Administrator

Administrator

       የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከኪነጥበብ ሙያ ማህበራት ጋር በመተባበር በአራት ዘርፎች የጥበብ ባለሙያዎችን አወዳድሮ ሊሸልም እንደሆነ ለአዲስ አድማስ ገለፀ፡፡
በድርሰት፣ ሙዚቃ፣ ስዕልና ፊልም ዘርፎች ለሚካሄደው ውድድር ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከአገር አቀፍ የሙያ ማህበራት ጋር በመሆን ለየዘርፉ አስር እጩ ተሸላሚዎችን አቅርቧል፡፡
ከየዘርፉ ሦስት አሸናፊዋች የ”ሽልማት ለጥበብ 2006” ተሸላሚ እንደሚሆኑ የገለፀው ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፤ ህብረተሰቡ ከእያንዳንዱ ዘርፍ ሦስት (በደረጃ ቅደም ተከተል) እጩ ተሸላሚዎችን በSMS 8181 መስመር መምረጥ እንደሚችል አስታውቋል፡፡
በአገሪቱ የሚገኙ የኤሌክትሮኒክስና የህትመት ሚዲያዎችም ከየዘርፉ የሚመርጧቸውን እጩ ተሸላሚዎች በተላከላቸው ቅጽ ሞልተው እንደሚልኩ ታውቋል፡፡ ከየጥበብ ዘርፉ የተመረጡ ዳኞችም በምርጫው የሚሳተፉ ሲሆን የሦስቱ ወገኖች ነጥብ ተደምሮ አሸናፊዎቹ እንደሚለዩ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የላከው መግለጫ ይጠቁማል፡፡
ለኪነጥበብ ባለሙያዎች እውቅና በመስጠት ጥበብን የሚያበረታታ ነው የተባለው ሽልማት በመጪው ጳጉሜ 1 ለአሸናፊዎች እንደሚሰጥ ለማወቅ ተችሏል፡፡  

በስዕልና ቅርፃ ቅርጽ ዘርፍ ዕጩ ተወዳዳሪዎች ድምጽ መስጫ ቅጽ
ስም         የSMS ቁጥር     ድምጽ
መዝገቡ ተሰማ     Vote 100
አለፈለገ ሰላም     Vote 101
ኤልያስ ስሜ     Vote 102
በቀለ መኮንን     Vote 103
ዳዊት አበበ         Vote 104
ወርቁ ጐሹ         Vote 105
ሚካኤል ፀጋው     Vote 106
ብስራት ሺባባው     Vote 107
ታደሰ መስፍን     Vote 108
አስኒ ጋለሪ         Vote 109

በሙዚቃ ዘርፍ እጩ ተወዳዳሪዎች  
 ስም         የSMS ቁጥር     ድምጽ
አስቴር አወቀ     Vote 200
ኩኩ ሰብስቤ     Vote 201
ታደለ ገመቹ     Vote 202    
ፀጋዬ እሸቱ                 Vote 203
ሚካኤል በላይነህ    Vote 204
ግርማ ተፈራ     Vote 205
አብረሃም ገ/መድህን    Vote 206
አበባ ደሳለኝ     Vote 207
ጃሉድ አወል    Vote 208
ቴዎድሮስ ካሳሁን     Vote 209

በፊልም ዘርፍ እጩ ተወዳዳሪዎች
ስም         የSMS ቁጥር     ድምጽ
ዳይናማይት     Vote 300
ያልታሰበው         Vote 301
ቀሚስ የለበስኩ’ለት    Vote 302
ረቡኒ        Vote 303
አይራቅ         Vote 304
ኒሻን        Vote 305
400 ፍቅር         Vote 306
ገዳይ ሲያረፍድ    Vote 307
የሎሚ ሽታ         Vote 308
የመጨረሻዋ ቀሚስ     Vote 309

በስነፅሁፍ ዘርፍ እጩ ተወዳዳሪዎች
ስም             የSMS ቁጥር     ድምጽ
ደራሲ ይልማ ሀብተየስ        Vote 400
ደራሲ መስፍን ሀብተማርያም     Vote 401
ደራሲ ታደሰ  ሊቨን        Vote 402
ደራሲ ሀይለመለኮት መዋል    Vote 403
ደራሲ ፀሐይ መላኩ        Vote 404
ደራሲ እንዳለጌታ ከበደ        Vote 405
ደራሲ አያልነህ ሙላት        Vote 406
ደራሲ የዝና ወርቁ        Vote 407
ደራሲ ኢሳያስ ወርዶፋ         Vote 408
ደራሲ አስፋው ዳምጤ         Vote 419

ከዕለታት አንድ ቀን ሁለት ትናንሽ ልጆች ወደ ት/ቤት እየሄዱ ይጨዋወታሉ። የአንደኛው ልጅ አባት ወፍራም ናቸው፡፡ በዛ ላይ ሀብታም ናቸው፡፡ ትልቅ ህንፃም ይገነባሉ፡፡ የሁለተኛው ልጅ አባት ምስኪን ናቸው፡፡ ከሲታ ናቸው፡፡ በአንዲት የጭቃ ቤት ነው የሚኖሩት፡፡
የሀብታሙ ልጅ - የእኛን ፎቅ አየኸው? ሰማይ ሊነካ ነው!
የደሀው ልጅ - አዎ፣ ታድላችኋል እናንተ!
የሀብታሙ ልጅ - እናንተ ለምን እንደኛ ፎቅ  አትሰሩም?
የደሀው ልጅ - እኔንጃ!
የሀብታሙ ልጅ - ገንዘብ የላችሁም?
የደሀው ልጅ - እኔ እንጃ፡፡ ቆይ አባቴን እጠይቃለሁ፡፡
የሀብታሙ ልጅ - የእኔ አባት ወፍራም ነው
የደሀው ልጅ - የእኔ አባት ግን በጣም ቀጭን ነው
የሀብታሙ ልጅ - ለምንድነው አባትህ የከሱት? ምግብ አትበሉም እንዴ?
የደሀው ልጅ - ኧረ እንበላለን፡፡ ግን እንጃ አባቴ ቀጭን ነው፡፡
የሀብታሙ ልጅ - ታዲያ ለምን ከሱ?
የደሀው ልጅ - እኔንጃ ቆይ እቤት ስደርስ እጠይቀዋለሁ፡፡
እኒህ ልጆች ሁሌ እንዲህ እንዲህ እያወሩ ት/ቤት ይሄዳሉ፡፡ በኋላም ተመልሰው ወደቤት ሲሄዱ እንደዚሁ እያወሩ ወደ ቤት ይመለሳሉ፡፡
ደሀው ልጅ ቤት ሲደርስ ለአባቱ፡-
“አባዬ?”
“ወይ ልጄ?”
“ጓደኛዬ ሁል ቀን እኛ ትልቅ የግንብ ፎቅ ቤት ነው ያለን፡፡ እናንተ ግን ጭቃ ቤት ነው ያላችሁ፡፡ ደሞ ያንተ አባት ቀጭን ናቸው፡፡ የእኔ አባት ግን ወፍራም ናቸው ይለኛል፡፡ በጣም ያበሽቀኛል፡፡ ይሄ ለምን ሆነ አባባ?”
አባትየውም፣
“አይዞህ ልጄ፡፡ አየህ እነሱ ያን የሚያክል ፎቅ የገነቡት ገንዘብ ከባንክ ተበድረው ነው። እኛ በራሳችን ነው የሰራነው፡፡ ስለውፍረትም ያልከው፤ ማን ያውቃል? የወፈረ ሁሉ ጤነኛ፣ የከሳ ሁሉ በሽተኛ አይምሰልህ፡፡ “ዕዳ የሌለበትን ድህነት እና በሽታ የሌለበትን ክሳት የሚያህል ነገር የለም!” አለው፡፡
                                         *           *              *
“La v’ertit‘e est de la buche des enfants” ይላሉ ፈረንሳዮች፡፡ ዕውነት ያለው ህፃናት አፍ ውስጥ ነው፤ ማለታቸው ነው፡፡ ህፃናቱ የሚያዩትን የተጨበጠ ዕውነት አወሩ፡፡ ውስጡ ያለውን ሚስጥር አባቶቹ ያውቃሉ፡፡ ላይ ላዩን ትላልቅ የሚመስል፣ ላይ ላዩን ያሸበረቀ የሚመስል፣ ውስጡ ሲታይ ግን በሙስና የተሞላ አያሌ ሀብት በሀገራችን ይታያል፡፡ እስኪታወቅ እንጂ አንድ ቀን ህዝብ ያወቀ የጠየቀ ዕለት ለውርደት መዳረግ አይቀሬ ነው፡፡
ሙያው ሌላ፣ ሀብቱ ሌላ የሆነ አያሌ ሰው አለ፡፡ ከስውር ምዝበራ ወደግልፅ ሌብነት የተሸጋገረ ዐይን-አውጣ ሙስና አሳሳቢ የሀገር ድቀትን ማምጣቱ አይቀሬ ነው፡፡ ከግለሰብ ሙስና ወደ ቡድን ሙስና፣ ከቡድን ሙስና ወደ ድርጅታዊ/ተቋማዊ ሙስና፣  እየተሸጋገረ ያለ ሙስና በዚያው በትራንስፎርሜሽን ንፍቀ-ክበብ ውስጥ የታቀፈ በመሆኑ በቀላሉ የማይመነጠር የአረም እሾክ ነው፡፡ ዱሮ “በቀይ ካባ ስውር ዳባ” እንደሚባለው መሆኑ ነው፡፡ ከዚህም ይሰውረን! ከሁሉም በላይ ደግሞ A Law - maker is a law – breaker (አጥር - አጣሪ አጥር - ሰባሪ እንዲሉ) ሲሆን አሳሳቢ ነው፡፡ Who guard the guards ጠባቂዎቹንስ ማን ይጠብቃቸዋል? እንዲሉ ፈረንጆች፤ ይሄም አሳሳቢ ጉዳይ ነው! ከዚህም ይሰውረን፡፡
የአፍሪካ ኢኮኖሚ ዕድገት የ2014 ዓ.ም ሪፖርት “ለአፍሪካ የትራንስፎርሜሽን ዕድገት ኢንቨስትመንትን ማጫጫር” በሚለው ፅሁፍ፡-
“ኢንቨስትመንት የረዥም ጊዜን ዕድገትና ልማትን የሚሾፍር ዋና አቅም ነው፡፡ ምርታዊ አቅምን ይገነባል፡፡ ኢኮኖሚ መዋቅርን በሥር-ነቀል መልክ ይለውጣል፡፡ ሥራ የማስያዝ አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ድህነትን ይቀንሳል” ይልና፤ ሆኖም የአህጉሩ አማካይ የኢንቨስትመንት መጠን አሁንም እንደዚያው ዝቅ እንዳለ በመሆኑ የሀገራዊ ልማት ግቡን ለመምታት የሚያስችለውን ያህል ሊሆን አልቻለም፡፡ ስለሆነም በዚህ ከቀጠለ የአፍሪካ ቅርብ ጊዜ ልማት ተሰባሪ ነው፣ ሸውሸዌ (fragile) ነው” ይላል፡፡ የጉዳዩ አንኳርም ሀገራዊና ዓለምአቀፍ ፖሊሲን ማጣጣም ነው፤ ብሎ ይደመድመዋል፡፡ የሀገራችን የኢኮኖሚ ዕውቀት ባለቤቶች በአግባቡ የመጠቀምን እስትራቴጂ ስራዬ ብሎ፣ ይሆነኝ ብሎ መያዝ ብልህነት ነው፡፡ አለበለዚያ ኢኮኖሚያችን እንኳን ዘላቂ ሊሆን ለእለቱም ተሰባሪ ነው የሚሆነው፡፡
ጥቂት ከበርቴዎች በባንክ ብድር የሚገነቡዋቸው ህንፃዎች ብድራቸውን ለመመለስ የማይችሉበት አረንቋ ውስጥ ገብተው ውስጡን ለቄስ መሆናቸውን ባንክ ከሚያወጣቸው ጨረታዎች ለመገንዘብ ዐይንን ማሸት አያስፈልግም፡፡ የሚያማምሩ መኖሪያ ቤቶች፣ ሰማይ ጠቀስ ፎቆች፣ ሰፊ ቦታ ላይ ተንጣለው የተንሰራፉ ግን ያላለቁ የግንባታ ግቢዎች የአስደንጋጭ ዕዳ ባለቤቶች መሆናቸው፤ አልፎ ተርፎም ሙስና ውስጥ የተዘፈቁት ሲጋለጡ ሲታይ እጅግ አሳዛኝ አገር ውስጥ እንደምንኖር እንገነዘባለን፡፡ አንዱ በላቡ ለመኖር ይፍጨረጨራል፤ ሌላው “በጥበቡ” ገንዘብ እየመዘበረ ፎቅ ይሰራል፡፡ ሁለቱም ዜጋ ይባላሉ! ዞሮ ዞሮ ሙስና መጋለጡ ስለማይቀር ጤና ይነሳል! ከዚህ ይሰውረን፡፡ “ዕዳ የሌለበትን ድህነት እና በሽታ የሌለበትን ክሳት የሚያህል ነገር የለም!” የሚባለው ለዚህ ነው፡፡






Saturday, 16 August 2014 10:34

ኧረ ተው ኢህአዴግ ተረጋጋ!

“ዴዣ ቩ” - በአምስት አመቱ የተደገመ ታሪክ የጋዜጠኞችን ማሰርና ማሳደድ፤ ንግድ ቤቶችን ማሸግና ማዋከብ

የ2001 ዓ.ም ዘመቻ - ለ2002 ምርጫ?
ዘመቻው የተጀመረው በአዲስ ዘመን ላይ በወጡ ፅሁፎች ነበር። “የውጭ ሃይሎች በአገራችን ጉዳይ ጣልቃ እየገቡ ነው” በሚል ውግዘት ዩኤስአይዲ ላይ ጣት ከመቀሰር ቢነሳም፤ ብዙም ሳይቆይ ነው ነፃ የግል ጋዜጦች ላይ በማነጣጠር ዘመቻ የተካሄደው። ከዚያ ኢቴቪ “ጥናታዊ ዘገባ” ሰርቻለሁ ብሎ በወቅቱ ሲታተሙ የነበሩ ጋዜጦችን የኩነኔ መዓት አወረደባቸው - በአብዛኛው ከሕትመት የወጡ የድሮ ጋዜጦችን እያሳየ። ብዙም ሳይቆይ ወከባና እስር መጣ። የቪኦኤ ጋዜጠኛ ለበርካታ ቀናት እንደታሰረና የኤፒ ጋዜጠኛ እንዳይታሰር በመስጋት ከአገር እንደወጣ የሚያስታውሱ የሙያ ባልደረቦች እንደሚሉት፤ ወከባው የበረታው ግን በግል ጋዜጦች ላይ እንደነበር ይገልፃሉ - የአዲስ ነገር ጋዜጣ መዘጋትንና የጋዜጠኞቹ መሰደድን በመጥቀስ።
ከመነሻው ዩኤስአይዲ ላይ የተጀመረው ውግዘት ብዙ ባይዘልቅም፣ ወደ ሌሎች አለማቀፍ ድርጅቶች ተሸጋገረ እንጂ አልከሰመም። ውግዘቱ ብዙ አለማቀፍ ድርጅቶችን ቢያዳርስም፤ ዋናው ኢላማ ግን ሂዩማን ራይት ዎች ነበር። የኋላ ኋላም በአለም ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ፤ በሂዩማን ራይት ዎች ላይ ሰለማዊ ሰልፍ እስከመውጣት ተደርሷል።
የመንግስት ዘመቻ በፖለቲካ መስክ ላይ ብቻ ያተኮረ አልነበረም - በኢኮኖሚ መስክም ጭምር እንጂ። ከልክ ባለፈ የብር ህትመት ሳቢያ በመንግስት የተፈጠረው ከፍተኛ የዋጋ ንረት፣ በወቅቱ ከተከሰተው የዝናብ እጥረት ጋር ተዳምሮ በጣም አሳሳቢ ሆኖ ነበር። አሳዛኙ ነገር፤ ሁሉም ችግር በነጋዴዎች ላይ ተሳበበ። እናም፤ ነጋዴዎች አበሳቸውን እስኪያዩ ድረስ ዘመቻ ተካሂዶባቸዋል።
እነዚህ የ2001 ዓ.ም ዘመቻዎች ተገቢ ባይሆኑም፣ ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው ቢበዛም፤ “ምንም መነሻ አልነበራቸውም” ማለት አይደለም። አንደኛ፣ የ97 የምርጫ ቀውስ ገና መንፈሱ አልደበዘዘም ነበር። በዚያ ላይ ከአገር ውስጥና ከውጭ አገር መንግስት ላይ ቀላል የማይባሉ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ጫናዎች ወይም ፈተናዎች ተጋርጠው እንደነበር አይካድም። ከአገር ውስጥ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ፈተናዎች በተጨማሪ የሂዩማን ራይትስ ዎች ዘመቻ ራሱ ቀላል አልነበርም - በተለይ የኢትዮጵያ ጦር የሶማሊያ አክራሪዎችን ለመዋጋት ከተሰማራ በኋላ።
የኢትዮጵያ ጦር ስምሪት ከአሜሪካ ድጋፍ አግኝቷል የሚለው ስሜት ለኢህአዴግ እንዲያ ፈታኝ ይሆንበታል ብሎ ማን ገመተ? ከአሜሪካ መንግስት ጋር የሚተባበር አገር ላይ ክፉኛ ጥርሳቸውን የሚነክሱት ሂዩማን ራይትስ ዎች እና ኒው ዮርክ ታይምስ ናቸው፤ ኢህአዴግን ከግራና ከቀኝ ወጥረው የያዙት። በዚያው ልክ፤ የአሜሪካና የአውሮፓ መንግስታት ጫናም የሚናቅ አልነበረም። ከዳያስፖራ ፖለቲካው ጋር በአገር ውስጥ የ”መድረክ” ተቀናቃኝነት፣ የዋጋ ንረት፣ የረሃብ አደጋ ... ኢህአዴግ፤ በእነዚህ ተደራራቢ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ፈተናዎች ምክንያት ስለተጨናነቀ ሊሆን ይችላል ወደ አላስፈላጊ ዘመቻ ያመራው።
አሳዛኙ ነገር ምን መሰላችሁ? የያኔዎቹ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ፈተናዎች ዛሬ ቢደበዝዙም፣ ልክ እንደያኔው፣ በነፃ ፕሬስ ላይ የእስር እና የስደት፤ እንዲሁም በቢዝነስ መስክ የእሸጋና የወከባ ታሪክ ዛሬም እየተደገመ ነው።

የ2006 ዓ.ም ዘመቻ - ለ2007 ምርጫ?
አለማቀፉን የፕሬስ ነፃነት ተቋም (አርቲክል 19ን) በማውገዝ የተለኮሰው የዘንድሮ ዘመቻ፤ አዲስ ዘመን የግል መፅሔቶችን በመወንጀል ባሰራጨው “ጥናታዊ ሪፖርት” ነው ጎልቶ የወጣው። በኢቴቪ የተሰራጩትንም ዘገባዎች ተመልክታችኋል። ዘጠኝ ፀሐፊዎችና ጋዜጠኞች ሲታሰሩም ታዝበናል። ሰሞኑን ደግሞ ጋዜጠኞች ሲሰደዱና ሕትመቶች ሲቋረጡ እያየን ነው።
ከላይ እንደጠቀስኩት፤ ያኔ በ2001 ኢህአዴግ ብርድ ብርድ ቢለው አይገርምም። የ97ቱ ትዝታ ገና አልደበዘዘም። 2001 ላይ በሶማሌ ክልል ከፍተኛ ግጭት ነበር። የጎዳና ላይ አመፅ፣ በወቅቱ ገና ፋሽኑ አላለፈበትም። በአገር ውስጥ ቅጥ ባጣ የብር ህትመት ከተፈጠረው የዋጋ ንረት በተጨማሪ፣ የረሃብ አደጋው ታክሎበት፤ በዚያ ላይ አለማቀፍ የኢኮኖሚ ቀውስ ተደምሮበት፤ የአገሬው ኢኮኖሚ ከፍተኛ አደጋ ላይ ነበር።
ዘንድሮ ግን ያን ያህልም የሚያሰጋ የዋጋ ንረት አልተከሰተም። የመንግስት ሰራተኞች የደሞዝ ጭማሪ ስለተደረገ የዋጋ ንረት ይከሰታል በሚል ሰፊ የፕሮፓጋንዳና የማስፈራሪያ ዘመቻ ቢካሄድም፤ እንደተለመደው የቢዝነስ ስራን በማውገዝ የንግድ ቤቶችን በገፍ የማሸግ ዘመቻ ቢካሄድም፤ ለዚህ መነሻ የሚሆን ሰበብ እንኳ የለም። የማዕከላዊ ስታትስቲክስ የሐምሌ ወር ሪፖርት እንደሚያሳየው፤ ከሰኔ ወር የሚያንስ እንጂ የሚበልጥ የዋጋ ንረት አልተፈጠረም። ደግሞም አይገርምም። መንግስት አለቅጥ የብር ኖት ከማተም እስከተቆጠበ ድረስ፤ ከፍተኛ የዋጋ ንረት ሊከሰት አይችልም።
ዘንድሮ ከ2001 ዓ.ም የሚለየው፣ አስደንጋጭ የዋጋ ንረት ባለመፈጠሩ ብቻ አይደለም። ትልቅ የረሃብ አደጋም አልተፈጠረም። በእርግጥ የኑሮ ችግር እንደያኔው ዛሬም አለ። ሰባት ሚሊዮን ገደማ የሴፍቲ ኔት ተረጂዎችና ደራሽ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ከ6 ሚሊዮን በላይ ሰዎች አሉ። እንደምንም ብለው ኑሯቸውን የሚገፉ ችግረኞችም ቁጥራቸው ጥቂት አይደለም። ነገር ግን፤ የዘንድሮው ረሃብ፣ ችግርና ድህነት ካለፉት አመታት ይሻል እንደሆነ እንጂ አይብስም።

የፖለቲካ ጫና እና ፈተናስ - ድሮና ዘንድሮ
በ2001 ዓ.ም፤ ምንም እንኳ ከምርጫ 97 ፉክክር ጋር የሚስተካከል ባይሆንም፤ በስምንት የፖለቲካ ፓርቲዎች የተመሰረተው “መድረክ”፤ ጠንካራ እንቅስቃሴ ያካሂድ ነበር። ከመድረክ በተጨማሪ፤ የዜጎችን ትኩረት ለመሳብ የሚጣጣሩ አዳዲስ ፓርቲዎች ብቅ ብቅ ይሉ ነበር። ከያኔው ጋር ሲነፃፀር፤ ዘንድሮ ኢህአዴግን ክፉኛ የሚቀናቀን ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ የለም። አዳዲስ ፓርቲዎችንም እያየን አይደለም።
መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ ነፃ ማህበራትና ነፃ ጋዜጦች ለመንግስት እንደ ፈተና የሚቆጠሩ ከሆነም፤ ከ2001 ወዲህ ቁጥራቸው በእጅጉ ቀንሷል፤ ህልውናቸውን ያላጡትም ተዳክመዋል። በአጭሩ፤ በአገር ውስጥ ኢህአዴግን ለስጋት የሚዳርግ ከባድ የፖለቲካ ጫና ወይም ፈተና አይታይም።
ከአገር ውጭም  ያን ያህል የጎላ ስጋት የለም። በሶማሊያ በኩል የነበረው የአልሸባብ ስጋት ረግቧል። በኤርትራ በኩል፤ ብዙም እንቅስቃሴ አይስተዋልም። በእርግጥ በአሜሪካ፣ በአውሮፓና በደቡብ አፍሪካ የዳያስፖራ ፖለቲካው የተለወጠና የተጠናከረ ይመስላል። ግን ብዙም አልተለወጠም። በ1996 ዓ.ም “ህብረት” ለመፍጠር ሲሰባሰቡ የነበሩት የተቃዋሚ ፓርቲዎች ብዛትና እንቅስቃሴ ምን ያህል ከፍተኛ እንደነበር ማስታወስ እንችላለን። የቅንጅት መሪዎች ከእስር ከተፈቱ በኋላ፣ እነ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ እና ሌሎች ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ በውጭ አገራት ያካሄዱት እንቅስቃሴም ከፍተኛ ነበር። የዳያስፖራ ፖለቲካ እንደወትሮው፣ ለገዢው ፓርቲ የሚመች ባይሆንም፣ ዛሬ ከድሮው የባሰ ፈታኝ ሆኗል የሚባልለት አይደለም።
የውጭ መንግስታትና አለማቀፍ ተቋማትማ፤ በአብዛኛው ድምፃቸው ጠፍቷል ማለት ይቻላል። አንዳንዶቹ ድምፃቸውን ለማሰማት ቢሞክሩም ያን ያህልም ብዙ ጆሮ እያገኙ አይደለም። በ2001 ዓ.ም ላይ ታች እያሉ ድምፃቸውን አጉልተው ሲያሰሙ የነበሩ አለማቀፍ ተቋማትን በጥቂቱ እናስታውሳቸው።

የውጭ መንግስታትና አለማቀፍ ተቋማት - ድሮና ዘንድሮ
“በሶማሌ ክልል መንግስት ጭፍጨፋ አካሂዷል” ከሚለው የሂዩማን ራይትስ ዎች ሪፖርት ጀምሮ፤ የኒውዮርክ ታይምስ ተከታታይ የትችት ዘገባዎችን ጨምሮ በ2001 ዓ.ም የውጭ መንግስታትና የአለማቀፍ ተቋማት ጫና ለኢህአዴግ እጅግ ከባድ ሆኖበት ነበር።
“መንግስት የአገሬውን ረሃብ ደብቋል” የሚሉ የረድኤት ድርጅቶች የሚያሰራጩት ተከታታይ መግለጫ ታክሎበት፤ “ገዢው ፓርቲ በ77ቱ ረሃብ ለእርዳታ የመጣ ገንዘብ ለመሳሪያ መግዣ አውሎታል” የሚል የቢቢሲ ሰፊ ዘገባ፣ “በኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ተስፋ ጨልሟል” የሚል የኢንተርናሽናል ክራይስስ ግሩፕ ሪፖርት፣ ከዚያም “የሰብአዊ መብት ረገጣ ተባብሷል” የሚል የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያቤት ሪፖርት... የያኔው ጫና ቀላል አልነበረም። የአሜሪካ ኮንግረስ በኢትዮጵያ ላይ ማዕቀብ ለመጣል ያወጣውና በእንጥልጥል የነበረው  ኤች.አር 2003 የተሰኘው ህግም ለኢህአዴግ እጅግ ፈታኝ መሆኑ አልቀረም።
የዚያ ሁሉ ርብርብ መነሻ፤ “ለውጥ ማምጣት እንችላለን” የሚል ተስፋ ነው። “መንግስት ላይ ከፍተኛ ጫና በማሳደር ወይም ተቃውሞ በማበረታታት፤  ገዢው ፓርቲ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር በድርድር ተቻችሎ እንዲሰራ መገፋፋትና ለውጥ ማምጣት ይቻላል” የሚል አስተሳሰብ በስፋት ይታይ ነበር - በውጭ መንግስታትና በአለማቀፍ ተቋማት ዘንድ።
ይህ አስተሳሰብ ግን፤ ባለፉት አምስት አመታት ተሸርሽሯል። አንደኛ፣ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በአፍሪካም ሆነ በሌሎች አገራት ላይ ጫና የማሳደር ፍላጎት የላቸውም። ሁለተኛ፣ የአሜሪካና የአውሮፓ አገራት በኢኮኖሚ ቀውስ ስለተመቱ፣ አብዛኞቹ መንግስታት በራሳቸው ውስብስብ ችግር ውስጥ ተጠምደዋል። በመጨረሻ ደግሞ፣ በኪሳራ የተደመደመው የአረብ አገራት አብዮት መጣ።
በእርግጥ፤ “በአረብ አገራት ውስጥ የነፃነት ለውጥ ማምጣት ይቻላል” የሚለው የምዕራብ መንግስታት አስተሳሰብ እየተሸረሸረ የመጣው፣ በአፍጋኒስታን እና በኢራቅ ጦርነት ማግስት ነው። በአፍጋኒስታን የአክራሪው የታሊባን አገዛዝ ቢወገድም፤ በኢራቅ የሳዳም ሁሴን አምባገነንነት ቢወገድም፣ የነፃነት መንፈስ አልሰፈነም። በሃይማኖት ወይም በጎሳ እየተቧደኑ ስልጣን ለመያዝ ሲጨፋጨፉ፣ በአንዳች አጋጣሚ ስልጣን ላይ የወጣ ቡድን አምባገነንነትንና ግጭትን ለማስፈን ሲጣጣር ነው የታየው። በሁለተኛው የአለም ጦርነት ማግስት፣ በጃፓን እና በምዕራብ ጀርመን ላይ የተፈጠረው የነፃነት ለውጥ በአፍጋኒስታንና በኢራቅ አልተደገመም።
ምናልባት ጥሩ ለውጥ የሚመጣው፣ በውጭ ሃይል ጣልቃ ገብነት ሳይሆን፣ በፖላንድ እና በቼክ እንደታየው፣ የአገሬው ህዝብ በሚያካሂደው የተቃውሞ እንቅስቃሴ ይሆን እንዴ? በግብፅ፣ በሊቢያ፣ በቱኒዚያ፣ በሶሪያ የተቀሰቀሰው የህዝብ ተቃውሞ፣ “የፀደይ አብዮት” በሚል ስያሜ ተስፋ የተጣለበትም በዚህ ምክንያት ነበር - ለውጥ ያመጣል በሚል። ደግሞስ፣ እንደ ሙዓመር ጋዳፊ የመሳሰሉ አምባገነኖች ከስልጣን ሲወገዱ፣ ብዙዎች ቢደሰቱ የተስፋ ብርሃን ቢታያቸው ምን ይገርማል?
ነገር ግን በፓላንድ እና በቼክ እውን ለመሆን የበቃው የነፃነት ለውጥ፣ በእነ ግብፅ እና በእነ ሶሪያ አልተደገመም። ሊቢያና ሶሪያ፣ በደርዘን በሚቆጠሩ ታጣቂ ቡድኖችና ጎራዎች አማካኝነት የጦርነትና የግጭት ማጥ ውስጥ ገብተዋል። በቱኒዚያና በግብፅ፤ ለወጉ ያህል የፖለቲካ ምርጫዎች ተካሂደዋል። ነገር ግን፤ “ለውጥ” እና “ምርጫ”፣ በቀጥታ “የነፃነት ለውጥ” እና “የነፃነት ምርጫ” ይሆናሉ ማለት አይደለም። በግብፅ፣ ምርጫውን ያሸነፉት የሃይማኖት አክራሪዎች ናቸው። የጦር ሃይል ኮሎኔል በነበሩት በሁስኒ ሙባረክ ከሚመራው መንግስት ይልቅ፤ በመሃመድ ሙርሲ የሚመራው የአክራሪዎች መንግስት፣ በአምባገነንነት የባሰ ሆኖ አረፈው። አሁን የመንግስት ስልጣን ወደ ጦር ሃይል ተመልሷል - በጄኔራል አልሲሲ።
በሊቢያም እንዲሁ፤ የነፃነት ተስፋ አይታይም። ተቀናቃኞቹ ቡድኖች፣ አንድም አክራሪዎች ናቸው፤ አልያም በቀድሞ የጦር ጄኔራል ስር የተሰለፉ የስልጣን ጥመኛ ቡድኖች ናቸው፤ ወይም ደግሞ በጎሳ የተቧደኑ ታጣቂዎች። የሶሪያም ተመሳሳይ ነው። የኢራቅም እንዲሁ። በአጭሩ፣ መልካም የነፃነት ለውጥ አልመጣም። በዚህም ምክንያት፤ “መልካም ለውጥ እንዲመጣ መገፋፋትና ጫና ማሳደር እንችላለን” የሚለው የምዕራብ መንግስታት የቀድሞ ዝንባሌ ዛሬ ተሸርሽሯል።
እናም፣ ጋዜጠኞች በገፍ ሲታሰሩ ወይም ሲሰደዱ፣ በተቃውሞ ሰልፍ ላይ ሰዎች ሲገደሉ ወይም የፓርቲዎች ፉክክር የማይታይበት ምርጫ ሲካሄድ፣ አለማቀፍ ተቋማትና የምዕራብ መንግስታት ዛሬ ዛሬ፣ ብዙም ድምፃቸውን አያሰሙም። የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ ስለ ጋዜጠኞችና ፀሐፊዎች መታሰር ሲጠየቁ የሰጡትን ምላሽ ማየት ይቻላል።
እንደ ድሮ ቢሆን፤ ጆን ኬሪ እስኪጠየቁ ድረስ ባልጠበቁ ነበር። የጋዜጠኞችን እስር እንደሚያወግዙ በመግለፅ ከእስር እንዲለቀቁ ጥሪ ያቀርቡ ነበር። ዛሬ ግን እንደ ድሮ አይደለም። ጆን ኬሪ እዚሁ አገር መጥተው ስለ ጋዜጠኞች መታሰር አልተናገሩም። ትንፍሽ አላሉም። ጥያቄ ሲቀርብላቸውም፤ “የጋዜጠኞቹና የፀሐፊዎቹ መታሰር ያሳስበናል...” የሚል ምላሽ ነው የሰጡት። በቃ? “ያሳስበናል” በሚል ነው ጉዳዩን ያለፉት።
ከአገር ውጭ የሚመጣ ጫና ተመናምኗል። እንደ ሂዩማን ራይትስ ዎች የመሳሰሉ አለማቀፍ ተቋማት፣ በየጊዜው እንደተለመደው መግለጫና ሪፖርት ማውጣት አቁመዋል ማለት አይደለም። ነገር ግን፤ የአሜሪካና የአውሮፓ መንግስታትን ወደ እርምጃ የማነሳሳት አቅማቸው ተዳክሟል። ምናለፋችሁ? ከአሜሪካና ከአውሮፓ መንግስታት እንዲሁም ከአለማቀፍ ተቋማት ይሰነዘር የነበረው ግፊትና ጫና፣ ዛሬ ከሞላ ጎደል ከስሟል ማለት ይቻላል። “ያሳስበናል” ከሚል የአንድ ደቂቃ መግለጫ ያለፈ ጫና እየጠፋ መጥቷል።
በአጭሩ፤ ከአገር ውስጥና ከውጭ አገር በ2001 ዓ.ም ኢህአዴግን ሲያስጨንቁ የነበሩ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ፈተናዎች፣ ዛሬ በአብዛኛው ጠፍተዋል፤ ወይም ደብዝዘዋል። እና ለምድነው የያኔው የወከባ ታሪክ ዛሬ የሚደገመው? ኧረ ተው ኢህአዴግ ተረጋጋ!





  በምስራቅ አፍሪካ አገራት በተከሰተው የዝናብ እጥረትና የእርስበርስ ግጭቶች ሳቢያ የምግብ እጥረት መፈጠሩን የገለፀው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤  በቀጠናው ከ14 ሚሊዮን በላይ ህዝብ የምግብ እርዳታ እንደሚያስፈልገው አስታወቀ፡፡
የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር የምስራቅ አፍሪካ ቃል አቀባይ ማቲው ኮንዌይን ጠቅሶ የዘገበው አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ፤ በቀጠናው የሚታየው የምግብ እጥረት ችግር እየከፋ የመጣ ሲሆን በዘጠኝ አገራት የሚገኙ 14 ነጥብ 4 ሚሊዮን አፍሪካውያን የምግብ እርዳታ ካላገኙ የከፋ ችግር ይደርሳል ብሏል፡፡
የምግብ እርዳታ ከሚያስፈልጋቸው ህዝቦች አብዛኞቹ የሚኖሩት በጦርነት በመታመስ ላይ ባለችው ደቡብ ሱዳንና ሶማሊያ ውስጥ እንደሆነ የጠቆመው አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ፤ በተደጋጋሚ በድርቅ የሚመታው የኬንያ ሰሜናዊ ክፍልም የችግሩ ተጠቂ እንደሆነ አመልክቷል፡፡በሱዳን 5 ሚሊዮን፣ በደቡብ ሱዳን 3.5 ሚሊዮን በኢትዮጵያ 2 ነጥብ 7 ሚሊዮን፣ በጅቡቲ 120ሺ ያህል ዜጎች የምግብ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል ተብሏል፡፡
ከሶስት አመት በፊት በአካባቢው ተመሳሳይ ችግር ተከስቶ እንደነበር ያስታወሱት የኦክስፋም ሪጅናል ዳይሬክተር ፍራን ኢኩኢዛ በበኩላቸው፤ በወቅቱ ከደረሰው ጥፋት በመማር በአፋጣኝ ለችግሩ ምላሽ መስጠት ከተቻለ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ከሞት መታደግና በሚሊዮኖች የሚቆጠሩትንም ከረሃብ ስቃይ  ማዳን እንደሚቻል ተናግረዋል፡፡

    ኢትዮጵያውያን ስደተኞችን በህገወጥ መንገድ ወደ ማላዊ አስገብቷል በሚል ተከስሶ ጉዳዩ በፍ/ቤቱ እየታየ የነበረውን ባሻ አድነው የተባለ ኢትዮጵያዊ ስደተኛ ከፍርድ እንዲያመልጥ አድርገዋል የተባሉት የማላዊ የአገር ውስጥ ጉዳዮችና የደህንነት ሚኒስትር ፖል ቺቢንጉና የኢሚግሬሽን ጉዳዮች ዋና ሃላፊ ሁድሰን ማንካዋላ መታሰራቸውን ኒያሳ ታይምስ የተሰኘው ድረገፅ ዘገበ፡፡
የኢትዮጵያዊው ስደተኛ የክስ ሂደት ሳይጠናቀቅና ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ሳይሰጥ ተከሳሹን በሙስና ወደ አገሩ እንዲያመልጥ በማድረግ ወንጀል ተሳትፈዋል በሚል የተከሰሱትን ሁለት ባለስልጣናት ጉዳይ የሙዙዙ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት እያጣራ ሲሆን ባለስልጣናቱ ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ የእስራት ቅጣት ሊጣልባቸው እንደሚችል ዘገባው አመልክቷል፡፡ ከሁለቱ ባለስልጣናት ጋር ተባብረዋል የተባሉ ሶስት የመንግስት ኃላፊዎችም ክስ እንደተመሰረተባቸው ተጠቁሟል፡፡
ባለፈው ግንቦት ከሌሎች ሁለት የማሊ ዜጎች ጋር በመተባበር ዘጠኝ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በህገወጥ መንገድ ድንበር አቋርጠው ወደ ማሊያዊ እንዲገቡ አድርጓል በሚል የተከሰሰውን ኢትዮጵያዊው ስደተኛ ባሻ አድነው ጉዳይ ሲመረምር የቆየው ፍ/ቤቱ፤ ባለፈው ማክሰኞ የእስር ትዕዛዝ ያስተላለፈበት ሲሆን ግለሰቡ ግን ባለስልጣናቱ ተሳትፈውበታል ተብሎ በተጠረጠረ ሙስና ከአገር እንዲወጣ መደረጉ ተረጋግጧል፡፡
ፍርድ ቤቱ ክስ የመሰረተው በሚኒስትሩ፣ በሁለት የኢሚግሬሽን ሃላፊዎች፣ ተጠርጣሪውን በቁጥጥር ውስጥ ባዋለው የፖሊስ መኮንንና ወደ ፍርድ ቤት ሲያመላልሰው በነበረው የስደተኞች ጉዳይ ሃላፊ ላይ ሲሆን ተጠርጣሪዎች የፊታችን ሰኞ ፍርድ ቤት ቀርበው ቃላቸውን እንዲሰጡ ታዝዟል፡፡
ባለስልጣናቱ በተጠረጠሩበት ወንጀል ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ስልጣን ከያዙ ወዲህ በሙስና የተያዙ የመጀመሪያዎቹ የመንግስት ባለስልጣናት እንደሚሆኑ የጠቆመው ዘገባው፤ ጉዳዩ አዲሱ አስተዳደር እንዲህ ያሉ ጉዳዮችን እንዴት እንደሚያስተናግድ የሚፈተንበት ይሆናል ብሏል፡፡
የኡጋንዳ ፖሊስ ካባላጋላ በተባለች ከተማ ዙሪያ ባደረገው ለሁለት ቀናት የዘለቀ አሰሳ፤ ሁለት ኢትዮጵያውያንንና አንድ ኡጋንዳዊን በሽብርተኝነት ጠርጥሮ በቁጥጥር ስር ማዋሉን ኒው ቪዥን የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ዘገበ፡፡
አበበ መኮንንና አስፋው ወንድወሰን የተባሉትን ኢትዮጵያውያንና ጁማ ሲምዋንጋ የተባለውን ኡጋንዳዊ ከአስር ቀናት በፊት በሽብርተኝነት ጠርጥሮ ማሰሩን የገለጸው ዘገባው፤ ግለሰቦቹ ከተያዙ በኋላ ጉራንጉር ውስጥ በተከራዩት መኖሪያ ቤታቸው ፍተሻ መደረጉን አስረድቷል፡፡
የአገሪቱ ፖሊስ ተጠርጣሪዎችን ከየት አግኝቶ በቁጥጥር ውስጥ እንዳዋላቸው የገለጸው ነገር የለም፡፡

     ታዋቂው ማይክሮሶፍት ኩባንያ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም ጋር በመተባበር ለ200 ሺ ኢትዮጵያውያን ስራ ፈጣሪዎች ድጋፍ የሚያደርግ ፕሮጀክት ሊጀምር እንደሆነ ተገለፀ፡፡
ኦል አፍሪካ ዶት ኮም እንደዘገበው፤ የኩባንያው የምስራቅ አፍሪካ ቅርንጫፍ በስራ ፈጠራ ዘርፍ የሚካሄደውን ልማት ለማሳደግ ከልማት ፕሮግራሙ ጋር በተፈራረመው የትብብር ስምምነት፣ የተመድ የልማት ፕሮግራም በአገሪቱ ድጋፍ ለሚያደርግላቸው 200 ሺ ስራ ፈጣሪዎች ስልጠናና ክትትልን ጨምሮ ዘርፈ ብዙ እገዛዎችን ያደርጋል፡፡
በስምምነቱ መሰረት፤ የኩባንያው በጎ ፈቃደኛ ስራ አስፈጻሚዎች ለኢትዮጵያውያኑ ስራ ፈጣሪዎች በስትራቴጂና በማርኬቲንግ ላይ

ያተኮረ ሙያዊ ስልጠናና ድጋፍ የሚያደርጉ ሲሆን፤ ምርጥ ስራ ፈጣሪዎችን የመደገፍ፣ ለ “ፎርአፍሪካ ኢንሺየቲቭ” የፈጠራ ሽልማት እንዲታጩ የማገዝና የኩባንያውን አጋዥ ሶፍትዌር ተጠቃሚ እንዲሆኑ የማስቻል ስራ ያከናውናሉ ተብሏል።
ባለሙያዎቹ ከዚህ በተጨማሪም ስራ ፈጣሪዎቹ ለወደፊት በማይክሮሶፍት የአነስተኛና መካከለኛ ተቋማት ማዕከል በኩል ምርቶችንና አገልግሎቶችን እንዲለዋወጡና አለማቀፍ እውቅና እንዲያገኙ እገዛ እንደሚያደርጉ ዘገባው አስረድቷል፡፡
አዲሱ የትብብር ስምምነት፣ ማይክሮሶፍት ኩባንያ የአፍሪካን ኢኮኖሚያዊ ልማት ለማፋጠንና የአገር በቀል ስራ ፈጣሪዎችን አቅም በመገንባት አህጉሪቱ በአለማቀፍ ደረጃ ያላትን ተወዳዳሪነት የማጎልበት ዓላማ ይዞ የሚንቀሳቀሰው “ፎርአፍሪካ ኢኒሺየቲቭ” የተሰኘ ፕሮግራም አካል እንደሆነም ተጠቁሟል፡፡

    የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋልያዎቹ የብራዚል ጉዞ  በ20ኛው ዓለም ዋንጫ  ተሳትፎ  ባይሳካም፤ ለሁለት ሳምንት ዝግጅት መሄዳቸው አልቀረም፡፡
በአሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ጥረት በብራዚል በካምፕ በአይነቱ የተለየ ዝግጅት የሚያደርጉት ዋልያዎቹ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ  ተሳታፊነት ብራዚልን በመርገጥ አስደናቂ ብቃት ያሳየችውን አልጄርያ ከመግጠማቸው በፊት ጥሩ ብቃት ላይ እንደሚደርሱ እየተነገረ  ነው፡፡ ከብራዚል ክለቦች ጋር የወዳጅነት ጨዋታ የሚያደርገው ብሄራዊ ቡድኑ  በቆይታው የሚያገኘው ጥቅም ያመዝናል። አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ቋሚ ተሰላፊ ቡድናቸውን ለመለየት ያሰቡ ይመስላል፡፡ ባሬቶ በሃላፊነቱ በቆዩባቸው ጊዜያት ቋሚ አምበል አለመሾማቸው ሙሉ ቋሚ ተሰላፊዎች አለመለየታቸውን ያመለክታል፡፡ ፍቅሩ ተፈራ፤ አበባው ቡጣቆ እና ፍፁም ገብረማርያም አምበሎች እንደሚሆኑ እየተገመተ ነው፡፡ አዳነ ግርማ፤ ሳላዲን ሰኢድና መስኡድ መሃመድም ለሃላፊነቱ ብቁ መሆናቸውም ይገለፃል፡፡ 19 አባላትን ያካተተው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን  የመጀመርያው ልዑክ ረቡዕ ወደ ብራዚል ተጉዟል፡፡ ቀሪዎቹ ዛሬ ይበራሉ፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በብራዚል በሚኖረው የ14 ቀናት ቆይታ 33 አባላት ያሉት ልዑክ ይኖረዋል። በብራዚሊያ የሚገኘው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በነገው ዕለት ከሰሜን ብራዚል ከመጣው ሬምዋ ከተባለ ክለብ ይጫወታል፡፡ የዛሬ ሳምንት ደግሞ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ጨዋታ አስተናግዶ በነበረው የማኔ ጋሪንቻ ስታድዬም ሁለተኛውን ጨዋታ ያደርጋል፡፡  ከ2 ሳምንት በኋላ  ደግሞ ሬዮ ግሬምዬ ከተባለ ክለብ ጋር ሶስተኛውን የወዳጅነት ጨዋታ ያደርጋል፡፡ ሦስቱም የብራዚል ክለቦች በአገሪቱ የክለብ ውድድር በ4ኛ ዲቪዚዮን የሚጫወቱ ናቸው፡፡ ጨዋታዎቹ አቋምን ከመፈተሽ ባሻገር ተጫዋቾቹን ለማስተዋወቅ ጥሩ እድል እንደሚፈጥር አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ተናግረዋል፡፡
በ2015 እኤአ ላይ ሞሮኮ ለምታስተናግደው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በሚካሄድ  የምድብ ማጣርያ የሚሳተፈው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከአልጄርያ ጋር  ከመጫወቱ በፊት ቢያንስ ስምንት የወዳጅነት ጨዋታዎች ሊያደርግ ይችላል፡፡ ዋልያዎቹ ባለፈው ሰሞን  በሉዋንዳ ላፓላንካ ኔግራስ ከተባለው የአንጎላ ብሄራዊ ቡድን ጋር በመጀመርያ የወዳጅነት ጨዋታቸው ተገናኝተው 1ለ0 ተሸንፈዋል፡፡
በሉዋንዳ 11 ዲ ኔቨምብሮ ስታድዬም በተደረገው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ አንጎላ ያሸነፈችው ፍሬዲ የተባለ ተጨዋች በ16ኛው ደቂቃ ላይ ባገባት ብቸኛ ግብ። የአንጎላው ፕሬዝዳንት ጆሴ ኤድዋርዶ ዶሳንቶስ የክብር እንግዳ ነበሩ፡፡
ከብራዚል መልስም  በነሀሴ ወር ሁለት የደርሶ መልስ የወዳጅነት ጨዋታዎችን ፈርኦኖቹ ከተባለው የግብፅ ብሄራዊ ቡድን ጋር ለማድረግ ቀጠሮ መያዙም አስታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በምድብ 2 የመጀመርያ የማጣርያ ጨዋታው ጳጉሜ 2 ላይ በአዲስ አበባ ስታድዬም ከአልጄርያ  ይገናኛል፡፡ አልጄርያና ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ የማጣርያ እና ዋና ውድድሮች 6 ጊዜ ተገናኝተዋል። እኩል አንዴ ተሸናንፈው በ4 ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል፡፡ በምድብ 2 ከአልጄርያ፤ ከማሊ እና ከኢትዮጵያ ጋር ማጣርያ የምትገባው አራተኛ ቡድን ማላዊ ሆናለች፡፡ ማላዊ ምድቡን የተቀላቀለችው በሁለተኛ ዙር ቅድመ ማጣርያ ቤኒን ጥላ በማለፍ ነው፡፡
በተያያዘ ዜና የሴካፋ ዋና ፀሃፊ ኒኮላስ ሙንሶኜ በሞሮኮው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመካከለኛው እና የምስራቅ ዞን አንድ ተወካይ መኖሩ አይቀርም ብለዋል። ከዞኑ አራት ቡድኖች በምድብ ማጣርያው የሚካፈሉ ሲሆን ኢትዮጵያ እና ሱዳን በቀጥታ ወደ ምድብ ሲገቡ በቅድመ ማጣርያ ያለፉት ደግሞ ሩዋንዳ እና ኡጋንዳ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ በማጣርያ  በሜዳዋ በምታደርጋቸው ጨዋታዎች ባለፈው ሁለት ዓመት ያሳየችው ብቃት ለጥንካሬዋ ምክንያት እንደሚሆን ኒኮላስ ሙንሶኜ ገልፀዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከወራት በኋላ የመካከከለኛው እና ምሰራቅአፍሪካ ሻምፒዮና አዘጋጅ እንደሆነች ይታወቃል።

         ቁልፍ መረጃዎችን እያወጣ በዓለማቀፍ ደረጃ ክፉኛ ሲያሳጣት የከረመውን ኤድዋርድ ስኖውደን የተባለ ግለሰብ አሳድዳ ለመያዝና ለመፋረድ ደፋ ቀና ማለቷን የቀጠለችው አሜሪካ፣ አሁን ደግሞ ከእሱ የባሰ የብሄራዊ ደህንነት መረጃዎቼን እየዘረፈ በማውጣት ጉድ የሚሰራኝ ሌላ ሚስጥር መንታፊ ግለሰብ መጥቶብኛል ስትል ባለፈው ረቡዕ በይፋ መናገሯን ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
ስኖውደን የሚያወጣቸውን መረጃዎች እያተመ ለንባብ በማብቃት የሚታወቀው ዘ ኢንተርሴፕት የተባለ የአገሪቱ ጋዜጣ፣ ባለፈው ማክሰኞም ከዚህ ማንነቱ ያልተገለጸ ግለሰብ ያገኘውን የአገሪቱ ብሄራዊ ደህንነት መረጃ ለንባብ ማብቃቱን ተከትሎ ነው የአሜሪካ መንግስት አሁንም ሌላ አዲስ መረጃ ዘራፊ እንደመጣበት ያመነው፡፡
ዘ ኢንተርሴፕት ለንባብ ያበቃው ጽሁፍ፣ በኦባማ የስልጣን ዘመን አሜሪካ በሽብርተኝነት ጠርጥራ የምትመዘግባቸው ግለሰቦች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱንና  የግለሰቦችን መረጃ በሚስጥር እያፈላለገች የመያዝና የመሰለል ስራዋን የበለጠ አጠናክራ መግፋቷን የሚያትት ነው ተብሏል፡፡
ጋዜጣው ግለሰቡ ያወጣቸው መረጃዎች አገሪቱ በሽብርተኝነት ጠርጥራ ከመዘገበቻቸው ዜጎች ውስጥ 40 በመቶ ያህሉ ከአሸባሪ ቡድኖች ጋር ምንም አይነት ግንኙነት እንደሌላቸው የሚያረጋግጡ ናቸው ማለቱን የጠቆመው ዘገባው፣ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት ግን ጋዜጣው ወጡ የተባሉትን የሚስጥር መረጃዎች በአግባቡ ካለመረዳት የተሳሳተ ድምዳሜ ላይ መድረሱን  መናገራቸውን  አስረድቷል፡፡
ማንነቱ ባልተገለጸው ግለሰብ አማካይነት ወጡ ያላቸውን መረጃዎች ጠቅሶ ጋዜጣው እንዳስነበበው፣ አሜሪካ እስከ 2013 ነሃሴ ወር ድረስ 5ሺህ ያህል ዜጎቿን በከፍተኛ፣ 18 ሺህ ያህሉን ደግሞ በመለስተኛ ደረጃ በሽብርተኝነት ጠርጥራ የመዘገበች ሲሆን፣ 1ሺህ 200 የራሷን ዜጎች ጨምሮ ሌሎች ተጨማሪ 16 ሺህ የተለያዩ አገራት ዜጎችንም ‘በአየር መንገዶችና በድንበር አካባቢዎች ጥብቅ ፍተሻ ሊደረግባቸው የሚገቡ’ በማለት ስማቸውን መዝግባ ይዛለች፡፡
ግለሰቡ ያወጣቸው እነዚህ አዳዲስ መረጃዎች፣ ስኖውደን መረጃ በማውጣቱ ሰበብ ለእስር እንዳይዳረግ በመስጋት ከአሜሪካ አምልጦ ወደ ሩስያ ከኮበለለ በኋላ በነበረው ጊዜ በአገሪቱ ብሄራዊ የጸረ ሽብርተኝነት ማዕከል  የተዘጋጁ እንደነበሩ መረጋገጡን ጠቁሞ፣ ይህም መረጃዎቹን ያወጣው ሌላ ግለሰብ መሆኑን  የሚያሳይ ነው መባሉን ገልጿል፡፡ የአገሪቱ ባለስልጣናት የአዲሱን መረጃ መንታፊ ማንነት ለማወቅ ጥረት እያደረጉ ሲሆን፣ ግለሰቡ ምናልባትም በሚመለከታቸው የአገሪቱ የደህንነት መረጃ ተቋማት ውስጥ የሚሰራ ሊሆን እንደሚችል መገመቱን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ግለሰቡ ምን ያህል የሚስጥር መረጃዎችን እንዳወጣም ሆነ መረጃዎቹ አፈትልከው መውጣታቸው በአገሪቱ መንግስት ላይ የሚያስከትለውን ጉዳት በተመለከተ የአገሪቱ መንግስት ያለው ነገር ባይኖርም፣ መረጃዎቹ ‘ሚስጥራዊና ለውጭ አገራት መንግስታት ተላልፈው የማይሰጡ መረጃዎች’ በሚል  መለያ በአገሪቱ የደህንነት መረጃ ተመዝግበው እንደነበር ዘገባው ጨምሮ ጠቁሟል፡፡
አዲሱ መንታፊ ያወጣቸው መረጃዎች ስኖውደን ከዚህ በፊት ካወጣቸው የደህንነት መረጃዎች ጋር ሲነጻጸሩ በሚስጥራዊነታቸው አነስተኛ እንደሆኑ ዘገባው ጠቁሞ፣ ስኖውደን ካወጣቸው 1 ነጥብ 7 ሚሊዮን የአገሪቱ የደህንነት መረጃዎች አብዛኞቹ ‘ጥብቅ ሚስጥሮች’ እንደነበሩ አስታውሷል፡፡

የቻይናው የሞባይል ቀፎ አምራች የግል ኩባንያ ዚያኦሚ፣ የእነጋላክሲና አይፎን ዘመን አክትሟል፣ ከአሁን በኋላ ከማንም በላይ ከፍ ብዬ የምታየው የአገሬ ‘የስማርት ፎኖች’ ንጉስ እኔ ነኝ እያለ ነው፡፡
በአገረ ቻይና የስማርት ፎን ገበያ ዋነኛ ተፎካካሪው የነበረውን የደቡብ ኮሪያው ሳምሰንግ በዘንድሮው ሁለተኛ ሩብ አመት ለመጀመሪያ ጊዜ በሽያጭ ያስከነዳውና ተወዳጅነቱ እየጨመረ የመጣው ዚያኦሚ፣ ይህ ስኬቱ በአገሩ ምድር የስማርት ፎን ገበያ መሪነቱን እንዳስጨበጠው ሲኤንኤን ሰሞኑን ከሆንግ ኮንግ ዘግቧል፡፡
ከአራት አመታት በፊት የተመሰረተው የቻይናው ስማርት ፎን አምራች ዚያኦሚ፣ በአገሪቱ ገበያ ያለውን ድርሻ በአጭር ጊዜ ውስጥ በፍጥነት በማሳደግና ባለፈው አመት ተመሳሳይ ጊዜ ከነበረው የገበያ ድርሻ 240 በመቶ ጭማሪ በማድረግ በአሁኑ ወቅት 14 በመቶ ማድረሱ የተነገረ ሲሆን፣ በሩብ አመቱ ለገበያ ያቀረባቸው ስማርት ፎኖች ቁጥርም 15 ሚሊዮን መሆኑ ተዘግቧል፡፡
ዚያኦሚ በተጠቀሰው ጊዜ 97 በመቶ የሚሆነውን ምርቱን ለቻይና ገበያ ያቀረበ ሲሆን፣ የካፒታል አቅሙም ከ10 ቢሊዮን ዶላር በላይ መድረሱ ተነግሯል፡፡  
ሳምሰንግን ጨምሮ ዋነኛ ተፎካካሪዎች የነበሩት ሁዋዌ፣ ሌኖቮና ዩሎንግ በሩብ አመቱ በአማካይ 10 በመቶ የገበያ ድርሻ መያዛቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ዚያኦሚ በቻይና ቀዳሚውን የገበያ ድርሻ ቢይዝም ከአገር ውጭ እምብዛም እንደማይታወቅ አስታውሷል፡፡
ኩባንያው በአገር ውስጥ እያስመዘገበ ያለውን ስኬት በማስፋፋት በአለም አቀፉ የስማርት ፎን ገበያ ተወዳዳሪና መሪ የመሆን ራዕይ ሰንቆ እየሰራ እንደሚገኝ የተገለፀ  ሲሆን፣ ይህን እቅዱን ለማሳካት በሚችልበት መንገድ ዙሪያ ባለፈው አመት ከጎግል ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ጋር የጋራ እንቅስቃሴ መጀመሩም ተዘግቧል፡፡
ዚያኦሚ ወደ አለማቀፉ የስማርት ፎን ገበያ ዘልቆ ለመግባትና ንግስናውን ድንበር ለማሻገር የጀመረውን ጉዞ፣ ምርቶቹን ወደ ሩስያ፣ ኢንዶኔዥያ፣ ሜክሲኮ፣ ታይላንድና ቱርክ በመላክ ለመጀመር እንደተዘጋጀ ታውቋል፡፡
የኩባንያው ስማርት ፎኖች በአሁኑ የቻይና ገበያ በ130 ዶላር እየተሸጡ ሲሆን፣ ዋጋቸው ከአፕል ምርቶች ጋር ሲነጻጸር በአንድ ሶስተኛ ያነሰ እንደሆነ ተነግሯል፡፡


ትዳር መመስረት የፈለጉ ወንዶች ለመንግሰት ፕሮፖዛል ማቅረብ አለባቸው
የአገሪቱ ወንዶች ከ4 አገራት ሴቶች ጋር መጋባት አይችሉም

ሳኡዲ አረቢያ ከሌሎች አገራት ሴቶች ጋር ትዳር መመስረት ለሚፈልጉ ዜጎቿ ጥብቅ የሆነ የትዳር መመሪያ ማውጣቷንና የአገሪቱ ወንዶች ከአራት አገራት ሴቶች ጋር እንዳይጋቡ መከልከሏን ቢቢሲ ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡
የሳኡዲ መንግስት ያወጣውን የትዳር መመሪያ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ከሌሎች አገራት ሴቶች ጋር ትዳር መመስረት የሚፈልጉ ዜጎች፣ የትዳር ፕሮፖዛልና የሚኖሩበት ከተማ ከንቲባ ፊርማ ያረፈበት የነዋሪነት መታወቂያ ለአገሪቱ ፖሊስ ማቅረብና ማስገምገም ይጠበቅባቸዋል፡፡
የመካ ከተማ ፖሊስ አዛዥ የሆኑት አሳፍ አልቁሪሽ እንዳሉት፣ መንግስት ትዳር ፈላጊዎች የሚያቀርቡለትን ፕሮፖዛል ገምግሞ ፍቃድ ይሰጣል፡፡ አዲሱ መመሪያ እንደሚለው፤ ትዳር ፈላጊው ዕድሜው ከ25 ዓመት በላይ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ ከዚህ ቀደም ትዳር የነበረውና የተፋታ ከሆነ ደግሞ፣ ከሌሎች አገራት ሴቶች ጋር አዲስ ትዳር መመስረት የሚችለው፣ ፍቺው ከተፈጸመ ከከ6 ወራት ጊዜ በኋላ ነው፡፡
“ዘ መካ” የተባለው የአገሪቱ ጋዜጣ ሰሞኑን በጉዳዩ ዙሪያ ያወጣውን ዘገባ ጠቅሶ ቢቢሲ እንደገለጸው፣ ትዳር ፈላጊው የቀድሞ ትዳሩን በህጋዊ ፍቺ ያላፈረሰ ከሆነ፣ አዲስ ትዳር መመስረት የሚችለው በመንግስት ከሚተዳደር ሆስፒታል የቀድሞ ሚስቱ በጸና መታመሟን ወይም መሃን መሆኗን የሚያረጋግጥ አልያም የቀድሞ ሚስቱ አዲስ ትዳር ቢመሰርት እንደማትቃወም የሚገልጽ ማስረጃ ሲያቀርብ ነው፡፡ አዲሱ የሳኡዲ አረቢያ መንግሰት ለአገሪቱ ትዳር ፈላጊ ወንዶች ያወጣው የጋብቻ መመሪያ፣ ወንዶቹ በአገሪቱ ውስጥ በተለያዩ ሙያዎች ተቀጥረው ከሚሰሩ የፓኪስታን፣ ባንግላዴሽ፣ ቻድ እና በርማ ሴቶች ጋር በፍጹም ትዳር መመስረት እንደማይችሉ ጥብቅ እገዳ የሚጥል መሆኑን ዘገባው ያስረዳል፡፡
ሳኡዲ አረቢያ በአለም አቀፍ ደረጃ በርካታ የውጭ አገራት ዜጎች በተለያዩ ስራዎች ተሰማርተው የሚገኙባት ቀዳሚዋ አገር መሆኗን የጠቀሰው ዘገባው፣ ዘጠኝ ሚሊዮን ከሚደርሱት ከእነዚህ የውጭ አገራት ሰራተኞች መካከል 30 በመቶ የሚሆኑት ወይም 500 ሺህ ያህሉ የትዳር እገዳ ከተጣለባቸው አራቱ አገራት የመጡ ሴቶች መሆናቸውን ጨምሮ ገልጧል፡፡