
Administrator
“የፊልም ኢንዱስትሪው ወደፊትም ወደኋላም እየተጐተተ ነው”
ላለፉት 15 አመታት በፊልም ሙያ ላይ የተሰማራው ቴዎድሮስ ተሾመ፤ በፊልም ፅሁፍ ደራሲነት፣ በተዋናይነት፣ በዳሬክተርነትና በፕሮዲዩሰርነትም ሰርቷል፡፡ በሙያ ዘመኑ አምስት ፊልሞችን ሰርቶ ለእይታ ያበቃው አርቲስቱ፤ ስድስተኛውን ፊልሙን “ሦስት ማዕዘን” በሚል ርዕስ የሰራ ሲሆን የነገ ሳምንት ሐምሌ 21 ያስመርቃል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መልካሙ ተክሌ በአዲሱ ፊልሙ ላይ በማተኮር ከአርቲስት ቴዎድሮስ ጋር ያደረገውን ቃለምልልስ እነሆ፡፡
“ቀይ ስህተት” የተሰኘው ፊልምህ ሲወጣ የቀይ ሽብር ሰማእታት ታሰቡ፡፡ “አባይ ወይስ ቬጋስ” ሲታይ አባይን መገደብ ተጀመረ፡፡ አሁን ደግሞ የስደተኞች ጉዳይ ትኩረት ሲይዝ በስደት ዙርያ የሚያጠነጥነው “ሦስት ማእዘን” የተሰኘ ፊልምህ ሊወጣ ነው፡፡ ፊልሞችህ ወቅት ተኮር ሆኑሳ?
የ“ሦስት ማእዘን” ቀረፃ ያለቀው ከአንድ ዓመት በፊት ነው፡፡ የተፃፈው ከሦስት ዓመት በፊት ነው፡፡ በተለይ በሙያው ውስጥ ያሉ እንደዚህ ሊያስወሩ ይችላሉ፡፡ በትግል የማትጥለውን ሰው ለመጣል እንዲህ አይነት ስትራተጂ ትቀይሳለህ፡፡ የዚህን ፊልም ማስታወቂያ ከጀመርን አስራ አንድ ወር ሆኖናል፡፡ የሕገወጥ ስደት ወሬ ሰፊ ሽፋን ማግኘት የጀመረው ከስድስት ወር ወዲህ ነው፡፡ “አባይ ወይስ ቬጋስ” ፕሮጀክት ሁለት ዓመት ፈጅቷል፡፡ ይኼ ፊልም መታየት ከጀመረ በኋላ ነው የግድቡ አዋጅ የታወጀው፡፡ “አበድኩልሽ” ከሚል የገበያ ሥራ ስታልፍ ችግሮች ቀድመው ሊታዩህ ይችላሉ፡፡
“ሦስት ማእዘን”ን በልደትህ ቀን ለገና ለማስመረቅ አስበህ እንደነበር ሰምቻለሁ፡፡ ለምን እስካሁን ዘገየህ?
ፊልሙ አልደረሰልኝም፡፡ ፊልሙን በልደቴ ቀን ለማስመረቅ አስቤ ነበር፡፡ ይኼ መረጃ እንዴት እንደደረሰህ አላውቅም፡፡
ማትያስ ሹበርት የፊልሙ የፎቶግራፊ ዳይሬክተር እንደሆነ ተገልጿል፡፡ አንዳንድ ወገኖች ግን ባለሙያው ሙሉ ቀረፃውን እንዳልሰራ ይናገራሉ፡፡
ዘጠና ዘጠኝ በመቶውን ቀረፃ የሰራው እሱ ነው፡፡ እዚህ የቆየው ለስልሳ ቀናት ነው፡፡ ቀረፃው በሰባ አምስት ቀናት ተጠናቀቀ፡፡ እሱ ከሄደ በኋላ አስራአምስት ቀን ሙሉ ተቀረፀ ማለት አይደለም፡፡ ከሱ መሄድ በኋላ የሦስት ቀን ቀረፃ ብቻ ነው የነበረው፡፡
ፊልሙን በውጭ ሀገር ፊልም ዘርፍ ለኦስካር ሽልማት እንዲታጭ ለማድረግ አስባችኋል፡፡ ከምን ተነስታችሁ ነው?
ሥራችን ለኦስካር ይመጥናል ብለን ስለምናስብ ነው፡፡ ካሁን በፊት የሰራኋቸው ፊልሞች እዚህ ውድድር ውስጥ አልገቡም፡፡ የኦስካር ፈተና ከባድ ነው፡፡ ውጤቱን አብረን እናያለን፡፡ የእኛ መዝገበ ቃላት ሁልጊዜ “አይቻልም” የሚል ነው፡፡ አይቻልም ስለሆነ ሁሌም አንችልም፡፡ “ሦስት ማእዘን” ግን ይችላል ብለን እናስባለን፡፡ ስለዚህ የሚከፈለውን መስዋእትነት ለመክፈል ዝግጁ ነን፡፡ ኦስካር መግባታችን ግን ከማትያስ ሹበርት ጋር አይገናኝም፡፡
ሀገር ውስጥ ፍጆታ በተሰራ ፊልም ለዓለም አቀፍ ሽልማት መታጨት ይቻላል?
የሚያጨው ሌላ አካል ነው፡፡ እኛ እንደማንኛውም ተወዳዳሪ እንወዳደራለን፡፡ ስራችንን ለውድድር አቅርበን ዘመቻ እናደርጋለን፡፡ ይህ ራሳችንንና ፊልሙን ለማሳደግ ያለን ፍላጐት አካል ነው፡፡ እኛ ብቻ ሳንሆን የሀገራችን የፊልም ኢንዱስትሪ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እንዲሆን ሙከራ እናደርጋለን፡፡
በፊልሙ ውስጥ ለተሳተፈ ለእያንዳንዱ የውጪ አገር ዜጋ ተዋናይ 40ሺ ዶላር ከፍለሃል ተብሏል…
ውሸት ነው፡፡ በነፃም አልሠሩም፣ የተጠቀሰውን ያህል ገንዘብም አልተከፈላቸውም፡፡
“ሦስት ማእዘን” ከሌሎቹ ፊልሞችህ በተለየ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ መቀረፁን ፊልሙን ለጋዜጠኞች ባሳየህ ወቅት ተናግረሃል፡፡ እስቲ ስለእሱ አብራራልኝ…
በ49 ሴ.ግሬድ ሙቀት በበረሀ መቀረፁ ይመስለኛል፡፡ እያንዳንዱ ፊልም የራሱ ተግዳሮት አለው፡፡ የባለሙያ፣ የበጀት…ችግር አለ፡፡ ይኼን የተለየ የሚያደርገው በረሃው ነው፡፡ ከቤት ውጭ ነው የተቀረፀው፡፡ የውሃ ጥሙ ስቃይ ነው፡፡ ቀዝቃዛ ውሃ አፍ ከመድረሱ በፊት ይሞቃል፡፡ በእርግጥ ሁላችንም ተሰዳጅ ሆነንበታል፡፡ ሌላው ደግሞ ውጭ ሀገር ሲቀረጽ የገጠመን የውጭ ምንዛሬ ችግር እና የቋንቋ መሠናክል ነው፡፡
ወደ ፊልም ሙያ በገባህበት የጀማሪነት ጊዜህ ታዋቂው የፊልም ባለሙያ ሚሼል ፓፓታኪስ ያመቻቹልህን የውጭ ሀገር የትምህርት እድል ሳትጠቀምበት እንደቀረህ ሰምቻለሁ፡፡ ለምን ይሆን?
ከጀመርን የባህል ተቋም ጋር በመሆን ጋና እንድሄድ ነበር የታሰበው፡፡ አጋጣሚው ጥሩ ነበር፡፡ ግን በዚያ ሰዓት ለአራት ዓመት እዚያ ሄጄ ቢሆን ኖሮ አሁን ላለሁበት ደረጃ አልደርስም ነበር፡፡ የራሴ ራእይ ነበረኝ፡፡ የአሁኑን ጊዜ ያለመ፡፡ የባህል ተቋም ኃላፊዋን ለአራት ዓመት ከምትልኪኝ የሦስት ወር ካለ ላኪኝ ብያት ነበር፡፡ እናቴ በህይወት ስላልነበረችና የቤተሰብ ሃላፊነት እኔ ላይ በመውደቁ፣ ለረዥም ጊዜ ውጭ ሀገር መቆየቱን እምቢ አልኩ፡፡ ወንድሞቼንና እህቶቼን ሜዳ ላይ በትኜ መሄድ አልችልም ነበር፡፡
ከዚያ በኋላስ የፊልም ትምህርት የመማር እድል ገጠመህ ወይስ በልምድ ብቻ ቀጠልክ?
ሎስ አንጀለስ የፊልም ትምህርት ቤት ተምሬአለሁ፡፡ ዲግሪዬን በሚቀጥለው ወር እወስዳለሁ፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ውጭ የነበርኩት ለዚህ ነው፡፡
በልጆችህ ላይ ወዳንተ ሙያ የመግባት አዝማሚያ አይተህባቸዋል?
ሦስተኛ ሴቷ ልጄ በተለይ ሙዚቃ ላይ ክንፍ ትላለች፡፡ ያልተለመደ ነገር አላት፤ አካሄዷን እናያለን፡፡ ልጆቼ ምርጫቸውን የሚወስኑት በራሳቸው ጊዜ እንጂ በእኔ ምርጫ አይደለም፡፡ ድራማ እና ፊልም ያያሉ፡፡
“ሦስት ማእዘን” ሲመረቅ መግቢያው 300 ብር መሆኑ “ራስን ማዋደድ ነው” ብለው የሚተቹ ወገኖች አሉ…
ይሄ በዛብን የሚሉ በሌላ የምርቃት ቦታ በመቶ ብር መግባት ይችላሉ፡፡ ከበዛ በሚቀጥለው ቀን በመደበኛ ዋጋ ይታያል፡፡ አምስት መቶ ብር እና አንድ ሺህ ብር ለማድረግም አስበን ይበዛል ብለን ነው የተውነው፡፡ የምርቃት ፕሮግራሙ ልዩ ሥነ ሥርአት ስላለው እኮ ነው፡፡
ለ15 ዓመታት በፊልም ኢንዱስትሪው ውስጥ እንደቆየ ባለሙያ የአገራችንን የፊልም እድገዘ እንዴት ትገመግመዋለህ?
የሁሉም ሀገር የፊልም ኢንዱስትሪ የራሱ ዝግመተ ለውጥ አለው፡፡ ይወለዳል፡፡ ይድሃል፡፡ ያድጋል፤ ትልቅ ኢንዱስትሪ ይሆናል፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ እያለፍን ነው ያለነው፡፡ በዚህ ውስጥ የሚፈጠሩ ችግሮች የሁሉም ኢንዱስትሪ ገጽታዎች ናቸው፡፡ የሀገራችን የፊልም ኢንዱስትሪ ከሁለት አቅጣጫ እየተጐተተ ነው፡፡ የሚለፋ ሰዎች አሉ፡፡ ወደ ፊት ያራምዱታል፡፡ ወደ ፊት ሄደ ብለህ ስታስብ ደግሞ አሸር ባሸር የሚሰሩ ሰዎች አሉ፡፡ ወደ ኋላ ይጐትቱታል፡፡ ስለዚህ መሀል ላይ ተወጥሮ ነው ያለው - ወደ ፊትም ወደ ኋላም እየተጐተተ፡፡
የኢትዮጵያ የፊልም ኢንዱስትሪ የግሎባላይዜሽን ተፅእኖ ያሰጋዋል የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ አንተ ምን ትላለህ?
ኢንዱስትሪውን ኢንዱስትሪ ለማድረግ ሦስት ግብአቶች ያስፈልጋሉ፡- ተመልካች፤ ፕሮዲዩሰር እና አከፋፋይ፡፡ አከፋፋይ ሲኖር የጥራት ደረጃ ይመጣል፡፡ ይኼንን ደረጃ ለማምጣት ፕሮዲዩሰርም ተጠንቅቆ ይሰራል፡፡ ተመልካችም ጥራት ምን እንደሆነ ስለሚገባው ያንን መጠየቅ ይጀምራል፡፡ እኛው እንሰራለን፣ እኛው እናስተዋውቃለን፣ እኛው እናከፋፍላለን፡፡ “ሦስት ማእዘን” የራሱ ዓለም አቀፍ አከፋፋይ አለው፡፡
አሁን ሰዎች በፊልም ገቢ ብቻ መተዳደር ጀምረዋል፡፡ ስለዚህ ፊልም እንደ ኢንዱስትሪ ቆሟል ማለት ይቻላል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በሚሊዮን የሚቆጠር ብር ለመንግስት ቀረጥ እየተከፈለበት ነው፡፡ የፊልሞች በዓለምአቀፍ የባህልና ቋንቋ ተጽእኖ ሥር መውደቅ እንደፊልም ሰሪዎቹ የአእምሮ ዝግጅት የሚወሰን ነው፡፡ ሁሉም ፊልም ግሎባላይዝድ ሆኗል ማለት ይከብዳል፡፡
ዘንድሮ ከወጡ የአማርኛ ፊልሞች መካከል የወደድከው አለ?
“የመጨረሻዋ ቀሚስ” ጥሩ ነው፡፡ “ኒሻን” የተለፋበት ቆንጆ ፊልም ነው፡፡ ኮሜዲ የሆነው “ኢምራን” ጥሩ ነው፡፡ “ሰምና ወርቅ” በጣም ቆንጆ ነው፡፡ ሁሉንም ፊልም አያለሁ፡፡ ግዴታም አለብኝ፤ በሲኒማ ቤቴ ምክንያት፡፡ ዘንድሮ የወጡትን ፊልሞች ሁሉ ለመዘርዘር ጊዜም የለንም፡፡ ልቤ ውስጥ የቀሩትን ፊልሞች ከሞላ ጐደል ጠቅሼልሃለሁ፡፡
ድርጅትህም ስምህም ከዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ጋር የተገናኘ ነው፡፡ ስለ ሴባስቶፖል መድፍ ፊልም ለመስራት አስበህ ታውቃለህ?
ሴባስስቶፖል ለኔ የመጀመርያው የቴክኖሎጂ ሙከራ ነው፡፡ መድፍ ነው፡፡ እኔ የምመራው የፊልም ድርጅት የእኔ መድፍ ነው፡፡ እስካሁን ስድስት ተኩሼበታለሁ፡፡ ሰባት፣ ስምንት፣ ዘጠኝ አስር እያልኩ እተኩሳለሁ፡፡ ታሪክን አጣቅሼ የራሴን አርማ ለማውጣት ከሴባስቶፖል የበለጠ የለም፡፡ አፄ ቴዎድሮስና ገብርዬ ያሉዋቸውን ታሪኮች ፊልም የማድረግ ህልም አለኝ፡፡ አንድ ቀን ይሰራል፤ ግን ጥናት ይፈልጋል፡፡
ከ”ሦስት ማእዘን” ቀጥሎ ምን እንጠብቅ?
“ሦስት ማእዘን” ቁጥር ሁለት ይከተላል፡፡ ቀረፃው ተጠናቋል፡፡ “ሦስት ማእዘን” ቁጥር ሦስትም አለ፡፡ ምንአልባት ይኸው ፊልም እስከ አስር ሊቀጥል ይችላል፡፡ መፅሔት ተፈራ የምትባል ልጅ ያመጣችው “ሀገር” የሚል የፊልም ፅሁፍም አለ፡፡ የሷን ቆንጆ ድርሰት እንደገና እያዋቀርኩት ነው፡፡ እሱን የመስራት እቅድ አለኝ፡፡ ዳግማዊ ፈይሳ የፃፈው “የጠቅላይ ሚኒስትሩ ልጅ” የሚል ፅሁፍም በፕሮጀክት እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ ከዚያ “ግድብ” የሚል ሃሳብ አለኝ፡፡ ያስፈልጋል አያስፈልግም የሚለውን ግን እወስናለሁ፡፡
ለኢትዮጵያ ምን አደረግህላት፣ ኢትዮጵያስ ምን አደረገችልህ?
ኢትዮጵያ ወለደችኝ፤ አሳደገችኝ፡፡ እኔ ምን እንዳደረኩላት አላውቅም፡፡ ምክንያቱም የማደርገው ነገር በሙሉ ለመኖር፣ ለራሴ ደስታ ለማግኘት፣ ህይወት ጣፋጭ እንድትሆንና ልጆቼን ለማሳደግ በማደርገው ሩጫ ውስጥ የሚካተት ስለሆነ፣ ለኢትዮጵያ ይህን አደረግሁላት ልል አልችልም፡፡
የዓመቱ ከፍተኛ ተከፋይ ተዋናዮች
- ሮበርት ዳውኒንግ ጁኒየር፤ 75
- ሚሊዮን ዶላር
- ቻኒንግ ታተም፤ 60 ሚሊዮን ዶላር
- ሂውጅ ጃክማን፤ 55 ሚሊዮን ዶላር
- ማርክ ዎልበርግ፤ 52 ሚሊዮን ዶላር
- ዘ ሮክ ወይም ድዋይን ጆንሰን፤ 46
- ሚሊዮን ዶላር
- ሊያናርዶ ዲካርፒዮ፤ 39 ሚሊዮን ዶላር
- አዳም ሳንድለር፤ 37 ሚሊዮን ዶላር
- ቶም ክሩዝ ፤ 35 ሚሊዮን ዶላር
- ዴንዘል ዋሽንግተን፤ 33
- ሚሊዮን ዶላር
- ሊያም ኔሰን፤ 32 ሚሊዮን ዶላር
ለብሔራዊ ትያትር አዲስ ሥራ አስኪያጅ ተሾመ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ትያትርን ላለፉት ሁለት አመታት በተጠባባቂ ሥራ አስኪያጅነት ሲመሩ በቆዩት አቶ ደስታ ካሳ ምትክ አርቲስት ተስፋዬ ሽመልስ የትያትር ቤቱ አዲስ ሥራ አስኪያጅ ሆኖ ተሾመ፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የተፈረመ የሹመት ደብዳቤ የደረሰው አርቲስት ተስፋዬ፤ ከሐምሌ 4 ጀምሮ ትያትር ቤቱን እንዲመራ በደብዳቤው ላይ ተገልጿል፡፡ መደበኛ ሥራውን ከመጀመሩ በፊትም ዘንድሮ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ ሆነው በተሾሙት አቶ ሙልጌታ ሰኢድ አማካኝነት ከትያትር ቤቱ ሠራተኞች ጋር ተዋውቋል፡፡ በትያትር ፀሃፊነቱ የሚታወቀው አርቲስት ተስፋዬ፤ “ስንብት” እና “ሰማያዊ አይን” የተሰኙ ትያትሮችን ለመድረክ ማብቃቱ ይታወቃል፡፡
በፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በጋዜጠኛነት የሰራው አርቲስቱ፤ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በሸገር ኤፍኤም ሬዲዮ የአየር ሰአት ገዝቶ የራሱን ፕሮግራም ሲያቀርብ ቆይቷል፡፡
ሰዓሊያን የጐዳና ትርዒት አቀረቡ
የ“አለ ኪነጥበባት” ትምህርት ቤት ሰዓሊዎች ከ“ነፃ አርት ቪሌጅ” ጋር በመተባበር የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ስለ ሥዕል እና ቅርፃ ቅርፅ ያላቸው ግንዛቤ እንዲዳብር “ሰምና ወርቅ” የተሰኘ የጐዳና ላይ ትርዒት በማዘጋጀት የመነጋገርያ ሃሳብ አቀረቡ፡፡ ባለፈው ረቡዕ የቀረበው ዝግጅት በ”አለ ኪነጥበባት” ትምህርት ቤት ተጀምሮ ከአራት ሰአታት የከተማዋ ጉብኝት በኋላ የተጠናቀቀ ሲሆን አራት ኪሎ፣ ፒያሳ፣ ተክለሃይማኖት፣ ሜክሲኮ፣ ራስ መኮንን ድልድይ፣ መርካቶና ጃንሜዳን ያካተተ ነው፡፡ በጐዳና ትእይንቱ ሰዓሊ ታምራት ገዛኸኝ፣ ተስፋሁን ክብሩ፣ ዳንኤል አለማየሁ፣ ሙልጌታ ካሳ እና ለይኩን ናሁሰናይ እና ሌሎች ተሳትፈዋል፡፡ ረዳት ፕሮፌሰር በቀለ መኮንን፣ ዶክተር ኤልሳቤጥ ወልደጊዮርጊስ እና የውጭ አገር ኮሙኒቲ አባላት በክብር እንግድነት ተገኝተዋል፡፡
“የሰው ነገር” ነገ በሸገር ይጀመራል
“የሰው ነገር” የተሰኘ አዲስ የሬዲዮ መዝናኛ ፕሮግራም ነገ በሸገር ኤፍኤም 102.1 እንደሚጀመር ማርቭል ፕሮሞሽን እና ኮሙኒኬሽን አስታወቀ፡፡ በየሳምንቱ እሁድ በ8 ሰዓት የሚቀርበውን ዝግጅት የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ጋዜጠኞች የነበሩት ሲሳይ ጫንያለው፣ ዘላለም ሙላቱ፣ ብስራት ከፈለኝና ስዩም ፍቃዱ እንደሚያቀርቡት ድርጅቱ አስታውቋል፡፡ “የሰው ነገር” በፊልም፣ በሙዚቃ፣ በሥነ ፅሁፍ፣ በስዕል እና ሌሎች የጥበብ ዘርፎች ላይ የሚያተኩር ሲሆን ፕሮግራሙ መዝናኛና ቁምነገርን በሚዛናዊነት እንደሚያቀርብ ተገልጿል፡፡
“የጨረቃ ጥሪ” እና “ሉሲ ተሸጣለች” ለንባብ በቁ
በፊልም ባለሙያው ተስፋዬ ማሞ ወንድም አገኘሁ የተፃፈው “የጨረቃ ጥሪ” ወንጀል ነክ ረዥም ልቦለድ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ ልቦለዱ ከ21 ዓመት በፊት የተፃፈ መሆኑን ደራሲው ገልጿል፡፡
በ1982 ለንባብ የበቃችው “ዕፀበለስ” የተሰኘች መፅሐፉ በአንባቢያን ዘንድ መወደዷ በፈጠረበት ግለት ተነሳስቶ “የጨረቃ ጥሪ” የተባለውን ሁለተኛ መፅሐፉን ቢፅፍም የህትመት ብርሃን ሳያይ መቆየቱን ተናግሯል፡፡
በኤችዋይ ኢንተርናሽናል ፕሪንቲንግ የታተመው ባለ 212 ገፅ ልቦለድ መፅሐፍ፤ ለኢትዮጵያ ገበያ በ50 ብር፣ ከኢትዮጵያ ውጭ ደግሞ በ15 ዶላር ይሸጣል፡፡ “ሉሲ ተሸጣለች” የተሰኘው ረዥም ልቦለድም ለንባብ የበቃው በዚህ ሳምንት ነው፡፡
በአንድነት አየለ ኃይሌ የተፃፈው ባለ 289 ገፅ መፅሐፍ፤ በአሀዱ ማተሚያ ቤት የታተመ ሲሆን ለሀገር ውስጥ በ44.96 ብር ፣ ለውጭ ሀገራት በ45 ዶላር እንደሚሸጥ ታውቋል፡፡
“ጳጉሜ፣የኢትዮጵያ ቀን መቁጠርያ የማን ነው?” ዛሬ፤ “ነገር በምሳሌ” ሐሙስ ይመረቃሉ
*“የኢትዮጵያ የእግር ኳስ ጉዞ” መፅሐፍ ለገበያ በቃ
“ጳጉሜ፣ የኢትዮጵያ ቀን መቁጠርያ የማን ነው?” የሚል መፅሐፍ ዛሬ ገርጂ በሚገኘው የዩኒቲ ዩኒቨርስቲ አዳራሽ እንደሚመረቅ አዘጋጁ አስታወቁ፡፡
የመፅሐፉ አዘጋጅ የምጣኔ ሀብት ባለሙያው አቶ ፋሲል ጣሰው፤ የቀን አቆጣጠሩ የኢትዮጵያ ብቻ አይደለም የሚል መሟገቻ በመፅሐፋቸው ያቀረቡ ሲሆን ወርሃ ጳጉሜ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ማስገኘት አለባት በማለትም፣ ሠራተኞች ተጨማሪ ደመወዝ፣ የቤት አከራዮች የኪራይ ገንዘብ ጳጉሜን ታሳቢ በማድረግ ማግኘት እንዳለባቸው ገልፀዋል፡፡ በምረቃ ሥነስርዓቱ ላይ ዶ/ር አረጋ ይርዳውን ጨምሮ ሌሎች የሚድሮክ የሥራ ኃላፊዎች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ መፅሐፉ ለሀገር ውስጥ በ100 ብር፣ ለውጭ ሀገራት በ35 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡በሌላም በኩል “ነገር በምሳሌ” ቁጥር 1 መፅሐፍ በመጪው ሐሙስ በ10፡30 በብሉ በርድ ሆቴል ይመረቃል፡፡
አቶ አብርሃም ሐዲሽ ያዘጋጁት ባለ 103 ገፅ መፅሐፍ፤ የሥራ ባህል እንዳይዳብር መሰናክል ሆነው የቆዩ ልማዶችን ለመዋጋት የመፍትሄ ሀሳቦችን ያቀርባል፡፡ መፅሐፉ በ30 ብር እየተሸጠ ነው፡፡በፈለቀ ደምሴ (ኤርምያስ) የተዘጋጀው “የኢትዮጵያ እግር ኳስ ጉዞ” መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ በበርካታ መረጃዎች እና ፎቶግራፎች የተደገፈው ባለ 179 ገፅ መፅሐፍ፤ በፋርኢስት ትሬዲንግ የታተመ ሲሆን ዋጋው 47 ብር ነው፡፡ በመፅሐፉ የኋላ ሽፋን ላይ የቀድሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን እና የቡና ክለብ ተጫዋች አሰግድ ተስፋዬ፣ ጋዜጠኛ ኢብራሂም ሻፊ አህመድ፣ የቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ ምክትል አሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ እና የኢትዮጵያ የሴቶች ብሔራዊ ቡድን ተጫዋች አልፊያ ጃርሶ አስተያየታቸውን አስፍረዋል፡፡
ሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ በራፐሩ ስም ፌሎሺፕ መሰረተ
ላለፉት 20 ዓመታት በሂፕሆፕ ሙዚቃ ከፍተኛ ተወዳጅነት እና ስኬት ባገኘው ራፐር ናስ ስም ሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ፌሎውሺፕ ማቋቋሙን አስታወቀ፡፡ በሂፕሆፕ ሙዚቃ ታሪክ ያላቸውና ነባራዊ ገፅታን በረቀቀ መንገድ የሚያንፀባርቁ ሃሳቦችን በብዛት በመስራት ክብርና ዝና የተቀዳጀው ናስ፤ በሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ናስር ጆንስ ፌሎሺፕ ተቋቁሞለታል፡፡ ዌብ ዱ ቦይስ ኢንስቲትዩት እና ሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ የሂፕሆፕ ክምችት ፌሎሺፑን የሚያስተዳድሩ ሲሆን የሂፕሆፕ ሙዚቃ ባህል፤ በታሪክ እና በፈጠራ ሂደት የሚኖረውን ሚና ለማጎልበት በሚል እንዲሁም ከሂፕሆፕ ጋር የተገናኘ የኪነጥበብ ትምህርት ለሚወስዱ ተማሪዎች ድጋፍ እንደሚሰጥበት ታውቋል፡፡ በሙሉ ስሙ ናስር ቢን ኦሉ ዳራ ጆንስ ተብሎ የሚታወቀው ራፕሩ፤ ባለፈው ዓመት “ላይፍ ኢዝ ጉድ” በሚል መጠርያ 11ኛ አልበሙን ለገበያ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡
ዊቴከር የሰራበት ፊልም በርእስ ኩረጃ ተከሰሰ
ኦስካር ተሸላሚው ፎረስት ዊቴከር በመሪ ተዋናይነት የሰራበት አዲስ ፊልም ርእሱ ተኮርጇል በሚል መከሰሱን ሎስ አንጀለስ ታይምስ ገለፀ ፡፡ “ዘ በትለር” የተባለው የፊልሙ ርእስ እ.ኤ.አ በ1916 ዓ.ም ከተሰራ ድምፅ አልባ ፊልም የተወሰደ ነው የሚል ነው ክሱ፡፡ ከአንድ ወር ባነሰ ጊዜ ውስጥ በመላው ዓለም ለእይታ የሚበቃው ፊልሙ፣ በተመሰረተበት ክስ ከተሸነፈ ርእሱን ለመቀየር ይገደዳል፡፡ “በሲኒማው ኢንዱስትሪ ታሪክ ለ122 ጊዜያት ርእሶች ተደጋግመዋል፣ ተመሳስለው ተገኝተዋል” ይላል ፊልሙን የሰራው የዌይንስተን ኩባንያ ስራ አስኪያጅ - “ዘ በትለር” ፊልም ላይ የተለየ ነገር መነሳቱ አግባብ አይደለም በሚል ሲከራከር፡፡
በ25 ሚሊዮን ዶላር በጀት በዋርነር ብሮስ የተሰራው “ዘ በትለር”፤ ለስምንት የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች በአገልጋይነት ስለሰራ አንድ ጥቁር አሜሪካዊ የህይወት ታሪክ ያሳያል፡፡ ፎረስት ዊቴከር በዚህ አዲስ ፊልሙ ለኦስካር የሚያበቃ የትወና ብቃት ማሳየቱን የጠቀሰው ሎስ አንጀለስ ታይምስ፤ በዚሁ ፊልም ላይ ኦፕራ ዊንፍሬይ፤ ሊያም ኔሰን እና ሮቢን ዊልያምስ መተወናቸውን አመልክቷል፡፡ እ.ኤ.አ በ2006 “ዘ ላስት ኪንግ ኦፍ ስኮትላንድ” በተባለው ፊልም ላይ የኢድ አሚንን ገፀባህርይ በመጫወት በምርጥ ተዋናይነት ኦስካር የተሸለመው ፎረስት ዊቴከር፤ በተመሳሳይ የጎልደን ግሎብ እና የባፍታ ሽልማቶችንም ወስዷል - በምርጥ ተዋናይነት፡፡ የ52 ዓመቱ የፊልም ባለሙያ ከተዋናይነቱ በተጨማሪ በፊልም ፕሮዱዩሰርነትና ዳሬክተርነትም ይታወቃል፡፡
የትግራይ ጉዞ ማስታወሻ
ተናጋሪዋ ምድር
ትግራይ የትራጀዲና ኮሜዲ መድረክ ናት!
ከክርስቶስ ልደት 2006 ዓመት በፊት “አልሙጋህ” የተባለ ጣኦት ይመለክበት የነበረውን አዲአካውህን ጐብኝተን ውቅሮ ስንገባ ነው ጽሑፌን በይደር የቋጨሁት፡፡
ውቅሮ ለጥ ባለ ሜዳ ላይ የተመሰረተች ዘመናዊ ከተማ ናት፡፡ ከዚያች ውብ ከተማ ዳር እንደደረስን የከተማዋ ከንቲባና ነዋሪዎችዋ እንደሌሎች ከተሞች ነዋሪዎች ሁሉ በጭፈራ፣ በሆታና በዕልልታ ነው የተቀበሉን፡፡ ደመቅ ያለ ቁርስም ከቡና ጋር ጋብዘውናል፡፡ እንግዳን በክብር መቀበልና መጋበዝ የትግራዮች ባህል መሆኑን በተደጋጋሚ ስላየን ብዙም ላይደንቅ ይችላል፡፡ ግን የውቅሮ ከተማ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች ሊወደሱበት የሚገባ አንድ እንግዳ ነገር ተገንዝበናል፡፡ በውቅሮ ቅዳሜ የሥራ ቀን ነው፡፡ ህዝቡን ለማገልገል ሲባል ሠራተኛው በሙሉ ፈቃደኝነት ቅዳሜን በሥራ እንደሚያሳልፍ ተነግሮን “ይበል በሌሎች የሀገሪቱ ከተሞችም ይለመድ” ብለናል፡፡
የውቅሮ ቆይታችንን በአጭሩ አጠናቀን መጓዝ ስላለብን፣ ወደ አውቶቡሳችን መሰባሰብ ጀምረናል፡፡ ጊዜውም የተሳፈርንበት አውቶቡስም እሽቅድምድም የያዙ ይመስል በየፊናቸው ይከንፋሉ፡፡ አውቶቡሳችን ሲከንፍ ተናጋሪዋን ምድር እየቃኘን፣ በአየነው ተራራ፣ ወይም የተፈጥሮ ጥበቃ እየተደመምን ስንጓዝ ሌላ አስደናቂ ነገር ሲቀበለን፤ በቃ ትግራይ ማለት ቢገልጧት፣ ቢገልጧት ተነብባ የማታልቅ ግዙፍ መጽሐፍ ትመስላለች፡፡
በዚህ አይነት ስንጓዝ ቆይተን በአገራችን ታሪክ የመጀመሪያው ውቅር ቤተክርስቲያን ከሚገኝበት አብርሃ ወአጽብሃ ቀበሌ ደረስን፡፡ አብርሃ በአራተኛው መቶ ክፍለዘመን የአክሱም ንጉሥ የነበረና ክርስትና መንግሥታዊ ሃይማኖት እንዲሆን የደነገገ ነው፡፡ የአብርሃ ወአጽብሐ ቀበሌ በስሙ የተሰየመውም በዚሁ ታሪካዊ ምክንያት ሲሆን መቃብሩም በዚሁ ቤተክርስቲያን ውስጥ ይገኛል፡፡
ስለቤተክርስቲያኑ የአሰራር ጥበብና በውስጡ ስለሚገኙት ቅርሶች፣ ስለ ሶስቱ ቤተመቅደሶች፣ ስለ ቦታው አቀማመጥ፣ ወዘተ ብዙ እጅግ ብዙ ማለት ይቻላል፡፡ ግን ቦታም ጊዜም የለም፣ እንደ ጉብኝታችን ሁሉ ጽሑፌንም ፈጠን ማድረግ አለብኝ፡፡ አለዚያ ጋዜጣችን ትግራይ ላይ ብቻ ቢከርምም ስለ ትግራይ ምስጢር፣ ስለ ትግራይ ተአምራዊነት ጽፎ መጨረስ አይቻልም፡፡ የገደላትና ተአምራት ፀሐፊዎች እንዲህ አይነቱ እጹብ ድንቅ የሆነ ጉዳይ ሲገጥማቸው “ሰማዩ ሰሌዳ ወይም ብራና፣ የክረምቱ ዝናም ቀለም ቢሆኑም ጽፌ መጨረስ አልችልም” ይላሉ፡፡ የትግራይ ጉዳይ ያለምንም ማጋነን ለእኔ እንዲያ ነው፡፡
አብርሃ ወአጽብሐ ቀበሌ ከታሪካዊው ቤተክርስቲያኗ በተለይ የምትደነቅበት አጋጣሚም ተፈጥሯል፡፡ ቀበሌዋ እጅግ ከተራቆቱት የክልሉ ቀበሌዎች አንዷ ነበረች፡፡ ግን በህዝቡ እንደ ብረት የፀና ትግስትና ጥረት ዛሬ ተቀይራለች፤ ተራሮችዋ በተፈጥሮ ደን እየተሸፈኑ ናቸው፡፡
የአብርሃ ወአጽብሐ ቀበሌ ስም ሲነሳ የአንድ ጀግና አርሶ አደር ስም አብሮ መወሳቱ ግድ ነው፡፡ ስሙ “አባ ሐዊ” ይባላል፡፡ በትግርኛ “አባ እሳት” ማለት ነው፡፡ ትክክለኛ ስሙ ግን ገብረሚካኤል ዓደይ ይባላል፡፡ “አባ ሐዊ” የሚለው ቅጽል ስም የወጣለት በግብሩ ነው፡፡ ሲናገር እሳት ነው፤ ሲሰራ ደግሞ የበለጠ ነበልባል ነው፡፡ ኃላፊዎች ከቢሮአቸው ቁጭ ብለው ወይም ህዝብን ሰብስበው “እንዲህ ብታደርጉ የተሻለ ምርት ታገኛላችሁ፤ ወይም ምርታችሁ እንዲያድግ ይህን ፍጠሩ ማለት የለባቸውም፡፡ እንዲህ ብለው ሲያዝዙ ህዝቡ “የምትነግረን እውነት ከሆነ ለምን አንተ አልከበርህም?” የሚል ጥያቄ ቢያነሳ መልስ የለውም፡፡ ስለዚህ መሪዎች ሠርቶ በማሳየት አርአያዎች እንጂ የወሬ ጀግኖች መሆን የለባቸውም” ብሎናል በኩራት፡፡
አብርሃ ወአጽብሃ ቀበሌ እጅግ ዘግናኝ ከሆነ ድህነትና መራቆት የተራቀቀችው በአባ ሐዊ ፋና ወጊነትና አመራር ሰጭነት መሆኑን ተገንዝበናል፡፡ አባ ሐዊ በዚህ የልማት ጀግንነቱ በዓለምአቀፍ ደረጃ አንድ ጊዜ፣ በአገር አቀፍ ደግሞ 15 ጊዜ ተሸልሟል፡፡ የአባ ሐዊ የአመራር ጥበብ ቀድሞ ሠርቶ በማሳየት በመሆኑ፣ በህዝቡ ዘንድ ትልቅ አመኔታና ከበሬታን አግኝቷል፡፡
ከአባ ሐዊ ጓሮ ተገኝተን በአይናችን አይተን ያረጋገጥነው እውነትም ይኸው ነው፡፡ ያ አስፈሪ የነበረ ራቁት መሬት በደን ከመሸፈኑም በላይ ልዩ ልዩ አትክልቶችና ፍራፍሬዎች ተንዠርግገው ይታያሉ፡፡ የሰው ልጅ ከፈለገ አጥፊ ከፈለገ ደግሞ ተፈጥሮን ከነሙሉ ለዛዋና ክብሯ ሊመልሳት እንደሚችል መልካም አብነት ነው፡፡
ከአባ ሐዊ ጓሮ የተንዠረገጉትን ልዩ ልዩ አትክልትና ፍራፍሬዎችን በአድናቆት ከጐበኘን በኋላ ወደ እንግዳ መቀበያው ወሰደን፡፡ የእልፍኝ ቅርጽ ካለው እንግዳ መቀበያ ቤቱ ቁጭ እንዳልን፣ በሚያስገርም ፍጥነት ሻሽ የመሰለ ማር በዳቦ እያደረገ ለእያንዳንዱ ተጓዥ አደለ፡፡
ጠንክረው ከሰሩ ጣፋጭ ውጤት እንደሚገኝ ከአባ ሐዊ ተምረን፣ አመስግነንም ጉዟችንን ቀጠልን፡፡ አክሱም ገብተን ማደር ስላለብን እንጂ ልክ እንደ ማሩ ሁሉ ያንን የሚጣፍጥ አንደበቱን እያዳመጥን ትንሽ ጊዜ ብንቆይ ደስታውን አንችለውም ነበር፡፡
የጥበብ ተጓዦች ጉዞ ከጀመሩበት ዕለት አንስተው በአውቶቡሱ ውስጥ መዝፈን፣ ማቅራራትና መዘመር ወይም ግጥምና ዜና በማንበብ ራሳቸውን ማዝናናት የተካኑበት ቢሆንም ከአብርሃ ወአጽብሐ ቀበሌ ጉብኝታቸው በኋላ ግን የሆነ ህመም የያዛቸው ይመስል እየፈዘዙ መጡ፡፡
እርግጥ ነው ትግራይ ግራ ታጋባለች፤ ትግራይን ከራስ እስከ እግሯ ሳይጐበኙ “ኢትዮጵያዊ ነኝ” ማለትም ይከብዳል፡፡ ወይም ያሳፍራል፡፡ ትግራይ ተራራዋ ሁሉ፣ ከርሰምድሯ ሁሉ፣ ገዳሟ መስጊዷ ሁሉ የአገሪቱን ወይም የመላ አፍሪካን ምስጢር ደብቀው ይዘዋል፡፡
ጉዟችን ቀጥሏል፡፡ መንገዱ ገና እየሰፋ ስለሆነ ኮረኮንች ነው፡፡ በአብርሃ ወአጽብሐ ቀበሌ ህዝብ ጥንካሬ፣ በአባ ሐዊ የአመራር ስልት፣ በገዳሙ ጥንታዊነት ድንቅ ጥበብ እየተደነቅን ስንጓዝ በስተግራ በኩል እውቅ ቀራጺ ተጠንቅቆ ያዘጋጀው የሚመስሉት የገርዓልታ ሰንሰለታማ ተራሮች ከፊት ለፊታችን ድንቅ አሉ፡፡ ተራሮቹ እንደ ማንኛውም ተራራ የድንጋይ ቁልሎች አይደሉም፡፡ ይልቁንም ከአፍ እስከ ገደፋቸው የአገራችን የሥልጣኔ፣ የታሪክ፣ የሥነ ጥበብ፣ የሥነ ሕንፃና የሥነ ፈለክ ምስጢሮች የታጨቁባቸው የምስጢር ጐተራዎች ናቸው፡፡
አስደናቂውን የአባ ቶምዓታን ቤተክርስቲያን ጨምሮ በአብዛኞቹ ተራሮች ላይ ከ34 በላይ ከአንድ አለት የተፈለፈሉ አብያተክርስቲያናት አሉ፡፡ እያንዳንዳቸውን ጐብኝቶ ለመጨረስ ቢያን ለአንዱ ቤተክርስቲያን የአንድ ቀን ቆይታን ይጠይቃል፡፡
በገርዓልታ ተራሮች ተፈጥሮአዊ አቀማመጥ፣ በውስጣቸው ስላሉ ምስጢራት እየተደነቅን በመጓዝ ላይ ሳለን ከፊት ለፊታችን፤ ግን በርቀት አስደናቂው እና በር አልባው የደብረዳሞ ተራራ በኩራት ተጀንኖ ታየን፡፡
ደብረ ዳሞ በ6ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አባ አረጋዊ የሚባሉ መነኩሴ የመሠረቱትና እንደ ግዑዝ ነገር በመጫኛ ብቻ እየተጐተቱ የሚወጡበት ታላቅ ደብር ነው፡፡ የመጐብኘት ዕድሉ ስላልነበረን ውስጤ እያዘነ ግን ደግሞ በካሜራዬ ምስሉን ለማስቀረት እየሞከርኩ ማለፍ ግድ ሆነ፡፡ ጥላሁን ገሠሠ “በዓይን እየተያዩ የመናፈቅ ጣጣ…” ያለው እንዲህ አይነቱ የውስጥ ስቃይ ገጥሞት ይሆን?
ትግራይ የሃይማኖት፣ የስልጣኔ፣ የፍልስፍና፣ የዕውቀትና የማንነት ምስጢራት ዋሻ ብቻ ሳትሆን የትራጄዲና ኮሚዲ መድረክም ናት፡፡ አሁን ደግሞ ሐውዜን ገባን፡፡ ሐውዜን መራራ ትራጄዲ ከተተወነባቸው መድረኮች አንዷ ናት፡፡ በቀድሞው መንግሥት የጦር አውሮፕላኖች በአንድ የገበያ ቀን በሺዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊ ዜጐች እንደ ቅጠል ረግፈውባታል፡፡
የትራጄዲውን መድረክ ሐውዜንን በሀዘን ተሰናብተን ወደፊት እየተጓዝን ነው፡፡ ትግራይ ክልል ውስጥ ተራራ ላይ ቢወጡ አስደናቂ ጥበብ ይነበባል፤ መሬቱን ቢቆፍሩ እጅግ የሚገርም ምስጢር ይገኛል፡፡ ስለሆነም ማየት ያለብን ብዙ ነገር ቢኖርም በጊዜ አክሱም ለመግባት መፍጠን ይጠበቅብናል፡፡ ግን ደግሞ ውቧን ከተማ አድግራትን ማግኘት አለብን፡፡
አድግራትም የተለመደው ህዝባዊና ደማቅ አቀባበል ከምሳ ግብዣ ጋር ተደረገልን፡፡ ምሳው ደግሞ ከሚጣፍጠው የትግራይ ባህላዊ ምግብ “ጥህሎ” እና ከንፁህ የማር ጠጅ ጋር ነበር፡፡ በነገራችን ላይ “አድግራት” ማለት “አድገራሕት” ማለትም “የእርሻ አገር” ማለት መሆኑን አቶ ከበደ አማረ አስረድተውናል፡፡ ለጥ ካለ ሜዳ ላይ የተመሰረተች በመሆኗ እውነትም ለእርሻ ምቹ የነበረች መሆኗን መገንዘብ አያዳግትም፡፡
አድዓራት ውብ ከተማ ናት፡፡ የዩኒቨርሲቲው መመሥረት ከሻዕቢያ ጦርነት በኋላ ተቀዛቅዛ የነበረችውን ከተማ አነቃቅቷል፡፡ የአድግራት ከተማ ባለሥልጣናትና ነዋሪዎችን ግብዣ አጠናቀን በምስጋና ተሰነባበትንና ጉዟችንን ቀጠልን፡፡ የእኛ ነገር መሄድ፣ ማየት፣ ባየነው ነገር መደነቅ ነው፡፡ ድካም የሚባል ነገር የለም፡፡ ከሁሉ የሚገርመኝ የ78 አመቱ አዛውንት አቶ አስፋው ዳምጤ የእግር ጉዞን የሚጠይቁ ታሪካዊ ቦታዎችን ለመጐብኘት ከወጣቶች እኩል፤ ብዙ ጊዜ ግን ቀድመው ሲራመዱ ማየት የትግራይ መስህብ ቦታዎች ምን ያህል ጉጉት ፈጣሪዎች እንደሆኑ ያስረዳል፡፡
ወደፊት እየገሰገስን ነው፡፡ ከፊትለፊታችን ደግሞ የዓለም ጥቁር ህዝቦች ብቻ ሳይሆኑ ራሳቸው ጣሊያኖች በወርቅ ቀለም ብዙ እጅግ ብዙ ቁምነገሮችን የጻፉለት አድዋ ይጠብቀናል፡፡ ጊዜው ግን ከእኛ ፈጥኖ እየተጓዘ ነው፡፡ የአክሱም ከተማ ከንቲባ አቶ አበራም ህዝቡን አሰልፈው እየጠበቁን ነው፡፡ ስለዚህ ዝነኛዋን አድዋን በዝምታ አልፈን፣ ስንመለስ በደንብ ልንጐበኛት ቀጠሮ ይዘን ወደ አክሱም ገሰገስን፡፡
ጉዞ ወደ አክሱም ማለት ደግሞ ወደ ጥንተ ታሪክ፣ ወደ ማንነታችን መፍለቂያ በከፍተኛ ጉጉት መጓዝ ማለት ነው፡፡ በተለያዩ ጽሑፎችና ምስሎች አይተን የምንጓጓላትን አክሱምን ልናያት፣ አይተንም በአግባቡ ልናውቃት ነው፡፡ ግን ጊዜው ከእኛ ጋር እልህ የተጋባ ይመስል ይከልባል፤ እነሆ 1፡30 ሆነ፡፡
እናም የናፈቅናትን አክሱምን ሌባ ይመስል በጨለማ ገባንባት፡፡ ለብዙ ሰዓታት ሲጠብቁን የቆዩት የከተማዋ ባለሥልጣናትና ህዝቡም እስከዚህ ሰዓት ድረስ በከፍተኛ ትዕግስት ሲጠብቁን አምሽተው ነበርና በክብር ተቀበሉን፡፡ ሞቅ ያለ ራት ከጋበዙን በኋላ ወደተያዙልን ሁለት ሆቴሎች አመራን፡፡ በየደረስንበት ቦታ ሁሉ የቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ “እኔም ከጥበብ ተጓዦች ጐን አልለይም” ብሎ ሲከተለን እንደነበር በዚህ አጋጣሚ መግለጽም ማመስገንም እፈልጋለሁ፡፡ አክሱምን ሲነጋ በደንብ እናያታለን፡፡