Administrator

Administrator

Monday, 16 March 2015 09:40

የውሃ ህክምና ፈውስ

የውሃ ህክምና (ሃይድሮቴራፒ) ጥንታውያን ግሪኮች፣ ግብፆችና ሮማውያን ከበሽታ ለመፈወስ  ሲጠቀሙበት የኖሩት ህክምና ሲሆን በቀላሉ ሊገኝ የሚችልም ነው፡፡ ውሃ በፈሳሽ፣ በበበረዶና በጋዝ መልኩ የተለያዩ ጠቀሜታዎችን ይሰጣል፡፡ ቀዝቃዛ፣ ሙቅና ፍል ውሃም አገልግሎቱ ለየቅል ነው፡፡
ውሃን በመጠጣት የሚገኝ ፈውስ
 ንፁህ ውሃን በመጠጣት ለህመም ፈውስ ማግኘት ከብዙ ሺህ ዓመታት በፊት ሲተገበር የቆየ ህክምና ነው። ውሃን መጠጣት የሰውነታችን በሽታ የመከላከል አቅምን                                                                                ያዳብራል፡፡ ውሃን በመጠጣት የኩላሊት፣ የጨጓራ፣ የፊኛ፣ የመገጣጠሚያ አካላት፣ አንጀትና ጣፊያ በሽታዎችን፣ ኪንታሮት፣ የሳንባ ምች፣ የተለያዩ ተላላፊ በሽታዎችን፣ የጡንቻና አጥንት ጤና ችግሮችን ማስወገድ ይቻላል፡፡
ሁልጊዜ ጠዋት ቁርስ ከመመገባችን በፊት ከአምስት ብርጭቆ ያላነሰ ውሃ ብንጠጣ ለተለያዩ ውስጣዊ የጤና ችግሮቻችን መፍትሄ እናገኛለን፡፡ ውሃ በተፈጥሮው የአሲድነት ፀባይ የሌለው በመሆኑ ለሰውነታችን ውስጣዊ ኡደት መቀላጠፍ የሚሰጠው ጠቀሜታ ከፍተኛ ነው። በአግባቡ ሳይሰለቀጡ ወደ አንጀታችን የሚገቡ ምግቦች በቀላሉ እንዲብላሉና በጥቅም ላይ እንዲውሉ በማድረግ ረገድ ውሃ የሚሰጠው ጠቀሜታ ከፍተኛ ነው፡፡
ውሃን በመነከር የሚገኝ ፈውስ
በጣም የቀዘቀዘ ውሃ ማይግሪን ለተባለው ራስ ምታት ፍቱን መድኀኒት ነው፡፡ ህመሙ በሚነሳበት ወቅት በጣም የቀዘቀዘ ውሃን ለአምስት ደቂቃዎች ያህል አናት ላይ በመያዝ ህመሙን ማስታገስ ይቻላል፡፡
ቀዝቃዛ ውሃ ለአለርጂ፣ ለጡንቻ መዛል፣ ለአዕምሮ መረበሽ (ለድብርት)፣ ለውጥረት፣ ለትኩሳትና ለሌሎችም በሽታዎች ፍቱን መድኀኒት ነው፡፡ ውሃ በሞቃትና በፍል መልኩ ጥቅም ላይ ሲውል ደግሞ ለመገጣጠሚያ ችግሮች፣ ለጉንፋን፣ ለብርድ፣ ለኢንፍሉዌንዛ ፍቱን መድኀኒት ነው። የሙቀት መጠኑ 750c የሆነ ውሃ ህመም በሚሰማን ቦታ ላይ ማፍሰስ (መነከር) ከህመም እፎይታን ሊያስገኝ ይችላል፡፡
ውሃን በበረዶ መልክ መጠቀም  
በመገጣጠሚያ አካላት ላይ በአደጋ (መውደቅ፣ መጋጨት) ለሚደርስ ጉዳትና በዚህ ሳቢያ በሰውነታችን ላይ ለሚከሰት እብጠት፣ የጡንቻ መሸማቀቅ ወይም ውልቃት በረዶ ፈጣን ፈውስን ያስገኛል፡፡ በረዶ በተጎዳው ሰውነታችን ላይ ሲደረግ ከህመም እፎይታን ከማግኘታችንም በሻገር እብጠቱን ለመቀነስ ያስችላል፡፡
ውሃን በመታጠን መፈወስ
ውሃን አፍልቶ መታጠን (በጋዝ መልኩ) ለጉንፋን፣ ለሳል፣ ለኢንፍሉዌንዛና ለጉሮሮ ህመሞች ፈጣን ፈውስ ይሰጣል፡፡  
የውሃ ህክምና ጥንቃቄዎች
በውሃ ህክምና በመታገዝ ፈውስ ለማግኘት በምንሞክር ወቅት ያሉብንን የጤና ችግሮች በሚያባብስ መልኩ እንዳይሆንብን ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡ ቁስለት ባለባቸው የሰውነት አካላት ላይ ሙቅም ሆነ ቀዝቃዛ ውሃ መጠቀም የለብንም፡፡
እርጉዝ ሴቶች በውሃ ህክምና ከመጠቀማቸው በፊት ከሃኪማቸው ጋር መማከር ይኖርባቸዋል፡፡ በተለይ ህክምናውን በብልት (በማህፀን አካባቢ) ላሉ ችግሮች መጠቀም የሚፈልጉ እርጉዝ ሴቶች ህክምናውን ከመጀመራቸው በፊት ሃኪማቸውን ማማከር ይገባቸዋል፡፡

Monday, 16 March 2015 09:42

ካፌይን እና መዘዞቹ

ካፌይን አዕምሮን ለማነቃቃት የሚረዳና በተለይ በቡና፣ በሻይና በተለያዩ የለስላሣ መጠጦች ውስጥ በስፋት የሚገኝ ኬሚካል ነው፡፡ ካፌይን ከእነዚህ መጠጦች በተጨማሪ በቸኮሌቶች፣ በብስኩቶችና በተለያዩ የህመም ማስታገሻና የራስ ምታት መድሃኒቶች ውስጥ ይገኛል፡፡ ይህ ኬሚካል ሱስ የማስያዝ ባህርይው ከፍተኛ ነው፡፡ የተጠቀሱት መጠጦችና ምግቦች እንዲሁም መድሃኒቶች ካፌይን የመያዝ አቅማቸው እንደየሁኔታው የተለያየ ሲሆን በቡና ውስጥ የሚገኘው የካፌይን መጠን ከፍ ያለ ነው፡፡ አንድ ስኒ ቡና ከ100-150 ሚሊ ግራም ካፌይን በውስጡ ይይዛል፡፡ አንድ ሰው በቀን በአማካይ 80 ሚሊ ግራም ካፌይን ይወስዳል ተብሎ ይገመታል፡፡ ከመጠን ያለፈ ካፌይንን መጠቀም ለከፋ የጤና ችግር ይዳርጋል፡፡ በካፌይን ሳቢያ ከሚከሰቱ የጤና ችግሮች መካከል የካፌይን ስካር (ኢንቶክሲኬሽን)፣ ሱሰኝነት፣ የእንቅልፍ ማጣትና ጭንቀት ይጠቀሳሉ፡፡  
የካፌይን ስካር (ኢንቶክሲኬሽን)
ከ250 ሚሊ ግራም በላይ የሆነ ካፌይን ከተወሰደ የካፌይን ስካር ይጀምራል፡፡ የዚህ ችግር ምልክቶች ጭንቀት፣ መቅበጥበጥ፣ የህሊና መረበሽ፣ ማቅለሽለሽ፣ ማላብ፣ የሽንት መብዛት፣ እንቅልፍ ማጣት፣ እጅና እግርን የመውረር ስሜት መኖርና መነጫነጭ ናቸው፡፡ የካፌይን መጠኑ እየጨመረ ከሄደ እና 1000 ሚሊ ግራም ከደረሰ የአፍ መኮላተፍ፣ የሃሳብ መደነጋገርና የልብ ትርታ መዛባት ሊከተል ይችላል፡፡ መጠኑ ከዚህ እየጨመረ ከሄደም ድንገተኛ የልብ ምት መቆም (ሞትን) ሊያስከትል ይችላል፡፡
የካፌይን ሱሰኝነት
ራስ ምታት፣ ድብርት፣ ጭንቀት፣ ድካም፣ ማቅለሽለሽና ማስመለስ፣ እንቅልፍ እንቅልፍ የማለት ስሜት--- በካፌይን ሱሰኝነት ምክንያት የሚከሰቱ የጤና ችግሮች ናቸው፡፡
ይህ ችግር ካፌይኑ ከቀረ ከ10-12 ሰዓታት ውስጥ የሚጀምር ሲሆን ከጥቂት ቀናት ተደጋጋሚ ስሜት በኋላ ሊጠፋ የሚችል ነው፡፡
የእንቅልፍ ማጣትና ጭንቀት
መረበሽ፣ መነጫነጭ፣ በአንድ ቦታ ተረጋግቶ አለመቀመጥ፣ መርበትበትና መጨነቅ በካፌይን ሰበብ ከሚከሰቱ የጤና ችግሮች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ ካፌይን ለእንቅልፍ ማጣት ሰበብ ከመሆኑም በተጨማሪ  ለድብርት፣ ለጭንቀትና ለውጥረት ዋንኛ ምክንያትም ነው፡፡
የመፍትሔ እርምጃዎች
የሚወሰደውን የካፌይን መጠን በአንድ ጊዜ ለመቀነስ መሞከር አይመከርም፡፡ ይልቁንም ዕለት በዕለት ቀስ እያሉ የሚወስዱትን የካፌይን መጠን በመቀነስ በሂደትም ማቆም በካፌይን ሰበብ ከሚደርሱ የጤና ችግሮች ሊታደገን ይችላል። ካፌይን የሌለባቸውን ምግቦችና መጠጦች ለይቶ በማወቅ እነሱ ላይ ትኩረት በማድረግ መጠቀም፣ ራስን በሌሎች ነገሮች ለማዝናናት መሞከርና ውሃን አብዝቶ መጠጣት በካፌይን ሳቢያ የሚከሰቱትን የጤና ችግሮች ለማስወገድ ይረዳል፡፡

ኢህአፓም “አሲምባ”ን ማስጎብኘት ይችላል----

  ልጅ ያሬድ የተባለው ታዋቂ ኮሜዲያን ሰሞኑን በዋሽንግተን ሆቴል (የአዲስ አበባው ነው!) ባቀረበው የኮሜዲ ምሽት ላይ የታደመችው የሥራ ባልደረባዬ ሰምታ ካጣጣመቻቸው ቀልዶች ውስጥ  ጥቂቶቹን ስለነገረችኝ እኔም ለናንተ ላጋራችሁ፡፡ (“sharing is caring” አሉ!)
ወደ ልጅ ያሬድ ቀልድ፡- አንድ የሆነ ሰፈር ነው አለ፡፡  ሌላው ጋ 3 ብር የሚሸጠውን አንድ እንጀራ 4 ብር ነው የሚሸጡት ---- ለምንድን ነው እዚህ ሰፈር  4 ብር የሚሸጠው ሲል ይጠይቃቸዋል፡፡ ምን ቢሉት ጥሩ ነው --- እኛ ሰፈር ውሃ ስለሌለች ሊጡን በሃይላንድ ውሃ ነው የምናቦካው፡፡ (የጨረሰች  ቀልድ!)  
ባለፈው ሳምንት ትዝ ይላችሁ እንደሆነ ስለ ህወሃት 40ኛ ዓመት በዓል ሳወጋችሁ አንዳንድ ተቃዋሚዎች፤ ኢህአዴግ በዓሉን ለምርጫ ቅስቀሳነት እየተጠቀመበት ነው የሚል ክስ መሰንዘራቸውን ጠቅሼ ነበር (ነገርዬው ባይሆን ለወቀሳ እንጂ ለክስ እንኳን አይበቃም!) የሆኖ ሆኖ ---- ተቃዋሚዎች ለምን እንዲህ ያለ ወቀሳ ሰነዘሩ ብዬ ሳሰላስል ሁለት መላ ምቶች ብልጭ አሉልኝ፡፡ አንደኛው፤ ህወሃት ለምን ለበዓሉ አልጠራንም የሚል የአበሻ ቅያሜ ቢጤ ይመስለኛል፡፡ ለነገሩ አይፈረድባቸውም፡፡ ለምን መሰላችሁ ----- ሱዳኖችንና የቻይና ኮሙኒስት ፓርቲን በሰበብ አስባቡ እየጋበዙ ለአገር ቤት ተቃዋሚ ጀርባ መስጠት ያናድዳላ፡፡ (ቀላል ያጨሳል!)  
በነገራችሁ ላይ በእንዲህ ያሉ መልካም አጋጣሚዎች (የህወሃት 40ኛ ዓመትን ማለቴ ነው!) ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ የዘለቀውን የፖለቲካ ኩርፍያ (የኩርፍያ ፖለቲካም ያስኬዳል!) ለመስበር መትጋት እኮ ብልህነት ነው፡፡ (አረ ብልጥነትም ጭምር!) ፖለቲከኞቻችን ሌላው ቢቀር … ለአዲሱ  ትውልድ የሚያስረክቡትን አገር ማሰብ አለባቸው፡፡ (ኩርፍያ የሞላት አገር ማን ይረከባል!)
እናላችሁ----በተለይ የመንግስትን ስልጣን የያዘው ኢህአዴግ ተነሳሽነቱን መውሰድ አለበት ባይ ነኝ፡፡    (ከተቃዋሚም ቢገኝ አንጠላም!) አያችሁ ቢገባን እኮ---ለሰላምና ለፍቅር መሸነፍ ከማሸነፍ እኩል ነው፡፡ (ኧረ ኩርፊያው ይሰበር!) አሁንስ እኔ ለእነሱ ደከመኝ… (ስፖንሰር ከተገኘ “ኩርፊያው ይሰበር” የሚል የ6 ወር አገራዊ ንቅናቄ ለመጀመር አስቤያለሁ!)
ሁለተኛውን መላ ምት እንኳ ሳምንትም ጠቀስ አድርጌዋለሁ (የአርቲስቶች ደደቢትን መጎብኘት ማለቴ ነው!) ዛሬ ግን ችግሩን ብቻ ሳይሆን መፍትሄውንም ይዤአለሁ፡፡ ባለፈው ጠቀስ እንዳደረግሁላችሁ ተቃዋሚዎች በዚህ ነገር ደስ የተሰኙ አይመስሉም፡፡ ለዚህ ነው ኢህአዴግ በዓሉን ለምርጫ ቅስቀሳ ተጠቀመበት የሚል ወቀሳ የመጣው፡፡ (ሁሉ ነገር በአስተማማኝ ግምት ላይ የተመሰረተ ነው!)
ለነገሩ እስቲ ራሳችሁን በተቃዋሚዎች ቦታ አድርጋችሁ አስቡት፡፡ (ለአፍታ የእነሱን ጭንቅላት ልዋስ!) እናላችሁ--ለምሳሌ አርቲስቶችን ደደቢት ድረስ ወስዶ ማስጎብኘት ለምን አስፈለገ? (ያውም በምርጫው 11ኛ ሰዓት ላይ!) ግን እኮ ጥያቄው መቅረብ የነበረበት ለራሱ ለህወሃት ነው! የጉብኝቱ ዓላማ እንደተባለው ታሪክን ለትውልድ ማስተላለፍ ነው? (እንዴት አሁን ትዝ አላቸው?) ወይስ በምስኪንነት ሆድ አባብቶ አሊያም በጀግንነት ቀልብ ማርኮ የአርቲስቶችን ድምፅ ለመግዛት ነው? እኒህ ሁሉ ጥያቄዎችና መላምቶች  የእኔ አይደሉም … እኔ ለእነሱ የመታሁት መላ እንጂ!! (ራሴን በተቃዋሚዎች ጫማ ውስጥ አስገብቼ ማለት ነው!)
እናም ማንም ተቃዋሚ የሆነ (ያውም ደግሞ ያኮረፈ!) ከላይ ከቀረቡት ውስጥ ልቡ ወደ ሁለተኛው ጥያቄና መላ ምት እንደሚያደላ ሳይታለም የተፈታ ነው!! እናም ለዚህ ይሆናል የህወሃትን 40ኛ ዓመት  ለምርጫ ቅስቀሳ ተጠቀሙበት የሚለው ክስ (ይቅርታ ወቀሳ!) የመጣው፡፡ አሁን ወደ መፍትሄው እንግባ፡፡ የእኔ ሃሳብ ምን መሰላችሁ? ተቃዋሚዎችም ልክ እንደ ህወሃት የየራሳቸውን “ደደቢት” ለአርቲስቶች እንዲያስጎበኙ ዕድል መስጠት! (ከከተማ ሳይወጡ ደደቢት!) ግን ምን መሰላችሁ? ምንም እንኳን ተቃዋሚዎች እንደ ህወሃት በረሃ ገብተው ባይዋጉም አልታገሉም ማለት ግን አይደለም፡፡ የሰላማዊ ሰልፍ ዕውቅና ማግኘት፣ ህዝባዊ ስብሰባ ለማካሄድ አዳራሽ ወይም ሆቴል መከራየት፣ በየክልሉ ካሉ ትናንሽ የወረዳ ንጉሶች ጋር መወዛገብ፣ ሰላማዊ ፈቃዱ ህገወጥ ነው ከሚል የጸጥታ ኃይል ጋር መጋፈጥ (ዱላና ድብደባን ያካትታል!) ------ እኒህ ሁሉ የትግሉ አካል ናቸው፡፡
 ሌሎችም የትግል ቦታዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ---ተቃዋሚዎች ፓርቲያቸውን ለመመስረት ሃሳብ የጠነሰሱበት ሥፍራ፣ በኢህአዴግ ካድሬ ተዋከብን የሚሉበት ቦታ፣በየጊዜው እነሱ ወይም ጓዶቻቸው የታሰሩበት፣(ቃሊቲ፣ዝዋይ፣ማዕከላዊ--ወዘተ) እነዚህ ሁሉ የእነሱ የትግል ቦታዎች ናቸው፡፡ አብዛኞቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የሚጋሩት አንድ የድል ቦታም አላቸው -የህዝብ ማዕበልን የሚያስታውሳቸው፡፡ መስቀል አደባባይ!! (የ97 ምርጫን ልብ ይሏል!) አያችሁ----ተቃዋሚዎችም ለአርቲስቶች ሊያስጎበኙት የሚችሉት ከበቂ በላይ የትግል ቦታና ታሪክ  አሏቸው፡፡ (የየራሳቸው ደደቢት እንደማለት!) በነገራችሁ ላይ የትጥቅ ትግሉን ያሸነፈው ኢህአፓ ቢሆን ኖሮ---- አርቲስቶቹ የሚጎበኙት ደደቢትን ሳይሆን አሲምባን ይሆን ነበር፡፡
 እናላችሁ … ተቃዋሚዎች አርቲስቶችን ሰብስበው የየራሳቸውን “ደደቢት” ቢያስጎበኙ ኩርፊያውን ለማርገብ የሚያግዝ ይመስለኛል፡፡ (አርቲስቶች የህዝብ ሃብት ናቸው ብዬ እኮ ነው!) በነገራችሁ … ላይ የህዝብ ሃብት ያልሆነ ነገር እኮ ፈልጋችሁ አታገኙም! ለምሳሌ መሬት የህዝብ ሃብት ነው (ይቅርታ እና የመንግስት!)፣ ቲቪና ሬዲዮ ጣቢያም የህዝብ ሃብት ነው፡፡ የኢህአዴግ ኢዶውመንቶች ራሳቸው - የህዝብ ሃብት ናቸው፡፡ የሥልጣን ባለቤት ማነው? ህዝብ ነው!! የመንግስት ሹማምንት የማን አገልጋይ ናቸው? የህዝብ!! ግን እኮ አርቲስቶች ሃብታቸውን ሲጠየቁ----ሃብታችን ህዝብ ነው ይላሉ፡፡ (ከምራቸው እንዳይሆን!)

አቶ ደስታ አስፋው
(በኢህአዴግ ፅ/ቤት የህዝብና ውጭ
ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ)
         አዲስ አድማስ ጋዜጣ በቆየባቸው 15 ዓመታት ውስጥ ጠንካራም ደካማም ጎኖች እንዳሉት ታዝቤያለሁ፡፡ ከጠንካራ ጎኖቹ መካከል የተለያዩ ጉዳዮችን በተከታታይ በመረጃ መልክ ለህዝብ ማድረሱ ነው፡፡ ከዚያ ውጪ አልፎ አልፎ የሚዛናዊነት ችግሮች ይታዩበታል፡፡ አዲስ አድማስ አሁን የደረሰበትን ደረጃ አይቶ፣ ጥንካሬዎቹን አጠንክሮ ጉድለቶቹን አርሞ ከቀጠለ፣ለሃገራችን የዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ሊያደርግ ይችላል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በግሌ ቢያንስ በመሰረታዊ የሙያው መርሆች ይሰራሉ ከምላቸው ጋዜጦች ውስጥ አስገባዋለሁ፡፡ አዲስ አድማስ የሚዲያ ሥራ በባህሪው የሚያጋጥመውን ተግዳሮት ተወጥቶ በየጊዜው ራሱን እያሳደገ፣ እዚህ መድረሱ ጥሩ ነው፤ ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል፡፡ ትልቁ ነገር ግን፣ ለህዝቡ መረጃ ለማድረስ በሚደረገው ጥረት የጋዜጠኝነትን መርህ መለኪያ ማድረግ ነው፡፡ የተሰሩ ጥሩ ነገሮችንም መዘገብ አለባችሁ፡፡ ለወደፊትም ጋዜጣው ደካማ ጎኑን አርሞ ጠንካራ ጎኑን ይበልጥ አጠናክሮ መቀጠል አለበት፡፡ እንኳን ለ15ኛ አመታችሁ አደረሳችሁ ለማለት እወዳለሁ፡፡  

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ብዙ ጋሻ ቡና መሬት፣ ይጭኑት አጋሠሥ ይለጉሙት ፈረስ ያላቸው የበለፀጉ አባት ያሉት ልጅ አባቱን እንዲህ ይላቸዋል፡፡
“አባዬ”
“ወይ”
“እንግዲህ ለአቅመ - አዳም ደርሻለሁ፡፡ እንዴት አድርገህ ነው የምትድረኝ?” ሲል ይጠይቃል፡፡
አባቱም፤
“ለመሆኑ ኃላፊነት ለመቀበል ዝግጁ ነህ ወይ?”
“አዎን፤ ዝግጁ ነኝ”
“እንግዲህ ለሁሉም ወሳኙ የቡና አዝመራችን ነው”
“እንዴት አባዬ?”
“አየህ ከአሁኗ ሰዓት ጀምረህ መሬቱን መኰትኮት አለብህ፡፡ አረሙን መንቀል አለብህ፡፡ ውሃ ማጠጣት አለብህ፡፡ ከዚያ በትዕግስት እስከአዝመራው ሰዓት መጠበቅ አለብህ”
“ከዚያስ አባዬ?”
“ከዚያ ደግሞ ትለቅማለህ?”
“ቡና ለቃሚ ሠራተኞች አሉን አይደለም እንዴ?”
“አሉን”
“ታዲያ እኔ ለምን እለቅማለሁ?”
“አየህ ኃላፊነት የበላይ ተቆጣጣሪነትን ብቻ አይደለም የሚጠይቀው፡፡ ወርደህ ሥራውን ማወቅ፣ አውቀህም ሠርተህ ማየትን ይጠይቃል፡፡”
“ከዚያስ በኋላ?”
“ከዚያማ አዝመራው የሰጠና ያልሰጠ መሆኑ ተጣርቶ ያንተም የእኔም ዕጣ - ፈንታ ይወሰናል”
“ይሄ ምን ማለት ነው አባዬ?”
“ይሄ ማለት አዝመራው የሰጠ ከሆነ አንተን ድል ያለ ድግስ ደግሼ እድርሃለሁ፡፡ የማር - ጨረቃህንም (Honey - moon) ወይም የጫጉላ - ሽርሽርህንም በየባህሩ ዳርቻ አደርግልሃለሁ፡፡
በአንፃሩ አዝመራው የሰጠ ካልሆነ ግን አንተም አታገባም፡፡ እኔም ያለችኝን ሚስት እፈታ ይሆናል!” አሉት፡፡
***
አዝመራው መስጠት አለመስጠቱ የእኛ መሠረታዊ ጥረት ውጤት ነው፡፡ ያልዘራነውን፣ ያላረምነውን፣ ያልኮተኮትነውን ማጨድ፣ ማዝመር አንችልም፡፡ ለምርጫ መዘጋጀት ማለት ነው፡፡ “ከሠርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ” ሩጫ መውጣት አለብን፡፡ በአንፃሩ ‘ገባው አልገባው አይደለም የፖለቲካ ምሥጢሩ፤ ተቀበለ አልተቀበለ ነው’ ከሚለውም የባለ ድሎች መዝሙር  መላቀቅ አለብን፡፡ ዲሞክራሲ ሂደት ነውና አሸናፊ ተሸናፊ የሚሆንበት ጊዜ እንደሚኖር አንርሳ፡፡
“ተቃዋሚዎች አንዴ በርቶ ተቃጥሎ ከመቅረት (Burn bright and burn out) የተሻለ መላ ማሰብ አለባቸው፡፡ ሁሉን አቀፍ ራዕይ ያለው ሥርዓት መፍጠርን ማሰብ አለባቸው፡፡ ሥርዓቱ ቢወድቅ የሚኖረን ፖለቲካዊ ስትራቴጂ ምን መሆን አለበት? እስከሚል ድረስ ማሰብ ያሻቸዋል” ትለናለች ኖኦሚ ክላየን፡፡
አንድ መምህር ተማሪዎቹን ሲያስተምር፤
“አንዳንዴ ትናንሽ የነገ እርምጃዎችን የግድ መቀበል ይኖርብናል፡፡ ሌላ ጊዜ ደግሞ ‘እንደ ጐሽ መሮጥ ይኖርብናል’ ያለውንም አንርሳ” ይላል፡፡ ሁልጊዜ ሩጫ አይመረን ማለቱ ነው፡፡  
ሎሬት ፀጋዬ እንደሚለን፤ “በሁሉም ጐራ ላሉ የአፍሪካ የሕዝብ መሪዎች፣ ገዢዎችና በስሙ ለሚነሱ አማጺያን ያለኝ መልዕክት አንድ ብቻ ነው፡፡ መርኋችሁ እውነት ለዲሞክራሲ ከሆነ ‘እኔ አውቅልሃለሁን’ ትታችሁ ሕዝቡን ተከተሉ” የሚል ብቻ ነው፡፡ ሕዝብ ይሄዳል፣ ይንቀሳቀሳል፤ ግመሉንም እየነዳ ይሄዳል፡፡ ግን አንድ ቦታ ሲደርስ “አትሒድ ከእንግዲህ በኋላ ያንተ አገር አይደለም” መባል የለበትም፡፡ የአፍሪካ መሪዎች ተልዕኮ መሆን ያለበት የህዝቡን የኑሮ ጉዞ፣ ነፃነቱን፣ ክብሩን፣ መብቱን፣ ማመቻቸትና መጠበቅ ነው መሆን የለበት፤ እንጂ የራሳቸውን ወይም የአዛዦቻቸውን ፍላጐት ማሟላት አይደለም፡፡ አዛዥ ሕዝብ ነው መሆን ያለበት!” ይህን ሁሉም እያንዳንዱ የፖለቲካ ፓርቲ ማወቅ ነው የሚገባው፡፡
“ያለመስዋዕትነት ድል የለም” የሚለው የዱሮ መፈክር ዛሬም ደርዝ አለው፡፡ እጅግ ረዥም መንገድ እንሄዳለን ብሎ ለተነሳ ፓርቲ ወይም ድርጅት፤ “ጉዟችን ረዥም ትግላችን መራራ” የሚለው ከዓመታት በፊት የነበረ መፈክር ይዘቱ ለዛሬም ፋይዳ አለው ብሎ ማሰብ የአባት ነወ፡፡ በተተነኮስን ቁጥር አገር ይያዝልን ማለት ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ መተንኮስና መገፋት ብቻ አይደለም መስዋዕትነት፡፡
ጨርሶ ከጨዋታው መባረርስ ቢሆን ብሎ ማሰብ ያሻል፡፡ አንድ ልብ፣ አንድ አፍ፣ አንድ ማህበር ሆነው እንዲኖሩ ማሰብ ቀዳሚ ነገር ነው!
“ከደደብ ሰዎች ጋር አትከራከር፡፡ ወደነሱ ደረጃ ዝቅ ያደርጉሃል፡፡ ከዚያ በኋላ በልምዳቸው ያሸንፉሃል!” (ማርክ ትዌይን)
ተፎካካሪያችንን በቅጡ ማወቅ፣ ድልን ያለጉራ፣ ሽንፈትን በፀጋ ለመቀበል ይጠቅማል፡፡ ዞሮ ዞሮ ባለጉዳዩ ብቻ የሚያቀው ነገር ሁሌም አለ፡፡ “የመቃብር ሥቃይ የሚታወቀው ለሟቹ ብቻ ነው” (The torture of the grave is known only to the dead) የሚለው የስዋሂሊ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው!

ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ከሦስት ዐሥርት ዓመታት የአሜሪካ ቆይታ በኋላ በሚሌኒየሙ መባቻ ወደ አገራቸው ተመልሰው ላለፉት ሰባት ዓመታት በማስተማር ሥራ ላይ ቆይተዋል፡፡ ምሁሩ በዋናነት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፍልስፍና መምህር ቢኾኑም በሕግ ፋክልቲ፣ በሴንተር ፎር ሂዩማን ራይትስ፣ በኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም፣ በአምስት ኪሎ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ፋክልቲ፣ በቴአትሪካል አርትስና በያሬድ የሙዚቃ ት/ቤትም አስተምረዋል፡፡ ለሰባት ተከታታይ ዓመታት በተጠቀሱት የትምህርት መስኮች በተለያየ ጊዜ ሲያስተምሩ ቢቆዩም ከጠየቁት የዓመት ዕረፍት (sabbatical leave) ጋር ተያይዞ ከዩኒቨርስቲው መሰናበታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡  አዲስ አድማስ ጋዜጣ በጉዳዩ ዙሪያ ከዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ጋር ተከታዩን አጭር ቃለምልልስ አድርጓል፡፡

    በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ እና በእርስዎ መካከል ምንድን ነው የተፈጠረው?
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አስተዳደር ጋር በኹለት ጥያቄዎች ዙሪያ የማይታረቅ ልዩነት ተፈጥሯል፡፡ በመጀመሪያ የዩኒቨርስቲው የሴኔት ሕግና የቅጥር ውሌ ላይ በግልጽ እንደሰፈረው÷ አንድ መምህር ለስድስት ዓመት በተከታታይ ከአስተማረ፣ ለአገለገለበት ዘመን የአንድ ዓመት የጥናትና ምርምር ዕረፍት (sabbatical leave) እንደሚሰጠው ተደንግጓል፡፡ ኾኖም ግን ዩኒቨርስቲው ‹‹የጡረታ ሥርዓተ - ሒደቱን አላሟላኽም›› በሚል በሕጉ ፊት የማይጸና ሰበብ ፈጥረው ይገባኻል ብለው ከፈቀዱልኝ በኋላ መልሰው ነጥቀውኛል፡፡ ለማንኛውም መምህር ሥርዓተ ሒደቱን የማስፈጸም ሓላፊነት የሰው ሀብት አስተዳደሩ ድርሻ ኾኖ ሳለ፣ እኔን ተጠያቂ ማድረጋቸው ብዙዎችን አስገርሟል::
በነገራችን ላይ የጥናት ዕረፍት ፈቃዴን የጠየቅኹት ከሦስት ዓመት በፊት፣ ስድሳ ዓመት ሳይሞላኝ ነበር፡፡ በየሰበቡ ሲጓተት ስለቆየ ወደ ስድሳ ዓመቱ ገደብ ደረስኹ፡፡ ጉዳዩ ወደ ማኅበራዊ ፍርድ ቤት ከመሔዱ አስቀድሞ ውስጣዊ ተቋማዊ መፍትሔ ለማበጀት ወደ ዩኒቨርስቲው የቦርድ ሰብሳቢ ቀርቦ ምላሽ ስጠባበቅ ከሦስት ወራት በላይ ተቆጥረዋል፡፡
የሥራ ውሌን በተመለከተ፣ የፍልስፍና ትምህርት ክፍል የእኔን የአገልግሎት ቆይታ እንደሚፈልግና በተለይም በቅርቡ ለሚጀምረው የሦስተኛ ዲግሪ መርሐ ግብር ተሳትፎዬ እንደሚጠቅም በሙሉ ድምፅ ተስማምቶ በመወሰኑ ውሌ እንዲራዘም ለማኅበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ አካዳሚክ ኮሚሽን ጽፎልኝ ነበር፡፡ የማኅበራዊ ሳይንስ ትምህርት ክፍል ሓላፊዎች በተሰበሰቡበት፣ ኮሚሽኑ ጉዳዩን በአጀንዳ ይዞ ከተወያየበት በኋላ የፍልስፍና ትምህርት ክፍሉን ጥያቄ ዳግመኛ በሙሉ ድምፅ ተስማምቶበት፣ ውሳኔው በማኅበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ ዲኑ በፕ/ር ወልደ አምላክ በዕውቀት በኩል የዩኒቨርስቲው ፕሬዝዳንት ይኹንታቸውን እንዲሰጡበት(እንዲያጸድቁት) ተጠይቆ ነበር፡፡ ፕሬዝዳንቱ ግን ከአራት ወራት ያኽል ቸልተኝነት በኋላ ‹‹ወረቀቱ ይመጣለታል›› በሚል ለተከታዩ ሴሚስተር እንዳልደለደል በአዲሱ ዲን በኩል ለትምህርት ክፍሉ ሊቀ መንበር መመሪያ አስተላለፉ፡፡ መመሪያው የእኔን መሰል ጥያቄ ባቀረቡ ሌሎች መምህራን ላይም የተላለፈ ነበር፡፡ ከሦስት ወራት በላይ ደመወዜን ይዘው መክፈል ከአቆሙ በኋላ ‹‹ለሚመጣው ሴሚስተር አትመድቡት›› ማለት በአካዳሚያ ቋንቋ ግለሰቡ ተሰናብቷል ማለት ነው፡፡
በመሠረቱ፣ የትምህርት ክፍሌና አካዳሚክ ኮሚሽኑ የሥራ ውሌን መራዘም ተስማምተው ላቀረቡት ጥያቄ ሲኾን እንደወጉ ማጽደቅ አልያም በአስቸኳይ ውሳኔን ማሳወቅ ሲገባ፣ ፕሬዝዳንቱ ከሦስት ወራት በላይ ማቆየታቸው ኢ-ሕጋዊ ነው፤ ሕጉን ጠብቆ በወጉ ለቀረበ ጥያቄ ከሦስት ወራት በላይ ምላሽ አለመስጠት እብሪት፣ ትዕቢትና ማናለብኝነት እንጂ ሌላ ሊኾን አይችልም፤ በተመሳሳይ ወቅት አንድ ዐይነት ጥያቄ በደብዳቤ ከአቀረብነው መምህራን መካከል፣ ለምሳሌ ከኛው ትምህርት ክፍል ዶ/ር በቀለ ጉተማ በሥራው እንዲቀጥል በቃል ትእዛዝ ፈቅደው፣ ለእኔ በአግባቡ ውሳኔ ሳይሰጡ ‹በሚቀጥለው ሴሚስተር እንዳትመድቡት’ ማለት የአድልዎ አቀራረብ ብቻ ሳይኾን በዘፈቀደና በግፊት የሚካሔድ አመራር መኾኑን ያረጋግጣል፡፡ በሌላ በኩል፣ ፕሬዝዳንቱ ዶ/ር አድማሱ ዩኒቨርስቲውን ለመምራት ያላቸውን ብቃት ከዚህ ቀደም በአደባባይ ስለጠየቅኹ በቂም በቀልና ኹን ብለው እኔን ለመጉዳት የደረሱበት ውሳኔ ነው፡፡
የጥናትና ምርምር ዕረፍት(sabbatical leave) በተመለከተ በጊዜው የኮሌጁ ዲን የነበሩት ዶ/ር ገብሬ ይንቴሶ፤ የፕሬዝዳንቱን ፍላጎት ተከትለው ከላይ እንደጠቀስኹት የሰጡኝን ፈቃድ መልሰው ነጥቀውኛል፡፡ ጉዳዩን ለማየት ሥልጣን ወዳለው ፍርድ ቤት ከማምራቴ በፊት፣ የፕሬዝዳንቱን ምላሽ ከወዲኹ ባውቀውም አቤቱታዬን የግድ ለእርሳቸው ማቅረብ ነበረብኝ፡፡
በኮሌጁ የቀድሞ ዲን ውሳኔ ላይ ከዐሥር ገጽ ያላነሰ አባሪ ሰነዶች አያይዤ ጠዋት ላቀረብኹት አቤቱታ፣ ከቀትር በኋላ ‹‹በጥልቅ መርምረን›› በሚል በአንድ መሥመር የኮሌጁ ውሳኔ እንደማይሻር የሚገልጽ ፌዝና የቀልድ ምላሽ ነው የተሰጠኝ፡፡ ይህ የሚያሳየው ፕሬዝዳንቱ ለዩኒቨርስቲው መምህራን ከበሬታ የሌላቸውና አመራራቸውም ከሞራላዊነት የተራቆተ መኾኑን ነው፡፡ እኔ ግን ታዋቂው አርበኛ አበበ አረጋይ በአንድ ወቅት በፋሽስት ጣልያንና በባንዳ ለተከቡበት የተራቡ ጭፍሮቻቸው ‹‹ሞተን አንጠብቃቸውም፤ ተረጋግታችኹ ብሉ›› እንዳሉት፣ ከማባረር ያልተናነሰ የዘገየ አንድ ብጣሽ ወረቀት ገና ለገና ይመጣል ብዬ ሞቼ አልጠብቃቸውም፡፡
ከዚህ ቀደም የጡረታ ጊዜያቸው ደርሶ ለማራዘም የተፈቀደላቸው መምህራን አሉ ? ማለትም በዩኒቨርስቲው አሠራር የጡረታ ጊዜያቸው የደረሰ መምህራን ውላቸውን ማራዘም ይችላሉ?
በተለምዶ ስድሳ ዓመት የሞላቸው መምህራን የውል ማራዘሚያ ጊዜ ይጠይቃሉ፡፡ እኔ የማውቃቸውና በተደጋጋሚ የተጨመረላቸው መምህራንም አሉ፡፡ በጣም አስገራሚና በግቢው አነጋጋሪ የኾነው የእኔና የዶ/ር መረራ ጉዲና የውል ማራዘሚያ ጊዜ መከልከሉ ነው፡፡
ግን የዚህ ኹሉ መነሻ ምንድን ነው ብለው ይገምታሉ?
ከኹሉ በፊት የእኔ መከልከልና መሰናበት ከፖሊቲካ እይታ አኳያ የመነጨ መኾኑ የታወቀ ነው፡፡
ማለት…
በዩኒቨርስቲው በማስተማር ሥራ በቆየኹባቸው ባለፉት ሰባት ዓመታት፣ በጽሑፍና በተለያዩ መድረኮች የማደርጋቸው የዐደባባይ አእምሯዊ እንቅስቃሴዎች አልተወደዱም፡፡ እንዲያውም ለሹመኞች ቅርበት ያላቸው አንዳንድ ወዳጆቼ እንዳጫወቱኝ፣ ‹‹ዳኛቸው፣ ዩኒቨርስቲውን እንደ ደጀንና ገዥ መሬት ተጠቅሞ መድፍ ሲተኩስብን ቆይቷል›› ተብዬአለኹ፡፡ በርግጥ ይህ ዓይነቱ አቋም ከተወሰደ በኋላ በሥራ ገበታዬ እንድቀጥል አለመደረጉ አይገርመኝም፡፡
ከዩኒቨርስቲው በዚኽ መልኩ ሲሰናበቱ ምን ተሰማዎ?
እንደ እውነቱ ከኾነ የተደበላለቀ ስሜት ነው በውስጤ የተፈጠረው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ፣ ይህ ነገር ከሰባት ዓመት በኋላ መኾኑ አስደስቶኛል። ይኸውም የመጣኹበትን የማስተማር ዓላማ ከሌሎች ባልደረቦቼ ጋር በመኾን ለመስኩ ተተኪና ምሉዕ የኾኑ ተማሪዎች ለማፍራት በመብቃታችን አስደስቶኛል፡፡ ይህ ክልከላና ስንብት በቂ ምሩቃን ባላፈራንበት ከሦስትና ከአራት ዓመት በፊት ቢከሠት ኖሮ አዝን ነበር፡፡ በኹለተኛ ደረጃ፣ ‹የዓመት ዕረፍት(ሳባቲካል) አይሰጥኽም፤ ከእንግዲኽ ማስተማርም አትችልም› ስባል ለራሴ በጥልቀት ተሰምቶኝ ያልኹት፣ ‹‹አኹን ገና ኢትዮጵያዊ ኾንኩ፤ ኢትዮጵያዊ ማለት መብቱ የሚረገጥ ማለት ነው›› የሚል ነበር፡፡ በዚኽ ሰባት ዓመት ቆይታዬ ከአሜሪካ ሳልፈታ ይዠው የመጣኹት የነፃነትና የመብት አቅዋም፣ ከአገራችን ፖሊቲካዊ ነባራዊ ዕቀባ በተፃራሪው እንደ ልቤ እንድተችና ያለገደብ እንድናገር አስችሎኝ ነበር፡፡ አኹን ግን ሥርዓቱ ‹ይኼ አሜሪካ አይደለም፤ እንደ ጎረቤትኽ ሳይኾን እንደቤትኽ እደር› ብሎኛል፡፡ ይህን ስል ግን፣ እኔ በዕድሜዬ የምወልዳቸው ልጆች በኾነ ባልኾነ ክሥ ወኅኒ ቤት ተወርውረው ባሉበት ኹኔታ ከሥራ አባረሩኝ ብዬ የማለቅስ ሰው አይደለኹም፡፡ በእኒኽ ብሩህ ተስፋ ባላቸው ወጣቶች ላይ ከደረሰው አንጻር ሲታይ መብቴ መረገጡ እውነት ቢኾንም፣ የአገራችን ተረት ‹‹እናቱ ውኃ ልትቀዳ የወረደች ልጅና እናቱ የሞተችበት ልጅ አንድ ጋር ቆመው ያለቅሳሉ›› እንደሚባለው ይመስልብኛል፡፡
በመጨረሻም በአንድ በኩል፣ በውጭ ለብዙ ዓመት ቆይቼ ስመጣ የኢትዮጵያ ሕዝብ የት ከረምክ ሳይለኝ፣ ችሎታዬ በሚፈቅድልኝ ቦታ ሥራ ሰጠኝ፡፡ ለዚኽ ትልቅ ምስጋና ነው የማቀርበው፡፡ ኾኖም በሌላ በኩል የውስጥ አስተዳደሩና የውጭ የፖሊቲካ ኃይሎች በመተባበር መክረው ከሕዝብ ባገኘኹት ቸርነት ላይ ወይነውብኛል!
ከዚኽ በኋላስ ምን ዓይነት ሥራ ላይ ለማተኮር ያስባሉ?
ይህን ጥያቄ ዴሞክራሲና የሕግ የበላይነት ባለበት አገር ብትጠይቀኝ ኖሮ፣ ጉዳዩ በራሴ የሚወሰን በመኾኑ አኹኑኑ እመልስልኽ ነበር፤ ነገር ግን እንደ ቤትኽ እደር ተብዬአለኹና የጥያቄው ምላሽ በእኔ ብቻ የሚወሰን አይደለም፡፡ እንዲያውም ጥያቄው በአንድ ወቅት ዐፄ ኃይለ ሥላሴ አሉ የተባለውን ያስታውሰኛል፡፡ አንድ ሹም ጃንሆይ ፊት ቀርበው የንጉሡ ትችትና ተግሣጽ ሲገጥማቸው፣ ‹‹እንዲያውም ግርማዊ ሆይ፣ የሰጡኝ ሹመት ይቅርብኝ፤ የአባቴን ርስት እያረስኩ እኖራለኹ›› አሏቸው፡፡ ጃንሆይም ወዲያው ‹‹እርሱንም እኛ ስንፈቅድ ነው…›› አሉ ይባላል፡፡
እኔም እንደ አቅሜ ለመሥራት ፍላጎት ቢኖረኝም፣ በቀጣይ ምን መሥራት እንደምችልና እንደማልችል ብያኔው በመሠረቱ ከእኔ ውጭ ነው፡፡ በተቻለኝ መጠን ግን በአለችኝ ቀሪ ዕድሜ አገሬን ለማገልገል ዝግጁ ነኝ፡ በዚኹ አጋጣሚ በቅርቡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሚገኝበትን ተቋማዊ ኹኔታ በተመለከተ አንድ ጽሑፍ እንደማቀርብ ከወዲኹ ለማሳወቅ እወዳለኹ፡

መንግስት ልማቱ ግጭትን ለማስወገድ ያለመ ነው ብሏል

የተለያዩ የአለም አገራትን፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን፣ የአፍሪካ ልማት ባንክንና ለጋሽ ተቋማትን ጨምሮ 27 አባላትን የያዘው ዲቨሎፕመንት አሲስታንስ ግሩፕ የተባለ አለማቀፍ ቡድን፤ በደቡብ ኦሞ በመከናወን ላይ የሚገኙ ሰፋፊ የመንግስት የስኳር ፕሮጀክቶች በአካባቢው ግጭቶችን ሊቀሰቅሱ እንደሚችሉ ባለፈው ረቡዕ ማስጠንቀቁን ብሉምበርግ ዘገበ፡፡
የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተክለ ማርያም በበኩላቸው፤ በደቡብ ኦሞ የሚከናወኑ የልማት ስራዎች ግጭትን ለመከላከል ያለሙ እንደሆኑና በአካባቢው የሚኖሩ ማህበረሰቦችም የልማት ዕቅዶቹን በተመለከተ በቂ ግንዛቤ እንዲይዙ ለማስቻል በስፋት መሰራቱን ከብሉምበርግ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ተናግረዋል፡፡
የስኳር ኮርፖሬሽን ከቻይና ልማት ባንክ ባገኘው ብድር በደቡብ ኦሞ አካባቢ ስድስት የስኳር ፋብሪካዎችን ለመገንባትና በ150 ሺህ ሄክታር ላይ የሸንኮራ አገዳ ልማት ለማከናወን እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፣ የሸንኮራ አገዳ ልማቱ የአካባቢውን ነባር ነዋሪዎች አኗኗር ሊያቃውስ ይችላል ተብሎ እንደሚሰጋ ቡድኑ ማስታወቁን ገልጧል፡፡
በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰራተኞች በስኳር ፕሮጀክቶቹ ውስጥ ለመስራት ከሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ወደ አካባቢው መግባታቸውም፣ በአካባቢው የጎሳ ግጭቶችን ሊቀሰቅስ ይችላል ያለው ቡድኑ፤ ፕሮጀክቶቹ  በአካባቢው የሚከናወኑ የንብ ማነብ፣ የከብት እርባታ፣ የእርሻና የመሳሰሉ ስራዎች ላይ ተጽዕኖ ሊፈጥሩ እንደሚችሉም ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የስኳር ፕሮጀክቶቹ ተግባራዊ በሚደረጉበት የደቡብ ኦሞ አካባቢ የሚኖሩ አርብቶ አደር ጎሳዎች፣ በፕሮጀክቶቹ ሳቢያ የግጦሽ መሬት እጥረት ሊያጋጥማቸው እንደሚችል፤ ፕሮጀክቶቹ በጥድፊያ መከናወናቸውም በአካባቢው ግጭቶች የመከሰት ዕድላቸውን ከፍ በማድረግ ረገድ አስተዋጽኦ እንደሚያደርግና ጉዳዩ በአግባቡ ካልተያዘም በአካባቢው አለመረጋጋት ሊከሰት እንደሚችል ቡድኑ ስጋቱን መግለጹንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
መንግስት በአካባቢው የሚያከናውናቸውን የስኳር ፕሮጀክቶች በተመለከተ ግልጽነትን ማሳደግ፣ የማህበረሰቦችን ሃሳብ ማስተናገድና የፕሮጀክቶቹ ትግበራ ላይ የሚታየውን ጥድፊያ በመቀነስ የልማት ሽግግሩ ግጭትን በማያስከትል መንገድ እንዲከናወን ማድረግ ይገባዋል ብሏል ቡድኑ፡፡
የቡድኑ አመራሮች ባለፈው ነሃሴ ወር ያደረጉትን ጉብኝት ጨምሮ ባለፉት ሶስት አመታት በተደጋጋሚ ወደ ደቡብ ኦሞ በማቅናት፣ ከስኳር ፕሮጀክቶች ጎን ለጎን በመከናወን ላይ የሚገኘውን የመንግስት የመልሶ ማስፈር ፕሮግራም ተጽዕኖ በተመለከተ ግምገማ ሲያደርጉ መቆየታቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡

“የአራዳ ጊዮርጊስ ደብር በገንዘብ ብክነት እና በመልካም አስተዳደር እጦት መቸገሩ ተገለጸ” በሚል ርዕስ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ የካቲት 21 ቀን 2007 ዓ.ም የወጣውን ዘገባ  “የተባለው ሁሉ ሀሰት ነው” ሲሉ የደብሩ ማህበረ ካህናት አወገዙ፡፡
ዘገባው ከሃቅ የራቀ መሆኑን ለአዲስ አድማስ የገለፁት ካህናቱ፤ በአስተዳዳሪውና በሰራተኛው መካከል ችግር አለ ተብሎ በዘገባው የተጠቀሰው ከእውነት  የራቀ ነው ብለዋል፡፡ “የደብሩ አስተዳዳሪ ሰራተኞችና ባለሙያዎችን በዛቻ ቃል ያሸማቅቃሉ የተባለውም ፈፅሞ ሃሰት ነው፤ አባታችን ይኸን አያደርጉም” ሲሉ  ተናግረዋል፡፡
“በአሁን ሰዓት ያለው አስተዳደር፣ ሰበካ ጉባኤውና የልማት ኮሚቴው በልዩ ሁኔታ ያለምንም ተፅዕኖ ሁሉም በራሱ በጎ ፍቃድ እየሰራ ነው” ብለዋል፤ ካህናቱን ወክለው የተናገሩት ሊቀ ካህናት ቄሰ ገበዝ ብርሃኑ፡፡
መምህር ወልደሰላም አለሙ በበኩላቸው፤ ደብሩ የሰላም፣ የአንድነትና የልማት ቦታ መሆኑን ጠቅሰው “በመልክአ መንክራት ኃይሉ አብርሃ የሚመራው አስተዳደር የሰላም አስተዳደር ነው” ብለዋል፡፡ በዘገባው ላይ ለግንባታ የተያዘው በጀት ከ61 ቢሊዮን ብር ወደ 80 ሚሊዮን ብር አሳማኝ ባልሆነ ምክንያት እንዲያድግ ተደርጓል የተባለው ውል ተደርጎ ሁላችንም አምነንበትና ፈርመን እድሳት የተደረገበት ነው እንጂ የደብሩ አስተዳዳሪ ብቻቸውን የወሰኑት ነገር የለም ብለዋል፡፡የደብሩ አስተዳዳሪ ለማህበረ ካህናቱ ሳያሳውቁ በራሳቸው የወሰኑት ውሳኔም የለም ሲሉም የአዲስ አድማስ ዘገባን አስተባብለዋል፡፡ “በኮንተራክተር መረጣ ወቅትም አስተዳዳሪው አማክረውን ነው ኮንትራክተሩ እንዲመረጥ የተደረገው” ብለዋል፤ መምህር ወልደ ሰላም፡፡
አስተዳዳሪው እንኳን ሰራተኛን ሊያሸማቅቁ የተጣላን አስታራቂና ሃገሪቷ ሰላም የምትሆነው ቤተክርስቲያን ሰላም ስትሆን ነው ብለው የሚያምኑ አለቃችን ናቸው ብለዋል - መምህር ወልደሰላም፡፡ በቤተ ክርስቲያኑ የገንዘብ ብክነት እንዳለ ተደርጎ የተዘገበው ሃሰት ነው ያሉት መምህሩ፤ እንኳን በገንዘብ ብክነት ሊታማ ከ40 ሚሊዮን በላይ ተቀማጭ ገንዘብ ያለው ነው ብለዋል፡፡ ይህም ለአዲስ አበባ አድባራት በሙሉ ምሳሌ እንደሆነ በመግለፅ፡፡
የማህበረ ካህናቱ ተወካዮች “አዲስ አድማስ ጋዜጣ ከቤተክርስቲያናችን ላይ እጁን ያንሳ” ሲሉም ጠይቀዋል፡፡  


አቶ ተሻገር ሽፈራው
(በአ.አ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን መምህር)

     አድማስን ከሌሎች ጋዜጦች ለየት የሚያደርገው በርካታ ጉዳዮች አሉት፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱ አጫጭር ልቦለድ ሳያቋርጥ ማስተናገዱ ሲሆን ሌላው የርዕሰ አንቀፁ ይዘትና አፃፃፍ ነው፡፡ የአማርኛ ቋንቋ አጠቃቀሙም ጥንቃቄ የተሞላበት መሆኑ ይሰማኛል፡፡ እየተጀመሩ መቋረጥ የአገራችን ጋዜጦች መገለጫ በሆነበት ዘመን፣ አዲስ አድማስ 15 ዓመታትን መዝለቁም ልዩ ያደርገዋል፡፡ አድማስን ማንበብ የጀመርኩት ገና ሲጀመር ነው፡፡ በደንብ አውቀዋለሁ፡፡ ላለፉት 15 ዓመታት የራሱን ማንነት (የጋዜጣ ሰብዕና) ገንብቶ ቀጥሏል፡፡ እኔ በማስተምርበት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎቼ ለምረቃ ጥናት ሲሰሩና አሳይመንት ስሰጣቸው አዲስ አድማስን በብዛት ይጠቀማሉ፡፡
በአጠቃላይ ጋዜጣው “አዲስ አድማስ” ተብሎ ባይፃፍበት እንኳን የሚታወቅና ለሁሉም አንባቢ የቤተሰባዊነት ቀረቤታ ያለው ሲሆን ከማነባቸው ሁለትና ሶስት ጋዜጦች ቀዳሚው ጋዜጣ ነው፡፡ በህትመት ዋጋ መናር ይመስለኛል የገፁ ብዛት እየሳሳ መጥቷል፡፡ ያም ሆኖ አድማስን ማንበብ አላቆምኩም፡፡ ለተወሰኑ አመታት እየገዛሁ አስቀምጠው ነበር፡፡ አሁንም አጓጊና ቀልብን የሚስቡ ዜናዎች ሲኖሩት እገዛዋለሁ፡፡ ቅዳሜ ቅዳሜ መግዛት የማልችልበት ቦታ ብሆን እንኳ በዌብሳይት  ሳላነብ የምቀርበት ጊዜ የለም፡፡ በሁላችንም ህሊና ውስጥ በጎ ተፅዕኖ ያሳረፈ ጋዜጣ ነው፡፡ የተዋጡና እንደ ጎደሉ የሚሰሙ አምዶችና ጸሐፍት አሉት፡፡ የቀድሞዎቹም የአሁኖቹም ግን እንደየጊዜያቸው አሪፎች ናቸው፡፡ በተረፈ ጉድለቶቹን እየሞላ፣ እያስተካከለ፣ እያገለገለን ሌሎች አስራ አምስት ዓመታትን እንዲቀጥል እመኛለሁ፡፡

ጥላሁን ጉግሣ
(የቴያትርና የፊልም ደራሲ፣ ዳይሬክተር፣
ተዋናይና የማስታወቂያ ባለሙያ)
       አዲስ አድማስ ጥሩ ጋዜጣ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ ጥሩነቱ በቀለሙ ወይንም በወረቀቱ አይደለም፤ በይዘቱ ነው፤ በሚሰጣቸው መረጃዎች፡፡ በአምዶቹ አስተማሪነትና አዝናኝነት ነው፡፡ መረጃዎቹ የጋዜጠኞቹን መረጃ የመፈልፈል ብቃት የሚመሰክሩ ናቸው። አምዶቹ የተለያዩ ሰዎችን የህይወት ተሞክሮና ልምድ የምንማርባቸው ናቸው፡፡ ላለፉት 15 ዓመታት በጥንካሬ ለመቆየታችሁም ሚስጥሩ ይኸው ነው፡፡ ለወደፊቱም በዚሁ እንድትቀጥሉና የተሻሉ ስራዎችን እንድታስነብቡን እመኛለሁ፡፡