Administrator

Administrator

Sunday, 10 May 2015 15:38

የነፃነት ጥግ

ነፃነት፤ ሰዎች መስማት የማይፈልጉትን የመናገር መብት ነው፡፡
ጆርጅ ኦርዌል
ሃላፊነት ለነፃነት የሚከፈል ዋጋ ነው፡፡
ኢልበርት ሁባርድ
መንግስት ገደብ ካልተበጀለት በቀር ሰው ነፃ አይሆንም፡፡
ሮናልድ ሬገን
ነፃነት የነፍሳችን ኦክሲጅን ነው፡፡
ሞሼ ዳያን
በመናገር ነፃነት አምናለሁ፤ ነገር ግን በመናገር ነፃነትም ላይ ሃሳባችንን የመግለጽ መብት ሊኖረን ይገባል ብዬ አምናለሁ፡፡
ስቶክዌል ዴይ
ነፃነት ካልተጠቀሙበት የሚከስም ነገር ነው፡፡
ሃንተር ኤስ.ቶምፕሰን
የመፃፍና የመናገር ነፃነት ሰዎችን የማብሸቅ ነፃነትን ይጨምራል፡፡
ብራድ ቶር

የብሩንዲው ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ የአገሪቱ ህገ-መንግስት ከሚፈቅደው ውጭ ለሶስተኛ ዙር በምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸው ህገወጥነት እንደሆነና ውሳኔውን አጥብቆ እንደሚቃወመው የአፍሪካ ህብረት አስታወቀ፡፡
የፕሬዚዳንቱ ውሳኔ በአገሪቱ የቀሰቀሰው ህዝባዊ ቁጣ እየተባባሰ መምጣቱ፣ ምርጫውን በሰላማዊ መንገድ ለማካሄድ አመቺ አይደለም ያለው የአፍሪካ ህብረት፣ የምርጫ ታዛቢ ቡድኑን ወደ አገሪቱ እንደማይልክም አስታውቋል፡፡ከስልጣናቸው እንዲወርዱ በአሜሪካ እየተደረገባቸው ያለውን ጫና የተቃወሙት ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ በበኩላቸው፤ ቀጣዩ ምርጫ በሰላማዊ መንገድ መከናወን እንዲችል ህዝቡ ተቃውሞውን እንዲያቆም ጥሪ አቅርበው፣ ለአራተኛ ዙር አገሪቱን ለመምራት እንደማይፈልጉና ከዚህ በኋላ በምርጫ እንደማይወዳደሩ ቃል ገብተዋል፡፡
ፖሊስ የአገሪቱን ዜጎች ደህንነት ለመጠበቅ ሲል በተቃውሞው የተሳተፉትን ሰዎች በማሰር ላይ እንደሚገኝና፣ ዜጎች ከመሰል ድርጊታቸው የሚታቀቡና ተቃውሞው የሚቆም ከሆነ የአገሪቱ ፖሊስ በቁጥጥር ስር ያዋላቸው ዜጎች በሙሉ እንደሚፈቱም ፕሬዚዳንቱ አስታውቀዋል፡፡በብሩንዲ ያለው ሁኔታ አደገኛ ነው፡፡ ምርጫውን ለመታዘብ አንችልም፡፡ ፕሬዚዳንቱ ለሶስተኛ ዙር መወዳደራቸውም አግባብነት የለውም፤ የአገሪቱ ህገመንግስት ሊከበር ይገባል ብለዋል የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽነር ንኮዛና ድላሚኒ ዙማ፤ ከቻይናው ሲሲቲቪ ቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ከትናንት በስቲያ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ፡፡አገሪቱን በመምራት ላይ የሚገኘው ሲኤንዲዲ-ኤፍዲዲ ፓርቲ ከሁለት ሳምንታት በፊት የወቅቱን የአገሪቱ ፕሬዚደንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ በመጪው ምርጫ በዕጩነት ማቅረቡን ተከትሎ በተቀሰቀሰው ተቃውሞ ከ15 ሰዎች በላይ መሞታቸውንና በርካቶች መቁሰላቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ተቃውሞው ተጠናክሮ መቀጠሉን ጠቁሟል፡፡ሮይተርስ በበኩሉ፤ ከትናንት በስቲያ በአገሪቱ መዲና ቡጁምቡራ ለተቃውሞ የወጡ ዜጎች የገዢው ፓርቲ የወጣቶች ክንፍ አባል ነው ያሉትን አንድ ግለሰብ በእሳት አቃጥለው መግደላቸውንና የተለያዩ ሱቆችን ማጋየታቸውን ዘግቧል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ለሶስተኛ ዙር ምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸው የህግ ጥሰት ነው ያሉት የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና የሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖች፣ የአገሪቱ ህገመንግስት አንድ ፕሬዚዳንት በመሪነት መቆየት የሚችለው ለሁለት ዙር ብቻ እንደሆነ ቢወስንም፣ ፕሬዚዳንቱ ግን ህገመንግስቱን በጣሰ ሁኔታ በስልጣን ላይ ለመቆየት እየተዘጋጁ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
የፕሬዚዳንቱን የምርጫ ተሳትፎ አግባብነት በተመለከተ ጉዳዩን ሲመረምር የቆየው የብሩንዲ ህገመንግስታዊ ፍርድ ቤት በበኩሉ ባለፈው ሰኞ ይፋ ባደረገው ውሳኔው፣ ፕሬዚዳንቱ የመጀመሪያውን ዙር በፓርላማ እንጂ ቀጥታ በህዝቡ ተመርጠው ስልጣን ባለመያዛቸው እንደ አንድ ዙር አይቆጠርባቸውም፣ በዘንድሮው ምርጫ መወዳደር ይችላሉ ብሏል፡፡
የፍርድ ቤቱ ምክትል ፕሬዚዳንት ሳላይሬ ኒምፓጋሪትሴ ግን፣ ከመንግስት በተደረገ ጫና የተላለፈ ውሳኔ ነው በሚል ተቃውመው፣ ፊርማዬን አላስቀምጥም በማለት አገር ጥለው የተሰደዱ ሲሆን የአገሪቱ መንግስት ቃል አቀባይ በበኩሉ፤ ግለሰቡ ውሳኔውን እንዲያስተላልፉ ምንም አይነት ጫና እንዳልተደረገባቸው መግለጻቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ለአመታት የዘለቀው ከ300 ሺህ በላይ ዜጎችን ለህልፈተ ህይወት የዳረገው የአገሪቱ ደም አፋሳሽ የእርስ በእርስ ጦርነት እ.ኤ.አ በ2005 ከተቋጨ ወዲህ አስከፊው የተባለውንና ከሰሞኑ የተቀሰቀሰውን ተቃውሞና አመጽ ተከትሎ፣ በአገሪቱ ውጥረት መንገሱንና 40 ሺህ የሚደርሱ የአገሪቱ ዜጎች ለደህንነታቸው በመስጋት ወደ ሩዋንዳ፣ ታንዛንያና ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኦፍ ኮንጎ መሰደዳቸውንም ዘገባው አስታውቋል፡፡
ለፕሬዚዳንትነት የሚወዳደሩት ኦዲፋክስ ንዳቢቶሪየ የተባሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል ባለፈው ረቡዕ  አመጹን አነሳስተዋል በሚል በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ ከተደረገባቸው በኋላ መለቀቃቸውን እንዲሁም በአገሪቱ መዲና ቡጁምቡራ ከትናንት በስቲያ የተቀሰቀሰውን ተቃውሞ በቁጥጥር ስር ለማዋል ፖሊስ በወሰደው እርምጃ አንድን ግለሰብ ተኩሶ መግደሉንና ሶስት ዜጎችንም ማቁሰሉን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

መስራቾቹ ትርፋማ እንደሚሆኑ እርግጠኛ ሆነዋል
ሶስቱ ሰራተኞች በሶስት ሽፍት ይሰራሉ
ታላላቅ ኩባንያዎች ምርቶቹን ለመግዛት ተመዝግበዋል


ክላውድ ዲዲኤም የተባለውና በባለሶስት አውታር ህትመት ዘርፍ ላይ ተሰማርቶ ለመስራት ዝግጅቱን ያጠናቀቀው  የአሜሪካ ኩባንያ፣ በ3 ሰራተኞች ብቻ በሚያከናውነው የምርት እንቅስቃሴ ትርፋማ ስራ እንደሚያከናውን መስራቾቹ በእርግጠኝነት መናገራቸውን ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
በአይነቱ የመጀመሪያው የሆነውና ሙሉ ለሙሉ በማሽን አማካይነት የሚሰራው ይህ ኩባንያ፣ የዘመናዊ ቴክኖሎጂ ውጤት በሆኑ 100 ባለ ሶስት አውታር ማተሚያ ማሽኖቹ አማካይነት በሳምንት ለ 7 ቀናት ለ24 ሰዓት የማምረት ስራውን የሚያከናውን ሲሆን፣ እያንዳንዳቸው በሶስት ሽፍት ለ8 ሰዓታት የሚሰሩ 3 ሰራተኞች ብቻ እንዳሉትም ገልጽዋል፡፡
ከኩባንያው መስራች አንዱ የሆኑት ሚች ፍሪ ባለፈው ረቡዕ ለሲኤንኤን እንደገለጹት፣ ኩባንያው የምርት ስራውን በማተሚያ ማሽኖቹና በሶስቱ ሰራተኞች አማካይነት በተቀላጠፈ ሁኔታ እያከናወነ ሲሆን፣ ምርቶቹን የማሸግና ለደንበኞች የማድረስ ስራውን ደግሞ ዩፒኤስ የተባለ አጋር ድርጅት እያከናወነው ይገኛል፡፡
ኩባንያው የተለያዩ ቁሳቁሶችን በባለ ሶስት አውታር ማተሚያ ማሽኖች አማካይነት በማምረት ለደንበኞቹ የሚያቀርብ ሲሆን አሰራሩ የተቀላጠፈ በመሆኑ ለማምረት አንድ ሳምንት ያህል ጊዜ የሚወስዱ ዕቃዎችን በ24 ሰዓታት ውስጥ ሰርቶ ማጠናቀቅ የሚችልበት ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ሚች ፍሪ ገልጸዋል፡፡
ኩባንያውን ለማቋቋም 1 ሚሊዮን ዶላር ወጪ መደረጉን የጠቆመው ዘገባው፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ በርካታ ደንበኞችን ማፍራት መቻሉንና በቀጣይም የባለ ሶስት አውታር ማተሚያ ማሽኖቹን ቁጥር ወደ አንድ ሺህ ከፍ ለማድረግ ዕቅድ ይዞ በቅርቡ ወደ ስራ እንደሚገባ አስታውቋል፡፡
ተቀማጭነቱ በኒውዮርክ የሆነው ሁማንስኬል የተባለ የቤት ዕቃዎች አምራች ኩባንያ፣ ታዋቂው የቅንጦት የእጅ ሰዓቶች አምራች ኩባንያ ዴቮን ዎርክስ እንዲሁም ግዙፉ ፍሌክስትሮኒክስን ጨምሮ በርካታ ድርጅቶች ከዚህ በአይነቱ የተለየ ኩባንያ ምርቶችን ለመግዛት ደንበኝነት መመስረታቸውንም አስታውቋል።

ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ የመፃሕፍት ንባብ እና ውይይት ፕሮግራም በነገው ዕለት “ዘ ማሳካር ኦፍ ደብረ ሊባኖስ ኢትዮጵያ 1937” በተሰኘው የደራሲ ኢያን ካምፔል መጽሐፍ ላይ በነገው ዕለት በብሔራዊ ቤተመፃሕፍትና ቤተመዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ ውይይት ያካሂዳል፡፡
ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ የሚያቀርቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፍልስፍና መምሕር የሆኑት ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ሲሆኑ የሥነ ፅሁፍ ቤተሰቦች በዚህ ውይይት ላይ እንዲታደሙ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጋብዟል፡፡
ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ለ6 ወራት ያህል በየ15 ቀኑ የሚያደርገውን የመፃህፍት ውይይት አቋርጦ እንደነበር ይታወሳል፡፡

ደራሲው ዘውዱ ደስታ የምንድስና ባለሙያ ሲሆን በዘርፋ በሃገራችን ውስጥ ትልልቅ ፕሮጀክቶች ላይ ሰርቷል፡፡ እየሰራም ይገኛል፡፡ደራሲው የህይወት ልምዱን ፤የንባብ ክህሎቱን ፤የብዙ ጊዜ ገጠመኞቹን ፤ትዝብቱንም ጭምር  ሳንሱሲ ውስጥ ከትቧል፡፡
ቀድሞ ሳንሱሲን እንዲያነቡ እድሉን ያገኙ ፀሀፊያን ከሶስት  በላይ አንኳር ጉዳችን  ደራሲው በመፅሀፋ እንዳስቀመጠና እንዲህም ሆኖ ግን ቁምነገሮቹ ተደጋጋፊና ተመጋጋቢ በመሆናቸው ለአንባቢያን የአይን መግለጫ ነው ብለዋል፡፡
ደራሲው ዘውዱ ደስታ ከአዲስ አበባ ምዕራብ  መዝለቂያ በሆነችው ሳናሱሲ ላይ መቼቱን አድርጎ የፈጠራቸው የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገር ገጸባህርያት ፤አንዳንዶቹ በልባችን ሙቀትና ቁመት ሲጎልምሱ አንዳንዶቹ ሰንፈው ሲፈርሱ በአጠቃላይ እንድንወዳቸው እንድንጨክንባቸው እና እንድንወያይባቸው ያደርጋል፡፡
ሳንሱሲ መጽሀፍን ማግኘት ለምትሹ አንባቢያን በተለያዩ መጽሃፍት መደብሮች ቀድሞ ይሸጥ ከነበረው  136 ብር  ደራሲው ዋጋውን አስተካክሎ በ96 ብር አቅርቦታል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አውራዶሮና ሚስቱ በአንድ ቄስ የእህል መጋዘን አጠገብ ሲጓዙ አውራዶሮው አንድ ባቄላ አግኝቶ ሲውጥ፤ አነቀውና፤ ውጪ ነብስ ግቢ ነብስ ሆነ፡፡ ሚስቲቱ ዶሮ የምታደርገው ብታጣ ውሃ ፍለጋ ወደ ወንዝ ወረደች፡፡
“ወንዝ ሆይ! እባክህ ባለቤቴ ባቄላ አንቆት፣ መተንፈስ አቅቶት ሊሞትብኝ ነው፡፡ ትንሽ ውሃ ስጠኝና ነብሱን ልታደገው?” አለችው፡፡
ወንዝም፤ “ወደ ሎሚ  ዛፍ ሄደሽ አንድ የሎሚ ቅጠል ካመጣሽልኝ ውሃ እሰጥሻለሁ” አላት፡፡
ዶሮይቱ ወደ ሎሚ ዛፍ ሄደችና፤
“ሎሚ ዛፍ ሆይ! ባለቤቴ ባቄላ አንቆት መተንፈስ አቅቶት፣ ሊሞትብኝ ነው ብዬ ወንዝን ውሃ ስጠኝ ብለው፤ “የሎሚ ቅጠል ካመጣሽ እሰጥሻለሁ” አለኝ፡፡ እባክህ አንዲት ቅጠል ስጠኝ?” አለችው፡፡
የሎሚ ዛፍም፤
“ወደ ቄሱ ቤት ሠራተኛ ሄደሽ የመርፌ ክር ካመጣሽልኝ እሰጥሻለሁ” አላት፡፡
እመት ዶሮ ወደ ቄሱ ቤት ሠራተኛ ሄዳ ጉዳይዋን አስረዳች፡፡
የቤት ሠራተኛዋም፤ “ወደ ላም ሄደሽ ትንሽ ወተት ካመጣሽልኝ ክሩን እሰጥሻለሁ” አለቻት፡፡
እመት ዶሮ ወደ ላም ሄዳ “ትንሽ ወተት ስጪኝ ባክሽ” ብላ ጉዳይዋን ሁሉ ዘረዘረችላት፡፡
ላምም፤ “ወደ አጫጆቹ ዘንድ ሄደሽ ትንሽ ጭድ ካመጣሽልኝ እሰጥሻለሁ” አለቻት፡፡
እመት ዶሮ እንደፈረደባት ወደ አጫጆቹ ሄዳ “እባካችሁ ትንሽ ጭድ ስጡኝ” አለቻቸው፡፡
አጫጆቹም “ወደ ቀጥቃጮች ሄደሽ ትንሽ ማጭድ ከሰጡሽ ጭዱን እንሰጥሻለን” አሏት፡፡
እመት ዶሮ ወደ ቀጥቃጮቹ ሄዳ ለመነቻቸው፡፡
ቀጥቃጮቹ ደግሞ “ወደ ከሰል አክሳዮቹ ጋ ሄደሽ አንድ አራት ራስ ከሰል አምጪልንና የጠየቅሽንን እንሰጥሻለን” አሏት፡፡
ወደ ከሰል አክሳዮቹ ላዕያውያን (Laians) ምርር ባለ ምስኪን ቃና አስተዛዝና፤
“ከሰል አክሳዮቹ ሆይ፤ ባለቤቴ አውራዶሮ ባቄላ አንቆት፣ መተንፈስ አቅቶት ሞት አፋፍ ቢደርስ፣ አንድ ጉንጭ ውሃ ወንዝን ብጠይቀው፣ የሎሚ ቅጠል ከሎሚ ዛፍ አምጪ፤ የሎሚ ዛፍ ጋ ብሄድ ከቄሱ ሠራተኛ የመርፌ ክር አምጪ፤ የቄሱ ሠራተኛ ከላም ወተት አምጪ፤ ላም ጋ ብሄድ ከአጫጆቹ ጭድ አምጪ፤ አጫጆቹ ጋ ብሄድ ከቀጥቃጮች ማጭድ አምጪ፤ ቀጥቃጮቹ ዘንድ ብደርስ ከላዕያውያን ከሰል ካመጣሽ እንሰጥሻለን አሉኝ፡፡ እባካችሁ እናንተ እንኳ እሺ በሉኝ፡፡”
ከሰል አክሳዮቹ ራሩላትና ከሰሉን ሰጧት፡፡
እመት ዶሮ እየከነፈች ከሰሉን ይዛ ለቀጥቃጮቹ ሰጠች፡፡ ማጭድ ተቀብላ ለአጫጆች፤ ከነሱ ጭድ ተቀብላ ለላም፤ ከላም ወተት ወስዳ ለቄሱ ሰራተኛ፤ ከሷ የመርፌ ክር ተቀብላ ለሎሚ ዛፍ፤ ከሎሚ ዛፍ ቅጠል ተቀብላ ወደ ወንዙ በረረች፡፡ ከወንዙ ውሃ ተቀብላ ወደ አውራ ዶሮ ባሏ ከነፈች፡፡
አውራ ዶሮ ባሏ ግን ለአንዴም ለሁሌም ፀጥ ብሏል፡፡ ሞት ቀድሟታል፡፡
*   *   *
ችግር ሠንሠለቱን ሲተረትር ሰው በማህል ያልቃል፡፡ አያድርስ ነው፡፡
ገጣሚ ደበበ ሰይፉ፤ በ “አክሱም ጫፍ አቁማዳ” ግጥሙ ትግራይ ለሸዋ፣ ለአርሲ ለሲዳሞ፣ ለወለጋ፣ ለጐንደር፣ ለኤርትራ እህል ተለማምነው፤ የተላከችው አቁማዳ አንዳችም እህል ሳይገባባት ተመልሳ ለባለቤቱዋ ለትግራይ ባዶዋን ትመጣለች፡፡
“…አክሱም ላይ ሠቀላት
ከባዶ አቁማዳ ነው፣ እሚዛቅ ፍቅራችን” ብሎ ይደመድማል፡፡ አንድምታው ብዙ ነው፡፡ የችግሩ መጠን ይለያያል እንጂ በየሠንሠለቱ ቀለበት ላይ ችግር አለ፡፡ ቢሮክራሲያችንም እንደዚያው ነው! ሁሉም ለየግብዓቱ ጥሬ ዕቃውን ይጠይቃል፡፡ ይሄን ሠንሰለት ሙስና ብንለውም፤ ወይም የቅብብሎሽ ሂደት፤ አሊያም ዱላ ቅብብሎሽ፤ ዞሮ ዞሮ የታነቀው ህዝብ ለአንዲት ፍሬ መሞቱ አሳዛኝ ሀቅ ነው!
የችግሮቻችን ብዛት የመፍትሔዎቻችንን ውስብስብ ገፅታ ከወዲሁ ጠቋሚ ነው፡፡ የቆዩ ችግሮች መፍትሔ ሳያገኙ፤ አዳዲሶቹን ለመፍታት መጣራችን ራሱ አንድ ተጨማሪ ችግር ይሆንብናል፡፡ የሀገራችን ቁልፍ ጉዳይ ችግርን በሌላ ችግር መፍታት መሆኑ አሳሳቢ ከሆነ ቆይቷል፡፡ አብሮ መታየት ያለበት ግን ችግርን የመገንዘብ አቅማችንም አናሳ መሆን ነው፡፡
አንድ ፈላስፋ እንዳለው፡-
“The Problem is us; the Solution us” (ችግሩም እኛ፤ መፍትሔውም እኛ እንደማለት) ስለዚህ “እንዳልተመለሰው ባቡር” ያልተመለሱ ጥያቄዎች ሲደመሩ አዲስ ጥያቄ እያረግን ማሰብ ይበጃል፡፡
ሀ+1= ለ
ሀ= የዱሮ ችግር፣ “1” = አዲሱ ችግር፤ “ለ” = ያሁኑ ሁኔታ፤ እያልን ማስላት ነው፡፡ የዱሮ ችግር ብለን በመዝገብ የተያዙ ሂሳቦችን ካላወራረድን ነገ ኦዲተር አይለቀንም!
ከዲሞክራሲ ምን ጐሎ ነበር? ከፍትሕ ምን ጐሎ ነበር? ከሙስና መፍትሔ ምን ጐሎ ነበር? ከመልካም አስተዳደር ምን ጐሎ ነበር? ከሹምሽር ሥራ ምን ጐሎ ነበር? ህዳሴውስ ተመርምሯል ወይ? ከምርጫ ዝግጅት አሁን ምን ጐሎዋል? ከዱሮ ምርጫዎችስ ምን ጐሎ ነበር? በዚህ ሁሉ ድምር ሂሳብ ዛሬ ምን ላይ ነን? በአየር ጊዜ ክርክር አድማጩ ህዝብ እየረካ ነው? ምርጫው የተበላ ዕቁብ ነውን? የሚለው አስተሳሰብ መክኗል ወይስ በየልቡ ያኮበኩባል፡፡
በተፅዕኖ ከመምረጥ ጀምሮ አንዳንዱን ጠፍቶ ድንገት የመጣ ተመራጭ “አፋልጉኝ” እስከማለት የደረሰ፤ በስላቅ በሚኖር ህብረተሰብ ውስጥ ምርጫው አድሎ የሌለውና ዕውነተኛ (ነፃ) [Fair and Free] ነው ብሎ ለመኩራት፣ ለመተማመንና “አሹ!” ለማለት ከባድ ነው፡፡ “ዐባይን ጭብጦዬን ከወሰደብኝ በኋላ አላምነውም!” ያለውን ባላገር ደግመን ደጋግመን እንድናስብ የሚያደርገን ፖለቲካዊም ባህላዊም ተፈጥሮ ያለን ነንና እንዴት ይሆን ወደፊት የምንገፋው ማለት አመላችን ነው!
“አይሠግሩም ተብሎ
ፈረስና በቅሎ፤
አይሮጡም ተብሎ
ፈረስና በቅሎ፤
እንዲያው በጥላቻ:-
ትመረጥ ይሆናል ኤሊ ለኮርቻ!” የሚለው አገርኛ አባባል፤ ጥቂት ቆም ብለን እንድናስብ ዐይናችሁን ክፈቱ ይለናል፡፡

ጠ/ሚ ኃይለማርያም የግብጽን መንግስት አመስግነዋል
   በሊቢያ ታግተው የቆዩና የግብጽ መንግስት ባደረገው ድጋፍ የተለቀቁ 27 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ትናንት ማለዳ አዲስ አበባ የገቡ ሲሆን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖምና ሌሎች ባለስልጣናት በቦሌ አለማቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ በመገኘት ለስደተኞቹ አቀባበል አድርገዋል፡፡በግብጽ ወታደራዊ ሃይል ድጋፍ ከእገታ ተለቀዋል የተባሉት እነዚሁ ስደተኞች ከትናንት በስቲያ ካይሮ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ሲደርሱ በአገሪቱ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ አቀባበል እንደተደረገላቸው  ሮይተርስ፣ ፕሬዚደንቱ፤ “ስደተኞቹ በሊቢያ የታጠቁ ሃይሎች ታግተው በአስከፊ ሁኔታ ውስጥ የቆዩ ናቸው” ማለታቸውን የአገሪቱ የዜና ተቋም “ሜና መዘገቡ ታውቋል፡፡የዜና ተቋሙ ስለስደተኞቹ ማንነት፣ ስለተለቀቁበት ሁኔታ እና ታግተው በቆዩበት ወቅት ስለነበረው ሁኔታ ግልጽ መረጃ ባይሰጥም፣ ሮይተርስ በበኩሉ፤ የሊቢያ ባለስልጣናት ከግብጽ የስለላ ተቋማት ያገኙትን መረጃ በመጠቀም በዴርና እና ሚስራታ ከተሞች በታጠቁ ሃይሎች ታግተው የነበሩትን እነዚህን ስደተኞች እንዳስለቀቁ መረጃ ደርሶኛል ብሏል፡፡ ተቀማጭነታቸውን አዲስ አበባ ያደረጉ
አንድ የግብፅ ዲፕሎማት በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያውያኑ ከሊቢያ የወጡት በወታደራዊ ሃይል ድጋፍ ሳይሆን የግብፅ መንግስት ባደረገው ዲፕሎማሲያዊ ጥረት እንደሆነ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ከኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች አንዱ በበኩሉ፣ የሊቢያ መንግስት ከነበርንበት ቦታ ወደ አገሪቱ የጸረ ህገወጥ ስደት አካል ከወሰደን በኋላ፣ የግብጽ መንግስት ወደ ካይሮ አምጥቶናል ሲል መናገሩን ዘገባው አስረድቷል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ በበኩላቸው፤ የስደተኞቹን መለቀቅ ተከትሎ ከትናንት በስቲያ ከግብጹ ፕሬዚዳንት አል ሲሲ ጋር በስልክ ባደረጉት ንግግር፣ ግብጽ ኢትዮጵያውያኑን ለማስለቀቅ ላደረገችው አስተዋጽኦ ምስጋናቸውን ገልጸው፤ መሰል ጥረቶች በግብጽ፣ በአረቡ አለምና በአፍሪካ አገራት መረጋጋትን ለመፍጠር አስተዋጽኦ ያበረክታሉ ማለታቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም በፌስቡክ ገጻቸው ላይ ባወጡት መረጃ እንዳሉት፤ በሊቢያ ከሚገኙት ኢትዮጵያውያን ስደተኞች መካከል የመጀመሪያዎቹ 11 ስደተኞች ባለፈው ረቡዕ በካርቱም በኩል ወደ አዲስ አበባ መግባታቸውን ጠቁመዋል፡፡

Saturday, 02 May 2015 12:48

የተፈጥሮ እውነታዎች

ብብታችን በአንድ ስኩዌር ኢንች ክፍሉ ብቻ እስከ 516ሺ የሚጠጉ ባክቴሪያዎች አሉበት፡፡
አንድ ሰው በህይወት ዘመኑ በአማካይ 18 ኪሎ ግራም የሚሆን የቆዳ ግፋፊ ያስወግዳል።
በየቀኑ 100 ቢሊዮን ቀይ የደም ሴሎች በሰውነታችን ውስጥ ይፈጠራሉ፡፡
የወንድ ልጅ የዘር ፍሬ በየቀኑ 10 ሚሊዮን አዳዲስ ስፐርሞችን ያመርታል፡፡ ከጠቅላላ የሰውነት ክብደቱም 0.08 ኪ.ግ ይመዝናል፡፡
የሴቶች የእንቁላል ማኮሪያ (Ovary) በአንዴ ግማሽ ሚሊዮን የሚሆኑ የእንቁላል ሴሎች መያዝ ይችላል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 400 የሚሆኑት ብቻ የማፍራት ዕድልን ያገኛሉ፡፡
ልባችን በቀን ውስጥ 100ሺህ ጊዜ ይመታል፡፡
በሰውነታችን ውስጥ ካሉ ጡንቻዎች በሙሉ የምላስ ጡንቻዎቻችን በጣም ጠንካሮች ናቸው፡፡
ልክ እንደ ጣት አሻራ፣  የእያንዳንዱ ሰው የምላስ አሻራም የተለየ ነው፡፡
በጭንቅላታችን ላይ በአማካይ 100ሺህ ፀጉሮች ይገኛሉ፡፡ እያንዳንዱ ፀጉር በየዓመት 5 ኢንች ይረዝማል፡፡

 የታሪክ አፃፃፉ ምን ይመስላል? ደራሲው ታሪኩ የተፈፀመበትን ዘመን የተረዳው እንዴት ነው? መረጃዎቹን ከፖለቲካ፣ ከኢኮኖሚ፣ ከባህል… አንፃር እንዴት ነው የመዘነው? የሚሉ ጥያቄዎችን በማንሳት ሚዛናዊነት መመዘን ይቻላል፡፡ ማነው መዛኙ ለሚለው ፀሐፊያንም አንባቢያንም ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ታሪከ ፀሐፊ ፖለቲከኛ ሊሆን ይችላል። አንድን ታሪክ ሲጽፍ ምክንያታዊ መሆን ከቻለ ሚዛናዊ ታሪክ ፀሐፊ ነው ሊባል ይችላ

     ላለፉት 10 ዓመታት በየሁለት ሳምንቱ የመፃህፍት ላይ ውይይት ሲያካሂድ የቆየው ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ፤ በገጠመው ውስጣዊ ችግር ምክንያት የተለመደውን መድረክ ማዘጋጀት ካቋረጠ ስድስት ወራት ሆኖታል፡፡ ይህንን ክፍተት ለመሙላት የጀርመን ባህል ማዕከል፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መፃሕፍት ኤጀንሲ እና እናት ማስታወቂያ ድርጅት በጋራ በመሆን በወር አንዴ የመፃሕፍት ላይ ውይይት እንደሚያካሂዱ የተገለፀ ሲሆን የመጀመሪያው ዝግጅትም ባለፈው እሁድ በወመዘክር አዳራሽ ተከናውኗል፡፡
ለውይይት የተመረጠው “የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግሥት” በሚል ርዕስ በአምባሳደር ዘውዴ ረታ ተጽፎ ባለፉት ሁለት ዓመታት ሦስት ጊዜ ለመታተም የበቃው መጽሐፍ ሲሆን፤ ለውይይት የመነሻ ሀሳብ ያቀረቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት አቶ አበባው አያሌው ነበሩ፡፡ የመጽሐፉ ደራሲ አምባሳደር ዘውዴ ረታ ከአገር ውጭ በመሆናቸው በዕለቱ ሊገኙ አልቻሉም፡፡
“የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግሥት ዘመን በአገሪቱ በርካታ ታሪኮች የተከናወኑበት በመሆኑ ልዩ ወቅት ነበር፡፡ ዘመናዊ ለውጥ በአፄ ቴዎድሮስ ዘመን ተጀመረ የሚሉ አሉ፤ በተግባር የታየው ግን በአፄ ኃይለሥለሴ ጊዜ ነው፡፡ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ አወዛጋቢ ንጉሥ ነበሩ፡፡ የሚያደንቋቸው አሉ፡፡ በኋላ በአገሪቱ ለታየው ምስቅልቅል ትልቅ አስተዋጽኦ አድርገዋል ብለው የሚከሷቸውም አሉ፡፡ በዚህ ዙሪያ ብዙ የተፃፈ ቢሆንም ወደፊትም ብዙ የሚፃፍበት ይመስላል፡፡ አብዮተኞቹ ታሪክ ፀሐፊዎች አፄ ኃይለሥላሴን ሲያጠለሹ፤ በንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት ውስጥ ያገለገሉ ታሪክ ፀሐፊዎች ያሞግሷቸዋል፡፡ ሦስተኛው ዓይነት ታሪክ ፀሐፊዎች የውጭ አገር ሰዎች ሲሆኑ የተደረገውን ሐቅ ከማስቀመጥ ውጭ ነገሩ ጥሩ ነው፣ መጥፎ ነው ብለው ትንታኔ ውስጥ አይገቡም፡፡ ከዚህ አንፃር እነዚህ ሚዛናዊ ሆነው ይታያሉ።”
በዚህ መልኩ ገለፃ የጀመሩት አቶ አበባው አያሌው፤ የአምባሳደር ዘውዴ ረታን መጽሐፍ የቃኙት በሰባት መመዘኛዎች እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ ደራሲው ለጉዳዩ ያላቸው ቅርበት ምን ይመስላል? የመረጃ ምንጫቸው ምን ነበር? መረጃዎቹስ በመጽሐፉ ውስጥ በምን ያህል ተንፀባርቀዋል? ሚዛናዊነቱ ምን ይመስላል? በመጽሐፉ የተገለፀው ዘመን ታሪክ ምን ያህል ሙሉ ሆኖ ቀርቧል? የታሪክ ሃተታውና የቋንቋ አጠቃቀሙ ምን ይመስላል? መጽሐፉ ምን አዲስ ነገር አሳወቀን?
እነዚህን ጥያቄዎች አንስተው ምላሽ በመስጠት ማብራራት የቀጠሉት የዩኒቨርሲቲው ምሁር፤ የአገርም ሆነ የግለሰቦች ታሪክ በአንድ ሰው ብቻ ተጽፎ እንደማያበቃ ጠቁመው በአፄ ኃይለሥላሴ ዙሪያ 56 ያህል መፃሕፍት መታተማቸውን ገልፀዋል፡፡
ደራሲው ለፃፉበት ርዕሰ ጉዳይ ቅርበት ነበራቸው፡፡ የማስታወቂያ ሚኒስቴር ሰራተኛ፣ የቤተ መንግሥት ጋዜጠኛና በኋላም የማስታወቂያ ሚኒስቴር ረዳት ሚኒስትር ሆነው ያገለገሉ  ከመሆኑም ባሻገር በአምባሳደርነትም ተሹመው መስራታቸው የቃል፣ የሰነድና የፎቶግራፍ መረጃዎችን ለማግኘት ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳደረገላቸው አቶ አበባው ገልፀዋል፡፡
አምባሳደር ዘውዴ ረታ በአገር ውስጥና በውጭም መረጃዎችን ማግኘታቸው ብቻ ሳይሆን ያገኙትን በጥንቃቄ ማስቀመጥ በመቻላቸው “የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግሥት” በተሰኘው መጽሐፋቸው ላይ በሚገባ ተጠቅመበውበታል፡፡ በአገር ውስጥ ከጽሕፈት ሚኒስቴር ሰነዶችን በቀጥታ አግኝተዋል። በዘመኑ ታላላቅ ባለስልጣናት ከነበሩት መኮንን ሀብተወልድ፣ ወልደጊዮርጊስ ወልደዮሐንስ፣ ይልማ ደሬሳ ከመሳሰሉት ቤተሰቦችም ብዙ መረጃ ሳያኙ አልቀሩም ተብሏል፡፡
“የቃል መረጃም በብዛት ተጠቅመዋል፡፡ ይህ በጥንቃቄ መታየት ያለበት ነው፡፡ ምስክርነቱን የሰጠው ሰው ማነው? የፖለቲካ አመለካከቱ፣ ዕውቀቱ … መጠየቅና መጣራት አለበት። የቃል ምስክርነት እውነታነቱ ሌላ ማመሳከሪያ ካልተገኘለት ለዘመን ፍርድ ክፍት ተደርጎ የሚተው ነው” ያሉት አቶ አበባው፤ በተመሳሳይ በዚህ መልኩ ጥያቄ አስነስቶ እስካሁንም እያነጋገረ  ነው በማለት “ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ” የተሰኘውን መጽሐፍ በምሳሌነት ጠቅሰዋል፡፡
የቃልና የሰነድ መረጃዎች በስፋት ጥቅም ላይ ውለውበታል የተባለው “የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግሥት” መጽሐፍ፤ በማጣቀሻነት የተጠቀማቸው መፃሕፍት ቁጥር ትንሽ እንደሆኑና የመረጃ አገላለጽ ችግር እንደሚታይበት ተጠቁሟል፡፡ የመረጃ ምንጩ ሰውም ይሁን ሰነድ የት እንደሚገኝ መገለጽ አለበት። በመጽሐፉ ላይ አባሪ ማኖር ገጽ ያበዛል ተብሎ ከተፈራ መረጃዎች ከየትኛው ሰነድ እንደተወሰዱ በግርጌ ማስታወሻ ቢገለጽ ጥሩ ነበር፡፡ ምክንያቱም ደራሲው ያገኘውን ምንጭ አንባቢያንም እንዲደርሱበት ያግዛል ተብሏል፡፡ መጽሐፉ በርካታ ፎቶግራፎችን ቢይዝም “የኤርትራ ጉዳይ” ከሚለው መጽሐፋቸው ጋር ሲነፃፀር ይኸኛው መጽሐፍ የያዛቸው ፎቶግራፎች ቁጥራቸው ማነሱም ተገልጿል፡፡
“የታሪክ ጠላት ፖለቲካ ነው፡፡ ፖለቲካ ታሪክን ወደራሱ ፍላጎት ይዞት ይሄዳል፡፡ ከዚህ አንፃር አምባሳደር ዘውዴ ረታ በመጽሐፋቸው ምን ያህል ሚዛናዊ መሆን ችለዋል?” ያሉት ምሁሩ፤ ደራሲው በአንዳንድ ቦታ ኃይለሥላሴን ከብዙ ነገሮች ነፃ ሲያደርጓቸው ይታያል፡፡ የታሪክ ፀሐፊ አይበይንም። ፍርዱን ለአንባቢያን ነው መተው ያለበት፡፡ እንዲህም ሆኖ መጽሐፉ ባነሳው ርዕሰ ጉዳይ ዙሪያ በአገር ውስጥ የነበረውን ብቻ ሳይሆን ዓለም አቀፍ ሁኔታና ተጽዕኖንም እያመሳከረ ታሪኩን ሚዛናዊ ለማድረግ ሞክሯል ተብሏል፡፡
ከ1923-1948 ዓ.ም ያለውን ዘመን ማዕከል አድርጎ የተዘጋጀው የአምባሳደር ዘውዴ ረታ መጽሐፍ፤ የ25 ዓመታቱን ታሪክ በምን ያህል መጠን ሙሉ አድርጎ አቀረበ? ለሚለውም ጥያቄ የአምስቱ ዓመት የአርበኞች ተጋድሎ ታሪክ አለመፃፉ (ደራሲውም ይህንን በመጽሐፉ መግቢያ አንስተውታል)፤ አፄ ኃይሥላሴ በስደት በእንግሊዝ በነበሩበት ጊዜ አኗኗራቸው ምን ይመስል እንደነበር አለመገለፁ፤ ከድል በኋላ አርበኞች፣ ባንዳዎች፣ ስደተኞች፣ ምሁራን በውስጣቸው የነበረው ትግል ምን እንደነበር አለመብራራቱ፤ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት አውሮፓውያን ለስደተኛ መንግሥታት ዕውቅና ሲሰጡ ኢትዮጵያ ዕድሉ ስለመነፈጓ በስፋት አለመፃፉ … የመሳሰሉት የመጽሐፉን ሙሉእነት ጥያቄ ውስጥ ያስገባዋል ብለዋል - አቶ አበባው፡፡
መጽሐፉ በታሪክ አተራረክና በቋንቋ አጠቃቀሙ የተሳካለት መሆኑን የመሰከሩት አቶ አበባው  መጽሐፉ ምን አዲስ ነገር አሳየን? ለሚለውም “ትኩረት ያልተሰጣቸው ጥቃቅን ነገሮችን አሳይቶናል፡፡ ማን ምን ብሎ ጠይቆ፤ ማን ምን ብሎ መለሰ የሚለውን ሁሉ እናይበታለን። የ1923ቱ ሕገ መንግሥት ሊፀድቅ በሂደት ላይ እያለ በዘመኑ ምሁራንና ባለስልጣናት መሐል የተደረገውን ሰፊ ክርክር አቅርቦልናል (የሞኝ ዘመን መጽሐፍ ሆኖ ነው እንጂ በህገ መንግሥቱ ዙሪያ የቀረበው ርዕስ ብቻ አንድ መጽሐፍ ይወጣው ነበር)፡፡ በሊግ ኦፍ ኔሽን የተደረገውን ክርክር በተመለከተ በአገር ውስጥና በውጭ አገራት ሰዎች ዘንድ ያለው አመለካከት ምን ይመስል እንደነበር በስፋት ገልጿል፡፡ ስለ መኮንን ሀብተወልድ፣ ወልደጊዮርጊስ ወልደዮሐንስ፣ ይልማ ደሬሳ ካሁን ቀደም የማናውቃቸውን አዳዲስ መረጃዎች ሰጥቶናል፡፡ የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዲፕሎማሲያዊ ክህሎት ምን ያህል ውጤታማ (በባሩድ ሳይታጠኑ በንግግርና ውይይት በማሳመን) መሆናቸውን አይተንበታል፡፡ መጨረሻ ላይም የንጉሠ ነገሥቱ ምኞት፣ የምሁራኑ ፍላጎትና የባለሥልጣናቱ መሻት መለያየቱንና ሁሉም ብቻውን መቆሙን አመላክቶናል፡፡” ብለዋል፡፡
አቶ አበባው መጽሐፉን አስቃኝተው ከጨረሱ በኋላ ከተሰብሳቢዎች የተለያዩ አስተያየትና ጥያቄዎች ቀርበዋል፡፡ አምባሳደር ዘውዴ ረታ አንዳንዴ በሚጽፉት ስሜታዊ ገለፃ ፀሐፊ ትዕዛዛትን ይመስላሉ፡፡ በዚህ ላይ የምትለን ነገር አለ? ደራሲው የታሪክ ሰው አይደሉም፤ አምባሳደር (ዲፕሎማት) ናቸው የሚሉ ክርክሮች አሉ፡፡ ማረፊያው የቱ ነው? ታሪክን ፖለቲካ ስለሚጎትተው ታሪክ ፀሐፊ ሚዛናዊ እንዲሆን እንዴት ይጠበቃል? ታሪክ ፀሐፊ ይመዘናል ከተባለ፤ መዛኙ ማነው? ታሪክ ፀሐፊው ላይ የቀረበው አድናቆትና ነቀፌታን ለመዳኘት ዲስፕሊኑ ከየት ነው የሚገኘው?
ለቀረበላቸው ጥያቄዎች መልስ የሰጡት አቶ አበባው አያሌው፤ “የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግሥት” የተሰኘው መጽሐፍ የንጉሡ ታሪክ ላይ ትኩረት ቢያደርግም አምባሳደር ዘውዴ ረታ ጸሐፊ ትዕዛዝ አይደሉም ብለዋል፡፡ በተፈጥሮም የተገኘ ይሁን በልምድ አተራረክና አቀራረቡ ጥሩ የሆነ መጽሐፍ አቅርበውልናል፡፡ ታሪክን ማንም ይጽፈዋል። ፀሐፊዎቹም ህዝባዊና ሙያዊ ተብለው በሁለት ይከፈላሉ፡፡ ተነባቢነት ያላቸው አብዛኞቹ የታሪክ መፃሕፍት የተፃፉት በጋዜጠኞች ነው፡፡ አምባሳደር ዘውዴ ረታ በማስታወቂያ ሚኒስቴር ስለሰሩ የታሪክ መጽሐፉ ለመፃፍ ችለዋል፡፡
“በታሪክ መጽሐፍ ውስጥ ሚዛናዊነት መኖሩን የምናረጋግጠው ደራሲው ምን መረጃ አገኘ? መረጃውን እንዴት አቀረበው? አተረጓጎሙስ እንዴት ነው? የሚሉትን ጥያቄዎችን በማንሳት፤ ጥያቄዎቹ የሚተነተኑበትን ሂደት ተከትሎ በመመርመር ነው። የታሪክ አፃፃፉ ምን ይመስላል? ደራሲው ታሪኩ የተፈፀመበትን ዘመን የተረዳው እንዴት ነው? መረጃዎቹን ከፖለቲካ፣ ከኢኮኖሚ፣ ከባህል… አንፃር እንዴት ነው የመዘነው? የሚሉ ጥያቄዎችን በማንሳት ሚዛናዊነት መመዘን ይቻላል፡፡ ማነው መዛኙ ለሚለው ፀሐፊያንም አንባቢያንም ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ታሪከ ፀሐፊ ፖለቲከኛ ሊሆን ይችላል። አንድን ታሪክ ሲጽፍ ምክንያታዊ መሆን ከቻለ ሚዛናዊ ታሪክ ፀሐፊ ነው ሊባል ይችላል” በማለት አቶ አበባው ማብራሪያቸውን ቋጭተዋል፡፡      

ከወር በፊት በጋለሪያ ቶሞካ በተከፈተው “ውስጣዊ ግለትና እንፋሎት” የተሰኘ የስዕል ትርዒት ላይ ነገ ከረፋዱ 4፡00 ሰዓት ጀምሮ በቶሞካ ውይይት እንደሚካሄድ ዳይሬክተሩ ጋዜጠኛ ነብዩ ግርማ ገልጿል፡፡ የወጣት አሸናፊ ማስቲካ ስራዎችን በ14ኛው ዙር የስዕል ትርዒቱ ለእይታ ያቀረበው ጋለሪው፤ ሳር ቤት ካናዳ ኤምባሲ ፊት ለፊት በሚገኘው ጋለሪያ ቶሞካ በርካታ የስዕል አፍቃሪያን፣ ሰዓሊያን፣ ጋዜጠኞችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በሚገኙበት ከ35 በላይ በሚሆኑ የወጣቱ ሰዓሊ ስራዎች፣ የአሳሳል ዘይቤና በስዕል ፍልስፍናው ዙሪያ ሰፊ ውይይት እንደሚካሄድ ለማወቅ ተችሏል፡፡