Administrator

Administrator

        በአፍሪካ ፖለቲካዊና የውጭ ግንኙነት ጉዳዮች ላይ በርካታ መፅሃፍትን በመፃፍ የሚታወቁት የፖለቲካ ተመራማሪው ዶ/ር ዴቪድ ሆይሌ “አለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ የአውሮፓ ጓንታናሞ ቤይ?” የተሰኘ መፅሃፍ ለንባብ አበቁ።
ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤቱ አፍሪካን ዳግም በቅኝ ግዛት ለመያዝ ታልሞ የተቋቋመ አውሮፓዊ ፍ/ቤት ነው የሚሉት ዶ/ር ዴቪድ፤ አውሮፓ ከ120 ዓመታት በኋላም በተቋሙ አማካይነት አፍሪካውያንን ለመዝረፍ እየሞከረች ነው ብለዋል።
“አውሮፓውያን፤አፍሪካንና ሌሎች ታዳጊ ሃገራትን በዘመናዊ ባርነት ለመግዛት እንዲሁም  ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ሉዓላዊነታቸውን ለማሳጣት የሚጠቀሙበት መሳሪያ ነው” በማለት መፅሃፉ ዓለም አቀፉን የወንጀለኞች ፍ/ቤት ያብጠለጥላል።
ባለፈው ሳምንት  በመዲናችን በተካሄደው 22ኛው የአፍሪካ መሪዎች ጉባዔ ላይ የተመረቀውን የዶ/ር ዴቪድ መፅሃፍ ያሳተመው የአፍሪካ የጥናትና ምርምር ማዕከል እንደሆነ ታውቋል። የመጽሐፉ ዋጋ  14.99 ዶላር  ነው፡፡ ዶ/ር ዴቪድ ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ አምስት መፅሃፍትን ያሳተሙ ሲሆን በቅርቡም የአሁኑ መፅሃፍ ተከታይ ለንባብ እንደሚበቃ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በኢትዮጵያ የኢራን ኢምባሲ የባህል ክፍል የሚዘጋጀው አመታዊው የኢራን የፊልም ፌስቲቫል ካለፈው ሰኞ ጀምሮ በብሄራዊ ትያትር ተካሄደ፡፡
የኢራንን እስላማዊ አብዮት 35ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የተከናወነው ይህ የፊልም ፌስቲቫል፣ የሁለቱን አገራት ባህላዊ ግንኙነት የማጠናከርና የኢራን የፊልም ኢንዱስትሪ የደረሰበትን ደረጃ የማስተዋወቅ አላማ እንዳለው በኢትዮጵያ የኢራን አምባሳደር አሊ ባህሪኒ በፌስቲቫሉ መክፈቻ ላይ ተናግረዋል፡፡ የኢራን ኢምባሲ የባህል ክፍል፣ በሁለቱ አገራት መካከል የተፈረመውን የባህል፣ የትምህርትና የሳይንስ ትብብር መሰረት በማድረግ የኢትዮጵያን ፊልም ለማሳደግ የሚያግዙ ስራዎችን እንደሚያከናውንም ገልጸዋል፡፡
ለሶስት ተከታታይ ቀናት በተካሄደው በዚህ የፊልም ፌስቲቫል ላይ፣ ‘ኤም ፎር ማዘር’፣ ‘ዘ ሶንግስ ኦፍ ስፓሮውስ’ እና ‘ኦን ፉት’ የተሰኙ፣ በአለማቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ያገኙ ስኬታማ የኢራን ፊልሞች ለእይታ በቅተዋል፡፡

          በኢትዮጵያ እግር ኳስ የሰሞኑ አበይት መነጋገርያ አጀንዳ የ62 ዓመቱ ሰውነት ቢሻው ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት መነሳታቸው ነበር፡፡ ሰውነት ከሃላፊነታቸው ከተነሱ በኋላ ለሱፕር ስፖርት አስተያየት ሲሰጡ ለስንብታቸው በፌደሬሽን ላይ ያቀረቡት ቅሬታ የለም፡፡ በስንብታቸው ማግስት ከዋልያዎቹ በኋላ ዋንኛው ትኩረታቸው ከቤተሰባቸው ጋር ማሳለፍ እንደሆነ የተናገሩት ሰውነት ቢሻው አሰልጣኝነት የማይተውት ሙያቸው እንደሆነ በመግለፅ በአገር ውስጥ የሚወዳደሩ ክለቦችን ወይንም በአፍሪካ ደረጃ ብሄራዊ ቡድኖችን ለማሰልጠን ፍላጎት እንዳላቸው ገልፀዋል፡፡
‹‹የአሰልጣኝነት ስራ አስቸጋሪ እና ምስጋና የሚያሳጣ ነው፡፡ የምትወደደው በከፍተኛ ደረጃ ውጤታማ ስትሆን ብቻ ነው፡፡ በህይወት ውስጥ በተለያዩ  ሁኔታዎች ሊያጋጥሙ የሚችሉ ውጣውረዶችን በፀጋ መቀበል ያስፈልጋል፡፡ መባረሬ ድንገተኛ ዜና አልሆነብኝም። በደቡብ አፍሪካ ከተደረገው የቻን ውድድር ስንመለስ ከመቅፅበት ሁኔታዎች ሲቀየሩ አስተውያለሁ፡፡ ከስንብቱ በፊት ተዘጋጅቶ በነበረው የግምገማ መድረክ፤ በብሄራዊ ቡድኑ የነበሩ ችግሮችን አስረድቼ ነበር፡፡ ይሁንና ቡድኑ በቻን ተሳትፎው ለገጠመው ውጤት ማጣት እኔ ምክንያት እንደሆንኩ አስቀድሞ የተወሰነ ነበር፡፡ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በነበረኝ ሃላፊነት ባስመዘገብኳቸው ውጤቶች እኮራለሁ፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ላገኛቸው ስኬቶች 100 ፐርሰንት ብቃቴን በመስጠት አገልግያለሁ፡፡ ›› በማለት አሰልጣኝ ሰውነት ለሱፕር ስፖርት የስንብት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡
ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከተሰናበቱ በኋላ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው  የት ይሄዳሉ የሚል ጥያቄ መነሳት ጀምሯል፡፡ አሰልጣኙ በዓለም ዋንጫ የመጨረሻ የደርሶ መልስ ትንቅንቅ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በናይጄርያ ከተሸነፈ በኋላ በማግስቱ ወደ ጊኒ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ሊሄዱ ነው ተብሎ ተወርቶ ነበር። በዚሁ ጊዜም አሰልጣኙ አገሬን ትቼ የትም አልሄድም፤ በብዙ ሺ ዶላሮች እንድሰራላቸው የጠየቁኝ ነበር ግን አልተቀበልኳቸውም፤ ፍላጎቴ በኢትዮጵያ መቀጠል ነው ብለው አስተባብለው ነበር፡፡ ከሳምንቱ አጋማሽ ስንብታቸው በኋላ ደግሞ ከቦትስዋና እግር ኳስ ፌደሬሽን ጋር ለአዲስ ስራ ግንኙነት ፈጥረዋል እየተባለ ነው፡፡
የዛሬ ሳምንት ቅዳሜ እለት በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ከተደረገው የግምገማና የምክክር መድረክ ከሁለት ቀናት በኋላ የእግር ኳስ ፌደሬሽን ስራ አስፈፃሚ  ከቀኑ 9 ሰዓት እስከ ምሽቱ 4 ሰዓት ልዩ ስብሰባ አድርጓል። ስብሰባው በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና በረዳት አሰልጣኞቻቸው  ቀጣይ ሁኔታ ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ ከዚሁ የስራአስፈፃሚ ስብሰባ በኋላ በማግስቱ ረቡዕ ካሳንቺስ በሚገኘው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፅህፈት ቤት ስራ አስፈፃሚው አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ ጠርቷል። ከቀኑ 10 ሰዓት የነበረው ጋዜጣዊ መግለጫ በጣም በተጣበበ ጊዜ ቢጠራም በርካታ የስፖርት ጋዜጠኞች መገኘታቸውን ያደነቁት የፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ መግለጫው በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኞች  ስንብት ላይ ያተኮረ መሆኑን በይፋ ገልፀዋል። ከኤሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል የግምገማ እና የምክክር መድረክ፤ ከማክሰኞው የስራ አስፈፃሚ ስብሰባ እስከ ረቡዕ ጋዜጣዊ መግለጫ የነበሩትን ሁኔታዎች ከዚህ በታች እንደቀረበው ተዳስሰዋል፡፡
ሰውነትና ዋልያዎቹ በባለድርሻ አካላት ሲገመገሙ
ከሳምንት በፊት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን በተዘጋጀው የግምገማ እና የምክክር መድረክ ላይ ከ59 በላይ የስፖርት ጋዜጠኞች መገኘታቸው ያለምክንያት አልነበረም፡፡ በእለቱ  በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና በብሄራዊ ቡድናቸው ላይ የሚደረገው ግምገማ የመጨረሻ ውጤት የሚዲያውን ትኩረት የሳበው ጉዳይ ነበር፡፡ በሙሉ ቀን በተካሄደው የግምገማ እና የምክክር መድረክ ላይ የስፖርት ኮሚሽን ተወካዮች፤ የሙያ ማህበራት ተወካዮች፤ የክለብ አመራሮች፤ የእግር ኳስ ፌደሬሽን ስራ አስፈፃሚ አባላትና  ባለሙያዎችና በስፖርቱ ላይ ያገባኛል የሚሉ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ በመክፈቻ ንግግር ባስጀመሩት በዚህ ስብሰባ ላይ በጠዋት ፕሮግራም የፌደሬሽኑ ዋና ፀሃፊ የአስተዳደር ዘርፍ ካቀረቡት ሪፖርት በኋላ በቴክኒኪ ኮሚቴ ሰብሳቢው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን የነበረውን ተሳትፎ በቁጥሮች የመዘነ ግምገማ ተሰጥቷል፡፡ በመቀጠል የቀረበው ደግሞ የቻን ተሳትፎ እንዴት እንደነበር የሚያብራራ የሰውነት ቢሻው መግለጫ ነበር፡፡ በእለቱ የነበሩ ጋዜጠኞች እነዚህ መግለጫዎች ሲቀርቡ ተከታትለዋል፡፡ የአስተዳደር ዘርፉ ሪፖርት የ2 ዓመት ተኩል ስራን በአጭሩ የተነተነ ነበር፡፡ ሪፖርቱ በሰውነት ቢሻው ዘመን የነበረው  ብሄራዊ ቡድን አጠቃላይ የአስተዳደር እና የፋይናንስ ሂደት በአጭሩ መግለፁን የታዘቡ አንዳንድ ጋዜጠኞች የአሰልጣኙ መሰናበት ፍንጭ ነው ብለው ነበር፡፡ በአንፃሩ የሚዲያ ባለሙያዎች በቴክኒክ ኮሚቴው ግምገማ ብሄራዊ ቡድኑን በመዘኑ በቁጥሮች መወሳሰብ ግራ ተጋብተዋል፡፡ የቴክኒክ ኮሚቴው አሰልጣኙን ከውድድር በኋላ ከመተቸት ከውድድሩ በፊት በቂ መረጃ  በመስጠት ለምን አልሰራም በሚል ቁጭት ብዙዎች ግምገማውን አልተማረኩበትም፡፡ ከዚያ በኋላ ግን የዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው አስገራሚ ማብራርያን ሁሉም ባለድርሻ አካል በትኩረት አዳምጦታል፡፡ ሰውነት በግምገማው መድረክ ያቀቡትን መግለጫቸውን ሲጨርሱ ከብሄራዊ ቡድን ጋር በመስራት ለመቀጠል ያላቸውን ፍላጎት በመግለፅ ነበር፡፡ ለጋዜጠኞች ከአሰልጣኙ ማብራርያ ቀልባቸውን የወሰደው በብሄራዊ ቡድኑ ውጤት ማጣት ተጠያቂ ነኝ ብለው በልበሙሉነት መናገራቸው ነበር፡፡  ይሁንና ዓላማቸው የነበሩትን ልጆች በመያዝ እና አዳዲስ ተተኪዎችን በመፈለግ ብሄራዊ ቡድኑን ለቀጣዩ የሞሮኮው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ማሳለፍ እንደሆነ ሲናገሩ ግን ማጉረምረም ነበር፡፡  ፌደሬሽኑ የግምገማ እና የምክክር  መድረኩን ያዘጋጀው በቅርቡ ይፋ ለሚያደርገው የ5 ዓመት መሪ ስትራቴጂክ እቅድ ግብዓት የሚሆኑ ሃሳቦችን ለማግኘት አስቦ መሆኑን በመግለፅ ሚዲያዎች በቡድን ለሚደረገው ምክክር እንዲሳተፉ ጋብዞ ነበር። ጋዜጠኞች በመድረኩ መሳተፋቸው ተገቢ አለመሆኑን አምነውበት ሳይሳተፉ ቀርተዋል፡፡
በእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ዋና ፀሃፊ አቶ ይግዛው በቀረበው የአስተዳደር ዘርፍ ሪፖርት መንግስት በስፖርቱ እየተጫወተ ያለውን ወሳኝ ሚና ጎልቶ ወጥቷል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ባለፉት ሁለት ዓመታት ተኩል በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ እና ዋና ውድድር፤ በዓለም ዋንጫ 3 ዙር የማጣርያ ምእራፎች፤ በሴካፋ እና በቻን ውድድሮች በነበረው ጉዞ ፌደሬሽኑ በአስተዳደራዊ ዘርፉ ካከናወናቸው ተግባራት የትጥቅ ድጋፎች እና ማበረታቻ ሽልማቶች ዋናዎቹ ነበሩ፡፡ ዋና ፀሃፊው አቶ ይግዛው ለአሰልጣኞች፤ ለተጨዋቾች፤ ለቡድን መሪዎች፤ ለልዑካኖች እና ልዩ ልዩ አስተዋፅኦ ላደረጉ ሰዎች በድምሩ 14 ሚሊዮን 875ሺ ብር ወጭ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡ ዋና ፀሃፊው አልገለፁትም እንጂ ብሄራዊ ቡድኑ በነበረው ስኬት በስፖንሰርሺፕ፤ በገቢ ማሰባሰብ እና በተለያዩ እንቅስቃሴዎች የተገኘው ብር ከ80 ሚሊዮን ብር በላይ ነበር፡፡ ባለፈው ሁለት ዓመት ተኩል ብሄራዊ ቡድኑን በስፖርት ትጥቆች አቅርቦት አለመቸገሩን  የገለፁት ዋና ፀሃፊው ፤ ለብሄራዊ ቡድኑ ከፌደራል ስፖርት ከ1060 በላይ የተለያዩ ትጥቆችን፤ ከኦሎምፒክ ኮሚቴ 236 ቱታዎች መገኘቱን በመጥቀስ መንግስት በፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን በኩል   ለብሄራዊ ቡድኑ የማበረታቻ እና የምስጋና  ድጋፎችን በመስጠት የነበረው ትኩረት የሚመሰገን ነውም ብለዋል፡፡ በብሄራዊ ቡድኑ ስኬት የገቢ ምንጮቹን ያሰፋው ፌደሬሽኑ 1116 የስፖርት ቱታዎች ከ886ሺ በላይ በማውጣት ገዝቷል ፤ ብሄራዊ ቡድኑ በልምምድ ስፍራ እንዳይቸገር፤ በመኝታ እና በምግብ  ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት ሲያገኝ እንደነበርም  ዋና ፀሃፊው አቶ ይግዛው ገልፀዋል፡፡ በአስተዳደራዊ ዘርፍ የተፈጠረው ችግር የቡድን መሪዎች በየጊዜው እና በዘፈቀድ ሲቀያየሩ ከመቆየታቸው በተያያዘ እንደነበር ዋና ፀሃፊው አቶ ይግዛው በሪፖርታቸው አንስተዋል፡፡  ይሄው ዝርክርክ የፌደሬሽን አሰራር ታሪካዊ ቀውስ አስከትሏል፡፡ በዓለም ዋንጫ ማጣርያ ብሄራዊ ቡድኑ  በቢጫ ካርድ ቅጣት መሰለፍ ያልነበረበት ተጨዋች አጫውቶ በሰራው ጥፋት ለ3 ነጥብ መቀነስና ለገንዘብ ቅጣት መብቃቱ በአስተዳደር ዘርፉ የታየ የአሰራር ችግር  ነበር ብለዋል፡፡
“በቻን ውድድር ኢትዮጵያን ወክሎ የቀረበው የሰውነት ቡድን ፋውል የሚያበዛ፤ የግብ እድሉን የማይጠቀም፤ የአካል ብቃት ችግር የታየበት፤ በስነልቦና ያልጠነከረ፤ በደንብ ያልተዘጋጀ ነበር”  በማለት አሰልጣኙን በመተቸት የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ በግምገማው መድረክ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን የነበረውን ተሳትፎ በቁጥሮች ላይ በተመሰረተ ሪፖርት ፈትሸዋል ፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ በቻን ተሳትፎው በመብቃቱና በአህጉራዊ መድረክ ያለበትን ደረጃ በማሳየቱ ተጠቃሽ ውጤት መሆኑን የገለፁት ባለሙያው ለወጣቶች መነቃቃት የነበረው አስተዋፅኦ ትልቅ ጥንካሬ እንደሆነና የዜጎች መነጋጋርያ አጀንዳ መሆኑ ይደነቃል ብለዋል፡፡ የብሄራዊ ቡድኑ ድክመቶች በሁለት ነጥቦች እንደሚጠቃለሉ የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ ሲያስረዱ፤ የመጀመርያው በቻን ተሳትፎ ዋና አሰልጣኙ እና ረዳቶቻቸው ለወጣት እና ተተኪ ተጨዋቾች እድል አለመስጠታቸው በብሄራዊ ቀጣይ እድገት ተፅእኖ የሚፈጥር መሆኑን ባለመረዳት ነው ብለው፤  በሌላ በኩል የብሄራዊ ቡድኑ የተፎካካሪነት ብቃት በውጤት የታጀበ አለመሆኑ በግልፅ ከብዙ ችግሮች ጋር ታይቷል ብለዋል፡፡
የቴክኒክ ኮሚቴው ግምገማ  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን ተሳትፎው ከሊቢያ፤ ከኮንጎ እና ከጋና ጋር ባደረጋቸው ጨዋታዎች ከ3ቱ ቡድኖች በድምር የሚበልጥ ፋውል እንደሰራ፤ የግብ እድሎችን መጠቀም እንዳልቻለ፤ በኳስ ቅብብል ረገድ ውጤታማ ያልሆኑ እንቅስቃሴዎችን እንዳበዛ፤ በአጨዋወቱ ኳስ ወደ ኋላ በመመለስ መጥፎ አዝማሚያ እንዳሳየ፤ በመከላከል ላይ የጥንቃቄ ጉድለት እና ድክመት እንዳለበት፤ ኳስን በጭንቅላት መግጨት እና የተቃራኒ ቡድን ኳሶችን ከአደጋ ነፃ እንደማያወጣ፤ በመስመር ብዙም እንደማይጫወት አመልክቷል። የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ በአጠቃላይ አሰልጣኞች ለብሄራዊ ቡድን በመረጧቸው ተጨዋቾች መሄድ የሚገባቸውን እድል ነፍገው የማይገባቸውን ማሰለፋቸው ዋና ስህተት እንደነበር ሲገልፁ፤ የተጨዋቾች የአካል ብቃት  አለመሟላትና ለስነልቦና ችግሮች መጋለጥ የቡድኑን አቅም ያቃወሱ ምክንያቶችእንደነበሩም ተረድተናል ብለዋል፡፡ አሰልጣኞች ቡድኑን በብቃት እንዳላዘጋጁ፤ ለዝግጅታቸውም ከክለቦች ጋር በቅንጅት ስለማይሰራ በቡድኑ ብቃት ላይ ተፅእኖ መፍጠራቸውንም የቴክኒክ ኮሚቴው ግምገማ አብራርቷል፡፡
ለሰውነት ምስጋና ይግባቸው
የፌደሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ እንደገለፁት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና ረዳቶቻቸው ቡድኑን ተረክበው ባገለገሉበት ባለፈው ሁለት ዓመት ተኩል እግር ኳሱን ያነቃቁ በርካታ ውጤቶች እና ለውጦች ተመዝግበዋል፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ከ31 ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ መብቃቱ  የመጀመርያው ድንቅ ስኬት እና አበይት የታሪክ ምእራፍ ነበር፡፡ ለ20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ እስከመጨረሻው የማጣርያ ምዕራፍ በመጓዝ ብሄራዊ ቡድኑ ከአፍሪካ 10 ምርጥ ቡድኖች ተርታ መግባቱም ይታወሳል፡፡  በአፍሪካ አገራት የእግር ኳስ ሻምፒዮንሺፕ ቻን ውድድር ኢትዮጵያ ለመጀመርያ ጊዜ መሳተፏም ተጠቃሽ ስኬት ነበር፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ባለፈው ሁለት ዓመት ከመንፈቅ ባስመዘገበው ውጤት በ2015 የአፍሪካ ዋንጫ ያለቅድመ ማጣርያ በቀጥታ ለምድብ ማጣርያ የመወዳደር እድልም አግኝቷል፡፡  
አቶ ጁነዲን ባሻ ባለፈው ሁለት ዓመት ተኩል የተገኘውን ስኬት ባጠቃለለ ንግግራቸው ‹‹ ለብዙ ዘመናት ብሄራዊ ቡድኑ ብዙ ጎል የሚገባበት፤ ተከታታይ ሽንፈቶችን የሚያስተናግድ፤ እናሸንፋለን ብለን በአዕምሯችን እንዳናስብ ያደረገን ነበር፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውና መላው ቡድናቸው ይህን የቀየረ ውጤት አስመዝግበዋል፡፡ የኢትዮጵያን ህዝብ የእግር ኳስ ስሜት አነቃቃትዋል፤ ወደ ስታድዬም  እንዲመጣ አድርገዋል፤ ኢትዮጵያ ታሸንፋለች ተብሎ መታሰብ እንዲጀምር አስችለዋል፡፡  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ማልያ ከዳር እስከዳር እንዲለበስም ምክንያት ሆነዋል፡፡›› በማለት  ምስጋና አቅርበዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በኢትዮጵያ እግር ኳስ በፈጠሩት መነቃቃት እንደ ብሄራዊ ጀግና የሚታዩ ታላቅ ሰው መሆናቸውን በድፍረት መናገር ይቻላል፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ከፍተኛውጤት አላቸው። በ50ሺህ ብር ወርሃዊ ደሞዛቸው ከፍተኛው ተከፋይ ነበሩ።
በሰውነት የስራ ዘመን በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ትልቁ ስኬት ከመመዝገቡም በላይ የአገሪቱ የእግር ኳስ ደረጃ ተሻሽሏል፤ ከዋልያዎቹ መካከል አንዳንዶቹ ወደ 6 የተለያዩ አገራት ወደ የሚገኙ ክለቦች በመሰማራት በዝውውር ገበያው ተፈላጊነታቸው ጨምሯል፡፡
የሰውነት መሰናበቻ ምክንያቶች
ስራ አስፈፃሚው በዋና አሰልጣኙ ሰውነት ቢሻው እና በረዳቶቻቸው ለተገኙ ውጤቶች ክብርና ምስጋና እንደሚገባ ቢገልፅም በብሄራዊ ቡድኑ ቀጣይ ጉዞ ላይ ባደረገው ልዩ ስብሰባ የተገኘውን ውጤት ለማስቀጠል እንቅፋት የነበሩ ድክመቶችን መርምሯል፡፡ በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የሚመራው ብሄራዊ ቡድን ከናይጄርያ ጋር ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ ባደረጋቸው ሁለት ጨዋታዎች የባከኑ እድሎች ነበሩ፡፡ ከዚያም ኬንያ ባዘጋጀችው የሴካፋ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ ቡድን ለዋንጫ ተጠብቆ ከምድቡ በጊዜ የተሰናበተበት ሁኔታም ብዙ ጥያቄዎችን ፈጥሯል። በመጨረሻም  በደቡብ አፍሪካው የቻን ውድድር ቡድኑ በነበረው ተሳትፎ ደካማ አቋም ማሳየቱ እና የፉክክር ደረጃው ኋላቀር መሆኑ መረጋገጡ ሁሉንም ያሳሰበ ነበር።  ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ብሄራዊ ቡድን ዳግም ወደሽንፈት መመለሱን የፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ሲታዘብ ቆም ብሎ ማሰብ እንዳስፈለገው የተናገሩት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ የኢትዮጵያ እግር ኳስ በቀጣይ ወዴት ያመራል፤ መንግስት እና ህዝብ ከስፖርቱ ምን ለውጥ ይፈልጋሉ የሚለውን መክረንበት ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና ረዳቶቻቸው በብሄራዊ ቡድኑ ያላቸው ቆይታ ማብቃት እንዳለበት ከውሳኔ ላይ ደርሰናል ብለዋል፡፡
አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ከስራ እንደተሰናበቱ የተገለፀላቸው   በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ሃላፊዎች፤ የሚዲያ ባለሙያዎች እና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት የግምገማ መድረክ ላይ በሃላፊነታቸው ስለመቀጠል ፍላጎታቸው ከተናገሩ 3 ቀናት በኋላ ነበር፡፡ አሰልጣኞቹ መሰናበታቸውን ካወቁ በኋላ ውይይት ተደርጎ በተሰራው ሁሉም መደሰቱን፤ ግንኙነታቸው እንደሚቀጥል፤ ከስፖርቱ ጎን በመሆን እንደሚቀጥሉ ቃል መግባታቸው ተነግሯል፡፡
‹‹ሰዎች ጥሩ ይሰራሉ፡፡ ጊዜዎች ይቀያየራሉ፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና ረዳቶቻቸው በዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ደርሶ መልስ ፍልሚያ ከናይጄርያ ጋር፤ በሴካፋ እና በቻን ውድድሮች ይዘው በቀረቡት  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የማሸነፍ ስሜት ቀነሰ፤ የውጤት ማጣት ተከታታለ፤ በእርግጥ ተጨዋቾችም አሰልጣኞችም በጨዋታዎቹ የተቻላቸውን ሁሉ አድርገዋል፡፡ በክለቦች መካከል ያለው ውድድር አለማደጉ፤ በታዳጊዎች ላይ የሚሰሩ ተግባራት ያልጠነከሩ መሆናቸው፤ እና የአደረጃጀት እና የአሰለጣጠን ብቃት አለማደግ ለብሄራዊ ቡድኑ ድክመት የሚጠቀሱ ምክንያቶች ናቸው፡፡ የውጤት ማጣቱ አዝማሚያ የመጣው ባለንበት ልክ እና ደረጃ ነው። እግር ኳስ ያለበትን ደረጃ ቆም ብለን ማሰብ ነበረብን ›› በማለት ለታሪካዊው ውሳኔ ያደረሱ ዝርዝር ሁኔታዎችን አቶ ጁነዲን ባሻ ገልፀዋል፡፡
 በፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ በኩል ብሄራዊ ቡድኑ በመቀጠል በ2015 በሞሮኮ ለሚዘጋጀው የአፍሪካ ዋንጫ እንዲያልፍ ይፈለጋል፡፡  በታዳጊ እና ወጣት  ቡድኖች አህጉራዊ ውድድሮች ንቁ ተሳታፊ የመሆን ፍላጎትም አለ። የስፖርቱ ባለድርሻ አካላት ለለውጥ ተነሳስተው በዘላቂ ልማትና የእድገት ሂደት  እንዲሰሩ የማስተባበር እቅድም አለ፡፡ በአጠቃላይ የአሰልጣኝ ሰውነት ስንብት ስራውን ከጀመረ 4 ወራት የሆነው የፌዴሬሽን አመራር አዲስ የለውጥ ምእራፍ መክፈቱን ያበሰረበት ነበር፡፡
የአሰልጣኞቹ የኮንትራት ውል መቋረጡ ትልቅ ውሳኔ በመሆኑ በግልፅ መታወቅ አለበት ያሉት ጁነዲን ባሻ፤ አሰልጣኞች ስራቸውን ራሳቸው አልለቀቁም ወይም በክፉ ስሜት አልተሰናበቱም ብለዋል፡፡ ዋና አሰልጣኙና ረዳቶቻቸው በማንኛውም የሰራተኛ ህግ መሰረት ስንብታቸው እንደሚከናወን የገለፁት የፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት በክብር እና በምስጋና ይሸኛሉ እንጂ የካሳ ክፍያ የላቸውም ብለዋል፡፡ የስራ አስፈፃሚው አሰልጣኞቹን ለመቀየር መወሰኑን በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ሲገልፅ ሌላው የፌደሬሽን ዝርክርክ አሰራርም ተጋልጧል፡፡ የአሰልጣኞቹ የቅጥር ኮንትራት ጉዳይ ነው፡፡ የአንዱ በጥቅምት፤ የሌላው በህዳር የሌላው በታህሳስ ውል የሚያበቃበት ነበር ያሉት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ የቅጥር ኮንትራት በግልፅ የሚታወቅ መሆን ቢኖርበትም አሰልጣኞቹ ኮንትራታችሁ አልቋል ብለንና ኮንትራታቸውን አቋርጠን ለማሰናበት ያልፈለግነው፤ የቡድኑን የስራ ስሜት ላለማመሳቀል እና ላለመረበሽ በመወሰናችን ነበር ብለዋል፡፡ አሁን በስልጣን ላይ ያለው ፌደሬሽን ሃላፊነቱን ከተረከበ ከ3 ቀናት በኋላ ብሄራዊ ቡድኑ ወደ ዓለም ዋንጫ ለማለፍ የደርሶ መልስ ማጣርያውን ከናይጄርያ ጋር በአዲስ አበባ ይጀምር ነበር። በሴካፋና በቻን ውድድሮች ከዚያ በኋላ  በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ መደረጋቸውን በማገናዘብ ይሆናል፡፡ ሆኖም ግን  በተለይ የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የቅጥር ኮንትራት ውል ጥቅምት 28 አብቅቶ በይፋ ኮንትራራታቸው እንደተራዘመ ሳይገለፅ እስከ ታህሳስ 28 እየሰሩ እንዲቀጥሉ መደረጉ ፌደሬሽኑን ያስተቸዋል፡፡  
አሰልጣኞቹ እንዲሰናበቱ የተደረገው በሴካፋ እና በቻን ውድድሮች ላይ ባሳዩት ድክመት ብቻ እንዳልሆነ በመግለጫው የተናገሩት ሌላው የፌደሬሽኑ  የስራ አስፈፃሚ አባል እና ምክትል ፕሬዝዳንት የሆኑት  አቶ ተክለወይኒ ናቸው፡፡ በቻን ውድድር የኢትዮጵያ ቡድን ለዋንጫው ትልቅ ግምት ተሰጥቶት እንደነበር ከናይጄርያ እና ጋና ተርታ ይጠቀስ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ተክለወይኒ፤ ይህን በመንተራስ የፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ከአሰልጣኞቹ፤ ከረዳቶቻቸው እና ከተጨዋቾች ጋር ሲመካከር በቻን ያለው ግብ ዋንጫ ማምጣት ወይም ግማሽ ፍፃሜ መድረስ እንደሆነ ገልፆላቸዋል፡፡  የቡድኑ አባላት ይህን ግብ ለማሳካት ስንት ሽልማት ይጠብቀናል ብለው ሲደራደሩ ደህና ሽልማት ታገኛላችሁ ብለን ተማምነን ነበር ብለዋል፡፡  ከቻን ጉዞ በፊት በነበረው ጋዜጣዊ መግለጫ ዋና አሰልጣኙ ዋንጫ ለማምጣት ወይም ግማሽ ፍፃሜ ለመድረስ ቃል የገቡትን ካልሆነ ተሸንፎ መመለስ የሚለውን ጨመሩበት፡፡ ተገቢ አልነበረም፡፡ ‹‹በቻን ውጤት ላይ ያደረግነው  የውስጥ ግምገማ ብሄራዊ ቡድኑ ለተሰጠው ግምት በቂ ጥረት አላደረገም ነው፡፡ አህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ አካላት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአፍሪካ ደረጃ በተሳተፈባቸው ውድድሮች ጥሩ መጫወቱን ገልፀውልናል፡፡ ጎንለጎን ግን የቡድኑ ደረጃ ደካማ እንደሆነና የተፎካካሪነት ብቃቱም መሻሻል እንደሚያስፈልገው መክረውናል፡፡ ስለሆነም የአሰልጣኞቹ መቀየር አስፈልጓል›› በማለት አቶ ተክለወይኒ ማብራርያ ሰጥተዋል፡፡  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በየጨዋታው ብዙ የግብ እድሎች አምልጦታል፤ ተጨዋቾቹ ጥሩ ቢጫወቱም ውጤት ግን አላገኙም፤ ለውድድሮቹ በአሰልጣኞቹ የተደረገው ዝግጅት በፕሮፌሽናል መንገድ አልነበረም። ይህ ሁሉ ዝርዝር ምክንያት የፌደሬሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክለወይኒ ትልቅ ክፍተት ብለውታል። ‹‹ያሉብን ክፍተቶች የማይስተካከሉ ከሆነ የኢትዮጵያ ህዝብ የሚፈልገው ውጤት መቼም ሊሳካ አይችልም ስለዚህም ስርነቀል ለውጥ ያስፈልጋል በሚል ከመግባባት ላይ ደርሰናል ››ሲሉም ተጨማሪ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወቅታዊ ብቃት ላይ የፊፋ ባለሙያዎች ያደረጉትን ትንተና ለአሰልጣኞቹ መቀየር ተጨማሪ ምክንያት እንደነበር በመግለፅም  ለእግር ኳሱ ጠቅላላ ህዳሴ የሚያመጣ ስትራቴጂ እንደሚያስፈልግ ለታመነበት አቅጣጫ ውሳኔው አስፈላጊ ነበር ብለው ተናግረዋል፡፡
የሰውነት  ተተኪ ከየት? ከአገር ውስጥ ከባህር ማዶ
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ስራ አስፋፃሚ የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ቀላል ስራ አለመሆኑን ትልቅ ሃላፊነት እንደሆነ መገንዘቡን ሰሞኑን ገልጿል፡፡ የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና የረዳቶቻቸውን ስንብት የወሰነው ግን በአጣብቂኝ ውስጥ ሆኖ ይመስላል፡፡ ስራ አስፈፃሚው በፕሬዝዳንቱ በኩል አሰልጣኞቹን ያሰናበትነው ሌላ አሰልጣኝ ለመቅጠር በመጓጓት ማለቱም ተስፋ ሰጪ አይመስልም፡፡ በአዲስ አሰልጣኝ ቅጥር ለኢትዮጵያ እግር ኳስ እድገት የሚመች አደረጃጀት ለመፍጠር መታሰቡን የገለፁት ፕሬዝዳንቱ ፤ ቦታውን ክፍት ማድረግ የመጀመርያው ተግባር እንደሆነ መታወቅ እንዳለበት በማስረዳት የህዝብ ጉዳይ ስለሆነ በግልፅ፤ ያለወከባ እና በጥንቃቄ ተገቢው መስፈርት ወጥቶ በሚደረግ ውድድር መሰረት የሚፈፀም እንደሚሆን ቃል ገብተዋል፡፡
የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ በአዲሱ አሰልጣኝ ቅጥር የመጀመርያ ሙከራ በአገር ውስጥ ያሉ ባለሙያዎችን ማሰስ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ከሰውነት ቢሻው ስንብት በኋላ ብሄራዊ ቡድኑ ጋር ስማቸው እየተያያዘ ካሉ የአገር ውስጥ አሰልጣኞች መካከል ስዩም ከበደ፤ ፀጋዬ ኪዳነማርያም እና ገብረመድህን ሃይሌ እና ሌሎችም ይጠቀሳሉ፡፡ የፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት ለአሰልጣኙ ቅጥር ወደውጭ የምንወጣበት ሁኔታ ካለ የገንዘብ ምንጮቻችን በመፈተሽ የምናደርገው ይሆናል ሲሉም አስረድተዋል፡፡ የቀድሞው የጊዮርጊስ ክለብ አሰልጣኝ የነበረው፤ በሱዳኑ አልሂላል ክለብ የሰራውና በምስራቅ አፍሪካ ክለቦች ካለው ልምድ ባሻገር የሩዋንዳ እና የኡጋንዳ ብሄራዊ ቡድንን ያሰለጠነው ሰርቢያዊ ሰርዶጆቪች ሚሉቲን ሚቾ ከውጭ አሰልጣኞችቀድሞ ስሙ ተጠርቷል፡፡
በቀድሞው ፌደሬሽን የተገባላቸውቃል ሳይፈፀምላቸው ቅር ተሰኝተው የነበሩት ቤልጅማዊው ቶም ሴንትፌንትም እየተጠቀሱ ናቸው፡፡ ቶም ሴንትፌይት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ሃላፊነት ለመረከብ በይፋ ጥሪ በማክበር የመጀመርያ የውጭ አሰልጣኝ ናቸው።  ከቤልጅዬም ለሱፕር ስፖርት በሰጡት ማብራርያ ‹‹ሰውነት ቢሻው ለብሄራዊ ቡድን ባስገኘው ስኬት ምስጋና ይገባዋል። ረዳቴ ሆኖ አብረን ስንሰራ በነበረበት ወቅት እንደ አስራት መገርሳ እና ጌታነህ ከበደን የመሳሳሉ ተጨዋቾች ለቡድኑ በመምረጥ አስተዋፅኦ ነበረኝ። በእርግጥ አገሪቱን ለቅቄ የወጣሁት ከፌደሬሽኑ ጋር በተፈጠሩ አለመግባባቶች ነበር፡፡ ተመልሼ ብሄራዊ ቡድኑን የማሰልጠን እድል ባገኝ ብዙ ልሰጠው የምችለው ነገር አለ፡፡ በተለይ ዋልያዎቹ በትልልቅ ግጥሚያዎች የሚገጥማቸውን ፈተና የሚወጡበትን አቅም ማስተካከል እችላለሁ፡፡ የኢትዮጵያ ቡድን በፈጠራ እና በቴክኒክ የዳበረ ጥሩ አሰልጣኝ ካገኘ ምርጥ መሆን የሚችል ነው።›› በማለት ቶም ሴንትፌይት ለሱፕር ስፖርት ተናግረዋል፡፡
ፌደሬሽኑ የአሰልጣኙ ቅጥር በቀና መንገድ፤ አሳማኝ መመዘኛ እና መስፈርት ተዘጋጅቶ የሚከናወን እንደሆነ ሲያስታውቅ፤ ፍለጋውን በጋዜጦች ማስታወቂያዎችን በማውጣት፤ የተለያዩ ጥቆማዎችን ከባለድርሻ አካላት እና ከሙያተኞች በመቀበል፤ በብሮድካስት ሚዲያዎች በማስተዋወቅ ይሰራበታል ብሏል፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ እንደገለፁት በአሰልጣኝ አዲስ ቅጥር የማፈላለግ ተግባር ላይ  የቴክኒክ ኮሚቴ ሃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡ ኮሚቴው በአንድ ሳምንት ጊዜ  ለሃላፊነቱ ብቁ የሆኑ ሰዎችን ዝርዝር እንዲያቀርብ ይጠበቃል፡፡
ቀጣዩን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ለመቅጠር ፌደሬሽኑ ያሰበው የህዝብ ፍላጎት አድጓል፤  ዓለም አቀፍ ደረጃ ይዘን ተፎካካሪ ሆነን እንቅረብ ከሚል አቅጣጫ በመነሳት ነው፡፡ ከአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው መሰናበት  በኋላ ግን ለብሄራዊ ቡድኑ የሚመጥን አሰልጣኝ ፍለጋው ፈታኝ እንደሚሆን  መገመቱ  ስጋትን የጋረጠ ሆኗል፡፡
በአገር ውስጥ የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውን ተተኪ ለማግኘት አሁን ጊዜው የሚያስቸግር ይመስላል፡፡ ብቁ ናቸው የሚባሉ አሰልጣኞች በአመዛኙ  በብሄራዊ ቡድን ደረጃ ብዙም ልምድ የሌላቸው፤ የሙያ ብቃታቸው ያን ያህል የማያስመካ፤ አንዳንዶቹ በክለብ አሰልጣኝነት ሃላፊነታቸውን ለመልቀቅ የሚቸገሩ ናቸው፡፡ እነዚህ እና ሌሎችም ምክንያቶች ተተኪ አሰልጣኝ ከአገር ውስጥ የማግኘቱን እድሉን ያጠብበዋል፡፡ ከአገር ውጭ አሰልጣኝ ለመቅጠር ደግሞ ከዚህ በፊት ያሉ ተመክሮዎች የሁኔታውን አስቸጋሪነት በይበልጥ ያጎሉታል፡፡ ከአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በፊት ሁለት የውጭ አገር አሰልጣኞች ነበሩ፡፡  በትውልድ ናይጄርያዊ ሆነው ስኮትላንዳዊ ዜግነት ያላቸው አሰልጣኝ ኢፌም ኦኑራ እና ቤልጅማዊው ቶም ሴንትፌንት ናቸው፡፡
ሁለቱም አሰልጣኞች ከብሄራዊ ቡድን ጋር የነበራቸው ቆይታ አወዛግቧል፡፡ ከዚያ በፊት የነበሩትን ፈረንሳዊ አሰልጣኝ ዲያጎ ጋርዚዬቶ እና የፌደሬሽኑ እሰጥ አገባም በማስታወስ  ብዙ ልምድ መቅሰም ይቻላል፡፡ በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ለማሰልጠን ብቁ ናቸው ተብለው ከውጭ የመጡ አሰልጣኞች ያለው መጥፎ አመላከት ካልተወገደ የሚያሳስብ ይሆናል፡፡ የውጭ አሰልጣኞች የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የማሰልጠን ሃላፊነቱ በምቹ ሁኔታ በነፃነት እንዲሰሩበት  የተሰጣቸው አልነበሩም፡፡ በቂ የስራ ጊዜ በኮንትራት ውላቸው አያገኙም ነበር፡፡  
ከአገር ውስጥ ባሉ አሰልጣኞች ምንም አይነት ክብር አይሰጣቸውም፤ ተባብሮ ከመስራት ይልቅ እንደውም ለውጥ አያመጡም በሚል አስተሳሰብ ዘመቻ ሲደረግባቸው አጋጥሟል፡፡ በሌላ በኩል ለአሰልጣኞቹ የሚከፈለው ደሞዝ እና ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ መጠየቁም ይፈትናል፡፡  ብዙውን ጊዜ የውጭ አገር አሰልጣኞች ቅጥር  ለማከናወንና ክፍያ በመፈፀም ፌደሬሽኑ እቅዱን  እውን የሚያደርገው ክቡር ሼህ አላሙዲ ድጋፍ ላይ በመተማመን ነበር። ክቡር ሼህ አላሙዲ ይህን አይነቱን ድጋፍ መስጠት ካቆሙ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ አስቀድመው የነበሩ ድጋፎችም በተለያዩ መንገዶች ሲመዘበሩ እና ሲባክኑ ማጋጠሙም ጥሩ ታሪክ አይደለም፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ በአሰልጣኞቹ የቅጥር ሁኔታ ላይ ፌደሬሽኑ ከየትኛው አካል ጋር ተመካክሮ እንደሚሰራ፤ በምን አይነት መስፈርት አወዳድሮ እንደሚቀጥር እና ለምን እንደቀጠረ በግልፅ ሁኔታ ያልተሰራበት ሆኖ መቆየቱን ማስታወስ ይቻላል። ሌላው ዋና አደጋ የውጭ አገር አሰልጣኞች ከተቀጠሩ በኋላ የሃላፊነት ቆይታቸው በአላስፈላጊ ጫናዎች ሲያጥር፤ በአሰለጣጠን ፍልስፍናቸው እና በቋንቋቸው ከብሄራዊ ቡድን ጋር መግባባት ሲያዳግታቸው፤ ከአገሪቱ ሚዲያዎች ጋር ተቀራርበው ለመስራት ሲቸገሩ እና ከፌደሬሽኑ አካላት ጋር መግባባት ሲሳናቸው እንደነበር ማስታወሱ ተስፋ ያስቆርጣል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአህጉራዊ እና በዓለም አቀፍ ውድደሮች በብቁ ተፎካካሪነት እንዲሳተፍ የሚያበቃውን ፕሮፌሽናል አሰልጣኝ  እንዴት ሊያገኝ ይችላል ብቻ ሳይሆን ከተገኘስ የሚጠይቀውን ውድ ክፍያ ማን ይችላል የሚሉ ጥያቄዎች ስጋት ይፈጥራሉ። የሊቢያን ብሄራዊ ቡድን በማሰልጠን በቻን ውድድር ዋንጫ ለማንሳት የቻሉት ፈረንሳዊው ሃቪዬር ክሌሜንቴ ደሞዛቸው እስከ 20 ሺ ዶላር ነው፡፡ በአጠቃላይ አንድ የውጭ አገር አሰልጣኝ ለመቅጠር በወቅቱ የገበያ ሁኔታ ኢትዮጵያ ከ15 እስከ 20 ሺ ዶላር በወር መክፈል ሊኖርባት ይችላል፡፡ ይህ ገንዘብ ታድያ ከየት ይመጣል፤ ከሼህ አላሙዲ ወይንስ ከመንግስት መልስ የሚያስፈልገው ጥያቄ ነው፡፡
ከሰውነት በኋላ ፌደሬሽኑ እና የህዳሴ ስትራቴጂው
በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል በተካሄደው የግምገማ እና የምክክር መድረክ ላይ ከፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት በመቀጠል የመክፈቻ ንግግር ያሰሙት የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ አንበሴ እንየው ነበሩ። ኮሚሽኑ እንደመንግስት የእግር ኳሱ ከፍተኛ ባለድርሻ አካል መሆኑን የጠቀሱት ምክትል ኮሚሽነሩ አቶ አንበሴ፤  እግር ኳስ አንጋፋ እና ፈርቀዳጅ ስፖርት እንደሆነ በመግለፅ የህዝብ አጀንዳና አንድ የልማት ጉዳይ ስለሆነ የግምገማ እና የምክክር መድረኩ በስፖርቱ ህዝብን የሚያስደስት እና የሚያረካ ውጤት ላይ ለሚደረስበት የለውጥ እንቅስቃሴ መነሻ መሆን አለበት ሲሉ ተናግረዋል፡፡
በቀድሞው ፌደሬሽን አማካኝነት ከ2004 እሰከ 2007 በሚል የ3 ዓመት ስትራቴጂክ እቅድ ተዘጋጅቶ እንደነበር ያስታወሱት ምክትል ኮሚሽነሩ፤ በአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ውድድሮች ለመሳተፍ በሚል ትኩረት ተሰጥቶ በመሰራቱ በተወሰነ መልኩ እቅዱን ማሳካት መቻሉን አመልክተዋል፡፡ ወደፊትም በተሻለ ሁኔታ መሰራት ስላለበት  በአሁኑ ፌደሬሽንም በስትራቴጂክ እቅድ መመራት ያስፈልገዋል ብለዋል፡፡ አቶ አንበሴ እንየው እግር ኳስ የእድገታችን ልዩ መገለጫ መሆን አለበት የሚል ማሳሰቢያቸው  መንግስት ለስፖርቱ ከፍተኛ ትኩረት መስጠቱን ያረጋገጠ ነበር፡፡ በየክልሉ በርካታ ስታድዬሞች እየተገነቡ ናቸው፡፡ አካዳሚዎችም ተመስርተዋል፤ እየተሰሩም ናቸው፡፡  መንግስት በስፖርቱ ሊገኝ የሚችለውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እና የአገር መልካም ገፅታ ገብቶታል፡፡ የእግር ኳሱ ባለድርሻ አካላት በመንግስት በኩል ለስፖርቱ  የተሰጠውን ትኩረት ያህል ብዙ መስራት እንዳለባቸው መረዳት ይገባል፡፡
በእግር ኳስ ኢትዮጵያ አሸንፋ እንድትወጣ ሁሉም ይፈልጋል ያሉት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ በስፖርቱ ኢንቨስትመንት እስከዛሬ ከተደረገው የበለጠ ማሳደግ አለብን ይላሉ፡፡ እንደ ጋና አይነት አገራት በርካታ ታዳጊ ፕሮፌሽናሎችን በማፍራት በአሁኑ ጊዜ ከ354 በላይ ተጨዋቾች በላይ በመላው ዓለም በማሰማራት ከፍተኛ ተጠቃሚ መሆናቸውን ማጥናት እንደሚያስፈልግ ያስረዱት ፕሬዝዳንቱ ፤ ኢትዮጵያ ወጣት ፕሮፌሽናሎችን ለማውጣት ምን መስራት እንዳለባት፤ ስንት አካዳሚዎች ይበቁናል ስንት አካዳሚዎች አሉን እንዴት እንስራባቸው በሚል መንቀሳቀስ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
የስራ አስፈፃሚው እንደሚያስበው በኢትዮጵያ እግር ኳስ የወደፊት ጉዞ ላይ አሰልጣኝ መቀየር ብቻ ለውጥ አያመጣም፡፡ በእርግጥ የዋና ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ቁልፍ ሃላፊነት ቢሆንም ጎን ለጎን በስፋት ለውጥ የሚያስፈልጋቸውም ሁኔታዎችም አሉ፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽን የማስፈፀም ብቃት እና አደረጃጀት ለውጥ እንደሚያስፈልግ ታምኖበታል፡፡ በወጣቶች አና ታዳጊዎች ላይ ባተኮረ ስትራቴጂ ከስርመሰረቱ ካልተሰራ አሰልጣኝ ተጨዋች ሊያገኝ አይችልም በሚል አስተሳሰብም ለውጥ ለመፍጠር ታስቧል፡፡ የስራ አስፈፃሚው አባላት እንደገለፁት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ላይ ስርነቀል ለውጥ ለማምጣት ለሚያስችለው ስትራቴጂክ እቅድ የባለሙያ ቡድን ተቋቁሞ ሰነዱ እየተዘጋጀ ነው፡፡  በየካቲት ወር ሰነዱ ሙሉ ተዘጋጅቶ የሚያልቀው ይህ የስትራቴጂ እቅድ በአምስት አመት መርሃ ግብር የተነደፈ መሆኑ ተገልፆ አሁን ያለው ፌደሬሽን በስልጣን ላይ በሚቆይባቸው ቀሪዎቹ 3 ዓመታት በስፋት እንደሚሰራበት፤ ለሚቀጥለው የፌደሬሽን አመራር የሚያወርሰው እንደሚሆንም ተስፋ ተደርጓል፡፡ የፌደሬሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክለወይኒ እንደገለፁት በዚሁ የስትራቴጂ ሰነድ ላይ ከ300 እስከ 400 የሚደርሱ ባለድርሻ አካላትን በማሰባሰብ ውይይት ለማድረግ ፍላጎት እንዳለ ጠቁመው በስትራቴጂክ እቅዱ መሰረት የብሄራዊ ቡድኑ አጠቃላይ አደረጃጀት እና መዋቅር፤ አሰራሩ፤ የሰው ሃይል አደረጃጀቱ በአጠቃላይ እንደሚገመገም እና በተገቢው  መንገድ ከተሰራበት ለውጥ መፍጠር እንደሚቻል ፅኑ እምነት አለን ብለዋል፡፡ በስትራቴጂክ እቅዱ የኢትዮጵያን እግር ኳስ ፕሮፌሽናላይዝድ ማድረግ ወሳኝ መሆኑን ስራ አስፈፃሚው ተስማምቶበታል፡፡
በዚህ የፕሮፌሽናሊዝም አቅጣጫ መሰረት የፕሪሚዬር ሊግ፤ የብሄራዊ ሊግ እና ሌሎች የወጣት እና ታዳጊ ውድድሮች ፕሮፌሽናላይዝድ ማድረግ እነደሚያስፈልግ፤ የክለቦችን አቅም እና አደረጃጀት በማሳደግ ፕሮፌሽናላይዝድ ሆነው እንዲንቀሳቀሱ ማስቻል እንደሚገባ እና የኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት እንደከፍተኛ የሰው ሃይል በመጠቀም እግር ኳሱ እንደኢኮኖሚው አድጎ እንዲታይ መሰራት አለበት በሚል ነው፡፡ በወጣት እና በታዳጊ ፕሮጀክቶች፤ መንግስት፤ ክለቦች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በስፋት እንዲንቀሳቀሱም ይደረጋል፡፡
የፌደሬሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክለወይኒ ሃጎስ እንደሚናገሩት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ወደፊት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተፎካካሪ ሆኖ ለመቀጠል የሚችለው በእውቀት እና በስትራቴጂ እቅድ ሲሰራበት፤ የፕሮፌሽናሊዝም አቅጣጫዎችን ሲከተል ነው ፡፡ በዚህ ረገድ አሁን በስልጣን ላይ የሚገኘው የፌደሬሽን ስራ አመራር ብዙ ጥረት ማድረግ እንደሚጠበቅበትና ኢትዮጵያ ዛሬ በከፍተኛ ደረጃ የሚያፎካክረውን ስፖርት የሚመጥን ደረጃ አግኝታ እንደ ብራዚል ፤ እንደ ስፔን እና እንግሊዝ ተጠቃሚነት እንዲኖራት በመመኘት መስራት ያስፈልጋል በማለት ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡

የፍ/ቤቱን ሸፍጥ ያጋለጡት አውሮፓዊ በአፍሪካ መሪዎች ተደንቀዋል
አፍሪካን ቅኝ ለመግዛት የሚደረግ አዲስ ኩሸት ነው ተብሏል
“አውሮፓ የሚሏት እርም የለሽ አህጉር፣ እነሆ ከአንድ መቶ ሃያ አመታት በኋላም አፍሪካንና አፍሪካውያንን ለመዝረፍ እየሞከረች ነው!” አሉ እንግሊዛዊው የፖለቲካ ተመራማሪ ዶክተር ዴቪድ ሆይሌ፡፡
“አውሮፓውያን ያቋቋሙትን ‘አለማቀፍ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት’ የተባለ መላ ተጠቅመው አፍሪካውያንን ባህር አሻግረው እያጋዙ፣ ሆነ ብለው በሰየሙት የይስሙላ ችሎት ላይ እያቆሙ ነው” ሲሉ ደገሙ ዶክተር ዴቪድ ሆይሌ፡፡
ይህም በአዳራሹ ውስጥ የነበሩ በርካቶችን በደስታ አፍለቀለቀ፡፡ ዙሪያ ገባውንም በጭብጨባ አደበላለቀ፡፡ እርግጥም የሰውዬው ንግግር ብዙዎችን ማስደሰቱ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ምክንያቱም በዚህ አዳራሽ ውስጥ ከታደሙት የተለያዩ የአፍሪካ አገራት መሪዎች አብዛኞቹ፣ ከአለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድቤት ጋር ቂም የተያያዙና በባላንጣነት የሚተያዩ ናቸው፡፡
በአፍሪካ ፖለቲካዊና የውጭ ግንኙነት ጉዳዮች ላይ በርካታ መጽሃፍትን ለንባብ በማብቃት የሚታወቁት የፖለቲካ ተመራማሪው ዶክተር ዴቪድ ሆይሌ፣ ባሳለፍነው ሳምንት በዚሁ በአዲስ አበባ በተካሄደው 22ኛው የአፍሪካ ህብረት ጉባኤ ላይ ነበር፣ የአገራቱ መሪዎች በተገኙበት ሁለት መጽሃፍቶቻቸውን በይፋ ያስተዋወቁት፡፡
በአፍሪካውያን መሪዎች ተጨብጭቦላቸው ከተመረቁት የዶ/ር ዴቪድ ሆይሌ መጽሃፍት አንዱ፣ ‘የአለማቀፉ ወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ የአውሮፓ ጓንታናሞ ቤይ?’ የሚል ርዕስ አለው፡፡ መሪዎቹ ያጨበጨቡት ለርዕሱ ብቻ አይደለም፡፡
“አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፣ ለአውሮፓውያን አፍሪካን እንዳትረጋጋ በማድረግ፣ ፖለቲካዊ የበላይነቷን የማሳጣትና የማዕድን ሃብቷን በገፍ የመዝረፍ ድብቅ አጀንዳቸው ማስፈጸሚያ ሆኖ ከርሟል!... ተቀማጭነቱ በሄግ የሆነው ፍርድ ቤቱ፣ አፍሪካን እንደገና ቅኝ ለመግዛት የሚደረግ አዲስ አውሮፓዊ ኩሸት መገለጫ ነው!...” ለሚለው መደምደሚያው ጭምር እንጂ፡፡
ዶክተር ዴቪድ እንደሚሉት፣ ፍርድ ቤቱ በአለም ዙሪያ በሚገኙ 130 በላይ አገራት ተፈጸሙ በተባሉ ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶችና ወንጀሎች ዙሪያ ከ8ሺህ 300 በላይ የክስ ማመልከቻዎች ቢደርሱትም፣ እስካለፈው የፈረንጆች አመት 2013 መጨረሻ ድረስ የወንጀል ምርመራ የጀመረው በ8 አገራት ላይ ብቻ ነው፡፡ ይሄም ብቻ አይደለም፡፡ ሰውዬው እንደገለጹት፣ የፍርድ ቤቱን ተልዕኮ ጥያቄ ውስጥ የሚከተው ሌላው አስገራሚ ነገር፣ እነዚሁ ስምንት አገራትም ሁሉም አፍሪካዊ መሆናቸው ነው - ኡጋንዳ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ የመካከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ሱዳን፣ ኬንያ፣ ኮትዲቯር፣ ማሊና ሊቢያ፡፡
“አንድ እንኳን አፍሪካዊ ያልሆነ አገር፣ በፍርድ ቤቱ የወንጀል ምርመራ እየተደረገበት አይደለም። ራሱን አለማቀፍ የፍትህ ተቋም አድርጎ የሰየመው ይህ የይስሙላ ፍርድ ቤት፣ በአፍጋኒስታንና በኢራቅ የሰሯቸውን የጦርነት ወንጀሎች በተመለከተ በቂ ማስረጃ ከያዘባቸው የተለያዩ አውሮፓ አገራት መንግስታት፣ አንዱን እንኳን ለፍርድ ለማቅረብ አልደፈረም!... ይህም የተቋሙን አድሏዊነት ቁልጭ አድርጎ ያሳያል” ብለዋል ዶ/ር ዴቪድ፡፡
የአውሮፓን ‘ሸፍጥ’ ባጋለጠው አውሮፓዊ የባዳ ዘመዳቸው፣ ዶ/ር ዴቪድ ልባቸው ቅቤ የጠጣ የአፍሪካ መሪዎችም፣ “እኛም ሰሚ አጥተን ነው እንጂ፣ ለፍትህ ቆሜያለሁ እያለ ፍትህን ስለሚገድለው ስለዚህ ወገኛ ተቋም ቀድመን ተናግረናል” ሲሉ በኩራት ተናግረዋል፡፡
አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ እ.ኤ.አ በ2013 በኬኒያው ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬኒያታና በምክትላቸው ዊሊያም ሩቶ ላይ ክስ መመስረቱን ተከትሎ፣ የፍርድ ቤቱ ጉዳይ ከአፍሪካ ህብረት ቀዳሚ የመነጋገሪያ አጀንዳዎች አንዱ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ህብረቱ በዚህ ተቋም ላይ እምነት እንደሌለውና አካሄዱም አህጉሪቱን ክፉኛ የሚጎዳ ህገወጥ ተግባር እንደሆነ በይፋ ከመናገር አልፎ፣ በአህጉሪቱ መንግስታት ላይ የሚሰነዝረውን ውንጀላም መሰረተ ቢስ ሲል አጣጥሎታል፡፡
ህብረቱ በጥቅምት 2013 በጠራው የመሪዎች ልዩ ጉባኤ ላይ የአለማቀፉን የወንጀለኞች ፍርድ ቤት እውቅና የሚነሳ ውሳኔ አሳልፏል፡፡ ተሰሚነት ያላቸው የአህጉሪቱ ቁልፍ መሪዎችም፣ በተቋሙ ላይ ያላቸውን ተቃውሞ በተለያዩ አህጉራዊና አለማቀፋዊ መድረኮች ላይ ማስተጋባታቸውን ቀጥለዋል፡፡
የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ “አፍሪካ ላይ ወዳነጣጠረ የፖለቲካ መሳሪያነት ዘቅጧል” ሲሉ በይፋ የተቹትን ይሄን ፍርድ ቤት፤ የኡጋንዳው ፕሬዚደንት ዮሪ ሙሴቬኒም እንዳይሞት እንዳይድን አድርገው ዘልፈውታል፡፡
የመፅሃፉ ደራሲ ዶ/ር ዴቪድም የአፍሪካ መሪዎች ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ በተቋሙ ላይ የሚሰነዝሯቸውን ትችቶች የሚደግፍ ንግግር ነው በህብረቱ ጉባኤ ላይ ያሰሙት፡፡ “ራሱን አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት እያለ የሚጠራው የውሸት ፍርድ ቤት ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ ያከናወናቸውን ተግባራት ተመልከቱ፡፡ እጅግ ብዙ የመሰሪነት ስራዎችና ተንኮሎችን ሲጎነጉን፣ የአፍሪካ አገራትን በማስፈራራት አልያም መደለያ በማቅረብ በግዳጅ የፍርድ ቤቱ አባል ሆነው እንዲቀጥሉ ሲሞክር እኮ ነው የኖረው!” በማለት፡፡
በህብረቱና በአለማቀፉ ወንጀለኞች ፍርድ ቤት መካከል የተፈጠረው የጠላትነት ስሜት ከጊዜ ወደ ጊዜ ማደጉን ተከትሎ፣ የአፍሪካዊ መንግስታት አለማቀፍ ወንጀሎችን የሚዳኝ የራሳቸውን ክልላዊ የፍትህ ተቋም ወደመፍጠር እንዲገቡ አስገድዷል፡፡
ዶ/ር ዴቪድ እንደሚሉት፤ አውሮፓውያን ይሄንን የአፍሪካ ህብረት አማራጭ ለማሰናከል በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላር መድበው እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ፡፡ እ.ኤ.አ በ1998 በአለም ዙሪያ የሚገኙ 122 አገራትን በአባልነት ይዞ በተመሰረተው አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፣ 34 አገራትን የፍርድ ቤቱ አባላት በማድረግ ከሁሉም አህጉራት ቀዳሚ የሆነችው አፍሪካ ናት፡፡ “ፍርድ ቤቱ 18 የእስያ ፓሲፊክ፣ 18 የምስራቅ አውሮፓ፣ 27 የካረቢያንና 25 የምዕራብ አውሮፓ አገራትን በአባልነት ቢይዝም፤ ጣቱን የቀሰረው ግን በፈረደባት አፍሪካ ላይ ብቻ ነው፡፡ ይህ ነው ፍርድ ቤቱን ፍትሃዊነት በጎደለው ሁኔታ ፍትህን አስከብራለሁ ብሎ የሚዳክር የይምሰል ተቋም የሚያደርገው” ብለዋል ዶክተር ዴቪድ፡፡
በአፍሪካ ጉዳይ ላይ ጥልቅ ጥናት በማድረግ የሚታወቁት ዶ/ር ዴቪድ፤ ስለ አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ጸረ - አፍሪካ ተቋምነት ሲናገሩ ቅንጣት ታህል ማመንታት አይታይባቸውም።
“አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት አውሮፓዊ ተቋም ነው፡፡ አፍሪካን እዳኛለሁ ብሎ የተነሳ አውሮፓዊ ፍርድ ቤት ነው፡፡ እውነታው ይሄና ይሄ ብቻ ነው!!” በማለት ነው፣ ዶ/ር ዴቪድ በህብረቱ 22ኛ ጉባኤ ላይ ተገኝተው በሙሉ ልብ የተናገሩት፡፡ ይህ የዶክተሩ ንግግር፣ አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ ለፍርድ ይቅረቡ ብሎ በወሰነባቸውና ከችሎት ፊት ሊገትራቸው በሚፈልጋቸው በእነኡሁሩ ኬንያታና ኦማር ሃሰን አል በሽር ልብ ውስጥ ትልቅ ደስታ ፈጥሯል፡፡
ዶ/ር ዴቪድ ሆይሌ ለንባብ ያበቁት አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ የአውሮፓ ጓንታናሞ ቤይ?’ የተሰኘና 345 ገጾች ያሉት መጽሃፍ፤ አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት አጠቃላይ ዓላማና የመጨረሻ ግብ፣ አፍሪካን መልሶ በአውሮፓውያን ቅኝ ግዛት ስር ማድረግ እንደሆነ ያትታል፡፡ ፍርድ ቤቱ ራሱን እንደገለልተኛና ከአድልኦ የጸዳ ተቋም አድርጎ ለማሳየት ቢጥርም እውነታው ግን ከዚህ የራቀ ነው ባይ ናቸው ዶክተሩ፡፡
ፍርድ ቤቱ 60 በመቶ የሚሆነውን በጀቱን የሚያገኘው ከአውሮፓ ህብረት እንደመሆኑ፣ በአውሮፓ አገራት የሚፈጸሙ ወንጀሎችን በድፍረት ለማጋለጥና ወንጀል ፈጻሚዎችን ለፍርድ ለማቅረብ ሞክሮ እንደማያውቅ ገልጸዋል፡፡ ይልቁንም ፍርድ ቤቱ፣ እጅ ያጠራቸውንና ከአጋሮቹ ጋር የፖለቲካ ንክኪ ያላቸውን የአፍሪካ አገራት እየመረጠ በመወንጀል፣ እድሜ ዘመኑን የገፋ የአውሮፓውያን ተላላኪ ነው ይላሉ፤ ዶክተሩ በመጽሃፋቸው፡፡
“አፍሪካ ከቅኝ አገዛዝ ቀንበር ለመውጣትና ነጻነቷን ለመጎናጸፍ ለዘመናት ታግላለች፡፡ ትልቅ መስዋዕትነትም ከፍላለች፡፡ አሁን ደግሞ ከወደ አውሮፓ ዘመን የወለደው ሌላ ‘ህጋዊ’ የቅኝ ግዛት ሙከራ እየተሰነዘረባት ይገኛል፡፡ እዚህ ላይ ዝም ማለት የለባትም፡፡ መክታ መመለስ እንጂ!” ብለዋል ጸሃፊው፡፡
ዶ/ር ዴቪድ በመጪው መጋቢት ወር በይፋ ለንባብ ያበቁታል ተብሎ የሚጠበቀውና ‘ጀስቲስ ዲናይድ፣ ዘ ሪያሊቲ ኦፍ ዘ ኢንተርናሽናል ክሪሚናል ኮርት’ የሚል ርዕስ በሰጡት ሁለተኛው መጽሃፋቸውም፣ ፍርድ ቤቱ በአፍሪካ አህጉር ላይ አነጣጥሮ እየሰራ ያለውንና ለወደፊትም ሊሰራ ያሰባቸውን ኢ-ፍትሃዊ ተግባራት በዝርዝር ይዳስሳል ተብሏል፡፡

ጥንት ዱሮ አያ ቋቴ የሚባሉ ብልህ ሰው ነበሩ ይባላል፡፡ የአያ ቋቴ መታወቂያ ሰው እህል ለመዝራት ገና መሬቱን ሳያለሰልስ እሳቸው እርሻ መጀመራቸው ነው፡፡
“አያ ቋቴ?” ይላቸዋል አንዱ፡፡
“አቤት” ይላሉ
“ምነው እንዲህ ተጣደፉ? በጊዜ እርሻ ጀመሩ?”
“በጊዜ ቋቴን (የዱቄት እቃዬን) ልሞላ ነዋ” ይላሉ፡፡
“መሬቱ የት ይሄድቦታል? ቀስ ብለው አያርሱትም ታዲያ?”
“አርሼውስ የት ይሄድብኛል? ብዘራበትስ መች እምቢ ይላል?”
አያ ቋቴ በጊዜ በማለዳ እየተጣደፉ ሄደው አዝመራቸውን ሲሰበስቡ፤ ገና ያልዘሩ ሰዎች፤
    “አያ ቋቴ?”
    “አቤት”
“አሁን አዝመራው የት ይሄድብዎታል? እንዲህ ሰማይ ዐይኑን ሳይገልጥ እየሮጡ የሚሄዱት?”
“ፈጥኖ የደረሰ እህል አንድም ለወፍ አንድም ለወናፍ ነው፡፡ በጊዜ እጅ የገባ ነገር ጥሩ ነው፡፡ ቋቴ በጊዜ ሞልቶ ቢገኝ ምን ይጎዳኛል?” ይላሉ፡፡  
ቆይተው እየተጣደፉ ሊያስፈጩ እህል በአህያ ጭነው ሲሄዱ ሰዎች ያገኙዋቸዋል፡፡
    “አያ ቋቴ?”
    “አቤት”
    “ወዴት ነው እንዲህ እየተጣደፉ የሚሄዱት?”
    “ወደ ወፍጮ ቤት”
    “እንዲህ በጠዋት፣ እንዲህ እየሮጡ?”
    “አዎን እንዲህ በጠዋት፣ እንዲህ እየሮጥሁ”
    “ምነው ጦር መጣ እንዴ? ፀሐይ ሞቅ ሲል ቀስ ብለው አይሄዱም?”
    “ለቋቴ፡፡ ቋቴ በጊዜ እንዲሞላ ነዋ!”
አያ ቋቴ እህላቸውን አስፈጭተው ማጠራቀሚያ ቋታቸው ውስጥ ከትተው እያስጋገሩ ሲበሉ፣ ሰዉ ገና እርሻ ላይ ወዲያ ወዲህ ይላል፤ በማህል አንዱ ይመጣና
    “አያ ቋቴ?”
    “አቤት”
    “የምንበላው አጣን እባክዎ ዱ    ቄት ያበድሩን”
ሌላው አዛውንት ይመጡና፤
    “የእገሌ ቤተሰብ በረሀብ ሊያልቅ ነው እባክዎ ትንሽ ዱቄት ካለዎት?”
ቀጥሎ የእድሩ ዳኛ ይመጡና፤
“አያ ቋቴ”
    “አቤት”
“እባክዎ የእገሌ ልጅ ሞቶ ለቀስተኛውን እምናበላው አጣን፤ እንደሚያውቁት እህል አልደረሰልንም?”
አያ ቋቴም አይ ያገሬ ሰዎች፤ “ለልመና ሲሆን ሰው ሳይቀድማችሁ ትነሳላችሁ፡፡ እኔ ለቋቴ ማለዳ ስነሳ ታሾፋላችሁ! መቼ ነው ጊዜ ቋት መሆኑ የሚገባችሁ?” አሉ ይባላል፡፡
    *     *     *
ከአያ ቋቴ የምንማረው ለዓላማችን ስንል በጠዋት መነሳትን ነው፡፡ አስቀድሞ መዘጋጀትን ነው፡፡ በጊዜ መሰነቅን ነው፡፡ በጊዜ መክተትን ነው፡፡ ጊዜ የትግል ቋት ነው፡፡ “ጊዜ የስልጣን እጅ ነው” ይላሉ አበው፡፡ ሰው ሳይቀድመን ለልመና ከመነሳት ይሰውረን፡፡
ገጣሚው ራልፍ ኤመርሰን “አልኮል፣ ሐሺሽ፣ ፕሩሲክ አሲድ፣ ካናየን ደካማ ሱሶች ናቸው፡፡ ዋና መርዘኛ ዕፅ ጊዜ ነው” ይለናል፡፡
“የሰዓቱ እጀታ ከምናስበው በላይ እየተንቀረፈፈ ነው፡፡ ረፍዶብናል!” የሚሉት መዝሙር አላቸው ቦሄማውያን፡፡ መርፈዱን መገንዘቢያችን ደቂቃ ወይም ሰከንድ ላይ ነን፡፡ በወሬ የምንፈታው ጦር የለም። በወሬ የምንፈታው ዳገት የለም፡፡ ሁሉ ነገር ሥራ ይፈልጋል፡፡ ነገን ዛሬ እንሻማው፡፡ “ዛሬ ላይ ሆነን ከነገ መስረቅ ነው (Plagiarizing the future)” እንደተባለው ነው፡፡
ዛሬ፤ የለመድነውን ይዘን ከመቀጠል ሌላ የአስተሳሰብ ለውጥ ሽታው ጠፍቷል፡፡ ዕውቅናና ገንዘብ የማሰባሰቢያውን ማሺን እጁ ያስገባ ሰው የሚነግስበት ዘመን ሆኗል! ይሄንን ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ብለን እየተጓዝን ነው፡፡ ሆኖም ፓርቲ እየዘቀጠ ሲሄድ ባለፀጋ መሆን (Fattening) ይበረክታል፡፡ ዝነኛ መሆን ግብ ይሆናል፡፡ ቲፎዞ በመሰብሰብ የሚመራ መሪ ባዶ ገረወይና ነው፤ እንደሚባለው ዓይነት ነገር ይዘወተራል፡፡ ይለመዳል፡፡ ዲሞክራሲ ይህ ከሆነ ዲሞክራሲ ራሱ ገና ዲሞክራሲያዊ መሆን ያስፈልገዋል። (Let’s Democratize Democracy-Fareed Zekaria)
ለማስመሰል በማይሆን ተስፋ መፅናናት ብዙዎቻችንን ላልተጨበጠ መንገድ ይዳርገናል፡፡ አስተሳሰባችን አሜሪካዊው ድራማቲስት ብሩክ አትኪንሰን “አንድ ቀን በፀሐይ ዙሪያ” በሚለው ፅሑፍ ተስፈኝነትን ሲገልፅ፤ ካለው ጋር የሚሄድ ነው፡፡ “አንዳች ተዓምራዊ-ሚሥጥራዊ መንገድ ፍቅር ሁሉንም ድል ይመታል፣ መልካሙ ነገር መጥፎውን በሁለንተናዊው ዓለም ሚዛን መሰረት ይረታል፤ እናም በ11ኛው ሰዓት ክፉ ነገር በእኛ ላይ ከመምጣቱ በፊት አንዳች ገናናና ታላቅ ኃይል ያቆመዋል፤ ይከለክልልናል!” ከዚህ ቢሰውረንና ለመስራት ብንነሳ፣ ለመደራጀት ብንዘጋጅ፣ ውጣ ውረዳችንን ከወዲሁ በተጨባጭ ልንበግረው ብንጣጣር ይሻላል፡፡ ልባችን ዘውድ ለመጫን ያስብ እንጂ እጃችን አፈር አልጨበጠም፡፡
የተለመደ መፈክር፣ የተለመደ የአፍ ወረርሺኝ፣ የተለመደ ከላይ ወደታች ትዕዛዝ፣ የተለመደ ዝቅጠት፣ የተለመደ በሙስና ወደ ሀብት ጉዞ፤ ተፈጥሮ የሰጠን ይመስል ተቀብለነው የምንኖር ልማድ ሆኗል። መብራት ሲጠፋ ለመድነው፡፡ ውሃ ሲጠፋ ለመድን፡፡ ስልክ መስመር ሲጠፋ ለመድን፡፡ ኑሮ ሲከፋ ለመድን፡፡ ይሄንኑ ማማረርንም ለመድን… በመልመድ ተሞላን፡፡
ዛሬ በአገራችን ኢ-ሜይል ሳይሆን “ስኔይል” ተሽሏል እየተባለ ነው፡፡ ከኢሜይል ይልቅ የቀንድ-አውጣ ጉዞ ይሻላል እንደ ማለት ነው፡፡ በአጠቃላይ አነጋገር እየተንቀረፈፍን ነው፡፡ የቴሌ ሥርዓት ዋናው አንቀርፋፊያችን ነው እተባለ ነው፡፡ በእንሰቅርት ላይ ጆሮ ደግፋችን መዓት ነው!
Death and taxes and childbirth! There’s never any convenient time for any of them!
የ “ነገም ሌላ ቀን ነው” ደራሲ ማርጋሬት ሚሼል “ሞት፣ ቀረጥ እና ልጅ-መውለድ ምኔም ምቹ ጊዜ ኖሮት አያውቅም” ትላለች፡፡ ምጡ ከደረሰ ማሰቃየቱ አይቀርም ነው፡፡ ሦስቱ አንድ ላይ ሲመጣማ የመርገምት ሁሉ መርገምት ነው፡፡
በ11ኛው ሰዓት ይላሉ ፈረንጆች፡፡ አዬ፤ አማርኛ ቢያውቁ “ሰርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ” ይሉ ነበረ። ይሄንን ክፉኛ ለምደናል፡፡ ዕዳ የምንከፍለው በ11ኛው ሰዓት ነው፡፡ ስልክ የምንከፍለው በ11ኛው ሰዓት ነው። (ስልክ ባይኖርም)!! መብራት የምንከፍለው በ11ኛው ሰዓት (ውሃው ባይኖርም)!! ለፈተና የምናጠናው በ11ኛው ሰዓት (ትምህርት ቢደክምም ባይደክምም)!! ወደ ሐኪም የምንሄደው በ11ኛው ሰዓት!! (ቢጭበረበርም ባይጭበረበርም)!! ይሄን ልማድ ካልተውን መቼም ህይወትን አንረታም፤ ባላንጣችንንም ተፎካካሪያችንንም አናሸንፍም!!
ሼክስፒር በፀጋዬ ገ/መድህን ብዕር፤
“ዛሬ ለወግ ያደረግሺው፣ ወይ ለነገ ይለምድብሻል
ልማድ ፊት እንዳሳዩት ነው፣ ወይ ይጠፋል ወይ ያጠፋል
ከርሞም የሰለጠነ እንደሁ፣ ተፈጥሮ ይሆናል ይባላል”፡፡ የሚለን ለዚህ ነው፡፡”    

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ…ተቀምጠን እየሰቀልን እኮ ቆመን ማውረድ አቃተንሳ! ልክ ነዋ…ይኸው በምኑም፣ በምናምኑም በአጋጣሚም ቢሆን ‘ወደ ላይ’ ያወጣናቸው “አይ፣ በቃችሁ…” ምናምን ስንል የሚሰማን አጣን፡፡
እኔ የምለው… መቼም ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… “የተሸነፍነው ስፖርት ጋዜጠኞቹ ግራ አጋብተውን ነው…” ምናምን ተባለ የተባለው…በቃ እንደዚህ የ‘ቻርሊ ቻፕሊን ወራሾች’ ምናምን ሆነን እንቅር! ጭራሽ ታክቲክና ስትራቴጂ በጋዜጠኞች ሆነና አረፈው!
ችግሩ ምን መሰላችሁ…በዛ መያዣ መጨበጫ ባጣን ሰሞን ጋዜጠኞች የኳስ ሰዎቻችንን አወጣን አወጣንና እላይ ‘ጉብ’ ማድረግ! ነገሩ ሲረጋጋና ጎል እያቃሙንና ውራ እያደረጉን ሲልኩን “ለነገሩ እኮ ብዙ ይቀራችኋል…” ሲባል ማን ይስማ! እናላችሁ… እንዲሁ “ከዚህ ያክል ቡድኖች መካከል ምርጥ ተባልን…” “ዓለም በጉጉት የሚጠብቀው የናይጄሪያና የኢትዮጵያ ጨዋታ…” እያልን ነገር ስናሳምር ከረምንና ጭራሽ ቤተክርስትያን የገባች እንትን ጋዜጠኞች ሆነው አረፉት!
(ለነገሩ እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…አንዳንዶቻችን ጋዜጠኞችም እኮ አለ አይደል…ስናደንቅ ‘ቃላት አመራረጥ’ አልቻልንበትም ነበር፡፡ ቀስ ብለን በምትንቃቃ መሰላል በጥንቃቄ እየተረገጠ እንዲወጣ ከማድረግ ይልቅ መንኮራኩር ውስጥ ከተን እንተኩስና ከዛ ማውረዱ መከራ፡፡
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
ደግሞላችሁ…በስነ ጥበባችን አካባቢ መኮፈስ፣ ‘ማበጥ’፣ ምናምን በሽ እንደሆነ ነው የሚወራው። እናላችሁ…አንድ ፊልም ሲወጣ ለስፖንሰርሺፕ እንዲመችም፣ ለፈረንካውም “መቼም ግሩም የሆነ ፊልም” “ግሩም ትወና” ይባልና ሰዉ ሆዬ ያለክሬንና ያለክንፍ ላይ ወጥቶ ቁብ!
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
እናላችሁ… ያስቸገረን ነገር ኖር ከተሰቀሉበት ማማ ለመውረድ ፈቃደኛ አለመሆን ነው፡፡ አንድ ሰሞን እግር ኳሳችንን  ጄኔቭ ድረስ ሲያሯሩጥ የነበረው… ውረድ እንውረድ ብሎ ነገር የለም፡፡
ደግሞላችሁ…አንዳንድ ምሁራን ዘንድ ብትሄዱ…አለ አይደል… በቤተሰብ ጉባኤ፣ የቢራውን ሂሳብ እንዴት ‘እንደሚያዘጋ’ ዘዴው የገባው… የዓይን መነጽር የሚሰካና የኮቱን ኮሌታ ገደድ የሚያደርግ ሁሉ የአሪስቶትል ደቀ መዝሙር የሚያደርግ ምስኪን ተማሪ… ላይ አውጥተው ያስቀምጧቸውና እንዴት ይውረዱ! “ኧረ እንደ እሱ አይነት ችሎታ ያላቸው መአት አሉ፣ እነሱ እንኳን ላይ ሄደው ሊሰቀሉ አጠገባቸው መሰላልም አሳንሰርም የለም…” ሲባሉ ማን ሰምቶ! ነገርዬው… “እኔን ውረድ የምትሉኝ ማናችሁና ነው…” አይነት ነገር ነው፡፡
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
ሙዚቃ አካባቢ ብትሄዱ… አለ አይደል… አንዱ ዕድለኛ አንድ ሲንግል ይለቅና ምን አለፋችሁ፣ እዚህም እዛም የእሱ ዘፈን ከተማውን ሰቅዞ ይይዘዋል፡፡ ዕድሜ ለኤፍ ኤሞች ምን ችግር አለ! (እኔ እንደውም ከዕለታት አንድ ቀን “ኤፍ ኤም ላይ ‘እንዲህ ተደብቆ የከረመው ድምፀ መረዋ…’ ምናምን የሚሉኝ ከሆነ ሲንግል የማልለቅሳ!” ማለቴ አይቀርም፡፡
እናላችሁ…አንዳንድ ፕሮግራሞች ላይ ስለሆነ ሙዚቃ ወይም ስለ ፊልም ሲወራ ግርም ይላችሁና… “እንደው የሥራው ባለቤቶች የዚሀ አይነት ከመሬት እጅግ ከፍ ብሎ ከመንግሥተ ሰማያት ትንሽ መለስ የሚል አደናቆት ለራሳቸው ይሰጣሉ?” ያሰኛችኋል፡፡
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
አንድ የሆነ የማስቲካም ይሁን የመኪና ማስታወቂያ ላይ ሁለት ቀን ብልጭ ብላ የጠፋች እንትናዬ…በቃ ላይ ወጥታ ጉብ! “ኧረ ቀስ ብለሽ ተራመጅ፣ እንደ ሞዴል ‘ለመነስነስ’ ትደርሽበታለሽ…” ቢባል ማን ሰምቶ! በዚህ ላይ ደግሞ ዙሪያዋን ከበው “አንቺ እኮ የሀበሻ ክሌኦፓትራ ማለት ነሽ…” ምናምን የሚላት አሟሟቂ መአት ስለሆነ ኮከቦቹን ልትነካ ደርሳ ‘ማን፣ ኧረ ማን’ ነው ውረጂ የሚላት!”
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
እናላችሁ… የእልፍኝ አስከልካይ ረዳት እንኳን ሳንሆን እንደ ናፖሊዮንነት የሚቃጣን…አለ አይደል… ላይ አውጥተው ሲሰቅሉን ነው፡፡ ስሙኝማ…ምን ይገርመኛል መሰላችሁ…ሰዋችን ከደግነትም ይሁን፣ “ቲራቲር እንሥራበት …” ከማለት ሲያመሰግንና ሲክብ ምን አለፋችሁ…“አሞራ በሰማይ ሲያይሽ ዋለ…” አይነት ነገር ነው፡፡
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
እናላችሁ፣ ነገርዬው እኮ… አለ አይደል… ሰውን የማይሆን ቦታ አውጥቶ ጉብ ማደረግ፣ ልክ ለራሰ በራ ሰው ለልደቱ የማበጠሪያ ስጦታ እንደመስጠት ነው። አሃ፣ ምን ያደርግለታል… አንደኛውን ጭንቄውን ሊነቀስበት ካልሆነ፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
(“ኧረ የራስህ ጭንቄ! ሁለተኛ፣ አይደለም ክትፎና አሮስቶ ዲቢቴሎ ጮርናቄ እንኳን አታገኛትም። ማበጠሪያህን ብላ…” ምናምን የምትሉ ወዳጆቼ ብስጭታችሁ ስለገባኝ ደብዳቤ ሳታስገቡ፣ ኮሚቴ ሳይቋቋም ይቅርታ አድርጌላችኋለሁ፡፡ የቮድካው ተረኛ ማን ነበር!)
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
ስሙኝማ… እግረ መንገዴን… እንደ ድሮ ቢሆን ኖሮ “ጥር የልጃገረድ ጠር…” አበቃ ማለት ነበር! ለነገሩ ጥያቄ አለን… ለጥር ብቻ የተሰጠው ‘የልጃገረድ ጠርነት ለአሥራ ሦስቱም ወራት ይሰጥልንማ! እኔ የምለው…በዛ ሰሞን፣ ‘ያልተነካ’ ምናምን ነገሩ አሥር ሺህ ብር ያወጣል ነው የተባለው! እኔ የምለው…እሱም እንደ ‘ክትፎ’… አለ አይደል… ‘ኖርማልና ስፔሻል’ ነገር አለው እንዴ! አሀ..ማወቅ አለብና! ነገ ድንገት ዲታ ከሆንን ምድረ ሀብታም ሲያደርግ የነበረውን ነገር ሁሉ “ምን የተለየ ነገር  ቢኖረው ነው! ብለን መሞከራችን አይቀርማ!
እግረ መንገዴን…በቀደም አንድ ድረ ገጽ ላይ “ባልና ሚስት መናጠቅ ብሶበታል” ምናምን የሚል ነገር አንብበን ነበር፡፡ አንድ ተረት አለች…
“አገባሻለሁ ያለ ላያገባሽ ከባልሽ ሆድ አትባባሽ”
ይሄ እንግዲህ ያኔ መነጠቅ እንግዲህ የሚያስፎክር ባልነበረበት ጊዜ ይባል የነበረ ነው፡፡
ዘንድሮ ግን ነገርዬው ተሻሽሎ ምን ሊባል ይችላል መሰላችሁ…
“ባልሽ ነኝ ያለሽ መወሸሙ ላይቀር፣ የማንን ጎፈሬ ታበጥሪ ነበር”
ቂ…ቂ…ቂ… ‘ግጥም ተገጠመ’ ይሏችኋል እንዲህ ነው!
እኔ የምለው…እንገዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… ማስታወቂያው ሁሉ ‘ግጥም፣ በግጥም’ የሆነው…የግጥም ምሽት ስለበዛ ነው እንዴ! ግራ ገባና…አንዳንዱ የማስታወቂያ ‘ግጥም ድርደራ’ እኮ…የድንጋይ ዘመን ትውስታ ነገር ይመስላል። ይሄኔ እኮ የእኔ ቢጤ አሟሟቂ “ፐ! የሠራኸውን ማስታወቂያ ስሰማ እኮ…ምን አልኩ መሰለህ…ይሄ ሰውዬ ኢትዮጵያ ውስጥ መወለድ አልነበረበትም ነው ያልኩት!” እያለ ‘እዛ ላይ’ ሰቅሏቸዋል!
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
ስሙኝማ…ቦተሊከኞችማ አንዴ ካወጧቸው… አለቀ በሉት! ማን ‘እናቱ የወለደችው’ ነው እነሱን ካሉበት ዙፋን ዝቅ ለማድረግ የሚሞክረውስ…አይደለም መሞከር ማንው የሚያስበውስ! ታዲያላችሁ… የአገራችንን መሽቶ ሲነጋ ‘ጠርቶ የማይጠራ’ ቦተሊካችንን ነገሬ ስትሉ የሚያባላን ስር የሰደደ እምነት ምናምን ሳይሆን ይቺ የ‘ውረድ እንውጣ’ ነገር አትመስላችሁም! “በሦስተኛው ዓለም ቦተሊካ ወጣህ ማለት በቃ ወጣህ ማለት ነው!” ብሎ እቅጩን የሚነግረን ሰው እየጠበቅን ነው፡፡ እናላችሁ…ዘላለም “ማን ባሞቀው ወንበር ማን ይቀመጣል፣ ሰማይ ከምድር ይደባለቃል! ” እየተባለ…የምንጨፍረው “ሠላሳ አንድ ዓመት…” ጠብቀን በምንገባባት የኳስ ውድድር ብቻ ሆኗል፡፡
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
ደህና ሰንብቱልኝማ!


የተሽከርካሪዎችን አቅምና ብቃት የሚለካ ቴክኖሎጂ ፈጥሯል

ኢትዮጵያዊው የምህንድስና ባለሙያ ናሆም በየነ ያቋቋመው ‘ኔቪቲ’ የተሰኘ የቴክኖሎጂ ኩባንያ፣ በየአመቱ በአሜሪካ በሚካሄደው ‘ኢቭሪዴይ ሄልዝ አዋርድስ ኦፍ ኢኖቬሽን’ የተባለ ሽልማት የመጨረሻው ዙር እጩ ተሸላሚ ሆነ፡፡
ኔቪቲ ኩባንያ ያመረተው ‘ናቪሴክሽን ሲስተም’ የተባለ የወጣቱ ኢትዮጵያዊ ፈጠራ፤ ‘ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ’ በተባለው ዘርፍ ለሽልማት ከተመረጡት የመጨረሻዎቹ እጩዎች አንዱ መሆኑ የተገለጸው፣ ላስቬጋስ ውስጥ በተካሄደው የዘንድሮው ዲጂታል ሄልዝ አመታዊ ጉባኤ ላይ እንደሆነ ታዲያስ መጽሄት ከኒዮርክ ዘግቧል፡፡
ኢትዮጵያዊው ናሆም ለሽልማቱ ያሳጨውን ፈጠራ የሰራው፣ በፒትስበርግ ዩኒቨርሲቲ ትምህርቱን በመከታተል ላይ በነበረበት ወቅት በ “ሪሃብሊቴሽን ሳይንስ” ዘርፍ ካከናወነው የዶክትሬት ድግሪ የመመረቂያ ጥናቱ በመነሳት እንደሆነ ተገልጿል፡፡የአሽከርካሪዎችን አቅምና ብቃት ለመለካት የሚያስችሉ መረጃዎችን በተደራጀ ሁኔታ ለመሰብሰብና በመንጃ ፈቃድ አሰጣጥና እድሳት ላይ ጉልህ አስተዋጽኦ ለማበርከት የሚችል የተቀናጀ ቴክኖሎጂ እንደሆነ የተነገረለት ‘ናቪሴክሽን ሲስተም’ በብዙዎች ዘንድ አድናቆትን ያገኘ ሲሆን፤ በአሽከርካሪዎች ደህንነት ላይ ለውጥ የሚፈጥር አዲስ ግኝት እንደሆነ እየተነገረለት ይገኛል፡፡
“የኩባንያዬ ግብ ቤተሰቦች መቼ ማሽከርከር መጀመርም ሆነ ማቆም እንደሚገባቸው የሚያሳይ መረጃ እንዲያገኙ ማድረግ ነው፡፡ አሁን አሁን ማሽከርከር የጤና ጉዳይ እየሆነ መጥቷል። ምክንያቱም በአለም ላይ ከሚከሰቱ የመኪና አደጋዎችና ግጭቶች 93 በመቶ የሚሆኑት ከአሽከርካሪዎች ስህተት ጋር በተያያዘ የሚፈጠሩ ናቸው፡፡” ብሏል፤ ናሆም፡፡
በአሜሪካ በአሽከርካሪዎች ደህንነት ላይ የሚታዩ ችግሮች፣ የመንጃ ፈቃድ አሰጣጥ ስርአቱን በቴክኖሎጂ ፈጠራ ማገዝ እንደሚገባ ማመላከታቸውን የጠቆመው ናሆም፤ ኩባንያው በቀጣይም በተለይ በእድሜያቸው ለጋ ለሆኑና ላረጁ ሰዎች የመንጃ ፈቃድ በሚሰጥበትና በሚታደስበት ጊዜ አግባብነቱን የሚያረጋግጡ መሰል የተሻሻሉ የመኪና ቴክኖሎጂዎችን የመፍጠር ስራውን በስፋት እንደሚቀጥል ተናግሯል፡፡
ናሆም የመጀመሪያ ዲግሪውን ከቴክሳስ ዩኒቨርሲቲ በሜካኒካል ኢንጂነሪንግ፣ሁለተኛ ዲግሪውን ደግሞ ከስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ በባዮ ሜካኒካል ኢንጂነሪንግ ተቀብሏል፡፡ ከፒትስበርግ ዩኒቨርሲቲም በ “ሪሃብሊቴሽን ሳይንስ” ዶክትሬቱን አግኝቷል፡፡ በ2012 “ኔቪቲ” የተባለ ኩባንያውን በማቋቋም ወደስራ ከመግባቱ በፊትም፣ በናሳ ጆንሰን የጠፈር ምርምር ማዕከል በኤሌክትሮኒክስና የኮምፒውተር መሳሪያዎች ዲዛይንና ፈጠራ መስክ ሲሰራ እንደቆየ ታውቋል።


13 ሺ ሠራተኞች ያስተዳድራል
ዘመናዊ ሆስፒታል፣ ት/ቤት፣ ስታዲየም፣ ፍ/ቤት ሠርቷል
ተባይን በአርተፊሻል ተባይ ያጠፋል
ባለቤቱ ለሕዳሴው ግድብ 25 ሚ.ብር ሰጥተዋል
ለአየር መንገድ በሳምንት 12 ሚ.ብር ይከፍላል

በኬንያ ትልቅ የአበባ እርሻ ነበራቸው። እንደቀድሞው አይሁን እንጂ አሁንም አለ፡፡ በኢትዮጵያ ኢንቨስት እንዲያደርጉ የጋበዟቸው በወቅቱ የንግድና ኢንዱስትሪ ሚ/ር የነበሩት አቶ ግርማ ብሩ ናቸው፡፡ ግብዣውን ከመቀበላቸው በፊት ግን ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታ እንዳለ አስጠኑ፡፡ ፍጹም ምቹ ባይሆንም መሥራት የሚያስችል ሆኖ አገኙት፡፡ ከዚያ በ1997 ዓ.ም በምሥራቅ ኦሮሚያ ዞን፣ በቱሉ ዲምቱ ወረዳ፣ በዝዋይ ከተማ በ500 ሄክታር መሬት ላይ በኢትዮጵያ ትልቁን የአበባ እርሻ በ80 ሚ.ዩሮ መሠረቱ - ሆላንዳዊው ሚ/ር ገረት ባርንሆርንና (Berrit Barnoorn) ልጃቸው ሚ/ር ፒተር ባርንሁርን፡፡ በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ወደ ውጭ ከምትልከው አበባ 65 በመቶው የዚህ እርሻ ምርት ነው፡፡ 13 ሺህ ሠራተኞች ያሉት ድርጅቱ፤40 የአበባ ዓይነት ያመርታል፡፡ ምርቱን በሙሉ የሚያቀርበው ለውጭ ገበያ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 95 በመቶውን የሚያቀርበው የአበባ ዋጋ ቢወደድም ሆነ ቢረክስ፣ በተወሰነ ዋጋ ለማቅረብ ለተስማማቸው ሱፐርማርኬቶችና ሱቆች ነው፡፡ 5 በመቶውን ብቻ ነው በጨረታ የሚሸጠው፤ ሼር ኢትዮጵያ፡፡

የኢትዮጵያ ሆርቲካልቸር (አበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ) አምራች ላኪዎች ማህበር፣ የአባሎቹን እርሻ እንድንጐበኝ በጋበዝን መሠረት፣ ጥቂቶቹን የአበባ እርሻዎች አይተናል፡፡ ለዛሬ ግን ሼር ኢትዮጵያ የአባባቢን ደህንነት ለመጠበቅና ማህበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት የሚያደርገውን ጥረት እናያለን፡፡ ሼር ኢትዮጵያ ምርቱን ወደ አውሮፓ ለሚያጓጉዝለት የኢትዮጵያ አየር መንገድ በየሳምንቱ 12 ሚሊዮን ብር እንደሚከፍል፣ የእርሻው ባለቤት ሚ/ር ገረት ባርንሆርን (በግላቸው) ለታላቁ ህዳሴ ግድብ 25 ሚሊዮን ብር መለገሳቸውንና ድርጅቱ ከቀድሞው ጠ/ሚ የኘላቲንየም ዋንጫ መሸለሙን የድርጅቱ ሕዝብ ግንኙነት ኦፊሰር አቶ ከማል ሁሴን ገልጸዋል፡፡ አሁን በጉብኝቱ ወቅት የታዘብኩትንና አቶ ከማል የነገሩንን ላጫውታችሁ፡፡ ሼር ካሉት 96 ግሪን ሀውሶች (የአበባ ማብቀያ ዳሶች) ወደ አንዱ ስንገባ፣ አቶ ከማል “ድሮ ቢሆን የኬሚካሉ ሽታ አያስገባችሁም ነበር፤ አሁን ግን ይኸው እንደምታዩት ምንም የለም” አሉ፡፡ የምን ኬሚካል? በማለት ጠየቅን፡፡ “አበባውን የሚያጠቁትን ተባዮች ለመከላከል ኬሚካል እንጠቀም ነበር፡፡

አሁን ግን ኬሚካል የምንጠቀመው ለፈንገስ ብቻ ነው፡፡ አበባ የሚያጠቁ ጀርሞችን ለማጥፋት የምንጠቀመው የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት እውቅና በሰጠው Integrated pest management control system Imps በተባለ ዘመናዊ ሰው ሠራሽ ዘዴ (አርቴፊሻል ጀርም) ነው፡፡ “ቅደም እዚያ ጋ ያያችኋት ልጅ እስካውት ትባላለች፡፡ የእሷ ሥራ፣ የአበቦቹን ቅጠሎች በሚያጐላ መነፅር (ማይክሮስኮፕ) እያየች ጀርም መኖሩን ማረጋገጥ ነው፡፡ ጀርም ካየች እዚያ ቦታ ላይ ነጭ ወረቀት ታስቀምጣለች፡፡ ‘እዚህ ቦታ አበባ የሚጠቃ ጀርም አለ’ ማለቷ ነው፡፡ ጀርሞችን ለማጥፋት የተመደቡ ሰዎች ደግሞ፣ አርቴፊሻል ጀርም ፈጣሪውን ዱቄት ነገር ያደርጉበታል፡፡ አርቴፊሻል ጀርሙ ይፈጠርና አበባ አጥቂዎቹን ጀርሞች እያሳደደ ከእነዕንቁላላቸውና ዕጫቸው ይበላቸዋል፡፡ አንዳንድ ሰዎች አርቴፊሻል ጀርሙስ በአባባቢ ላይ ጉዳት አይፈጥርም ወይ በማለት ይጠይቃሉ፡፡ ነገር ግን ምንም ጉዳት አይፈጥርም፡፡ ምክንያቱም እውነተኛው ጀርም ከሌለ አርቲፊሻሉ የሚበላው ነገር ስለሌለው ይሞታል” በማለት አስረድተዋል፡፡ በተንጣለለው የሼር ኢትዮጵያ ግቢ ውስጥ ብቻውን አይደለም ያለው፡፡ ከሼር ውጭ የራሳቸው አስተደደር ያላቸው ዝዋይ ሮዝ፣ ኤክው፣ አርበርና ኘራም የተባሉ አበባ አምራች ድርጅቶች አሉ፡፡ እነዚህ ራሳቸውን የቻሉ ድርጅቶች ቢሆኑም በሼር ስር ናቸው፡፡ ሼር 13 ሺ ሠራተኞች አሉት ሲባል የአራቱን ድርጅቶች ሠራተኞች ጨምሮ ነው፡፡ አፍሪ ፍሎራ / Afri flora / የሚለው ስም ከሼር ኢትዮጵያ ጋር ተያይዞ ስላየን ምንድን ነው? ብለን ጠየቅን፡፡ የሼር ኢትዮጵያን የአበባ ምርት በመላው ዓለም የሚሸጥና የድርጅቱ የንግድ ምልክት መሆኑን አቶ ከማል ነገሩን፡፡

ይህ ብቻ አይደለም። አፍሪ ፍሎራ ከሼር ውጭ የሆነ የራሱ አስተዳደር ያለው፣ ለድሃው ሠራተኛ የቆመ፣ ሚዛናዊ የአበባ ሽያጭ ተካሂዶ ሠራተኛውም ከሽያጩ እንዲጠቀም የሚያደርግ ፌር ትሬድ (Fair Trade) አራማጅ የግል ድርጅት ነው፡፡ ሼር የዚህ ድርጅት አባል ስለሆነ፣ ሠራተኞቹም ከፌር ትሬድ ከሚገኘው ሽያጭ ገቢ ተጠቃሚ ናቸው፡፡ እንዴት መሰላችሁ፣ የአንድ አበባ ዋጋ አንድ ዩሮ ቢሆን በፌር ትሬድ ዓላማ መሠረት አፍሪ ፍሎራ በሁለት ዩሮ ይሸጥና አንዷን ዩሮ ለሠራተኛው ያደርጋል፡፡ በዚህ ዓይነት ሠራተኛው የሽያጩን ግማሽ ያገኛል ማለት ነው፡፡ ታዲያ ገንዘቡ በጥሬው መጥቶ ለሠራተኛው በጥሬው አይከፋፈልም፡፡ የሠራተኛውን ጤናና ደህንነት ለማስጠበቅ፣ ሙያዊ ክህሎቱን ለማዳበርና ለማሻሻል …. በአጠቃላይ ሠራተኛውን ለሚጠቅም ነገር ይውላል፡፡ በዚህ መልኩ ከፌር ትሬድ የሚመጣውን ገንዘብ ሼር ኢትዮጵያ የሚያስተዳድረው ብቻውን ሳይሆን ከሠራተኛው ከተመረጠ ኮሚቴ ጋር ነው፡፡ ሼር ኢትዮጵያ ለሠራተኞቹና ለህብረተሰቡ ካደረገው ነገር አንዱ ሁሉም ሠራተኞች በነጻ፣ የዝዋይ ከተማና የአካባቢው ነዋሪዎች ደግሞ በአነስተኛ ክፍያ የሚታከሙበት ሆስፒታል መገንባቱ ነው፡፡ ከስድስት ዓመት በፊት ከ100 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተሠራው ዘመናዊ ሆስፒታል፤ የዘመኑ ቴክኖሎጂ ውጤት የተገጠመለት ስለሆነ በሚሰጠው የሕክምና አገልግሎት ዘመናዊነት አዲስ አበባ ከሚገኘው ኮሪያ ሆስፒታል ቀጥሎ ይመደባል ተብሏል፡፡ “ከኬንያ የመጣ ሶፍትዌር የተገጠመለት ሲሆን ከካርድ ክፍል እስከ ምርመራ፣ ላቦራቶሪ፣ ፋርማሲ፣ አልጋ ክፍሎች…. ድረስ በኔትዎርክ ስለተያያዙ በሆስፒታሉ የወረቀት ሥራ የለም፣ በሽተኛው ለሕክምና ወደ ሆስፒታሉ ሲመጣ የተሰጠውን ቁጥር እያሳየ አስፈላጊውን አገልግሎት ያገኛል” ይላሉ ኦፊሰሩ፡፡ እንደማንኛውም ሆስፒታል፣ ተኝተውና በተመላላሽ ለሚታከሙ ሕሙማን ሁሉን አቀፍ የመከላከልና የማከም አገልግሎት እንደሚሰጡ የሆስፒታሉ ሜዲካል ዳይሬክተር ዶ/ር ደምሳቸው ጌታቸው ገልጸዋል፡፡ በዚህ አካባቢ በ100 ኪ.ሜ ዙሪያ ሆስፒታል ያለው አዳማና ሻሸመኔ ነው፡፡

የመውለጃ ቀኗ የደረሰ ሴት ሆስፒታል ወደሚገኝበት ስትወሰድ አጣዳፊ ምጥ ይዟት፣ ጨቅላውም ሆነ የእናቲቱ ጤና ችግር ላይ እንዳይወድቅ ሆስፒታሉ አማራጭ ሆኗል ብለዋል ዶ/ር ደምሳቸው፡፡ 140 አልጋ፣ ሁለት ስፔሻሊስት ሐኪም (የጽንስና የማህጸን እንዲሁም የቀዶ ሕክምና)፣ 6 ጠቅላላ ሐኪም፣ 4 የጤና መኮንን፣ 3ዐ ነርሶች፣ 7 አዋላጆች በአጠቃላይ 147 ሠራተኞች እንዳሏቸው የጠቀሱት ሚዲካል ዳይሬክተሩ፤ በቀን ከ300 በላይ ለሆኑ ተመላላሽ ታካሚዎች አገልግሎት እንደሚሰጡም ተናግረዋል፡፡ እንደማንኛውም ሆስፒታል መንግሥት በሚከተለው የጤና ፖሊሲ መሠረት የሕጻናት ክትባት፣ ለነፍሰ ጡሮች የጽንስና የማኅፀን ክትትል፣ የወባ፣ የቲቢ፣ የኤች አይቪ ኤድስ…. ሕክምና በነጻ ይሰጣል፡፡ በአጠቃላይ በማንኛውም በሽታ፣ ሠራተኛውን በነጻ፣ የአካባቢውን ማህበረተሰብ በአነስተኛ ክፍያ ያክማል፡፡ በሆስፒታሉ አጐቷን አስተኝታ ስታስታምም ያገኘናት ራሄል ባህሩም፤ ለካርድ 15 ብር፣ በቀን ደግሞ ለአልጋ 45 ብር እንደሚከፍሉ ገልጻ፣ ከግል ሐኪም ቤቶች ጋር ሲነጻጸር ተመጣጣኝ መሆኑን ገልጻለች፡፡ “ሆስፒታሉ የግል ቢሆንም የአካባቢውን ነዋሪ እንደ መንግሥት ሆስፒታል አነስተኛ ዋጋ ነው የምናስከፍለው፡፡ ለምሣሌ ለካርድ 15 ብር፣ ተኝቶ ለሚታከም በሽተኛ ቁርስ ምሣ ራት በልቶ፣ የሐኪምና የነርስ ክትትል ተደርጐለት በቀን 45 ብር ነው የምናስከፍለው፡፡ ክፍያው ከሌላ የሕክምና ተቋም ጋር ሲነጻጸር ነጻ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ለድርጅቱ ሠራተኞች ቀዶ ሕክምናን ጨምሮ ሁሉም ሕክምና በነጻ ነው፡፡ ከአቅም በላይ ከሆነ ደግሞ ኬንያ ልከን እናሳክማለን” ብለዋል ዶ/ር ደምሳቸው፡፡ ሌላው ሼር ኢትዮጵያ ለማህበረሰቡ እየሰጠ ያለው አገልግሎት በትምህርት ዘርፍ ነው፡፡

በመዋለ ህፃናት የጀመረው ሼር ኢትዮጵያ ት/ቤት ዘንድሮ 9ኛ ክፍል ከፍቷል፡፡ አቶ ግርማ ቢሆን የሼር ኢትዮጵያ ት/ቤት ዳይሬክተር ናቸው፡፡ ት/ቤቱ በዚህ ዓመት ግማሹ የሠራተኛው ልጆች፣ ቀሪው ግማሽ ደግሞ ከዝዋይ ከተማና ከአካባቢው ማህበረሰብ አቅም እንደሌላቸው አስመስክረው የተቀበሏቸውን 4,200 ተማሪዎች በነፃ እያስተማሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በመንግስትም ሆነ በግል ት/ቤቶች የማይታዩ አሠራሮች እዚህ ይገኛሉ፡፡ ት/ቤቱ የሚገኘው በኦሮሚያ ክልል ቢሆንም ትምህርት የሚሰጠው በአፋን ኦሮሞና በአማርኛ ቋንቋ ነው፡፡ አቶ ግርማ፤ ወላጅ ልጁን አምጥቶ ሲያስመዘግብ ይማርልኝ ብሎ ባስመዘገበው አፍ መፍቻ ቋንቋ በኦሮምኛ ወይም በአማርኛ እናስተምራለን፡፡ በመዋለ ህፃናት በሁለቱም ቋንቋ የሚማሩ 1500 ያህል ህጻናት ሲኖሩ በ24 ክፍሎች ተደልድለው ይማራሉ፡፡ በሁለቱም ቋንቋ አሁን በ1 ኛ 2ኛ፣3ኛ፣4ኛ አራት አራት ክፍሎች እናስተምራለን፡፡ ከ8ኛ በላይ ግን የምናስተምረው በእንግሊዝኛ ነው፡፡ አሁን 89 መምህራን ሲኖሩን አብዛኞቹ በዲግሪ የተመረቁ ናቸው፡፡ ላቦራቶሪው ጥቃቅን ነገሮችን አጉልቶ በሚያሣይ ዘመናዊ አጉይ መነፅሮች (ማይክሮስኮፕ) እና ለመማር በሚረዱ ቁሣቁሶች ተሟልቷል፡፡ የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ (አይሲቲ) ላቦራቶሪ በበርካታ ኮምፒዩተሮችና ባለሙያዎች የተደራጀ ስለሆነ፣ ህፃናት ከሁለተኛ ክፍል ነው የኮምፒዩተር ትምህርት የሚጀምሩት፡፡

የ5ኛ ክፍል ተማሪ ፎቶሾፕ ስትሠራ አይተናል፡፡ ቤተ መጻህፍቱ በትምህርት ሚኒስቴር ካሪኩለም መሠረት በአዳዲስ መጻህፍት ተሞልቷል፡፡ በት/ቤቱ የደረስነው በምሳ ሰዓት አካባቢ ስለነበር፣ መዋለ ህፃናት የሚማሩ ህፃናት ተሰልፈው ምሣ ወደ ሚበሉበት አዳራሽ ሲገቡ ተመለከትን። ህፃናቱ የድሃ ልጆች ስለሆኑ ቁርስና ምሣ በነፃ እንደሚበሉ፣ ዩኒፎርም፣ መጻሕፍት፣ ደብተርና እስክሪብቶ በነፃ እንደሚሰጣቸው ተነገረን፡፡ የሼር ኢትዮጵያ ባለቤት ሚ/ር ገረት ባርንሁርን “በአገሬ እየተራበ የሚማር ሰው አይቼ አላውቅም” ብለዋል፡፡ “በመማር ማስተማር ሂደት አንዳችም ችግር የለብንም፤ በወር አንድ ጊዜ ከእርሻው ባለቤት ጋር ተቀምጠን እንወያያለን፡፡ የሆነ ችግር ቢያጋጥመን እዚያው እናቀርብና ፈጣን ምላሽ ይሰጡናል፡፡ በቅርቡ እንኳ ለ9ኛ ክፍሎች ትምህርት ሚኒስቴር ያወጣቸውን አዳዲስ መጻህፍት 93 ሺህ ብር አውጥተው ገዝተውልናል” ብለዋል አቶ ግርማ፡፡ የልጆቹስ ውጤት እንዴት ነው? አልናቸው አቶ ግርማን፡፡ “የልጆቹ ውጤት በጣም ጥሩ ነው። በቅርቡ በምስራቅ ሸዋ ዞን 13 ወረዳ ት/ቤቶች መካከል በተደረገ ውድድር 1ኛ የወጣው የእኛ ተማሪ ነው፡፡

ባለፈው ዓመት የ8ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና የወሰዱ ተማሪዎቻችን 100 ፐርሰንት ነው ያለÕት። በ10ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተናም 100 ፐርሰንት ለማሣለፍ ብቻ ሳይሆን ውጤታቸውም በጣም ከፍ እንዲል እየሠራን ነው” ብለዋል፡፡ ሚ/ር ባርንሁርን፤ “ሼር ኢትዮጵያ በመላው ዓለም በጣም ተወዳጅና ስመጥር እንደሆነው ሁሉ ሼር ኢትዮጵያ ትምህርት ቤትም ታዋቂ እንዲሆን እፈልጋለሁ፡፡ ለዚህም አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ አደርጋለሁ፡፡ ተማሪዎችን የመቀበል አቅሙ ከ10 በመቶ ወደ 15 በመቶ ማደጉን አይቻለሁ፡፡ በዚህም ‘ትምህርት ለሁሉም’ የሚለውን የተባበሩት መንግስታት የሚሌኒየም ልማት ግብ እያሟላን ነው ብለዋል፡፡ሼር ኢትዮጵያ በተመሣሣይ ስም ተመዝግቦ በብሔራዊ ሊግ የሚጫወት የእግር ኳስ ቡድን አለው፡፡ ድርጅቱ ለዚህ ክለብ በዝዋይ ከተማ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያሟላ ስታዲየም ሠርቷል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሼር ኢትዮጵያ ለአዳሚቱሉ ወረዳ ዘመናዊና ለፍርድ ሂደት አስፈላጊ የሆኑ የፍ/ቤት ቁሣቁሶች የተገጠመለት እንዲሁም ብሮድባንድ ኢንተርኔት ያለው ደረጃውን የጠበቀ ፍ/ቤት ሠርቶ አስረክቧል፡፡ የአካባቢ ደህንነትን ለመጠበቅም ሠራተኞቹን በማስተባበር ዛፍ እየተከለ ነው፡፡ የዛፍ ተከላ ፕሮግራሙ የተጀመረው አምና ቢሆንም ከ26 ሺህ በላይ ችግኞች በዝዋይ ከተማ ብቻ ሳይሆን በገጠሩም አካባቢ ተተክለው፣ ድርጅቱ የችግኞቹን እድገት የሚከታተሉ ሠራተኞች መመደቡን አቶ ከማል አስረድተዋል፡፡ ከአበባው እርሻ የሚፈሰው ውሃ ወደ ሐይቁ ገብቶ እንዳያበላሽ ከሆላንድ መንግሥት ጋር በመተባበር፣ ውሃ የሚጠራቀምበት ጉድጓድ ቆፍሮ፣ ውሃው ተጣርቶ በሪሳይክሊንግ ተመልሶ አበባውን እንዲያጠጣ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

አንበሳ የኢትዮጵያዊነታችን ትልቅ መገለጫ ነው
በሽያጭ የኦሮምኛ ዘፈኖችን የሚወዳደራቸው የለም

ዝነኛው ድምጻዊ ታደለ ሮባ በቅርቡ “ምስጋና” የተሰኘ አዲስ አልበም አውጥቷል፡፡ ከሙያ ባልደረባው ብርሃኑ ተዘራ ጋር
4 አልበሞችን ቢያወጣም ሙሉ አልበም ለብቻው ሲያወጣ ግን የአሁኑ የመጀመሪያው ነው፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ
አበባየሁ ገበያው በሙያውና በህይወቱ ዙርያ አነጋግራዋለች፡፡

በቀበሌ ኪነት በኩል ነው ወደ ሙዚቃ የገባኸው ወይስ በሌላ?
አዎ፤ የ12 ቀበሌ የታዳጊ ኪነት ቡድን ውስጥ እጫወት ነበር፡፡ አሊ ቢራ የሰፈራችን ልጅ ነው፡፡ ያኔ ትንሽ ስለነበርኩ

በደንብ አላስታውስም እንጂ የጊታሯን አምፕሊፋየር የሰጠን እሱ ነበር፡፡  እንደ አጋጣሚ ሆኖ ደግሞ የአሊ ቢራ ዘፈኖች

“እንጀራዬ” ሆኑ፡፡ ዛሬ ለደረስኩበት ደረጃ የእሱ አስተዋጽኦ ቀላል አይደለም፡፡
ተወልደህ ያደግህበት ሰባተኛ የአርቲስቶች መፍለቂያ ነው፡፡ ከሰፈሩ ብዙ አርቲስቶች የወጡበትምክንያት ምን

ይመስልሃል? ከውሃው ይሆን እንዴ?
አዎ…እነጐሳዬ፣ አለማየሁ ሂርጳ፣ አብዱ ኪያር፣ ቴዲ አፍሮ፣ አብነት አጐናፍር፣ ወንድሙ ጅራ፣ መውደድ ክብሩ… የእዛ

አካባቢ ልጆች ናቸው፡፡ በተወዛዋዥነትም ብዙ አሉ - ከዚያ ሰፈር የወጡ። እንደሚመስለኝ የመርካቶ ጐረቤት በሆኑ

ሰፈሮች ያደጉ ልጆች ድፍረት አላቸው፡፡ ድፍረትም ታለንትም፡፡ የቦሌ ልጅ ሆነው ከግቢ የማይወጡ፣ ታለንቱ

ቢናራቸውም ላይጠቀሙበት ይችላሉ። ደግሞ የእኛ ሰፈር አርቲስቶች ብቻ ሳይሆኑ ትላልቅ የእግር ኳስ ተጫዋቾችም

የወጡበት ነው። የቡናና የጊዮርጊስ ተጫዋቾች የማን መሰሉሽ? ዛሬ ግን ሰፈራችን ሜዳ የለም፤  ኳስ ሜዳው ፎቅ

ተሰርቶበታል፤ አስራ ሰባት ሜዳም ትምህርት ቤት ሆኗል፡፡ ለእዚህ እኮ ነው የብሔራዊ ቡድኑ ተጫዋቾች የክፍለ ሀገር

ልጆች ብቻ የሆኑት፡፡ የሜዳው ነገር ሊታሰብበት ይገባል፡፡  
እስቲ ስለ “ላፎንቴ”… አመሰራረት ንገረኝ…
ነፍሱን ይማርና የላፎንቴን አንደኛው አባል የነበረው ፀጋቸው የሚባል ጓደኛችንና አለማየሁ ኢርጳ አሮሠ ሆቴል ይሠሩ

ነበር፡፡ “ጐበዝ ልጅ አለ” ብለው  ለአሮሠ ሆቴል ባለቤት ለአቶ ሮባ ነገሩትናእኔም እዛ መጫወት ጀመርኩ፡፡ አሮሠ ሳለሁ

የማልጫወተው ዘፈን አልነበረም፡፡ ኪሱዋሂሊ፣ ጉራጊኛ፣ ሱዳንኛ፣ አረብኛ፣ እንግሊዝኛ፣ ኦሮምኛና ትግርኛ ሁሉ እሠራ

ነበር፡፡ ከተፋ ስትሰሪ  ይሄ የሚጠበቅ ነው፡፡ እዛ እየሠራን ሳለ “ያየህራድ አላምረው ሮያል ፓላስ” የሚባል ቤት

ተከፈተ። እዚያ ቤት ከተማው ውስጥ አሉ የተባሉ ዘፋኞች ይሰሩ ነበር፡፡ እኛም ለጥቂት ወራት እዛ ከሰራን በኋላ እኔ፣

አበበ ተካ፣ ብርሃኑ ተዘራና ፀጋቸው ሆነን “ላፎንቴን” በሚል ስራ ጀመርን፡፡ አበበ ወዲያው ወጣ፡፡
አንድ ጊዜ የኦሮምኛ ዘፋኞች ተሰባስባችሁ ማህበር ለማቋቋም ስትንቀሳቀሱ ነበር፡፡ ምን ደረሰ? ዓላማውስ ምን ነበር?
አዎ አንድ ማህበር በኦሮምኛ ዘፋኞች ተቋቁሞ ነበር፡፡ ስብስባው ጨፌ ላይ ነበር የተደረገው። እንቅስቃሴው አሁን ምን

ደረጃ ላይ እንደደረሰ አላውቅም፡፡ የኮፒ ራይት ጥሰትን ለማስቀረት ጠበቅ ብሎና በደንብ ታስቦበት ቢሰራ ጥሩ ነበር፡፡

በነገራችን ላይ በሽያጭ በኩል የኦሮምኛ ዘፈኖችን የሚወዳደራቸው የለም፡፡ እኛ የማናውቃቸው ዘፋኞች አሉ - ሃረር፣

አርሲ፣ ባሌ… የእነሱ አልበም እስከ 100 ሺ ቅጂዎች ይሸጣል፡፡ የእኛ እኮ እንደነሱ አይሸጥም፡፡ የእነሱ እንደገና “በርን”

ባይደረግ …. ሶስት መቶ ሺና ከዛም በላይ ይሸጥ ነበር፡፡  
በሙዚቃ ሥራ ምን ያህል አድጌያለሁ ትላለህ?
የትምህርት መጨረሻ የለውም፡፡ ግን በሙዚቃ ሥራ በስያለሁ፡፡ በፊት እየዘፈንኩኝ ሳላውቀው፤ ከቅኝት (ሪትም) ሁሉ

እወጣ ነበር፡፡ አሁን በደንብ በስየበታለሁ፤ ግን ገና ይቀረኛል፡፡ በሙዚቃ መሳሪያ በኩል ጊታርና ኪቦርድ ለራሴ መጫወት

እችላለሁ። መማሩና መብሰሉ ነገም የሚቀጥል ሂደት ነው፡፡
የአዲሱ አልበምህ ሽፋን ላይ በአንበሶች ተከበህ ትታያለህ፡፡ አንበሶች ትወዳለህ ወይስ ሌላ ትርጉም አለው?
ከልጅነቴ ጀምሮ አንበሳ እወዳለሁ፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን ከጥንት ጀምሮ (በአባቶቻችን ዘመን) በአንበሶች ታጅበን ነበር

የምንዋጋው፡፡ ከትውልድ እስከ ትውልድ ብዙ ነገሮቻችን የአንበሳ ነበረ፡፡ አንበሳ አውቶብስ፣ የአየር መንገድና የቴሌ

አርማ …ብቻ የተለያዩ ነገሮቻችን የአንበሳ አርማ ነበራቸው፡፡ አንበሳ የኢትዮጵያዊነታችን ትልቅ መገለጫ ነው ብዬ

አምናለሁ፡፡ ከአንቺና ከእኔ ጀምሮ አንበሶች ነን…አንቺ አሁን የሴት አንበሳ ነሽ፡፡
እርግጠኛ ነህ?
አዎ! የሴት አንበሳ ነሽ…/ሳቅ/ እኔ ደግሞ በእምነቴ ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ነኝ፡፡ ግን ኮኮቤ ሊዮ ነው - ባላምንበትም፡፡

ሊዮ ደግሞ ምልክቱ አንበሳ ነው። በዚህ የአንበሳ ፍቅሬ ነው በአንበሶች ታጅቤ የምታይኝ፡፡ እንደ ንጉስ ለመሆን ወይንም

ፖለቲከኛ ሆኜ አይደለም፡፡ ከህፃንነቴ ጀምሮ አንበሳ እወዳለሁ። አንድ ሰው የሚፈልገው ነገር ማድረግ አለበት የሚል

እምነት ስላለኝ የምፈልገውን አድርጌያለሁ፡፡ በአልበሙ ላይ የሚታዩት ሁለቱ የእውነት አንበሶች ሲሆኑ እኔ ደግሞ የሰው

አንበሳ ነኝ፡፡
በምትሰራቸው ነጠላ ዜማም ይሁን ሙሉ አልበም ላይ አዳዲስ ወጣቶችን በፊቸሪንግ ታስገባለህ? ወጣቶቹን ለማገዝ

አስበህ ነው?
እንደ አቅሜ ሙዚቃ የማዳመጥ ችሎታ አለኝ ብዬ እገምታለሁ፡፡ እኔ የማሰራቸው ልጆች ችሎታውና ተሰጥኦው

ቢኖራቸውም ምቹ ዕድልና መድረክ ላያገኙ ይችላሉ፡፡ እኛ ደግሞ በህዝብ ውስጥ አለን..እናም አዳዲስ ልጆች ከእኛ ጋር

በመሆን ከህዝብ ጋር መተዋወቅ  አለባቸው ብዬ አምናለሁ። በዚህ እነሱም እኛም እንጠቀማለን፡፡ ችሎታቸውን

ስለምናደንቅ ነው የምናሰራቸው፡፡ በፊት ከላፎንቴን ጋር ፊቸሪንግ የሰሩ ልጆች በሙሉ አሁን ትላልቅ ቦታ ደርሰዋል፡፡

ሁሉም ራሳቸውን ችለው ቆመዋል፡፡
ወደ ፊልም ኢንዱስትሪው እየመጣህ ነው አይደል?
አዎ፡፡ ወደ ፊልም ገብቻለሁ፤ በቅርቡ የሚወጣ ፊልም አለኝ፡፡ እግዚአብሄር ካስተካከለው የተመልካችን አስተያየት አይቼ

ወደፊት የምቀጥልበት ይሆናል፡፡
የአልበም ስራ በሌለ ጊዜ ምንድነው የምትሰራው? ናይት ክለብ…
እኔ ብዙ ጊዜ እዚህ አልሰራም፡፡ ከኢትዮጵያ ውጭ ነው፡፡ አሁን ግን አልበሜን ከሰራሁ በኋላ ማናጀሬና ማርኬቲንጉ

አንዳንድ ነገሮችን እያጠኑ ነው፡፡ ባለፈው ጎንደር ሄጄ፤ ከስፖንሰሬ ከዳሸን ቢራ ጋር አንዳንድ ነገሮችን አስተካክለናል፡፡

ከሰሞኑ ደግሞ ደሴና ኮምቦልቻ ሄጄ ነበር፤ አንድ የአፋር ባለሃብት ሆቴል ከፍተው ለምርቃቱ  እንድገኝ ስለፈለጉ ነው፡፡

ቀጥለን ደሞ ወደ ደቡብና ምስራቁ ክፍል እንሄዳለን፡፡
ከአዲስ አልበም በኋላ ኮንሰርት የተለመደ ነው፡፡ ጥያቄ አልቀረበልህም?
ከአሁኑ ለንደን ፕሮግራም እንድይዝላቸው ጠይቀውኛል፡፡ ግን አልሄድም፤ ምክንያቱም አልበሙ በደንብ መሰማትና

መደመጥ አለበት። ሰው ከእኔ ጋር እንዲዘፍን እንጂ እኔ ብቻዬን እንድዘፍን አልፈልግም፡፡ የለንደን ያልኩሽ  ከፋሲካ

በኋላ ስለሆነ ለእኔ ጥሩ ጊዜ ነው፡፡
እስከ አሁን ስንት አልበም ሰራህ?
ከብርሃኑ ተዘራ ጋር አራት አልበሞች ሰርተናል….‹‹ተው አምላኬ››፣ ‹‹እንዲች እንዲች››፣ ‹‹እጅ አንሰጥም›› እና ‹‹ባቡሬ››፡፡

ከዛ በኋላ የተለያዩ ነጠላ ዜማዎች ሰርቼአለሁ፡፡ ለብቻዬ አልበም ሳወጣ ይህ አዲሱ ‹‹ምስጋና›› የመጀመሪያዬ ነው፡፡  
አርቲስቶች ችግር ሲደርስባቸው ቀድመህ ትደርሳለህ ይባላል?…
የተወሰንን አርቲስቶች በክፉም በደጉም የምንገናኝ ነን፡፡ አርቲስቶች ችግር ሲደርስባቸው የሰው እጅ ከሚያዩ፣ ለዚሁ

ዓላማ የሚሆን አንድ ነገር መከፈት አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ለምሳሌ እድር የለንም፡፡
አሁን እያሰብን ነው፡፡ ለቅሶ ላይ ወይም የሆነ ቦታ ስንገናኝ ለምን አንመሰርትም እንባባላለን። በጓደኞች መካከል ችግር

ሲፈጠር ለመፍታት እንጥራለን፡፡ እኔ ብቻዬን ምስጋናውን (ክሬይቱን) መውሰድ አልፈልግም፡፡ በተረፈ ሜሪ ጆይ ውስጥ

ሁለት የማሳድጋቸው ልጆች አሉኝ፡፡ መናገር የማልፈልጋቸው ሌሎች እንቅስቃሴዎችም አሉ፡፡ በአጠቃለይ ግን ጥሩ ነው፡፡
የሞባይል ስልክህን መጥሪያ (ሪንግቶን)እንደሰማሁብ  ከአዲሱ አልበምህ ሳይሆን አይቀርም …ተሳሳትኩ?
14ኛው ዘፈን ነው - ‹‹እስዋን ተዋት›› የሚለው። የግጥሙ መነሻ ሃሳብ የማሚላ ነው፡፡ ሙሉውን ግጥም የሰራው ሳሚ

ሎሬት ነው፡፡ በጣም ጎበዝ የሰፈሬ ልጅ ነው፤ ሳሚ፡፡ ዘፈኑ ቀዝቀዝ ብሎ መልዕክቱም ደስ ይላል፡፡
“እስዋን ተዋት” ነው የሚለው፡፡ አንዳንዴ ጓደኞችሽ  ያንቺ ባህሪ ያልሆነውን ነገር ያወራሉ አይደል…”ተዋት በቃ! ተዋት

አትሟት.እኔ እስዋነቷ ነው የምፈልገው… በቃ እንደዚህ አትበሏት..ተዋት” ..ነው የሚለው፡፡ ልጅቷ ሳቅ፣ ጨዋታና ጭፈራ

ትወዳለች፤ ሌላ ምንም ጥፋት የለባትም፡፡ ግን አለ አይደል ሁልጊዜ ነጌቲቩን የሚያወሩ አሉ፡፡ እነሱን ነው … “ተዋት”

የሚለው፡፡

ባለፋት አምስት ዓመታት ሦስት የግጥም መጻሕፍትን አሳትሟል - “እውነትን ስቀሏት” በ2001 ዓ.ም፣ “ከፀሐይ በታች”

በ2004 ዓ.ም እና  “ጽሞና እና ጩኸት” በያዝነው ዓመት፡፡  ሦስተኛው መጽሐፉ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ በጣይቱ

ሆቴል ጃዝ አምባ አዳራሽ በተመረቀበት ወቅት በመድበሉ ላይ ዳሰሳ ያቀረቡት፣ መምህርና ሐያሲ አስቻለው ከበደ

በማጠቃለያቸው ላይ፤ ሰሎሞን ሞገስ (ፋሲል)፤ ተስፋ የሚጣልበት ገጣሚ ነው ሲሉ ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ግጥሞቻቸውን በመጽሐፍ ሰንደው የሚያቀርቡ ገጣሚያን በአብዛኛው “የእኔ ነው” የሚሉትን አሻራ ለመተው ሲታትሩ

ይታያሉ በአንድ ርዕስ ስር ተዘጋጅተው የተለያዩ ክፍሎች የተሰጣቸውን ግጥሞችን በማቅረብ፣ ግጥሞቹን ርዕስ አልባ

በማድረግ፣ ስንኞቹን በተለያየ ቅርጽ በመሰደር እንዲሁም አዲስ ይዘት፣ ቅርጽና ሃሣብ በማስተዋወቅ። ሎሬት ፀጋዬ

ገብረመድህን በ1966 ዓ.ም ባሳተመው “እሳት ወይ አበባ” የግጥም መጽሐፉ መግቢያ “…. አንዳንድ መምህራን የዚህን

ድንጋጌ ዘይቤ (ስታይል) ስም ስላላገኙለትና እኔም ስላልሰየምኩለት “የፀጋዬ ቤት” ይሉታል” ብሏል፤ ለየት ስላለ

የአገጣጠም ስታይሉ ሲገልጽ፡፡
ገጣሚያኑ በቅርጽና ይዘት ላይ አዳዲስ ነገሮችን “ለመፍጠር” የሚነሽጣቸውና የሚያተጋቸው ገጣሚነት የሚሰጣቸው

“ነጻነት” (Poetic Licesence እንዲሉ) እንደሆነ አንዳንድ የዘርፉ ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ “ጽሞና እና ጩኸት”

በተሰኘው ሦስተኛው የሰሎሞን ሞገስ (ፋሲል) የግጥም መድበል፤ “በግጥም እንስከር” የሚለው  ግጥሙ ሲያበቃ በግርጌ  

ማስታወሻው ላይ ግጥሙ ቤት የማይመታ እንደሆነ ጠቁሞ ማብራሪያ ያቀርባል፡-
“ቤት ሰበር ግጥሞች አንዱ የግጥም ዘርፍ እንዲሆኑና ይህ አዲስ የግጥም መልክ በወጣት ገጣሚዎች ይበልጥ እንዲዳብር

በመመኘት፣ እንደ መነሻ በገጽ 45፣51፣56 እና 64 ያሉ ቤት ሰበር ግጥሞችን አቀርቤያለሁ፡፡ ቤት ሰበር ግጥሞች ቤት

አይምቱ እንጂ ዜማ ያላቸው፣ ምጣኔያቸውን የጠበቁና ቤት ከመምታት ውጪ የተቀሩትን የግጥም ባሕሪያት ሁሉ

የሚያሟሉ ናቸው፡፡ በከፊል ቤት የሚመታ ግን በከፊል ቤት የሚሰብር ግጥም ደግሞ ከፊል ሰበር ግጥም ልንለው

እንችላለን፡፡ ቤት አለመምታት (ቤት መስበር) አንዱ የግጥም ባህሪ ሆኖ ቢተዋወቅስ?”
ለግጥም ማስተማሪያነት የሚያገለግሉ ወይም ስለ ግጥምና ቅኔ ምንነት በማጣቀሻነት ሊቀርቡ የሚችሉ መጻሕፍትን

ያዘጋጁ ጥቂት የማይባሉ ደራሲያን አሉ። የዘሪሁን አስፋው “የሥነ ጽሁፍ መሠረታዊያን”፣ የብርሃኑ ገበየሁ “የአማርኛ ሥነ

ግጥም”፣ የአለማየሁ ሞገስ “የአማርኛ ግጥምና ዜማ ማስተማሪያ”፣ የአቤ ጉበኛ “መስኮት”፣ የፍቅረድንግል በየነ “ሰምና

ወርቅ ሰዋሰው”፣ የአስፋው ተፈራ “ፀጋዬ“፣ የታደለ ገድሌ  “ትንቅንቅ” … መጻሕፍት ይጠቀሳሉ፡፡
ገጣሚ ሰሎሞን ሞገስ (ፋሲል) “ቤት አለመምታት ወይም ቤት መስበር አንዱ የግጥም ባሕሪ ሆኖ ቢተዋወቅስ?” በሚል  

በአማርኛ ግጥም አጻጻፍ ላይ አዲስ ነገር ለማከል ላሳየው ጉጉነት፣ ደራሲ አቤ ጉበኛ ከ42 ዓመታት በፊት መልስ

ሰጥቶበታል፡፡ ደራሲው “መስኮት” በሚል ርዕስ በ1964 ዓ.ም  ባሳተመው የመጀመሪያ የግጥም መጽሐፉ መግቢያ ላይ፣

ቤት የማይመታ ወይም የሚሰብር አገጣጠም ቀደም ብሎ የሚታወቅ መሆኑን ይገልጻል፡፡
“ቤት የማይመቱ ሁለት ግጥሞች በዚህ መጽሐፌ ውስጥ ገብተዋል፡፡ እነሱም በእንግሊዝኛ (ብላንክ ቨርስ) በሚባለው

የግጥም ዓይነት የሚታዩ ሲሆን፣ በሀገራችንም ይህ የግጥም ዓይነት እንግዳ አለመሆኑን ለማሳየት ነው፡፡ ቤት የማይመታ

ግጥም በሀገራችን በጣም የታወቀና የተለመደ ነው፡፡ ለምሳሌ ከውጪ ቋንቋ ከተተረጐሙ መጻሕፍት መካከል እንደ

መዝሙረ ዳዊት፣ መኀልየ ሰለሞን ያሉት ቤት በማይመታ ግጥም የተጻፉ ናቸው፡፡ በሀገር ውስጥ ከተደረሱት አብዛኞቹ

የያሬድ ቅኔዎች ቤት የላቸውም፡፡”
በመጽሐፌ ቤት የማይመቱ ወይም የሚሰብሩ ግጥሞችን ያቀረብኩት አዲስ ነገር ፈጥሬያለሁ ለማለት ሳይሆን የአሠራር

ልማዱ እንዳለ ለማሳየት ነው የሚለው አቤ ጉበኛ፤ አንድ ቃል አንድ ቤት እንድትመታ የሚደረግበት አጭር የግጥም

መንገድ እንኳ አዲስ አለመሆኗን ማወቅ ጠቃሚ ነው ብሎ የሚከተለውን የሆታ ግጥም በማሳያነት አቀርቧል፡-
በወጨፎ፤
ፈጀው ጠልፎ፤
በውጅግራ፤
ተካው ጅግራ፤
በናስ ማሰር፤
ፈጀው ነስር
“ዕውቀት ከአንዱ ወደ ሌላው የሚተላለፍና የሚወራረስ በመሆኑ የፋርሳዊው ገጣሚ የኦማር ኻያምን አገጣጠም በአማርኛ

የግጥም ሥራዎቼ ለመጠቀም ሞክሬያለው፤ በአማርኛ ቋንቋ ግጥም የመጻፊያ መንገዶቻችን በጣም ብዙ ስለሆኑ ከሌላው

መዋስ የሚያስመኘን አይደለም፡፡ በአማርኛ ብቻ ሳይሆን በሌሎች የአገራችን ቋንቋዎች ያለው የአገጣጠም ስልት ቢጠና

ተጨማሪ ስልቶችም ሊገኙ ይችላሉ” ይላል፡፡
በአማርኛ ቋንቋ የግጥም አጻጻፍ ስልት ውስጥ ቤት የማይመቱ የአገጣጠም ዘዴዎች በብዛት እንዳሉ ሲያብራራ፤ በዝርው

ጽሁፍና ለዚያም ማሳያ ግጥሞችን ያቀረው አቤ ጉበኛ፤ ይህንን ያደረገበት ዋነኛው ምክንያት “ፈረንጆች ከሚሉት ውጭ

በአገራችን ዕውቀት ያለ ለማይመስላቸው ሰዎች” ምላሽ ለመስጠት መሆኑን ጠቁሟል፡፡
የሀዘንና የለቅሶ ግጥሞች እንዴት እንደሚጻፉ፣ ገጸ ባህሪ ያለውና የሌለው ግጥም አዘገጃጀት፣ ስለፉከራና ሽለላ አጻጻፍ፣

ስለ በገናና የሆታ ግጥም ምንነት፣ ስለ የእንካ ሰላንታያ ግጥም አገጣጠም፣ ለመንፈሳዊ አገልግሎት የሚውሉ የ“ምሕላ”

ግጥሞች ምንነት፣ ስለ አዝናኝና አስደሳች ግጥሞች፣ ስለ ቅኔ አጻጻፍና የምክር ግጥሞች … ማብራሪያና ምሳሌዎችን

ጠቅሷል፡፡ ቤት ለማይመታ ወይም ለሚሰብር ግጥም “የቅን ሰው መዝሙር” የተሰኘ ግጥሙን በማሳያነት አቅርቧል፡፡
እጅግ ይገርመኛል እጅግ ይደንቀኛል፤
ነገሩን ሳስበው ቁሜ ተቀምጨ፡፡
አንዳንድ ግራ ሰዎች ሲጠሉኝ ሳያቸው፤
ምርር አርገው ከልብ ምንም ሳልነካቸው፤
እንዲሁ በዓለም ላይ በመኖሬ ብቻ፤
ምናልባት ምናልባት ይሆን ቆጭቷቸው፤
ዓየርን ፀሐይን በተካፈልኳቸው?
አንድ ቀን ሳላስብ በማንም ላይ ክፉ፤
ለመጉዳት ሃሣብም መንገድም ሳይኖረኝ፤
እንዲህ ያሉ ፀሮች ለማፍራት የቻልሁ፤
በሰው ክፉ አስቤ ክፉ ብፈጽም፤
ዕድል ባሰናክል ባበላሽ ጥቅም፤
ለንብረት ለሕይወት ጠላት ብሆን ኑሮ፤
ኸረ ጠላቶቼ ስንት ሊሆኑ ነበር?
ግን ጠላት ከማፍራት ግን ጠላት ከማብቀል፤
ቅንነት ይበልጣል ከክፋት ይልቅ፤
ይታገላል እንጂ ሊያሳስት ሰውን፤
ይፈታተናል ወይ ሰይጣንን ሰይጣን፣
መልአክና ሰይጣን ጓድ ይሆናሉ ወይ?
እኔ አለሁኝ እንጂ ለማንም ሰው ክፉ፤
ግድ አለኝ ጠማሞች በከንቱ ቢለፉ?
ሰሎሞን ሞገስ(ፋሲል) በ”ጽሞና እና ጩኸት” የግጥም መጽሐፉ፣ ቤት አለመምታት አንዱ የግጥም ባህሪ ሆኖ

ቢተዋወቅስ? በሚል ላቀረበው ጥያቄ ከ42 ዓመታት በፊት አቤ ጉበኛ “መስኮት” በሚል የግጥም መጽሐፉ ከላይ

በቀረበው መልኩ ማብራራቱን ለማስታወስ ያህል ነው፡፡ መምህርና ሐያሲ አስቻለው ከበደ እንደመሰከሩለት፤ ሰሎሞን

ሞገስ (ፋሲል) ተስፋ ከሚጣልባቸው ወጣት ገጣሚያን አንዱ እንደሆነ በሦስቱ መጻሕፍቱ ባቀረባቸው ግጥሞች ብቃቱን

አሳይቷል፡፡ ግጥምና አገጣጠምን ለማሳደግ አዲስ ሃሣብና መንገድ ለመፍጠር ሲያስብ ግን የተመኘው ነገር ቀድሞ

ያልነበረ መሆኑን መፈተሽ ያለበት ይመስለኛል፡፡