Administrator

Administrator

የኢትዮጵያን ፊልም 50ኛ ዓመት በዓል ምክንያት በማድረግ በኢዮሃ ሲኒማና በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የተዘጋጀው የፊልም ስልጠና ረቡዕ ተጠናቀቀ፡፡ ስልጠናው የተሰጠው ወደ 60 ለሚጠጉ የፊልም ባለሙያዎችና ጋዜጠኞች ሲሆን በፊልም መመሪያና ስነ ምግባር፤ በፊልም ዝግጅት፣ በፊልም ስክሪፕት አፃፃፍና በፊልም ትወና ላይ ያተኮረ እንደነበር በማጠናቀቂያው ላይ ተገልጿል፡፡
ለአራት ቀናት በቆየው በዚህ ስልጠና ላይ ዮናስ ብርሃነ መዋ፣ ብርሃኑ ሽብሩ፣ ሄኖክ አየለ እና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የመጡ የስነ ልቦና ባለሙያዎች በአሰልጣኝነት መሳተፋቸውም ታውቋል፡፡

የገጣሚ ሶልያና አብዲ “ሼም ይናፍቅሃል” የተሰኘ የግጥም መድበልና ሲዲ ዛሬ ከ3ሰዓት ጀምሮ በጣይቱ ሆቴል ጃዝ አምባ አዳራሽ ይመረቃል፡፡
በመድበሉ ውስጥ የተካተቱት ግጥሞች በሴቶች ጥቃት፣ በህገወጥ ጉዞ አስከፊነት፣ በወጣትነትና በፍቅር ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ሲሆን የግጥሙ ሲዲ ደግሞ በኢትዮጵያ ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድኖች (ዋሊያዎቹና ሉሲዎች) ጀግንነት ላይ የሚያተኩር ነው ተብሏል፡፡ 94 ያህል ግጥሞችን የያዘው መድበሉ በ30 ብር ለሽያጭ ቀርቧል፡፡

“በሰው ለሰው” ድራማ የአዱኛን ገፀ - ባህሪ ወክሎ በመጫወት እና በበርካታ ስራዎቹ አድናቆትን ያተረፈው አርቲስት ይገረም ደጀኔ፤ “ቆምኩኝ ለምስጋና” የተሰኘ የምስጋና የመዝሙር ሲዲ ያወጣ ሲሆን፤ ሰኞ ገበያ ላይ እንደሚውል ተገለፀ፡፡ አርቲስቱ ለመዝሙሩ ከተከፈለው 40ሺህ ብር ላይ 20ሺህ ብሩን ለሜቄዶንያ አረጋዊያን መርጃ በእርዳታ ሲሰጥ ቀሪውን እያገለገለ ላደገበት ሰንበት ት/ቤት መለገሱን ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡
በመዝሙር ሲዲው ውስጥ 11 መዝሙሮች የተካተቱ ሲሆን፤ አምስቱን ለብቻው ሁለቱን ከዘማሪ ዲያቆን ፍቃዱ አዱኛ ጋር በጋራ መስራቱንና ቀሪዎቹ አራት መዝሙሮች በዘማሪ አዱኛ እንደተሰሩ ይገረም ገልጿል፡፡
“የዘመርኩት ማመስገን ስለምወድ” ነው ያለው አርቲስቱ፤ ሌሎችም የተሰጣቸውን ፀጋ ተጠቅመው የድርሻቸውን እንዲያበረክቱ ለማነቃቃት በስራው ላይ መሳተፉን ተናግሯል፡፡  
“ወደፊት ከእኔ ጋር በበጎ ስራዎች ላይ ለመሰማራት የሚፈለግ ሰው ካለ አብሬ ለመስራት ዝግጁ ነኝ” ብሏል - አርቲስት ይገረም ደጀኔ፡፡ አርቲስቱ ከዚህ ቀደም ለአቡነ መልከፀዴቅ ገዳም ለገቢ ማሰባሰቢያ የሚውል የመዝሙር ቪሲዲ ከሙያ አጋሮቹ ጋር መስራቱ ይታወሳል፡፡  

Saturday, 21 June 2014 14:58

የፍቅር ጥግ

(ስለጋብቻና ፍቺ)
አባት ለልጆቹ ሊያደርግ የሚችለው ትልቁ ነገር፣ እናታቸውን ማፍቀር ነው፡፡
ቴዎዶር ኼስበርግ
ሰዎች በትዳር የሚዘልቁት፣ ስለፈለጉ ነው እንጂ በሮች ስለተቆለፉባቸው አይደለም፡፡
ፖል ኒውማን
ፍቺ አካልን እንደመቆረጥ ነው፡፡ አንዳንዴ አስፈላጊ ሊሆን ይችላል፡፡ ከተቻለ ግን ባይሆን ይመረጣል፡፡ ምክንያቱም ዘላቂ አካል ጉዳተኝነትን ያስከትላል፡፡
ቢል ዶኸርቲ
ፍቺ ለልጆች እንዲሁም ለሌሎች ህይወት ያላቸው ነገሮች ሁሉ ጤናማ አይደለም፡፡
ዲያኔ ሶሊ
የተሻለ ነገር እስኪመጣ ድረስ ጋብቻን እንደተቋምከእነችግሮቹ  እደግፈዋለሁ፡፡
ዴቪድ ብላንከንሆርን
(የአሜሪካ እሴቶች ተቋም)
እያንዳንዱ ፍቺ የትንሽዬ ስልጣኔ ሞት ነው፡፡
ፓት ኮንሮይ
የህብረተሰብ የመጀመሪያው ማሰሪያ ጋብቻ ነው፡፡
ሲሴሮ
በማህበራዊ ጥናት አንድ አባባል አለ፡- “እናት በመላው ህይወትህ ሁሉ እናት ናት፡፡ አባት ግን አባት የሚሆነው ሚስት ሲኖረው ብቻ ነው”
ሊህ ዋርድ ሲርስ
(የጆርጅያ ጠ/ፍርድ ቤት ዋና ዳኛ)
ድሮ ወላጆች ብዙ ልጆች ነበራቸው፡፡ አሁን ልጆች ብዙ ወላጆች አሏቸው፡፡
ጉሮ ሃንሰን ሄልስኮግ
አንዳንዴ ባልና ሚስት መጣላታቸው አስፈላጊ ነው፡፡ የበለጠ እርስ በርስ እንዲተዋወቁ ያደርጋቸዋል፡፡
ገተ
ትክክለኛውን ፍቅር ከመፍጠር ይልቅ ትክክለኛውን አፍቃሪ በመፈለግ ጊዜያችንን እናጠፋለን፡፡
ቶም ሮቢንስ

    ያልተቋረጠ የሽብር ጥቃት ከራሳቸው ላይ አልወርድ ብሎ እጅግ ግራ የተጋቡ ሁለት የአፍሪካ ሀገራት አሉ ከተባለ ከኬንያና ናይጀሪያ ውጭ ሌላ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ያላባራ የሽብር ጥቃት ሰለባ የሆነችው ኬንያ፤ ባለፈው እሁድና ሰኞ በተከታታይ የወረደባት የሽብር መአት የጦርነት ቀጠና አስመስሏታል፡፡
የአልሸባብ አባላት ሳይሆኑ እንዳልቀረ በሰፊው የተጠረጠሩ ሽብርተኛ ታጣቂዎች ባለፈው እሁድ የሱማሊያ አዋሳኝ የኬንያ ግዛት ከሆነችው የላሙ ደሴት አቅራቢያ በምትገኘው የምፒኪቶኒ ከተማ ላይ ድንገት አደጋ ጥለው አርባ ስምንት ኬንያውያንን ገድለዋል፡፡ እሁድ እለት ማታ ላይ ከተፈፀመው ከዚህ ጥቃት ያመለጡ የአይን እማኞች፤ ሽብርተኛ ታጣቂዎቹ ቤት ለቤት እየዞሩ የቤቱ አባወራ ሙስሊም መሆኑንና የሶማሊያ ቋንቋ ተናጋሪ መሆን አለመሆኑን ያጣሩ እንደነበረ ጠቁመው በተለይ ሆቴል ውስጥ ካገኟቸው ወንዶች ውስጥ ሙስሊም ያልሆኑትን ብቻ ለይተው በማውጣት፣ሚስቶቻቸው ፊት በጥይት ደብድበው እንደገደሏቸው አስረድተዋል፡፡
የምፒኪቶኒ ከተማ ነዋሪም ሆነ መላ ኬንያውያን የዚህ ጭካኔ የተሞላበት ጭፍጨፋ ድንጋጤ ገና በወጉ እንኳ ሳይለቃቸው ሰኞ እለት ከከተማዋ በቅርብ ርቀት ላይ በምትገኘው የማጂምቤኒ ከተማ እነዚሁ ሽብርተኛ ታጣቂዎች ባደረሱት ጥቃት የአስር ኬንያውያንን ህይወት ቀጥፈዋል፡፡
ድፍን አለሙም ሆነ መላ ኬንያውያን እንደጠረጠሩት፣ የሶማልያው ሽብርተኛ ቡድን አልሸባብ ኬንያ በሶማልያ ላይ ለፈፀመችው ወታደራዊ ጣልቃ ገብነትና በሙስሊሞች ላይ ላደረሰችው በደል ሁለቱንም ጥቃቶች በማድረስ የእጇን እንደሰጣት በመግለፅ ሃላፊነቱን ወስዷል፡፡
የኬንያው ፕሬዚደንት ኡሁሩ ኬንያታ ግን አልሸባብ የሰጠው መግለጫ ፈጽሞ ሊዋጥላቸው አልቻለም፡፡ በሽብር ጥቃቱ ከተገደሉት አብዛኞቹ የእሳቸው ብሔር አባላት የሆኑ ኪኩዩዎች መሆናቸውን መሰረት በማድረግ ሃላፊነቱን ከወሰደው አልሸባብ ይልቅ በዘረኝነት የታወሩ ባሏቸው ኬንያውያን ፖለቲከኞች ላይ ጣታቸውን በመቀሰር ተጠያቂ አድርገዋቸዋል፡፡ የፕሬዚዳንቱን ውንጀላ ተከትሎም የኬንያ ፖሊስ በሽብር ጥቃቱ እጃቸውን አስገብተዋል ያላቸውን በርካታ ኬንያውያንን ከያሉበት ለቃቅሞ ወህኒ ከርችሟቸዋል፡፡

Saturday, 21 June 2014 14:51

የብራ መብረቅ በናይጀሪያ

ቦኮ ሃራም ባጠመደው ቦንብ 21 ወጣቶች ሲሞቱ፤ 27ቱ ቆስለዋል

ናይጀሪያውያን የእኛን ቡድን በደርሶ መልስ ጨዋታ አሸንፎ ለ20ኛው የአለም ዋንጨ ባለፈው የአፍሪካ ሻምፒዮን ብሔራዊ ቡድናቸው በእጅጉ ደስተኞች በመሆናቸው የብራዚሉ የአለም ዋንጫ እስኪጀመር በጣም ቸኩለው ነበር፡፡
አብዛኞቹ ናይጀሪያውንም ቡድናቐው ተካፋይ የሆነበት የብራዚሉ የአለም ዋንጫ,ኧ እስከ ፍፃሜው ድረስ (ያለው የአንድ ወር ጊዜ በየአደባባዩ ተሰብስበው የሚዝናኑበት አሪፍ የፌሽታ ጊዜ እንደሚሆንላቸው ሙሉ እምነት ነበራቸው፡፡
የሰሜን ምስራቅ ግዛቶች ውስጥ በሚኖሩት ናይጀሪያውያን ዘንድ ግን ይህን መሰሉ ስሜት ብዙም አልቆየም፡፡ ፅንፈኛ እስላማዊ አሸባሪ ቡድን የሆነው ቦኮ ሃራም በዋናነት ይንቀሳቀስበታል በሚባለው በዚህ አካባቢ የዓለም ዋንጫን መመልከት የታገደው ከጨዋታው ቀደም ብሎ ነው፡፡ ቦኮ ሀራም በዮቤና በአዳማዊ ግዛቶች “አዳሜ ሁሉ የአለም ዋንጫ ውድድርን በአደባባይ ተሰብስቤ እየጨፈርኩ በቴሌቪዥን እከታተላለሁ ስትል ውርድ ከራሴ!” በማለት በበራሪ ወረቀት የሰጠው ማስጠንቀቂያ ብዙዎችን ከፍ ያለ ስጋት ውስጥ መጣሉ አልቀረም፡፡
በእግር ኳስ ፍቅር ልባቸው ክፉኛ የነደደ በርካታ ናይጀሪያውያን ግን ስጋታቸውን እንደያዙም ቢሆን ሰብሰብ ብለው እየጨፈሩ ውድድሩን ከመመልከት ወደኋላ አላሉም፡፡ የዮቤ ግዛት የዳማቱሩ ከተማ ነዋሪ የሆኑ እግር ኳስ አፍቃሪ ናይጀሪያውያን ባለፈው ማክሰኞ ያደረጉትም ይህንኑ ነበር፡፡
ለቦኮ ሀራም ግን የእነዚህ ናይጀሪያውያን ድርጊት ማስጠንቀቂያን ቸል የማለት ተራ ስህተት ሳይሆን በሞት የሚያስቀጣ ከፍተኛ ወንጀል ነበር፡፡ እናም የቅጣት ቦምብ ተጠመደላቸው፡፡ ባለፈው ሳምንት ብራዚልና ሜክሲኮ እየተጫወቱ ሳለ ማንም ባላሰበውና ባልጠበቀው ሁኔታ የተጠመደው ቦምብ ድንገት ፈነዳ፡፡ አገር ሰላም ብለው ጨዋታውን በመከተተል ላይ ከነበሩት ወጣቶች መካከል ሃያ አንዱ ወዲያውኑ ሲሞቱ፤ ሃያ ሰባቱ የሚሆኑት ደግሞ ቀላልና ከባድ ጉዳት ደረሰባቸው፡፡ ብዙዎችን ድንጋጤ ውስጥ የከተተ የብራ መብረቅ!

Saturday, 21 June 2014 14:42

ጎል ለምን በዛ?

20ኛው ዓለም ዋንጫ በጎል ብዛት የተንበሻበሸ ሆኗል፡፡ ትናንት ከምድብ 4 የሁለተኛ ዙር ጨዋታዎች በፊት በተደረጉት 23 ግጥሚያዎች ላይ 66 ጎሎች ከመረብ አርፈዋል፡፡ በአማካይ በአንድ ጨዋታ 2.87 ጎሎች ማለት ነው፡፡ ዓለም ዋንጫ በ32 ቡድኖች በሚደረጉ 64 ጨዋታዎች መካሄድ ከጀመረ ወዲህ በየውድድሩ አንድ ጨዋታ አማካይ የጎል ብዛት 2.5 ነው፡፡  በ2002 እኤአ ላይ 2.5፤ በ2006 እኤአ 2.3 እንዲሁም በ2010 እኤአ 2.3 ጎሎች በአንድ የዓለም ዋንጫ ጨዋታ በአማካይ ሲመዘገብ ነበር፡፡  ለጎሎች መብዛት የተለያዩ ምክንያቶችም እየቀረቡ ናቸው፡፡ ብራዙካ የተባለችው ኳስ አመቺነት፤ የቡድኖች አጨዋወት በአመዛኙ በማጥቃት ላይ የተመሰረተ መሆኑ፤ በርካታ ምርጥ የአጥቂ መስመር ተሰላፊዎች በየብሄራዊ ቡድኖቻቸው አስገራሚ ብቃት ማሳየታቸውና የብራዚል ስታድዬሞች ማራኪ ድባብ ይጠቀሳሉ፡፡ ብራዚላዊ ዚኮ  በዓለም ዋንጫው ጎሎች የበዙት የየብሄራዊ ቡድን አሰልጣኞች ግብ እንዳይቆጠርባቸው ከመከላከል ይልቅ አስቀድመው በማግባት ለማሸነፍ በተከተሉት ታክቲክ መሆኑን አስተያየት ሰጥቷል፡፡ ብዙዎቹ አሰልጣኞች የቡድናቸውን አጨዋወት በማጥቃት ላይ እንዲመሰረት ማድረጋቸውን ታዝቢያለሁ ብሏል ዚኮ፡፡ የጎሎች መብዛት የዓለም ዋንጫውን የፉክክር ድባብ አድምቆታል፡፡ በበየጨዋታው አጓጊ ድራማዎችና ልብ ሰቃይ ትእይንቶች እየተፈጠሩ ናቸው፡፡
በኮከብ ግብ አግቢነቱ ፉክክር ሶስት ተጨዋቾች በሶስት ጎሎች ተያይዘዋል፡፡ የጀርመኑ ቶማስ ሙለር እና ሆላንዳውያኑ ሮበን ቫን ፕርሲ እና አርያን ሩበን ናቸው፡፡ እያንዳንዳቸው ሁለት ጎሎች ያስመዘገቡት 7 ተጨዋቾች ደግሞ   የብራዚሎ ኔይማር፣ የአውስትራሊያው ቲም ካሂል፣ የኮሎምቢያው ጀምስ ሮድሪጌዝ፤ የክሮሽያው ማርዮ ማንዱዚክ፣ የፈረንሳዩ ካሬም ቤንዜማ፤ የአይቬሪኮስቱ ጀርቪንሆ እና የኡራጋዩ ሊውስ ሱዋሬዝ ናቸው፡፡



የፊፋ  ሽልማትና ቦነሶች
ለሽልማትና ለክለቦች ክፍያ በፊፋ የተዘጋጀው 576 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡ በ19ኛው ዓለም ዋንጫ ከነበረው በ37% ጨምሯል፡፡  ተጨዋቾቻቸውን ለሚያሳትፉ ክለቦች  ፊፋ 70 ሚሊዮን ዶላር እንደየደረጃው የሚከፍል ሲሆን ይኸም ከ4 ዓመት በፊት ከነበረው በ75 % ጭማሪ ታይቶበታል፡፡ ፊፋ በዓለም ዋንጫው ለሚሳተፉ ብሔራዊ ቡድኖች ለዝግጅት የሚሆን አስቀድሞ  1.5 ሚሊዮን ዶላር  ከመስጠቱም በላይ በውድድሩ ተሳታፊነት ብቻ ለ32ቱ አገራት ለእያንዳንዳቸው 8 ሚሊዮን ዶላር ይከፍላቸዋል፡፡ በገንዘብ ሽልማቱ ዝርዝር አከፋፈል መሰረት ዋንጫውን የሚያሸንፍ 35 ሚሊዮን ዶላር ሲከፈለው  ፤ ለሁለተኛ 25ሚ ዶላር፤ ለሦስተኛ ደረጃ 22 ሚሊዮን ዶላር ለ4ኛ ደረጃቨ 20 ሚሊዮን ዶላር  ይበረከታል፡፡ በሩብ ፍፃሜ የሚሰናበቱ 4 ቡድኖች እያንዳንዳቸው 14 ሚ. ዶላር ፤በጥሎ ማለፍ የሚሰናበቱ 8 ቡድኖች ለእያንዳንዳቸው 9 ሚ ዶላር እንዲሁም ከምድብ ለሚሰናበቱ 16 ቡድኖች 8ሚ.ዶላር ይከፋፈላል፡፡
የማበረታቻ ቦነስ እና ሌሎች ክፍያዎችን ለመስጠት ላለፉት 6 ወራት በየአገሩ ቃል ሲገባ ነበር፡፡  የስፔን ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች  የሻምፒዮናነት ክብራቸውን ካስጠበቁ በነፍስ ወከፍ 979ሺ ዶላር እንደሚታሰብላቸው ቃል መገባቱ  ከፍተኛው ቦነስ ነበረ፡፡ በትልልቅ ውድድሮች ላይ ከፍተኛ ግምት እየተሰጠው ብዙ  ለማይቀናው የእንግሊዝ ብሔራዊ ቡድንም  ለዋንጫ ድል የቀረበው ቦነስ ለእያንዳንዳቸው 587ሺ ዶላር ነው፡፡
 በአዘጋጇ ብራዚል  448ሺ ዶላር ቦነስ እንደምትሰጥ ሲገለፅ ለፈረንሳይ ቡድንም በተመሳሳይ መጠን  ቀርቧል፡፡ በጀርመን  408ሺ ዶላር ፤  በአሜሪካ 405ሺ ዶላር  እንዲሁም በሆላንድ ደግሞ 371ሺ ዶላር ቦነስ ለእያንዳንዱ ተጨዋች በነፍስ ወከፍ  ለመስጠት ተዘጋጅቷል፡፡
በማበረታቻ የቦነስ ክፍያዎች ዙሪያ በተለይ ብሔራዊ ቡድኖች እና ፌደሬሽኖቻቸው ከፍተኛ ውዝግብ መግባታቸው የተለመደው በአፍሪካ ነው፡፡ የካሜሮን ብሔራዊ ቡድን ተጨዋቾች በፌደሬሽን በኩል ስለሚሰጣቸው ክፍያ ውዝግብ ገብተው የምንፈልገው ካልተሟላ ልምምድ እናቆማለን ብለው መነጋገርያ ሆነዋል፡፡ በመጨረሻም የካሜሮን እግር ኳስ ፌደሬሽን ለእያንዳንዱ ተጨዋች በዓለም ዋንጫው አጠቃላይ ተሳትፎ 91.5ሺ ዶላር በመመደብ ውዝግቡን ሲያበርድ የተጨዋቾቹ ፍላጎት እስከ 160ሺ ዶላር ነበር፡፡  የጋና ብሔራዊ ቡድን ተጨዋቾች በበኩላቸው በየጨዋታው በሚያስመዘግቡት ድል የሚሰጣቸው የቦነስ ክፍያ 30% አስቀድሞ እንዲከፈላቸው ጠይቀዋል፡፡

ሲመረጡ “ልከኛ” የነበሩ የፓርላማ አባላት “ዙጦ” ሆነዋል

      የደቡብ አፍሪካ መንግስት ለበርካታ ዓመታት ኤችአይቪ/ኤድስን ለመቆጣጠር ከፍተኛ ትግል ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ የጤና ባለሙያዎች እንደሚሉት፤ አሁን ትኩረቱን ከልክ በላይ ውፍረት ላይ ማድረግ አለበት፡፡ መቀመጫውን ለንደን ባደረገው “Lancet” የተሰኘ የህክምና ጆርናል ላይ የታተመ ዓለም አቀፍ ጥናት እንዳመለከተው፤ ከደቡብ አፍሪካ አዋቂ ሴቶች ውስጥ 70 በመቶ ያህሉና 40 በመቶው ወንዶች ከልክ በላይ ወፍራሞች ናቸው፡፡ ልጆቹም ቢሆኑ ከውፍረት አላመለጡም ይለናል ጥናቱ፡፡ ሩብ ያህሉ ልጃገረዶችና 20 በመቶ የሚሆኑ ወንድ ልጆች ሲበዛ ወፍራም ናቸው፡፡ በዚህም የተነሳ ከስኳር በሽታ እስከ ልብ ህመም ድረስ ላሉ ደዌዎች የመጠቃት ዕድላቸው ከፍተኛ ነው - ዘ ኢኮኖሚስት እንደዘገበው፡፡
በደቡብ አፍሪካ ብቻ ሳይሆን በቀሩት የአፍሪካና ሌሎች ድሃ አገራትም በቀጣዮቹ ሁለት አስርት ዓመታት ከልክ በላይ የሆነ ውፍረት በከፍተኛ መጠን እንደሚጨምር የጠቆመው ጥናቱ፤ ከመጠን ያለፈ ውፍረት ከከተሞች መስፋፋትና ከኢኮኖሚ ዕድገት ጋር ተያይዞ የሚከሰት እንደሆነ አመልክቷል። ህፃናት በምግብ እጥረት በከፍተኛ ደረጃ በሚቀጭባቸው አካባቢዎች የአዋቂዎች ከልክ በላይ ውፍረት ይበልጥ እየጨመረ መምጣቱ አያዎ (Paradox) ነው ብለዋል-ተመራማሪዎች፡፡
ከልክ በላይ ውፍረት ለተለያዩ በሽታዎች የሚያጋልጥ ቢሆንም አብዛኞቹ ደቡብ አፍሪካውያን ግን በውፍረታቸው ደስተኞች ናቸው፡፡ የኑሮ ዘይቤያቸውንና የአመጋገብ ልማዳቸውንም የመቀየር ፍላጎት የላቸውም፡፡ ቃለ-መጠይቅ ከተደረገላቸው 25ሺ500 ደቡብ አፍሪካውያን መካከል 88 በመቶ የሚሆኑት አሪፍ ነው ብለው የሚያምኑት የሰውነት አቋም ወፍራምነትን እንደሆነ ጥናቱ ይጠቁማል፡፡
የጤና ሚኒስትሩ አሮን ሞትሶአሌዲ ግን በዚህ አይስማሙም፡፡ የህክምና ዶክተር የሆኑት ሚኒስትሩ፤ ጠዋት የእግር ጉዞ በማድረግና ጤናማ የአመጋገብ ልማድን በመተግበር  መሸንቀጥ እንደሚገባ አርአያ በመሆን እያሳዩ ይገኛሉ፡፡ የሥራ ባልደረቦቻቸው የእሳቸውን ምሳሌነት እንዲከተሉ ያደረጉት ጥረት ግን አልተሳካም፡፡
በያዝነው ወር መጀመርያ ላይ የደቡብ አፍሪካ የፓርላማ አባላት ካፊቴሪያቸው  ከልክ በላይ ለሆነ ውፍረት የሚዳርጉ ምግቦችን ያቀርባል ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡ አባላት ሲመረጡ “ጥሩና ልከኛ” ነበሩ ያለችው የአፍሪካ ብሄራዊ ኮንግረስ የፓርላማ አባል ሼይላ ሲትሆል፤ “አሁን ግን ሁሉም ዙጦ ሆነዋል” ብላለች - ዘ ኢኮኖሚስት እንደዘገበው።
በነገራችሁ ላይ ኢትዮጵያን በተመለከተ የወጣ ጥናት እንደሚጠቁመው፤ ለጊዜውም ቢሆን ከልክ በላይ ውፍረት እኛን አያሰጋንም፡፡ ሌላ የሚያሰጋን ነገር ግን አልጠፋም፡፡ ውፍረቱ ኢትዮጵያ ውስጥ የሌለው አመጋገባችን ላይ የተለየ ጥንቃቄ አድርገን አይደለም፡፡ በከተማ መስፋፋትና በኢኮኖሚ ዕድገት ገና በመሆናችን ነው፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የእንግሊዙ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ባወጣው ሪፖርት፤ ኢትዮጵያ በድህነት ከዓለም በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ይፋ አድርጓል - ከኒጀር ቀጥሎ ማለት ነው፡፡ ጐበዝ ድህነትን ለማጥፋት ብዙ ትጋትና ረዥም ጉዞ ይጠብቀናል፡፡ ግን የማይቻል ነገር የለም!!       


የምግብ ጭማሪ ምንድነው?
የምግብ ጭማሪ ማለት እንደ ምግብ አካል የሚቆጠር ሲሆን ምግብን ለማጣፈጥ፣ ለማቅለም፣ ሳይበላሽ ለማቆየት ወይም ለማሳመር የሚረዳ በምግብ ላይ የሚጨመር ማንኛውም ንጥረ ነገር ነው፡፡
የምግብ ጭማሪዎች በምግብ ውስጥ ለምን ይጨመራሉ?
የምግብ ጭማሪዎች የተለያዩ ጥቅሞች ያሉት ሲሆን ከዚህ በታች የተዘረዘሩት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
የምግብን ደህንነትን ለመጠበቅ - የተለያዩ የምግብ ጭማሪዎች ምግብን ለብክለት የሚያጋልጡ እንደ ሻጋታ፣ የተለያዩ ፈንገሶችና ባክቴሪያዎች እንዳይራቡና እንዳያድጉ ምቹ ያልሆነ ሁኔታን በመፍጠር ምግቡ ለረጅም ጊዜ ሳይበላሽ አገልግሎት ላይ እንዲውል ለማድረግ ጥቅም ላይ ይውላሉ፡፡
ተፈጥሯዊ የምግብ ንጥረ ነገርን ማሻሻል - የተለያዩ የምግብ ንጥረ ነገሮች እንደ ቫይታሚን፣ መዓድናት፣ ፋይበሮችና ሌሎች ለሰውነታችን አስፈላጊ የሆኑ ንጥረ ምግቦችን በተለያዩ የምግብ ጭማሪዎች መልክ በማዘጋጀት፣ በተፈጥሮ ምግቡ ውስጥ ያልነበረውን ወይም በተፈጥሮ ምግቡ ውስጥ የሚገኝ ቢሆንም በተለያዩ የምግብ ዝግጅቶች ወቅት የሚወገዱትን የምግብ ንጥረ ነገሮችን በመተካት፣ የምግቡን የንጥረ ነገር ይዘት በማሻሻል፣ በነዚህ ንጥረ ምግቦች እጥረት ሊከሰቱ የሚችሉ የህብረተሰብ የጤና ችግሮችን ለመከላከል ይረዳል፡፡
የምግብ ቃናን፤ ጣዕምን፣ ልስላሴንና እይታን ያሻሽላሉ - የተለያዩ ምግብ ጭማሪዎች በምግብ ውስጥ የሚጨመሩት የምግቡን ጣዕም ለመጨመር፣ ቃናውን ለማሻሻል፣ ቀለሙን ከተፈጥሯዊ ቀለሙ በማሻሻል ሳቢ ወደ ሆነ ቀለም ለመለወጥ እንዲሁም ልስላሴን በመጨመር የምግቡን ተፈጥሯዊ ይዘት በማሻሻል የምግቡን ተፈላጊ ለማድረግ ነው፡፡
የምግብ ጭማሪ ጥራትና ደህንነት ቁጥጥር
የምግብ ጭማሪን ምግብ ውስጥ በመጨመር የምግብን ተፈጥሯዊ ባህሪ በመለወጥ፣ የምግቡን ተወዳጅነት ለማሳደግ የሚደረገው ተግባር ከአባቶቻችን ጋር የቆየ ባህል ነው፡፡ ለምሳሌ ጨውን ፈጭቶ እንደ ሥጋና ዓሣ በመሳሰሉት በከፍተኛ ሁኔታ የሚበላሹ የምግብ አይነቶች ውስጥ በመጨመር፣ የምግቦቹን የመጠቀሚያ ጊዜ ለማስረዘም ይጠቀሙበት ነበር፡፡ የተለያዩ ቅመማ ቅመሞችን በመጠቀምም የምግቦቹን ጣዕምና ቃና የተሻለ ያደርጉ  ነበር፡፡
በአሁኑ ጊዜም ህብረተሰቡ ጣዕሙና ቃናው የተሻለ፣ በተለያዩ የምግብ ንጥረ ነገሮች የበለፀገ፣ ደህንቱ ተጠብቆ ለረዥም ጊዜ ሊጠቀምበት የሚችልና እይታው ማራኪ የሆነ ምግብ ለማግኘት ፍላጐቱ ከፍተኛ በመሆኑ፣ የተለያዩ የምግብ አምራች ድርጅቶች የተለያዩ የምግብ ጭማሪዎችን መጠቀም፣ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መጥቷል፡፡
የምግብ ጭማሪ ጥራትና ደህንነት አስመልክቶ፣ ከፍተኛ ሳይንሳዊ ምርምሮች እየተደረጉም ይገኛሉ፣ በሀገራችንም የነዚህን የምግብ ጭማሪዎች ጥራታቸውንና ደህንነታቸውን ጠብቀው ለህብረተሰቡ እንዲደርሱ የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድኃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደር እና ቁጥጥር ባለስልጣን፣ የተለያዩ የጥራትና ደህንነት ማረጋገጫ ሥራዎችን እያከናወነ ነው፡፡ ከነዚህም መካከል በሀገር ውስጥ እንዲሁም ውጭ አገር ተመርተው ወደ ሀገራችን በመግባት ለህብረተሰቡ እየቀረቡ የሚገኙትን የምግብ ጭማሪዎች ጥራትና ደህንነት ለማረጋገጥ የተለያዩ የቁጥጥር ስራዎችን ያከናውናል፡፡
ህብረተሰቡም የቁጥጥሩ ባለቤት በመሆን፣ የራሱን ጤና ራሱ ይጠብቅ ዘንድ፣ የምግብ ጭማሪዎች ጥራታቸውንና ደህንነታቸውን የጠበቁ እንዲሆኑ ለማረጋገጥ የሚከተሉትን ነጥቦች ማጤን ይጠበቅበታል፡፡
የምግቡን ጭማሪ ይዘትና ባህሪ በተቻለ መጠን ማወቅ፣
ሊያስከትል የሚችለውን የአጭርና የረዥም ጊዜ የጤና ችግር መገንዘብ፣
የምግብ ጭማሪው ማሸጊያ ላይ የተለጠፈውን ገላጭ ጽሑፍ በትኩረት መመልከትና ቢያንስ የሚከተሉትን መረጃዎች ያካተተ መሆኑን ማረጋገጥ:-
የምግብ ጭማሪው የንግድ ስም፣
የምግብ ጭማሪው አምራች ድርጅት፣ ስምና ሙሉ አድራሻ፣
የምግብ ጭማሪው በሌላ ምግብ ላይ በሚጨመርበት ጊዜ በምን ያህል መጠን መሆን እንዳለበትና ምን አይነት የባህሪ ለውጥ በምግቡ ላይ እንደሚያመጣ የሚገልፅ ጽሑፍ መኖሩን ማየት፣
በማሸጊያው ላይ በግልፅ “የምግብ ጭማሪ” የሚል ጽሑፍ መፈለግ፣
ምግቡ የተመረተበትና የመጠቀሚያ ጊዜው የሚያበቃበት ቀን፣
የምርት መለያ ቁጥር፣
የምግብ ጭማሪው አግባባዊ የአጠቃቀም፣ የአያያዝና የጥንቃቄ ሁኔታ የሚጠቁም ጽሑፍ መታተሙን ምግቡን ከመግዛቱና ከመጠቀሙ በፊት በጥሞና ተመልክቶ ማረጋገጥ ይኖርበታል፡፡
ምንጭ፡ (“የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና ጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን” የተገኘ)   

             በአርባ ምንጭ የአዞ እርባታ ጣቢያ ለጉብኝት ታድመናል፡፡ የጣቢያው አስጎብኚ ወ/ት ህይወት አሰፋ ትባላለች፡፡ ስለ አዞ አፈጣጠር ስታብራራ መስማት ያልፈለገን ሰው ሳይቀር በማራኪ አቀራረቧ እንዲያደምጣት ታስገድዳለች፡፡ አቀራረቧ እስከዛሬ በርካቶቻችን ስለ አዞ የምናውቀውን እውነታ አጥርቶ ትክክለኛ መረጃ እንድንይዝ የሚያደርግ ነው፡፡ ህይወት የተረከችውን የአዞ አፈጣጠር እንዲህ አቅርቤዋለሁ፡፡
“የአዞ ተፈጥሮ በህይወት አንደበት”
ሃይቅ ዳርቻ ላይ አዞ እናት ከውሃው ከ20 እስከ 30 ሜትር ትርቅና፣ 60 ሣ. ሜትር ያህል አሸዋውን ቆፍራ እንቁላሎቹን ትቀብራለች፡፡ እንቁላሎቹ አዞ ለመፈልፈል 90 ቀናት ይበቃቸዋል፡፡ ጫጩት አዞ ገና እንደተፈለፈለ አሸዋ ውስጥ ሆኖ ድምፅ ማሰማት ይችላል፡፡ አንድ አዞ ከ 3 ዓመት እስከ 6 ዓመት ባለው ጊዜ ውስጥ ለእርድ ይደርሳል፡፡ አዞ አናቱ ካልተመታ አይሞትም፡፡
የሚታረደውም እንደሌሎች የእርድ እንስሳት ከአንገቱ ስር ሳይሆን በጀርባው በኩል ነው፡፡ ምክንያቱም የስረኛው ቆዳ እጅግ ተፈላጊ ስለሆነ እንዳይጎዳ ነው፡፡
ቆዳቸው እስከ 400 ዶላር ይሸጣል፤ ስጋቸው ግን በማርቢያ ጣቢያው መልሶ ለራሳቸው ምግብነት እየዋለ ቢሆንም እየተገነባ ያለው ዘመናዊ ቄራ ሲጠናቀቅ፣ ሃገሪቱ የአዞ ስጋ ወደ ውጭ ትልካለች፡፡ አንድ ኪሎ የአዞ ስጋ በአሁኑ ወቅት እስከ 160 ዶላር ይሸጣል።
የአዞን ፆታ ለመለየት በሚገባ ስለ አዞ የሚያውቁ ሰዎች ያስፈልጋሉ፡፡ ማንም ሰው በእይታ ብቻ ይሄ ወንድ ነው፣ ይህቺ ሴት ነች ብሎ መለየት አይችልም። ባይን የሚታይ የፆታ መለያ አዞ ጨርሶ የለውም፡፡ የአዞዎች የፆታ ሁኔታ በባለሙያዎች የሚለየው የተፈለፈሉበትን አሸዋ ሙቀት በመለካት ነው፡፡ ሙቀቱ ከፍተኛ ከሆነ ወንዶች ይሆናሉ፤ ቀዝቀዝ ካለ ሴቶች ይሆናሉ፡፡
እናት አዞ፤ በአሸዋ ውስጥ የቀበረችውን እንቁላል በየጊዜው እየተመላለሰች ደህንነቱን ትከታተላለች። ከተፈለፈሉ በኋላ ድምፃቸውን ከአሸዋ ውስጥ ስትሰማ በአፏ እየያዘች ታወጣና ውሃ ዳር ሳር ውስጥ ታስቀምጣቸዋለች፡፡ ይህን የምታደርግበት ምክንያት ጫጩት አዞዎች ትናንሽ ነፍሳትን እንዲመገቡ ነው፡፡ በሌላ በኩል በውሃ ውስጥ የሚገኙ ትላልቅ አዞዎች እንዳይበሉባትም ለመከላከል ነው፡፡ እናት አዞ ልጆቿን ከአደጋ ለመጠበቅ ዛፍ ላይ ወጥታ 360 ዲግሪ እየተመለከተች በትጋት ቅኝት ታደርጋለች፡፡
ጫጩት አዞዎች ከጥርስ ጋር ስለሚፈጠሩ ገና ከአሸዋ ውስጥ ሲወጡ መናከስ ይጀምራሉ። የጥርሳቸው ብዛት ከ62 እስከ 66 ይደርሳል፡፡ አዞ በነዚህ ጥርሶቹ እየቆረጠ ዋጥ ማድረግ እንጂ ማኘክ፣ ማላመጥ የሚባል ጣጣ አያውቅም። ከስጋ ውጪም አዞ ሌላ ምግብ አያውቅም። አዞ ተንቀሳቃሽ ምላስ የለውም፤ ለዚህ ነው የማያላምጠው፡፡
አስጎብኚያችን ህይወት እዚህ ጋ ጥያቄ ልጠይቃችሁ አለች፡፡ የአዞ እንባ የሚባለው ምንድን ነው? አዞ ምግብ ሲበላ ያለቅሳል የሚባለውስ? ብላ ጠየቀችን፡፡ በርካቶች የመሰላቸውን ሞከሩ፤ አንዳቸውም ግን መልሱን አላወቁትም፡፡ እኔው መልስ ልስጥ አለችን፡፡
አዞ ቆዳው ጥቅጥቅ ነው፡፡ የላብ ማስወጫ የለውም። በብዛት ቆርጦ ሲውጥ ጉሮሮው ይጨናነቃል፡፡ ጎሮሮው ሲጨናነቅ ላብ ያልበዋል፡፡ ላቡ በአይኑ በኩል ይወጣል፡፡ ስለዚህ የአዞ እንባ ላብ ነው፡፡ አዞ ያስለቅሳል እንጂ አያለቅስም” አለችን፡፡
ስለ አዞ አንዳንድ እውነታዎች
አንዲት አዞ በአንድ ጊዜ ከ30-70 የሚደርስ እንቁላል ትጥላለች፣ በአመት አንድ ጊዜ ብቻ የምትጥል ሲሆን 85 በመቶው ይፈለፈላል። በአለም ላይ 25 ዓይነት የአዞ ዝርያዎች ሲኖሩ አራቱ በአፍሪካ ይገኛሉ፡፡ሰ በኢትዮጵያ የሚገኘው አደገኛው የናይል አዞ የሚባለው ብቻ ነው፡፡
አንድ ትልቅ አዞ ከ7-8 ሜትር ሲረዝም፣ ከ500-700 ኪ.ግ ይመዝናል፡፡ ከ120-150 አመትም ይኖራል፡፡ የአዞ ቆዳ በአለማቀፍ ደረጃ እጅግ ተፈላጊ ሲሆን ከ27-37 ሣ. ሜትር ስፋት ያለውና ሽንቁር የሌለው ንፁህ ቆዳ 1ኛ ደረጃ ተብሎ እስከ 400 ዶላር ይሸጣል፡፡