
Administrator
“ኢህአዴግ በርቱ ብሎናል…
“የመግባባት አንድነት ሠላም ማህበር” ከተቋቋመ ገና አራት ወሩ ቢሆንም፣ ኢህአዴግን ጨምሮ በርካታ የፖለቲካ ፓርቲዎችን አነጋግሮ አዎንታዊ ምላሽ እንዳገኘ ይናገራሉ፡፡ ህገመንግስቱ ለአገራችን የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ጅማሮ በቂ ነው የሚሉት የማህበሩ ስራ አስኪያጅ አቶ ፋንታሁን ብርሃኑ፤ የፍርድ ቤቶች ነፃነት፣ የፕሬስ ነፃነትና የማህበራት ነፃነት ስላልተከበረ የአገሪቱ ችግሮች እየተባባሱ መምጣታቸውን ይጠቅሳሉ፡፡ በየጊዜው የሚከሰቱ ችግሮች ዘላቂ መፍትሔ ሳያገኙና በመንግስት እየተዳፈኑ፣ የኋላ ኋላ የሚፈነዱ ፈንጂዎች እየሆኑብን ነው የሚሉት አቶ ፋንታሁን፤ በቀልን በማስወገድና ችግሮችን በግልግል ዳኝነት በመፍታት ዘላቂ ሰላምን ማምጣት ይቻላል በሚል የተቋቋመ ማህበር መሆኑን ይገልፃሉ፡፡ ጋዜጠኛ ሠላም ገረመው “የኢትዮጵያ ህዝብ የነፃነትና የስልጣን ባለቤትነቱን እንዲጨብጥ እንሰራለን” ከሚሉት የማህበሩ ስራ አስኪያጅ አቶ ፋንታሁን ብርሃኑ ጋር ያደረገችው ቃለምልልስ እንደሚከተለው ተጠናቅሯል፡፡
ማህበሩ በፖለቲካዊ ጉዳዮች ዙሪያም ጭምር የሚሰራ ነው፡፡ ከፖለቲካ ፓርቲ ወገንተኝነት የፀዳ ነው? ማህበራችን ሙሉ በሙሉ ገለልተኛ ነው፡፡ የአገራችንን ችግሮች ስንመለከት ከጊዜ ወደ ከጊዜ እየከፋ እጅግ በጣም ፈታኝ ሁኔታ ውስጥ እየገባን ነው፡፡ ይህን ፈተና ለማሸነፍ ተገቢውን ያህል ሁነኛ ነገር አልተሠራም፤ ብዙም አልተጮኸም፡፡ ሌላው ትልቁ ችግር በቀል ነው፡፡ በአገራችን የሚከሰቱ የመንግስት ለውጦች ላይ ሁሉ በቀል አለ፡፡ ሁሌም ደም መቃባት አለ፡፡ አሁን ላለው ገዢ ፓርቲም ይህንን ፍራቻችንን እንነግረዋለን፡፡ ሁላችንም የበቀል ስሜቱ ይብቃን ማለት አለብን፡፡ ሠላም እንምጣ እያልን ነው ወደ ተግባር ለመግባት የመጀመሪያ ስራዎቻችን የጀመርነው፡፡ የማህበሩ አላማ ምንድነው? ብዙ አሳሳቢ ነገሮችን እናያለን፡፡ የነፃ ፕሬስ ጋዜጠኞች ይሰዳዳሉ፡፡ የፍርድ ቤት ነፃነት ላይ የመንግስት አስፈፃሚ አካላት ጣል ገብነት አለ፡፡ የተለያዩ አይነት ግጭቶች በመንግስት ሃይል ይዳፈናሉ እንጂ መፍትሔ አያገኙም፡፡ ይሄ ያሳስበናል፡፡ እንዲህ አይነቱ አሳዛኝ ታሪክ እስከመቼ ይቀጥላል? ብለን እንሰጋለን፡፡
ሀገራችን በዓለም ህዝብ ፊት የምትታወቀው በእርስ በርስ ጦርነት፣ በረሃብ፣ በተመፅዋችነትና በስደት ነው፡፡ ከሶስተኛ ዓለም ሀገራት ከመጨረሻዎቹ ተርታ ላይ ነው የምትገኘው፡፡ አሳዛኙ ታሪክ መቀየር አለበት፡፡ ኢትዮጵያ በሶስት ሺህ አመታት ታሪክዋ ያጣችውን ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ለማምጣት ህዝቦች በሀገራዊ ጉዳይ ላይ ተፈቃቅደውና ተዋደው፤ የፈቀዱትን የሀገር መሪ የመምረጥ፣ ካልፈቀዱም የማውረድ መብት የሚያገኙበት የህዝብ የስልጣን ባለቤትነት እንዲረጋገጥ የዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ያስፈልገናል፡፡ በአንድ ሀገር መልካም አስተዳደር እውን የሚሆነው፣ በግልፅነትና በተጠያቂነት መርህ ላይ የተመሰረተ የመንግስት አሰራር የሚሰፍነው፤ ሙስና፣ አድልዎና ወገንተኝነት በተጨባጭ መረጃና በህዝብ ነፃ ተሳትፎ እየተጋለጠ የሚወገደው፣ ለፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት የተመቻቸ ሁኔታ የሚፈጠረው ዲሞክራሲያዊ መንግስት ሲኖር ነው፡፡ ለዚሁም ዲሞክራሲያዊ ህገ-መንግስት ያስፈልጋል፡፡ የእኛ አገር ህገመንግስት፣ ለዴሞክራሲያዊ ስርዓት ጅማሮ በቂ ነው፡፡ ህግ አውጪው አካል ለምሳሌ ፓርላማው ህግ የማውጣት ስልጣን ይኖረዋል፡፡ ህጎቹ ተግባራዊ የሚሆኑት በአስፈፃሚ አካል ነው - ለምሳሌ በጠቅላይ ሚኒስትርና ካቢኔ፡፡ ማንኛውም የመንግስት አካል ከህግ ውጭ እንዳይሰራ የመቆጣጠርና የህጎችን ትርጓሜ እየተነተነ የመዳኘት ስልጣን ደግሞ የፍርድ ቤቶች ነው፡፡
ህገ መንግስቱ በዚህ መልክ የህግ ተርጓሚነት ስልጣን የፍርድ ቤቶች እንደሆነ ቢገልፅም፤ የፍ/ቤቶች ነፃነት በአስፈፃሚው አካል ጣልቃ ገብተን ይጣሳል፡፡ ስለዚህ አስፈፃሚው ጣልቃ ገብነት ሊገታ ይገባዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አስፈፃሚው አካል፣ በፓርላማ (በህግ አውጪው) አካል እውነተኛ ቁጥጥር ሊደረግበት ይገባል፡፡ ፓርላማውም እንዲሁ በህዝብ ቁጥጥር ስር መሆን ይኖርበታል፡፡ በህዝብ ነፃና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ የተወከለ መሆን አለበት፡፡ በየጊዜው የሚቀረፁ ህጎችና ፖሊሲዎች ህገ-መንግስቱን እንዳይሸራርፉ የህገ-መንግስቱ ገለልተኛ ጠባቂ አካል ያስፈልጋል፡፡ የእኛ አላማም ይህንን ለማስገንዘብ ነው፡፡ በሀገራችን መልካም አስተዳደር ሰፍኖና የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ራዕያችን እውን ሆኖ ልማት እንዲስፋፋ፣ መሰረታዊ ችግሮች መቀረፍ አለባቸው፡፡ ፍርድ ቤቶች ሙያዊ ብቃት፣ ተቋማዊ ጥንካሬ ተጎናፅፈው በነፃነትና በገለልተኛነት የሚሰሩበት ስርዓት መዘርጋት፣ ለዘላቂ ሰላምና ለአስተማማኝ ዲሞክራሲ ዋስትና ይሆናል፡፡ ገለልተኝነቱ የተረጋገጠ ጠንካራ የዳኝነት ስርዓት ካልተዘረጋ፣ ህገ መንግስትና ህግ በመውጣቱ ብቻ የሰላምና የዲሞክራሲ ዋስትና ሊሆን አይችልም፡፡ የዳኝነት ስርዓት ፍትህን የማንገስ፣ የህግ የበላይነትን የማረጋገጥ፣ ሰላምና መረጋጋትን የማስፈን ራዕይ ሊሰነቅ ይገባል፡፡ ይህን ለማስገንዘብ እንሰራለን፡፡ የሰላም የልማትና የዲሞክራሲ ግንባታ፣ በመንግስት የተናጠል ጥረት በተዓምር እውን ሊሆን አይችልም፡፡ ይቻላል ከተባለም የዴሞክራሲ ግንባታ ተዳፍኖ፣ በመቶ አመት ታሪክ ከድህነት ወደ መካከለኛ ገቢ ማሸጋገር ይቻል ይሆናል፡፡
ግን እዚያም የትም አይደርስም፡፡ ስለዚህ በመንግስት ጥረት ብቻ እውን ሊሆን አይችልም ማለት ነው፡፡ የህዝብ ተሳትፎ ያስፈልጋል፡፡ በነፃነት የሚንቀሳቀሱ ህዝባዊ ማህበራት፣ የሙያ ማህበራት (ለምሳሌ የመምህራን ማህበር) የንግድ ማህበር፣ ሀገር በቀል የበጎ አድራጎት ድርጅቶች፣ ተፎካካሪ ፓርቲዎች እንዲያብቡ በህገመንግስቱ የተዘረዘሩ መብቶችን በተግባር ማስከበር አለበት፡፡ ግማሽ መንገድ ድረስ ተጉዞ ሊቀበላቸው ይገባል፡፡ በተለይ የማህበራት አደረጃጀት ላይ የሚስፋፋ የመንግስት ጣልቃ ገብነት ተወግዶ ማህበራት በነፃነት መንቀሳቀስ አለባቸው፡፡ ጣልቃ ገብነቱ ካልተገታ ግን ስርዓት አልበኝነት ይነግሳል፡፡ ግጭቶች ሁሌም እየተራገቡ ከድጡ ወደ ማጡ እየዘቀጡ የሚጓዙበት ጉልበት ያገኛሉ፡፡ የሀገራችን ችግርም ይሄው ነው፡፡ የተሻለ ለውጥ የማግኘት ጭላንጭል ከአመት አመት እየተዳፈነ ግጭቶች መፍትሄ ሳያገኙ ይቀጥላሉ፡፡ የሚከሰቱ ግጭቶች ሁሌም የሚረግቡት በዘላቂ መፍትሄ ሳይሆን በመንግስት ሃይል ነው፡፡ በመንግስት የሃይል የበላይነት ለጊዜው ግጭቶች ቢዳፈኑም፤ ከአደጋ አያላቅቀንም፡፡ የተዳፈነ እሳት እንደማለት ነው፤ ወይም ጊዜ ጠብቆ የሚፈነዳ ፈንጂ ይሆናል፡፡ ማህበሩ መንግስትን የሚተችበት ጉዳይ ምንድነው? ዘላለማዊ ገዢ መሆን የለበትም ነው የምንለው፡፡
ማንኛውም መንግስት ስልጣን መያዝ ያለበት ህዝብ በምርጫ ለአምስት ዓመት በኮንትራት ሲሰጠው ብቻ ነው፡፡ በህግ የተገደበ የኮንትራት ውክልና እንጂ ዘላለማዊ ስልጣን አይደለም፡፡ ዘላለማዊ ገዢ ፈጣሪ ብቻ ነው፡፡ ለሰላምና ለመግባባት የሚሰራ ማህበራችን የፍቅር ማህበር ነው፡፡ የፍቅር ምንጭ ፈጣሪ በመሆኑ፤ ማህበራችን በውሸት ለመቀባትና ስም ለመለጠፍ አልተፈጠረም፡፡ ነጩን ነጭ፤ ጥቁሩን ጥቁር እንላለን፡፡ እውነትና ሰላም የናፈቃት አገር ነች፡፡ በኢትዮጵያችን በየጊዜው የሚፈጠሩ ግጭቶች ከመጥበብ ይልቅ እየሰፉ፣ እልቂት ማየትና ዋይታ ማዳመጥ እንደ ባህል እየቆጠርን እንገኛለን፡፡ ጆሮም እውነትን ማዳመጥ የናፈቀበት ዘመን ውስጥ ነን፡፡ የሃሳብ ልዩነትን በመከባበርና በመቻቻል ከማስተናገድ ይልቅ፣ የጎሪጥ በመተያየትና ተለያይቶ በመጠቋቆር የጥቁር ህዝብ የአንድነት ታሪክንና አሻራን መናድ ያብቃ፡፡ እያለ ስርዓት አልበኝነት ውስጥ እየተዘፈቅን እንገኛለን፡፡
የቋንቋ፣ የብሄር፣ የሀይማኖት፣ የጎሳ ልዩነታችን የኢትዮጵያ ውበት መሆኑ በወረቀት ላይ ብቻ ሆነብን፡፡ ማህበራችን እነዚህን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለመቅረፍ ኢትዮጵያውያን ሁሉ በእውነት እንድንቆምና በአንድነት ለአንድነት እንድንነሳ፣ በመቻቻል ለመከባበር እንድንግባባ ይሰራል፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምስራቅ እስከ ምእራብ ለአንድነት ለእውነትና ለሰላም፣ ለፍቅርና ነፃነት እንስራ፤ ግጭትና ረሀብ፣ ፍርሃትና አድልዎ ከሀገራችን ይወገዱ፡፡ እውነት፤ ፍቅር እንደ ውሃ ጠማን፡፡ የእውነትና የፍቅር ፏፏቴዎች ይፍለቁ፡፡ በሰላምና በነፃነት እጦት ተራቆትን፡፡ የሠላምና እና የነፃነት ሸማ እንልበስ እያልን በአንድነት እናዚም፡፡ መጠቋቆርንና መጋጨትን ጥላቻንና በቀልን ከውስጣችን አስወግደን፣ እውነትንና ፍቅርን፣ ሰላምንና ነፃነትን በልባችን ለማሳደር የመግባባት አንድነት መድረክ እንፍጠር ስንል፣ መንግስት ህዝብ የጣለበትን አደራ ባለመወጣቱ እየተቸገርን ነው፡፡ በሃገሪቱ ውስጥ የታሰሩና በግዞት የሚገኙ የነፃው ፕሬስ ሰራተኞችና የፖለቲካ እስረኞች ምህረት ሊያገኙ እንዲቻል ከመንግስት አካላት ጋር እንዲሁም ከሽምግሌዎች ጋር በመወያየት እልባት ላይ ለመድረስ እንሰራለን፡፡ ይህ ብቻ ግን አይደለም፡፡
በኢትዮጵያ ውስጥ ዘላቂ ሰላም የሚያመጣ ስርዓት መፍጠር አለብን፡፡ በኢትዮጵያ ጉዳይ ያገባናል የሚሉ በሃገሪቱ ውስጥ ያሉ ተፎካካሪ ፓርቲዎች፣ መንግስት፣ በውጪ ያሉ የፖለቲካ ኃይሎች፣ የሙያ ማህበራት፣ ምሑራንና ታዋቂ ግለሰቦች፣ በአጠቃላይ ሁሉንም ወገን የሚያሳትፍ፤ ለአንዴም ለመጨረሻ ጊዜም በቀል የሚያከትምበት ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ለማምጣት ብሔራዊ የምክክር እርቅ ጉባኤ እውን እንዲሆን እንሰራለን፡ ለዚህም በሮች እንዳይዘጉ፣ የተዘጉትም እንዲከፈቱ እናደርጋለን፡፡ የሠላም ሸንጎ ተመስርቶ የሰላም ጉባዔ እንዲካሄድ እናደርጋለን፡፡ ከሀገር ሽማግሌዎች፣ ከሀይማኖት አባቶች፣ ከአባት አርበኞች፣ ከጡረተኞች፣ ከምሁራን (ከመምህራን)፣ ከንግዱ ማህበረሰብ፣ ከትራንስፖርት ሰራተኛው፣ ከገበሬው፣ ከሠራተኛው፤ ከጋዜጠኛው፤ ከአካል ጉዳተኞች፤ ከሴቶች፤ ከወጣቶች፣ ከተማሪዎች፣ ከታዋቂ ግለሰቦች እና ከሌሎችም የተውጣጣ ሀገር አቀፍ ግጭት አስወጋጅ የሰላም ም/ቤት ሸንጎ እንመሰርታለን፡፡ “ሠላም ማህበር” ፍቅር፣ ነፃነት፣ ዲሞክራሲ፣ መልካም አስተዳደር ለናፈቀው የኢትዮጵያ ሕዝብ የመግባባት አንድነት መድረክ ይሆናል፡፡ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ተነጋግራችኋል? ከኢህአዴግስ? ጉዳዩን ስንጀምረው በማህበሩ አላማና ሃሳቦች ላይ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ተነጋግረናል፡፡ ከገዢው ፓርቲና ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ተነጋግረናል፡፡ እኛ፣ “ተቃዋሚ ፓርቲ” ናቸው አልንም፡፡ ምክንያቱም “ተቃዋሚ” ሲባል ጠላትነት ይመስላል፡፡ ተፎካካሪ ናቸው፡፡ አነጋግረናቸዋል፡፡ የኢህአዴግ ፓርቲ አመራሮችንም አነጋግረናል፡፡ “መውጫ ቀዳዳ አጥተን አዘቅት ውስጥ ነበርን፤ እናንተ በመምጣታችሁ ደስ ብሎናል፤ በርቱ” ብለውናል፡፡ ሃሳባችንን ደግፈዋል፡፡
ምርጫ ቦርድም ተቀብሎን ጥሩ ምላሽ ሠጥቶናል፡፡ ኢህአዴግ … መንግስት አላማችሁን ደግፎታል? አላማችንን ተቀብሎት ነው ማህበሩን የመሠረትነው፡፡ ስለዚህ አሁንም በንግግራችን ወቅት ጥሩ ጅምሮች ነው እያየን ያለነው፡፡ በእርግጠኝነት ተቀብለውናል ማለት ይቻላል፡፡ የታሳሪ ጋዜጠኞች ጉዳይ እንዲሁም ከፖለቲካ ጋር በተያያዘ የታሰሩ ሰዎች ጉዳይ ላይ ሃሳባችሁ የሚሰምር ይመስላችኋል? መንግስትን እናውቀዋለን፡፡ ምንም እንኳ ማህበራችን ዕውቅና እንዲያገኝ ቢፈቅድም፣ ምንም እንኳ መንግስት ሃሳባችንን ቢጋራም፣ ለእሱ እስካልተመቸው ድረስ በተለያዩ ወገኖች ላይ የተለያየ ስያሜ እየለጠፈ፣ ሠዎችን በመወንጀል የማሰር ተግባሩን መቀጠሉ አይቀርም፡፡ ይሄ ለእሱ ትክክል ነው፡፡ እኛ ደግሞ ይህንን እንቃወማለን፡፡ ጊዜ ሊፈጅ ይችላል እንጂ ከአላማችን አንዱ፣ ሁሉንም የፖለቲካ እስረኞች ጉዳይ ከዳር ማድረስና በቀልና ቂምን ማስወገድ ነው፡፡
የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት ተነሱ
የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት በመሆን ለረጅም ጊዜ ያገለገሉት አቶ ኡሞድ ኡቦንግ ከክልል ፕሬዚዳንትነታቸው ተነስተው በፌደራል መንግስት መመደባቸው ታወቀ፡፡ ሰሞኑን በክልሉ በተካሄዱ ተከታታይ የስራ አስፈፃሚ፣ የማዕከላዊ ኮሚቴ እና የተለያዩ የስራ ሃላፊዎች ስብሰባ ላይ አቶ ኡሞድ ከክልል ፕሬዚዳንትነታቸው በመነሳት በፌደራል መንግስት በስራ ሃላፊነት መዛወራቸውን መግለፃቸውን ምንጮቻችን አመልክተዋል፡፡ ቀጣዩ የክልሉ ፕሬዚዳንት በሚቀጥለው ሳምንት በሚካሄድ ጉባኤ እንደሚመረጥ እና የአቶ ኡሞድ ኦቦንግ ከክልሉ ፕሬዚዳንትነት መነሳት በይፋ እንደሚነገር ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ የክልሉ የስራ ሃላፊ ተናግረዋል፡፡
አቶ ኡሞድ በየትኛው የፌዴራል መንግስት መስሪያ ቤት እንደተመደቡ አለመታወቁንና የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንትና የድርጅቱ ሊቀመንበር በመሆን እያገለገሉ የሚገኙት አቶ ጋት ሉዋክ፤ ቀጣዩ የክልሉ ፕሬዚዳንት እንደማይሆኑ በስፋት እየተነገረ መሆኑን ምንጮቻችን ገልፀዋል፡፡ አቶ ኡሞድ የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት ከመሆናቸው በፊት የክልሉ የፀጥታ ሃላፊ በመሆን አገልግለዋል፡፡
“ሁላችንም በኪሳችን ትናንሽ ዘውድ ይዘን ነው የምንዞረው!”
ማን ያውቃል!?
ኢህአዴግና ህዝብ፣ ኑሮና “መታደስ”
ቀጠሮ እንዳላቸው፣ የምርጫ ቀን ሲደርስ-
የኢህአዴግ ባለሥልጣናት በአዘቦቱ ቀን የት እየገቡ ነው?
እናንተ---- በቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ፣ ፋውንዴሽን ምስረታ ላይ የተገኙት የኡጋንዳው ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒ ያሉትን ሰማችሁልኝ? የእኛን አገር ለማመስገን ብለው የራሳቸውን ሞለጩት እኮ፡፡ ለነገሩ አሳዘኑኝ እንጂ አላዘንኩባቸውም፡፡ እንዴ --- የእውነት ተቸግረው ቢሆንስ! (ወልደው ሳይጨርሱ አሉ--) እናላችሁ --- የእኛ አገር ከሳቸው አገር ዩጋንዳ የተሻለች መሆኗን ሲናገሩ እንዲህ አሉ - “እዚህ አገር ጥሩ ነው ፤ አየር መንገዳችሁ ጥሩ ይሠራል ፤እኛ አገር እኮ ፓይለቶቹ ራሳቸው ከአውሮፕላኑ ላይ ኢንጂኑን ይሰርቁታል” (ሃሳቡ እንጂ ንግግራቸው ቃል በቃል አልተቀዳም!) እኔ የምለው ግን ---- ሰውየው “ገበና” የሚባል ነገር አያውቁም እንዴ? ወይስ ኡጋንዳ “ገበና” የለም? (ባይኖር ነዋ!) ሌላው ሁሉ ቢቀር ግን “የአገር ገፅ ግንባታ” የሚባል ነገር አያውቁም እንዴ? ምናልባት ገንብተው ጨርሰው ይሆናላ! አያችሁ ---- እኛ እኮ ሁሌ እያፈረስን ስለምንገነባ ነው! በነገራችን ላይ ሙሴቪኒ ለ“መለስ ፋውንዴሽን” 500ሺ ዶላር ነው የለገሱት፡፡ ደቡብ ሱዳን ደግሞ 1ሚ ዶላር ሰጥታለች፡፡
ሱዳን 2ሚ ዶላር --- ለግሳለች፡፡ በዚህም በዚያም ብሎ ብቻ 50ሚ ዶላር የተሰበሰበ መሰለኝ፡፡ እኔ የምለው---ለምን እንዲህ አናደርግም! አንድ ቀን ሁሉንም የአፍሪካ መሪዎች ሰብስበን (ዲሞክራት ነው አምባገነን ሳንል) ለህዳሴው ግድብ እንዲያዋጡ ብንጠይቃቸውስ? እውነቴን እኮ ነው ---- በተለይ ነዳጅ ያላቸው አገራት ዳጎስ ያለ ገንዘብ ይሰጡናል ብዬ እገምታለሁ፡፡ እኛን ያቅተናል ብዬ እኮ አይደለም ---(50 ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክሙ ---ለ50 አገራት ጌጡ ብዬ እኮ ነው!) በዚያ ላይ -- ግድቡ ሲጠናቀቅ “ሃይል” መዋሳቸው ይቀራል? (ነውር ከሆነ ግን ይቅር !) እኔ የምላችሁ --- ከቤኒሻንጉል የተፈናቀሉት የአማራ ተወላጆች ወደ ክልሉ ይመለሱ መባሉን ሰማችሁ? (የሰው አገር ስደት አንሶን በገዛ አገራችን---?) የክልሉ ፕሬዚዳንት ስለተፈናቀሉት ዜጎች ተጠይቀው ሲመልሱ ምን እንዳሉ ታውቃላችሁ --- “ነገሩ የተፈፀመው ኪራይ ሰብሳቢ በሆኑ የበታች አመራሮች ግብታዊ እርምጃ ነው” ብለዋል፡፡
እኔ ግን አንድ ጥያቄ አለኝ፡፡ ይሄ “ኪራይ ሰብሳቢ” የሚል ቃል ፍቺው ተለወጠ እንዴ? ምናልባት ኢህአዴግ የቃሉን ትርጉምና አጠቃቀም ለውጦት ከሆነም “ኢንፎርም” እንደረግ ! እንዴ --- ዜጎችን ከገዛ አገራቸው በሃይል ያፈናቀሉ የወረዳ “አምባገነኖች” እንዴት በአቅም ማነስ የተገመገሙ ይመስል “ኪራይ ሰብሳቢ” በሚል ይታለፋሉ? (ማን ነበር “ሁላችንም በኪሳችን ትናንሽ ዘውድ ይዘን ነው የምንዞረው” ያለው?) አይገርምም --- ሁሉም መንገስ ይፈልጋል ለማለት እኮ ነው! እውነቴን ነው --- ኪራይ ሰብሳቢ የተባሉት የበታች አመራሮች እኮ ህዝብ ብቻ አይደለም ያፈናቀሉት፤ ህገመንግስትም ነው የናዱት፡፡
ህገመንግስት በኀይል መናድ --- ከዚህ በላይስ አለ እንዴ? (ሥልጣን ብቻ ሳይሆን የዜጎች መብትም ሲጣስ እኮ ህገመንግስት መናድ ነው!) “ኪራይ ሰብሳቢዎቹ” የዜጎችን ሰርቶ የመኖር መብት ብቻ አይደለም የደፈጠጡት! ህዝብን ከህዝብ ፤ ብሄርን ከብሄር ለማጋጨት-- ለማፋጨት---ለማቃቃር---- ለማናቆር ሞክረዋል (ህዝቡ ኩም አደረጋቸው እንጂ!) ይሄ ማለት ደግሞ --- አገርን መበጥበጥ--- ማናወጥ ---መቀወጥ --- ይመስለኛል (ጀርባቸው ይመርመር!) እናላችሁ ----- እነዚህ የበታችም ይሁኑ የበላይ አመራሮች “ኪራይ ሰብሳቢ” የሚለው ታፔላ ጨርሶ አይመጥናቸውም (ኒውክሌር ላስወነጨፈ ድንጋይ እንደመወርወር እኮ ነው!) የሽብር ሥራ ሰርቶማ በ“ኪራይ ሰብሳቢነት” ስም ማምለጥ የለም (ፌር አይደለማ!) ለማንኛውም ግን የክልሉ መንግስት ጥፋት መፈፀሙን አምኖ --- የተፈናቀሉት እንዲመለሱ መጠየቁ ያስመሰግነዋል (እንደሌሎቹ “ካፈርኩ አይመልሰኝ” ባለማለቱ!) አሁን የሚቀረው እንግዲህ ህዝብን ያፈናቀሉ አመራሮችን ለህግ ማቅረብ ብቻ ነው (አደራ እንዳይዘነጋ!) ዛሬ ምን እንዳማረኝ ታውቃላችሁ? (ሥልጣን እንዳትሉ ብቻ!) እኔን ያማረኝ ምን መሠላችሁ ---- ከኢህአዴግ ጋር ፊት ለፊት መፋጠጥ! (“ከኢህአዴግ ጋር ወደፊት!” አልወጣኝም!) እንደዚህ ካልኩማ ---ቅስቀሳ አደረግሁ ማለት ነው - የምርጫ! (ምን ቤት ነኝ ብዬ?) እናላችሁ… ከኢህአዴግ ጋር ትንሽ ብንፋጠጥ ደስ ይለኛል፡፡ በ“ሃርድ” እኮ አይደለም፤ በ“ፒስ ነው”፡፡
እውነቱን ልንገራችሁ አይደል… እኔ ተአምር ቢመጣ ከኢህአዴግ ጋር አልጣላም፡፡ ሰው እንዴት ከ20 ዓመት በላይ የገዛውን መንግስት ይጣላል? (አንዳንዴ በኃይል አንዳንዴ በልምምጥ ቢሆንም ) ወዳጆቼ… የእኔ ዓላማ ጠብ ሳይሆን መፋጠጥ ነው - ፊት ለፊት መነጋገር፣ መመያየጥ---- ያለ ፍርሃት፤ ያለ ይሉኝታ--- እውነቷን ---- ማፋጠጥ! አንዳንድ የኢህአዴግ ካድሬዎች ይሄን ምኞቴን ሰምተው ምን አሉ መሰላችሁ ? “መጀመርያ የሥነምግባር ደንብ ፈርም!” እኔ እኮ --- እንደ አንዳንድ ተቃዋሚዎች “እንደራደር” ወይም “የጋራ መንግስት እናቋቁም” አልወጣኝም፡፡ እንድንፋጠጥ ብቻ ነው የፈለግሁት፡፡ የሆድ የሆዳችንን እንድናወራ! አስተዳድርሃለሁ ያለኝን መንግሥት ፊት ለፊት መጠየቅ ደሞ መብቴ ነው (ልማታዊ መንግስት ይከለክላል እንዳትሉኝ!) በነገራችሁ ላይ ኢቴቪም እኮ በቅርቡ “ፊት ለፊት” የሚል “የማፋጠጫ” ፕሮግራም ጀምሯል (የአበሻ Hard talk በሉት!) የእኔ ከኢቴቪ የሚለየው በምን መሰላችሁ? እነሱ የመንግስት መ/ቤት ሃላፊዎችን ብቻ ነው የሚያፋጥጡት፡፡ እኔ ግን ትላልቆቹን ነው (“የአመራሩ ቁንጮ” የሚባሉትን!) የእድል ነገር ሆኖ ግን የተመኘኋቸውን የአመራር ቁንጮዎች ለማናገር አልቻልኩም ለምን አትሉም ? የአመራሩ ቁንጮዎች ሁሉ ሰሞኑን ቢሮ አልነበሩም - የህዝብ እሮሮ እንዲያዳምጡ በየክፍለከተማው ተልከው ነበር፡፡
ህዝቡንና እቺን አገር ወደፈለጉት አቅጣጫ የሚቀዝፉት “ካፒቴኖች” እንኳንስ እኔን ሊያናግሩ እርስ በርስም የሚነጋገሩ አይመስለኝም፡፡ እንዴ ሰሞኑን ጊዜ የለማ! (የህዝቡ እሮሮ ተሰምቶ የሚያልቅ መሰላችሁ?) የኑሮ ውድነት--- የመብራትና የውሃ ችግር----የቴሌኮም ኔትዎርክ መቆራረጥ----የመኖርያ ቤት እጦት---- የስኳርና የዘይት መጥፋት----የእህል ዋጋ መናር---- ሥራ አጥነት---የትምህርት ጥራት ችግር----ወዘተ ሲሰሙ እየዋሉ ሲሰሙ ማደር ነው (ተጠራቅሞ እኮ ነው!) አያችሁ --- የኢህአዴግ አመራሮች ከህዝብ ጋር የሚገናኙት በአምስት አመት አንዴ ነው - ምርጫ ሲጠባ! ያን ጊዜ ነው ዘርፈ ብዙ ችግሮቻችንን የምንዘከዝከው፡፡ እነሱም ይሰሙናል፤ እኛም እንናገራለን፡፡ በምርጫ ሰሞን የኢህአዴግ ባለስልጣናት እንኳንስ የመልካም አስተዳደር ችግር ቀርቶ --- የትዳር ችግራችንንም ብንነግራቸው በደንብ ይሰሙናል፡፡ ምን ትዝ አለኝ መሰላችሁ? የአብዬ መንግሥቱ ለማ “ማን ያውቃል” የምትል ግጥም - ማን ያውቃል? የመስቀል ወፍና የአደይ አበባ ቀጠሮ እንዳላቸው መስከረም ሲጠባ---- እቺን ግጥም ከኢህአዴግ የመስቀል ወፍነት ጋር ያስታወስኩት አንድ ወዳጄ ደግሞ፣ የጥበብ ቆሌ ቀረበችውና (ኢንስፕሬሽን ለማለት ነው) በአብዬ መንግስቱ ስታይል እንዲህ ሲል ተቀኘልኝ- ማን ያውቃል!? ኢህአዴግና ህዝብ፣ ኑሮና “መታደስ” ቀጠሮ እንዳላቸው፣ የምርጫ ቀን ሲደርስ--- (ለኢህአዴግና ለዘንድሮ ምርጫ ይሁንልኝ) እኔ ግን አንዳንዴ የኢህአዴግ ነገር ግርም ይለኛል፡፡ እስካሁን አራት ያህል ምርጫ አካሂዷል አይደል --- ግን ሁሌ ጀማሪ ነው የሚመስለው፡፡
በቃ ትዝ የምንለው ምርጫ ሲመጣ ብቻ ነው፡፡ ያኔ ሩጫ ነው -ዘመቻ! (“ሠርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ”) በጣም የሚገርመው ደግሞ ምን መሠላችሁ --- ዘመቻ ከመውደዱ የተነሳ የህዝብ እሮሮ እንኳን የሚሰማው በዘመቻ ነው፡፡ እናላችሁ… ሰሞኑን ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት (የመርከቧ ካፒቴኖች የሚባሉት) የህዝብ እሮሮና አቤቱታ በማዳመጥና በማወያየት ተጠምደው ሰነበቱላችሁ፡፡ በኢቴቪ አይታችሁ ከሆነ እኮ --- የቀረ ባለሥልጣን የለም፡፡ ጠ/ሚኒስትሩን ብቻ ነው ያላየናቸው፡፡ ይቅርታ አድርጉልኝና ---- እነዚህ ቱባ ቱባ የመንግሥት ባለሥልጣናት በአዘቦት ቀን (ምርጫ በሌለበት ጊዜ ማለቴ ነው) የት ነው የሚገቡት? (ሰው ይናፍቃል አይሉም እንዴ?) እኔማ መብራት ሌሊት ሌሊት ለጅቡቲ እንሸጣለን እንደሚሉት፣ ራሳቸውንም እየሸጡ እንዳይሆን ብዬ ነው፡፡ ገብቷችኋል አይደል ---- ምርጫ የሌለ ጊዜ --- ጎረቤት አገር የሚያስተዳድሩ ስለመሰለኝ እኮ ነው! (ለምሳሌ ሶማሊያ ወይም ደቡብ ሱዳን) ለማንኛውም ግን ለጊዜው እኛም ናፍቆታችንን ተወጥተንባቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ የምናገኛቸው በ2007 ምርጫ ነው፡፡ እስከዚያ መቻል ነው - ናፍቆቱን! (ወደን ነው!)
ንጉሥና ዝንጀሮ፣ ራሱ ይከምራል፣ ራሱ ይበትናል
ጐራዴን፣ እጀታዋን የያዘ ያሸንፋል
***
(የትግሪኛ ተረት) በዓላት ሁሉ ቢሰባሰቡ መስቀልን አያህሉም!
ቂል ከሰረቋት በኋላ ትነግዳለች!
ያለ የማያልፍ ይመስለዋል፣ ያለፈ ያልነበረ ይመስለዋል!
(የጉራጊኛ ተረት)
***
ሞኝ ባል ሚስቱን ይስማል!
ዕዳ የሌለበትን ድህነትና በሽታ የሌለበትን ክሳት የመሰለ የለም (የወላይታ ተረት)
ያለ ጊዜዋ የበቀለች ማሽላ፣ ወይ ለወፍ ወይ ለወንጭፍ! (የአማርኛ ተረት)
አንድ የጃፓኖች ተረት እንደሚከተለው ይተረታል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ዛፍ ላይ በመውጣት በጣም ድንቅና አንደኛ የተባለ ሰው ነበረ፡፡ ምስኪን ደሃ ነው፡፡ ግን ባለሙያ ዛፍ - ወጪ ነው፡፡ አንድ እጅግ ረዥም የሆነ ዛፍ ላይ እንዲወጣ፣ ላንድ ሌላ ሰው ሊያስተምር መመሪያ እየሰጠው ነበር፤ አሉ፡፡ የሚማረውን ዛፍ-ወጪ ከላይ ከላይ ያሉትን ቅርንጫፎች እንዲቆርጣቸው፤ ትዕዛዝ ሲሰጠው፤ “በል፤ በጣም ከፍ ያሉትን ቅርንጫፎች በደንብ ቁረጣቸው” አለው፡፡ ዛፍ-ወጪው ተማሪም እንደታዘዘው የጫፍ የጫፎቹን ቅርንጫፎች ቆረጠ፡፡ እየቆረጠ ሳለ ግን ታች ወርዶ ሊከሰከስ የሚያስችልበት በጣም አንሸራታች ጫፍ ላይ ደረሰ! አስተማሪ ሆዬ አደጋ ላይ ሊወድቅ መድረሱን እያየ ዝም አለ፡፡ የዛፍ አወጣጥ ተማሪው እንደምንም አንሸራታቹን ቦታ አልፎ መውረድ ጀመረ፡፡
መሬት ሊደርስ በጣም ጥቂት ሲቀረው፤ “ተጠንቀቅ! የምትረግጠው እርከን እንዳያንሸራትትህ በጣም በጥንቃቄ፤ ውረድ!” አለው አስተማሪው፡፡ ይሄኔ አንድ መንገደኛ ሰማና፤ “ይገርማል! ዋናው አደጋ ጋ ሲደርስ ዝም ብለህ ስታበቃ አሁን ትመክረዋለህ እንዴ? ከዚህ ከፍታማ እራሱ በመረጠው መንገድ ዱብ ሊል ይችላል” አለና ጠየቀው፡፡ “ዋናው ነጥብ እሱ ነው፡፡ ሰውዬው በጣም አደገኛ ከፍታ ላይ ሳለማ ከአሁን አሁን ወደቅሁኝ በሚል ሥጋት፣ እራሱ ይጠነቀቃል፡፡ እራሱ ለራሱ ይፈራል፡፡ አሁን መሬት ሊደርስ ሲል ግን ሀሳቡን ጥሎ፣ ሰውነቱን ያላላና ሁሉን ይንቃል! ይሄኔ ነው አደጋ ያለው! ሁሌ ስህተቶች የሚሠሩት ሰዎች ቀለል ያለ ቦታ ሲደርሱ ነው” ይህንን ሀሳብ ያቀረበው አስተማሪ ሰው በጣም ደሀ ከሆነ መደብ የተፈጠረ ሰው ነው፡፡ የተናገረው ነገር ግን ከጠቢባን ደረጃ የሚመደብ ነው፡፡ በእግር ኳስ ጨዋታም ላይ ይሄ አባባል ሚዛን የሚደፋ ነው፡፡ በጣም ከሚያጨናንቅ አዳጋች ሁኔታ ውስጥ ኳሷን ካራቁ በኋላ፤ የምትቀጥለው ኳስ ቀላል ትመስላለች፡፡ ያለ ጥርጥር ግን ብዙ ጊዜ ኳሷን ይስቷቷል!
***
ዛፍ አወጣጥ የሚያስተምረን ሰው አወራረድ ያስተምረን ዘንድ እንመኝ፡፡ የወጣ ሁሉ አይቆይም፡፡ የቆየ ሁሉ ደግሞ መውረድ አይቀርለትም፡፡ በአናቱ ቅቤ ጣል ያለበት ሽሮ ከበላን በድህነታችን ላይ ካፒታሊዝም ሥርዓት እንደመጨመር ነው፡፡ የታደልን እኛ ብቻ ነን ብንል ምፀቱ አይገለንም!! በአናቱ ከሚጨመር ሥርዓት ያድነን!! አንድ ኢትዮጵያዊ ፀሀፊ የሮዛ ሉክሰምቡርግን አስተሳሰብ በመጥቀስ የነቆጠውን፤ ስለ ምርጫ ስናስብ አቅም ይሆነን ዘንድ አሁን እናስበው፡- “ነፃነት፣ ቁጥራቸው የፈለገውን ያህል በርካታ ቢሆን፣ ለመንግሥት ደጋፊዎችና ለፓርቲ አባሎች ብቻ የሚሰጥ መብት አይደለም፡፡ ነፃነት ሁልጊዜም የተለየና ተቃዋሚ ሀሳብ ያለው ወገን መብት ነው፡፡ ይህን የምለው ለፍትህና ለርትዕ፣ ልዩና አምልኮ - ባዕዳዊ ፍቅር አድሮብኝ አይደለም፡፡ የፖለቲካ ነፃነት ህብረተሰብን የሚያድሰው፣ በዚህ ሀቅ ላይ ሲመሰረት ብቻ በመሆኑ ነው፡፡ ነፃነት የተወሰኑ ምርጥ ወገኖች ልዩ-መብት (ፕሪቪሌጅ) ከሆነ የይስሙላ ነፃነት ነው የሚሆነው፡፡ ከላይ የጠቀስነው አበሻ ፀሀፊ፤ የምርጫውን አሀዝ ብቻ ሳይሆን የህዝቡን ልብ እንገነዘብ ዘንድ የሚከተለውን እንመርምር ይለናል፡- “ወድቀው ከታሪክ ፊት በሀፍረት ሊሰናበቱ ሳምንት ሲቀራቸው ሁሉ 98 ከመቶ በሆነ ድምፅ ይመረጡ የነበሩት የምስራቅ አውሮፓ “ዲሞክራቶች” ነበሩ፡፡ “ዲሞክራሲያዊ ምርጫ”ን የይስሙላ ያደርገው የነበረውም ይኸው ነው፡፡ 90 በመቶም በላይ ድምፅ እያገኘ በሕዝብ ዘንድ ይጠላ የነበረውን የ (ምስራቅ) ጀርመን ኮሙኒስት ፓርቲ አስመልክቶ “ሕዝቡ ሌላ ፓርቲ መምረጥ ካልቻለ፣ ፓርቲው ሌላ ሕዝብ ይምረጣ እንግዲህ” ብሎ ቀልዶ ነበር ቤርቶልድ ብሬሸት፡፡” ለለውጥ ያህል ደግሞ የዛሬን ትንተና በተረቶቻችን ግንዛቤ እናጅበው፡፡ ስለ ፊውዳላዊ ሥርዓት ቅሪታችን ይህን ልብ እንበል፡- እንኳን ራሳቸውን ተመተው፣ ምንጊዜም ካሣ ተቀባይ ናቸው!! ስለምርጫችን ይህን ልብ እንበል፡- ልቅደም እንጂ፣ የሩጫ መልክ አለው ወይ! እማሆይ የተቆረጠ ማሽላ ይጠብቃሉ እናቷ መራቂ ልጇ አሜን ባይ! ቂል ከሰረቋት በኋላ ትንግዳለች ያለጊዜዋ የበቀለች ማሽላ፣ ወይ ለወፍ ወይ ለወንጭፍ ብትሸልም ለሚስትህ፣ ብትፎክር በሠርግህ ዋዜማ! ብትቆርጥ እሾሃም ዛፍ፣ ብትፎክር በሰርግ ዋዜማ! ስለተቃውሞዋችን ይህን አንርሳ አህያ ቢጠፋው ደውላ ገልጦ አየ! ሰለ ጊዜ ምርጫችን ይህንን እናስምር ያለጊዜዋ የበቀለች ማሽላ፣ ወይ ለወፍ - ወይ ለወናፍ ንገሥ ቢሉት ዛሬ ሰንበት ነው አለ፣ ስለ ፕሬሳችን ይሄን በጥልቅ እንመርምር አፌ ዝም ብሎ እጄን ይጐራረሱበታል ስለሙስናችን ይህን እንፀልይ ካመጡ እንበላለን፣ ከሞቱ እንሰማለን፤ አለች የሌባ ማስት ስለ መልካም አስተዳደራችን ይህን እንበል ምን እንዳታደርግ ያሏትን በቅሎ፣ ሙጃ ላይ ያስሯታል ስለ ኢኮኖሚ መብታችን ይህን እንነቁጥ የደሀ ጀርባ በይሰጡኛል ያልቃል? ስለ ፖለቲካ ሥልጣን ይህን ምንጊዜም አንርሣ ጥፍሯን ሳትቆረጥ ቀለበት አደረጉላት ከላይ የርዕሰ አንቀጽ ፍሬ - ርዕስ ያደረግናቸው ተሰብስበው የነገ ምርጫችንን ይባርኩልን ዘንድ እንፀልያለን!!
ጊዮርጊስ እና ደደቢት በወሳኝ ምዕራፍ ላይ ናቸው
ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት ወደ ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌዴሬሽን ካፕ የሁለተኛው ዙር የማጣርያ ምእራፍ ለመግባት ነገ ወሳኝ የመልስ ጨዋታዎቻቸውን ያደርጋሉ፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፕ ተሳታፊ የሆነው ደደቢት ነገ በአዲስ አበባ ስታድዬም በመጀመርያ ዙር የመልስ ጨዋታ የሱዳኑን አልሼንዲ ያስተናግዳል፡፡ ከ2 ሳምንት በፊት ደደቢት የመጀመርያ ጨዋታውን ከአልሼንዲ ጋር በሱዳን አድርጎ 1ለ0 ተሸንፎ የነበረ ሲሆን ነገ በሜዳው ይህን ውጤት ለመገልበጥ 2ለ0 በላይ ማሸነፍ ይጠበቅበታል፡፡በኮንፌደሬሽን ካፑ የመልስ ጨዋታ ከደደቢት እና ከአልሼንዲ የሚያሸንፈው በሁለተኛ ዙር ሊገናኝ የሚችለው ከግብፁ ኢስማኤልያ እና ከማላጋሲው ቲኮ ቦኒ አሸናፊ ነው፡፡ ሁለቱ ክለቦች በመጀመርያ ጨዋታቸው ሲገናኙ 2ለ0 ያሸነፈው ኢስማኤልያ ነበር፡፡ በሌላ በኩል በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳታፊ የሆነው ቅዱስ ጊዮርጊስ ለመጀመርያ ዙር የመልስ ጨዋታ ከዲጆሊባ ጋር ለመፋለም ወደ ማሊ ዋና ከተማ ባማኮ ትናንት ተጉዟል፡፡
ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሁለት ሳምንት በፊት በሜዳው የማሊውን ዲጆሊባ 2ለ0 አሸንፎ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ የመልስ ጨዋታ ከቅዱስ ጊዮርጊስ እና ከዲጆሊባ የሚያሸንፈው በሁለተኛው ዙር ሊገናኝ የሚችለው ከግብፁ ዛማሌክ እና ከዲ.ሪ. ኮንጎው አኤስ ቪታ አሸናፊ ነው፡፡ ሁለቱ ክለቦች በመጀመርያ ጨዋታ ተገናኝተው 1ለ0 ያሸነፈው ዛማሌክ ነበር፡፡ የአፍሪካ ሻምፒየንስ ሊግ በአዲስ የውድድር አካሄድ ከ15 አመታት በፊት ከተጀመረ ወዲህ ኢትዮጵያን በመወከል ዘንድሮ 10ኛውን ተሳትፎ የሚያደርገው ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሁለተኛው ዙር ለማለፍ ተቸግሮ መቆየቱን ስለክለቡ የአህጉራዊ ውድድር ታሪክ በኢትዮፉትቦል ድረገፅ የቀረቡ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ የአፍሪካ ሻምፒየንስ ሊግ በአዲስ የውድድር አካሄድ ሲጀመር ተሳታፊ ሊሆን የበቃው ቅዱስ ጊዮርጊስ በመጀመሪያው ዙር ከውድድሩ የተሰናበተው በግብፁ ክለብ ዛማሌክ ተሸንፎ ነበር፡፡
ግብፅ ላይ 2ለ0 ተሸንፎ በመልሱ ጨዋታ አንድ አቻ ተለያይቶ 3ለ1 በሆነ ድምር ውጤት ተበልጦ ነበር ፡፡ ቀጣይ ተሳትፎውን ያገኘው ከ2 የውድድር ዘመናት በኋላ ነበር፡፡ በቅድመ ማጣሪያው የኡጋንዳውን ቪላ ካምፓላን 5ለ2 በሆነ ድምር ውጤት ረትቶ አለፈ፡፡ ከዚያ በኋላ በመጀመሪያው ዙር ከቡሩንዲው ክለብ ቪታሎ ተገናኘ፡፡ ከሜዳው ውጭ 2ለ2 አቻ ቢለያይም በሜዳው 2ለ1 ተሸንፎ በድምር ውጤት በቪታሎ ተበልጦ ወደቀ፡፡ በቀጣዩ የውድድር ዘመን ደግሞ በቅድመማጣርያው ነው ውድደሩን የተሰናበተው፡፡ ከኬንያ ተስካር ጋር ተገናኝቶ አዲስ አበባ ላይ 1ለ1 ኬንያ ላይ ደግሞ ያለግብ አቻ ተለያይቶ ከሜዳ ውጭ ባገባ በሚለው ህግ መሰረት ተስካር ሊያልፍ በቅቷል፡፡በ2003 እኤአ ላይ በሻምፒዮንስ ሊጉ የመሳተፍ እድል ባገኘበት ወቅትም ቅድመ ማጣሪያውን ማለፍ አልቻለም፡፡
በኡጋንዳ ክለብ አዲስ አበባ ላይ 3ለ1 ተሸንፎ ከሜዳው ውጭ 1ለ0 ቢያሸንፍም አላለፈም፡፡ በ2004 እኤአ ላይ በመጀመሪያ ዙር ከውድድሩ ሲሰናበት በሱዳኑ አልሂላል ኦምዱርማን ተሸንፎ ነበር፡፡ በመጀመሪያው ጨዋታ በሜዳውና ደጋፊው ፊት 2ለ1 ተሸንፎ ስለነበር ካርቱም ላይ አንድ አቻ መለያየቱ ሊያሳልፈው አልቻለም፡፡በ2006 እኤአ የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎው በመጀመሪያው ዙር የተገናኘው ከግብፁ ኢኤንፒፒአይ ጋር ነበር ፡፡ ከሜዳው ውጭ 0ለ0 በመለያየት በሜዳው ደግሞ 1ለ0 በማሸነፍ ወደ ሁለተኛው ዙር ገባ፡፡ ያጋጠመው የጋናውን ኸርትስ ኦፍ ኦክ ነበር፡፡ በሁለተኛው ዙር የመጀመሪያ ጨዋታ አዲስ አበባ ላይ 4ለ0 በሆነ ውጤት ሀርትስ ኦፍ ኦክን አሸነፈ፡፡ በመልሱ ጨዋታ ግን ያልተጠበቁ ክስተቶች ተፈጠሩ፡፡ በጊዮርጊስ ላይ በጋና ዋና ከተማ አክራ እንግልት ደረሰበት፡፡
የጨዋታው ዳኛ አወዛጋቢ ውሳኔዎችን አሳለፉ፡፡ ባለሜዳዎቹ 2ለ0 እየመሩ ተጨማሪ የፍፁም ቅጣት ምትም አገኙ፡፡ በዚህ ወቅት በደሉን መቋቋም ያልቻሉት የቅዱስ ጊዮርጊስ ተጫዋቾች የኦህንጃን ስታድየምን ሜዳን ጨዋታው ሳይጠናቀቅ አቋርጠው ወጡ፡፡ የውድድሩ አስተዳዳሪ ካፍ ውሳኔም ወደ ጋናው ክለብ አጋደለ፡፡ ቅ/ጊዮርጊስ ወድቆ ኸርትስ ኦፍ ኦክ እንዲያልፍ ተደረገ፡፡በተከታዩ የውድድር ዘመን በ7ኛው የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ቅዱስ ጊዮርጊስ በመጀመርያ ዙር የኮንጎ ብራዛቪሉን ኤቶል ዲ ኮንጎን በማስተናገድ 1ለ0 አሸነፈ፡፡ በመልሱ ጨዋታ ግን 2ለ0 ተሸነፉ ፡፡
ከዚህ በኋላ በቀጣዮቹ ሁለት የውድድር ዘመናት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ውስጥ በተፈጠረው ውዝግብ ምክንያት ፊፋ ሀገሪቱን ከማንኛውም ኢንተርናሽናል ውድድር በማገዱ ቅ/ጊዮርጊስም መሳተፍ በነበረበት ሻምፒዮንስ ሊግ ላይ በ2009 እኤአ ላይ ሣይሳተፍ ቀረ፡፡ በ2010 እኤአ ላይ ወደ የአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ውድድር ቅዱስ ጊዮርጊስ ተመለሰ፡፡ በቅድመ ማጣርያ የተደለደለው ከሱዳኑ ኤልሜሪክ ጋር ነበር፡፡ የመጀመሪያው ጨዋታ አዲስ አበባ ላይ ሁለቱ ክለቦች አንድ እኩል አቻ ተለያዩ፡፡ የመልሱ ጨዋታ በኤልሜሪክ ስታዲየም ሲደረግ ቅ/ጊዮርጊስን 3ለ1 ተሸንፎ ከውድድሩ ተሰናብቷል፡፡ ነገስ ምን ይገጥመው ይሆን?
የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ‹መለስ ዋንጫ› የመጀመርያ ዙር ተጠናቀቀ
የ2005 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ‹መለስ ዋንጫ› የመጀመርያ ዙር ትናንት የተጠናቀቀ ሲሆን ነገ በጊዮን ሆቴል በሚደረግ ስብሰባ አጠቃላይ ሂደቱ ሊገመገም ነው፡፡ የሊጉ ውድድር ዘንድሮ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ እና የዓለም ዋንጫ የማጣርያ ግጥሚያ እንዲሁም ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት በአህጉራዊ ውድድሮች በነበራቸው ተሳትፎ በተደጋጋሚ እየተቋረጠ ፉክክሩ ከመደብዘዙም በላይ፤ በተመልካች ድርቅ እና በየስታድዬሙ በሚያጋጥሙ የዲስፕሊን ግድፈቶችም አስቀያሚ ገፅታ የተላበሰ ነበር፡፡ የ2005 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ‹መለስ ዋንጫ› የመጀመርያ ዙር ሲጠናቀቅ እሰከ 13ኛ ሳምንት በተደረጉ 85 ጨዋታዎች 186 ጎሎች ከመረብ ሲያርፉ በሊጉ አንድ ጨዋታ በአማካይ 2.19 ጎሎች ሲመዘገቡ ቆይቷል፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ለስፖርት አድማስ በላከው መግለጫ እንዳመለከተው የሊጉ የመጀመርያ ዙር አፈፃፀም ነገ በግዮን ሆቴል ሲገመገም በስብሰባው ላይ የክለቦች የቦርድ ሰብሳቢዎች ወይም ፕሬዝዳንቶች እንዲሁም ስራ አስኪያጆቻቸው እንደሚሳተፉ ይጠበቃል፡፡
በሌላ በኩል የሃገር ውስጥ ተጨዋቾች ዝውውርን በተመለከተ አዲስ የዝውውር ወቅት እንደሚጀመር የፌደሬሽኑ ኢመርጀንሲ ኮሚቴ አሳውቋል፡፡ ኢመርጀንሲ ኮሚቴው መደበኛው የሃገር ውስጥ ተጨዋቾች የዝውውር መስኮት ከየካቲት 30 እስከ መጋቢት 15 መካሄዱን ገልፆ አዲሱ የዝውውር መስኮት ሁለተኛው ዙር ከተጀመረ በኋላ ለ15 ቀናት እንዲካሄድ ወስኗል፡፡ የ2005 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ‹መለስ ዋንጫ› ሁለተኛ ዙር ሚያዚያ 3 እንደሚጀመር ሲታወቅ አዲሱ የሃገር ውስጥ ተጨዋቾች የዝውውር መስኮት እሰከ ሚያዝያ 18 የሚካሄድ ይሆናል፡፡ በተያያዘ ዜና በፊፋ እውቅና የሚያገኝ የተጨዋቾች ወኪልነትን ለመስራት ለሚፈልጉ አመልካቾች ባለፈው ማክሰኞ ፈተና የተሰጠ ሲሆን ከፊፋ የመጣውን የፅሁፍ ፈተና 5 ሴት እና 15 ወንድ አመልካቾች እንደተፈተኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ባለፈው ሰሞን በአዳማ ከተማ በሚገኘው የአበበ በቂላ ስታዲየም አዳማ ከተማ እና መከላከያ ባደረጉት የሊግ ጨዋታ በተፈጠሩት የዲስፕሊን ግድፈቶች ላይ የሊግ ኮሚቴ ከውድድሩ አመራሮች በቀረበው ሪፖርት መሰረት ልዩ ልዩ መረጃዎችን በመመርመር ጉዳዩን አጣርቶ ውሳኔ መሰጠቱን ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በአዳማ ከተማና በመከላከያ ክለቦች መካከል በተደረገው የሊግ ጨዋታ ላይ በተፈጠሩ አለመግባባቶች እና የዲስፕሊን ግድፈቶች ግጥሚያው ለ20 ደቂቃ ተካሂዶ እንደተቋረጠ ይታወሳል፡፡ከኮሚሽነሩ እና ከ4ኛ ዳኛው በቀረበው ሪፖርት መሰረት ዋና ዳኛ ደረጃ ገብሬ ለመከላከያ ቡድን በሰጡት የፍፁም ቅጣት ምት አግባብነት ዙርያ ውሳኔያቸውን በመቀያየር በራሳቸው ላይ ሁከት በመፍጠር ወጥ አቋም ይዘው የዳኝነት ተግባራቸውን ባለመወጣታቸው የሚመለከተው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ዳኞች ኮሚቴ ውሳኔ እንዲሰጥበት መወሰኑን የሊግ ኮሚቴው መግለጫ አመልክቷል፡፡ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ኮሚቴ ስለጨዋታው መቋረጥ ከዕለቱ የውድድር አመራር አካላት በቀረበው ሪፖርት መሰረት በየአዳማ ከተማ ክለብ ተጨዋቾችና አመራሮች ጨዋታውን አንቀጥልም በማለት ለመጫወት ፍቃደኛ አለመሆናቸውን መገለፁን ጠቅሶ፤ ጨዋታው በእነሱ ምክንያት የተቋረጠ በመሆኑ፤ በኢትዮጵያ የእግር ኳስ ፌዴሬሽን የዲሲፕሊን መመሪያ እና የክለቦች የውድድር ደንብ መሰረት 0 ነጥብና 0 ግብ ተመዝግቦለት ክለቡ በፎርፌ ተሸናፊ እንዲሆን ተወስኗል፡፡
በተጨማሪም ቡድኑ ለፈጸመው ጥፋት በኢትዮጵያ የእግር ኳስ ፌዴሬሽን የዲሲፕሊን መመሪያ ብር 15 ሺህ ብር እስከ ሚያዚያ 9 ቀን 2005 ዓ.ም. 6፡00 ሰዓት ድረስ በቅጣት ገቢ እንዲያደርግ ተወስኗል፡፡ የአዳማ ከተማ ተጨዋች ዳኛውን ጠልፎ በመጣሉ፤ የአዳማ ቡድን አመራር ቡድናችን ጨዋታውን አይቀጥልም በማለት ጨዋታው እንዳይቀጥል እና ለጨዋታው መቋረጥ ምክንያት በመሆናቸው በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የዲሲፕሊን መመሪያ መሰረት የዲሲፕሊን ኮሚቴ ውሳኔ እንዲሰጥበት ተወስኗል፡፡ የአዳማ ከነማ ቡድን በጉዳዩ ላይ ያቀረበው የክስ አቤቱታ በተመለከተ የሊግ ኮሚቴው ባስተላለፈው ውሳኔ አንድ የቴክኒክ ክስ የሚመሰረትበትን መስፈርት ስላላሟላ ከደንብ ውጭ ተመዝግቦ የቀረበ የክስ አቤቱታ በመሆኑ ክሱ ውድቅ እንዲሆን መወሰኑንም አስታውቋል፡፡ በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ኮሚቴ የመከላከያ ቡድንን በተመለከተ ባሳለፈው ውሳኔ ክለቡ ጨዋታውን ለመቀጠል ፍቃደኛ ሆኖ እያለ የአዳማ ከነማ ቡድን ጨዋታውን ለመቀጠል ፍቃደኛ ባለመሆኑ ዳኛው ያሰናበተው እንደሆነ ገልፆ፤ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የዲሲፕሊን መመሪያ መሰረት በፎርፌ አሸናፊ ሆኖ 3 ነጥብና 0 ግብ እንዲመዘገብለት ወስኗል፡፡
“የዳንኤል ክብረት ዕይታዎች” 3ኛ አመቱን ያከብራል
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በተለያዩ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ባህላዊና ሃይማኖታዊ ጉዳዮች ዙርያ መጣጥፎች የሚያቀርብበት “የዳንኤል ዕይታዎች” የጡመራ መድረክ (Blog) የተመሠረተበት ሶስተኛ አመት ሚያዚያ 5 ቀን 2005 ዓ.ም በአዲስ አበባ አክሱም ሆቴል አዳራሽ ከቀኑ 7፡00 ሰዓት ጀምሮ በሚካሄድ ፕሮግራም እንደሚከበር ተገለፀ፡፡ በዕለቱ በሚካሄደው ፕሮግራም ላይ “የዳንኤል እይታዎች” ጡመራ ላይ የቀረቡ ጽሑፎች ቅኝት፣ የኢትዮጵያውያን ማህበራዊ ድረ ገፆች ዳሰሳ፣ የማህበራዊ ሚዲያ ህጋዊና ሥነ ምግባራዊ ሃላፊነት በሚሉና ተያያዥ ርዕሰ ጉዳዮች ዙርያ ጥናታዊ ጽሑፎች እንደሚቀርቡና ሰፊ ውይይት እንደሚካሄድም የፕሮግራሙ አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ትውልድን በመቅረጽ ለሀገርና ለህዝብ የሚበጁ በጐ ሥራዎች የሚያከናውኑና ሃሳብ የሚያመነጩ ግለሰቦችና ተቋማት እውቅናና ሽልማት እንደሚሰጣቸው ታውቋል፡፡ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት፤ ደራሲና የቤተክርስቲያን ተመራማሪ ሲሆን፤ 16 መፃሕፍትን በግሉ፣ ሶስት መፃሕፍትን ከሌሎች ጋር ለህትመት አብቅቷል፡፡ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ መጣጥፎችንም በጋዜጦችና መፅሄቶች ላይ አስነብቧል፡፡
“የጥበብ ዋርዲያ” ሥራ ሊጀምር ነው
ፊልሞች በህገወጥ መንገድ እንዳይገለበጡና እንዳይሰረቁ የሚከላከል “የጥበብ ዋርድያ” የተሰኘ ሶፍትዌር መስራቱን የገለፀው ሴባስቶፖል ሲኒማ፤ ከሚቀጥለው ወር ጀምሮ ሥራ ላይ እንደሚውል ሰሞኑን አስታወቀ፡፡ ሶፍትዌሩ ፊልም ሰሪዎች ፊልም በሚያሳዩ ወቅት “ይሰረቅብኛል” ከሚል ስጋት ያድናቸዋል ተብሏል፡፡
ባለፈው ረቡዕ በሴባስቶፖል ሲኒማ መግለጫ የሰጡት ሶፍትዌሩን ያዳበሩ ባለሙያዎች እንዳሉት፤ ሶፍትዌሩ አንድ ፊልም በሕገወጥ መንገድ ሳይገለበጥ በአንድ ጊዜ ብዙ ቦታ እንዲታይ ያስችላል ብለዋል፡፡ ፊልሙ ስንት ጊዜ እንደታየ ጭምር ለማወቅ ያስችላል የተባለው ሶፍትዌር፤ ፊልሞቹን በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ በማስቆለፍ ከስርቆት ስጋት ነፃ እንደሚያወጣ ተገልጿል፡፡
ራፕሮች ወደ ንግዱ እያዘነበሉ ነው
ታዋቂ ራፕሮች ከተለያዩ ኩባንያዎች ጋር በሚሰሯቸው የስፖንሰርሺፕ ውሎች እና ማስታወቂያዎች ሃብታቸውን እያሳደጉ መሆናቸውን ሴለብሪቴኔትዎርዝ አስታወቀ፡፡ የራፕ ሙዚቃን መጫወት፤ ማሳተም እና የተለያዩ የሙዚቃ ዝግጅቶችን በማቅረብ የሚገኘው ገቢ እጅግ እያነሰ መምጣቱን ዘገባው አመልክቷል፡፡ ሴሌብሪቲ ኔትዎርዝ ከሙዚቃ ውጭ የእውቅ ራፕሮች ገቢ በጣም እያደገ መምጣቱን ያመለከተው የ2013 የዓለም ራፕሮች የሃብት ደረጃን ሰሞኑን ይፋ ሲያደርግ ነው፡፡ ሲን ኮምበስ ወይም ፒዲዲ ባለፈው አንድ አመት በሃብቱ ላይ ተጨማሪ 80 ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝቷል ያለው ሴሌብሪቲ ኔትዎርዝ 580 ሚሊዮን ዶላር አስመዝግቦ በአንደኝነት እንደሚመራ ገልጿል፡፡
ለፒዲዲ ሃብት ማደግ ከአልኮል መጠጦች አንዱ ከሆነው የቮድካ አልኮል ብራንድ ሲሮክ የተባለ ምርት ላይ በሚሰራው ንግድ ሽያጭ በመድራቱ ነው ያለው ሴሌብሪቲ ኔትዎርዝ ራፕሩ ይህን ኩባንያ ቢሸጥ እስከ 150 ሚሊዮን ዶላር የተጣራ ገቢ ሊያገኝ እንደሚችል ጠቁማል፡፡ ባለፈው አንድ ዓመት በሃብቱ ላይ ተጨማሪ 25 ሚሊዮን ዶላር የጨመረው ጄይዚ በ500 ሚሊዮን ዶላር የሃብት ግምቱ ሁለተኛ ደረጃ ሲይዝ፤ ቢትስ ባይ ድሬ በተባለ የጆሮ ማዳመጫ ምርቱ ያለፈውን አንድ አመት 100 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ሰብስቦ የሃብት መጠኑን 360 ሚሊዮን ዶላር ያደረሰው ዶር ድሬ ሶስተኛ ሆኗል፡፡ ሌሎች ራፕሮች ማስተር ፒ በ350 ሚሊዮን ዶላር፤ ሴንት በ260 ሚሊዮን ዶላር፤ በርድ ማን በ150 ሚሊዮን ዶላር፤ ኤሚነም በ140 ሚሊዮን ዶላር፤ ስኑፕ ዶግ በ130 ሚሊዮን ዶላር፤ አይስ ኪውብ በ120 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም ሊል ዋይኔ በ110 ሚሊዮን ዶላር የሃብት መጠን እስከ 10 ያለውን ደረጃ አግኝተዋል፡፡
21ኛ “ግጥም በጃዝ” ረቡዕ ይቀርባል
አንጋፋና ወጣት ከያንያን የግጥም፣ የቅንጭብ ትያትር፣ የወግና ሌሎች የኪነጥበብ ሥራዎቻቸውን በጃዝ ሙዚቃ ታጅበው የሚያቀርቡበት “ግጥም በጃዝ” ሃያ አንደኛ ዝግጅት የፊታችን ረቡዕ ከቀኑ 11፡30 ሰዓት እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ ገለፁ፡፡ ባሁኑ ዝግጅት ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፣ ሞገስ ሀብቱ፣ ምስራቅ ተረፈ፣ በረከት በላይነህ፣ ግሩም ዘነበ ግጥሞቻቸውን ሲያቀርቡ፣ ወ/ሮ ሰሎሜ ታደሰ ዲስኩር እንዲሁም ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ወግ ያቀርባሉ፡፡