Administrator

Administrator

የሩስያ ዜግነት ያላቸው አባላትን የያዘ አለማቀፍ የድረገጽ ሌቦች ቡድን የአሜሪካን ግዙፍ ኩባንያዎች ጨምሮ በዓለም ዙሪያ የሚገኙ ታላላቅ ድርጅቶችን፣ የንግድ ኩባንያዎችንና የግለሰቦችን የድረገጽ መረጃዎችና ፓስ ዎርዶችን (የሚስጥር ቁልፎች) መዝረፉን ቴሌግራፍ ዘገበ፡፡
ሆልድ ሴኪዩሪቲ የተባለውን ተቋም ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ቡድኑ ከ420 ሺህ በላይ በሚሆኑ የኩባንያና የግለሰብ ድረገጾች ላይ የፈጸመው ይህ የስርቆት ተግባር፣ በዘርፉ በአለም ዙሪያ የተፈጸመ ትልቁ የመረጃ ዘረፋ ነው፡፡ ዘራፊዎቹ 500 ሚሊዮን የሚሆኑ የኢሜይል አድራሻዎችን የሚስጥር ቁልፍ በርብረው እንዳገኙ የጠቆመው ዘገባው፣ መሰል ተግባር ከተፈጸመባቸው መካከልም በዓለማችን ከፍተኛ የፋይናንስ አቅም ያላቸው ኩባንያዎች እንደሚገኙበት የሆልድ ሴኪዩሪቲን መስራች አሌክስ ሆልደን መናገራቸውን አስረድቷል፡፡
አስር ያህል አባላትን የያዘው ይህ የዘራፊዎች ቡድን ተቀማጭነቱን ያደረገው፣ ከካዛኪስታንና ከሞንጎሊያ ጋር በሚዋሰነው የሩስያ ደቡብ ማዕከላዊ አካባቢ እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን፣ አባላቱ በሃያዎቹ የዕድሜ ክልል ውስጥ እንደሚገኙ ተነግሯል፡፡
የቡድኑ አባላት የራሳቸውን የኮምፒውተር ፕሮግራም በመፍጠርና የድረገጾችን መረጃ በመስረቅ በሚያገኙዋቸው የሚስጥር ቁልፎች አማካይነት የኩባንያዎችንና የግለሰቦችን የመረጃ ልውውጥና ሚስጥር በእጃቸው እንደሚያስገቡ ተገልጿል፡፡
ኒውዮርክ ታይምስ በበኩሉ፣ቡድኑ የዝርፊያ ስራውን በረቀቀ መንገድ ማከናወን ከጀመረ ጥቂት አመታት እንደሆነው ገልጾ፣ የሚስጥር ቁልፎችን በመዝረፍ የሚያገኛቸውን የኩባንያዎችና የግለሰቦች ሚስጥሮች መደራደሪያ በማድረግ የገንዘብ ምንጭ አድርጎ እንደሚጠቀም ተነግሯል፡፡

በናትናኤል ፋንቱ የተፃፈው “ከነፍስ እስከ ዩኒቨርስ” የተሰኘ መፅሀፍ ባለፈው ሳምንት ለንባብ በቅቷል፡፡ መፅሀፉ በዋናነት በስነ ፈለክ ምርምር፣ በፕላኔቶች፣ በፀሐይና መሰል ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነው፡፡ “ከነፍስ እስከ ዩኒቨርስ” ስለምንኖርባት ዓለም ምን ያህል እናውቃለን፣ ማወቁስ ለምን አስፈለገ? ስለክዋክብት ማወቅስ ምን ይጠቅማል ለሚሉትና ተያያዥ ጥያቄዎች መጠነኛ መልስ ይሰጣል ተብሏል፡፡ በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች የተከፈለው መፅሀፉ፤ 156 ገፆች ያሉት ሲሆን በ40 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ የመፅሀፉ አዘጋጅ ናትናኤል ፋንቱ ከዚህ ቀደም “የእኔ ስላሴዎች - ህይወት፣ ፍቅርና ሳቅ”፣ “ስለ አረንጓዴ አይኖች”፣ “ሴቶች ለምንድን ነው ወሬ የማያቆሙት?” እና “የአምላክነት ቅምሻ” የተሰኙ መፃህፍትን ማሳተሙ ይታወሳል፡፡

በቀድው የ“አዲስ ነገር” ጋዜጣ አዘጋጅ ጋዜጠኛ ግርማ ተስፋው የተደረሰው “ሰልፍ ሜዳ” የተሰኘ ልብወለድ መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡ የልቦለዱ ማጠንጠኛ ከአብዮት በኋላ በሚያጋጥም የህይወት ፈተና ላይ በተዋቀረ በተለይም የሰው ልጆች በአብዮት ማግስት ለሚኖሩት ህይወት ትርጉም ማጣት፣ ብቸኝነት፣ ድብታና የባዶነት አዘቅት ውስጥ መስጠም በመፅሀፉ እንደ ዋንኛ ጭብጥ ተነስቷል፡፡
240 ገፆች ያሉት ልቦለዱ፤ በሊትማን መፃህፍት አከፋፋይነት የቀረበ ሲሆን በ49 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም “የጠፋችውን ከተማ ሐሰሳ” የተሰኘ የግጥም መድበል ለንባብ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡

የጋዜጠኛ ግርማ ወ/ማርያም “የ ‘ኛ ነገር” የተሰኘ የግጥም መድበል ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ ማህበራዊ ትዝብቶች፣ ፖለቲካዊ ጉዳዮችና ሌሎች ርዕሶች የተዳሰሱበት የግጥም መፅሀፉ፤ 76 ግጥሞችን ያካተተ ሲሆን በ70 ገፆች የተቀነበበ ነው፡፡ መፅሀፉ ድንገት ከቤቱ እንደወጣ ለቀረውና በጣም ለሚያከብረው ደራሲ በዓሉ ግርማ መታሰቢያነት ይሁንልኝ ብሏል፡፡ መድበሉ በ25 ብር ይሸጣል፡፡ ጋዜጠኛው ከዚህ በፊት “አለቃ ሙስና እና…” በሚል ርዕስ መፅሃፍ አሳትሟል፡፡  

በነፃ አውጭ ታጋይነት ዓለም አቀፍ ዝናና አድናቆት ያተረፈውን የቼ ጉቬራን ህይወት የሚያስቃኝ “ቼ ጉቬራ! የአብዮተኛው ህይወት” የተሰኘ መፅሀፍ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ ገበያ ላይ ውሏል፡፡
መፅሀፉ ከጆን ሊ አንደርሰን “Che Guevara፡ A Revolutionary Life” እና ከሪቻርድ ኤል ሃሪስ “Che Guevara፡ A Biography” መፅሀፎች ተጠናቅሮ የተሰናዳ መሆኑን አዘጋጁ ብርሃነ መስቀል አዳሙ በመፅሃፉ መግቢያ ላይ ገልጿል፡፡
ድህረ ታሪኩን ጨምሮ በስድስት ምዕራፍ የተከፋፈለውና በ254 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ በ50 ብር ከ70 ለገበያ ቀርቧል፡፡

Saturday, 09 August 2014 11:37

ማራኪ አንቀጽ

“..ምን ልርዳችሁ? ምን ፈልጋችሁ ነው?” አሉ ግራ ተጋብተው፡፡
ተዘጋጅተንበት ስለነበር ሁላችንም በአንድ ድምፅ
“ዜግነት!!! ዜግነት!!!...ነፃነት!!...አባት ሀገር!!...አባት ሀገር!!! Our father land!!...Father land!!!” እያልን መጮህ ጀመርን፡፡
ወንበር ላይ ወጥቼ እያጨበጨብኩ፤
“ነፃነት!! ዜግነት!! ነፃነት!! ዜግነት!!...” በማለት መዝፈን ስጀምር ሁሉም እኔን እየተከተሉ መዝፈንና ግድግዳ እየደበደቡ ሲረብሹ፣ አቶ ተስፋዬ የሚሰማቸው ስላጡ ቢሮውን ለቀው ወጡ፡፡ የኤምባሲው ሰራተኞች በሙሉ ደንግጠው ሲመለከቱን ጭራሽ ባሰብን፡፡ ከአስር ደቂቃ በኋላ አቶ ተስፋዬ አምባሳደሩን፣ ቆንስሉንና ሌሎች ነጭ ሆላንዳዊያንን አስከትለው መጡ፡፡
“እባካችሁ ተረጋጉና የምትፈልጉትን ንገሩን፡፡” ቢሉንም እኛ ግን መጮሃችንን ቀጠልን፡፡
“እንዲህ መሆናችሁ ጥቅም የለውም፡፡ ይልቁንስ አምባሳደሩ አጠገባችሁ ስለሚገኝ ይህን ዕድል ተጠቅማችሁ ጥያቄያችሁን ብታቀርቡ ይሻላል” አሉ አቶ ተስፋዬ፡፡
ይህን ስንሰማ ቀስ በቀስ ተረጋጋን፡፡ ወዲያውኑ አምባሳደሩ ንግግር ጀመረ፡፡ አቶ ተስፋዬ የአምባሳደሩን ንግግር ማስተርጐም ሲጀምሩ ከቆምኩበት ወንበር ላይ ዘልዬ ወረድኩ፡፡
“አቶ ተስፋዬ እንዲያስተረጉምልን አንፈልግም። እንግሊዘኛ ቋንቋ የሚችል ሰው አለን፡፡ አንተ እኛን ለማስፈራራት ብቻ ነው የምትፈልገው፡፡” ብዬ ጮህኩኝ።
ኢዩኤል በእንግሊዝኛ መናገር ሲጀምር ፀጥታ ሠፈነ፡፡
“እኛ የተረሳን የሆላንድ ተወላጆች ነን። አባቶቻችን ጥለውን ጠፍተዋል፡፡ ስለዚህ ወደ ሀገራችን መሄድ እንፈልጋለን! ጥያቄያችን ይህ ነው፡፡” አለና በእንግሊዝኛ የተናገረውን ወዲያው በአማርኛ ለእኛ ተረጐመልን፡፡ አምባሳደሩ የተናደደ መሰለ፡፡
“የሆላንድን ዜግነት በጉልበት ማግኘት ትችላላችሁ?! ሁላችሁም ከዚህ ቢሮ አሁኑኑ ለቃችሁ ውጡ! በፖሊስ ሃይል ተገዳችሁ ከመውጣታችሁ በፊት አሁኑኑ በሰላም ውጡ!” ብሎ ድምፁን ከፍ አድርጐ ተናገረ፡፡
በመቀጠል ቆንስሉ ወደ እኛ ተጠግቶ “በሉ ውጡ!” እያለ ሲንጐራደድ፣ ሁሉም ልጆች “ምን እናድርግ?” በሚል ስሜት ተመለከቱኝ፡፡
“በለው! በለው!” አልኩና ከባድ ግርግር አስነሳሁ። ሰለሞን ታይሰን አይኑን አፍጥጦ ቆንስሉን ሲጠጋው ቆንስሉ ወደ ውጪ ሮጠ፡፡
“ነፃነት! ዜግነት! ነፃነት! ዜግነት! ዜግነት!” የሚል ጩኸት ተጀመረ፡፡
ሁሉም ሸሽተውን በርቀት ይመለከቱናል። ከሰላሳ ደቂቃ በኋላ አምስት የታጠቁ የኢትዮጵያ ፖሊሶች የእንጨት ዱላና ካቴና ይዘው መጡ፡፡ አምስቱም ፖሊሶች ተከታትለው ገብተው፤
“ፀጥ በል! ፀጥ በል! ለምንድነው የምትረብሹት?! ተነስ ውጣ! ውጣ!” እያሉ ያመናጭቁን ጀመር፡፡
ሳያስቡት ዘልዬ መጀመሪያ ወደኛ የተጠጋውን ፖሊስ ሁለቴ በቦክስ ስመታው፣ ተንገዳግዶ ጥግ ያዘ። ሰለሞን ሮጠና ጥግ የያዘውን ፖሊስ እግሩን ዘርጥጦ ጣለውና፣ በጉልበቱ ግንባሩን መቶት ራሱን አሳተው። የቀሩት ፖሊሶች ራሳቸውን ለመከላከል በያዙት ዱላ ሰለሞንን ፈነከቱት፡፡ በግብግቡ ውስጥ እንደምንም ብለው የተመታውን ፖሊስ ከቢሮ ጐትተው አወጡት። በመስታወት ውስጥ ቆመው ጠቡን የሚያዩት አምባሳደሩ፤ ቆንስሉና ሌሎችም ነጭ ሆላንዳዊያን በኛ ቁርጠኛነት ደንግጠዋል፡፡
በቢሮው ውስጥ የነበረውን አግዳሚ ወንበር አንስተን ለስድስት ተሸከምነውና ፊት ለፊት የሚያዩበትን መስታወት ለመስበር በወንበሩ መምታትና መደብደብ ጀመርን፡፡ በአምስተኛው ምት መስታወቱ ፈረሰ፡፡ ቢሮው ውስጥ የነበሩት አምባሳደሩ እና ሌሎች የኤምባሲው ሰራተኞች ቢሮውን ጥለው ከፖሊሶች ጋር ተቀላቀሉ። እንደማይቋቋሙን ሲረዱ ከሃያ በላይ የሚሆኑ ፖሊሶች አስጨምረው ከብዙ ትግልና መስዋዕትነት በኋላ ስለተዳከምን፣ ሁላችንንም በካቴና አስረው እየጐተቱ እና በዱላ እየቀጠቀጡ፣ በፖሊስ መኪና ወደ ፖሊስ ጣቢያ ወሰዱን፡፡ ፖሊስ ጣቢያ ስንደርስ ካቴናችንን እየፈቱ፣ አንድ ቤት ውስጥ አስገብተው ቆለፉብን፡፡ ሁላችንም በጣም ደክሞን ስለነበር ወለሉ ላይ በጀርባችን ተዘርረን ተኛን፡፡ ማታ ራት አቀረቡልን፡፡ በነጋታው ሁላችንም ሻወር ወስደን እስር ቤት ውስጥ መጫወትና ያደረግነውን ትግል ጀብዱ፣ ድፍረት፣ ቆራጥነት ስናወራ፣ የፖሊስ ጣቢያው መርማሪዎችና መቶ አለቃው በሩን ከፍተው መሃላችን ቆሙ፡፡ ለሁለት ደቂቃ አዩንና
“አመፀኛው ክልስ የታል? የዚህ አመጽ መሪ አንተ ነህ?” ብሎ አፈጠጠብኝ፡፡ የቀሩት መርማሪ ፖሊሶች “አመፀኛው ክልስ ተነስ!! አመፀኛ!!” እያሉ በጥፊ እየመቱኝ፣ ለምርመራና ጥየቃ የመቶ አለቃው ቢሮ አስገቡኝ፡፡
“አመፀኛው ክልስ ስምህ ማነው” አለ መቶ አለቃ፡፡
“ዳንኤል ሁክ” አልኩት…
(ከዳንኤል ሁክ “አመፀኛው ክልስ”
እውነተኛ ታሪክ መፅሃፍ የተቀነጨበ -2005 ዓ.ም)

Saturday, 09 August 2014 11:38

የፍቅር ጥግ

ስለጓደኝነት
ጨርሶ አታብራራ - ወዳጆችህ አያስፈልጋቸውም፤ ጠላቶችህ ደግሞ አያምኑህም፡፡
ቪክቶር ግራይሰን
(እንግሊዛዊ ፖለቲከኛ)
ዕጣፈንታ ዘመዶችህን ይመርጥልሃል፤ አንተ ደግሞ ጓደኞችህን ትመርጣለህ፡፡
ጃኪውስ ዴሊሌ
(ፈረንሳዊ ገጣሚና የገዳም ሃላፊ መነኩሴ)
ወዳጆችና መልካም ባህሪያት ገንዘብ ወደማይወስድህ ቦታ ይወስዱሃል ይዘውህ ይሄዳሉ፡፡
ማርጋሬት ዎከር
(አሜሪካዊ ገጣሚ፣ ደራሲና ጋዜጠኛ)
እኩያህ ያልሆኑ ጓደኞችን አትያዝ፡፡
ኮንፉሺየሽ
(ቻይናዊ ፈላስፋ)
ሺ ጓደኞች ያሉት አንዳቸውም ለክፉ ቀን አይደርሱለትም፡፡ አንድ ጠላት ያለው በየሄደበት ያገኘዋል፡፡
አሊ ቤን አቢ ታሌብ
(“Hundred sayings”)
አየህ፤ የአዕምሮህ ጓደኛ የሆነች ሴት ስታገኝ ጥሩ ነው፡፡
ቶኒ ሞሪሶን
(አሜሪካዊ ደራሲ)
የድሮ ጓደኞች ሸጋ ናቸው፡፡ ንጉስ ጄምስ፤ የድሮ ጫማዎቹ እንዲያመጡለት ሁልጊዜ ይጠይቅ ነበር፡፡ እነሱ ነበሩ ለእግሩ የሚደሉት፡፡
ጆን ሴልደን
(እንግሊዛዊ የታሪክ ምሁር፣ የህግ ባለሙያ እና ፖለቲከኛ)
በወይን ጠጅ የተመሰረተ ወዳጅነት ደካማ ነው፤ እንደወይን ጠጁ የአንድ ምሽት ብቻ ነው፡፡
ፍሬድሪክ ቮን ሎጋው
ጠላቶችህን ከመውደድ ይልቅ ለወዳጆችህ ትንሽ እንክብካቤ ጨምርላቸው፡፡
ኤድጋር ዋትሰን ሆዌ
(አሜሪካዊ ደራሲ)
ሰው ወደፊት በህይወቱ ወደፊት በተራመደ ቁጥር ከአዳዲስ ሰዎች ጋር ካልተዋወቀ ብቻውን ይቀራል፡፡ ጌታዬ ሰው ወዳጅነቱን ሳያቋርጥ ማደስ አለበት፡፡
ሳሙኤል ጆንሰን
(እንግሊዛዊ የመዝገበ ቃላት አዘጋጅና ፀሐፊ)

           በገጠር ገበሬው መኖርያ ቤቱን በእሾህ ያጥራል፡፡ በከተማ ደግሞ አጥር ከማጠር በተጨማሪ ቤት ጠባቂ ውሻ በማሳደግ፣ “ሃይለኛ ውሻ አለ” የሚሉ ማስጠንቀቂያዎች ተለጥፎ ማየት የተለመደ ነው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን እንዲህ ያለው ማስጠንቀቂያ “አደገኛ አጥር” በሚል እየተተካ የመጣ ይመስላል፡፡ ቀድሞ በጥቂት ግለሰቦችና ድርጅቶች እንዲሁም ኤምባሲዎች ጥቅም ላይ ይውል የነበረው የኤሌክትሪክ አጥር አሁን በብዛት ጥቅም ላይ መዋል ጀምሯል፡፡
“ኔምቴክ”  መቀመጫውን በደቡብ አፍሪካ ያደረገ፣ በ54 የተለያዩ የዓለም አገራት የኤሌክትሪክ አጥር በመስራት የሚታወቅ ዓለምአቀፍ ድርጅት ነው። ሚስተር ዲክ ኢራስመስ፤ በዚህ ድርጅት ውስጥ በኤክስፐርቶች ማናጀርነት ይሰራሉ። በቅርቡ በአዲስ አበባ በኤሌክትሪክ አጥር አተካከልና አጠቃቀም ዙሪያ በተዘጋጀ ስልጠና ላይ የኤሌክትሪክ አጥሮችን ወጪ በሚቆጥብና የላቀ ውጤት በሚያስገኝ ሁኔታ እንዴት መጠቀም  እንደሚቻል አሰልጥነዋል፡፡ ላለፉት 25 ዓመታት በዘርፉ ሲሰራ የቆየው “ኔምቴክ”፤ በተለያዩ የአፍሪካ አገሮች ተመሳሳይ ስልጠናዎችን በመስጠት ይታወቃል። በነገራችን ላይ ድርጅቱ ከሚሰራባቸው የዓለም አካባቢዎች አብዛኞቹ የሚገኙት በአፍሪካ ውስጥ ነው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ ከወንጀሎች መበራከት ጋር የተያያዘ እንደሆነ ዲክ ኢራስመስ ይናገራሉ፡፡
ኢራስመስ በኤሌክትሪክ አጥር አጠቃቀም ዙሪያ፣ ስለአደገኛነቱና በኢትዮጵያ ስላለው ሁኔታ እንደሚከተለው አስረድተዋል፡፡
የኤሌክትሪክ አጥሮች አጠቃቀም
የኤሌክትሪክ አጥሮች ውጤታማ እንዲሆኑ ከተፈለገ በመጀመሪያ በደንብ መተከል አለባቸው። የኤሌክትሪክ አጥሮች የሚተከሉት ሰውን ለመግደል አይደለም፡፡ ሌሎች ጉዳቶችንም ማድረስ የለባቸውም፡፡
ደቡብ አፍሪካ በአለም ላይ በርካታ ወንጀሎች ከሚፈፀምባቸው የአለማችን ክፍሎች አንዷ ናት። በአገሪቱ በሚፈፀሙ የተለያዩ ወንጀሎች ብዙ ሰዎች ንብረታቸውንና ህይወታቸውን ያጣሉ። የተለያዩ ወገኖች በኤሌክትሪክ አጥር አስፈላጊነት ላይ ጥያቄዎችን ቢያነሱም በወንጀሎች መበራከት የተነሳ፣ የኤሌክትሪክ አጥር ተጠቃሚዎች ቁጥር በእጅጉ እየጨመረ መጥቷል፡፡ የኤሌክትሪክ አጥር፤ ዝርፊያን ለመከላከልና ደህንነትን ለማረጋገጥ አስተማማኝ ብቃት አለው፡፡ በወጪም አንፃር ቢሆን የተጋነነ አይደለም፡፡
የኤሌክትሪክ አጥርን እኔ “ስሪ ዲ” ነው የምለው። “ዲተር”፣ “ዲቴክት እና “ዲሌይ” ማድረግ ነው ስራው፡፡ በመጀመሪያ አንድ ሰው አጥሩ ላይ ያለውን ማስጠንቀቂያ ሲያይ ወደዚያ እንዳይጠጋ ምልክት ይሰጠዋል፡፡ ያን አልፎ የሰው አጥር መንካት ሲጀምር “ዲቴክት” በማድረግ ገፍትሮ ይጥለዋል፡፡ በዚህም ግለሰቦች ወይም ቡድኖች ሊፈፅሙ ያሰቡትን ወንጀል እንዳይፈፅሙ በማዘግየትና ድምፅ በማሰማት  ሰዎች በንብረታቸው ወይም በህይወታቸው ላይ ሊፈፀም ከታቀደ አደጋ ይጠብቃቸዋል፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን የኤሌክትሪክ አጥሮች በሰው ህይወት ላይ የሞት አደጋ ማድረስ የለባቸውም፡፡
የማይሰሩ የኤሌክትሪክ አጥሮች
በመስክ ስልጠናው የታዘብኳቸው ስህተቶች አሉ፡፡ በተለይ የኤሌክትሪክ አጥሮቹ በትክክል አለመተከል ዋነኛው ነው፡፡ አጥሩን ያስተከሉ ሰዎች መስራት አለመስራቱን ስለማያረጋግጡ አጥሩ ቢኖርም ላይሰራ ይችላል፡፡ ዋናው ስህተት በሽቦውና በኤሌክትሪኩ መካከል ያለው ልዩነት ሰፊ መሆኑ ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ወንጀል ለሚፈፅሙ ሰዎች ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል፡፡  እንዲህ ሲሆን ከኪሳራውም ባሻገር ሰዎች ለዘረፋና በህይወት ላይ ለሚቃጣ አደጋ ይጋለጣሉ፡፡
ሌላው አጥሩ ላይ ሌሎች ነገሮች ተሰቅለው የሚታዩበት ሁኔታ መኖሩ ነው፡፡ የሆኑ ብረቶች ተቀላቅለው ያየሁባቸው ቦታዎች አሉ፡፡ ዛፍና አትክልቶች ከአጥሩ ጋር ይቀላቀላሉ፡፡ እነዚህ ነገሮች የኤሌክትሪክ አጥሩ በተገቢው መንገድ አገልግሎት እንዳይሰጥ እንቅፋት ይሆናሉ፡፡ በስልጠናው ወቅት የኤሌክትሪክ አጥር የሚተክሉ ሰዎች በተገቢው መንገድ እንዲተክሉ በንድፈ ሃሳብና በተግባር የታገዘ ስልጠና ሰጥተናቸዋል፡፡ ከቤት ውበት ጋር በተያያዘም አተካከሉ ላይ የሚደረጉ ጥንቃቄዎች ተዳስሰዋል፡፡
አጥሩን ሊነካ የሚሞክር ሁሉ ወንጀለኛ ነው ብሎ ለመደምደም አስቸጋሪ ስለሚሆን፣ ይህ አጥር በተተከለበት ቦታ ሁሉ በግልፅ ሥፍራ የማስጠንቀቂያ ማስታወቂያ መለጠፍ ግዴታ ነው። ይሄ በደቡብ አፍሪካ በህግ ተደንግጐ የተቀመጠ ጉዳይ ነው፡፡ ይህንን አጥር የሚተክሉ ሰዎች ተገቢ ስልጠና ያገኙ መሆን እንዳለባቸው ህጉ ይደነግጋል፡፡ ባለቤቱ ሰው የማይገድልና የጥራት ደረጃውን ያሟላ ምርት መሆኑን ማረጋገጥ እንዳለበት ተቀምጧል፡፡ ማስጠንቀቂያውን ያላዩ ሰዎች አጥሩን ቢነኩ እንኳን ገፍትሮ ይጥላቸዋል እንጂ አይገድላቸውም፡፡  
በዚህ አጥር እንስሳትም ቢሆኑ መጐዳት የለባቸውም፡፡ በኤሌክትሪክ አጥሩ ጉዳት የሚደርስባቸው በማንኛውም ኤሌክትሪክ ሊጎዱ የሚችሉ እንደ  ሸረሪትና እባብ አይነት እንስሶች ብቻ ናቸው፡፡ ወፎች የሚቆሙት  ብረቶቹ ላይ ስለሆነ ጉዳት አይደርስባቸውም፡፡
አፍሪካ ውስጥ ብቻ ሳይሆን በብዙ ቦታዎች እንደ ስዊድን፣ አውስትራሊያና ኔዘርላንድስ ባሉ አገራትም የኤሌክትሪክ አጥሮች ብዙ ህይወቶችንና የንብረት ጉዳቶችን ታድገዋል፡፡
አጥሮቹ መብራት በሌለበት ጊዜ የባትሪ መጠባበቂያ ስላላቸው ስራቸውን አያቋርጡም፡፡ እኔ እንዳየሁትና ከሌሎች ቦታዎች ጋር እንዳነፃፀርኩት፣  አዲስ አበባ ያለው የመብራት ሀይል አቅርቦት እምብዛም የከፋ አይደለም፡፡
ኬኒያ፣ ናይጄሪያና፣ ጋና በመሳሰሉት አገራት የሀይል አቅርቦቱ እጅግ አስቸጋሪ ነው፡፡ ተከታታይ የሀይል አቅርቦት በማይኖርባቸው ጊዜያት ወይም ቦታዎች ሶላር እንጠቀማለን፡፡
አዲሱ የ“ደህንነት” ኩባንያ
አቶ ሳምሶን ገብረስላሴ፤ የ“ሳሜክ ኢንጂነሪንግ” ባለቤትና ስራ አስኪያጅ ናቸው፡፡ በቅርቡ በ ደህንነት እና አደጋ መከላከል ስራ ላይ የተሰማራ አዲስ ድርጅት በአዲስ አበባ ከፍተዋል፡፡  “ሳሜክ ኢንጂነሪንግ ለንደን የሚገኘው የ “ሳሜክ” ኩባንያ እህት ድርጅት ነው፡፡ የደህንነት እና የአደጋ መከላከያ እቃዎችን ከውጪ በማስመጣት፣ በኢትዮጵያ በዚህ ስራ ላይ ለተሰማሩ ድርጅቶች ያቀርባል፡፡ እነዚህ ድርጅቶቹ መሳሪያዎቹን ከመግጠማቸው በፊት ስልጠናዎች በመስጠት ጥራቱን የጠበቀ ሥራ እንዲሰሩ ያግዛል፡፡ የ“ኔምቴክ” ስልጠናም የዚሁ አካል ነው፡፡ የ“ሳሜክ ኢንጂነሪንግ” ባለቤት አቶ ሳምሶን ገ/ሥላሴ፤ በኢትዮጵያ ስላለው የኤሌክትሪክ አጥሮች ተሞክሮአቸውን እንዲህ ይገልፁታል፡፡
“እኛ አገር ያለው ችግር አጥሩ  በብዛት የሚተከለው በልምድ ነው፡፡ ከዚህ በፊት የሚጠቀሙት ኤምባሲዎችና ትልልቅ መስሪያ ቤቶች ነበሩ፤ አሁን ግን ወንጀል እየተበራከተ ሲመጣ በመኖሪያ ቤቶች በስፋት እየተገጠመ ነው፡፡ አጥሩ መስራት አለመስራቱ የሚታወቀው ሌባ ያን አጥር ነክቶ ገፍትሮ ሲጥለው ነው፤ ተከላው በትክክል ስለማይከናወን ውጤታማነቱ አጠያያቂ ነበር። የሚገጥሙት ሠራተኞች መስራት አለመስራቱን ለማወቅ በቂ ስልጠናም ሆነ ማረጋገጫ መሳሪያዎች አልነበራቸውም፡፡
ከዚህ በፊት የተገጠሙትን ስናይ፤ መስመሩ የተላቀቀ፣ የተቆራረጠ፣ በቂ የኤሌክትሪክ ሀይል የሌለው ሁሉ አጋጥሞናል፡፡ ወደፊት ተከታታይ ስልጠናዎች ይኖራሉ፤ የሚተክሉት ሰዎች ብቃት ያላቸው እንዲሆኑና በአገራችን መንግስት የኤሌክትሪክ አጥር ህግ እንዲያወጣ ግፊት እናደርጋለን፡፡”
እስከዚያው ግን የኤሌክትሪክ አጥር ባለበት ሥፍራ ሁሉ ይሄንኑ የሚገልጽ ማስታወቂያ በግልፅ በሚታይ ቦታ ላይ መሰቀል እንዳለበት ባለሙያዎቹ በአጽንኦት ይናገራሉ፡፡

Saturday, 09 August 2014 11:32

የጸሐፍት ጥግ

የማየውን ስዬ አላውቅም፡፡ ሰውነቴ የሚነግረኝን ነው የምስለው፡፡
ባርባራ ሄፕዎርዝ
(እንግሊዛዊ ቀራፂ)
ለእውነተኛ የፈጠራ ሰዓሊ ፅጌረዳን እንደመሳል የሚያስቸግረው ምንም ነገር የለም፤ ምክንያቱም ያንን ከማድረጉ በፊት በመጀመርያ እስከ ዛሬ የተሳሉትን ፅጌረዳዎች ከአዕምሮው ማውጣት አለበት፡፡
ሔንሪ ማቲሴ
(ፈረንሳዊ ሰዓሊና ቀራፂ)
ከራስህ ውስጥ መተዳደርያህን መፍጠር በጣም እንግዳ ነገር ነው፡፡
ጄምስ ቴይለር
(አሜሪካዊ ዘፋኝና የዘፈን ግጥም ደራሲ)
በፈጠራ የታከለ የሂሳብ አሰራር ባለበት ማን ማጭበርበር ይፈልጋል?
ካታሪን ዋይትሆርን
(እንግሊዛዊ ጋዜጠኛና ፀሐፊ)
ዕድል ለዝግጁ አዕምሮ ታደላለች፡፡
ሉዊስ ፓስተር
(ፈረንሳዊ ሳይንቲስት)
ሁሉም ሰው የፈጠራ ችሎታ ቢኖረውም የጥበብ ሰዎች ግን ጥቂት ናቸው፡፡
ፖል ጉድማን
(አሜሪካዊ ፀሐፊ፣ አስተማሪና የሥነ-አዕምሮ ሃኪም)
ከሥርጭት በፊት ፈጠራ ይቀድማል  - አለበለዚያ የሚሰራጭ ነገር አይኖርም፡፡
አየን ራንድ
(ትውልደ ራሽያ አሜሪካዊ ፀሐፊና ፈላስፋ)
ደስታ ለሰውነት ጠቃሚ ነው፤ የአዕምሮን አቅም የሚያሳድገው ግን ሀዘን ነው፡፡
ማርሴል ፕሮስት
(ፈረንሳዊ ደራሲ)
ምስቅልቅሎሽ ግሩም ሃሳብ ይፈጥራል የሚል ታላቅ እምነት አለኝ፡፡ ምስቅልቅሎሽን እንደ ስጦታ ነው የምቆጥረው፡፡
(ሴፕቲማ ፓይንሴቴ ክላርክ
አሜሪካዊ የትምህርት ባለሙያ)

“ምነው ወዳጅህ እኮ ነኝ፤ ቢለው”
“ዝም በል! ዋናው አለመሳታችን ነው!” አለው

ከዕለታት አንድ ቀን ሁለት ጓደኛሞች ጫካ ሄደው እንጨት ቆርጠው ለመምጣት ይፈልጋሉ፡፡ አንደኛው በመጥረቢያ ቅርንጫፍ እየቆረጠ ሳለ እጁና ሳያስበው ቆርጦ ጣለው፡፡
ጓደኝየው የተቆረጠውን ክንድ በፌስታል ውስጥ ከትቶ፤ እጁ የተቆረጠ ጓደኛውን ይዞ ወደ ቀዶ - ጥገና ሐኪም ወሰደው፡፡
ዶክተሩም - “በጣም ዕድለኛ ነህ እኔ የተቆረጡ አካላትን መልሶ የማጣበቅ ክሂል ባለሙያ ነኝ፡፡ በአራት ሰዓት ውስጥ ተመልሰህ ና” አለው፡፡
ጓደኝየው - “እሺ ዶክተር ባሉኝ ሰዓት እመጣለሁ” ይልና ይሄዳል፡፡
ከተባለው ሰዓት በኋላ ሲመለስ፤ ዶክተሩ፤
“እጨርሳለሁ ካልኩበት ሰዓት ቀድሜ ጨረስኩ፡፡ ገዋደኛህ ጤንነቱ ተመልሶ እዚህ ታች ወዳለው ግሮሠሪ ሄዷል፡፡”
ጓደኝየው በደስታ ጮቤ እየረገጠ ወደተባለው መጠጥ ቤት ሄደ፡፡ ጓደኝየው ጭራሽ የዳርት ውርወራ ግጥሚያ ይዟል፡፡
ከጥቂት ሣምንታት በኋላ ጓደኛሞቹ አሁንም ወደጫካ ሄደው እንጨት ቆረጣ ላይ ተሰማሩ፡፡ ባለፈው እጁን የቆረጠው ሰው አሁን ደግሞ እግሩን ቆርጦ ጣለው፡፡ ጓደኝየው እንዳለፈው ጊዜ የተቆረጠውን እግር ፌስታል ውስጥ ከትቶ ጓደኛውን ይዞ ወደዚያው የአካል ቀዶ ጥገና ሐኪም ዘንድ ይዞት ሄደ፡፡
ሐኪሙም፤
“አየህ፤ የእግር ቀዶ - ጥገና ትንሽ ከበድ ያለ ነው፡፡ ከስድስት ሰዓት በኋላ ተመለስ” አለው፡፡
ጓደኝየውም፤
“እንዳልከው አደርጋለሁ ዶክተር” ብሎ ሄደ፡፡
ከስድስት ሰዓታት በኋላ ተመልሶ ውጤቱን ለማወቅ ወደ ሐኪም ሲመጣ፤
ሐኪሙ “ይገርምሃል ከነገርኩህ ሰዓት አስቀድሜ ሥራ አገባደድኩ፡፡ ጓደኛህ እዚያ ታች ወዳለው እግር ኳስ ሜዳ ሄዶልሃል” አለው፡፡
ጓደኝየው ሐኪሙ አመስግኖ ወደ ኳስ ሜዳው ወርዶ ሲያየው፡፡ ያ እግረ የተገጠመለት ጓደኛው ምን የመሳሰሉ ጎሎች እያገባ ነው፡፡
ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ግን፣ ያ ጓደኝየው እጅግ ከባድ የመኪና አደጋ ይገጥመውና አንገቱ ሙሉ ለሙሉ ተቆረጠ፡፡ ጭንቅላቱ ብቻውን ወደቀ፡፡
እንደተለመደው የፈረደበት ጓደኛ ጭንቅላቱን በፌስታል ከትቶ ቀሪውን የጓደኝየውን አካል ጭኖ ወደ ሐኪሙ በረረ፡፡
ሐኪሙም፤
“ጭንቅላት መግጠም እጅግ ከባድ ነው፡፡ ለማንኛውን ከአሥራ ሁለት ሰዓት በኋላ ተመለስ” አለው፡፡
ተመልሶ ሲመጣ፤ ሐኪሙ፡-
“ይቅርታ አድርግልኝ፡፡ ጓደኛህ ሞቷል” አለው፡፡
ጓደኛውም፤
“ዕውነትክን ነው፡፡ የጭንቅላት ነገር ከባድ መሆኑን እገምታለሁ” አለ፡፡
ሐኪሙም፤
“ቀዶ ጥገናውን እንኳ ደህና አድርጌ ነበር የሰራሁት፡፡ ግን አየህ፤ አንተ ስታመጣው እዛ ፌስታል ውስጥ ታፍኖ ትንፋሽ አጥሮት ነው የሞተው!”
*   *   *
እጅ እግሩን ከቆረጠበት አደጋ ያልተማረ፣ አንገቱን የሚቆረጥበት ሰዓት ይመጣል! ከስህተት አለመማር መዘዙ ራስን እስከማጣት ያደርሳል፡፡
የአካላችን ሁሉ አናት የሆነው ጭንቅላት የሁሉ ነገራችን መሪ ነው፡፡ አንዴ ካመለጠ የማይገጣጠም መሆኑም ይሄንኑ የሚያመላክተን ነው፡፡ ሁሉን ተግባራችንን በአቅል በአቅል የሚያስቀምጥልን፣ የሚያደራጁልን፣ መንገድ የሚያገባልን የህይወት መሪያችን እሱ ነው፡፡ በሀገር ደረጃ ሲታይም፤ ተቋሞቻችንን፣ ድርጅቶቻችንን፣ ት/ቤቶቻችንን፣ ኮሚሽኖቻችንን፣ ሚኒስቴሮቻችንን፣ ኢንዱስትሪዎቻችንን ወዘተ የሚመሩ ርዕሰ - አመራሮች እንደጭንቅላት ናቸው፡፡ የእነዚህ ጭንቅላቶች ልክ መሆን፣ ቅጥ መያዝና የድርና ማግ መቀናጀት ነው የሀገርን ጤና ልክነት የሚረጋግጠው፡፡ ይህ የጭንቅላት ክህሎት ከሌለ፣ ካልተባ፣ ከቀልብ ካልተዋሃደ ወጥነት ያለው አመራር ማግኘት አይቻልም፡፡ ጨርሶ ባዶ የሆነ ዕለት ደሞ መሄድ ቀርቶ መቆም ያቅታል፡፡
ገጣሚና ፀሐፌ ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን፣ በ “በልግ” መጽሐፉ፤
“በዚህ በያዝኩት ጎራዴ፣ አንተግክን ቀንጥሼ ብጥለውም”
ከባርኔጣህ በስተቀር፣ ዋጋ ያለው ነገር አይወድቅም”
የሚለን ለዚህ ነው
“የዕውቀት ማነስ ፓለቲከኛ አደረገኝ” ከሚል ሰው ይሰውረን፡፡ አንዳንድ ፖለቲካ እጅግ አስመሳይ ከመሆኑ የተነሳ “የፆም መኪያቶ” “መኪያቶ” የሚባለውን ዓይነት ይሆናል፡፡ ወይ ሙሉውን መፆም ነው፣ አሊያ የሚለውን ሃሳብ ጨርሶ መርሳት ነው፡፡ “ፀብ ክርክር ካለበት ጮማ - ፍሪዳ፤ ፍቅር ያለበት ጎመን ይሻላል” ይላሉ አበው፡፡ በላሸቀ ኢኮኖሚ ውስጥ የፖለቲካ ጀግና መሆን እያደር ሽባ እንደሚያደርገን መገንዘብ ጭንቅላት ይዞ ማሰብን አይጠይቅም፡፡ ስለዚህ አስቀድሞ ኢኮኖሚውን ማዳን ነው፡፡ የዝሆን ጥርስ አናት ያለው ጉልላት ላይ ያለ የታችኛው ህዝብ መከራ አይታየውም፡፡ ያም ሆኖ የማይለወጥ ነገር የለም ሁሉም የጊዜ ጉዳይ ነው፡፡ ወይም እንደ ቪክተር ፍራንክል፤
“ሁኔታዎችን መለወጥ ካልቻልክ ራስህን ለመለወጥ ትገደዳለህ” እንላለን፡፡ ቪክተር ከ2ኛው ዓለም ጦርነት ሆሎኮስት ቃጠሎ እልቂት የተረፈ ሳይካትሪስትና ፀሐፊ ነው፡፡ ከእልቂት ከተረፈ በኋላ በሰው ልጅ ላይ ምን ለውጥ እንደሚመጣ አስተውሏል፡፡ ለእያንዳንዱ ለውጥ ያ ሁሉ መስዋዕትነት መደገም አለበት ማለት አይደለም፡፡ ከማዕበሉ በኋላ የረጋ አየር፣ አየርም ቢሉ ለውጥ የሰፈነበት፤ ይመጣል ማለት እንጂ!
የበላይም ይናገር የበታች ለሀገራችን የሚጠቅመው መደማመጥ ነው፡፡ በአንድ አቅጣጫ ብቻ እንደሚኬድበት መንገድ (One way road) አንሁን፡፡ የሚነገረንን እንስማ፡፡ ሌላው ሰው ድንገት ከእኔ የተሻለ ሀሳብ ቢያቀርብስ? እንበል፡፡
ደራሲ ከበደ ሚካኤል
“አሁን የት ይገኛል ቢፈልጉ ዞሮ
መስማት ከማይፈልግ የባሰ ደንቆሮ”
ያሉትን አለመዘንጋት ከብዙ አባዜ ያድናል፡፡ እርግጥ ይህንንም የሚሰማ ካለ ነው፡፡
አበሻ በኢኮኖሚው መዘበትና ምፀት ማውራት ይችልበታል፡፡ ኢኮኖሚው አላፈናፍን ሲለው መውጫው በግጥም መተንፈስ ነው፡-
“በቆሎ፤ በዝናብ፣ ሲጠብስ እያያችሁ
ሰዉ ሥራ አይሰራም፣ ለምን ትላላችሁ!”
የፖለቲካ ምፀት ሲያምረው ደግሞ፤
ዐይነ ስውር ድንጋይ ወርውሮ፣ ጠላቱን ስቶ ወዳጁን መታ፡፡
“ምነው? ወዳጅህን? ወዳጅህ ነኝ እኮ!” ቢለው፤
“ዝምበል፡፡ ዋናው አለመሳታችን ነው!” አለ ይባላል፤ ይላል፡፡