቢሞትስ? ወዘተ. ማነው ጉዳዩን የሚከታተለው? ፋይሎቹ የት ይገኛሉ? ማነው ጉዳዩን በቀላሉ ተክቶት መሥራት የሚችለው? በነዚህና በበርካታ ጥያቄዎች ምክንያት ጉዳያቸው እንዳይበላሽ በጣም ይፈራሉ፡፡ ለዚህም ወደኛ ሀገር ኢንቨስት ለማድረግ ሲመጡ ሀገራችን ለኢንቨስትመንት ምቹ ነች ወይ? ብለው ከግምት ከሚያስገቧቸው መመዘኛዎች አንዱ ብቃት ያላቸው የሕግ ባለሞያዎች አሉ ወይ? የሕግ ድርጅቶች ወይም ፈርሞች አሉዋቸው ወይ? የሚለው ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ ከውጭ የሚመጡት ባለሀብቶች በዚህ ረገድ ደስተኞች አይደሉም፡፡ በተለይ ከፍተኛ ሥራ ሊሰሩ የሚችሉት ትላልቅ ድርጅቶች ብዙውን ጊዜ የሕግ ባለሞያ ድርጅቶች ወይም ፈርሞች ባለመኖራቸው ወደ ሀገራችን መጥተው በተለያዩ የሥራ መሥኮች መሰማራት ቢፈልጉም ይህ ጉድለት ያሳስባቸዋል፡፡
ሌላው ከዚህ ጋር መታየት ያለበት ሀገራችን ወደ ዓለም የንግድ ድርጅት ወይም WTO ለመግባት ድርድር ላይ መሆኗ ይታወቃል፡፡ የሕግ ሞያ በዚህ ረገድ ብዙ ዝግጅትና ሥራ የሚጠብቀው ይመስለኛል፡፡ ተወዳዳሪ ለመሆን ጠንካራ የጠበቆች ማኅበር ወይም ማኅበራት ያስፈልጉናል እንዲሁም የሕግ ባለሞያዎች ድርጅቶች ወይም የጠበቃ ፈርሞች ያስፈልጉናል፡፡ የነዚህ ተቋማት ያለመኖር ተወዳዳሪነታችንን መፈታተኑ አይቀርም። የሀገራችንን እና የሀገር ውስጥ ሥራዎችን እና ድርጅቶችን ጥቅምም በአግባቡ ለማስጠበቅ እንዲሁም ከውጭ የሚመጡ ድርጅቶች በተገቢው መንገድ ለመርዳትና ሀገራችንን ጠቅመው እነሱም እንዲጠቀሙ ለማስቻል የነዚህ ተቋማት በአግባቡ መደራጀት እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡
 ለመሆኑ ሞያውን የማስተዳደር ሥልጣን በሕግ ቢሰጥ ወይም ማኅበሩ በሕግ ቢቋቋም፣ሥራውን ለመስራት አቅሙ አለን ብላችሁ ታስባላችሁ?
 ሃ!ሃ! ይህ ብዙ ጊዜ የሚነሳ ጥያቄ ነው፡፡ እና በዚህ ጉዳይ ላይ ሳንነጋገር ብናልፈው ኖሮ ይቆጨኝ ነበር፡፡ በእኔ እምነት ችግር አይፈጠርም ባይ ነኝ። ቀድሞ ነገር አቅሙን የሚሰጠን እኮ ሕግ ነው። ሕጉ ሞያውን በማስተዳደር በኩል ማኅበራቱ ሊኖራቸው የሚገባውን ደረጃ ይወስናል፣ ሕጉ ማናቸውም ጠበቃ የጠበቆች ማኅበር አባል የመሆን ግዴታ አለበት የሚል ከሆነ፣ የጠበቆች ማኅበር የአባላቱን ሥነምግባርና የተከታታይ ሥልጠና እንዲወስዱ ፕሮግራም አዘጋጅቶ ያስፈጽማል የሚል ከሆነ፣ ጠበቆች በሕዝብ አገልግሎት ተግባር እንዲሳተፉ ፕሮግራም አውጥቶ ያስፈጽማል የሚል ከሆነና ሌሎችም ዝርዝር ጉዳዮችን የያዘ ሕግ ከወጣ  ማኅበሩ ወይም ማኅበራቱ ያንን ማስፈጸም የማይችሉበት ምንም ምክንያት አይኖርም፡፡ ማኅበሩ ወይም ማኅበራቱ እኮ ራሳቸውን የቻሉ ጽ/ቤቶችና ሰራተኞች ይኖሯቸዋል፡፡ ከባለሞያዎቹ ውስጥ ደግሞ ጥሩ ጥሩ ችሎታ ያሉዋቸው አባላት ለማኅበራቱ መሪነት ይመረጣሉ፡፡ የተለያዩ ኮሚቴዎች ይኖራሉ፣ አባላትም የአባልነት መዋጮዋቸውን በአግባቡ እንዲያዋጡ ስለሚደረግ የአባልነት መዋጮን መክፈል ግዴታም ስለሚሆን ሥራዎቹን ለማከናወን አስቸጋሪ አይመስለኝም፡፡ በዚያ ላይ ደግሞ መታወቅ ያለበት የሕግ ባለሞያዎች እኮ በተለይ በጥብቅና የተሰማሩት ከፍተኛ ትምሕርት ያላቸው፣ በተለያያ ደረጃ አገራቸውን በመንግሥት ሥራ ያገለገሉ፣ በግል ድርጅቶች የሰሩ፣ ከፍተኛ የአስተዳደርና የሥራ መሪነት ልምድ ጭምር ያካበቱ ናቸው፡፡ ስለዚህ እድሉ ከተፈጠረ ሞያቸውን ማገልገልና ወደ ተሻለ ደረጃ ማሸጋገር ያቅታቸዋል ብዬ አላምንም፡፡   
  ሌላ የሚያክሉት ነገር አለ?
 የተጠናከረ ተደራሽ፣ ብቁ፣ ነፃና ፍትሕን ማስፈን የሚችል የዳኝነት ሥርአት ለአንድ ሀገር ሰላምም ሆነ እድገት አጅግ አስፈላጊ ነው። ዳኝነት በአጠቃላይ የአንድ አገር ሕዝብ መብት፣ ሀብት፣ ሕይወት የሚጠበቅበት ሥርአት በመሆኑ አስፈላጊነቱን አበክሮ ለመግለጽ በቂ ቃል አይኖርም፡፡ እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ስለዚህ ዳኝነት እንዲጠናከርና በብቃት የሚሰራበት ሁኔታ እየተሻሻለ መሄዱ አስፈላጊ ነው፡፡  የዳኝነት ሥርዓቱ መጠናከር ሥንል፣ የዚህ ሥርዓት አንዱ አካል የሆነው የጠበቆች አገልግሎት፣ ነፃ የሆነና ብቃት ያለው፣ ሥነምግባር የጠበቀ የተሟላ አገልግሎት መስጠት መቻል አብሮ የሚታሰብ ነው፡፡ ምክንያቱም የፍትሕ ሥራ የሚሰራው በፍትሐብሄር ጉዳይ ሲሆን በዳኞችና በጠበቆች ነው፡፡ በወንጀል ፍትሕ ደግሞ በዳኞች፣ በተከላካይ ጠበቆች እና በአቃቤ ሕጎች ነው፡፡ ከነዚህ ውስጥ የአንዱ ወገን መጉደል ወይም መዳከም የፍትሕ ሥርአቱን በእጅጉ ይጎዳዋል፡፡ በተጨማሪም የሕግ ባለሞያዎች ከፍርድ ቤት ውጭም በበርካታ መስኮች ኢንቨስትመንትን ጨምሮ ሰፊ የሥራ ድርሻ አላቸው፡፡ ስለዚህ እነዚህ መሰረታዊ የፍትሕ ሥርአቱ አካላት እየተሻሻሉና እየተጠናከሩ መሄዳቸው ለሀገራችን ሰላም፣ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ፣ እድገትም ሆነ ልማት መሰረታዊ ሚና ያላቸው በመሆኑ፣ አሁን በተያዘው መልኩ ትኩረት ተሰጥቶት መቀጠሉና የሚጠበቅበትን አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ማድረግ ቀጠሮ የሚሰጠው ጉዳይ አይደለም የሚል እምነት አለኝ፡፡

“የሙስና አዋጁ እንደገና ሊፈተሽና ሊታይ ይገባዋል”
የአንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ ዋና ፀሃፊ የነበሩትና በአዲሱ ካቢኔ ውስጥ ሳይካተቱ የማዕከላዊ ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ አስራት ጣሴ፤ በቅርቡ አዲስ ጉዳይ መፅሄት ላይ ባሰፈሩት ፅሁፍ “ፍ/ቤትን ደፍረዋል” በሚል ተከሰው ያለዋስትና መብት በ5ኛ ፖሊስ ጣቢያ ጊዜያዊ ማረፊያ ቤት እና በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ለአስር ቀናት ከታሰሩ በኋላ ባለፈው ሰኞ ተሲያት ላይ ተለቀዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ በክሱ ዙርያ፣ በዋስትና መብትና በእስር ቆይታቸው ዙርያ ተከታዩን አጭር ቃለመጠይቅ አድርጎላቸዋል፡፡

የቀረበብዎትን ክስ እስቲ ያብራሩልን ?
ክስ የቀረበብኝ በፍትሃ ብሄር ወንጀል አንቀፅ 480 ነው፡፡ ይህ ደግሞ አንድ ሰው በችሎት ላይ ታዳሚ ሆኖ፣ በጠበቃነት ወይም በከሳሽና በተከሳሽነት ቀርቦ ያልተገባ ድርጊት ሲፈፅም የሚከሰስበት አንቀፅ  ነው፡፡ እኔም መጀመሪያ በዚህ አንቀፅ ነበር ክስ የቀረበብኝ፤ በኋላ ላይ ግን ወደ ወንጀል ዞሮ ተፈረደብኝ-  በአንቀፅ 449 ተራ ቁጥር 2(ለ)፡፡ በዚህ የወንጀል አንቀፅ… የተከሰሰ ግለሰብ ከፍተኛ ቅጣቱ የ6 ወር እስራት ነው፡፡ የፍርድ ማቅለያ አቅርብ ተባልኩ፤ ነገር ግን የለኝም አልኩ።  ምክንያቱም ጠበቃዬ አቶ ተማም አባ ቡልጉ መጀመሪያ በተከሰስኩበት አንቀፅ ነበር ክርክሩን ያቀረቡት፤ ነገር ግን ባልተከሰስኩበት አንቀፅ የ5 ወር እስር በ2 ዓመት ገደብ  ተፈርዶብኛል፡፡ ሁለት ዓመት ለኔ በጣም ረጅም ጊዜ ነው፡፡ ይሄን ነገር ፖለቲካዊ መነሾ (ፖለቲካሊ ሞቲቬትድ) እንዳለው አድርጌ ነው ማየት የምፈልገው፡፡ የ2007 ምርጫ ቀርቧል፤ በምርጫ ቅስቀሳው ላይ ንቁ ሆኜ መሳተፍ አለብኝ፤ በገዥው ፓርቲ እና መንግስት ላይ እንዲሁም በፍትህ ስርዓቱ ላይ አስተያየት መስጠት ይጠበቅብኛል፡፡ እነዚሀ ሁሉ ጉዳዮች መደረግ ባለባቸው ጊዜ ነው ይሄን እንደ ማስፈራሪያና ማሸማቀቂያ ለመጠቀም የተፈለገው። ለእኔ ብቻ ሳይሆን ለሃገሪቱ የፖለቲካ ስርዓት መሻሻል ለቆመው ተቃዋሚ ሁሉ መልእክቱ ጥሩ አይደለም ብዬ ነው የማስበው፡፡ ነገር ግን በተወሰነው ፍርድ ላይ ይግባኝ እንጠይቃለን፡፡
ወደ ማረፊያ ቤት ሲላኩ ለምን የዋስ መብት አልጠየቁም?
እንዳጋጣሚ ጠዋት ጠበቃ ይዤ ነው የቆምኩት፡፡ ፍ/ቤቱ ለከሰዓት ቀጠረን፡፡ ጠበቃዬ ሌላ ጉዳይ ስለነበራቸው፣ በእርግጠኝነት ክሱ የቀረበበት አንቀፅ ቢበዛ የሚያስቀጣው ገንዘብ ቢሆን ነው ብለውኝ ሄዱ፡፡ የኔ ፅሁፍ “ሽብርተኝነት የህወኀት ኢህአዴግ ስጋት” የሚል ሲሆን የፀረ-ሽብር ህጉን ነው በስፋት የሚተነትነው፡፡ “አኬልዳማ” እና “ጀሃዳዊ ሃረካት” የተሰኙት ዶክመንተሪ ፊልሞች በፅሁፉ የተነሱት እንደ ምሳሌ ነው፡፡ ይሄም በየጊዜው በኢሬቴድ እየተዘጋጀ የሚተላለፈው ሰውን ለማሸማቀቅ፣ ለመብቱ የሚቆመውን ሁሉ በሽብርተኝነት ለመፈረጅ ነው፤ በዚህም ደግሞ ፍትህ አልተገኘም በሚል የፍትህ ስርአቱን የሚተች ነው እንጂ በተለየ መልኩ ችሎቱን የሚዘልፍ አይደለም” የሚል መከራከሪያ የህገ-መንግስቱን አንቀፅ 29 (ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትን የሚደነግገውን) በመጥቀስ ጭምር ጠበቃዬ ከተከራከረ በኋላ ግፋ ቢል ቅጣቱ የገንዘብ ነው፤ የእስራት ቅጣት የለውም ብሎኝ ነበር፡፡ ከሰዓት በኋላ ግን ፍ/ቤቱ “ጥፋተኛ ሆነው ስላገኘንዎት በቀጥታ ፖሊስ ወደ ማረፊያ ክፍል እንዲወስድዎ” የሚል ትዕዛዝ አስተላለፈ። በዚያ መሃል የዋስትና መብቴን በተመለከተ ፍ/ቤቱ ይጠይቀኛል ብዬ ነበር የጠበቅሁት፤ ዝም ሲለኝ ግን መጠየቅ የማልችል መሰለኝና እኔም ዝም አልኩ፡፡ በዚህ ምክንያት ቃል በቃል የዋስትና መብቴ ይጠበቅ የሚል ጥያቄ አላነሳሁም፤ ነገር ግን ፍ/ቤቱ “በዚህን ያህል ዋስትና ተለቀዋል፤ በውጭ ሆነው ይከራከሩ” የሚል ትዕዛዝ ማስተላለፍ ይችል ነበር፡፡ ከትእዛዙ በኋላም ወደ አምስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ተወስጄ ከአርብ እስከ ሰኞ ያሉትን ቀናት እዚያ ካሳለፍኩ በኋላ ቀሪዎቹን ቀናት ደግሞ በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት እንድቆይ ተደርጓል፡፡
በማረሚያ ቤት የገጠምዎት ችግር ነበር?
በጭራሽ! በግሌ አንድም ማዋከብና ማንገላታት አልገጠመኝም፡፡ ከእስረኞቹ የተደረገልኝ አቀባበልም ጥሩ ነበር፡፡ በርካታ እስረኞች አውቀውኛል፡፡
በእውነት የእስር ጊዜዬ የተመቸ እንዲሆን አድርገውልኛል፡፡ መጀመሪያ ያስገቡኝ ዞን አንድ የሚባለው ውስጥ ነበር። 1602 እስረኞች ነበሩ፤ ሁላችንም መሬት ነበር የምንተኛው፡፡
ለኔ ጥሩ ቦታ በመስጠት ተንከባክበውኛል። የማረሚያ ቤቱ ኃላፊዎች እና ፖሊሶችም ያደረሱብኝ ምንም ጫና እና እንግልት የለም፤ ማንንም እስረኛ እንደሚያስተናግዱት አስተናግደውኛል፡፡
የፍ/ቤቱ የገደብ ውሳኔ አስተያየት እንዳልሰጥ ታስቦ የተደረገ ይመስላል ብለዋል፡፡ ከአሁን በኋላ አስተያየቶችና ትችቶችን ከመሰንዘር ይቆጠባሉ ማለት ነው? ውሳኔው ተፅዕኖ ይፈጥርብዎታል?
በምንም አይነት አይፈጥርብኝም፡፡ በምንም ሁኔታ ተፅዕኖ ሊፈጥርብኝ አይችልም፤ አይገባምም፡፡  ይሄን ተፅዕኖ ለመቋቋም የማልችል ከሆነ፣ እንደ ፖለቲከኛ ብቻ ሳይሆን እንደ ዜጋም ለመኖር ያስቸግረኛል፤ ስለዚህ በምንም መመዘኛ ተፅዕኖ አያደርግብኝም፤ ነገም ተመልሼ መታሰር ካለብኝም እታሰራለሁ፡፡ እነ አንዷለምም፣ እስክንድርም፣ በቀለ ገርባም እኮ እድሜ ልክ ተፈርዶባቸው ለዲሞክራሲ የሚፈለገውን ዋጋ እየከፈሉ ነው፡፡ የተሰጠውን ማስጠንቀቂያ ብቀበለውም በኔ አቋም ላይ የሚያመጣው አንዳችም ለውጥ የለም፡፡
በእስር ቤት ቆይታዎ ምን ታዘቡ?
በእውነት በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በቆየሁባቸው ስምንት ቀናት በዚህች ሃገር የፍትህ ስርአቱ እንዴት ፈታኝ እንደሆነ ተረድቻለሁ፡፡ በዚህች ሃገር ፈታኙ ጉዳይ የፍትህ ጉዳይ እንደሆነ፣ የልማቱም ተግዳሮት የፍትህ እጦት መሆኑን፣ የሃገር ሰላምና መረጋጋትን የሚፈትነውም የፍትህ አለመኖር እንደሆነ ለመታዘብ ችያለሁ፡፡ ሌሎችም በርከት ያሉ ጉዳዮች አሉ፡፡ ለወደፊት በማስረጃ እስደግፎ ማቅረብ ይጠይቃል፡፡ ሁኔታዎች ከፈቀዱ በዝርዝር ለማቅረብ ፍቃደኛ ነኝ፡፡ በዚህ አጋጣሚ አንዱ የታዘብኩት፣ እኛ ፖለቲከኞቹ ብዙ ጊዜ ሰጥተን የምንተቸው የፀረ-ሽብር አዋጁን ነው፤ በማረሚያ ቤት ቆይታዬ የተረዳሁት ግን፣ የፀረ - ሙስናም አዋጅ ሊፈተሽና ሊታይ እንደሚገባው ነው፡፡ ይህ አዋጅም በአንድ ወይም በሌላ መንገድ የፖለቲካ ባላንጣን ማጥቂያ መሳሪያ ሊሆን እንደሚችል ታዝቤአለሁ፡፡ የማረሚያ ቤት አያያዝ ባልተፃፈ ህግ የሚመራበት ሁኔታ እንዳለም ተረድቻለሁ፡፡ አንድም የግል ጋዜጣ እና መፅሄት ማረሚያ ቤት ሲገባ አላየሁም፡፡ ይሄ የሰብአዊ መብት ጥሰት ነው፤ ስለዚህ በአጠቃላይ የፍትህ ስርዓቱ መፈተሽ አለበት፡፡
ለስንተኛ ጊዜ ነው የታሰሩት?
በዚህ ስርዓት ለሁለተኛ ጊዜ ነው የታሰርኩት፤ በምርጫ 97ም ታስሬ ነበር፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን ሁለት የድርጅት አሰሪዎች ስለሰራተኞቻቸው ዳተኝነት ይወያያሉ፡፡
አንደኛው፡-
“እኔ መቼም እንደሚገባኝ፤ እኔ ድርጅት ውስጥ እንዳለው እንደ አቶ እገሌ ደደብ፣ ደንቆሮ ሰራተኛ በዓለም ቢዞሩ አይገኝም ባይ ነኝ፡፡”
ሁለተኛው፤
“ለምን እንዲህ አልክ? ምን አጥፍቶ አግኝተኸው ነው?” አለው፡፡
“ይህን ዳተኛው ቆይ ልጥራውና ምን ዓይነት ደደብ እንደሆነ ላሳይህ”
የተባለው ሰውዬ ተጠርቶ መጣ፡፡
“ይሄኔ አሰሪው ይህን አምስት ብር ይዘህ ሂድና ማርቼዲስ መኪና ገዝተህልኝ ና”፤ አለው፡፡ ሰራተኛው ዝም ብሎ ገንዘቡን ተቀበለና ሄደ፡፡”
ሁለተኛው፤
“አይ ወዳጄ የዛሬ ሰራተኛ ሰራተኛ መስሎሃል? የእኔን ሰራተኛ ጉድ ብትሰማ ምን ልትል ነው?”
አንደኛው፤
“እንዴት?! አሁን ከነገርኩህ የበለጠ ደደብ ሰራተኛ ይኖራል እንዴ?”
ሁለተኛው፤
“ቆይ ላስጠራውና ምን ዓይነት ጉደኛ እንደሆነ አሳይሃለሁ” አለና፤ የተባለውን ሰራተኛ አስጠርቶ፤
ወደ ሰራተኞች ክበብ ሂድና እኔ እዛ መኖር አለመኖሬን አይተህ ና” አለው፡፡ ሰራተኛው እሺ ብሎ ምንም ሳይል፣ ጥያቄም ሳይጠይቅ፣ ወጥቶ ወደ ክበቡ ሄደ፡፡
እደጅ ሁለቱ ሰራተኞች ይገናኛሉ፡፡ ጉዱ እዚህ ላይ ነው፡፡ ሁለተኛ የተላከው ሰራተኛ ለመጀመሪያው እንዲህ አለው፣
“አለቆቻችን ደደቦች መሆናቸውን አየህልኝ?”
“ምን ትጠራጠራለህ? አገር ያወቃቸው ደደቦችኮ ናቸው፡፡ የእኔ አሰሪ ምን እንዳለኝ ታውቃለህ?”
“ምን አለህ?”
“5 ብር ሰጥቶኝ ማርቼዲስ መኪና ገዝተህ ና አለ፡፡ የደደብነቱ ደደብነት ግን ምን እንደሆነ ታውቃለህ? ምን ዓይነት ቀለም ያለው መኪና እንደሚፈልግ ሳይነግረኝ!”
“ኧረ ያንተ አለቃ በምን ጣሙ? የእኔው አለቃ ምን እንዳለኝ ታውቃለህ?”
“ምን አለህ?”
“ሂድና ክበብ ውስጥ እኔ መኖር አለመኖሬን አይተህ ና አለኝ፡፡ የደደብነቱ፤ ደደብነት እኔን ማንከራተት መፈለጉ ነው እንጂ፤ እስቲ ምናለበት ስልኩን ብድግ አድርጎ፣ ክበብ ደውሎ አለሁ የለሁም ብሎ ቢያረጋግጥ!!” አለ፡፡     
*      *      *
ዕውነተኛ ሰራተኛ የሌለው አገር ለውጥ አያመጣም፡፡ ልቡ ዳተኛ የሆነ ትውልድ ለውጥ አያመጣም፡፡ መሰረቱ የተናደ ህብረተሰብ ልመልስህ ቢሉት አይንድም፡፡ “መንገድ ሲበላሽ ትራፊክ ይበዛል፤ አገር ሲበላሽ ጃርት ያፈራል፤” ይላሉ ህንዶች፡፡ ሥነ-ልቦናችን በአሉታዊነት ነቅዟል። ያለሸር፣ ያለጥፋት፣ ያለሌብነት፣ ያለ ቢሮክራሲ ጥልፍልፍ … የሚታይ ደግ ነገር ጠፍቷል፡፡ አንድ ፋይል ካንድ ክፍል ሌላ ክፍል እንዲሄድ ገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ በስልክ ቀና መልስ ለማግነት እንኳን ገንዘብ አስፈልጓል፡፡ ምናልባት ፈገግ ለማለትም ገንዘብ የሚያስፈልግበት ዘመን ሳይመጣ አይቀርም፡፡ ስለመልካም አስተዳደር ማውራት የሚቻለው የፀዳ አዕምሮ ሲኖር ነው፡፡ የጌታ-ሎሌ አስተሳሰብ እያለ የስራ ሂደት ባለቤትነት ዘበት መሆኑን አንርሳ፡፡
የጀርመን ግንብ በአደባባይ እንዲፈርስ ተደረገ እንጂ ግንቡ ጭንቅላታችን ውስጥ አለ”፤ ይላሉ ጀርመኖች፡፡
ፍጥነት አስፈላጊ ቢሆንም፣ ምን ተይዞ ጉዞ ማለትን አንዘንጋ፡፡ ከአሁኑ፤ ከውሃ ልኩ ያላስተዋልነው ነገር ነገ ጠልፎ ሊጥለን ይችላል፡፡ ያለውን ችግር የለም፣ የሌለውን ችግር አለ ማለት ፈረንጆቹ Denial የሚሉት በሽታ ነው፡፡ እያወቁ መካድ! ይሄ ለማይቀለበስ (irreversible) ችግር ከዳረገን አለቀልን ማለት ነው፡፡
አንዴ የተቀጠፈች አበባ ለዘለዓለም ትሞታለች፤ ይለናል ኦማር ካህያም፡፡ (A flower once pluck’d forever dies)፡፡ የምንፈልገውን ማወቅ ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ካፒታሊዝም ከፈለግን የካፒታሊዝምን ትክክለኛ አውታሮች እንጨብጥ፡፡ የራሳችን ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት የምንገነባ ከሆነ፤ በወጉ ቀርፀነው፣ በወጉ መሬት ላይ አስፍረነው፣ በወጉ ተግብረነው መንገዱ ይሄ ነው እንበል፡፡ አንዱ አንድ አዞ ሌላው ሌላ እያዘዘ፤ ከተምታታ፤ ስራም አይሰራ፣ ለውጥም አይመጣ። ይሆናል ሲሉን አህያ አረድን፡፡
አይሆንም ሲሉን አውጥተን ጣልን፡፡
ለምን ጣላችሁት፣ ይሆን ነበርኮ ቢሉን
ወጥተን ብንፈልግ አጣን!
እንደተባለው የኦሮምኛ አገላለፅ፤ ሌሎች ያሉንን እየሰማንና ዕውነት ነው እያልን፣ አደጋችሁ ሲሉ እሺ፣ አላደጋችሁም ሲሉን እሺ እያልን፤ መሸነጋገል አይገባንም፡፡ ሁሉም ለየራሱ ጥቅም እንደሚሮጥና ግሎባላይዜሽን የራሱ መዘዝ፤ የራሱ አባዜ እንዳለው ላንዲትም ደቂቃ መዘንጋት አይገባም፡፡
“መንግሥት ዝሆን ነው፡፡ ሁሉን ነገር ዞሮ አያይም፤ ማሳየት ያስፈልጋል” ያለው የድሬደዋ ገበሬ አባባል አይረሴ ነው፡፡ ዐይን ያለው የሰው ያስፈልጋል፡፡ የሰው ጎዶሎ የሰው ድርጭት፣ መፃጉእ ነው እንዲያፈራ፤ የሰው ተራራ የሰው ዋርካ፣ ጀግና ነው እያፈራ ይላልና ልባም ዜጋ ለማፍራት መጣር አለብን፡፡ ሰራተኛ ትውልድ፣ ጠያቂ ትውልድ፣ ተፋላሚ ትውልድ፣ ማፍራት አለብን፡፡ መንገድ የሚመራ ሰውና ድርጅት የሚመራ፣ ህዝብ የሚመራ፤ ባትሪው እጁ ላይ ነው። ባትሪውን አብርቶ ዐይኑን ከጨፈነም፣ ዐይኑን ገልጦ ባትሪውን ካጠፋም፤ መንገዱ አይሳካም፡፡ ሁሉ ነገር ከጨላለመ በኋላ እገሌ ነው እገሌ ነው እያሉ መወነጃጀል፤ “ዐይን-አውጣ ሌባ ሰርቆ ያፋልጋል” ከመባል አያመልጥም! ልብና ልቡና ይስጠን!!

አቶ አስገደ ገ/ሥላሴ፤ ከህወኀት መስራቾች አንዱ)
የካቲት 11 ይዛችሁ የተነሳችሁት አላማ ምን ነበር?
እኛ በዛን ወቅት ይዘነው የተነሳነው አላማ፣ ደርግን በሰላማዊ መንገድ መጣል ስለማይቻል፣ በትጥቅ ትግል ገርስሰን እንደ መሬት ላራሹ ያሉ የህዝብ ጥያቄዎችን መመለስ ነበር፡፡ የመጀመሪያ አቋማችን የዘውዳዊውንና የደርግን ህገመንግስት መቀየር የሚል ሲሆን አቋሙ በማኒፌስቶ ፅንሰ ሀሳብ ላይ የተነደፈ አልነበረም፡፡ በቁርጥራጭ ወረቀትና በቃል ነበር የተያዘው፡፡ በሶስትና አራት ወራት ጊዜ ውስጥ ወደ ስልሳ ሰባት ሰው ትግሉን ተቀላቀለ፡፡ መጀመሪያ ላይ ሃገራዊ፣ ብሄራዊና መደባዊ ትግል በማካሄድ ህዝባዊ መንግስት መመስረት የሚል ዓላማ የነበረ ሲሆን ከአመራሩ አካባቢ ደግሞ “እኛ የምንታገለው ከአማራ ቅኝ ገዢዎች ነፃ ለመውጣት ነው፤ ስለዚህ ዓላማችን ነፃ ሪፐብሊክ ትግራይን መመስረት ነው” የሚሉ ሀሳቦች መፍለቅ ጀመሩ። ከአንድ ዓመት በኋላ ሃሳቡ በህወኀት መሪዎችና ለእነሱ ቅርበት በነበራቸው ታጋዮች ተረቀቀና በማኒፌስቶ ወጣ፡፡ አቶ ስዩም መስፍን ሱዳን ውስጥ አሳትመው አመጡት፡፡
አቶ ስዩም መስፍን የትግራይ ሪፐብሊክን በመመስረት ያምኑ ነበር?
አቶ ስዩምና አቶ አባይ ፀሃዬ ማኒፌስቶውን ከማርቀቅና ከማሳተም ጀምሮ እጃቸው ነበረበት። አቶ ስዩም መስፍን ስለሚያምንበት ሱዳን ወስዶ በአማርኛ፣ በእንግሊዝኛና በትግርኛ አሳትሞ አመጣው፡፡ ለታጋዮች እንዲሁም ወደ ከተማም ተሰራጨ፡፡ ማኒፌስቶው የፖለቲካ ፓርቲዎችን ትኩረት ስቦ ነበር፡፡ ከባድ ቁጣንም ቀስቅሷል፡፡ በተለይ በታጋዮች ዘንድ  “እንዴት ተብሎ ትግራይ ነፃ ሪፐብሊክ ትሆናለች!?” የሚል ጥያቄ አስነሳ፡፡ “ከአማራ ቅኝ ግዛት ነፃ መውጣት የሚባለው--- እኛ ኢትዮጵያዊ አይደለንም ወይ?!” የሚል ተቃውሞ ፈጠረ፡፡ ከዚያም የህወኀት አመራር “የነፃ ሪፐብሊክ ትግራይ” የሚለውን ነገር ሰርዣለሁ አልሰረዝኩም ሳይል ዝም ብሎ ተቀመጠ፡፡
በ1977 ዓ.ም በማሌሊት ጉባኤ፣ ከብአዴንና ከህወኀት ታጋዮች ጥያቄ ሲነሳ፣ ወዲያውኑ አስተካክለነዋል አሉ፡፡ ከዚያ በኋላ  ይሄ ጉዳይ አልተነሳም፡፡ የመጀመሪያ አላማችን “ብሄራዊ መደባዊ ገዢዎችን በመገርሰስ ህዝባዊ መንግስት እንመሰርታለን” የሚለው ጠነከረና የትግራይ ሪፐብሊክ መመስረት የሚለውን እያድበሰበሱት ሄዱ፡፡
ህወኃት የተነሳለትን አላማ አሳክቷል ማለት ይቻላል?
ወታደራዊ ድል አግኝቷል፡፡ ፖለቲካዊ ድል ግን አላገኘም፡፡ ለምን ቢባል? ይዞት የተነሳው ዓላማ ሰብዓዊ መብትን ማስከበር፤ የብዙሃን ፓርቲ ሥርዓትን ማስፈን፣ ዲሞክራሲያዊ ህገ መንግስት ማጽደቅ፣ የፕሬስ ነፃነት፣ ነፃ ምርጫ፣ የዜጎችን ነፃና ሰብዓዊ መብት መጠበቅ የሚል ነበረ፡፡ ይሄ መቶ በመቶ ተግባራዊ አልተደረገም፡፡ ህወሃት በትጥቅ ትግል ጊዜም ቢሆን ከራሱ አስተሳሰብ ውጪ ለሚተነፍስ ሁሉ (ልክ ደርግ እንደሚለው) “እምቢ ላለ ጥይት አጉርሰው” ይል እንደነበር ሁሉም ያውቀዋል፡፡ ደርግ ከተደመሰሰ በኋላ ለስሙ የብዙሃን ፓርቲ ተባለ እንጂ በሀቀኛ መንገድ እውን አልተደረገም፡፡
በሰላማዊ መንገድ የሚታገሉ ፓርቲዎች ቢቋቋሙም በ97 ዓ.ም እንዳይንቀሳቀሱ ተደርገዋል። አሁን ደግሞ ነገሩ ብሶበታል፡፡ የተለየ ፖለቲካዊ አቋም ያላቸው ፓርቲዎች ከህዝብ ጋር እንዳይገናኙና የብዙሃን ፓርቲ ስርአት እንዳይጠናከር እያደረገ ነው፡፡ ለህወኀት የፖለቲካ ፓርቲዎች አሸባሪዎችና ፀረ-ዲሞክራሲያዊ ናቸው፡፡
ጋዜጠኞችን ማሰሩ፣ የፖለቲካ ፓርቲ አባላትን ማሰቃየቱና ማፈኑ ህወሃት ብዙሃነትን እንደማያምን አመላካች ነው፡፡ የግለሰብ መብትን ከመጀመሪያውም አያምንበትም ነበር፡፡ አሁን የእኔ ጥያቄ  “ኢትዮጵያን እንዴት እናድናት?” ነው፡፡ ከህወሃት ውጪ ለዚች ሀገር ማንም የላትም የሚል አስተሳሰብ አለ፡፡ አጋር ድርጅቶች እና ወዳጅ ድርጅቶች የሚባሉት ከህብረተሰብ ፍላጎት በመነጨ የተፈጠሩ ሳይሆን የህወሃት መሪዎች እንደፈለጉ ሰርተው ያመጡዋቸው ናቸው፡፡
አንዳንድ ተቃዋሚዎች፤ ህወኀት አሁንም በኢህአዴግ ውስጥ የበላይነት እንዳለው ይናገራሉ። የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው? በትግሉ ወቅትስ እንዴት ነበር?
በመጀመሪያ እንደዚህ ዓይነት ነገር አልነበረም። መጀመሪያ መደባዊ ትግል  ይቅደም፤ የብሄር አደረጃጀት አሁን አያስፈልግም ተብሎ ነበር፡፡ የህወሃት መሪዎች ግን ብሄራዊ የትግል ታክቲክ ነው የሚያዋጣን ይሉ ነበር፡፡
የብሄር መብት ጥያቄን እንደ ታክቲክ ማለት ነው?
አዎ! የህወሃት የበላይነት ባይፈለግ ኖሮ ከኢህአፓ ጋር ምን ልዩነት ነበረው? ምንም ወደ ጦርነት የሚያመጣ ሁኔታ አልነበረም፡፡ የኢህአዴግ የመጨረሻው ውጤት ሲታይ ከፊውዳሊዝም የባሰ ካልሆነ በስተቀር የተቀየረ ስርዓት የለም፡፡ ያኔ ላቅ ያለ ንቃት የነበራቸው ምሁሮች ነበሩ፡፡ ትክክለኛ ዲሞክራሲ ፈላጊ ቢሆን ኖሮ ከኢህፓ፣ ከኦነግና ከሌሎችም ጋር እርቅ ወርዶ ለሁሉም ህዝቦች ትክክለኛ የሆነ ስርዓት በተፈጠረ ነበር፡፡
የእርስዎ መደምደሚያ ህወኀት ይዞት የተነሣው አላማ ከፖለቲካ አንፃር ግቡን አልመታም የሚል ነው?
ግቡን አልመታም ነው የምለው፡፡ ፓርቲዎች እንዳይንቀሳቀሱ የሚያግድ፣ የፕሬስ ነፃነት የሚዘጋ፣ ጋዜጠኞችን አሸባሪ እያለ የሚያፍን፣ የፖለቲካ መሪዎችን የሚያስርና የህዝብ ተቃውሞ የማይሰማ፣ የፓርቲዎችን ስብሰባ የሚያግድ፣ የራሱን መዋቅር በመዘርጋት ነፃ ምርጫ እንዳይካሄድ የሚያደርግ--- ስርዓት በመፈጠሩ የህወኃት ዓላማ ግቡን እንዳልመታ ያመለክታል፡፡
 አስራ አንዱ የህወኀት መስራቾች ስምና ቅፅል ስም
አምባዬ መስፍን (ስዩም)
አቶ ገሠሠ አየለ (ስኡል)
አቶ ንጉስ ታዬ (ቀለበት)
ወልደሚካኤል ገ/ስላሴ (አስገደ)
አረፋይኔ ካህሳይ (ፀሃዬ ካህሳይ)
ፋንታሁን ዘረፅዮን (ገዳይ ዘረፅዮን)
ሙሉጌታ ሀጎስ (አሰፋ ሀጎስ)
አብተው ታከለ (ሚካኤል)
ገሞሬ አምባዬ ወ/ጊዮርጊስ - (ገበሬ የነበረ)
አረጋዊ በርሄ (በሪሁን በርሄ)
ዘሩ ገሠሠ (አጋዚ ገሠሠ)

“ታጋዮች የተሰውለት ዓላማ ተረግጧል”
ህወኀት የተመሰረተበት 39ኛ ዓመት በዓል ባለፈው ማክሰኞ በመቀሌ ከተማ በደማቅ ስነ-ስርአት አክብሯል፡፡ በዚህ በአል ላይ በትግሉ ወቅት የተሰው ቀደምት ታጋዮች የታወሱ ሲሆን የህወኀት ታሪክም በተለያዩ የፓርቲው አባላት ተነግሯል፡፡ ከህወኅት ምስረታ ጀምሮ በትግሉ ውስጥ የቆዩና በተለያዩ ጊዜያት ከፓርቲው የተለዩ አንጋፋ ታጋዮች ግን ህወኃት አላማውን ስቷል ሲሉ ይተቻሉ፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኞች አበባየሁ ገበያው እና አለማየሁ አንበሴ ከእነዚህ አንጋፋ ታጋዮች መካከል አቶ ገብሩ አስራት እና አቶ አሰግደ ገ/ሥላሴን በህወኀት የትግል ዓላማ ዙርያ  አነጋግረዋቸዋል፡፡

“ታጋዮች የተሰውለት ዓላማ ተረግጧል”
አቶ ገብሩ አስራት (የህወኀት አንጋፋ ታጋይ እና የአረና ፓርቲ መስራች)
መነሻው ላይ የህወኀት አላማ ምን ነበር?      
በሃገሪቱ ላይ የሰፈነውን ጭቆና ማስወገድ ነበር፡፡ በወቅቱ የነበረው ስርዓት የግለሰብና የቡድን መብትን የማያከብር በመሆኑ የሃይማኖት መብትን ጨምሮ እነዚህን ሰብአዊ መብቶች ማረጋገጥ ነበር ዓላማው። መብቱ ብሄሮች እስከ መገንጠል የሚያደርሳቸው ጥያቄ ካለም መገንጠል ይችላሉ የሚል ሆኖ፣ ወሳኙ ግን ነፃነት የሚለው ነበር፡፡ የትግሉ ርዕዮተ ዓለም ማርክሲዝም ቢሆንም ማጠንጠኛው ነፃነትና የሰው ልጆች መብቶችን ማረጋገጥ ነበር፡፡
ትግሉ የትግራይ ሪፐብሊክን የመመስረት አላማ እንደነበረው ይነገራል፡፡ አሁን በስልጣን ላይ ያሉ የህወሃት ታጋዮች ግን ይሄ ዓላማ አልነበረም ይላሉ። እውነቱ የትኛው ነው?
ህወኀት ለአንድ ዓመት ያህል የተፃፈ አላማና ፕሮግራም አልነበረውም፡፡ በኋላ ግን አንድ ማኒፌስቶ ተዘጋጀ፡፡ በዚህ ማኒፌስቶ የትግራይ ሪፐብሊክን የማቋቋም አላማ ተቀምጦ ነበር፤ ነገር ግን በጉባኤ አልፀደቀም፡፡ በወቅቱ የነበሩ አመራሮች አፅፈው ያሰራጩት ሲሆን በታጋዮች ዘንድ ግን ተቀባይነት አላገኘም፡፡ ተቃውሞ ስላጋጠመውም ለስድስት ወር ብቻ ነው በስራ ላይ የዋለው፡፡ “ይሄ ትክክል አይደለም፤ ከኢትዮጵያ መገንጠል እንደመብት እንጂ እንደ አላማ መቀመጥ የለበትም” የሚል ተቃውሞ ከቀረበበት በኋላ የሪፐብሊክ ምስረታ አላማ ውድቅ ተደረገ፡፡
እርስዎ ለየካቲት 11 የሚሰጡት ትርጉም ምንድነው? አላማውንስ አሳክቷል?
ትልቁ ጥያቄ ይሄ ነው፡፡ በዘንድሮው አከባበር ላይ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ሳይቀሩ ስለጠላቶች ነው የሚያወሩት፡፡ የትኞቹ ጠላቶች እንደሆኑ አልገባኝም፡፡ አካሄዳቸውን የሚቃወመውን፣ መብቴ ተነክቷል ወይም ሙስና ተንሰራፍቷል እያለ የመልካም አስተዳደር ችግሩን የሚተቸውን ሁሉ በጠላትነት እየፈረጁት ነው ማለት ነው? ይሄ የየካቲት 11 አላማ አይደለም፤ መስተካከል አለበት። አሁን ያሉት አመራሮች ከስልጣናቸው በላይ የሚያሳስባቸው ምንም ነገር የለም፡፡ ሃሳባቸው እሱ ብቻ ነው፡፡ በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ታጋዮች ህይወታቸውን የገበሩለት ዓላማ አሁን በቦታው አለ ብዬ አላምንም፡፡
የህወኀት ትግል ያመጣው ውጤት እንዴት ይገመገማል?
ደርግን ለመጣል በተደረገው ትግል ውስጥ ህወኀት ብቻ ሳይሆን በርካቶች ታግለዋል፡፡ ኢህአፓ አለ፤ ሌሎችም እንደዚያው፡፡ ስለዚህ ህወኀት ብቻ ውጤታማ ነበር ማለት አይቻልም፡፡ ማንኛውም ፍትህና እኩልነትን አመጣለሁ ብሎ መስዋዕትነት የከፈለ ሁሉ የራሱ ቦታ አለው ብዬ አምናለሁ፡፡ በዚህ ረገድ ደርግን መጣሉ አስፈላጊ ነበር፤ ነገር ግን ሰዎች የተሰውለት አላማ ተረግጧል፡፡ በተለይ በትግራይ የተቃውሞ ፖለቲካ ነውር ሆኗል፡፡ መውጫና መግቢያ ታጥቷል፡፡ ስብሰባ ማካሄድ አልተቻለም። የካቲት 11 ደግሞ ስልጣን ላይ ለመቆየት ህዝቡን ማስፈራሪያ ነው የሆነው፡፡ ለፕሮፖጋንዳ ፍጆታ ብቻ እየዋለ ነው፡፡ በሰማዕታትና በተሰውት ታጋዮች ስም እየተነገደ ነው፡፡
የህወኀት የትግል ታሪክ በትክክል ለትውልድ የሚተላለፍበት መንገድ ተመቻችቷል ይላሉ?
በእርግጥ ብዙ የታሪክ መዛግብቶች አሉ። በትግሉ የነበሩና ዛሬ ወደ ጎን የተገፉ ወገኖችም ይህን ታሪክ የማረቅ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ አሁን ታሪክ እየተቀለበሠ ነው፡፡ እንደውም ታሪኩ እየተነገረ ያለው ትግሉን በማያውቁ፣ ታሪኩን ባልተረዱ ግለሰቦች ነው፡፡ ሺዎች የተሰዉለትን መራር ትግል ተረት እያደረጉት ነው፡፡ እንደተረት ውሸት እየቀላቀሉ እያወሩት ነው፡፡ በአሁን ጊዜ ይህን መሰል የታሪክ ቅልበሳ እየፈፀመ ያለው ጉልበት እና ገንዘብ ያለው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ ፓርቲው ራሱን የዚህ ታሪክ ብቸኛ ባለቤት እያደረገ ነው፡፡ እኔ ብቻ ሳልሆን ብዙ መስዋዕትነት የከፈሉ ታጋዮች በትግሉ ወቅት ያበረከቱት አስተዋፅኦ እንኳ አይነገርም፡፡ ጭራሽ ሺዎች የተሰዉበት ታሪክ ወደ አንድ ሰው እየተጠቃለለ ነው፡፡ መለስ እና በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ሰማዕታት እኩል እንኳ እየታዩ አይደለም፡፡ ይሄ መፈተሽ ያለበት ይመስለኛል፡፡
ከ1983 በኋላስ ህወኀትን እንዴት ይገመግሙታል?
ይሄ በአጭሩ መገለፅ የሚችል አይደለም፤ የራሱ ትንታኔ የሚያስፈልገው ጉዳይ ነው፡፡
ከአቶ መለስ ህልፈት በኋላ በህወኀት ላይ የታዩ ለውጦች አሉ?
አይ የለም! ዋናው ጥንስሱ ያለው የፓርቲው ርዕዮተ ዓለም ውስጥ ነው፡፡ አብዮታዊ ዲሞክራሲ የሚለው ነገር ዜጎችን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎችን፣ ማህበረሰቦችን ሁሉ ይፈርጃቸዋል፡፡ እሱን የሚያገለግሉትን ወዳጅ ሲላቸው፣ በተቃራኒው የተሰለፉትን ጠላት ሲል ይፈርጃቸዋል፡፡ ስለዚህ መሰረታዊ ችግሩ ርዕዮተ ዓለሙ ላይ ነው፡፡ በዚህ ርዕዮተ ዓለም የተዋቀረ መንግሥት ፀረ-ዲሞክራሲ ነው የሚሆነው፡፡ መጀመሪያ ላይ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሲቪክ ተቋማት፣ ፕሬሶች ነፃነት ተሰጥቷቸው ተቋቁመው ነበር፤ ከጊዜ በኋላ ግን ይሄን መፍቀዱ ለስልጣናቸው አስጊ ሆኖ ስላገኙት ይበልጥ አምባገነንና ጨቋኝ ስርአት መገንባትን አማራጭ አድርገዋል፡፡ “ቀይ መስመር”፣ “ፈንጂ ወረዳ” በሚል እነዚህ መብቶች ተሸራርፈው ቀዳሚው ትኩረት ስልጣንን ማስጠበቅ ሆኗል፡፡
የዘውድ ስርአቱ ካከተመ 40 ዓመት ተቆጥሯል። በእነዚህ ጊዜያት በተደረጉት የተለያዩ ትግሎች የተገኙት አንኳር ለውጦች ምንድን ናቸው?
የ1966 አብዮት ያመጣቸው መሰረታዊ ለውጦች አሉ፡፡ በአጠቃላይ ማህበረሰባዊ ለውጦች ተካሂደዋል፡፡ የፊውዳል ስርአት ተሰብሯል፡፡ የመሬት ስሪቱ አዲስ አቅጣጫ እንዲይዝ ተደርጓል፤ አዲስ ማህበራዊ ኃይል ተፈጥሯል፡፡ ገበሬዎች አዲስ ማህበራዊ ኃይል ነበሩ፤ ነገር ግን በደርግ ታንቀዋል። ይሄ ባይሆን ኖሮ በደርግ የ17 ዓመት የስልጣን ዘመን ብዙ ለውጥ ይመጣ ነበር ብዬ አምናለሁ። ኢህአዴግ ከመጣ በኋላ በኢኮኖሚ ፖሊሲው ትንሽ የተሻለ ነገር ታይቶ ነበር፡፡ ሆኖም ኢህአዴግ ከጥቅም አንፃር ስለሚያየው እንደገና ኢኮኖሚውን ሁሉ የመቆጣጠር ፍላጎት እያሳየ ነው፡፡ በእርግጥ አንዳንድ የኢኮኖሚ ለውጦች መኖራቸው የማይካድ ነው፤ ይሁን እንጂ ለውጡ በጠንካራ ፖሊሲዎች የተደገፈ አይደለም። ፓርቲው ኢኮኖሚውን የመቆጣጠር አባዜ ስለተጠናወተው በእድገቱ ላይ አሉታዊ አስተዋጽኦ እያሳረፈ ነው፡፡
አሁን ስላለው የፖለቲካ ትግል የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብቶች ቻርተር፣ በአለማቀፍ ደረጃ ዜጎች መብታቸውን ለማስከበር ማንኛውንም አይነት መንገድ መጠቀም እንደሚችሉ ይደነግጋል፡፡ ጨቋኝ ስርአትን መታገል ተገቢ ነው፡፡ እኛ በደርግ ጭቆና ጊዜ የነበረን አማራጭ ትጥቅ ስለነበረ በዚያ መንገድ ሄደናል። አሁን ካለው ሁኔታ አንፃር ስንመለከተው ግን ይሄ አካሄድ ወይም በጠመንጃ የመጣ ስልጣን ዲሞክራሲን ያሰፍናል ወይ የሚል ጥያቄ አለኝ፡፡ መንግስት መቀየር ይችላል ነገር ግን ዲሞክራሲያዊ ስርአትን ማምጣት የተለየ ነገር ይፈልጋል፡፡ ጠመንጃ ያነሳ ወገን፣ መብት ሁሉ ለሱ ብቻ እንደሚገባ ነው የሚያስበው፡፡ እኛ ከሌላው ይበልጥ ሞተንለታል የሚል ትምክህት ውስጥ ነው የሚከተው፡፡ አሁን ያለው ተጨባጭ ሁኔታ የትጥቅ ትግልን የሚፈቅድ አይመስለኝም፡፡ ስለዚህ የሰላማዊ ትግሉ መቀጠል አለበት፡፡ ድሮ “የፖለቲካ ስልጣን ከጠመንጃ አፈ ሙዝ ይመነጫል” ነበር የሚባለው፤ አሁን ግን የተገላቢጦሽ መሆን አለበት፡፡ የጠመንጃ አፈሙዝ በፖለቲካ ተገዢ መሆን ነው ያለበት፡፡

አብዮቱ ሲመነዘር፡ በሚሊዮኖች ረሃብና ሞት፣ በሚሊዮኖች ችጋርና ጉስቁልና የታጨቀ ነው።
መልኩ ሲታይ፡ በርካታ መቶ ሺ ዜጎች ያለቁበት ቀይ ሽብር፣ ነጭ ሽብርና የጦርነት እሳት ነው።
“አብዮተኛው ትውልድ”፣ ስለ አብዮቱ 40ኛ አመት የሚናገርበት አንደት ማጣቱ አይገርምም።

ልክ የዛሬ አርባ አመት፣ የነዳጅ ዋጋ ላይ የአስር ሳንቲም ጭማሪ እንደተደረገ ነው አገሪቱ በቀውስ የተናጠችው - በየካቲት ወር አጋማሽ 1966 ዓ.ም። በአዲስ አበባ ጎዳናዎች እየተዘወተረ ከመጣው ሰልፍ ጋር፤ የተማሪዎችና የአስተማሪዎች ረብሻ፣ የሰራተኞች አድማና የወታደሮች አመፅ ታክሎበት፣ አገር ምድሩ በተደበላለቀ ስሜት ተቀጣጠለ። ከከተሜነትና ከዘመናዊ ትምህርት፣ ከካቢኔና ከፓርላማ አሰራር፣ እንዲሁም ከመደበኛ የጦር ሃይል አደረጃጀት ጋር ገና መተዋወቅ የጀመረችው አገር፣ መላ ቅጡ ጠፋባት። ሁለት ወር አልቆየም። ጠቅላይ ሚኒስትሩና ካቢኔያቸው ስልጣን ለቀቀ። ለወታደሮች ደሞዝ ተጨመረ። ግን አገሬው አልተረጋጋም።
መንግስት መውጪያ መግቢያ ጠፋበት። ለአስተማሪዎችና ለሌሎች ሰራተኞች ሁሉ በአንዴ ደሞዝ የመጨመር አቅም የለም። የነዳጅ ዋጋ መደጎምም የማይሞከር ሆኗል። በመላው አለም ዋጋው አልቀመስ ብሏላ። በርካታ የአረብ አገራት በእስራኤል ላይ በከፈቱት ድንገተኛ ጦርነት ሳቢያ፣ ከጥቅምት እና ጥር 1966 ዓ.ም፣ በአለም ገበያ 3 ዶላር በበርሜል የነበረው የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ ከሶስት እጥፍ በላይ ንሯል - ከ10 ዶላር በላይ አልፏል። ኢትዮጵያ ውስጥ በቀድሞ ዋጋው መቀጠል አለበት ከተባለ፤ መንግስት ለሰራተኞችና ለወታደሮች የሚከፍለው ደሞዝ ያጣል። አጣብቂኝ ውስጥ ነው የገባው።
በዚያ ላይ፣ ከነዳጅ ዋጋ ንረት በተጨማሪ፣ በከፍተኛ ድርቅ ሳቢያ የእህል እጥረትና የዋጋ ንረት ተከስቷል። አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትርና ካቢኔ ቢሰየምም፣ ተደራርበው የመጡትን ችግሮች ለመፍታት የሚያስችል ምትሃት አልነበረውም። ለዚህም ይመስላል፤ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር “ትንሽ ፋታ” ለማግኘት የተጣጣሩት።  በዚህ መሃል፤ በደሞዝና በጥቅማጥቅም ጥያቄ ዙሪያ ወታደሮችን ለማስተባበር ከየአካባቢው ግንኙነት የፈጠሩ የበታች መኮንኖች፣ ሳይታሰብ በአለቆቻቸውና በመንግስት ላይ ከፍተኛ ጉልበት እያገኙ መጥተዋል። ለዚህም አንዱ ምክንያት፤ እንደየእለቱ ስሜትና አዝማሚያ፣ “ያኛው ሚኒስትር ጉቦኛ ነው፤ ያኛው ባለስልጣን ዘራፊ ነው፤ ይያዝልን፤ ይታሰርልን” የሚሉ የተለያዩ ጩኸቶች መራገባቸው ነው። አንድ ጉበኛ ወይም አንድ አጭበርባሪ ባለስልጣን ቢታሰር፤ ቅንጣት መፍትሄ እንደማያስገኝ ግን ግልፅ ነው። እናም፤ የአገሪቱ ቀውስና ትርምስ ሳይረግብ፣ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትርና ካቢኔያቸው በአምስት ወር ውስጥ ከስልጣን ወረዱ።
የቀውሱ አቅጣጫና መጨረሻ፣ ወዴት ወዴት ይሆን ብሎ የሚጨነቅ ብዙ ነው። “አቅጣጫውን እኔ አውቃለሁ፤ እኔ ዘንድ ሁነኛ መፍትሄ ይገኛል” የሚል አንጋፋና አዋቂ ሰው ግን አልነበረም። በእርግጥ፤ በቡድን “እኛ እናቃለን፤ መፍትሄውም በእጃችን ነው” እያሉ ነጋ ጠባ መፈክር የሚያስተጋቡና የሚጮሁ ሰዎች ነበሩ። ነገር ግን፣ የአዋቂነት አልያም የአንጋፋነት ደረጃ ላይ የደረሱ አይደሉም። ብዙዎቹ ገና የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ናቸው፤ ጥቂቶቹ ደግሞ አዳዲስ ምሩቃንና ወጣት ምሁራን። እነዚህ ናቸው “አብዮተኞቹ”። ከሌላው ሕዝብ በቁጥር ሲነፃፀሩ፤ እጅግ በጣም ጥቂት ቢሆኑም፤ አንድ በመቶ ያህል እንኳ ባይሆኑም፤ ከሌላው ሁሉ የላቀ ሃይል አግንተዋል። ሌላው ሁሉ ግራ ተጋብቶ ሲደናበር፤ “የአገሪቱን ችግር ተንትነው የሚያውቁበት መመኪያ፤ መፍትሄ የሚያበጁበት መሳሪያና የወደፊቱን ጉዞ የሚመሩበት አቅጣጫ” መያዛቸውን እየተናገሩ ማን ይስተካከላቸዋል? መመኪያቸው የማርክስ የሌኒን መፅሃፍ ነው። መሳሪያቸው፤ “አብዮታዊ እርምጃ” ነው። ጉዟቸው ደግሞ ሶሻሊዝም።
በአብዮተኞቹ አስተሳሰብ፣ “ከሁሉም የከፋው ሃጥያት፣ የግል አእምሮውን መጠቀም፤ ለራስ ሕይወትና ለራስ ኑሮ ማሰብ ነው” ... ራስወዳድና ግለኝነት እጅግ ወራዳ ፀረሕዝብነት ነው በማለት ያወግዙታል። “ከሁሉም የከፋው ወንጀል ደግም፣ የራስን ሕይወት ማሻሻልና የንብረት ባለቤት መሆን ነው” ... ቡርዧ ወይም ንዑስ ቡርዧ እያሉ ያንቋሽሹታል። “ከሁሉም የከፋ በደል ደግሞ፤ የሥራ እድል መፍጠርና ሰራተኞችን መቅጠር ነው” ... በዝባዥ ወይም ጨቋኝ ተብሎ ይኮነናል። በማርክስና በሌኒን መፃህፍት ውስጥ ተደጋግመው የሰፈሩ እነዚህ ሃሳቦች ናቸው የአብዮተኛው ትውልድ መመኪያና አለኝታ። የግለሰብ ነፃነትን እያወገዙ፣ የንብረት ባለቤትን እያንቋሸሹ፤ የነፃ ገበያ ስርዓትንና ብልፅግናን እየኮነኑ ጥዋት ማታ አብዮተኞቹ መፈክር ሲያሰሙ፤ በአጠቃላይ የስልጣኔ አስተሳሰቦችን እያንኳሰሱ ሲጮሁ፤ በልበሙሉነት የሚሞግታቸውም ሆነ የሚመክታቸው አልተገኘም። ገና በጭላንጭል ይታዩ የነበሩ የስልጣኔ አስተሳሰቦች ከነአካቴው ተዳፍነው፤ የአፈና፣ የዝርፊያና የግድያ ሃሳቦች እንደ አዲስ ነገሱ። ከዚያማ መንገዱ ጨርቅ ሆነላቸው፤ መፈክሮቻቸው በቀላሉ ወደ ተግባር ይሸጋገራሉ። ማውገዝ፣ ማንቋሸሽና መኮነን በቂ አይደለማ። “መርገጥ፣ መጨፍለቅ፣ መደምሰስ” የሚሉ የአብዮታዊ እርምጃዎች ተከትለው ይመጣሉ። ደግሞም አልዘገየም።
በየካቲት አጋማሽ “በግብታዊነት የፈነዳው አብዮት”፣ አመት ሳይሞላው ነው፤ ከሃሳብ ወደ ተግባር መሸጋገር የጀመረው። 120 የበታች መኮንኖች የተሰባሰቡበት ኮሚቴ፤ መስከረም ላይ ንጉሡን ከስልጣን ሲያስወግድ ባወጣው አዋጅ፤ መቃወም ወንጀል ነው ብሎ አወጀ። ሁሉም ሰው ከራሱ በፊት አገርን ማስቀደም እንዳለበት ሲያስረዳም፤ ኢትዮጵያ ትቅደም የሚለውን መርህ የሚቃወም፣ ለመቃወም የሚያስብ ወይም የሚያሳስብ... ወዬለት ሲል ዛተ። የራሴን ሃሳብ መግለፅ መብቴ ነው ብሎ መሟገት አይቻልም - ራስ ወዳድነትና ግለኝነት ተወግዟላ። ለማንኛውም የደርግ ዛቻ በባዶ አልነበረም። በእስር የቆዩ 59 የቀድሞ ባለስልጣናት፤ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡና ሳይከራከሩ እንዲገደሉ ህዳር ወር ላይ ተወሰነ - በአንድ የደርግ አባላት ስብሰባ። የየካቲቱ አብዮት አመት ሲሞላው፣ የደርግ የስልጣን ዘመን ገና መንፈቅ እንዘለቀ፤ ሌላ አዋጅ መጣ።   
በአብዮታዊ እርምጃ፤ ባንኮች፣ ፋብሪካዎች፣ የቢዝነስ ድርጅቶች ተወረሱ። መሬት ሁሉ የመንግስት ነው ተባለ። ከ500 ካሬ ሜትር በላይ መሬት፣ ከአንድ መኖሪያ ቤት በላይ ግንባታና ሕንፃ ሁሉ ተወሰደ። ማከራየት ወንጀል ሆነ። ሰራተኛ መቅጠር ተከለከለ። አብዮተኛው ትውልድ መመኪያና አለኝታ አድርጎ የዘመረላቸውን መፈክሮች ሁሉ፤ በላይ በላዩ ተግባራዊ ለማድረግ ብዙ ጊዜ አልፈጁም። መቃወም ብቻ ሳይሆን ለመቃወም ማሰብ አይቻልም የሚል የአፈና አዋጅ፤ ፋብሪካ መፍከትም ሆነ ሰራተኛ መቅጠር አይቻልም ብሎ ንብረትን የሚወርስ የዝርፊያ አዋጅ፤ ያለ ፍርድ እንዳሻው ማሰርና መረሸን የሚችል የግድያ ስልጣን ... ምን ቀረ? የግል ሃሳብን፣ የግል ንብረትን፣ የግል ሕይወትን ... በአጠቃላይ የግል ነፃነትን ገና ሳይፈጠር በእንጭጩ ለማጥፋት የሚያስፈልጉ የአብዮተኞቹ ሃሳቦችና መፈክሮች በሙሉ ሳይውሉ ሳያድሩ በደርግ ተግባራዊ ሆነዋል። አብዮተኞቹ ተሳክቶላቸዋል።
ሶስተኛው ደረጃ በራሱ ጊዜ የሚመጣ ውጤት ነው - የሃሳብና የተግባር ውጤት። የማያቋርጥ የአፈና፣ የዝርፊያና የግድያ ስርዓት። ማለትም የሶሻሊዝም ጉዞ። እዚህ ላይም፣ አብዮተኞቹ ምንም የጎደላቸው ነገር የለም - የተመኙትን ውጤት አግኝተዋል። ከንጉሡ ዘመን ጋር እያነፃፀርን ልናየው እንችላለን።
“እንደተመኘኋት አገኘኋት” - የአብዮተኞቹ ጉዞ
እንደምታውቁት፣ የአፈና፣ የዝርፊያና የግድያ ስርዓት ለኢትዮጵያ አዲስ አይደለም። ከአፈና ጋርም ነው መሃይምነትና ኋላቀርነት የሚንሰራፉት። ከዝርፊያ ጋር ደግሞ ድህነትና ረሃብ ይበረታሉ። ከግድያ ጋርም ሽብርና ጦርነት ይበራከታሉ። ኢትዮጵያ በእነዚህ ሁሉ ትታወቃለች። በንጉሡ ዘመንም እንዲሁ፣ አፈናው፣ ዝርፊያውና ግድያው ለአገሪቱ የሚያንስ አልነበረም። በእርግጥ፤ በዚያን ዘመን አንዳንድ የነፃነት ጭላንጭሎች እየተፈጠሩ ነበር። በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ፣ ከ1950ዎቹ ጀምሮ አፄ ኃይለስላሴ በተገኙበት ይዘጋጁ የነበሩ አመታዊ የግጥም ውድድሮችን መጥቀስ ይቻላል። ተማሪዎች በየአመቱ በሚያቀርቧቸው ግጥሞች፤ መንግስት ላይ ትችቶች ይሰነዝሩ እንደነበር አብዮተኞቹ አይክዱትም። የዩኒቨርስቲው ተማሪዎች የሚዘጋጁት ጋዜጣ ላይም፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ መረር ያሉ የተቃውሞ ፅሁፎች ታትመዋል። እንዲያም ሆኖ፣ የንጉሱ መንግስት፣ የሃሳብ ነፃነትን ያከብር ነበር ማለት አይደለም። ንጉሱ ከዩኒቨርስቲው አመታዊ የግጥም ውድድሮች ርቀው ጠፉ። የዩኒቨርስቲው ጋዜጣ ላይም እገዳ እንዲጣል አስደርገዋል። በአጭሩ፣ ንጉሡ የሃሳብ ነፃነትን በማስከበር የሚወደሱ አይደሉም።
አሳዛኙ ነገር፤ እጅግ የባሰ የአፈና ስርዓትን ጎትቶ የሚያመጣ አብዮት መፈጠሩ ነው። ስልጣን የያዘው ደርግ እና ከጎኑ የተሰለፉ አብዮተኞች፣ እንዲሁም ስልጣን ለመንጠቅ በተቃራኒ ጎራ የተሰለፉ አብዮተኛ ድርጅቶች ሁሉ፤ እንደየአቅማቸው የቻሉትን ያህል የአፈና ስርዓት ዘርግተዋል። ተቃውሞና ትችት መተንፈስ ጨርሶ ተከለከለ። ስልጣን የያዘ አብዮተኛ፣ “ተቃወምከኝ፣ ትችት ሰነዘርክ” ብሎ ካሰበ፤ “ፀረ አብዮት፣ ፀረ ሕዝብ” እያለ አፋፍሶ ያስራል፤ ይገድላል። ስልጣን ያልያዘ አብዮተኛም ቢሆን፣ አድፍጦ ይገድላል፤ ካልሆነለትም ስም የማጥፋት ዘመቻ ያፋፍማል። ይህም ብቻ አይደለም። በቃ፤ ለመቃወምና ለመተቸት ማሰብ ወይም ማሳሰብ፣ የአገር ክህደት ወንጀል ነው ተባለ። ምን ይሄ ብቻ?
በየመንደሩ የከተማና የገጠር ነዋሪዎች በቀበሌና በከፍተኛ፤ አልያም በፆታና በእድሜ፣ በስራ ቦታና በሙያ አይነት... የመሰባሰብ ግዴታ መሰባሰብ፣ የሴቶች ማህበር፣ የወጣቶች ማህበር፣ የወዛደሮችና የመምህራን ማህበር ... ወዘተ የማህበር አባል የመሆን ግዴታ፣ እናም ፓርቲንና መንግስትን የማወደስ የግዴታ ሸክም ተጫነባቸው። ቢያንስ ቢያንስ በንጉሱ ዘመን፣ ተቃውሞና ትችት የመሰንዘር ብዙ ነፃነት ባይኖር እንኳ፤ አፍን ይዞ ዝም ማለት ይቻል ነበር። ከአብዮቱ በኋላ ግን፣ ለፓርቲና ለመንግስት እየሰገዱ ውዳሴ የመዘመር ግዴታ መጣ። አይን ያወጣ ዘመናዊ አፈና ብለን ልንሰይመው እንችላለን።
ያው፤ አፈና በሚኖርበት ዘመንና ቦታ ሁሉ፣ በዚያው መጠን ወከባ፣ እስርና ግድያ ይኖራል። በእርግጥ፣ በአፄ ኃይለሥላሴ ዘመን፣ በቀጥታ ንጉሡን መተቸትና መቃወም ከባድ ቢሆንም፣ በጥቅሉ ጥንታዊውን የፊውዳል ሥርዓት መተቸት እንደ ወንጀል አይቆጠርም ነበር። ሃዲስ አለማዬህን ድርሰቶች በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል። እንዲያም ሆኖ፣ የመመረረ ተቃውሞ የሚሰነዝሩና የሚቀሰቅሱ ሰዎች በንጉሡ ዘመን መታሰራቸውና አንዳንዶችም መገደላቸው አልቀረም። በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ከዋናዎቹ የሶሻሊዝም አቀንቃኞች መካከል በገናናነት ስሙ የሚነሳው ጥላሁን ግዛው፣ በንጉሡ መንግስት ነው የተገደለው። ስም እየጠቀሱ፣ እገሌና እገሊት ብለው እየቆጠሩ፣ በንጉሡ ዘመን እነማን እንደተገደሉ የሚዘረዝሩልን የታሪክ ሰዎችን የምናጣ አይመስለኝም። ችግሩ ምን መሰላችሁ? የ66ቱ አብዮት ይህንን ሁሉ ታሪክ ገለባበጠው። ከአብዮቱ በኋላ፤ የሚታሰሩና የሚገደሉ ሰዎችን በስምና በቁጥር ለመዘርዘር መሞከር ከንቱ ሆነ። እንዲያውም ያልታሰሩትን መቁጠር ነበር የሚሻለው። እንደተራ ነገር፣ ከየቤቱና ከየጎዳናው በሺ የሚቆጠሩ ሰዎችን እያፋፈሱ በየቀበሌ ማጎር፤ ከዚያም እንደዘበት በረድፍ መረሸን... የአገራችን የሶሻሊዝም አብዮተኞች ያስመዘገቡት ውጤት፣ ከሌሎች አገራት ሶሻሊዝም አብዮተኞች የተለየ አይደለም። የጅምላ እስርና የጅምላ ግድያ፣ ሽብርና ጦርነት ነው ውጤቱ።
የአብዮተኞቹ ውጤት ግን ከዚህም የላቀ ነው። ራስወዳድነትን በማውገዝ የሰዎችን የብልፅግና ፍላጎት ለመስበር ያልፈነቀሉት ድንጋይ የለም። ግለኝነትን በመኮነን የንብረት ባለቤትነትን ለማጥፋት ያለ እረፍት ዘምተዋል። ዘመቻቸው ያለ ውጤት አልቀረም። በእርግጥ ቀድሞውንም ያን ያህል ንብረትና ብልፅግና አልነበረም። ነገር ግን፤ በአብዮተኞቹ ዘመቻ የብልፅግና ተስፋ ተዳፍኖ፣ የንብረት ምልክት ጠፍቶ፤ የአገሬው ሕዝብ ከቀድሞ በባሰ ድህነትና ችጋር ለከፋ ስቃይ ተዳርጓል።
በቀይ ሽብርና በነጭ ሽብር፤ በስልጣን ሽሚያና በጦርነት ከተፈጠረው እልቂት ያልተናነሰ ጥፋት የተከሰተውም በድህነት ምክንያት ነው። በ77ቱ ድርቅ፣ ወደ ሚሊዮን ገደማ ሰዎች በረሃብ እንደሞቱ በወቅቱ ተዘግቧል። የውጪ ለጋሾች ተሯርጠው ደራሽ እርዳታ ባያቀርቡ ኖሮ፤ በ81 እባ በ82 ዓ.ም እንዲሁም በ92 ዓ.ም ሚሊዮኖች በረሃብ ያልቁ ነበር። ታዲያ፤ የያኔዎቹ አብዮተኞች፣ አሁን በየካቲት ወር ወይም ዘንድሮ በ2006 ዓ.ም ስለ አብዮቱ አርባኛ አመት፣ አንዳች ቁምነገር ለመናገር የሚያስችል አንደበት ማጣታቸው ይገርማል?   

በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት እየታየ በሚገኘው 28 ተከሳሾች ላይ ለቀረበ የአቃቤ ህግ የቪዲዮ ማስረጃ አስተርጓሚ እንዲመድብ የታዘዘው የኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቪዥን ድርጅት፤ የፍ/ቤቱን ትዕዛዝ ተግባራዊ ባለማድረጉ ዋና ዳይሬክተሩ ፍ/ቤት ታስረው እንዲቀርቡ ታዘዘ፡፡
በእነ አማን አሠፋ መዝገብ በሚገኙ የሽብር ተጠርጣሪዎች ላይ አቃቤ ህግ የሰው ምስክሮችንና በሺዎች የሚቆጠሩ የሰነድ ማስረጃዎችን ለፍ/ቤቱ አቅርቦ ያጠናቀቀ ሲሆን በአረብኛና በኦሮሚኛ ቋንቋዎች ለቀረቡት የቪድዮ ማስረጃዎች ኢሬቴድ አስተርጓሚ እንዲመድብ ከፍ/ቤቱ የተላለፈውን ትዕዛዝ ተግባራዊ አላደረገም ተብሏል፡፡ በዚህም ዋና ዳይሬክተሩ አቶ ብርሃኑ ኪዳነማርያም ታስረው ፍ/ቤት እንዲቀርቡ ታዟል፡፡
ቀደም ሲል እነዚህን የሽብር ተጠርጣሪዎች አስመልክቶ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን “ጅሃዳዊ ሃረካት” የሚል ዶክመንተሪ ፊልም ተዘጋጅቶ መሰራጨቱ የሚታወስ ሲሆን አቃቤ ህግም በክስ ማመልከቻው፣ ተጠርጣሪዎች የአልቃይዳ ህዋስ ሆነው በአለማቀፍ የሽብር መዋቅር ውስጥ ተሳታፊ እንደነበሩ ማመልከቱ ይታወሳል፡፡

  • መሥፈርቱን የማያሟሉ ከሐምሌ 1 ጀምሮ እርምጃ ይወሰድባቸዋል  
  • በሥራ ላይ ካሉት ክሊኒኮች መስፈርቱን የሚያሟላ  አይኖርም ተብሏል
  • የግል ክሊኒኮች ማህበር በቂ የዝግጅት ጊዜ ሊሰጠን ይገባል አለ  


የመንግሥትና የግል የጤና ተቋማት አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችላቸውን መስፈርቶችና ደረጃዎች የሚወስን አዲስ መመሪያ ወጣ፡፡ የጤና ተቋማቱ በአዲሱ መስፈርት መሰረት ራሳቸውን እንዲያደራጁ እስከ ሰኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም ጊዜ የተሰጣቸው ሲሆን ከሐምሌ 1 ጀምሮ መሥፈርቱን ባላሟሉት ላይ እርምጃ ይወሰዳል ተብሏል፡፡
የኢትዮጵያ የምግብ የመድኃኒትና የህክምና መሳሪያዎች ቁጥጥር ባለስልጣን ያወጣውና በአገሪቱ የሚገኙ ሁሉንም የመንግስትና የግል የጤና ተቋማት ይመለከታል የተባለው አዲስ መመሪያ፤ ተቋማቱ ማሟላት የሚገባቸውን ዝርዝር ጉዳዮች ይፋ አድርጓል፡፡ በዚሁ መመሪያ ላይ እንደተገለፀው፤ ሆስፒታሎች የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል፣ አጠቃላይ ሆስፒታልና ስፔሻላይዝይድ ሆስፒታል ተብለው በ3 መደቦች የሚከፈሉ ሲሆን የጤና ማዕከላት፣ የጤና ጣቢያዎችና ልዩ ማዕከላትም በዘርፉ እንደሚጠቃለሉ ተጠቅሷል፡፡
መመሪያው ሆስፒታሎች እንደየደረጃቸው የተለያዩ አገልግሎቶችን መስጠት እንደሚገባቸው በዝርዘር የገለፀ ሲሆን የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎች ቢያንስ 35 አልጋዎች፣ አጠቃላይ ሆስፒታሎች 50 አልጋዎች እንዲሁም ስፔሻላይዝድ ሆስፒታሎች ከ300 የማያንሱ አልጋዎች እንዲኖራቸው ያስገድዳል። ሁሉም የጤና ተቋማት የማዋለድ አገልግሎት መስጠት እንደሚገባቸው የገለፀው መመሪያው፤ በክሊኒኮች ውስጥ አልጋ በማዘጋጀት ህሙማንን በመደበኛነት አስተኝቶ ማከም እንደማይቻልና መካከለኛ ክሊኒኮች ለድንገተኛ ህመምና ለማዋለድ አገልግሎት የሚሆኑ 10 አልጋዎች ብቻ ሊኖራቸው እንደሚገባ ይደነግጋል፡፡ ክሊኒኮችን በስም መሰየም እንደማይፈቀድም በዚሁ መመሪያ ላይ ተገልጿል፡፡
የኢትዮጵያ የምግብ የመድኃኒትና የህክምና መሣሪያዎች ቁጥጥር ባለስልጣን፣ የቁጥጥር አስተባባሪ ሲስተር የሺአለም በቀለ መመሪያውን ማውጣት ያስፈለገበትን ምክንያት ሲናገሩ፤ በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ በጤናው ዘርፍ ተሰማርተው ለህዝብ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙ የጤና ተቋማትን ለመቆጣጠርና ተቋማቱ በምን ደረጃ ላይ እንዳሉ ለማወቅ ባለመቻሉ፣ ይህንን ችግር በማስወገድ ተቋማቱ የሚሰጧቸው አገልግሎቶች ጥራታቸውን የጠበቁ እንዲሆኑ ለማድረግና ህብረተሰቡን ለአደጋ የሚያጋልጡ አሰራሮችን ለማስወገድ ነው ብለዋል። በጤናው ዘርፍ የሚታዩ ህገወጥ ተግባራትን በመቆጣጠር ለህብረተሰቡ ብቃት ያለው አገልግሎት እንዲሰጥ ለማድረግ እንደሆነም አክለው ገልፀዋል፡፡
ባለስልጣን መ/ቤቱ የጤና ተቋማቱ የሚተዳደሩበትን መመሪያና መስፈርት ህግ አድርጎ ከማፅደቁ በፊት ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሰፋ ያለ ውይይት ማድረጉን የጠቆሙት ሲስተር የሺዓለም፤ በመመሪያው ላይ የተካተቱና ለአሰራር እንቅፋት ይሆናሉ የሚባሉ ጉዳዮች ካሉ ማሻሻያዎችን ለማድረግ እንደሚቻል በተደጋጋሚ መገለፁን አስታውሰዋል፡፡ ይሁን እንጂ መመሪያው ሊያሰራን አይችልም የሚል ሃሳብ ከየትኛውም ወገን ባለመነሳቱ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ህግ ሆኖ እንዲፀድቅ መደረጉንም ገልፀዋል፡፡ በዘርፉ የተሰማሩ አካላት ድርጅቶቻቸውን በመመሪያው መሰረት እንዲያደራጁ እስከ ሰኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም ድረስ ጊዜ እንደተሰጣቸውና የጊዜ ገደቡ ሲጠናቀቅ ባለስልጣን መ/ቤቱ የራሱን እርምጃ እንደሚወስድ ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ የግል ክሊኒኮች ባለቤቶችና አሰሪዎች ማህበር ምክትል ሊቀመንበር አቶ አበበ ያለው በበኩላቸው፤ መመሪያው የአገሪቱን ወቅታዊ ሁኔታ ያላገናዘበና በዘርፉ የተሰማሩ በርካታ ባለሙያዎችን ከስራ ውጪ የሚያደርግ በመሆኑ ሊታሰብበት ይገባል ብለዋል፡፡ ህብረተሰቡ ጥራት ያለው የህክምና አገልገሎት እንዲያገኝና ዘርፉም ወደተሻለ ደረጃ ከፍ እንዲል ታስቦ የወጣውን መመሪያ እንደማይቃወሙ ምክትል ሊቀመንበሩ ገልፀው፤ሆኖም በአገሪቱ የተሰማሩ የጤና ተቋማትን ወቅታዊ ሁኔታ ያላገናዘበና ምንም የመፍትሔ ሃሳብ ያላቀረበ በመሆኑ ብዙዎችን ከስራ የሚያፈናቅል ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ከ500 በላይ አባላት ያሉት ማህበሩ፤ አዲሱን ህግና መመሪያ ተከትሎ በመስፈርቱ መሰረት በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ አገልግሎት መስጠት ይቻላል ብለው እንደማያስቡ ገልፀው መንግስት በቂ የዝግጅት ጊዜና የጤና ተቋም መገንቢያ ቦታ ሊሰጠንና የብድር አገልግሎት ሊያመቻችልን ይገባልም ብለዋል፡፡ “እንደዚያ ካልሆነ የምንሰራው ከግለሰቦች በተከራየናቸው ክሊኒኮች በመሆኑ መስፈርቱ የሚጠይቀውን ለማሟላት ስንል ማፍረስም ሆነ መቀየር አንችልም” ሲሉ ችግራቸውን ጠቁመዋል፡፡ መስፈርቱን ካላሟላችሁ መስራት አትችሉም ከተባለ ግን በርካታ ባለሙያዎች ከስራ እንደሚፈናቀሉና ህብረተሰቡም በቂ አገልግሎት ለማግኘት እንደሚቸገር መታወቅ ይገባዋል ብለዋል።
ሲስተር የሺዓለም በቀለ በበኩላቸው፤“በአገሪቱ ውስጥ በህጋዊ መንገድ ተመዝግበው አገልግሎት ከሚሰጡ የጤና ተቋማት መካከል አዲሱን መስፈርት በበቂ ሁኔታ የሚያሟሉ ተቋማት ስለመኖራቸው አፍን ሞልቶ መናገር አይቻልም” ይላሉ፡፡

እስካሁን ለ3ሺ ተማሪዎች ነፃ የትምህርት ዕድል ሰጥቷል

ሴንትራል ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በቅርቡ ከሳኡዲ ለተመለሱ 180 ያህል ኢትዮጵያዊያን ነፃ የትምህርት እድል መስጠቱን አስታወቀ፡፡ የዩኒቨርሲቲው መስራችና ፕሬዚዳንት ዶ/ር አብነት ግርማይ፣ በዩኒቨርሲቲው ሾላ ካምፓስ ከትላንት በስቲያ የትምህርት እድሉ የተሰጣቸው፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተወካይ፣ የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊና ጋዜጠኞች በተገኙበት በሰጡት መግለጫ፤ ዩኒቨርስቲያቸው ከዚህ ቀደም ከተለያዩ የመንግስትና የግል ተቋማት ለተመለመሉና ከፍለው መማር ለማይችሉ 3ሺህ ተማሪዎች ነፃ የትምህርት እድል መስጠቱን አስታውሰው፤ አሁን ደግሞ የትምህርት ሚኒስቴርን መስፈርት ላሟሉ የሳኡዲ ተመላሾች ተመሳሳይ እድል መስጠቱን ተናግረዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በአዲስ አበባ፣ በአዳማ፣ በሀዋሳና በባህርዳር በአጠቃላይ ስድስት ካምፓሶች ያሉት ሲሆን በእያንዳንዱ ካምፓስ 30 ተማሪዎች ገብተው እንዲማሩ መወሰኑ ተገልጿል፡፡
ተማሪዎቹን አስተምሮ ለማስመረቅ ከአራት ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚፈጅ የጠቆሙት ዶ/ር አብነት፤ ከሌቭል አንድ እስከ ዲግሪ ድረስ እንዲማሩ እድሉ መመቻቸቱን ገልፀዋል፡፡ የትምህርት አሰጣጡንና አጠቃላይ የዩኒቨርስቲውን ድባብ  በተመለከተ ተማሪዎቹ ገለፃ ከተደረገላቸው በኋላ የሚፈልጉትን የትምህርት አይነት፣ የት መማር እንደሚሹና የሚማሩበትን ሰዓት መምረጥ እንደሚችሉ ዶ/ር አብነት ተናግረዋል። “ትምህርታችሁን ጀምራችሁ እስክታጠናቅቁ ድረስ ራሳችሁን፣ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጁንና  የከተማ አስተዳደሩን የሚያስከብር ስርዓት እንድትከተሉ እጠይቃለሁ” ሲሉም ለተማሪዎቹ ምክርና ማሳሰቢያ ሰጥተዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ተወካይ በበኩላቸው፤ቢሯቸው ተማሪዎቹንና የትምህርት አቀባበል ሁኔታቸውን እንደሚከታተል ገልፀው፣ ለሁሉም መልካም እድል ተመኝተውላቸዋል፡፡ እድሉ የተሰጣቸው ተማሪዎችም ነፃ የትምህርት እድሉን በማግኘታቸው ከተማ አስተዳደሩንና ዩኒቨርሲቲውን አመስግነው ትምህርታቸውን በአግባቡ ለመከታተል ቃል ገብተዋል፡፡