Administrator

Administrator

በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ  ደደቢት እና  መከላከያ በቅድመ ማጣርያ  የመልስ ጨዋታዎቻቸው የምስራቅ አፍሪካ ክለቦችን ጥሎ ለማለፍ ትንቅንቅ ያደርጋሉ፡፡ ከሳምንት በፊት ደደቢት በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የዛንዚባሩን ኬኤምኬኤም በሜዳው 3ለ0 ሲያሸንፍ ጎሎቹን ዳዊት ፍቃዱ፤ ሺመክት ታደሰ እና ማይክል ጆርጅ ከመረብ አሳርፈዋል፡፡ በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ  መከላከያ ከሊዮፓርድስ ከሜዳ ውጭ በተገናኘበት ጨዋታ 2ለ0 ተሸንፏል፡፡
በኬንያው ብሄራዊ ስታድዬም ናያዮ በተደረገው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ለሊዮፓርድስ ሁለቱን ጎሎች ያስቆጠሩት አምበሉ ማርቲን ኢምባላምቦሊ እና ጃኮብ ኬሊ ናቸው፡፡ ደደቢት ከኬኤምኬኤም ጋር ከሜዳው ውጭ በሚያደርገው የመልስ ጨዋታ ከ2ለ0 በታች መሸነፍ፤ አቻ መውጣትና በማናቸውም ውጤት ማሸነፍ ጥሎ ለማለፍ ይበቃዋል፡፡
መከላከያ ደግሞ የኬንያውን ኤኤፍሲ ሊዮፓርድስ በሜዳው አስተናግዶ 3ለ0 ከዚያም በላይ በማሸንፍ የማለፍ  እድሉን ይወስናል፡፡  በቅድመ ማጣርያው ከኢትዮጵያው ደደቢት እና ከዛንዚባሩ ኬኤምኬኤም ጥሎ ማለፍ የሚችለው ክለብ በአንደኛ ዙር የማጣርያ ምእራፍ የሚገናኘው ከቱኒዚያው ክለብ ሲኤስ ኤስፋክሲዬን ጋር ነው፡፡
በሌላ በኩል ከኢትዮጵያው መከላከያ እና ከኬንያው ኤኤፍሲ ሊዮፓርድስ ጥሎ የሚያልፈው በአንደኛ ዙር የማጣርያ ምእራፍ የሚገናኘው  ከደቡብ አፍሪካው ሱፕር ስፖርት ዩናይትድ ወይም ከቦትስዋናው ጋብሮኒ ዩናይትስድ አሸናፊ ጋር ይሆናል፡፡ ሱፕር ስፖርት ዩናይትድ በቅድመ ማጣርያው የመጀመርያ ጨዋታ ጋብሮኒ ዩናይትድስን 2ለ0 አሸንፎታል፡፡

ዛሬ በእንግሊዝ በርሚንግሃም በሚካሄደው የ2 ማይል የቤት ውስጥ ውድድር የ23 ዓመቷ አትሌት ገንዘቤ ዲባባ የውድድር ዘመኑን ሶስተኛ የዓለም ሪከርዷን ልታስመዘግብ እንደምትችል ግምት አገኘች፡፡ ገንዘቤ ባለፈው ሁለት ሳምንት በ3ሺ ሜትር እና በ1500 ሜትር የቤት ውስጥ ውድድሮች ሁለት አስደናቂ የዓለም ሪከርዶችን አስመዝግባለች ዛሬ በበርሚንግሃም “ሳልስበሪ ኢንዶር ግራንድፕሪ” የ2 ማይል ሩጫ  ከ5 ዓመት በፊት በመሰረት ደፋር የተመዘገበውን ክብረወሰን ገንዘቤ ዲባባ ለመስበር እንደምትችል ተዘግቧል፡፡ ከተሳካላት በውድድር ዘመኑ 3 የዓለም ሪከርዶችን ያስመዘገበች ምርጥ አትሌት እንደምትሆን መረጃዎች አውስተዋል፡፡ ገንዘቤ በ2014 የውድድር ዘመን ከገባ ወዲህ በማሳየት ላይ የምትገኘው አስደናቂ ብቃት ከወር በኋላ በፖላንዷ ከተማ ስፖት በሚደረገው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ላይ በ3ሺ እና በ1500 ለድርብ የወርቅ ሜዳልያ ድሎች ግንባር ቀደም እጩም አድርጓታል፡፡
ገንዘቤ ከሳምንት በፊት በስዊድን ስቶክሆልም በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫ  ያሸነፈችው ርቀቱን በ8 ደቂቃ ከ16.60 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በማጠናቀቅ አዲስ የዓለም ክብረወሰን አስመዝግባ ነበር፡፡ ይህ ሪከርድ አስቀድሞ በመሰረት ደፋር ተመዝግቦ የነበረውን የሰዓት ክብረወሰን በ7 ሰኮንዶች ያሻሻለ ሲሆን ከ1993 እኤአ ወዲህ በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫ ሊመዘገብ ፈጣን ሰዓት ተብሎ ከፍተኛ አድናቆት አግኝቷል፡፡ አትሌት ገንዘቤ ዲባባ ከዚሁ የ3ሺ ማይል አዲስ የዓለም ክብረወሰኗ 5 ቀናት በፊት ደግሞ በጀርመን ካርሉስርህ በተደረገ የ1500ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫ በሪከርድ ሰዓት አሸንፋ ነበር፡፡ በ1500 ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫው አትሌት ገንዘቤ ያሸነፈችው ርቀቱን በ3 ደቂቃ ከ55፡17 ሰኮንዶች በማገባደድ ሲሆን አስቀድሞ በሩሲያዊ አትሌት ተይዞ የነበረውን ክብረወሰን በ3 ሰኮንዶች አሻሽላዋለች፡፡

የማህጸን በር ካንሰር፣
በማህጸን አካባቢ የሚፈጠር የቅማል ዘር በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት ከሚተላለፉ  መካከል ናቸው፡፡
ዶ/ር ሰሎሞን ኩምቢ (ተባባሪ ፕሮፌሰር) በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጽንስና ማህጸን ሕክምና ትምህርት አስተማሪ እና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ ዶ/ር ሶሎሞን በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎችን ምንነት እና መፍትሔያቸውን ለዚህ እትም ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
ጥ/    የግብረስጋ ግንኙነት ሲባል ምን ማለት ነው?
መ/    የግብረስጋ ግንኙነት ማለት በተለምዶ የወንድ ብልት በሴቷ ብልት ውስጥ ሲገባ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን እንደሰዎቹ ስምምነት የሚፈጸሙ ሌሎችም የግብረስጋ ግንኙነቶች አሉ?
ጥ/    በሰዎች ስምምነት የሚፈጸሙ ሲባል ምን አይነቶች ናቸው?
መ/    የግብረስጋ ግንኙነት እንደ ሰዎቹ ስምምነት ይፈጸማል ሲባል በእንግሊዝኛው (Oral & Anal) ማለትም አንዳንድ ጊዜ በአፍ እና በፊንጢጣም በኩል ይፈጸማል፡፡
ጥ/    በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎች ሲባል ምን አይነት ናቸው?
መ/    የሚከሰቱትን ችግሮች በግብረስጋ ምክንያት የሚከሰቱ አካላዊ ጠንቆች ቢባሉ የሚሻል ይመስለኛል፡፡ ችግሮቹ የተለያዩ ሲሆኑ በብዛት የሚታወቁት ግን የአባላዘር በሽታዎች ተብለው የሚጠቀሱት ናቸው፡፡ ከዚህ በተለየ ግን ለምሳሌ...
የማህጸን በር ካንሰር፣
የማህጸን በር ካንሰርን የሚያመጡት ቫይረሶች በመሆናቸው ከወንድ ወደሴት በሚተላለፉበት ወቅት ለበሽታው መከሰት እንደ አንድ ምክንያት ይቆጠራል፡፡ አንዲት ሴት የማህጸን በር ካንሰር እንዳይከሰትባት ለመከላከል ሲባል የሚሰጠው ክትባት የግብረስጋ ግንኙነት መፈጸም ከመጀመሩዋ በፊት ቢሆን የሚመረጥ መሆኑን የህክምናው ዘርፍ ባለሙያዎች ያስረዳለሉ፡፡  
በአስገድዶ መደፈር ወይንም በሰምምነት በሚደረግ ግንኙነት ምክንያት የሴቷ ብልት የውስጥ ክፍል መቀደድ፣
በማስገደድም ይሁን በስምምነት በሚፈጸም ግንኙነት ሳቢያ የሚከሰት የሽንት መቋጠር ችግር፣
በግብረስጋ ግንኙነት ጊዜ ከሚፈጠር አግባብ ያልሆነ የኃይል መጠቀም ወይንም የሰውነት አለመመጣጠን ሳቢያ የሚፈጸም ከሆነ በሴቷ ብልት አካባቢ የሚገኙትን አካላት ጭምር የሚያጠቃ ይሆናል፡፡
ማህጸን አካባቢ የሚፈጠር የቅማል ዘር፡-
በማህጸን አካባቢ የሚፈጠር የቅማል አይነት ከወንድ ወደ ሴት ወይንም ከሴት ወደ ወንድ ሲተላለፍ በሚፈጠረው የመራባት ሁኔታ ቅጫም ሊኖረው ሲችል ከዚያም ወደብብት እና ወደ አይን ፀጉር ጭምር ሊተላለፍ ይችላል፡፡ ስሜቱም በብልት ወይንም በብልት ጸጉር ላይ የማሳከክእና የማቃጠል ሊሆን ስለሚችል ሴትየዋ ወይንም ሰውየው እንደዚህ ያሉ ስሜቶች ከታዩባቸው ቶሎ መፍትሔ መውሰድ ይጠበቅባቸዋል፡፡   
የተለያዩ የቆዳ በሽታዎች በግብረ ስጋ ግንኙነት ምክንያት ሊተላለፉ ይችላሉ፡፡
ጥ/    ሁሉንም በሽታዎች በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ ማለት ይቻላል?
መ/    የሚተላለፉት …Sexually transmissible infectious… ተብለው የሚለዩት ናቸው፡፡ እነርሱም በአማርኛው ጨብጥ፣ ቂጥኝ፣ ውርዴ፣ አባኮዳ፣ ባምቡሌ፣ የሴቶችን ፈሳሽ የሚያመጣ ፕሮቶዝዋ፣ ካንዲዳ የሚባል የፈንገስ አይነት እና ሌሎችም በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ ተብለው የሚፈረጁ ሕመሞች አሉ፡፡ ነገር ግን በብዛት በማህጸን አካባቢ የማህጸኑ፣ የቱቦው እና የእጢው መቆሸሽ (Pelvic inflammatory disease) በሚባል የሚጠራውን ሕመም የሚያመጡት ጎኖሪያ (ጨብጥ)፣ ክላይሚድያ፣ ማይኮ ፕላዝማ እና ዩሪያፕላዝማ የሚባሉ የህዋስ አይነቶች ናቸው፡፡ ስለዚህ ከግብረስጋ ግንኙት ጋር የሚያያዝ ችግር ነው ብሎ መውሰድ ይቻላል፡፡
ጥ/    በተላላፊ በሽታዎቹ ምክንያት የሚከሰተው ሕመም ምን ይመስላል?
መ/    ከተላላፊ በሽታዎቹ ጋር ያሉት ጠንቆች ከማህጸን በላይ እርግዝና፣ ማህጸን ወይንም ብልት አካባቢ የሚኖር ሕመም፣ መካንነት ወይንም ልጅ አለመውለድ፣ በውስጥ አካል (ጉበት)፣ የሆድ እቃ አካባቢ መሰራጨት፣ የአእምሮ፣ የቆዳ፣ የልብ ኢንፌክሽን የማምጣት ...ወዘተ የመሳሰሉትን ሕመሞች ሊያስከትል ይችላል፡፡ ከተጠቀሱት ሕመሞች በተጨማሪም በአለም አቀፍ ደረጃ በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት በመተላለፍ በሽታ ከሚባሉት ውስጥ ኤችአይቪ ቫይረስም አንዱ ነው፡፡
ጥ/    ከግብረስጋ ግንኙነት ጋር ተያይዘው የሚመጡ የሰውነት ጠንቆች ሲባል ምን ማለት ነው?
መ/    ከግብረስጋ ግንኙነት ጋር ተያይዘው የሚመጡ የሰውነት ጠንቆች ሲባል ከላይ እንደገለጽኩት ግንኙነት የሚደረግበት የሴቷ ብልት መቀደድ፣ ፊስቱላ የመሳሰሉት ነገሮች ባህሪያቸው መተላለፍ ሳይሆን በግንኙነት ምክንያት የሚከሰቱ ጠንቆች ሊባሉ የሚችሉ ናቸው፡፡ የማህጸን በር ካሰርንም በቀጥታ ተላላፊ በሚል ከባድ ድምዳሜ መስጠት ባይቻልም ቀደም ሲል ካንሰሩ የነበረባት ሴትጋር በወሲብ የተገናኘ ሰው ወደሌላ ሴት ሲሄድ ቫይረሱን ሊያስተላልፍ ይችላል የሚሉ አስተያየቶች አሉ፡፡
ጥ/    ተላላፊ የተባሉት በሽታዎች በዚህ ዘመንም አሉ? ወይንስ?
መ/    በእርግጥ በግሌ በቅርብ ያጠናሁት ጥናት የለም፡፡ ነገር ግን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎችን ወይንም የአባላዘር በሽታዎችን በጤና ጣቢያ ደረጃ በቀላል እንዴት ማከም እንደሚቻል ለማሳየት መመሪያ ሲያወጣ የተሰራ ጥናት እንደሚያሳየው ጎኖሪያ፣ ክላሚድያ፣ ትሪኮሞኒያሲስ፣ ካንዲድያሲስ የተባሉት ሕመሞች አሁንም ያሉ ሲሆን እንዲያውም በመሪነት ደረጃ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡  ባጠቃላይ ግን ሕመሞቹ በሙሉ አሁንም አሉ ማለት ይቻላል፡፡
ጥ/    በተላላፊ በሽታዎች ምክንያት የሚፈጠሩ የማሳከክ ስሜቶችን ጨው በመሳሰለው ነገር በመጠቀም መታጠብ ምን ይህል ይረዳል?
መ/    አንዳንድ ሴቶች ውሀ በማፍላት በጨው የመታጠብ ወይንም የመዘፍዘፍ እርምጃን ይወስዳሉ፡፡ ይህ በሰዎች ዘንድ ጥሩ ስሜትን ሊፈጥር ይችላል፡፡ ጨው ተፈጥሮአዊ ነገር ስለሆነ ምናልባት የማቃጠል ስሜት ይኖረው እንደሆነ እንጂ ጉዳቱ ብዙም አይታየኝም፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ኬሚካሎችን እንደመታጠቢያ መውሰድ በቁስል ወይንም በተቆጣ ሰውነት ላይ ሌላ ችግር ሊያስከትል ስለሚችል አይመከርም፡፡ ጨው ግን ብዙም ጥቅሙ ባይታወቅም ጉዳት ግን የለውም፡፡
ጥ/    ሰዎች እንደመፍትሔ ሊወስዱት የሚገባ እርምጃ ምንድነው?
መ/    መፍትሔውን ስናስብ በቅድሚያ ትኩረት መደረግ ያለበት ጥንቃቄ የተሞላበት የግብረስጋ ግንኙነት ማድረግ ነው፡፡ ይህም ማለት መከላከል የሚቻልበትን ዘዴ መጠቀም ሲሆን ለዚህም አንዱ የሴቶችና የወንዶችን ኮንዶም መጠቀም ማለት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በተለይም ወጣቶች ከትዳር በፊት የግብረስጋ ግንኙነት ማድረግ እንደማይገባቸው ይመከራል፡፡ ይህ ሀይማኖታዊ ብቻ ሳይሆን በሳይንሱም መንገድ የሚመከር ነው፡፡ ለወጣቶቹ እንደአማራጭ የሚመከረው ፍቅራቸውን በመላፋት ወይንም በመሳሳም ደረጃ ገድበው እንዲይዙት ነው፡፡ ከዚህ በተረፈ የሰውነትን እምቅ የሆነ ስሜት ለማውጣት Masturbation መጠቀም አንዱ ሳይንሳዊ ምክር ነው፡፡ ሁኔታዎች ከዚህ በላይ የሚገፉ ከሆነ ግን ሁለቱም ፍቅረኛሞች ምርመራ አድርገው የጤንነት ሁኔታቸውን በማረጋገጥ ግንኙነት ማድረግ ይችላሉ፡፡ ይህ ምክር የሚሰጠው ለኤችአይቪ ብቻ ሳይሆን ለአባላዘር በሽታዎችም ነጻ መሆን አለመሆን ማረጋገጫነት የሚመከሩ ናቸው፡፡ ከምር መራው በሁዋላም ከዚያ ከሚያውቁት ሰው ጋር ብቻ ግንኙነት ማድረግ ይገባቸዋል፡፡ የአባላዘር በሽታ በወንዶች ላይ ቶሎ ሲገለጽ በሴቶች ላይ ግን በተፈጥሮ ምክንያት ቶሎ ላይታወቅ ይችላል፡፡ ስለሆነም ሕመሙም በጊዜው ስለማይደረስበት በሴቶች ላይ ይበረታል፡፡ ነገር ግን የአባላዘር በሽታዎች ሊታከሙ ወይንም ሕመማቸውን ለመቀነስ የሚ ችሉ ናቸው፡፡ ስለዚህም ባጠቃላይ የሚሰጠው ምክር...
ችግሩ ከመከሰቱ በፊት አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ
ችግሩ ከተከሰተ በግልጽ ከፍቅረኛ ወይንም ከትዳር ጉዋደኛ ጋር መመካከር
ችግሩ ከተከሰተ በአስቸኳይ ወደጤና ተቋም በመሄድ ማማከር ይገባል፡፡
    ሰዎች አስቀድመው አስፈላጊውን እርምጃ ከወሰዱ ቫይረሶቹ፣ ባክቴሪያዎቹ፣ ፈንገሶቹ እና የፕሮቶዞዋው እና ቅማሉን ጨምሮ የሚታከሙና ሊድኑ የሚችሉ ናቸው፡፡





ኮሪያ እስከ ሁለተኛው የአለም ጦርነት ማብቂያ ድረስ የጃፓን ቅኝ ግዛት ነበረች፡፡ የሁለተኛው የአለም ጦርነት በጃፓን ሽንፈት ተጠናቀቀ፡፡ ሽንፈቷን ተከትሎ የጃፓን አገዛዝ በኮሪያ ላይ አበቃ፡፡ አሜሪካን ቻይና እና ታላቋ ብሪታኒያ የካይሮ ስምምነት በመባል የሚታወቀውን ሰነድ አፀደቁ፡፡ የኮሪያ ሰሜኑ ክፍል በሶቪየት ህብረት፤ ደቡብ ክፍል ደግሞ በአሜሪካን የሞግዚት አስተዳደር ስር እንዲቆይ የሚያደርገው ስምምነት ተግባራዊ ሆነ፡፡ ይህ ክፍፍል ዘላቂ ይሆናል ተብሎ የታሰበ ባይሆንም፣ የሁለተኛውን የአለም ጦርነት ማብቃት ተከትሎ አሸናፊዎቹ ሀይሎች የቀዝቃዛው ጦርነት ሰለባ የማድረግ ብቃት ስለነበራቸው የተከናወነ ነበር፡፡ የቀዝ
ቃዛው ጦርነት ሁለት ተቃራኒ ጎራዎች ቀደም ብለው የኮሪያን ሰሜንና ደቡብ በመከፋፋላቸው፣ ኮሪያውያን የቀዝቃዛው ጦርነት ማሟሟቂያ ሆኑ። በ1950 ሰሜን ኮሪያ በቻይናው ማኦ ዜዱንግ እና በስታሊን አለሁ ባይነት ደቡብ ኮሪያን ወረረች። ከሶስት አመት በኋላ በተደረሰ ስምምነት ጦርነቱ አብቅቶ፣ ሰሜን እና ደቡብ  ኮሪያ የሚለው  ክፍፍል ቋሚ ሆኖ ፀና፡፡ የስምምነቱ አካል በሆነው እና የኮሪያን ጉዳይ ለማየት በሚል የተጠራው የጄኔቫ ኮንፈረንስም ምንም እንኳን ከብዙ አገሮች የአንድነት አንጀንዳ ብልጫ እንዲያገኝ ቢሞከርም የኮሪያውያኑን አንድ ማድረግ ሳይችል ተበተነ፡፡
እጣፈንታቸው በሌሎች እንዲወሰን ግድ የሆነባቸው ኮሪያዎች፤ ደቡብ እና ሰሜን ተብለው ሲለያዩ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ዝምድና ከድንበር ጋር አብሮ እንዲቆራረጥ ሆነ፡፡ ሰሜን ኮሪያ እና ደቡብ ኮሪያ የሚገኙ የአንድ ቤተሰብ አባላትን የነጠለው ውሳኔ፣ ከሀያ ሁለት አመታት በኋላ ይፋ በተደረገ ሚስጥር መፍትሄ ያገኘ መሰለ፡፡ የሁለቱ አገሮች መሪዎች በድብቅ አንዱ የአንዱን ዋና ከተማ እንደጎበኙ እና ዋና የጉብኝቱ አላማም የሁለቱ ኮሪያዎች ሰላማዊ ውህደትን በመሻት የተከናወነ መሆኑን የሁለቱ ሀገር መሪዎች ገለፁ፡፡ የሰሜንና የደቡብ ኮሪያ የጋራ ስምምነት የተባለ ሰነድ መፈራረማቸውን አወጁ። ይሁን እንጂ፤ ይህን ያስፈፅማሉ በሚል ከሁለቱ አገሮች በተውጣጡ ልዑካን የተቋቋመው ኮሚቴ ያለምንም ውጤት ከአንድ አመት በኋላ ታገደ፡፡ በ1990 የሁለቱ ኮሪያዎች ጠቅላይ ሚኒስትሮች  ሲኦል ላይ ተገናኝተው የኮሪያውያንን አንድነት በተመለከተ ውሳኔዎችን ቢያስተላልፉም፣ ከኒኩሊየር ማበልፀጊያ ፖለቲካ ጉዳይ ጋር የተያያዘ ውዝግብ በመፍጠሩ ውጤት አልባ ሆነ፡፡ ከአመት በኋላ፤ እንደገና የሰሜን እና የደቡብ ኮሪያ የጋራ ስምምነትን የሚገልፅ ሰነድ አወጡ፡፡  የሰነዱ ዋነኛ አላማም፤ የሁለቱን ኮሪያዎች ሰላማዊ ውህደት የሚመለከት እንደሆነ አወጁ፡፡
የዚህ ውህደት እርምጃ በ2000 ተጀምሮ በ2007 በሰሜን ኮሪያ መንግስት ውሳኔ እንዲቆም የተደረገው ከሀምሳ አመታት በላይ የተለያዩ ቤተሰቦችን የማገናኘቱ ስራ ሰሞኑን እንደገና አገርሽቶ የመገናኛ ብዙሀን ትኩረት ሆኗል፡፡ ቤተሰቦችን ማገናኘቱ በሚቀጥለው ወር እንደሚጀመር ከስምምነት ላይ ተደርሶ የነበረ ቢሆንም ደቡብ ኮሪያ ከአሜሪካን ጋር በምታደርገው የፖለቲካ ወንድማማችነት ምክንያት ውሳኔዬን ልሰርዝ እችላለሁ ስትል ሰሜን ኮሪያ አስጠንቅቃለች፡፡
በተለያዩ የፖለቲካ ወገንተኞች ፍላጎት እና ውሳኔ፤ እንዲሁም ፅንፈኛ አቋም በያዙ መሪዎቻቸው እሰጥአገባ ሳቢያ የተነጣጠለ የቤተሰብ አባላትን የማገናኘቱ ፕሮግራም ለኮርያዊያኖች ከጥልቅ ስሜታቸው ጋር የተያያዘ ጉዳይ ነው፡፡ ቀን በሄደ እና እድሜ በገፋ ቁጥር በሞት መለየት ሊመጣ እንደሚችል ሲያስቡት ጉጉታቸው የበለጠ ይበረታል፡፡
የደቡብ ኮሪያ የቀይመስቀል ማህበር ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በ1988 ከቤተሰባቸው ጋር ለመቀላቀል ማመልከቻ ካስገቡ 127፣400 በሰሜን ኮሪያ የሚኖሩ ዜጐች ውስጥ አርባ ሺህ ያህሉ ቤተሰቦቻቸውን መቀላቀል ሳይችሉ ህይወታቸው ማለፉን ለማወቅ ተችሏል፡፡ እስከ አሁን 16ሺ 200 ኮሪያውያን በአካል፣ 3ሺ 740 የሚሆኑት ደግሞ በቪዲዮ ከቤተሰባቸው ጋር እንዲገናኙ ለማድረግ ተችሏል፡፡ ቤተሰቦችን የማገናኘቱ ፕሮግራም ከመጀመሩ በፊት ባሉት ቀደምት አመታት፣ ኮሪያውያኑ በያሉበት ከቤተሰቦቻቸው ጋር የፖስታ የስልክም ሆነ የኢሜይል መልእክት መለዋወጥ የማይችሉ ሲሆን ያለ መንግስት ፈቃድም ድንበር ማቋረጥ ተከልክለው ቆይተዋል፡፡
የ“ሁለቱ ኮሪያዎች ውህደት” የሚለው መፈክር ለዘለቄታው ተግባራዊ አይሆንም የሚሉ ወገኖች አሉ። ለዚህ ሀሳባቸው በመከራከሪያነት የሚያቀርቧቸውን ማሳመኛዎች አንድ ሁለት ብለው ይዘረዝራሉ፡፡ አንደኛ፤ ሁለቱ ኮሪያዎች በመለያየት ባሳለፏቸው አመታት ውስጥ ብዙ የተለያዩ ማንነቶችን አብቅለዋልና ይህ ልዩነት መቼም ወደ መታረቅ ሊመጣ አይችልም፤ ይላሉ፡፡
ሁለተኛ፤ ተለያይተውም በቆዩበት ብዙ አስርት አመታት የነበራቸው ግንኙነት እጅግ የሻከረ መሆኑ ለውህደት ባይሆንም … ቢያንስ በሁለቱ መሀል ያለውን ውጥረት ለማርገብ ሊያግዝ ይችል ይሆናል። ሶስተኛው፤ ከቤተሰቦቻቸው ጋር መቀላቀል የሚፈልጉት ኮሪያውያን እድሜ ሰባ እና ከዛ በላይ በመሆኑ፤ ኮሪያን አንድ በነበረች ጊዜ የሚያውቃት ትውልድ እየከሰመ በአዲስ ትውልድ በመተካቱ ምክንያት ነው፤ ብለው ማሳመኛዎቻቸውን ይተነትናሉ፡፡ የውህደት ጥያቄውም ልክ እንደ ትውልዱ እየከሰመ ይሄዳል፤ ውህደቱ ለቀድሞው ትውልድ እንጂ ለአዲሱ ትውልድ ትርጉም የሚሰጥ ሊሆን አይችልም ይላሉ፡፡
በቀዝቃዛው ጦርነት ምክንያት ሁለት አገር የሆኑት ኮሪያውያን፤ ሰሞኑን ደግሞ ደቡብ ኮሪያ ከአሜሪካን ጋር ወግናለች በሚል ምክንያት ከሀምሳ አመታት በላይ ከተለዩዋቸው ቤተሰቦቻቸው ጋር የመገናኘት ህልማቸው ጥያቄ ላይ ወድቋል፡፡

“በሰው ስራ ታውቆ የራስን መስራት ፈተና አለው”

ከጥቂት ዓመታት በፊት በዝነኛው ድምፃዊ ሙሉቀን መለሰ ሥራዎች ከአድማጮች ጋር የተዋወቀውና ተወዳጅነትን ያተረፈው አርቲስት ብዙአየሁ ደምሴ፤ በቅርቡ “ሳላይሽ” የተሰኘ የራሱን የመጀመርያ አልበም ለጆሮ አብቅቷል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየው ገበያው አልበሙ ከወጣ ጊዜ አንስቶ ድምፃዊውን ለማግኘት ስትታትር ቆይታ ባለፈው ረቡዕ ምሽት ተሳክቶላታል፡፡ ድምፃዊውን አሁን ከሚኖርበት ካናዳ በስልክ አግኝታው በአዲሱ አልበሙና በሙያው እንዲሁም በህይወቱ ዙሪያ እንደሚከተለው አነጋግራዋለች፡፡

ደህና አደርክ ልበል፣ ደህና ዋልክ? እኛ ጋ ከቀኑ አስር ሰዓት ነው...
ደህና አደርክ ነው የሚባለው፤ እኛ ጋ ከጠዋቱ 1 ሰዓት ነው፡፡ ግን አንቺ እንዴት ዋልሽ..?
በጣም ደህና ነኝ፡፡ አንተስ እንዴት አደርክ..ለነገሩ ድምፅህም የጠዋት ድምፅ ነው…
አዎ! ከእንቅልፌ እየተነሳሁ ነው፤ ጠዋት ስለሆነ ነው ድምፄ የጎረነነብሽ…እግዚአብሄር ይመስገን በጣም ደህና ነኝ፡፡ አገር ሰላም ነው? ሁሉ አማን? እኔ ሰላም ነኝ
ቤተሰብህን ጠቅልለህ ነው እንዴ ካናዳ የገባኸው..?
ቤተሰቦቼ ኢትዮጵያ ናቸው፤ ልጆቼም ባለቤቴም፡፡
በዚያው ቀልጠህ ቀረህ እኮ! ለመሆኑ አካሄድህ ለስራ ነው ለኑሮ?
ለነገሩ አሁን ሁሉ ነገር ስላለቀ መምጣት እችላለሁ፡፡ ለተወሰኑ ጊዜያት ለስራ ነበር የሄድኩት።
አዲሱ ‹‹ሳላይሽ›› አልበምህ እንዴት ነው? ተቀባይነት አገኘ? እስካሁን ምን ያህል ቅጂዎች ተሸጡ?
በትክክል ይሄን ያህል ኮፒ ተሸጧል ማለት መረጃው የለኝም፡፡ ነገር ግን ሙዚቃዬን ካሳተመልኝ የናሆም ሪከርድስ ባለቤት ጋር በየቀኑ እንገናኛለን፡፡ እንደ አሳታሚ ሳይሆን እንደጓደኞች ነን፡፡ እናም ባለቤቱ፤ “ብዙ አልበም ሰርቻለሁ፤ በዚህ ፍጥነት የተደመጠ ብዙ አልገጠመኝም”፤ ብሎኛል፡፡ እንዲህ በመሆኑም በጣም ተደስቻለሁ፡፡ የካናዳን ነገር ደግሞ ከምነግርሽ በላይ ነው፡፡ ሙዚቃው እንዴት እንደሚደመጥ አልነግርሽም፡፡ በቃ ያስደነግጣል .. ይሄን ያህል እደመጣለሁ እንዴ? ብዬ በእጅጉ ተደንቄአለሁ፡፡ አሳታሚዬ ናሆም ሪከርድስ ደግሞ አሜሪካ ነው ያለው፡፡ እሱ እንደነገረኝ እዚያም እጅግ በጣም ጥሩ ነው፤ ኢትዮጵያ ይደመጣል የሚባለው ያህል ሳይሆን አይቀርም ከፍተኛ ተ    ቀባይነት አግኝቷል፡፡
እስከዛሬ እንግዲህ በሰው ዘፈን ነበር የምትታወቀው፡፡ ከሰው ዘፈን ወደ ራስ ሥራ የመሸጋገሩ ሁኔታስ ምን ይመስላል? መቼም ፈታኝ እንደሚሆን እገምታለሁ …
አዎ፤ ከሰው ዘፈን ወጥተሽ የራስሽን ኦርጂናል ስራ ስትሰሪ በጣም ከባድ ነው፡፡ ምክንያቱም የራስ ዘፈን ሲሆን ራስሽን ሆነሽ ነው የምርቀርቢው። በተለይ በሰው ስራ ታውቀሽ ቆይተሽ የራስሽን ስትሰሪ ትንሽ ፈተና አለው፡፡
በአዲሱ አልበምህ ላይ በድምጽህም ሆነ በአዘፋፈን ዘይቤህ የሙሉቀን መለሰ ተፅዕኖ ጎልቶ እንደሚታይብህ ይነገራል፡፡ ይህን አስተያየት ትቀበለዋለህ?
አንዳንድ ጊዜ የምትወጅው ነገር የግድ ይስብሻል። ጥሩ ነገር ማን ይጠላል ብለሽ ነው… (ሳቅ)
የመጀመሪያ አልበምህ ሙሉ በሙሉ የሙሉቀን መለሰ ነበረ፡፡ ለአንዱ ዘፈን እንደውም የቪዲዮ ክሊፕ ሁሉ ሰርተህለታል፡፡ በዚህም ከሙሉቀን ጋር ተጋጭተህ ነበር፡፡ በአዲሱ አልበምህ ደግሞ አንድ የሙሉቀን መለሰ ዘፈንን ተጫውተሃል፡፡ አሁንስ አስፈቅደኸው ነው?
አዲስ የሰራሁት አይደለም፤ ከመጀመሪያ አልበም የተረፈ ነው፡፡ እንደውም መጀመሪያ ላይ ማካተት አልፈለግሁም ነበር፡፡ በኋላ የመጣ  ሃሳብ ነው፡፡ እሱም ቢሆን ግን ለኤሌክትራ ባለቤት እንዲሁም ለግጥምና ዜማ ደራሲዎቹ  አስፈላጊው ክፍያ ተፈፅሟል፡፡ ‹‹አትከብደኝም እስዋ›› የሚለውን ነው በአዲሱ አልበም ውስጥ ያካተትኩት፡፡
በነገርሽ ላይ አሜሪካ ሳለሁ ከጋሽ ሙሉቀን ጋር በጣም እንገናኝ ነበር፤ ካናዳ ከመጣሁ ነው የተጠፋፋነው፡፡ እና ለዚህ የሙሉቀን ዘፈን ብቻ የወጣው ብር በጣም ብዙ ነው…የናሆም ሪከርድስ ባለቤት አቶ ኤልያስ ነው የከፈለው፡፡
አዲሱ አልበምህ መለቀቁን ተከትሎ ከተለያዩ አገራት የኮንሰርት ጥያቄዎች አልቀረቡልህም?
አሁን በተጨባጭ ብዙ ስራዎች፣ ብዙ ኮንሰርቶች እየመጡልኝ ነው፡፡ አልበሙ በየቤቱ ይግባ እንጂ ሥራው ችግር የለውም፤ ይመጣል፤ ሰው ውስጥ እስኪዋሃድ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ከፋሲካ በኋላ የኮንሰርት ጉዞዬን እጀምራለሁ፡፡ እስከዛ ግን ሁለት ነጠላ ዜማዎች እለቃለሁ፡፡ በተለይ አንዱ ነጠላ ዜማ በበዓል መዳረሻ ላይ ነው የሚሆነው፤ ያለቀ ስራ ነው፡፡
‹‹ሳላይሽ›› በሚለው አልበምህ ከህይወትህ ጋር የሳሰረ ዘፈን አካተሃል?
አዎ አለ፡፡ ‹‹የህልሜ ንግስት›› የሚለውን ለባለቤቴ ነው የዘፈንኩት፡፡ ከእግዚአብሄር በታች አጠገቤ ሆና ትረዳኝ የነበረች እሱዋ ነች፡፡ ‹‹ንገሪኝ›› የሚለውን ደግሞ ለእናቴ ነው የዘፈንኩት፡፡
አሁን ካናዳ ውስጥ በምን ስራ ነው የምትተዳደረው?
ሙዚቃ ነው የምሰራው፡፡ ከሙዚቃ ውጪ ምንም ነገር አልሰራም፡፡ ራሴን በሙዚቃው ዘርፍ ለማሳደግ ጥናቶች እያደረግሁ ነው፡፡ መተዳደሪያዬ ግን ሙዚቃ ነው፡፡
ለአዳዲሶቹ ዘፈኖችህ ቪዲዮ ክሊፕ ለመስራት አላሰብክም?
‹‹ሳላይሽ›› እና ‹‹ማመኔ›› ለሚሉት ዘፈኖች እዚህ ክሊፕ ሰርቼ እያለቀ ነው፡፡ በቅርቡ አድናቂዎቼ እጅ ይገባል፡፡
ቴዲ አፍሮ በስራህ እንደሚያደንቅህና ዝምድና እንዳላችሁ ሰምቻለሁ፡፡ ስለ አዲሱ አልበምህ አስተያየት ሰጠህ?
አዎ ዝምድና ነገር አለን፡፡ ዘፈኖቼን ብዙ የሰማ አልመሰለኝም፡፡ እስካሁን ምንም አይነት አስተያየት አልደረሰኝም፡፡
ካናዳ ለአርቲስቶች እንዴት ናት? ትመቻለች?
ውይ አትመችም፡፡ ከባድ ነው፤ እኔ እድለኛ ስለሆንኩ ነው፡፡ እዚህ ያለን አርቲስቶች የተወሰንን ነን፡፡ ሄኖክ አበበ፣ ፋንታሁን ሸዋንቆጨው፣ ይርዳው ጤናው፣ እና ሌሎችምሰ አሉ፡፡ ካናዳን እንደማረፊያ ነው የሚጠቀሙባት፤ የተለያዩ አገራት እየሄዱ ኮንሰርት እየሰሩ ይመጣሉ፡፡ ባለፈው ከአስቴር አወቀ ጋር ‹‹እንደ ወፍ›› በሚለው ዘፈን እየዞርኩ ኮንሰርት እንዳቀርብ አስበው ነበር፡፡ ነገር ግን ይኼንን አልበሜን ለመስራት አራት ዓመት ነው የፈጀብኝ፡፡ ትኩረቴ ሁሉ እሱላይ ነበር፡፡ አልበሜን ከዳር ሳላደርስ የትም አልንቀሳቀስም ብዬ ነው የቀረው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ኮንሰርት ለማቅረብ ሃሳብ የለህም? መቼ እንጠብቅ?
ኢትዮጵያ ላይ በቅርቡ አንድ ነገር ለማድረግ አስበናል፡፡ እስከዛው ለአድናቂዎቼ እንዲሁም ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ እጅግ እንደምወዳቸው መልዕክት አስተላልፊልኝ፡፡ እግዚአብሔር ሁሉን ነገር ስላስተካከለልኝ አመሰግናለሁ፡፡ ባለቤቴ፣ ልጆቼ፣ አባቴን ጨምሮ አብረውኝ የነበሩትን ሁሉ አመሰግናለሁ፡፡ ለዚህ አልበም በስኬት መጠናቀቅ ከመጀመሪያ እስከመጨረሻ አብረውኝ ለሰሩና ከጐኔ ላልጠፉት አማኑኤል ይልማና አቀናባሪ ወንድሜነህ ምስጋናዬ ይድረሳቸው፡፡ የናሆም ሪከርድስ ባለቤት አቶ ኤልያስንም በእጅጉ አመሰግነዋለሁ፡፡

እነሆ ወርሃ የካቲት መጣ፡፡
አበቦች አንገታቸውን ማስገግ የሚወዱበት ወቅት ነው፡፡ የሚኳኳሉበት፡፡ ከብጤዎቻቸው ይበልጥ አምረው ደምቀው ይመረጡ ዘንድ የሚዋትቱበት፡፡ “እኔን! እኔን!” የሚሉበት፡፡ አበቦች እንደዚህ ወቅት ተወዳጅ የሚሆኑበት ጊዜ ይኖር ይሆን?
የፍቅረኞች የመሽሞንሞኛ ቀን “ቫለንታይንስ ዴይ” ሰሞኑን ተከበረ አይደል! ከአንዱ ዓመት ወደ ሌላኛው እንደምን እየሰፋ፣ እየተንሰራፋ፣ እየገዘፈ እንደመጣ ለማስረገጥ ምስክር ጥራ አልባልም መቼም፡፡ ግድየለም የቢዝነስ ጋዜጦቻችን የስጦታ ገበያ ሸመታውን አስልተው፣ ከቀድመው ጊዜ ጋር አነጻጽረው ይነግሩናል፡፡ የሬዲዮ አሰናጆች ድምጻቸው አለሳልሰው፣ ሙዚቃቸውን አቀዝቅዘው የዕለቱን አዋዋል በተለይ ደግሞ አመሻሽ አትተውልናል፡፡ እኔ ግን “እባካችሁ --- የአምልኮተ- ሮማንስ ሩጫችሁን ቀንሱ!” እላለሁ፡፡
በመጀመሪያ ማጥራት ያለብን እሳቤ አለ፡፡ (አንድ ሰሞን ፈሊጥ እንደነበረው “ፍቅር አለ ወይስ የለም?” የሚል ሞኛሞኝ ክርክር ውስጥ ራሴን መዶል አልፈልግማ!) የቃላት አጠቃቀሙ በራሱ ችግር ያለበት ይመስለኛል፡፡ እርግጥ ነው አንዲት ቀዘባ እና ወዳጇ የሚጀመሩትን ፍቅር ነክ ግንኙነት ለመግለፅ love፣ relationship፣ dating  የተባሉ ቃላትን እያቀያየሩ  መጠቀም ተለምዷል፡፡ (“የከንፈር ወዳጅ” ይሏት ሀረግ ግን ትርጉሟ ተምታቷል እንጂ እንደምን ገላጭ ናት!) የኋለኞቹ ሁለት ቃላት (dating እና relationship) romance  በሚባለው ኮሮጆ ሊቋጠሩ የሚገባቸው ናቸው፡፡ እና በlove እና romance መካከል ትልቅ የትርጉም ልዩነት አለ፡፡
Love ጠሊቅ ነው፡፡ ረጅምም ነው፡፡ ጓደኝነት ነው፡፡ ንብቡነት ነው፡፡ አገልግሎት ነው፡፡ ተረት የሚመስል ስሜት አይደለም፡፡ እናት ወህኒ የወረደ ልጇን ለአፍታ እንኳ ቅያሜ ሳትይዝበት፣ለአንድም ቀን ሳታዛንፍ ተመላልሳ ስትጠይቀው እናያለን። አባት ግላዊ ምቾቱን ትቶ ከንጋት በፊት ከቤት ወጥቶ ሲፍገመገም እየዋለ፣ ማታውን ደግሞ ከልጆቹ ጋር ሲጫወት ለማምሸት ተብከንክኖ እቤቱ በጊዜ ይገባል፡፡ ባለትዳሮች ለሰላሳና አርባ አመታት ህመም እና ፈውሳቸውን ሲጋሩ እናስተውላለን፡፡ በጋሽ ስብሃት አጭር ታሪክ “ዔሊን ድንጋይ ያለበስክ” ላይ በአሮጊቷ በኩል የሚነገር ነው፡፡ (“ለምን ይለምናሉ?” ብሎ ጠየቃቸው ተራኪው አሮጊቷን። ልጃቸውን ብለው ተንከራተቱ፡፡ ልጃቸው አድጎ ሲያገባ ሚስቱ ጠላቻቸው፡፡ አሮጊቷ ልጃቸውን ፈተና ውስጥ ሊከቱት አልሻቱም፡፡ እርሱም አሁን ወልዷል፡፡ የልጁን ፍቅር ያውቁታል፡፡ ስለዚህ ሹልክ ብለው ወጡለት፡፡) ትንንሽ የሚመስሉ ትልልቅ መስዋእትነቶች ድምር ነው - love
Romance በአንፃሩ ይሄንን ሁሉ አይደለም። የሆሊውድ የእጅ ሥራ ነው (በርግጥ አንድሩ ሱሊይቫን የተባለ እና ከአስራ ምናምን ዓመታት በፊት በኒውዮርክ ታይምስ መፅሄት ላይ “The Love Bloat” የሚል ርዕስ ያለው መጣጥፍ ያሳተመ ፀሃፊ እንደሚለው፣ ሮማንስን  የፈጠረው ፈረንሳዊው ፈላስፋ ሩሶ ነው፡፡ ወደ እርሱ መመለሴ አይቀርም።) ሮማንስ ቀመር አለው፡፡ ቀመሩን አምርቶ ለዓለም ህዝብ ሁሉ የሚያስተምረው ደግሞ ሆሊውድ የተባለው ተረት አምርቶ የሚተዳደር ኢንዱስትሪ ነው፡፡ በቀመራዊ የሮማንቲክ ኮሜዲ ፊልሞች። (ሆሊውድና የአሜሪካ የሸማችነት ባህል ይሄንን አምልኮ ባይፈጥሩትም የተለጠጠ ፋይዳውን በመፍጠር ግን የድርሻቸውን ሚና እንደተጫወቱ አያጠራጥርም) አሁን ልፋቱ ሁሉ ተሳክቶለት የመላው ዓለም ወጣቶች፣በአምልኮተ ሮማንስ ተሰልበው ሲሸነጋገሉ ያመሻሉ፡፡ በሆሊውድ በተደረሰው ማኒፌስቶ መሰረት፣የሮማንስ መገለጫዎች የማያሻሙ ናቸው፡፡ አንዲትን ሴት ለdate መጠየቅ - ብዙ ጊዜ የራት ግብዣ ነው፡፡ ምርጥ ምግብ ቤት መመረጥ አለበት፡፡ በተቻለ መጠን ያንን ምሽት እንስቷ ተረት በሚመስል ስሜት ውስጥ ተንሳፋ እንድታሳልፈው እንዲያስችላት ይጠበቃል ከወንዱ። ልክ ለስራ ቅጥር የሚደረግ ፈተና የሚመስል አይነት ነገር አለበት፡፡ ከተሳካለት እና ምሽቱ በሚገባ ካለፈ ቤት ድረስ ይሸኛታል፡፡ ይስማታል፡፡ እና “ድንቅ ጊዜ ነው ያሳለፍኩት፣ አመሰግናለሁ” ይባባላሉ። ከዚያ ለጓደኞቻቸው “We are dating” ወይንም “We are seeing each other” ይላሉ፡፡ Love የምትባለውን ቃል ለረጅም ጊዜያት ምናልባትም ለወራት እና ዓመታት አይጠቀሙባትም፡፡ ወንድየው የልደት ቀኗን መርሳት የለበትም፡፡ የምትነግረውን ዝባዝንኬና እንቶ ፈንቶ ሁሉ ማዳመጥ አለበት፡፡ ደግሞ የተረት ተረቱ የመጨረሻው  ደረጃ (ጡዘት) በወርሃ የካቲት ይመጣል፡፡ የቅዱስ ቫላንታይን ቀን፡፡ አበባው ይገዛል፡፡ ወደ ምግብ ቤት ሄዶ ራት ይበላል፡፡ ስጦታም ይበረከታል፡፡ ከዚህም የተሻገረ ነገር ይኖራል፡፡ ሽርሽር ይሰናዳል፡፡ የ”አግቢኝ” ጥያቄ ይጠበቃል፡፡ ደግሞም ጥያቄው ድራማዊ መሆን አለበት፡፡ ይሄ የማይዛነፍ ቀመር የሚጠቅመው እንግዲህ የፊልም አምራቾችን፣ የምግብ ቤት ባለቤቶችን፣ የስጦታ እቃ ሻጮችን እና አበባ ነጋዴዎችን ነው፡፡ እነርሱም ለዕለቱ በሚገባ ነው የሚዘጋጁት፡፡ በዕለቱ ያለ ተጣማሪ መሆን የብቸኛነት ትርጉም ተደርጎ ይታሰባል፡፡
ልዩነቱ ግልጽ ነው፡፡ Love is authentic, Romance is counterfeit. ፍቅር ቱባ ነው። ሮማንስ ቅጂ፡፡ (ዲ.ኤች.ሎረንስ “Lady Chatterley’s Lover” ለተባለው አወዛጋቢ ልቦለዱ ማብራሪያ ይሁን ብሎ በፃፈው መጣጥፉ “Apropos of Lady Chatterley’s Lover” ላይ ይኼንን ኹኔታ አሳምሮ ገልፆታል፡፡ ሮማንስ  ውስጥ ያሉ ሰዎች “ምን ዓይነት ስሜት ሊሰማቸው እንደሚገባ ያውቁታል፣ ስለዚህም ያንን ስሜት ያድኑታል ግን እውነተኛ ስሜት አይደለም” ቃል በቃል ማስታወስ ባለመቻሌ ይቅርታ መጠየቅ ይገባኛል፡፡)
“ፍቅር ሁሉንም ነገር ይቆጣጠራል እንባላለን” ይላል- ከላይ የጠቀስኩት ጸሐፊ ሱሊይቫን ደግሞ፡፡ ነገር ግን በቫለንታይን ቀን የሚከበረው ፍቅር ምንም የሚቆጣጠረው ነገር የለም! ሩሶ የተባለው ተምኔታዊ ፈላስፋ በከበርቴው መደብ ጠባይ እና ነገረ ሥራ በመማረሩ ሰዎች ለእውነት፣ ለክብር እና ለስልጣን ያላቸውን ጥልቅ ስሜት በሌላ መተካት እንዳለበት አመነ፡፡ እና ወጣቶች በርስ በርስ ጥማት መንደዳቸው አስፈላጊ ነው ሲል ሰበከ፡፡ (በምዕራባውያን ባህል መዋደድ ለጋብቻ መሰረት መሆኑ ይለመድ የያዘው ከ19ኛው ክፍለ ዘመን በኋላ ነው፡፡ ከዚያን ጊዜ አንስቶም የፍቺ ቁጥር ጨመረ እንጂ ሲቀንስ አልታየም፡፡) ሮማንስ  ለዘመኑ ወጣቶች የሚሰጠው ብዙ ጥቅም አለ፡፡
ኢጓችንን ደባብሶ ይንከባከብልናል፡፡ በራሳችን ዙሪያ መተብተባችን ያለቅጥ እየጦዘ ነው የመጣው። ሮማንስ  ይህንን ራስ ወዳድነታችንን ያረካልናል። እንደ ወትሮው ልጅ መውለድ ዋነኛ ዓላማው ተደርጎ መታየቱ፣የቀረውን ወሲብ ልዩ ትርጓሜ የያዘ እንዲመስል ያደርገዋል፡፡ እናም ደግሞ ከመራር የህይወት ጥያቄዎች (ምን እንመን? ምንድን ነን? ወዘተ) ይገላግለናል፡፡ ይሸሽገናል፡፡
ይህ የኑሮ ፈሊጥ አሁን የእኛም ሆኗል፡፡ ችግር መሆን የሚጀምረው ግን ትክክለኛ ዋጋውን ያለአግባብ ለጥጠን የሌለውን ግዝፈት ከሰጠነው ብቻ ነው፡፡

በዓለም ላይ “የመርፊ ህግ” በመባል የሚታወቅ ህግ አለ፡፡ የምንሠራው ሥራ ሁሉ ስህተት ይሆናል ብሎ የማመን አዝማሚያ ነው፡፡ ስለዚህ ጉዳይ የሚተረክ አንድ ተረት አለ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሰው፤ በአንድ በጣም በራበው ጠዋት፤ ቁርስ አስቀርቦ መብላት ጀመረ፡፡ ዳቦውን ሁለት ላይ ከፈለና አንዱን ግማሽ ቅቤ ቀባው፡፡ ጥሩ አድርጐ ግማሹን ክብ ዳር እስከዳር አሳምሮ ነው በቅቤው ያዳረሰው፡፡ ከዚያ ሻዩን ለማወራረጃ ስለሚፈልገው ስኳሩን አስቀድሞ ከቶ ሻዩን ብርጭቆው ውስጥ ቀድቶ እያዘጋጀ ሳለ፤ ሳያስበው ያን የተቀባ ግማሽ ዳቦ ከጠረጴዛው ገፋና ጣለው፡፡
ዳቦው ወለሉ ላይ ወደቀ፡፡
ደንግጦ ወደ ወለሉ ሲያይ በጣም አስገራሚ ነገር ገጠመው፡፡ የዳቦው ያልተቀባው ወገን ወደመሬት፤ የተቀባው ወገን ወደላይ መሆኑን አየ፡፡ አንዳች ተዓምር እንዳየ ሆኖ ተሰማው፡፡ ተደነቀ፡፡
ወደ ጓደኛዬ ሄደና፤
“ዛሬ ጉድ ነው ያየሁት!” አለ፡፡
“ምን አየህ?”
“ብታምኑም ባታምኑም - ተዓምር ነው ያየሁት!”
“እኮ ምን አየህ? ንገረና!?”
“ቁርስ ስበላ ድንገት ግማሹ ቅቤ የቀባሁት ዳቦ መሬት ወደቀ፡፡ የሚገርመው ያልተቀባው ወገን ወደታች የተቀባው ወደላይ ሆኖ ተገኘ!”
“እረ ባክህ? ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል? የተቀባ ዳቦ ሲወድቅኮ፤ ብዙ ጊዜ የተቀባው ወደ መሬት፣ ያልተቀባው ወደላይ ነው የሚሆነው፡፡ አንተ ያጋጠመህ ተዓምር ካልሆነ በስተቀር ወደላይ ሊሆን አይችልም። ምናልባት ለእኛ አልታወቀን ይሆናል እንጂ አንተ ቅዱስ ሳትሆን አትቀርም፡፡ አምላክ ምልክት ሲሰጥህ ነው” አለ
አንደኛው ጓደኛው፡፡
ከዚህ በኋላ በአንድ ጊዜ ወሬው በመንደሩ ተነዛ፡፡ ሁሉ ሰው ጆሮ ደረሰ፡፡
ሁሉ ሰው መጠያየቅ ጀመረ፡፡
“ይሄ እንዴት ሊሆን ቻለ? ማንም ሰው ያልተቀባው ወገን ወደታች ይሆናል ብሎ አይጠረጥርም፡፡ ዳቦው በተሳሳተ ወገንኮ ነው የወደቀው?” ተባለ፡፡
ማንም መልስ ሊሰጥበት ያልቻለ ትልቅ ጥያቄ ሆነ፡፡
በመጨረሻው “ለሰፈሩ ሊቅ ጥያቄውን እናቅርብለትና እሱ ይመልስልን” ተባለ፡፡
ወደመምህሩ ሊቅ ሄደው የሆነውን ተዓምር ነግረው እንዲያብራራላቸው ጠየቁት፡፡
አዋቂው፤ “በዚህ ጉዳይ ላይ፤ ለመፀለይ፣ ሃሳቡን ለማብላላትና መለኮታዊ ምጥቀት ለማግኘት፤ አንድ ማታ ያስፈልገኛል” አለ፡፡
ጊዜው ተሰጠው፡፡
በነጋታው በጉጉት ህዝቡ እየጠበቀው ሳለ መምህሩ መጥቶ፤
“ነገሩ እንኳን በጣም ቀላል ነው፡፡ ያ ዳቦ የወደቀው በትክክል መውደቅ ባለበት በኩል ነው፡፡ ቅቤው የተቀባው ግን በተሳሳተው ወገን ነው!!” አለ፡፡
                                                            *   *   *
እርግጥ በሀገራችን አንፃር ስናየው፤ ዳቦው ከሌለ ግማሹም ሆነ ሙሉው ተቀባ አልተቀባ ማለት አስቂኝ ይሆን ይሆናል፡፡ የተረቱ ምልኪ ግን፤ ስለወደቀውም ዳቦ አሉታዊ አስተሳሰብ ሊኖረን አይገባም ነው፡፡ ከዚያ ቀጥሎ ዳቦው የዳነው በተሳሳተ ወገን ስለተቀባ ነው የሚለው ሌላው አሉታዊ ምላሽ ነው፡፡ ከዚህ ይሰውረን። ህዝቡም መምህሩም አፍራሽ ይሆኑብናልና!
አንዳንዴ አንዳንድ ምናባዊ ፅንሰ-ሀሳብ ምድር ላይ ቢሆን ምናለበት ያሰኛል፡፡ የዳንቴ ፍልስፍና ለዚህ ይበጀናል፡፡
ሰይጣንን ከማግኘታችን በፊት የወንጀለኞች መቀጫ፤ አውቀው ኃጢአት የሰሩ የሚቃጠሉበት፤ ቦታ አንድ ህግ አለው ይባላል፡- የወሸሙና የከጀሉ፤ በዲያብሎስ ይገረፋሉ፡፡ ሸፋጮች አወናባጆች፣ አይነ ምድር ውስጥ ይደፈቃሉ አጨናባሪ አትራፊዎች እግር-ወደላይ-ራስ ወደ ታች ሆነው አዛባ ውስጥ ይዘፈቃሉ። ጠንቋዮች፣ ጠጠር ጣዮች፣ ዛጎል ወርዋሪዎች፤ አንገታቸው ወደ ጀርባ የሚዞርበት ምስል ይኖራቸዋል። አወናባጅ ፖለቲከኞች የአፈር-ውሃ ጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ ይጣላሉ፡፡ አስመሳዮች መሸከም የማይችሉት ካፖርት ይጫንባቸዋል፡፡ ሌቦች በእባብ አለንጋ ይገረፋሉ፡፡ አጭበርባሪ የፖለቲካ አማካሪዎች በእሳት ይዋጣሉ የማይሆን ወሬ የሚነዙ ፍም ውስጥ ይቀበራሉ፣ ይለናል፡፡
ከዚህ ሁሉ ይሰውረን ዘንድ መንገዱን ያብጅልን! ይሄ የገባው እራሱን ይጠብቅ፡፡
የሃገራችን ውሃ፣ የመብራት፣ የስልክ… የባንክ፣፣ የቀረጥ ወዘተ የማይነጣጠሉ ችግሮች፤ የዘንድሮ ጉዴስ እኔም ገረመኝ፡፡
አንዱን ስለው አንዱ አንዱ ባሰብኝ!
የሚለውን የዱሮ የኦርኬስትራ ኢትዮጵያን ዘፈን ያስታውሰናል፡፡ በዚያው ዘመን ስለ ሎተሪ አዟሪ በሚዘፈን ዜማ፤
“እስኪ ተመልከቱት፣ ይሄንን ፈሊጥ
እሱ እድል የሌለው፣ ዕድልን ሲሸጥ!” የሚልም ነበር፡፡ ከሁሉም ይሰውረን፡፡
ዛሬ “የባሰ አታምጣ!” ብሎ መፅናናትም አስቸጋሪ ሆኗል፡፡ እንደዕውነቱ ከሆነ የዕውቀትና የሙያ ክህሎታችን ምን ዓይነት ለውጥ ያመጣል ማለት እንጂ “ፓርቲዬ ከመደበኝ የትም ቦታ እሰራለሁ” ብቻውን መፍትሄ አያመጣም፡፡ ችግሩ የተፈጠረው በፓርቲ ምደባ ምክንያት ከሆነስ? ብሎ መጠየቅም ያባት ነው፡፡ ህዝባችን ፓርቲን እንዲያልም ሳይሆን አገር እንዲያልም ብናስብ መልካም ሳይሆን አይቀርም፡፡
የሀገራችን አካሄድ ዕውን፣ በዳቦ የተሳሳተ ወገን መቀባት? ቅቤውን አፈር አይነካውም በማለት? ዓበው እንደሚሉት ከተምኔታዊ (utopian) ገጠመኝ ይልቅ ሌላውን ግማሽ ምን እናርገው? የትኛው ይበጃል? የሚለውን በቅጡ ማጤን ዛሬም ወሳኝ ነው! በወደቀው ላይ ከመፈላሰፍ እንዴት ቀጣዩን በወጉ እንያዘው? ማለት አንገብጋቢ ጉዳይ ነው፡፡
ከቶውንም በግሎባላይዜሽን (ትርጉሙ እኳኋን በእርግጥ ባልተረጋገጠው ፅንሰ ሀሳብ ተንተርሶ) አገርን ማሰብ የተሳሳተ ድምዳሜ ላይ እንዳያደርሰን ከልብ ማውጠንጠን ይኖርብናል፡፡ ምዕራባውያን አገሮች እስከዛሬ ያልታየ የፋይናንስ ድንገተኛ አደጋ (Financial Calamity) እየገጠማቸው መሆኑን በዋዛ አንየው! ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ እየተንኮታኮተ ያለውን የኢኮኖሚ የበላይነት በተምታታ ብዥታ እንደሚመለከተው መታየት ፀሐይ የሞቀው ሀቅ ነው፡፡ ይሄን የውስጥ ድንግርግር በዓለም ዙሪያ በተለይም በአዳጊ አገሮች ላይ በመጫን የንግድ፣ የሽብርተኝነት፣ “የዲሞክራሲን አስፋፋለሁ” መርህ ምህዋር ለማስቀየር መጣጣራቸውን ከመፍራት ይልቅ ማወቅ፣ እጅ ከመስጠት ይልቅ ሉዓላዊነትን ጠንክሮ ማሰብ፤ ደግ መሆኑን የዘመኑ የፖለቲካ ጠበብት እንደሚመክሩ ልብ እንበል፡፡ ዘይት፣ ነዳጅ፣ ማዕድን… ያላቸው አገሮች የሚያስነሱትን ብጥብጥ ያስታውሷል፡፡ የራሳችንን ህዝብ ኢኮኖሚያዊ አሳር ቸል አንበል፡፡ የራሳችንን ህዝብ ፖለቲካዊ ምሬት የራሱ ጉዳይ አንበል፡፡ የራሳችንን ህዝብ አስተዳደራዊ በደል ለሌላ ለማንም ብለን ሳይሆን ለነገ የራሳችን ሰናይ ማንነት ስንል ከጉዳይ እንፃፈው፡፡ የራሳችንን ህዝብ የሞራልና የስነ-ምግባር ምንነት በትምህርት በንቃት፣ በአስተዳደጋዎ አስምህሮት ስራዬ ብለን እንደግፈው፡፡ እነዚህን ከላይ የጠቀስናቸውን ፍሬ - ጉዳዮች በቅጡ አስበንባቸው ችግሮቻችንን በየደረጃውና በወቅቱ ካልፈታን ለጎረቤት አገሮች እያሳየን ነው የምንለውን የመፍትሄ - አሽነት ሚና የለበለጠ ያስመስልብናል!  ትላንት ሩዋንዳ፣ ሱማሌ፣ ጅቡቲ ወዘተ… በሞፈር - ዘመትነት መሄዳችንን የአንገት - በላይ ያረግብናል፡፡ “የራሷ ሲያርባት የሰው ታማስላለች” እንዳይሆን እንጠንቀቅ፡፡  


“በሁሉም ማዕከላት አገልግሎቱ ያለእንከን እየተሰጠ ነው”

በአዲስ አበባ ተግባራዊ በተደረገው የቅድመ ክፍያ የመብራት አገልግሎት አሰጣጥ ደንበኞች መማረራቸውን እየገለፁ ሲሆን መብራት ሃይል በበኩሉ፤ በሁሉም ማዕከላት አገልግሎቱ ያለእንከን እየተሰጠ ነው ብሏል፡፡
ካዛንቺስ በሚገኘው የቅድመ ክፍያ አገልግሎት ማዕከል፣በክፍያ አሰባሰብ ላይ ቅሬታ ሲያቀርቡ ያገኘናቸው አንዳንድ ተገልጋዮች፤ ክፍያው የሚሰበሰበው በአንድ ሠራተኛ ብቻ በመሆኑ ወረፋ በመጠበቅ የስራ ጊዜያቸውን እያባከኑ እንደሆነ በምሬት ገልፀዋል፡፡ ረጅም ወረፋ ሲጠብቁ ቆይተው  የምሣ ሰአት አሊያም የስራ መውጫ ደርሷል እየተባሉ ወደ ቤታቸው የሚመለሱ በርካታ ደንበኞች እንዳሉ የታዘበ አንድ ወጣት የቅድመ ክፍያ አገልግሎት ደንበኛ፤ እሱም ራሱ በተመሳሳይ ምክንያት ለሶስት ተከታታይ ቀናት ወደ ማዕከሉ መመላለሱን ገልጿል።
ከሃያት አካባቢ የአገልግሎት ካርዳቸውን ለማስሞላት ካዛንቺስ ድረስ መምጣታቸውን የገለፁት አንድ ጎልማሳ በበኩላቸው፤ ድርጀቱ በከተማዋ አንድ ማዕከል ብቻ በመክፈቱ እሳቸውን ጨምሮ በርካታ ተገልጋዮች ለእንግልት መዳረጋቸውን ተናግረዋል። የአገልግሎቱ መጀመር በተለይ የመብራት አጠቃቀምን በዘመናዊ መልኩ ለመቆጣጠር ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው የሚገልፁት ደንበኞች፤ መብራት ሃይል በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች የቅድመ ክፍያ አገልግሎት ማዕከላትን በስፋት በመክፈት፣ አገልግሎቱን በተደራጀ የሰው ሃይል በመስጠት ደንበኞችን ከእንግልትና ከምሬት መገላገል ይችላል  ብለዋል፡፡
የደንበኞችን ቅሬታና በአጠቃላይ አገልግሎቱን በተመለከተ ያነጋገርናቸው የኢትዮጵያ መብራት ሃይል ኮርፖሬሽን የውጭና ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ምስክር ነጋሽ፤አገልግሎቱ ከሁለት አመት በፊት እንደተጀመረና የደንበኞችን ወጪና ጊዜ ለመቆጠብ ታስቦ ተግባራዊ መደረጉን አስታውሰው፤ በከተማዋ አገልግሎቱን የሚሰጡ 29 ማዕከላት እንዳሉ፣ ሁሉም አገልግሎቱን በተቀላጠፈ መልኩ ለ174ሺ35 ደንበኞች ያህል እየሰጡ እንደሆነም ገልፀዋል፡፡ ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በአዳማ ያሉት 3 ማዕከላት እና በቢሾፍቱ ያሉት 2 ማዕከላት፣ በአጠቃላይ ለ26ሺ39 ደንበኞች የተቀላጠፈ አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነም ነው ኃላፊው የተናገሩት፡፡ የቢል ህትመት ወጪን እንዲሁም የቆጣሪ አንባቢንና የገንዘብ ሰብሳቢን ድካም በማስቀረት ረገድ አዎንታዊ ሚና እንዳለው የሚነገርለት የቅድመ ክፍያ ቆጣሪ አገልግሎት ተግባራዊ በተደረጉባቸው ሶስቱ ከተሞች ለ200ሺ104 ደንበኞች አገልግሎት እየተሰጠ እንደሆነም አክለው  ገልፀዋል፡፡
በከተማዋ አንድ የአገልግሎት ማዕከል ብቻ በመኖሩ ተቸግረናል የሚለውን የደንበኞች ቅሬታ አስመልክቶ  የተጠየቁት አቶ ምስክር ሲመልሱ “ካዛንቺስና ሜክሲኮ ያሉት እንደ ዋና ማዕከል እሁድን ጨምሮ አገልግሎት የሚሰጥባቸው እንጂ ብቸኛ ማዕከላት አይደሉም፤ በከተማዋ ያሉት 29 ማዕከላት በቂ ሙያተኛ ተመድቦላቸው አገልግሎቱን በተቀላጠፈ መልኩ እየሰጡ ነው” ብለዋል፡፡ በቅርቡም የሃይል ብክነትን  ለመቆጣጠር የሚያስችሉ ሌሎች ዘመናዊ ቆጣሪዎችን ተግባራዊ ለማድረግ መስሪያ ቤቱ እቅድ መያዙን አቶ ምስክር ጠቁመዋል፡፡  

ጊዜው ቢከፋም ለጋሾች እጃቸው አልታጠፈም
50 በጎ አድራጊዎች 7.7 ቢሊዮን ዶላር ለግሰዋል
ከሴቶች ለጋሾች ይልቅ ወንድ ለጋሾች በርክተዋል

በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2013 ለተለያዩ የበጎ አድራጎት ስራዎች ገንዘባቸውን ከለገሱ አሜሪካውያን መካከል፣ የፌስቡክ መስራቹ  ማርክ ዙከርበርግና ባለቤቱ ፒሪሲላ ቻን ቀዳሚዎቹ መሆናቸውን ክሮኒክል ኦፍ ፌላንትሮፒ የተባለው ተቋም ይፋ አደረገ፡፡
ጥንዶቹ የአመቱን የወደር የለሽ የቸርነት ክብር የተጎናጸፉት፣ ሲሊከን ቫሊ ፋውንዴሽን ለተሰኘው የበጎ አድራጎት ድርጅት 990 ሚሊዮን  ዶላር ዋጋ ያለው የፌስቡክ የአክሲዮን ድርሻ በመለገሳቸው ነው፡፡ ይህ በአመቱ በአሜሪካ ምድር የተሰጠ ከፍተኛ ልግስና፣ ፋውንዴሽኑን ከአገሪቱ ታላላቅ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ተርታ ያሰልፈዋል ተብሏል፡፡
ዙከርበርግና ሚስቱ በአመቱ የአገሪቱ 50 አባ መስጠቶች ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት አሜሪካውያን በእድሜ ለጋዎቹ ሲሆኑ በሰላሳ አመት እድሜ ላይ የሚገኙት ጥንዶቹ፣ ባለፉት ሁለት አመታትም ለዚሁ የበጎ አድራጎት ድርጅት 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ የአክሲዮን ድርሻ በልግስና አበርክተዋል።
ጥንዶቹ የለገሱት ገንዘብ በትምህርትና በጤና ዘርፎች ለሚከናወኑ ስራዎች ይውላል ተብሏል፡፡
ክሮኒክል ኦፍ ፌላንትሮፒ የአመቱ ለጋስ ብሎ በሁለተኛነት ያስቀመጣቸው፣ ቴክሳስ ኢነርጂ የተባለው ኩባንያ የቀድሞ ስራ አስኪያጅ ጆርጅ ሚሼል ናቸው፡፡ ባለፈው ሃምሌ ከዚህ አለም በሞት የተለዩት እኒህ ባለጠጋ፣ቤተሰባቸው ለበጎ አድራጎት ድርጅት እንዲሰጥላቸው አደራ ብለው በሄዱት 750 ሚሊዮን  ዶላር ነው ለዚህ ክብር የበቁት፡፡
ከናይኪ ኩባንያ መስራቾች አንዱ የሆኑት ፊል ናይት እና ባለቤታቸው ፔኔሎፔም፣ ለኦሪገን ሄልዝ ኤንድ ሳይንስ ዩኒቨርሲቲ ፋውንዴሽን የካንሰር ምርምር እንዲውል መዥረጥ አድርገው በሰጡት 500 ሚሊዮን  ዶላር ከአገሪቱ የአመቱ ቀዳሚ ለጋሶች ሶስተኛ ሆነዋል፡፡ የአሜሪካን የወደር የለሽ ቸሮች ዝርዝር በቀዳሚነት ሲመሩ የቆዩት የማይክሮ ሶፍቱ መስራች ቢል ጌትስና ባለቤታቸው ሚሊንዳ ጌትስ፣ በ2013 ክብራቸውን ማስጠበቅ ባይችሉም በአመቱ ከ181 ሚሊዮን  ዶላር በላይ ለግሰዋል ተብሏል፡፡ ጥንዶቹ በ2004 ለበጎ አድራጎት ተግባር ለመስጠት ቃል የገቡትን 3 ነጥብ 3 ቢሊዮን  ዶላር ቀስበቀስ መክፈል መቀጠላቸው ተነግሯል፡፡
በክሮኒክል ኦፍ ፌላንትሮፒ የ2013 ወደር የለሽ ለጋሶች ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት 50 አሜሪካውያን፣ ለተለያዩ የበጎ አድራጎት ስራዎች በድምሩ 7 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ሰጥተዋል - በ2014፡፡
በአመቱ 296 ሚሊዬን ዶላር በመስጠት በለጋሾች ዝርዝር ውስጥ የአምስተኛነትን ደረጃ የያዙት ጆን አርኖልድ እና ባለቤቱ ላውራ፣ ድጋፍ የሚሹ ወገኖቻቸውን ብቻም ሳይሆን መንግስታቸውንም በመርዳት የሚታወቁ ጥንዶች ናቸው፡፡ ባልና ሚስቱ ባለፈው ጥቅምት ወር የአሜሪካ መንግስት መዘጋቱን ተከትሎ በተከሰተ የአቅም ማጣት ችግር ላይ ፈጥነው ደርሰዋል፡፡ መንግስት በወቅቱ ትምህርት ቤቶቻቸው ተዘግተው ቤት ሊውሉ የነበሩ 7ሺህ ያህል አሜሪካውያን ህጻናትን ትምህርት ማስቀጠል የቻለው፣ እነዚህ ጥንዶች ባበደሩት 10 ሚሊዮን  ዶላር ነው፡፡
በአመቱ የለጋሾች ዝርዝር ውስጥ ዙከርበርግን ጨምሮ በቴክኖሎጂው ዘርፍ የተሰማሩ ሌሎች አምስት ታዋቂ ግለሰቦችም ተካተዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል የኢቤይ መስራች ፔሪ ኦሚድያር፣ የጎግል መስራች ሰርጌይ ብሪንና ከማይክሮሶፍት መስራቾች አንዱ የሆኑት ፖል አለንና ሚስቶቻቸው ይጠቀሳሉ።
ወንዶች በሚበዙበት በዚህ ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት ለጋሾች፣ የአገሪቱ ኢኮኖሚ እየተንገራገጨ ባለበት ወቅት ሳይሰስቱ በሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር ለበጎ አድራጎት ስራ መለገሳቸው ያስደንቃቸዋል ተብሏል፡፡
ለጋሾቹ በአመቱ ከሰጡት ገንዘብ አንድ ሚሊዮን ዶላር ያህሉን የወሰዱት የእርዳታ ድርጅቶች፣ ሆስፒታሎችና ኮሌጆች ሲሆኑ፤ የተቀረውም በህክምና ምርምር፣ ሰብአዊ አገልግሎቶች፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በህጻናትና ወጣቶች ወዘተ ዙሪያ ለሚሰሩ ድርጅቶችና ተቋማት እንደሚውል ተነግሯል፡፡


Monday, 10 February 2014 07:47

‘ድፍረት’ ፊልም ተሸለመ

በኢትዮጰያዊው ፊልም ባለሙያ ዘረሰናይ ብርሃኔ ተጽፎ የተዘጋጀው ድፍረት ፊልም፣ በ2014 ሰንዳንስ አለማቀፍ የፊልም ፌስቲቫል በ‘ወርልድ ሲኒማ ድራማቲክ ኦዲየንስ’ ዘርፍ ተሸላሚ ሆነ፡፡
ታዲያስ መጽሄት ከኒዮርክ እንደዘገበው፣ በእውነተኛ ታሪክ ላይ ተመስርቶ የተሰራውና የ99 ደቂቃ ርዝማኔ ያለው የዚህ ፊልም ዳይሬክተር ዘረሰናይ ብርሃኔና ፕሮዲዩሰሯ ምህረት ማንደፍሮ ባለፈው ቅዳሜ በተከናወነው የፌስቲቫሉ የመዝጊያ ስነስርዓት ላይ ተገኝተው ሽልማቱን ተቀብለዋል፡፡
በሰንዳንስ አለማቀፍ የፊልም ፌስቲቫል ላይ በመካፈል የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ፊልም የሆነውና በተለያዩ የአሜሪካ ሲኒማ ቤቶች ተዘዋውሮ ሲታይ የሰነበተው ድፍረት፣ በተመልካቾች ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነት በማግኘቱ ነው በዘርፉ ተሸላሚ ለመሆን የበቃው፡፡
ከፊልሙ ኤክስኪዩቲቭ ፕሮዲዩሰሮች አንዷ የሆነችው ታዋቂዋ የሆሊውድ የፊልም ተዋናይት አንጀሊና ጆሊ፣ ከሳምንታት በፊት ድፍረት በኢትዮጵያ የፊልምና የኪነጥበብ ዘርፍ ላይ የራሱን አሻራ ያሳረፈ ስራ ነው ስትል አድናቆቷን መግለጧ ይታወሳል፡፡