Administrator

Administrator

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ በትግራይ ክልል ሽራሮ ከተማና በአማራ ክልል አብርሃ ጅራ ከተማ አዳዲስ የምርት መቀበያ ቅርንጫፎችን መክፈቱን አስታወቀ፡፡
ሰሞኑን ተመርቆ  አገልግሎት መስጠት የጀመረው በትግራይ ክልል ሽራሮ የሚገኘው ቅርንጫፍ በፀለምቲ፣ አስገደ ፅምብላ፣ ታህታይ አድያቦ፣ ላዕላይ አድያቦ፣ መደባይ ዛና፣ ነአደር አዴት፣ መረብለኧ፣ ወኔለኧ፣ ቆላ ተምቤን፣ ጣንቋ አበርገሌ፣ ሰሀርቲ ሳምረ እና ወልቃይት አካባቢ የሚመረቱ ምርቶችን ለግብይት የሚያመቻች ነው ተብሏል፡፡ በተጨማሪም በአካባቢው ያሉ ሌሎች ወረዳዎችም ተጠቃሚ ይሆናሉ ተብሏል፡፡ በአማራ ክልል የሚከፈተው የአብርሃ ጅራ ቅርንጫፍ በምዕራባዊ አርማጭሆ በሚገኙት በአብርሃ ጅራ፣ አብደራፊ ኮርሁመር፣ ጐብላ፣ ግራር ውሃ፣ መሃሪሽ እና ዘመነ መሪኬ እንዲሁም በፀገዲ በሚገኙ አካባቢዎች የሚመረቱ ምርቶች የሚቀርቡበት ይሆናል ተብሏል፡፡
በምርት ገበያው አሠራር እነዚሁ ቅርንጫፎች እንደሌሎቹ ቅርንጫፎች ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የምርት ናሙና በመውሰድ፣ ክብደትና ጥራት የሚለኩበት እንዲሁም አስተማማኝ የመጋዘን አገልግሎት የሚሰጡ ይሆናሉ፤ ለአርሶ አደሮቹም ዘመናዊና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት ለአገሪቱ ምርት ግብይት መሻሻል የጐላ አስተዋጽኦ ያበረክታሉ ተብሏል፡፡ ምርት ገበያው በአሁን ወቅት በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ የምርት ማስረከቢያ ማዕከላቱን ከ17 ወደ 19 ከፍ ማድረጉም ተጠቁሟል፡፡

Saturday, 29 November 2014 11:29

የምሬት ድምጾች

ሀና ላላንጎ የአስራ ስድስት አመት ታዳጊ ናት ፡፡ አየር ጤና አካባቢ  ከትምህርት ቤት ወደ ቤቷ ለመሄድ በተሳፈረችበት ሚኒባስ ታክሲ ተገዳ ከተወሰደች በኋላ በደረሰባት የቡድን የመደፈር ጥቃት ምክንያት ህይወቷ አልፏል፣ ጉዳዩ በህግ ተይዟል፡፡ የኢትዮጵያ ሴቶች ማህበራት ቅንጅት  ሰላም ለሴቶች ከጓዳ እስከ አደባባይ  በሚል መርህ ዘንድሮ ስለሚከበረው ዘመቻ በፆታዊ ጥቃት ዝግጅት እና በሃና ጉዳይ ላይ በራስ ሆቴል ፕሮግራም አዘጋጅቶ ነበር፡፡ በወቅቱ መድረኩ ላይ ስለሀና የተሰጡ አስተያየቶችን መርጠን ለጋዜጣው በሚመች መልኩ ኤልሳቤት ዕቁባይ አቅርባዋለች፡፡

“አውሬ ያለ ጫካ አይኖርም”
ዶክተር ምህረት ደበበ

ለሀና ቤተሰቦች መፅናናት እንዲሆን የሀና ሞት የብዙዎች ትንሳኤ እንዲሆን እመኛለሁ፡፡ ሁላችንም ራሳችንን አንድ ጥያቄ እንድንጠይቅ እፈልጋለሁ፡፡ ሀናን ማን ገደላት ሀና በአንድ ቀን አልሞተችም፡፡ ሀናን የገደሏት ሰዎች አንድ ቀን አልተጠቀሙም፡፡ አንደኛ፤ ሀናን የገደላት የሀናን ገዳይ የፈጠረ ህብረተሰብ ነው፡፡ ድርጊቱን የፈፀሙ ሰዎች ሲወለዱ እና በጨቅላ እድሜያቸው እንዲህ አይነት ሰዎች እንዳልነበሩ እናውቃለን፡፡ የእኛ የእጅ ስራ ናቸው፡፡ ሁለተኛ፤ ሀና የዛን ቀን አባቷ እንደተናገሩት በብዙ ሰዎች አጠገብ እና የማዳን ሀይል ወይም ችሎታ በነበረበት ሁኔታ ውስጥ ነው ያለፈችው፡፡ ሀና ላይ ይህን ድርጊት የፈፀሙ ሰዎችን ብዙዎች የኮነኑ ሲሆን፤ እንዲያውም ፌስቡክ ላይ አውሬዎች ተብለዋል፣ ግን አውሬ ያለጫካ አይኖርም፡፡ እያንዳንዳችን ጫካ ሆነናል፡፡ ይዘዋት የገቡበት ግቢ ሰፊ ነው፡፡ የነዛ ሰዎች ጎረቤቶች ገድለዋታል፡፡ ቸልተኝነት ሊሆን ይችላል የአካል ሊሆን ይችላል ግን ድፍረት ነው፡፡   ድፍረት ማለት የአንድን ሰው ክብር ማዋረድ ማለት ነው፡፡ የማዳን ሀይል ያላቸው ፍትህ ማስፈፀም የሚገባቸውም ገድለዋታል፡፡ ያንን መቀበል አለብን፡፡  በጣም የሚገርመው ነገር ደግሞ ሀናን ሆስፒታል ያሉ የጤና ባለሙያዎች ናቸው የገደሏት ፡፡ ደፍረዋታል፣ እኔ ሀኪም ስለሆንኩኝ አፍሬያለሁ፡፡ እኔ ግማሹን ጊዜዬን አሜሪካን ነው የምሰራው፡፡ እዛ ቢሆን ሊደረግ የሚችለውን ነገር ስለማውቅ ሀና ምንም ስለሆነች ብቻ ሳይሆን ሰው ስለሆነች፣ የማንም ልጅ ስለሆነች ሳይሆን ሰው ስለሆነች፡፡ ሀና የተገደለችው በደፈሯት ሰዎች ቤት ውስጥ አይደለም፡፡
በሆስፒታል ውስጥ ነው፣ ሰው እንዴት ሆስፒታል ውስጥ ይሞታል? መጨረሻ ላይ የምለው ሀናን የገደልኳት እኔ ነኝ፤ ነው፡፡
እዚህ ላይ ሶስት ትላልቅ ነገሮች አሉ አንዱ ፆታ ነው፡፡ ሁለተኛው ወሲብ ነው፡፡ ሶስተኛው ጥቃት ወይም ሀይል ነው፡፡ እያንዳንዳችን ስለወሲብ የምንናገረው እና ስለወሲብ የምናስበው ነገር እስኪስተካከል ድረስ እንዲህ አይነት ነገር አይቆምም፡፡  ህመሙ ያለው ሴቶች ላይ በተጫነው ነገር ብቻ አይደለም፡፡ ወንድነት መስተካከል እስካልቻለ ድረስ  እንደዚህ አይነት ነገር አይቆምም፡፡ ይህ አይነቱ ትልቅ ድፍረት ከመፈፀሙ በፊት መንገድ ላይ ብዙ ትንንሽ ድፍረቶች አሉ፡፡ ትልቁ ድፍረት በቋንቋችን ውስጥ ታጭቋል፡፡ ቋንቋችን ምን ያህል ቫዮለንት እንደሆነ ፣ ምን ያህል የሰዎችን ክብር የሚያዋርድ እንደሆነ ከቤት እስከ መንገድ ማየት ይቻላል፡፡
ወንዶች ለሚያደርጉት ነገር ብዙ ማብራሪያ ይሰጣል፡፡ዛሬ እስቲ ገልብጠን እንየው፡፡  ግን ለምን አብዛኛው ወንድ እንደዛ አልሆነም፡፡ ወንድነት ምንድን ነው? ጀግንነት ምንድን ነው? ደካማን ማገዝ ፣መርዳት  እኔ አንድ የምለው ነገር አለ ሰዎች ካንገት በላይ ካላደጉ ካንገት በታች ነው የሚኖሩት፣ ካንገት በታች ደግሞ ምንም ማሰብ የሚችል ነገር የለንም፡፡ ስሜትን መግዛት የሚችል ነገር የለንም፡፡ እዚህ ብንቆጠር ሴቶች ይበዛሉ፣ ሴቶች እዚህ የመጡት ስላጠፉ ነው፡፡ መቆጣት እና መሰብሰብ የነበረበት ማን ነው ፡፡ ልክ እንደ ሀኪም ባለሙያነቴ አሁንም በወንድነቴ አፍራለሁ፣ አብዛኛው ፖሊስ ማን ነው?  ወንድ ነው ሴት ነው፣ አብዛኛው የጤና ባለሙያ ማን ነው? የመገናኛ ብዙሀን ባለሙያ ማን ነው? ወንድ፡፡ እንደዚህ አይደለም ካልን ለምንድን ነው አክት የማናደርገው፡፡
 ይህ የሴቶች ጉዳይ ተብሎ ታይቶ ይሆናል፡፡ አይደለም፡፡ የወንዶች ጉዳይ ነው፡፡ እኔ ልክ ድርጊቱን ከፈፀሙት ሰዎች እኩል ሀላፊነት መሸከም አለብኝ፡፡ የማህበረሰብ ለውጥ እስኪካሄድ ድረስ ብዙ መስራት ይጠበቅብናል፡


“ከዚህ በላይ ምን ሽብር አለ”
ወ/ሮ ሰሎሜ ታደሰ

በጣም አዝኛለሁ፣ ሆድ ብሶኛል፣ ደክሞኛል፡፡ የልብ ድካም ነገር ካለ፣ ድሮ በሽታ ነበር የሚመስለኝ፤ አሁን ግን የሚረዳ ማጣት ማለት ነው፡፡ የዛሬ ሁለት አመት ልክ እንደዚህ በኢትዮጲያ አየር መንገድ በበረራ አስተናጋጅነት ትሰራ በነበረችው በአበራሽ ላይ በተፈፀመው ድርጊት ደንግጠን አሁን በአይኔ መጣ የሚል እንቅስቃሴ ጀምረን ልክ የዛሬውን አይነት ሂደት አልፈን ነበር፡፡ አሁን ደግሞ እዛው ተመለስን፡፡ ማንንም ከመውቀሳችን በፊት እያንዳንዳችን ራሳችንን እንጠይቅ እንደተባለው ራሴን ጠየቅኩ፡፡ እኛ እንግዲህ በተነፃፃሪ ተጠቃሚ ከሚባው የህብረተሰብ ክፍል ነን፡፡ እውቀት አለን፣ ብዙ ነገሮችን የማየት እድል አለን፣ከሌላ የተሻለ ገንዘብ አለን፡፡ ግን እየሰራን ያለነው ስራ ውጤት የማያመጣው በበቂ እየሰራን አይደለም ማለት ነው ወይስ አልቻልንበትም ወይስ ተንቀን ነው ብዬ አሰብኩ፡፡  ወጣቶቹን ሳይ፣ ዶክተር ምህረትን፣ ሀይሌ ገብረስላሴን ሳይ ደግሞ ደስ አለኝ፡፡  ሌላው ያሰብኩት ደግሞ እዚህ አገር ሰው ሁሉ የሚፈራው ፀረሽብር ህጉን ነው፡፡ ግን ከዚህ በላይ ምን ሽብር አለ? ለኔ ሽብር ማለት በሰላም ወጥቶ አለመግባት ማለት ነው፡፡ ህጉ ይቀየርልን ሳይሆን ወደ ፀረ ሽብር ሕጉ ይቀየርልን፡፡ እነሱ ስለሚፈሩ ነው ጸረ ሽብርተኛ ህግ ውስጥ የከተቱት፡፡ ትንሽ ቀን መንግስት ቀጥቀጥ ቢያደርግ ብዙ ነገር እንደሚጠፋ መገመት ይቻላል፡፡
ወ/ሮ ሰሎሜ ታደሰ

“ይቺን አገር ያጠፋት ምንአገባኝ ነው”
አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ

የሃና ቤተሰቦችን እግዚአብሄር ያፅናቸው፡፡ይህ ነገር ዜና ሆኖ የወጣው ለምን እንደሆነ ሳንግባባ የቀረን አይመስለኝም፡፡ እንዲህ አይነቱ ድርጊት ብዙ የለም ብላችሁ ታስባላችሁ እጅግ ብዙ አለ፡፡ ሀና ስለሞተች ነገ በማህበረሰቡ ውስጥ ስለማይጠቋቆሙባት እና ሌሎች ከዚህ ጋር የተያያዙ ነገሮች ስለማይፈፀምባት እንጂ የሀና አይነት ሺዎች ናቸው - ሁሉንም ነገር በውስጣቸው ይዘው የተቀመጡ፡፡ ይቺን አገር ያጠፋት ምንአገባኝ ነው፡፡ጥቃት ሲፈፀም ብናይ ይበላት እንዲህ ሆኖ ነው እንዲህ አድርጋው ነው ይባላል፡፡ መንገድ ላይ የሆነ ነገር አጋጥሞኝ ጣልቃ ስገባ ምን አገባው ምን ቤት ነው የሚሉ አሉ፡፡ እነሱ ምን አገባቸው? እንዴት አያገባኝም?! የምኖርባት አገር እኮ ነች፡፡ ይቺን አገር ነው ጥሩ ሆና ማየት የምፈልገው ፡፡ ሌላው በጣም ያስደነገጠኝ በአምስት ሰዎች የተፈፀመ መሆኑ ነው፡፡ አምስት ሰዎች እንዴት አንድ አይነት አስተሳሰብ ውስጥ ገብተው ይህን ድርጊት ሊፈፀሙ ቻሉ፡፡ አንዱ እንኳን ጥያቄ አይፈጠርበትም? በዚች አገር ብዙ የሚሰቀጥጡ ታሪኮች አሉ፡፡ ነገር ግን ድርጊቶቹ የኛ ድምር ውጤት ናቸው፡፡ ይህን ከሰማሁ ጀምሮ ልጆቻችንን ለምን አመጣናቸው የሚል ስጋት ውስጥ ገብቼያለሁ፡፡ መፍትሄውን ከፖሊስ፣ ከፍትህ አካል ብቻ አንጠብቅ፡፡ እኔ እንዲያውም እድሜ ልክ ከማሰር በአደባባይ አርባ ጅራፍ መግረፍ ውጤት ሳያመጣ አይቀርም፡፡


ከአበባው መላኩ ጋር ስለጐንደርና ስለ ጉዋሳ የተጨዋወትነው

“ከግጥም ከመሰንቆ ልጆች ጋር እንዴት ተዋወቃችሁ?” አልኩት፡፡
“ግጥም በመሠንቆዎች ስለ ፓኤቲክ ጃዝ የሚያውቁት ነገር የአለ መሰለኝ፡፡ ወርሃዊውን ዝግጅት የመካፈል ልማድ እንዳላቸው ነግረውናል፡፡ በመጀመሪያ የሰማሁት የግጥም በመሰንቆ ቡድኖች ለግጥም በጃዝ ስጦታ ለመስጠት ይፈልጋሉ - ነው፡፡ በ3ኛ ዓመት ዝግጅት ሰዓት ሳይሆን መድረክ መስጠት ይቻላል…ከጐንደር ድረስ መጥተው፣ የጐንደርን ስም ጠቅሰው እንዴት ብለው ይመለሳሉ? ሌላም የሽልማት ፕሮግራም አለንና ያንን መጠቀም ይችላሉ አልን፡፡ መጡ ተገኙ ነገር ግን በራሳቸው ምክንያት ስጦታውን ሊያከናውኑ አልቻሉም” አለኝ፡፡ እኔ የጐንደሮቹን ግጥም በመሰንቆ ቡድኖች ጠይቄያቸው ቴክኒካል ችግር ለሁኔታው አለመመቻቸት ምክንያት ሆኗል ነው ያሉኝ፡፡ ዞሮ ዞሮ ስጦታው በበረከት በኩል እንዲደርሳቸው አድርገናል ነው ያሉት፡፡ መንፈስ ለመንፈስ ግን ተግባብተዋል ብዬ ዘለልኩት፡፡
“ዋናው ነገር ተገናኝተናል፡፡ መስከረም ላይ እኔን ጋበዙኝ፡፡ በረከትን ጠየኩት “ለግጥም የተሰጡ ልጆች ናቸው” አለኝ፡፡ “የግጥም አገልጋዮች ናቸው” አለኝ፤ አለ አበባው፡፡
የግጥም ዲያቆናት፣ ምዕመናን - ማለቱ ነው፡፡
“ወጪያችንን ችለን ለምን እንደግሩፕ አንሄድም?” ተባባልንና ሁላችንም የፓኤቲክ ጃዝ አባላት ሄድን፡፡ አንዳንዶቹ ጐንደርን አይተው ስለማያውቁ ደስ አላቸው፡፡ ሌሎቻችን ደግሞ የምናውቀው እኔ በ98 አውቀዋለሁ ግሩሜም ያቀዋል - ምሥራቅና ምህረት ናቸው የማያውቁት፡፡ አቀባበላቸው ግሩም ነበር! በጣም ደስ ብሏቸው ነበር…ግጥም ንባቡን በዋናነት እኔ ደጋገምኩ እንጂ ሁላችንም አቅርበናል! አዳራሹ ግጥም ብሎ ነበር! ብዙ ህዝብ ነበር፡፡ የቆመው ከተቀመጠው ይበልጥ ነበር! እኔ እንደዚህ አልጠበኩም፡፡ በአውሮፕላን ችግር ፕሮግራም ተሰርዞ፣ ባዲስ መልክ አዘጋጅተውት ያለቀኑ ተዋውቆ በፌስቡክ፣ በአንዳንድ ቦታ ብቻ አስተዋውቀውት ነው፡፡ ብዙ ሰው መጣ! እነሱም ተደምመው ነበር፡፡ በጣም መልካሙ ነገር ጥሩ የሚሰሙ ሰዎች ነበሩ፡፡ ያየነውንም ትዝብት ተናገርን ጐንደርን ያህል አገር ይዘው፣ በውስጡ ያለውን ታሪክ፣ ላለፉት 250 ዓመት ዘመን ላይ የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ትምህርት፣ የአስተዳደር መዲና የሆነች አገር ይዘው ያን ያን እሚሸት ነገር የሌለበት ነገር ትርፉ  ድካም ነው፡፡ ዘጥ ዘጥ ነው፡፡ ዞር ዞር በሉ - ወላጆቻችሁን ጠይቁ፡፡ ወደአቅራቢያችሁ ገዳማትና አብያተ ክርስቲያናት ጐራ በሉ - መዛግብቱን እዩ፡፡ መዛግብቱ ምን ይላሉ፡፡ በዚያ መጠን ሥሩ፡፡ ታላላቆቻችሁን ጋብዙ - ከዚያ ምን ተገኘ የሚለውን እዩ!...መከርን፣ ሸጋ ነው!
“የባህል ቤቱን እንዴት አገኛችሁት?”
“…ዘመናዊውን ዘፈን እንኳ ወዝ ይሰጡታል፡፡ ሐማሌሌን እንኳ አሳምረው ነው የሚዘፍኑት፡፡ ሕብረ - ብሔራዊ ስሜት አላቸው፡፡ የሁሉ እናት የመሆን ስሜት ነው ያላቸው!... በጣም ቆንጆ ነው! ሴቶች ድራም ይዘው ማየት በጣም ትፍስህት ሰጥቶኛል፡፡ የመጨረሻ ሙድ አለ፡፡ የግጥሞቹ ይዘት ላይ እኔ ትንሽ ያዝ አድርጐኛል! ስሞች እያነሳች ታወድሳለች! ቀረርቶ ሽለላዋ መልካም ነው - ሌላው ግን የሥነ - ቃሉ የግጥሙ ባለቤቶች ሆነው ምንም አዳዲስ ይዘት የላቸውም ወይ? ብያለሁ!” አለኝ፡፡
“የስቴጅ ግጥም አንባቢዎችንስ ብስለት ነገር እንዴት አየኸው?”
“ከ12 ዓመት በፊት ፑሽኪን አዳራሽ ይቀርቡ የነበሩ ግጥሞች ነበሩ! በወጣቶች፣ በሁሉም አቅጣጫ ወጣት ናቸው! ነጠላ ሀሳብ ላይ የማተኮር ችግር አያለሁ! ያንን ጊዜ ያስታውሰኛል፡፡ የተወሰኑ ተስፋ የሚጣልባቸው ነበሩ - በተለይ የዕይታ ነገርን ያበሰሉ ገጥመውኛል…የመለመልነውም ልጅ አለ - ከውስጣቸው፡፡ ልሣን ይባላል፡፡ Talent Hunt ነው፡፡
ከየቦታው ለፓኤቲክ ጃስ ከምነመለምላቸው ለምሣሌ ከወሎ አካባቢ ሼህ ቡሽራ የሚባሉ ናቸው መንዙማ አዋቂ ጋብዘን ሆቴላቸውን አበላቸውን ችለን ነበር - ሌላ መንግሥቱ ዘገየ” ቀብድ የበላች አገር” የሚል መጽሐፍ የፃፈ ነበር - መጽሐፉን አይተን በአድራሻ አገኘነው! እሱንም ቀለቡን ችለን ጋብዘናል! ሀሳቦች አሉን፡፡ ለምሳሌ ደብረዘይት አካባቢ ቶራ ቡላ የሚባል የሥ/ጽሑፍ ማህበር ነበር፡፡ እነሱም እንዲያቀርቡ አስበን ነበር፡፡ እነ ምንተስኖት ማሞን የደብረዘይቶቹን ነግረን ነበር፡፡ ወደ አዋሳ አካባቢም “60 ሻማ” እሚባል ማህበር ነበር፡፡ ይሄ ሃሳብ እያለ ነው እንግዲህ ጐንደሮች ሲጠሩን የሄድነው! እንደነሱ በአውሮፕላን ባይሆን በመኪና ነው!”
በበኩሌ አልኩት፤ “የናንተ አዳራሽ - የእኔ ኦፕን - ኤር ነው! ልዩነቱ ያ ነበር፡፡”
የጉዋሣ ነገር
በረዶ አገር ሄጄ አቃለሁ - አውሮፓ፡፡ እንደ ጉዋሣ ያለ ቀዝቃዛ ቦታ በህይወቴ አጋጥሞኝ አያውቅም፡፡ በነገራችን ላይ ዘፈኑ ግጥም ላይ
“አገሯ ዋሳ መገና፤ አገሯ ዋሳ መገና
ምነው አልሰማ አለች፣ ብጣራ ብጣራ”
“ዋሣ” ይመስለን የነበረው “ጉዋሣ” ነው፡፡ “መገና”ም የመሰለን “መገራ” መሆኑን ልብ እንበል፡፡
ከአዲሳባ ለተነሳ ሰው ወደ ደብረ ብርሃን ይኬድና፤ ጉዶ በረትን አልፎ ወደ ደብረ ሲና አምርቶ (ደብረሲና እንግዲህ ዳኛቸው ወርቁ በአደፍርሱ “እግዜር አገሮች ሰርቶ ሰርቶ የተረፈውን ኮተት ያከተባት ከተማ” ያላት ናት) ጣርማ በር ጋ ሲደረስ ወደ ግራ እጥፍ ነው፡፡ 180 ኪ.ሜ ላይ ማለት ነው፡፡ መዘዞና ባሽ ይቀጥላል፡፡ ወደ ግራ ቢሉ ሞላሌ አለ፡፡ ቀጥታውን ሲኬድና ሲቀጠል ግን ይጋም (Yigam) ይገኛል፡፡ ይጋምን ሲያልፉ ጉዋሣ አጥቢያ ይደርሷል፡፡ በዚያ ወደቀኝ ወደ ካድሉ ወደ አጣዬ ያስኬዳል፡፡ ግራ ግራውን ማህል ሜዳ እንግዲህ ዙሪያ ገባውን አለ፡፡ በማህል ሜዳ ተሻግሮ ወደ ግሼ ይዘለቃል፡፡ እኛ ግን ወደ ማህል ሜዳ ስንሄድ ሰፌድ - ሜዳን አልፈን ነው፡፡
ይሄ ሙሉቀን የዘፈነለት ጉዋሣ ለአዲሳባ ሰሜን ነው፡፡ የቅዝቃዜውን ነገር አለማንሳት ነው፡፡ ከባህር ወለል በላይ ከ3200 -3700 ሜትር ከፍታ ላይ ነው፡፡ የተሰባበረ ተራራ ይታያል፡፡
ፀጋዬ ገ/መድህን “በአንኮበር” ግጥሙ “የፈፋ አነባበሮ” ያለው ነው፡፡
ወደ ምዕራብ የሚጓዙና ሰንጥቀውት የሚያልፉ ስምጥ ሸለቆዎችና የባህር ሸለቆዎች አሉ፡፡ በአባይና በአዋሽ ማህል ያለ ውሃ ማገቻ ነው፤ ቢባል ድፍረት አይሆንም፡፡ የጉዋሣ ምሥራቃዊ ወገን ተረተሩን ቁልቁል ወደሸለቆው ልኮ ታላቁን ስምጥ ገደል ድንገት ሲተረትር ከመነሻው ይርቃል፡፡ ከፍታው መርገብ ይጀምራል፡፡ በ50 ኪ.ሜ ርቀት ውስጥ በ2600ሜ ዝቅታ ደረጃ ባንዴ ውርድ የሚል ታምረኛ ሥፍራ ነው፡፡ ከዚያ ወደ አዋሽ ግርጌ ወርዶ የታላቁን ስምጥ ሸለቆ ወለል ይቀላቀላል፡፡ የጉዋሣ ምዕራብ ደግሞ በድልዳላዊ አካሄድ ወደማህል ሜዳ ይገባል (3000 ሜትር ግድም) መልክዐ - ምድሩና ሠፈሩ እንግዲህ ይሄ ነው፡፡
ከጉዋሣ የግቻ ሣር (Afro alpine) [በአፍሪካ የራሳችን የሣር - ዝርያ ነው] እና በተራራው ትዕይንት መካከል የጉዋሣ ማህበረሰብ ሎጅ (ማረፊያ - መናፈሻ) አለ፡፡ ለዚያ ቦታ እንደወፍ ጐጆ ማለት ነው፡፡ ክፍሎቹ፤ በትልቅ ቅጽ ተገነቡ እንጂ በልማዳዊ መንገድ የተሠሩ የወፍ ጐጆዎች ማለት ናቸው፡፡ የጉዋሣ ማህበረሰብ ነው የሚያስተዳድራቸው፡፡ አራት ባላመንታ - አልጋ ክፍሎች (“ጭላዳ”፣ “ቅልጥም - ሰባሪ”፣ ቀይ ቀበሮ” የሚባሉ የከፋ ቀን በአገሩ በሚገኙት ብርቅዬ እንስሳት የተሰየሙ) አይቻለሁ፡፡ ከኒህ በተለየ፣ የእሳት መሞቂያን ያካተተ እልፍኝ፤ ምግብ - ቤትና ማድቤት ያለው ትልቅ የእንግዳ  ማረፊያ ክፍል አለ፡፡ የትምህርትና የመረጃ ማዕከል ባንድ ወገን ያለ ሲሆን፤ የመታጠቢያና መፀዳጃ ያለው ዘርፍ - ክፍልም አለ፡፡ ለካምፕ አመቺ ቦታ አለው፡፡ የገዛ ድንኳን ይዞ አሊያም ከማህበረሰቡ ቱሪዝም ማህበር ተከራይቶ ደንኩኖ መሥፈር ይቻላል፡፡ ሰው የገዛ ምግቡን ሸክፎ መምጣት እንዳለበት መቼም ግልጽ ነው፡፡
የጉዋሣ ማህበረሰብ አካባቢ ጥበቃ አጥቢያ በመኪና መንገድ የሚደረስበት ነው፡፡ ከአዲሳባ ማህል ሜዳ በሚሄደው ህዝብ ማመላለሻ ሽር ማለት ይቻላል፡፡
ጉዟችን መጀመሪያ ከደብረ - ብርሃን 15 ኪ.ሜ የምትገኘው “አማፂዎቹ” የተባለ ቦታ ቁርስ በመብላት እንደሚጀምር የጉዞ - መሪያችን አብስሮናል፡፡ “አማፂዎቹ”ን ለማወቅ መቼም ከስማቸው መረዳት ነው ዋናው” ነው ያለን ጉዞ መሪው፡፡ በኋላ የደረስነው አንድ ጉብታጋ ነው፡፡ ከዚያ ሆነው ቁልቁል ሲያዩ የሚያምር መልክዓ ምድራዊ ትርዒት አለ፡፡ የኢትዮጵያ አብያተ - ክርስቲያናትና ቤተ - መንግሥቶች ለምን ከፍታ ላይ እንደሚሠሩ ተወያየን፡፡ ከፍታ አንድም ለማየት አንድም ለመታየት ነው - ተባባልን፡፡
ከዚያ እንግዲህ ጣርማ - በር ላይ ታጥፈን ማረፊያ - መናፈሻው (Lodge) ጋ ደረስን፡፡ ምሣ በላን፡፡
ከዚህ ወዲያ ነው ጉዱ! የእግር ጉዞ ተጀመረ፡፡ የእግር ጉዞ ታሪክ አስረጂ አጠገባችን አለ፡፡ እኔ ብዙም ሳልራመድ ዳገቱ ያደክመኝ ገባ፡፡ አንዴ አረፍኩ፡፡ ትንሽ ሄጄ ልቤ ያለልክ ትመታ ጀመር፡፡ “በቅሎ ቢመጣልኝ ይሻላል” አልኩ፡፡ መቼም ከተሜዎች ናቸውና መድከማቸው አይቀርም ብለው ነው መሰል፣ አገሬው በቅሎ እየነዳ ይከተለናል፡፡
አንዷን በቅሎ አመጡልኝ፡፡ በበቅሎ ተጉዤ አላውቅም፡፡ እንዴት ልውጣ? ወደ አንድ ከፍ ያለ አፋፍ በቅሎዋን አስጠጉልኝና ተደጋግፌ ወጣሁ፡፡ በቅሎዋን የሚስቡልኝ አንድ አጭር ቆፍጣና አዛውንት ናቸው፡፡ ነገረ- ዕንቆቅልሹ ገረመኝ፡፡ እኒህ የ81 ዓመት ሽማግሌ መንገዱን እንደወጣት ይሸነሽኑታል፡፡ እኔ ደግሞ ከሳቸው በጣም በዕድሜ የማንሰው ዘመኔኛ በቅሎ ላይ ነኝ! የበቅሎ አነዳድ መመሪያ ተሰጠኝ:-
ዳገት ሲሆን ወደ ኮርቻው ቀዳማይ ድፍት!
ቁልቁለት ሲሆን ወደኋላ ልጥጥ ማለት!
“ቁልቁል መሳብ፣ ሽቅብ መሳብ” እንዳለው ደራሲው፤ ወጣነው፡፡ ወረድነው፡፡ አሥራ ሰባቱን ኪሎ ሜትር ተጓዝነው!
መኪናችን ዕቃችንን ሸክፎ ቀድሞን ደርሷል፡፡ ቀድመው ለጥናት የመጡ ፈረንጆች እዚሁ ግድም መሥፈራቸውን ምልክት አየን፡፡
ሰው ሁሉ ደረስን ብሎ እፎይ ማለት ሲቃጣው፤ “ፍራሽና አንዳንድ የመኝታ ዕቃ ይዛችሁ ሽቅብ ውጡ፤ መድረሻችን ገና ነው” ተባለ፡፡ ያዳሜ ወሽመጥ ቁርጥ አለ! እዚሁ አይቀር ነገር ሁሉም አንዳንድ ፍራሽና የመኝታ ዕቃ እየያዘ ዳገቱን ተያያዘው፡፡ እንዳይደረስ የለም ተደረሰ፡፡ እኔ ሙላዬ ተላቋል፡፡ ብሽሽቴ ቀልቷል!
ካምፕፋየር ሊደረግ እሳት ተያያዘ፡፡ ፍልጥ ተደመረ፡፡ ነደደ፡፡ ሙቀት መጣ፡፡
ጉሙን ግን ማን በግሮት፡፡ አርድ አንቀጥቅጥ ነው፡፡ አገሬው አሁንም ዕቃ ያመላልሳል፡፡ ብርዱ -10 (ኔጋቲቭ 10) ዲግሪ ሴንቲግሬድ ነው፡፡
ስለ ጉዋሣ ለማወቅ አፈ - ታሪካዊ ትውፊቱን አንብቤያለሁ፡፡
እንደቀበሊኛው አፈ ታሪክ ከሆነ ጉዋሣ የተፈጠረው አንድ መነኩሴ ከተራገሙ በኋላ ነው፤ ብሎ ይጀምራል፡፡ በዚያን ጊዜ ይህ ቦታ እጅግ የበለፀገ የግብርና ቦታ ነበር ይባላል፡፡ በጣም ምርጥ የተባለ ጤፍ ይመረትበት ነበር፡፡ አንድ መልካምና ብልህ የሆኑ አቼ ዮሐንስ የተባሉ መነኩሴ እዚያ ቦታ ይኖሩ ነበር፡፡ ሥራቸውን በሚገባ እያከናወኑ መሬቱንም ባርከውት ነበር፡፡ ሆኖም አንዲት ሴት ከመነኩሴው ልጅ ፀንሻለሁ ብላ በማውራቷ በመነኩሴውና በአገሬው ፊት አረጋግጪ ተብላ ሸንጐ ፊት ቀረበች፡፡
“ዋሽቼ ከሆነ ድንጋይ ያድርገኝ” ስትል ማለች፡፡
ወዲያውኑ ወደ ድንጋይ ተቀየረች፡፡ መነኩሴው ግን በዚህ ብቻ አልረኩም፡፡ ሰው እሷን በማመኑም በጣም ቅር ተሰኙ፡፡ ስለዚህም ያንን ቦታ
“አንተ ቦታ ከእንግዲህ የተረገምክ ሁን!! የመጨረሻ ቀዝቃዛና ጨፍጋጋ ሁን!! የበለፀገው የግብርና ምርትህም ከእንግዲህ ግቻ ይሁን!!” ብለው ረገሙት፡፡ ይህን ሲሉ ወዲያው የአካባቢው አየር ተለወጠ፡፡ መሬቱም ዛሬ የሚታየው የጉዋሣ ቦታ ሆነ፡፡ አፍሮ አልፓይን የሣር ዘር መሆኑ ነው፡፡ ያ መርገምት መንደሩን ደሀ አደረገው፡፡ ከብዙ ዓመታት በኋላ ያገር ሽማግሌዎች ይቅርታ ብንጠይቅ ይሻላል ተባባሉ፡፡ እኒያን መነኩሴም ፍለጋ ያልሄዱበት ቦታ የለም፡፡ ሆኖም መነኩሴው ከረዥም ጊዜ በፊት አርፈው ኖሯል፡፡ ሰዎቹ ግን አፅማቸውንም ቢሆን መፈለግ አለብን ብለው ፍለጋቸውን ቀጠሉ፡፡ የመነኩሴው መንፈስ ቢታደገን እንኳ ብለው በአጥቢያቸው አፅማቸውን ሊያሣርፉ አስበው ነው፡፡ አፅማቸው ተገኘና ፍሩክታ ኪዳነ ምህረት ዳግመኛ ተቀበሩ፡፡ ለሠራኸው ጥፋት የምትከፍለው ብዙ ነው! መንፈሣዊ ፀጋ ድህነትን ለማሸነፍ አስፈላጊ ነው!
ሰዎቹ ራሳቸውን በመውቀስ የድህነታችን ዕንቆቅልሽ ታሪኩ ይሄ ነው ይላሉ፡፡     
እንግዲህ ከአበባው ጋር ወደ ጓሣ አብረን ሄደናል፡፡ “ስማ፤” አልኩት፡፡ እርግጥ ካንተ የምለየው፤ እኔ ጉራጌ አገር ዘሙቴ ማርያም ነበርኩ፤ ከዚያ ጐንደር ከዚያ ጓሣ መሄዴ ነው! የእኔ የጓሣ አመለካከት አለ ያንተስ? አልኩና ጠየኩት፡፡
“እኔ የሀረር ሰው ነኝ - ደጋ አደለም - ቆላ ነው - የሚስማማኝም ቆላ ነው!
ከመሄዳችን በፊት የተሰጡኝን ማስገንዘቢያዎች አንብቤአለሁ! አለባበስ -የእጅ ጓንት ወዘተ ያንን ማሳሰቢያ በአክብሮት ካነበቡት አንዱ እኔ ነኝ! እኔ ብርድ በኃይል እፈራለሁ - ለምን እንደሆነ አላውቅም! መድረስ አይቀርም ደረስኩ፡፡ ከከፍታ በላይ ከፍታ ላይ አስደንጋጭ ቪው ነው ያየሁት! ዓለምን በተዛማጅ ከፍታ ማየታችን እየተፈታልኝ ነው የተጓዝኩት - ደስ ብሎኛል፡፡
ቦታው አስደናቂ እንደሆነብኝ ጓሤዎችም አስደንግጠውኛል! ሰው መውደዳቸውና ትህትናቸው! ሁለተኛ እርስ በርስ ያላቸው መግባባትና መከባበር! በተፈጥሮአችን እኛ ከተሜዎቹ እራሳችንን እንለይና የበዛብን ሲመስለን በጣም አጉረምራሚዎችና ተናዳጆች፤ በተለመደው መከባበር፣ ጠባይ ውስጥ አደለም ሥራችንን የምናከናውነው! ብሶተኛ ይበዛል - ፉከራው ይበዛል! ያ ነገር እዚያ የለም! ሸክም ተሸክመው በቅንነት ይኖራሉ እነሱ! ሰዎችን ለማገልገል፣ ለመርዳት ያላቸው ጉጉት፤ መመራመር ሳያስፈልግ እነሱ ተፈጥሮን ተገዳድረውታል ብዬ እላለሁ! ሠርፀው ገብተዋል፡፡ በቅሎ ላይ መውጣቴ፤ በህይወቴ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው በቅሎ ላይ የወጣሁትና፤ ደስ ብሎኛል! ለመጀመሪያ ጊዜም ነው 3700 ከፍታ ላይ የወጣሁት እዚህ ስገኝ!
በቅሎ ላይ መውጣቴ ጥቅሙ በእግሬ እንቅፋት እያየሁ መሄዴ ቀረና በቅሎ ላይ ሆኜ አካባቢውን አያለሁ፡፡ ዞር ስልም የጓደኞቼ ቅፍለት በጉም ውስጥ የሚጓዙ ከሌላ ፕላኔት ድንገት የተከሰተ ስዕል ይመስላል፡፡ በቅሎ ላይ ሆነን ቁልቁለት ወገብ መለመጥ፣ ዳገት ማቀርቀር ነው ዘዴው፡፡ የበቅሎ ጉዞ ስርዓቱ! ወሳኝ መመሪያ! ላለመውደቅ ለማሸነፍ ለመድረስ! የህይወት ልምድ ተመክሮ ነው!
መቼም ውቴል የሚባል ነገር የለም፡፡ እንግዳነታችን ለተፈጥሮ ነው፡፡ የሚያስተካክለንም ተፈጥሮ ነው፡፡ በተፈጥሮ ዳገት ላይ ጉምና ብርድ ለብሶ ለማደር መዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡
አንድ ሁለቴ ውሃ ተጐንጭቻለሁ፡፡ በቅሎዋ ላይ ሆኜ ጉም ግን እየዳበሰኝ ያልፍ ነበር፡፡ ጢሜ እርጥበት ጤዛ አለው፡፡ ገርሞኝ አገሬውን ጠየኩ፡፡ “ይህ የጉም ሽንት ነው አሉኝ!” ጉሙ ሸናብኝ መቀበል አለብኝ! ይሄ የመጀመያዬ ቀዝቃዛ አገር ነው” አለኝ፡፡
“የእኔ የአውሮፓ ልምድ ይለያል፡፡ መኪናው በረዶ ለብሶ ባካፋ ይዛቃል፡፡ ትልቁ ልዩነት እዚያ ቤት ስትገባ ባየር ማረጋጊያ ሙቅ አየር አለ፡፡ ኮትህን ማውለቅ ይጠበቅብሃል፡፡
ሁሉንም አንድ ላይ እናስበው፡፡ ከNTOው ገላጭ ሌላ አገሬውም ይግለጥልን፡፡ እኔን የመሩኝ ሰውዬ “ነዶና ሰው ተጣላ፤ አዝመራው እምቢ አለ” አሉኝ፡፡
ሌላ እንደኔ ገርሞህ ከሆነ ህፃናትና ሴቶች አላየንም (ውሻም አላየንም ብዬ ነበር) የህብረተሰቡ Pillar የሚባሉትን ሁለት አካላት ህፃንና እናት አላየንም፡፡ ለምሣሌ ዘሙቴ ማርያም ስሄድ ግብዳ ግብዳ ሻንጣችንን ጩጬ ጩጩ ልጆች ናቸው አንከብክበው ዳገት ቁልቁለቱን ፉት ያሉት! ምናልባት ማህል ሜዳ እሚባለውጋ ገብተን ባለመሆኑ ሊሆን ይችላል! ወንድ ይበዛል - ምናልባት ሴቶችና ልጆች እንዴት ነበር ልናገኝ እንችል የነበረው? ቆይ አዘጋጁን እጠይቀዋለሁ፡፡ ዕድሜያቸው ከፍ ያሉ ሽማግሌዎች በቅሎ መሳባቸው ገርሞኛል፡፡ እኔ በቅሎ ላይ ሆኜ ስጠይቃቸው ዞርም ቀናም ሳይሉ፣ ወግ ባይን ይገባል ሳይሉ፤ መልስ እየሰጡኝ ወደፊት ይገሰግሣሉ በቃ! ተፈጥሮን እኔ አደንቃለሁ፡፡ ለነሱ ተፈጥሮ ተፈጥሮ ነው በቃ! የኑስ የተባለው መንገድ ገላጫችን ያስረዳን የፀሐይ መውጣት መግባት ለነዚህ ሰዎች ጉዳይ አደለም፡፡ ስለ ኢሮብ ሰዎች ስለአዲግራት ሳወራቸው ነበር መኪና ውስጥ ሆነን፡፡ ኢሮቦች ምን ይላሉ መሰለህ “አናንተ ከደርግ ሸሽታችሁ ለመጠለልና ለመዋጋት ነው እዚህ የምትመጡት፡፡ እኛ ግን እንኖርበታለን፡፡ ኑሯችን ይሄው ነው!”
እዚህ አገር ጅቡ እንዳንተ አገር እንደ ሐረር ለትርዒት አይታይም፡፡ ጉልበተኛና ከመጣ የማይመለስ ነው አሉ! ጭላዳ ዝንጀሮ፣ ቅልጥም - ሰባሪ፣ ቀይ ቀበሮ እንደሚኖርበት ጅብም ጓሣኛ ሆኗል!
ማታ ካምፕ ፋየር አደረግን፡፡ ዘቡ መሣሪያ ይዘናል ሳይል ሽለላ ጀመረ፣ ዋሽንት ነፋ ጣሰው! ቅዝቃዜ መሸነፍ ጀመረ፡፡ ይህ ነገር ቢቀረፅ እንዴት አሪፍ ነበር፡፡ ቆጨኝና “እኛን ዓይነት ሰዎች አምጥታችሁ፣ በጥበብ የማርያም መንገድ ምንም ሊፈጠር እንደሚችል እያወቃችሁ፣ ምንም የዶክመንቴሽን ሥራ አለመሠራቱ በጣም ያሳዝናል፡፡
የመጀመሪያ ትምህርታችሁ ይሁን!” ብዬዋለሁ ለሀላፊው ለኤፍሬም (ኤፍሬም ከበቅሎ ቀድሞ ዳገት አፋፍ የሚወጣ፣ ቁልቁለት ወርዶ ቀድሞ ሜዳውን የሚረግጥ፤ ሰው ደከመኝ ብሎ ሲያርፍ እሱ ድንኳን ተከላና ሸከማ የሚጀምር፣ ቀጭን ትዕዛዝ በትህትና መስጠት የሚችል እንደ ኤስኪሞ ጀቦንቦን የለ ልብስ የለበሰ አምበሳ ኃላፊ ነው!)
ለላው ደግሞ ከአገሬው ጋራ መዋሃድ፣ ገብሱ ከየት እንደሚመጣ ማየት ነበረብን፡፡ እንደገጣሚ ይሰማኛል፡፡ ሰውን ስታውቅ ነው ተፈጥሮ ሙሉ የሚሆነው፤ አልኩኝ በልቤ፡፡ “ሎጁ ላይ ገለፃውን ሳናዳምጥ አቋርጠን መሄዳችን ቅር ብሎኛል” አለ አበባው፡፡ ልጁ፣ ገላጩ ዐረፍተነገሩን እንኳ ሳይጨርስ ነው መንገድ የጀመርነው፡፡ አሰቅቀነዋል - እኛም ሙሉ ሳንሆን ነው መንገድ የጀመርነው ማለት ነው፡፡ ዕውነት የሚመጣው የሰው ትንፋሽ ሲጨመርበት ነው - እኔ በዚህ አምናለሁ - አልኩት፡፡ ጆሮህ ቅላፄ ይናፍቃል - መፃፍ ማለት ያ ነውና! እኔ ቁጭት ነው ያለኝ!...Next time መምጣታችን አይቀርም ግን 1st Impression is last Impression የሚባለውን የሚያክል የለም! ገላጩ ልጅ እንደዛ ተገናኝተን ተዘጋጅቶ ካፉ የሚወጣውን ሳንሰማ ሄድን! ሰውየውን ከነቃናው ከነትንፋሹ ማግኘት ነበረብን፡፡ መግባባት ማለት ያ ነውና! የታሪክ ነጋሪውንም History የሚናገረውን በመንገድ ላይ ሙሉ ነገር አላገኘንም! በዚያም አንፃር ጐሎብናል! እንደወዳጅ ቀርበነው ማውጋት ነበረብን! ያ ጅምላውን ነገር ሙሉ አያደርገውም፡፡ እንደ ጋዜጠኛም እንደ Poetም ይመለከተኛል!…ገበሬው ጋ ችግር እንዳለ በቅሎ ሳቢው ነዶና ሰው ተጣላ ካሉኝ በኋላ የዘይት ዋጋ፣ የጨው ዋጋ የኢኮኖሚ ችግር እያልን ከተማ የምናወራውን From The Horses Mouth ከግብርናው ጌታ ሰማነው፡፡ ዕድገት አለ የለም ያኔ ትወስናለህ!
እንደተመክሮ ድንቅ ነገር ነው! ሪፖርት ሳይሆን ህይወት ሊኖረው ይገባል! ስሜቴን ልቀጥልልህ:-
ጣሰው ስለዋሽንት ቢነግረኝ በጣም ድንቅ ይሆናል! ጠባቂዎቹ እንደወታደር ጠባቂ ነን ብለው አልራቁንም - አብረውን ካምፕ ፋየር አደረጉ፡ የዕውነት ህዝባዊ ስትሆን ልባዊ - ህዝባዊ ነው የምትሆነው! መሣሪያውም፣ እኛም፣ ጠባቂዎቹም፣ ዋሽንቱም…እኩል እሳት የሚሞቅበት ነው ጉዋሣ! ህዝባዊነት፣ ቱሪስትነት፣ የአካባቢ ጥበቃና ጥበብ ሁሉም ማዕቀፋቸው እሳት ነው! እሳት ወይ አበባ እዚህም አለ፡፡ ለዚህ ነው በየፓርኩ ግጥም ይነበብ የሚለው ሃሳብ ትርጉም የሚኖረው! እንደማሳሰቢያ፤ ለአዘጋጆቹ ይህን እላለሁ:-
ቅድመ - ማስገንዘቢያ ቢኖር፡፡ ከከባዱ ወደ ቀላሉ ከመሄድ ለአፍቃሬ - ግጥሙ የፓኤቲክ ጃዝ ተከታታይ ከቀላሉ ወደ ውስብስቡ ቢኬድ (Law of dialectics)፡፡ ብቁ ዶክመንቴሽን (ምስለ - ዘገባ) ቢኖር፡፡ የማህበረሰቡ ተሳትፎ በቂ ቦታ ቢያገኝ፡፡ የማህበረሰቡ ክህሎት ተጠንቶ ከገጣሚያኑ ቢዋሃድ፡፡ ከተፈጥሮ ጋር መጣረርም ኅብር - መፍጠርም የጥበብ አካል መሆኑ ልብ ቢባል፡፡ የቴክኖሎጂ ግብዓት ከተፈጥሮው ሁኔታ ጋር መጣጣሙ ቢታሰብበት የተሻለ ታሪክ የመዘገብ አቅም ይኖረናል!


         በድሮ ጊዜ አንድ አንቱ የተባሉ አገረ ገዢ በየክፍለ ሀገሩ እየተዘዋወሩ ህዝቡን እየሰበሰቡ ያነጋግሩ ነበር ይባላል፡፡ አብረዋቸው አዋጅ ገላጮች ነበሩ፡፡ አዋጅ ገላጮቹ በታወጁ አዋጆች ላይ ጥያቄ ቢነሳ የሚያብራሩ የሚገልጡ ናቸው፡፡
ህዝብ ከተሰባሰበ በኋላ፣ ባለሟሉ ይነሳና
“የአገራችን ህዝብ ሆይ! አገረ ገዢው እዚህ ድረስ የመጡት የእናንተን ማናቸውም ብሶት ሊያዳምጡ ነውና ጥያቄያችሁን አቅርቡ” ይላል፡፡
አንዱ ባላገር ይነሳል፡-
“ጌታዬ የግጦሽ መሬት አንሶናል” ይላል
አገረ ገዢው ወደ ፀሐፊው ዞረው
“ይመዝገብ፡፡ እናስብበታለን”
ሌላ ባላገር ይነሳል፤
“ማዳበሪያ ይሰጣችኋል ተብለን እስከዛሬ አልመጣልንም!”
አገረ ገዢው - “ይመዝገብ፡፡ እናስብበታለን”
ሌላ ባላገር ይነሳል - “የዘር  እህል ይታደላል ተብለን ዛሬም አልተሰጠንም”
አገረ - ገዢው - “ይመዝገብ፡፡ እናስብበታለን”
ሌላ ባላገር በንዴት
“ጌታዬ! ባለፈውም እንዲሁ እናስብበታለን ሲሉ ነበር፡፡ መቼ ነው በተግባር የሚፈፀምልን? ሁሌ እናስብበታለን ነው እንዴ?”
አገረ - ገዢው - “ይሄም ይመዝገብ፡፡ እናስብበታለን!”
ይሄ በጣም ያናደደው አንድ የጎበዝ - አለቃ አገሬውን በመወከል ይናገራል፡፡
“ጌታዬ ሆይ! በእኛ ላይ የደረሰውን በደል የሚያህል የትም አገር አይገኝም! ፍትህ ሲጠፋ አቤት የምንልበት ቦታ የለም! ጤና ሲጠፋ የምንታከምበት ቦታ የለም! ትምርት ሲጠፋ የምን ማርበት ቦታ የለም፡፡ መንገዱ ሲጠፋ አሳብረን የምንሄድበት አቋራጭ እንኳን የለም፡፡ እህል ሲጠፋ አንጀታችንን የምንጠግንበት፣ ውሃ ጥም ስንቃጠል ጥማችንን የምንቆርጥበት ምንም መፍትሄ የለንም! አሁን እናንተ እያስተዳደርን አገር እየመራን ነው ትላላችሁ? እኛ ህዝቡን ማስነሳትኮ አላጣንበትም! እናንተም ደግ ደጉን አርጋችሁልን፣ እኛም ደግ ደጉን አስበንላችሁ ብንኖር አይሻልም?” አለ፡፡
አገሬው አጨበጨበ!
አገረ ገዥውም፤
“የአገሬ ህዝብ ሆይ!
ይሄ የጎበዝ አለቃ ጥሩ ይናገራል ግን ዕድሜ የለውም! አሉ
አገሬው አሁንም አጨበጨበ!
ያ ጎበዝ - አለቃም ከዚያን ቀን በኋላ አልታየም፡፡”
ሁል ጊዜ “እናስብበታለን” አያዋጣም፡፡ አፈፃፀም ያስፈልጋል፡፡ በዘመንኛው ቋንቋ ቢሮክራሲያዊ ማነቆ (Bureaucratic red - tape) መበጠስ አለበት እንደ ማለት ነው፡፡ ጥንት ንጉሡ የወሰኑትን አስፈፃሚዎቹ ባለሟሎች “እሺ” “እሺ” እያሉ በተግባር ግን አንዷንም ነገር አያውሉም ነበር ይባላል፡፡ ይሄ ክፉኛ ያቆሰለው በደለኛ ንጉሡ ዘንድ ይቀርብና፤
“ጃንሆይ! ሁሉም ነገር ይቅርብኝና አንድ ሃያ አጋሠሥ ይሰጠኝ” ሲል አቤት ይላል፡፡
ጃንሆይም “ለምንህ ነው?” ቢሉት፣
“የሸዋን መኳንንት ‹እሺታ› የምጭንበት”፣ አለ ይባላል፡፡ ውሳኔዎች፣ መመሪያዎች፣ አዋጆች፣ ወዘተ በሥራ ላይ ካልዋሉ፣ ካለንበት ንቅንቅ አንልም፡፡ ጌቶች ቢያስነጥሱ መሀረብ የሚያቀብሉ ዓይነት ሰዎች መቼም፣ የትም ድረስ አያራምዱንም! ጉዳያችሁን ተናገሩ፡፡ ብሶታችሁን አውጡ፡፡ ጥያቄያችሁን አቅርቡ፤ ብሎ ‹እድሜህ አጭር ነው› ከሚል ይሰውረን፡፡ ለአጥቂውም ለተጠቂውም ከሚያጨበጭብ ተሰብሳቢም ይሰውረን፡፡
ያልተመለሰ ጥያቄ ያልተከፈለ ዕዳ ነው፡፡ ነገ ዋጋ ያስከፍለናል፡፡ ዛሬ አድበስብሰን የምናልፈው ጥያቄ የነግ የቂም ቋጠሮ ይሆንብናል፡፡ ያ ደግሞ ዕድገትን ተብትቦ ያሰናክለዋል፡፡ የበላይ ወደታች የሚመራውን የበታች እንደ “ኮምፒዩተር ጌም” ሲጫወትበት የሚውል ከሆነ፤ እንኳን ትራንስፎርሜሽን መደበኛውም ዕድገት አይገኝም፡፡ “ሩቅ አሳቢ ቅርብ አዳሪ” መሆን የሚመጣው ለትልቁ ስዕል አስተዋፅኦ የሚያደርጉት ትናንሽ ስዕሎች በቅጡ ካልተሳሉና ሥጋና ደም ሳይለብሱ የቀሩ እንደሆነ ነው፡፡ የበታች አካላት ማያያዣ ክር ናቸው፡፡ እነሱ ከተበጣጠሱ የበላይ አካላት የሉም፡፡ ይሄ በቢሮክራሲያዊው ዓለም ብቻ ሳይሆን በፖለቲካ ፓርቲዎችም ዘንድ ያው ነው፡፡ ትናንሽ ስህተቶች ለግዙፍ ስህተት አሳልፈው ይሰጡናል፡፡ ያኔ ውድቀት ቅርብ ይሆናል፡፡
ሱን ሱ የተባለ የቻይና ጦር መሪ “በጦርነት ድል ማድረግ የሚደጋገም ነገር አይደለም፡፡ ሁሉ ቅርፁን ይለውጣል፣ ውሃ ሁሌም አንድ አይነት ቅርፅ የለውም - እንደመያዣው ዕቃ ይለዋወጣል፡፡ እንደባላንጣህ አካሄድ ቅርፅህን እየለዋወጥክ ድል መቀዳጀት ረቂቅ - ሊቅ (genius) ይባላል” ይለናል፡፡ ስለ ህይወት፣ ስለማናቸውም ትግል፣ ስለ ምርጫ፣ ስለለውጥ ስናስብ ሁሌም እንደሁኔታው  አካሄድን ቀይሮ በብስለት መጓዝን አንርሳ፡፡  ረቂቅ - ሊቅ የመሆን ጥበብ ይሄ ነው፡፡ በሌሎች ድክመት ላይ ከመንተራስ በራስ መተማመን ብልህነት ነው! አንዴ የሆነው ነገር ላይ ከማላዘን ይልቅ ሁኔታዎችን በሌላ አቅጣጫ ለመለወጥ (Reversal) መሞከር አዲስ ቅያስ ለማየት ይጠቅመናል፡፡ ሳይታለም የተፈታን ጉዳይ (de facto) ደግመን ደጋግመን መወትወት ያው ውሃ ወቀጣ ነው፡፡ የተሰረቀው ተሰርቋል፡፡ የተሄደው ድረስ ተሄዷል፡፡ የባላንጣችን አቅም ታውቋል፡፡ ዘዴና መላው በተደጋጋሚ ታይቷል፡፡ ስለዚህ የታወቀን መንገድ ትቶ ያልተሄደበትን መንገድ ወይም ብዙ ያልተሄደበትን መንገድ (The Road Less Travelled) ማሰብና ማስላት ይሻላል፡፡ የሆነውማ ሆኗል - “ለሰጠውም አላሳነሰው፣ ላልሰጠውም አላቀመሰው!”  

ፈቃድ ለማግኘት ከ1ሚ. ብር በላይ ካፒታልና 2 ሚ. ብር ዝግ ሂሳብ ያስፈልጋል
ኤጀንሲዎች ከተጓዥ ክፍያ ሊጠይቁ አይችሉም፡፡ 8ኛ ክፍል ያላጠናቀቀና የሙያ ማረጋገጫ የሌለው መሄድ አይችልም፡፡
ባለፉት 7 ወራት 50ሺ ኢትዮጵያውያን በህገ ወጥ ጉዞ የመን ገብተዋል፡፡

ወደ አረብ አገራት የሚሄዱ ሰራተኞች ላይ የሚደርሰውን ችግርና እንግልት ለማስቀረት በሚል ከአንድ ዓመት በላይ ተቋርጦ የቆየውን አሰራር ለማስጀመርና ለመቆጣጠር የተዘጋጀው ረቂቅ አዋጅ ውዝግብ አስነሳ፡፡
በሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የቀረበው ረቂቅ አዋጅ ወደ ውጭ አገር ሰራተኞችን የሚልኩ ኤጀንሲዎች፣ የግለሰብ ድርጅት ከሆነ አንድ ሚሊዮን ብር የሽርክና ማህበር ከሆነ ደግሞ አምስት ሚሊዮን ብር ካፒታል ሊኖረው ይገባል ይላል፡፡ ኤጀንሲው ለሰራተኛው መብትና ደህንነት ዋስትና ማስከበሪያ የሚውል 100 ሺህ ዶላር (ከሁለት ሚሊዮን ብር በላይ) በዝግ ሂሳብ የማስቀመጥ ግዴታ አለበት፡፡
 ኤጀንሲዎች ለስራ ወደ ውጭ አገር የላኳቸውን ሰራተኞች ለኢትዮጵያ ኤምባሲ በ15 ቀን ውስጥ ማስመዝገብና የስራ ፈቃድ ማግኘታቸውን የሚያረጋግጥ መረጃ ለሚኒስቴሩ ማቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡ ኤጀንሲዎች ለሚሰጡት አገልግሎት ምንም ዓይነት ክፍያን መጠየቅ አይችሉም፡፡ ረቂቅ አዋጁ በውጭ አገር ስራ ለመሰማራት የሚፈልጉ ዜጎችን ዕድል የሚያጠብና ህገ ወጥነትን የሚያባብስ ነው ሉ በውይይቱ ላይ ተሳታፊ የነበሩ ሰዎች ተናግረዋል፡፡ ኤጀንሲዎች በስራው ለመሰማራት የሚያስችሏቸውን መስፈርቶች በሙሉ አሟልተው ለመቅረብ በእጅጉ እንደሚቸገሩና ረቂቅ አዋጁ መሻሻልና መታረም እንደሚገባውም ተናግረዋል፡፡ የአረብ አገራት ጉዞ በመንግስት ከታገደ ወዲህ ባሉት ሰባት ወራት 50 ሺህ የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን የመን መግባታቸውንና ባለፈው ጥቅምት ወር ብቻ በህገወጥ መንገድ የመን የገቡ ኢትዮጵያውያን ቁጥር ስምንት ሺህ መድረሱን የተባበሩት መንግስታት ሪፖርት አመልክቷል፡፡


      በአፍሪካ፣ ወደ ግጭት ቀጣናዎች እየተሰማራ በስነ-ምግባርና በሙያ ብቃት ስምካተረፉት መካከል የኢትዮጵያ መካከል ሃይል አንዱ እንደሆነ የገለፀው ዘኢኮኖሚስት መጽሔት፤ ኢትዮጵያና ሩዋንዳ በሰላም አስከባሪነት ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ዘገበ፡፡
ቀደም ሲል ለሰላም አስከባሪነት የአውሮፓ ወታደሮች ሲሰማሩ እንደነበር መጽሔቱ አስታውሶ፤ ከ20 አመታት ወዲህ ግን በርካታ የአፍሪካ አገራት የአህጉራቱን ግጭቶች ለማብረድ የሰላም አስከባሪነት ስራዎችን እየተረከቡ ነው ብሏል፡፡
በተለይ ኢትዮጵያ እና ሩዋንዳ፤ እምነት የሚጣልባቸው ሰላም አስከባሪ ሃይል በማሰማራት መልካም ስም እንዳተረፉ መጽሔቱ ገልጿል፡፡
በርካታ ሺ ወታደሮችንና ቁሳቁሶችን፣ ለሰላም ተልዕኮ እንዲያሰማሩ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኩል በተደጋጋሚ የሚመረጡት ኢትዮጵያና ሩዋንዳ፤ ለሚያሰማሩት ጦር የስልጠና እና የጦር መሳሪያ ወጪያቸው በተመድ እንደሚሸፈንላቸው ዘኢኮኖሚስት ገልፆ፤ ይህም የመከላከያ ሃይላቸውን ይበልጥ ዘመናዊ ለማድረግ ያግዛቸዋል ብሏል፡፡
በዚህም በተጨማሪ ብዙዎቹ የአፍሪካ አገራት በራሳቸው ወጪ ለጦር መሳሪያ ገዢ የሚያውሉት ገንዘብ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል፡፡
የአንጐላ መንግስት ባለፈው አመት የመከላከያ በጀቱን ከ4.5 ቢሊዮን ዶላር ወደ 6 ቢ ዶላር (ወደ 120 ቢሊዮን ብር ገደማ) እንዳሳደገ መጽሔቱ ጠቅሶ፣ የናይጀሪያ መንግስትም ለአዳዲስ የጦር አውሮፕላኖች ግዢ አንድ ቢሊዮን ዶላር መመደቡን ዘግቧል፡፡
ከፍተኛ ገንዘብ ለጦር ሃይል በመመደብ በአፍሪካ ቀዳሚነቱን የያዘችው አልጀሪያየ በአመት 10 ቢ ዶላር ታወጣለች ብሏል - ዘገባው፡፡
የዛሬ 25 አመት ገደማ ሶቪዬት ህብረት የምትመራው የሶሻሊዝም አምባገነንነት ሲፈራርስ፣ በአፍሪካም በርካታ መንግስታት ከስልጣን እንደተወገዱና አንዳንዶቹም የተቃውሞ ፓርቲዎች እንዲንቀሳቀሱ የሚፈቅድ ማሻሻያ ለማድረግ እንደተገደዱ የሚታወስ ሲሆን፣ የነፃ ገበያ እና የዲሞክራሲ ስርዓት ጅምር ማሻሻያ ላይ በማተኮር ለመከላከያ ሃይል የሚያወጡት በጀት ለ15 አመታት ሳይጨምር እንደቆየ መጽሔቱ ያመለክታል፡፡
ባለፉት አስር ዓመታት ግን፣ የሃይማኖት አክራሪነትና የሽብር አደጋ፣ በዘር የሚቧደኑ ታጣቂዎችና ቡድኖች ግጭት፣ እንዲሁም የባህር ላይ ውንብድና ከፍተኛ ስጋት የሆነባቸው የአፍሪካ መንግስታት ለመከላከያ ሃይል ከፍተኛ ገንዘብ መመደብ ጀምረዋል፡፡
በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር የነበሩት ዴቪድ ሺን ለመጽሔቱ በሰጡት ገለፃ፣ አንዳንድ የአፍሪካ መንግስታት ጉድ የሚያሰኙ የጦር መሳሪያዎች እየገዙ ነው ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ T-72 የተሰኙ ዘመናዊ ታንኮችን ከዩክሬን ማስገባት ጀምራለች፡፡ ደቡብ ሱዳን ደግሞ መቶ ታንኮችን፡፡
ሰፊ የባህር በር ያላቸው እንደ ካሜሩን እና ሞዛንቢክ፣ ሴኔጋልና ታንዛኒያ የመሳሰሉ አገራት የባህር ሃይላቸውን በጦር መሳሪያ እያፈረጠሙ መሆናቸውን ዘኢኮኖሚክስ ጠቅሶ፣ አንጐላ ደግሞ የጦር አውሮፕላኖችን የሚሸከም ተዋጊ መርከብ ለመግዛት የጀመረችው ድርድር አስገራሚ መሆኑን ጠቁሟል፡፡
የአፍሪካ አገራት ጦር፣ በስልጠናና በመሳሪያ ይበልጥ “ፕሮፌሽናል” ለመሆን እየተሻሻሉ መጥተዋል የሚለው ዘኢኮኖሚስት፣ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገባቸው ለመከላከያ ሃይል ደህና ገንዘብ እንዲመድቡ ከማስቻሉም በተጨማሪ እንደ ኢትዮጵያና ሩዋንዳ ደግሞ በሰላም አስከባሪ ሃይል ተልእኮ አማካኝነት የማይናቅ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ገልጿል፡፡
እንዲያም ሆኖ የጦር መሳሪያ ግዢ በሁሉም አገራት ውጤታማ ሆኗል ማለት አይደለም፡፡ ኮንጐ ብራዛቪል ፈረንሳይ ሰራሽ ሚራዥ የጦር አውሮፕላኖችን ብትሸምትም፣ በብሔራዊ በዓላት የበረራ ትርዕት ከማሳየትና የበዓል ማድመቂያ ከመሆን ያለፈ ጥቅም አላስገኙም፡፡ ደቡብ አፍሪካም ከስዊድን 26 ተዋጊ አውሮፕላኖች ከገዛች በኋላ፣ በበጀት እጥረት ግማሾቹ ከአገልግሎት ውጭ የጋራዥ ሰለባ ሆነዋል፡፡
SU 30 አውሮፕላኖችን ከራሺያ የገዛችው ኡጋንዳ ደግሞ፤ ተስማሚ ሚሳይሎችን ስላልገዛች ዘመናዊዎቹን አውሮፕላኖች በአግባቡ ልትጠቀምባቸው አልቻለችም ብሏል መጽሔቱ፡፡   

ለአመት ያህል በበርሜር ወደ 110 ዶላር ንሮ የቆየው የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ፤ ካለፈው ሐምሌ ወዲህ እየወረደ በያዝነው ሳምንት ከ75 ዶላር በታች የደረሰ ሲሆን፤ የኢትዮጵያ የነዳጅ ዋጋ ላይ መንግስት እስካሁን ቅናሽ አላደረገም።
በአመት በአማካይ ከሰባት በመቶ በላይ እየጨመረ የመጣው የኢትዮጵያ የነዳጅ ፍጆታ፣ ባለፈው አመት 3.4 ቢሊዮን ዶላር (ከ65 ቢሊዮን ብር በላይ) ወጪ እንዳስከተለ ታውቋል። ሸቀጦች ወደ ተለያዩ አገራት በመላክ የሚገኘው የውጭ ምንዛሬ ባለፉት አራት አመታት እድገት ባለማሳየቱ አመታዊው ገቢ ከሶስት ቢሊዮን ዶላር ገደማ ብዙም ፈቅ ባለማለቱ፣ የነዳጅ ግዢን እንኳ ለመሸፈን የማይበቃ ሆኗል።
በአለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ ባለፈው አመት በነበረበት ቢቀጥል ኖሮ፣ በቀጣዩ አመት ኢትዮጵያ ሩብ ቢሊዮን ዶላር (5 ቢሊዮን ብር) ተጨማሪ ገንዘብ ለነዳጅ ግዢ ለማውጣት መገደዷ አይቀርም ነበር። ይሁን እንጂ፣ ያለማቋረጥ እየወረደ የመጣው የነዳጅ አለማቀፍ ዋጋ በስድስት ወራት ውስጥ ሲሶ ያህል ስለቀነሰ፣ ኢትዮጵያ ለነዳጅ ግዢ የምታውለው የውጭ ምንዛሬ ዘንድሮ እንደማያሻቅብ ተገምቷል።
 እንዲያውም የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በበርሜል ከ80 ዶላር በታች ሆኖ ከቀጠለ፣ የአንድ ቢሊዮን ዶላር (የ20 ቢሊዮን ብር ወጪ ቅናሽ ያስገኛል፡፡) በርካታ ነዳጅ አምራች አገራትን የሚቆጣጠሩ መንግስታት በአባልነት የተካተቱበት ኦፔክ የተሰኘው ማህበር፣ ሰሞኑን በነዳጅ ዋጋ ዙሪያ የተወያየ ቢሆንም፣ ውይይታቸው በአለም የነዳጅ ዋጋ ላይ ለውጥ እንደማያስከትል ትናንት ቢቢሲ ዘግቧል። እየወረደ የመጣው የነዳጅ ዋጋ፣ የበርካታዎቹን መንግስታት ገቢ እንደሸረሸረ የገለፀው ቢቢሲ፣ ከፍተኛ የበጀት ጉድለት ያጋጥማቸዋል ብሏል። “ዋጋ እንዲያንሰራራ የነዳጅ ምርት መቀነስ አለብን” የሚል ጥያቄ ከሁለት መንግስታት በኩል እንደቀረበ ዘገባው ጠቅሶ፣ ጥያቄው በአብዛኞቹ መንግስታት ተቀባይነት ሳያገኝ መቅረቱን አመልክቷል።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የነዳጅ ዋጋ መውረድ የጀመረው፣ በከፊል ከአለም ኢኮኖሚ መቀዛቀዝ ጋር በተያያዘ ምክንያት ቢሆንም፣ ዋናው ምክንያት ግን የአሜሪካ ኩባንያዎች ከፍተኛ የነዳጅ ምርትን የሚያስገኝ አዲስ ዘዴ በመፍጠራቸውና ተጨማሪ ነዳጅ ማምረት በመጀመራቸው እንደሆነ ፎርብስ መፅሔት ዘግቧል።
ከአለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ ውጣ ውረድ ጋር፣ የኢትዮጵያ መንግስት በንግድ ሚኒስቴር በኩል በየወሩ የነዳጅ ዋጋ ተመን የሚያወጣ ሲሆን፣ ከጥቂት ጊዜያት በስተቀር አብዛኛውን ጊዜ የዋጋ ተመኑ በነበረበት እንዲቀጥል አልያም የአለም ገበያን ተከትሎ እንዲጨምር ሲወስን መቆየቱ ይታወሳል።
ባለፉት ስድስት ወራትም እንዲሁ፣ በአለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ በፍጥነት እየወረደ ቢመጣም፣ በኢትዮጵያ ግን የችርቻሮ ዋጋ በነበረበት ደረጃ እንዲቀጥል አልያም እንዲጨምር የተደረገ ሲሆን፣ በያዝነው ወር መጨረሻ የዋጋ ተመኑ ላይ ምን አይነት ለውጥ እንደሚደረግበት ገና አልታወቀም። በተለመደው የመንግስት አሰራር፣ የዋጋ ተመን ውሳኔው በይፋ እስከሚገለፅበት እለትና ሰዓት ድረስ በሚስጥር ተጠብቆ ነው የሚቆየው።

          14ኛው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ነገ 40ሺ ተወዳዳሪዎችን በማሳተፍ ይካሄዳል፡፡ የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫውን ከማካሄዱ በፊት ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ሰሞኑን ውድድሩን ያጀቡ የተለያዩ ዝግጅቶች ነበሩት፡፡ የመጀመርያው ባለፈው ረቡዕ በኤግዚብሽን ማእከል የተከፈተው የስፖርት ኤክስፖ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በአፍሪካ ለመጀመርያ ጊዜ የዓለም የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ስራ አስኪያጅ ኮሚቴ ስብሰባም ተስተናግዷል፡፡ የዓለም የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር የስራ አስኪያጅ ኮሚቴ ስብሰባ ትናንት እና ከትናንት በስቲያ በቀነኒሳ ሆቴል ተካሂዷል፡፡ መስተንግዶውን ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከታዋቂው የአትሌቲክስ ስፖርት ፎቶግራፈር ዢሮ ሚሹዙኪ፤ ከቀነኒሳ በቀለ እና ከአትሌቲክስ ፌደሬሽን ጋር በመተባበር አከናውነዋል፡፡ በስብሰባው ላይ ለመገኘት ወደ ኢትዮጵያ የመጡት  ከ10 የተለያዩ አገራት የተውጣጡ 29 የስፖርት ባለሙያዎች ናቸው፡፡ ከመካከላቸው ከኦስትሪያ ፤ከዩክሬን፤ ከሮማንያ ፤ከፈረንሳይ፤ ከደቡብ ኮርያ፤ ከጃፓን፤ ከእንግሊዝ ከጣሊያን ከኬንያ እና ሌሎች የዓለም ክፍሎች የመጡ ባለሙያዎች ይገኙበታል፡፡

ባለፈው ረቡእ በቀነኒሳ በቀለ ሆቴል በተዘጋጀላቸው የእራት ግብዣ ላይ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ መስራች እና ሊቀመንበር ኃይሌ ገብረስላሴ ባሰማው ንግግር አትሌቲክስ ስፖርት ኢትዮጵያን ለዓለም ለማስተዋወቅ ሁነኛ አማራጭ እንደሆነ ትተዘባላችሁ ሲል ተናግሯል፡፡ በዚሁ የእራት ግብዣ ላይ የኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ለእንግዶቹ የአገር ልብስ ስጦታ ያቀረበ ሲሆን የአትሌቲክስ ፌደሬሽን ተወካዮች በበኩላቸው ኢትዮጵያ በስፖርቱ የ65 ዓመታት ታሪክ ማሳለፏን ጠቅሰው የታላላቅ አትሌቶች መገኛ በሆነች አገር ለምታዘጋጅቱ ትልቅ ውድድራችሁ እናመሰግናለን በማለት ለታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ድጋፍ ሰጥተዋል፡፡
14ኛው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዛሬ በጃንሜዳ አካባቢ እስከ 4ሺ ህፃናትን በማሳተፍ በሚካሄደው ከ500 ሜትር እስከ 2000 ሜትር ውድድር ነው፡፡ ነገ ጠዋት በጃንሜዳ አካባቢ ውድድሩን የሚያስጀምሩት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ የተከበሩ አባዱላ ገመዳ ሲሆኑ የእለቱ የክብር እንግዶች እንግሊዛዊው የትራያትሎን አትሌት አሊስተር ብራውንና ኬንያዊቷ ማራቶኒስት ኤድና ኪፕላጋት አብረዋቸው ይኖራሉ፡፡ በዋናው የአትሌቶች ውድድር 40 ክለቦችን የወከሉ ከ600 በላይ አትሌቶች የሚፎካከሩ ሲሆን ፤ ለአንደኛ 40ሺ ለሁለተኛ 25 ሺ እንዲሁም ለሶስተኛ 12ሺ 500 ብር በሁለቱምፆታዎች በሽልማት ይበረከታል፡፡  ከ15 አገራት የመጡ 300 ስፖርተኞች ከ40ሺው ስፖርተኛ መካከል ሲገኙበት የ13 አገራት አምባሳደራት በኢትዮጵያን ኤርላይንስ አዋርድ ለማሸነፍ ይሽቀዳደማሉ፡፡ትናንት በሂልተን ሆቴል በተሰጠው መግለጫ ላይ  በ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው በጋራ እየሮጥን በጋራ እንደሰት በማለት መልዕክት ያስተላለፈው ኃይሌ ገብረስላሴ፤ የውድድሩ እድገት ገና ይቀጥላል ብሏል፡፡ የክብር እንግዶች ከሆኑት አንዷ ኬንያዊቷ ኤድና ኪፕላጋት ኃይሌን ከ16 ዓመቷ ጀምራ እንደምታውቀው ገልፃ በምታደንቀው አትሌት የተዘጋጀ ውድድርን ለማስጀመር መጋበዟ ታላቅ ክብር ነው ብላለች፡፡ ኤድና ኪፕላጋት ከ12 በላይ ማራቶኖችን ያሸነፈች አትሌት ስትሆን  በሀለት የዓለም ሻምፒዮናዎች በማራቶን አከታትላ በማሸነፍ ሁለት የወር ሜዳልያዎች የተጎናፀፈች እና ዘንድሮ የለንደን ማራቶንን ለማሸነፍ የበቃች ናት፡፡ በሌላ በኩል ሌላው የክብር እንግዳ በለንደን ኦሎምፒክ በትራይትሎን ስፖርት የወርቅ ሜዳልያ ያገኘው አሊስተር ብራውንሊ በውድድሩ ለመሳተፍ መጓጓቱን ይናገራል፡፡ ትራያተሎን 500 ሜትር በዋና፤ 40 ኪሎሜትር በብስክሌት ግልቢያ እንዲሁም 10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫን በማካተት የሚካሄድ ስፖርት ነው፡፡ ለታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያን በአጋርነት ሲደግፉ ከቆዩት አንዱ የሆነው የእንግሊዙ ኖቫ ኢንተርናሽናል ዲያሬክተር ዴቪድ ሊንግተን ውድድሩ ባለው ማራኪ ድባብ ከዓለማችን ምርጡ ነው ካሉ በኋላ የውድድር ተቋማቸው በመላው እንግሊዝ ካካሄዳቸው ውድድሮች አሸናፊዎቹን ይዞ በመምጣት ዘንድሮ ተሳትፎ እንደሚያደርግ ገልጿል፡፡ ኖቫ ኢንተርናሽናል አስከ 1 ሚሊዮን ተሳታፊዎች ያገኙ ውድድሮችን በማዘጋጀት በመላው ብሪታኒያ የሚንቀሳቀስ ነው፡፡ በሌላ በኩልየኢትዮጵያ ቱሪዝም ኦርጋናይዜሽን ዲያሬክተር አቶ ሰለሞን ታደሰ የሩጫ ውድድሩ የቱሪዝም እንቅስቃሴን የሚያቀላጥፍ ብለው ሲያደንቁ፤ የውድድሩ ስፖንሰር የሆነው የኢትዮጵዩ ንግድ ባንክ ሃላፊ አቶ ኤፍሬም መኩርያ የኢትዮጵያ ትልቁ ባንክ የአፍሪካን ታላቅ ውድድር ስፖንሰር በማድረጉ ደስተኛ ነው ብለዋል፡፡

ጣሊያናዊው ጂያኔ ሜርሎ የዓለም የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር (AIPS) የወቅቱ ፕሬዝዳንት ናቸው፡፡ በታዋቂው የጣሊያን የስፖርት ሚዲያ ላ ጋዜታ ዴሎ ስፖርት ላይ በተለይ የአትሌቲክስ ስፖርት ዘጋቢ ሆነው ሲሰሩ 10 ኦሎምፒኮችን በቀጥታ በመዘገብ ከፍተኛ ልምድ ያካበቱ ባለሙያ ናቸው፡፡ ከስፖርት አድማስ የሚከተለውን አጭር ቃለምልልስ አድርገዋል፡፡
በኢትዮጵያ መሰብሰባችሁ  ምን ጥቅም አለው?
በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በአፍሪካ የመጀመርያው ስብሰባችን ማድረጋችን ወደፊት ብዙ እድሎችን ይፈጥራል፡፡ እያገኘን ያለው መልካም መስተንግዶ ደግሞ ወደፊትም ሌሎች ዓለም አቀፍ ስብሰባዎች እና ዝግጅቶችን ለማካሄድ የሚያነሳሳን ይሆናል፡፡ ከምናገኘው ልምድ ተነስተን ብዙ ተግባራት የምናከናውን ይመስለኛል፡፡ እኔ ወደ ኢትዮጵያ ስመጣ ለ3ኛ ጊዜ ቢሆንም ሌሎቹ የዓለም የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ስራ አስኪያጅ ኮሚቴ አባላት ግን የመጀመርያቸው ነው፡፡ በቆይታቸው የሚኖራቸውን ልምድ በመንተራስ ብዙ የጉብኝት እድሎችን ለኢትዮጵያ የሚፈጠሩ ይመስለኛል፡፡ ኢትዮጵያ በአትሌቲክስ ስፖርት ታላላቅ አትሌቶችን በማፍራት በመላው ዓለም ገንናለች፡፡  ይህ ስኬት  ደግሞ በዓለም ስፖርት ጋዜጠኞች ትኩረት ውስጥ አስገብቷታል፡፡ በአትሌቶቻችሁ ስኬት ነው  ወደ ኢትዮጵያ ብሎም ወደ አፍሪካ ለመጀመርያ ጊዜ በመምጣት የዓለም አቀፍ ማህበራችንን የስራ አስኪያጅ ኮሚቴ ስብሰባ ለማድረግ የበቃነው፡፡ ኃይሌና ቀነኒሳ እንዲሁም ሌሎች የኢትዮጵያ አትሌቶች ምስጋና ይገባቸዋል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ደጋግመን እንመጣለን፡፡
ስብሰባችሁ የሚያተኩርባቸው አጀንዳዎች ምንድናቸው ?
ዓለም አቀፉ ማህበራችን ከተመሰረተ 90ኛ ዓመቱን ዘንድሮ ያስቆጥራል፡፡ በስብሰባችን ይህን እናስባለን፡፡ በዋናነት የያዝናቸው አጀንዳዎች ግን በስፖርት ሚዲያው አሰራር ላይ ያተኩራሉ፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ እየተፈጠሩ ያሉ መሰናክሎች እና ችግሮችን በዝርዝር በመመልከት የመፍትሄ ሃሳቦችን እያቀረብን ውይይት እናደርጋለን፡፡ የስፖርት ሚዲያዎች በነፃነት መስራት የሚችሉባቸውን ሁኔታዎች እንዳስሳለን፡፡ በመረጃ ምንጮቻቸው የስፖርት ሚዲያዎች ማድረግ የሚገባቸውን ከለላ  የሚያጠናክሩባቸውን አቋሞች ለመቅረፅ እናስባለን፡፡ በሌላ በኩል አዲስ በጀመርነው እና ተተኪ የስፖርት ሚዲያ ትውልዶችን ለመፍጠር ያግዘናል ያልነው የወጣት ስፖርት ጋዜጠኞች የማስተር ስልጠና ፕሮግራም አወቃቀር ዙርያ ያሉ ጅምር ተግባራትን እንገመግማለን፡፡
የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ውድድርን ማህበራችሁ እንዴት ይመለከተዋል?
ካለኝ ልምድ በመነሳት የምናገረው ውድድሩ ዓለም አቀፍ ደረጃ እንዳለው ነው፡፡ የአትሌቲክስ ስፖርት ባህል በሁሉም ኢትዮጵያዊ የእለት እለት ህይወት እንዲቆራኝ ያደረገ ነው፡፡ የሙያ ባልደረቦቼ ከስብሰባው ጎን ለጎን የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ውድድርን ለመከታተል እቅድ አላቸው፡፡ ውድድሩን በጥልቀት ገምግመው ወደየአገሮቻቸው ሲመለሱ በርካታ የዘገባ ሽፋን ይሰጡታል፡፡ ይህ ደግሞ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያን ዝና እያሳደገ ይቀጥላል፡፡ በውድድሩ አገሪቱ እያገኘች ያለው ትኩረት ሌላው ስኬት ይመስለኛል፡፡
ስለ አበበ ቢቂላ ሲናገሩ ሰምቻለሁ፤  ከኢትዮጵያ አትሌቶች ጋር እንዴት ተዋወቁ?
በ1960 እኤአ ላይ በሮም ኦሎምፒክ ላይ ገና 13 ዓመቴ ብቻ ነበር፡፡ አበበ ቢቂላ የማራቶን ውድድር ሲያሸንፍ ተመለከትኩ፡፡ በጣም ለህይወቴ አስፈላጊውን መነቃቃት ነበር ያገኘሁት፡፡በአትሌቲክስ ስፖርተኛነት ቆርጬ የተነሳሁበት ታሪክም ሆነ፡፡  አፍሪካዊያን ሯጮች በዓለም የስፖርት መድረክ ያን ያህል ጥንካሬ አልነበራቸውም፡፡ በአበበ ቢቂላ ብቃት ግን ብዙ ተነሳሱ፡፡ እኔ በዚህ ታላቅ ኢትዮጵያዊ አትሌት  ተማርኬ  ከስፖርቱ ጋር በፍቅር ወደቅኩ፡፡ ጀግንነቱም በተተኪ የኢትዮጵያ አትሌቶች ሲደጋገም ለማየት ስታደል ደግሞ ተደሰትኩ፡፡ ከአበበ ቢቂላ በኋላ ምሩፅ ይፍጠር እና መሃመድ ከድርንም ለማወቅ ችያለሁ፡፡ በ80ዎቹ በሚላኖ ከተማ ውስጥ ከሃምሳ ሺ በላይ ስፖርተኞችን የሚያሳትፍ ውድድር ላይ ተሳትፈው ስለነበር ነው፡፡ ከእነሱ በኋላ እኔም ወደ ስፖርት ጋዜጠኝነቱ ስገባ እነ ኃይሌን ተዋወቅኩ፡፡ ከዚያም ቀነኒሳንም ጥሩነሽንም በደንብ የማውቃቸው እና የምከታተላቸው  ሆኜ አሳልፍያለሁ፡፡
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ለምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች በረጅም ርቀት የአትሌቲክስ ውድድሮች መወዳደርያዎች ጠፍተዋል፡፡ በውጤታማነት ከሌሎች የዓለም አገራት ልቀው መሄዳቸው ምክንያት ይመስለኛል፡፡ ይሁንና በውድድሮች መመናመን የሚቆረቆር አለመኖሩ ሁኔታውን አባብሶታል፡፡ የዓለም ስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ይህ ሁኔታ አሳስቦት ለምን አልተከራከረም?
 የዓለም ስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር በዚሁ የረጅም ርቀት የአትከሌቲክስ ውድድሮች መመናመን ዙርያ አስተያየት ለመስጠት ቢችልም ተፅእኖ በማሳደር ምንም አይነት ነገር ማስቀየር ግን  አይችልም፡፡ ይህን ሁኔታ ማረም ማስተካከል የሚችሉት አትሌቲክሱን የሚያስተዳድሩ አለማቀፍ ተቋማት ብቻ ናቸው፡፡ ዋናው ችግር እንደሚመስለኝ የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ከጥራት ይልቅ በብዛት ተሳትፏቸው የዓለምን ውድድሮች ማጨናነቅ መጀመራቸው ነው፡፡ ዛሬ ከዚሁ የአፍሪካ ክፍል እንደ ኃይሌ፤ ቀነኒሳ፤ ፖል ቴርጋት ልዩ የስፖርት ስብዓና ያላቸው ስፖርተኞች የሉም፡፡ ብዛት ብቻ ነው ያለው፡፡ ለምሳሌ በ10ሺ ሜትር ውድድር ድሮ አንድ ሁለት ኢትዮጵያዊ እና ኬንያዊ ቢኖሩ ነበር፡፡ ሌሎች አገራትም በተመጣጣኝ ኮታ  ከአውሮፓ፤ ከኤስያ፤ ከአሜሪካና ሌሎች የዓለም ክፍሎች ይወከሉ ነበር፡፡ ዛሬ ግን አስራምናምን ኬንያዊ እና ኢትዮጵያዊ በየውድድሩ መስፈርቱን አሟልቶ እየገባ የሌሎች አለም ክፍሎችን ፍላጎት እያመነመነው መጣ፡፡ ውድድር አዘጋጆችም ከእነስፖንሰሮቻቸው በዚህ ደስተኛ አይደሉም፡፡ ዓለም አቀፍ ሚዲያውም ስለ ሁለቱ የምስራቅ አፍሪካ አገራት አትሌቶች በመዘገብ ተሰላችቷል፡፡ እነዚህ ሁኔታዎች ለውድድሮች መጥፋት መንስኤ ይመስለኛል፡፡
ከኢትዮጵያ አትሌቶች ብቃት እና ስብዕና  ምን ያስደንቅዎታል?
በጣም ደስ የሚሉኝ እነዚህ ስፖርተኞች ከደሃ አገር ወጥተው በዓለም አቀፍ የውድድር መድረክ የሚገኑበት ጀግንነታቸው ነው፡፡ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች በአትሌቶቹ መካከል በተለይ በፊት የምታዘባቸው የቡድን ስራዎች እና አንድነታቸው ይማርከኛል፡፡ በኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ስፖርት ከህዝቦች ጋር ባህል ጋር የተሳሰረበት ሁኔታም ያስደንቀኛል፡፡
በኢትዮጵያ ላሉ የስፖርት ጋዜጠኞች ምን ምክር ይሰጣሉ?
ወደ ዓለም አቀፍ መድረክ የሚያወጣቸውን የትምህርትዐ የቋንቋ እና የልምድ ብቃት ያሳድጉ ነው የምለው፡፡ በተለይ በእንግሊዘኛ ቋንቋ ያላቸውን ችሎታ ማሳደግ አለባቸው፡፡ ለታላላቅ አትሌቶች የመረጃ ምንጭ መሆን ያለባቸው የራሳቸው አገር ሚዲያዎች እንጂ የሌላ አገር ተቋማት መሆን የለባቸውም፡፡ በአገር ውስጥ ያሉ የስፖርት እንቅስቃሴዎችን በተለይ ኢትዮጵያ የምትታወቅበትን የአትሌቲክስ ስፖርት በተለያየ ሁኔታ ለመላው ዓለም የሚያሰራጩበትን አሰራር ማሳደግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ በዓለም አቀፍ ውድድሮች ላይ የሚያገኙትን እድል ተጠቅመው በመስራትም ከሌሎች አገራት ባለሙያዎች ጋር ወቅቱን በጠበቀ መረጃ እና ተፅእኖ ፈጣሪነት እንዲሰሩ እመክራለሁ፡፡




* የግዳጅ ጋብቻ፣ ከሚገባው በላይ ማሰራት፣ ህገወጥ የሰዎች ዝውውር፣ ህጻናትን ጦር ሜዳ ማሰለፍ---
* በህንድ 14.3 ሚሊዮን ሰዎች የዘመናዊ ባርነት ሰለባዎች ናቸው
በአሁኑ ወቅት በአለማችን የተለያዩ አገራት 36 ሚሊዮን ያህል ሰዎች ዘመናዊ የባርነት ህይወት እየገፉ እንደሚገኙ ዎክ ፍሪ ፋውንዴሽን የተባለ ተቀማጭነቱን በአውስትራሊያ ያደረገ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም ሪፖርት ጠቅሶ ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡
ተቋሙ ለሁለተኛ ጊዜ ሰሞኑን ይፋ ያደረገው አመታዊ የባርነት መጠን አመልካች ሪፖርት እንደሚለው፣ በአለማችን የዘመናዊ ባርነት ሰለቦች ቁጥር ከአምናው በ23 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል፡፡
ጥናቱ ከተደረገባቸው 167 አገራት ቀዳሚውን ስፍራ የምትይዘው ህንድ ስትሆን፣ በአገሪቱ 14.3 ሚሊዮን ዜጎች የባርነት ኑሮን በመግፋት ላይ ይገኛሉ፡፡
ቻይና በ3.24 ሚሊዮን፣ ፓኪስታን በ2 ሚሊዮን፣ ኡዝቤኪስታን በ1.2፣ ሩስያ በ1 ሚሊዮን፤ ከሁለተኛ እስከ አምስተኛ ያሉትን ደረጃዎች ይዘዋል፡፡ ከአጠቃላይ ህዝባቸው ብዙ በባርነት ውስጥ የሚኖሩ ዜጎች ያሉባቸው አገራትን በተመለከተ ሪፖርቱ እንዳለው፣ ሞሪታንያ በ4 በመቶ፣ ኡዝቤኪስታን በ3.9 በመቶ፣ ሃይቲ በ2.3 በመቶ፣ ኳታር በ1.3 በመቶ እና ህንድ በ1.1 በመቶ ከአንድ እስከ አምስት ያሉትን ደረጃዎች ይዘዋል፡፡ዘመናዊ ባርነት በሁሉም አገራት ውስጥ እንዳለ የተቋሙ መስራችና ሊቀመንበር አንድሪው ፎሬስት መግለጻቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ዘመናዊ ባርነትን ለማጥፋት ትኩረት ሰጥቶ በመስራት ረገድ፣ አውስትራሊያ፣ ኦስትሪያ፣ ጆርጂያ፣ አየርላንድ፣ ኔዘርላንድ፣ ኖርዌይ፣ ስዊድን፣ ስዊዘርላንድ፣ እንግሊዝና አሜሪካ ቀዳሚነቱን እንደሚይዙ ገልጧል፡፡ እንደ ሪፖርቱ አገላለጽ፤ የሚገባቸውን ክፍያ ሳያገኙ ከሚገባቸው በላይ የስራ ጫና ያለባቸውና የተለያዩ ጥቃቶች የሚደርሱባቸው ህጻናት፣ ሴቶችና በተለያዩ የዕድሜ ክልሎች የሚገኙ ሰዎች፣ ከዘመናዊ ባርነት ሰለባዎች  ይመደባሉ፡፡ ሰዎች ነጻነታቸውን ተጠቅመው የፈለጉትን እንዳይሰሩ በመጨቆን፣ የገቢ ማስገኛ አድርጎ መጠቀም፣ የባርነት አንዱ ትርጓሜ ነው ያለው ሪፖርቱ፤ የግዳጅ ጋብቻ፣ ከሚገባው በላይ ማሰራት፣ ህገወጥ የሰዎች ዝውውር፣ ህጻናትን ወደ ጦር ሜዳ ማሰለፍና የመሳሰሉት የባርነት ተግባራት በስፋት እየተፈጸሙ እንደሚገኙ አመልክቷል፡፡