Administrator

Administrator

“ልቡን በላው”... ፈሊጣዊ አነጋገር እንዳይመስላችሁ። በደቡብ አፍሪካ የኬፕታውን ነዋሪ የሆነው የዚምባብዌ ተወላጅ እንደ አውሬ ነው፤ የባላንጣውን ልብ ሲበላ የተገኘው። አስደንጋጩ ወንጀል የተፈፀመው በቀድሞ ፍቅረኛው ቤት ውስጥ ነው።
የፀብ ምልክት አልነበረም ብላለች የቀድሞ ፍቅረኛው። ከተለያዩ ቆይተዋል። በድብቅ የተደረገ ነገር የለም። ከሱ ተለይታ ከ62 አመት አዛውንት ጋር መኖር ጀምራለች።  ባለፈው ረቡዕ እለት የቀድሞ ፍቅረኛዋ ቤቷ ድረስ ሲመጣ፤ ክፉ ነገር እንዳልጠረጠረች ገልፃ፤ መጠጥ ገዝቼ እንዳመጣ ገንዘብ ሰጥቶኛል ብላለች።
አፍታ አልቆየችም። መጠጥ ገዝታ ስትመጣ፤ ቤቱ ደም በደም ሆኗል። የ62 ዓመቱ አዛውንት በቀድሞ ፍቅረኛዋ ተወግተው ሞተዋል። አንገታቸው በስለት ቆስሏል። ፊታቸው ተነክሷል፤ በጥርስ ተቦጭቋል። ጩኸት ሰምተው የመጡ ጎረቤቶች ወደ ቤት መግባት እንዳልቻሉና በመስኮት ለማየት እንደሞከሩ ጠቅሰው፤ የአዛውንቱን ሆድ ቀድዶ ልባቸው ቆርጦ ሲበላ አይተናል ብለዋል። በድንጋጤ የተደናበሩት ጎረቤቶች ፖሊስ ከጠሩ በኋላ ነው ወንጀለኛው የተያዘው።

       ግንቦት 9 ቀን 2006 ዓ.ም በወጣው የጋዜጣችሁ ዕትም፣ ጤና ዓምድ ላይ “የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች በአሳሳቢ ደረጃ ላይ ናቸው ተባለ” በሚል ርዕስ ያወጣችሁትን ዘገባ የኢትዮጵያ የጥርስ ህክምና ባለሙያዎች ማህበር ተመልክቶታል፡፡
በጥርስ ህክምናም ሆነ በየትኛውም የህክምና ዘርፍ ያሉ ጉድለቶችን በማሳየት እርምት እንዲደረግና ህብረተሰቡ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኝ ማሳሰባችሁ አግባብነት ያለው ነው፡፡ ሆኖም የሰራችሁት ዘገባ ማህበረሰቡን ፍርሀት ውስጥ የሚከትና የተሳሳት መረጃ የሚሰጥ  ሆኖ አግኝተነዋል፡፡
ከሁሉም በላይ በማንኛውም ዜጋ ላይ እንዲደርስ የማንመኘው ችግር የደረሰባት እህታችን፤ የኛም ጉዳይ ነችና ህመሟ ይሰማናል፤ ችግሯም ይመለከተናል፡፡ ነገር ግን ባለሙያ ያልሆኑ ጥቂት ሰዎች በሚሰሩት የተሳሳተ ስራ /በእርግጥ የተባለው ታሪክ ከተከሰተ/ ምክንያት “አብዛኞቹ ክሊኒኮች” ተብሎ መዘገቡ በእጅጉ ያሳምማል፡፡
ለመሆኑ አንድ የጥርስ ህክምና ክሊኒክ ለመክፈት የሚያስፈልገውን መስፈርት አንብባችሁታል? ታዲያ ያን ሁሉ ገንዘብ አፍስሶ፣ የተሳሳተ ስራ በመስራት የሚደሰት ባለሙያ ይኖራል? ለመሆኑ የህክምና መሳሪያዎችን መቀቀያ ማሽን ዋጋው ስንት ነው? ደግሞስ ሃኪሙ ምን ያህል ሞኝ ቢሆን ነው በአግባቡ ንፅህናው ባልተጠበቀ መሳሪያ እየሰራ ከታካሚውም በላይ እራሱን ለበሽታ የሚያጋልጠው? እውነት እናውራ ከተባለ አይመስልም!!!
ዘገባውን የሰሩት ጋዜጠኛስ መሳሪያዎቹን “አየሁ አላየሁም” የሚሉት፣ ስለህክምና መሳሪያዎቹ እውቀት ኖሯቸው ነው ወይስ የነገሯቸውን ብቻ ይዘው ነው? መቼም ስለሚሰሩት ዘገባ መረጃ ቀድሞ መጠየቅ ግዴታ ይመስለናል፡፡ በእርግጥ ዕውቀቱ፣ ችሎታውና ልምዱ የሌለው በልምድ የሚሰራ ተራ ግለሰብ የህክምና ስህተት ሰራ ቢባል ያስኬዳል፡፡ ባለሙያ ያልሆነ ሰው ምን እንደሰራና ምን እንዳጠፋ ለይቶ አያውቅምና፡፡ እንዲህ ያለው ዘገባ፣ በአሁኑ ሰዓት የህክምና ባለሙያዎች ማህበረሰቡን በምን አይነት ሁኔታ ውስጥ ሆነው እያገለገሉ እንዳሉ ካለመረዳት ወይም ለመረዳት ካለመፈለግ የመነጨ በመሆኑ ማዘናችንን እንገልፃለን፡፡
የእህታችን ታሪክ የተገለፀበት መንገድና የተብራሩት ችግሮችን ለመተቸት እውነተኛውን ታሪክ ማግኘትና መገምገም ይጠበቅብናል፡፡ ሳናነሳ የማናልፈው ግን የጥርስ ህክምና ለመስጠት የሚችሉ የተለያዩ ባለሙያዎች መኖራቸውን እንድታወቁ ሲሆን ዘገባው የሚገልፀው አይነት የጥርስ አካል አለመኖሩንና በተጠቀሰው ሆስፒታል ውስጥ የጥርስ ህክምና ክፍል እንደሌለ እንዲሁም የጥርስ ሀኪም አለመኖራቸውን ነው፡፡ አስተያየት ሰጥተዋል የተባሉት የጥርስ ሀኪምም የማህበሩ አባል አይደሉም፡፡ በዘርፉ የተሰማሩ ባለሙያዎችን ጠይቀንም የሚያውቃቸው አንድም ሰው አላገኘንም፡፡ ከአንድ ባለሙያም ይህን አይነት አስተያየት እንደማይሰጥ ስለምናምን፣ የዘገባው አላማ ሌላ ሊሆን እንደሚችል ገምተናል፡፡
ህብረተሰቡ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኝ ማድረግ፤ ባለሙያውም ተገቢውን ስራ በተማረበት መስክ እንዲፈጽም ግዴታዎቹን በአግባቡ ተወጥቶ፣ መብቱም እንዲከበርለት መስራት የተቋቋምንበት ዋና ዓላማችን ነው፡፡ ለዚህም ሚዲያው ያለው ድርሻ ጉልህ መሆኑን ከልባችን እናምናለን፡፡ ነገር ግን የአገሪቱን አቅምና የባለሙያውን ሁኔታ ባለማጤን “አብዛኞቹ” ክሊኒኮች በሚል የወጣው ዘገባ፤ ለህብረተሰቡ የተሳሳተ መረጃ በማድረስ፣ ሥራችንን ካለውም በላይ ከባድና ውስብስብ ስለሚያደርግብን እባካችሁ በጥንቃቄ ዘግቡ እንላለን፡፡ በተረፈ ማናቸውንም መረጃዎች ለመስጠትና በዘርፉ ለሚከሰቱ ችግሮች አፋጣኝ የመፍትሔ እርምጃ ለመውሰድና በትብብር ለመስራት ፈቃደኞች መሆናችንን እንገልፃለን፡፡  

Saturday, 14 June 2014 12:22

ለማሸነፍ

ጋሻው በጠባቧ ስቱዲዮ ውስጥ በዘረጋት አነስተኛ አልጋ ላይ በጀርባው ተንጋሎ ይቃትታል፡፡ በእልህ ይቃጠላል ፣ በብሽቀት ይወራጫል፣ በምኞት ይንጠራራል . . .
እንደተንጋለለ ዓይኑን ፊት ለፊቱ በሰቀለው ፎቶ ግራፍ ላይ ወረወረ፡፡ እይታው እዚህ ትልቅ ባለቀለም ፎቶ ግራፍ ላይ ካረፈ በቀላሉ አይነሳም፡፡ ቀይ ዳማ ሴት፣  አንገቷን ቀለስ አድርጋ በዓይኖቿ ጠርዝ ታስተውለዋለች፡፡ ዛሬስ «አይ አሸናፊው» እያለች የምታሾፍበት መሰለው፡፡
ትልቁን የሀናን ፎቶ ግራፍ ዘወትር በዓይኑ እንዲዳብሰው ከሚጋብዙት ነገሮች ዋንኛው ዳሌዋ ነው ፡፡
ዳሌዋ ፣ልክ እንደ ዋንጫ ከላይ ሰፋ ብሎ ወደታች እየጠበበ መውረዱ ያስደንቀዋል፡፡
«ወይ የሰው ልጅ !»አለ ባግራሞት «ለካስ የዋንጫን ዲዛይን የኮረጀው ከውብ ሴቶች ዳሌ ነው።
አቤት ተንኮል ! ለካስ ለዋንጫ የመንሰፍሰፋችን ምስጢር ይህ ሆኗል? ሴቶቹም ቢሆኑ ለራሳቸው የአካል ቅርፅ ያላቸው ፍቅር ሳያውቁት ለዋንጫ እንዲሳቡ ያደርጋቸዋል፡፡ እኛም እንዲሁ ሳይገባን የወንድነታችን ስሜት በረቀቀ ሁኔታ ይማልላል. . . » እያለ ይፈላሰፋል፡፡
* * *
. . .  ሃና በፎጣ ተጠቅልላ ከባኞ ቤት እንደወጣች ወደ መኝታ ክፍሏ አመራች፣ ከውስጥ ሆና በሩን ዘጋች፡፡ ያገለደመችውን ፎጣ ከላይዋ ላይ ገፋ በመጠቅለል  ወረወረችው፡፡ ዕርቃኗን ሆነች ፡፡ እየተዟዟረች  ቁመናዋን  ገመገመች  ፣  በተፈጥሮዋ  ተደሰተች፡፡ «የሚሊኒየሙ አሸናፊ ሴት!»  አለችና ፈገግ ፣ ወዲያው ኮስተር፣ እንደመጸየፍ ደግሞ ፈገግ፣ አይኗን ቦዘዝ፣ ሰለምለም . . .   ይህን ጊዜ ጋሻው ወደ አዕምሮው ገባ ፡፡
አፈረች፡፡ እሮጣ  የወረወረችውን ፎጣ አነሳች፣ ተሸፋፍና ቆመች፡፡ ልቧ ደነገጠ፣ ሌሊት በህልሟ አይታዋለች፡፡ ጭልጥ ባለ የሳር ሜዳ ላይ ያገኛታል . . .
በህልሟ፡-
ይቀርባታል «ዛሬ ራቁትሽን ፎቶ ላነሳሽ ፈልጌ ነበር፡፡»
«ምንም ሳልለብስ?»
«አዎ! ዕርቃንሽን ትሆኚና እኔ በማሳይሽ ስታይል
አነሳሻለሁ፡፡ በዚህ ፎቶ የአለም «ሚስ ሞዴሊንግ»  አሸናፊዎች እንሆናለን!»
ትጓጓለች፣  ታቅማማለች፣  ይህን  ጊዜ  ጋሻው  ስውር ይልባታል «እሺ» ትላለች ዛሬ በእውኗ፡፡ ለሕልሙ አለም ጥያቄ በገሃዱ ዓለም መልስ ሰጠች። የሰማት ግን የለም፡፡ ብቻዋን ናት መኝታ ቤቷ ውስጥ፡፡
«እንዴ! ጋሻውንም ልወደው ነው?» ራስዋን በፍርሃት ጠየቀች፡፡ እሷን እንደመውደድ የሚያስፈራት ነገር የለም፡፡
ሰዓቷን ተመለከተች፡፡ ከቶማስ ጋር የመገናኛቸው ሰዓት! «የራሱ ጉዳይ!» አለች ብስጭት ብላ... ሦስት ጊዜ በተከታታይ ቀጥሯት መቅረቷን አልረሳችም፡፡ አሁን ደሞ አራተኛ መሆኑ ነው፡፡
«አሁንስ ያመራል»
«ያምርራ! ምን ያመጣል!» ከራስዋ ጋር ሙግት ገጠመች፡፡ በግቧ መሰረት ማንነቷን ማግኘት፣ የዓለም ምርጥ ሞዴሊስት በመሆን ራሷን፣ ቤተሰቧን፣ ሀገሯን ማኩራት ይጠበቅባታል፡፡ የዚህንም ጊዜያዊ የምስክር ወረቀት ከጋሻው እቅፍ ውስጥ መውሰድ ይኖርባታል፡፡
«የእኔ እጣፈንታ አለማቀፋዊ ዝና ነው! ከጋሻው በቀር የሚቀርቡኝ ወንዶች ሁሉ፣ ሚስት እንድሆናቸው፣ ምግብ እንዳበስልላቸው፣ ልጅ እንድወልድላቸው፣ ምናምን ነው የሚፈልጉኝ። ድንጋዮች! ከእንግዲህ እኔን ለእንዲህ  ዓይነቱ አነስተኛ ዓላማ ማጨቱ አበቃ፡፡
ዛሬ ሄጄ ከምንም በላይ ውድ የሆነ ዓላማዬን መስመር ማስያዝ አለብኝ፣ ሰማይ ጥግ ወደሚገኘው ዙፋኔ አስፈንጥሮ ለሚያደርሰኝ ለጋሻው በመውጣት፣ ፍቅርን በልቡ ማቀጣጠል፣ እሱን የሙጥኝ ይዤ አብሬው መተኮስ. . . »
እቅዷን በሃሳቧ እያውጠነጠነች ከመስታወቱ ዞር ብላ ልብስ መራረጠች፡፡ ከጉልበቷ በላይ የምትንጠለጠል ጉርድ ቀሚስ፣ እንበርቷን የምታሳየው ካኔተራ፣ ክፍት ጫማ፣ ከመስታወቱ ፊት ቆመች ቅልል ያለች ፍልቅልቅ ሴት «እምጵዋ!» የራሷን ምስል ሳመች ፡፡
ብር ብላ ከግቢያቸው ወጣች፡፡ ሚኒባስ ታክሲ መጣ፡፡ የጋቢናውን በር ከፍታ ገባች፡፡ ሹፌሩ ተነቃቃ፣ የሙዚቃውን ድምጽ ጨምሮ ተፈተለከ፡፡
የሞባይል ስልኳ በንዝረት መጥራት ጀመረች፣ ቁጥሩን ተመለከተችው፣ ቶማስ ነው! አላነሳችውም። ደጋግሞ ነዘራት፣ ዝም አለችው «ግፋ ቢል ያቺ ሳንቲሙ ነች የምትቀርብኝ ፣ ዘላለም በሱ ድጎማ እኖራለሁ እንዴ ? ገደል ይግባ !» እያጉረመረመች ወንበሯ ላይ ተመቻቸች፡፡
* * *
ጋሻው ከአስር ለሚበልጡ ዓመታት ፍላጎቱን ገድቦ፣ትዳር ሳይመሰርት፣ ንብረት ሳያካብት ፣ ትኩረቱን በሙሉ ሥራው ላይ በማድረግ ዓለማቀፋዊ አሸናፊነትን ለመቀናጀት ወጣ፣ ወረደ፣ አሸናፊነት እንደከበረ እንቁ ውድ ሆነችበት፡፡ ለበርካታ ጊዜያት፣ ተሳካልኝ ሲል ተንደባሏል፡፡
«አረ የድል ያለህ !» ውስጡ ጮኸ፡፡ እጁን ወደ ራስጌው አካባቢ ሰዶ አንድ ኤንቨሎፕ አወጣ፣ ሲውዲን ፣ እስቶኮልም ሚገኘው ዓለም አቀፍ የፎቶ ግራፍ ውድድር አዘጋጅ ማዕከል የተላከ ነው፡፡ በውስጡ መጽሔት ይዟል፡፡
አሱም የዚህ ውድድር ተካፋይ ነበር፡፡ በመጽሔቱ የላይኛው ሽፋን ላይ አሸናፊ የሆነው የዓመቱ ምርጥ ፎቶ ታትሟል፡፡ ምስሉ አክሊል የደፋች ንግስት በዙፋኗ ላይ እንደተቀመጠች ያሳያል፣ ድባቡ በጣም ደስ አለው፡፡ ፀጥታን ሳይቀር የመዘገበ ድንቅ የእንግሊዝ ሀገር ፎቶ ነው፡፡ ክብር፣ ውበትና ሰላም ይነበብበታል፡፡
መጽሄቱን ገለጠው፣ የሕንድ ቆንጆ! አሁንም
ገለጠው፣ እርጅና በአስፈሪ ክንዱ የደቆሳት የጀርመን አዛውንት! አረጋዊነትን ውብ አድርጎ አቅርቧል፡፡
አሁንም ገለጠው፣ የሩቅ ምስራቅ ልጃገረድ ዓይኗን ጭፍን አድርጋ ተንከተከተችበት! ቶሎ ገለጠው፡፡ አሁንም ገላለጠው! የሱ ሃና የለችም፡፡
እርር አለ! ወደ ፎቶ ግራፍ ሙያ የተሰማራበትን ቀን አስታውሶ ተፀፀተ፡፡ በመስራት ያሳለፋቸውን ከአስር የማያንሱ ዓመታትን ረገመ፡፡ አልቅሶ ቢወጣለት ተመኘ፣ ይህንንም አልቻለም!
በሩ ተንኳኳ. . . ከነ እልሁ፣ ከነብግነቱ ተነስቶ ከፈተው፡፡
ሃና ነች፡፡
ዓይኖቹ የጋለ ብረት መስለዋል፣ በመጀመሪያ ያረፋት በጡቶቿ ክፍላት ላይ ነው፣ ደነገጠ ፡፡
«አንድ» አለች በልቧ፡፡
ከዚያም  እይታው  ቁልቁል  ተንሸራቶ  ጭኖቿ  መሀል ተሰነቀረ፡፡
«ሁለት»
ወዲያው ሽቅብ አነጣጥሮ ከናፍሮቿን ቃኘ
«ሦስት» ፈገግ አለች፡፡
ከመቅጽበት ዓይኖቹን በዓይኖቿ ውስጥ ሰደዳቸው፣ ፍትወተ ሥጋ ቦግ ብሎ ታየው፡፡ አሁን እሱም ሳቀ፡፡ «ታድያስ ሃኒ» እጁን ዘረጋላት፡፡
የቀኝ ጉንጯን አስጠጋችለት፡፡
ሳመው፡፡
የግራ ጉንጯን ሰጠችው፡፡ ደገመው፡፡
ጉንጮቿ የተቀደሱላት መሰላት፡፡ እፎይታ ተሰማት፡፡
ወደ ውስጥ እንድትዘልቅ ጋበዛት፡፡ ሰተት ብላ ገባች . . .
ከሴቶች ጋር የሚኖርህ ቀረቤታ ላይ ጥንቃቄ ማድረግህን አታላላ፡፡ ሴቶቹን ሳይሆን እነሱን ተከትሎ የሚመጣው ትኩረትህን የሚሰርቅህን ስሜት ፍራው፣ ጥላው ሽሸው! ይህ ስሜት ባንተ ላይ ሲበረታ፣ስራ አስፈትቶ በሐሳብ ሲያናውዝ አይተኸዋልና የገዛ ህሊናው አንሾካሾከለት፡፡
ሃና ከስቱዲዮና   መኝታ ቤቱ ጋር በተያያዘችው ጠባብ ሳሎን ውስጥ ነግሳለች፡፡
«ዋው. . . ደረትህ እንዲህ ፀጉር በፀጉር አይመስለኝም
ነበር»
አሁን ይሄ ምን ያስደንቃል? በውስጡ ተቃወመ።
«ወደ ዓርባ ምንጭ እሄዳለሁ ያልከው መቼ ነበር?»
«ነገ ጠዋት አስራ ሁለት ሰዓት ገደማ ከዚህ እወጣለሁ»
ዓይኖቹን ማስቀመጫ እንዳጣለት ዕቃ እያንከራተተ መለሰላት፡፡
«ለምን እኔም አብሬህ አልሄድም? ወደ ደቡብ  እኮ ምንም ሀገር አላውቅም» በዓይኖቿ ቀስፋ ይዛው ትማፀነዋለች፡፡
«በእውነት?»
«ጋሻዬ ሙት ስልህ» ገላዋ ሁሉ በራ፡፡
«እነ ላንጋኖ፣ ሻላ፣ አዋሳ ሐይቆችን አታውቂያቸውማ?»
«የት አባቴ ሄጄ? »
«አዞ፣ ጉማሬ፣ ሰጎን  አይተሸ አታውቂማ?»
«ጋሻዬ ስሞትልህ?» ቅላፄዋ ሊያስፈነጥዘው ደረሰ፡፡ ሁለንተናው ሞቀ «በይ እንግዲህ ለለሊት 12 ሰዓት ተዘጋጂ ፣ እወስድሻለሁ»
«በጣም አመሰግናለሁ ጋሻዬ!»  ተወርውራ ተጠመጠመችበት፤ ዓይኖቹ ከስቱዲዮ ጋር ከተያያዘችው የመኝታ ቤቱ በር ላይ ተጣበቁ፡፡ የተገዛለት አላማ ተፈተነ፡፡
* * *
እሁድ፡፡
ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት፡፡
2000 ዓ.ም
በደቡቡ የኢትዮጵያ ክፍል፣ ከጂንካ ወጣ ብላ የምትገኝ፣ ቃቆ የምትባል ቦታ ላይ ፡-
«ከምድር እኩል የተፈጠረው ንፁህ አየር ይኸውልሽ» አለ ጋሻው እንደ ጥላ የምትከተለው ሃናን እያየ፡፡
«እንዴት ደስ ይላል ! የተራራው አቀማመጥ፣ የዛፎቹ አቋቋም፣ የወንዞቹ አወራረድ» ዙሪያ ገባውን አደነቀች፡፡
«በዚህች ቃቆ በምትባል አካባቢ በና የሚባል የጎሳ መጠሪያ ያላቸው ኢትዮጵያን ይኖራሉ፡፡ ወዲያ ማዶ ደግሞ ማሊ የሚባሉ አሉ ! የሁለቱም ጎሳ አባላት ልብስ የሚባል ነገር አያውቁም፣ እንዲያው ሀፍረታቸውን ለመሸፈን ያህል ብቻ ትንሽዬ ቆዳ ያንጠለጥላሉ. . .»
«አ . .  ሃ . . . ከቡስካ በስተጀርባ የተባለው መጽሀፍ
ውስጥ እንዳሉት ሀመሮች?»
«አዎ፡፡ አንብበሽዋል?»
«እንዴ? ለዛውም ደጋግሜ ነዋ»
«ብራቮ ሃኒ »
ዛሬ በመካከላቸው ከፍተኛ የመሳሳብ ስሜት አለ፣ በየደቂቃው ትደገፈዋለች፣ በየምክንያቱ ያቆላምጣታል፣ ብዙ ያወራሉ፣ በጋራ መምጣታቸውን ወደዱት፡፡
ረጅሙን የዙም ሌንስ በዘመናዊ ካሜራ ላይ እየገጠመ «አሁን እስከ ሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት   ማንሳት እችላለሁ!» አላት፡፡
በጣም ተደነቀች፡፡
ካሜራውን ለመግዛት ያየውን ፍዳ እየተረከላት፣ ወንዙ ዳር ያለችው ዛፍ ላይ ወጣና ወዲያ ማዶ ደን ላይ አነጣጠረ፡፡ ምንም የለም፡፡ ወዲህ አነጣጠረ እንደዚያው ነው፡፡ ዱብ ብሎ ወረደ፡፡
በዛፍና ቅጠላ ቅጠሉ መሃል እየተሽሎኮለኩ፣ በሳቅ እየተፍነከነኩ ገላጣ ቦታ ላይ ብቅ አሉ፡፡
አፍረቷ አካባቢ ብቻ ሦስት ማዕዘን ቁርበት ጣል ካደረገች የበና ልጃገረድ ጋር ተፋጠጡ፡፡ ደንግጣ እንደሐውልት ድርቅ አለች የበናዋ ቆንጆ። ጡቶቿ ለመተኮስ የተወደሩ ሮኬቶች ይመስላሉ፡፡ በቀይ አፈር የታሸው ፀጉሯ ቁልቁል ይጥመዘመዛል። ከቀላጭ ብረት የተሰሩ ሦስት ቀለበቶች በአንገቷ ዙሪያ ተጠምጥመዋል፡፡
ሃና አፏን ከፈተች፡፡ የበናዋ ቆንጆ ተክለሰውነት ትንግርት ሆኖባታል፣ ጠይምነቷ ወከክ ያደርጋል፡፡
ጋሻው ቀስ ብሎ ጣቶቹን ከካሜራው ጋር አገናኘ። ልጃገረዲቱ ሃናን በዓይኖቿ ወጋቻት፡፡ ጆሮዎቿም ትልልቅ ሎቲዎችን አንጠልጥለዋል፡፡ ክንዶቿ ከላይ እስከታች በመዳብና ቀላጭ ብረቶች አጊጠዋል፡፡
የጋሻው፣ የሃና፣ የበናዋ ጉብል የልብ ትርታ ቆሟል። የዓይን እርግብግቢት ሳይቀር ተቋርጧል። ፀጥታውን የሚያደፈርስ ጠፋ፣ የበና አሞሮች ክንፋቸውን ሳይቀዝፉ በርቀት ቁልቁል ያስተውላሉ...
የበናዋ ቆንጆ ፊት ላይ ታሪክ ይነበብ ጀመር፡፡ ቁጣ፣ ድፍረት፣ ግርምት!
ጋሻው  ካሜራውን  ዓይኑ  ላይ  ሳያደርግ  በግምት  በማንሳት ተክኗል፡፡ የበናዋ ጉብል አፈገፈገች። የሃና ዓይኖች ልጃገረዲቱ ባዶ እግሮች ላይ አረፉ። አልቦዎቿ አንፀባረቁባት፡፡ ጉብሊቱ አፈገፈገች፡፡ ጋሻው የካሜራውን መምቻ ተጫነ፡፡ ቀጭ!
ቱር አለች እንደሚዳቋ፡፡
«ወይኔ ጋሻዬ አመለጠችህ?» ሃና ጮኸች፡፡
የበና አሞሮች ክንፋቸውን አማቱ፡፡ እነሱም አንቋረሩ ለቆንጇቸው!
ጋሻው ዘሎ ከፍታ ላይ ወጣ፡፡ ካሜራውን ዓይኑ ላይ ነው፡፡ በሌንሱ ውስጥ የጉብሊቱ ምስል ይርመሰመሳል፡፡
«ከሞን!» ይላል ጋሻው ሌንሱን ዞር፣ ቀጭ! ዞር ቀጭ! በተከታታይ የካሜራውን መምቻ ተጫነው፡፡ ፊልሙ ሲያልቅ ቆመ፡፡ በፍጥነት ቀይሮ አነጣጠረ፡፡
የበናዋ ቆንጆ የለችም፡፡
ካሜራውን ለቀቀው፣ አንገቱ ላይ ተንጠለጠለ። ሁለት እጁን ወደ ቃቆ ደመና ወጠረ፣ አምላኩን ማመስገን ሲፈልግ ሁለት እጁን ወደላይ ይወጥራል፡፡
ከከፍታው ላይ ዱብ እንዳለ ካሜራውን ወደ ጀርባው አዞረና ሀናን አቀፋት፡፡
የበና አሞሮች ሌላ ትእይንት ያዩ ጀመር፣ መቅዘፋቸውን ትተው ቁልቁል አሰገጉ. . .
በመጪው ዓመት ካናዳ ቶሮንቶ ውስጥ በሚካሄደው ዓለም አቀፍ የፎቶ ግራፍ ውድድር አሸናፊነቱን ደመነፍሱ ከወዲሁ ሹክ
አለችው፡፡ ስለዚህ ሀናን እንዳቀፋት አንገቷ ሥር ይስማት ጀመር፡፡ የበናዋ ጉብል በስቱዲዮ የታጨቁ ፎቶ ግራፎቹን ነፃ ስታወጣለት ታየው፡፡
ሀና ከናፍርቷን ወደ ከናፍርቱ በመስደድ ላይ ነች፣ ጡቶቿ እስኪፈርጡ ተለጥፋበታለች፡፡
«ሄይ . . . ሄይ . . . ሄይ . . . ጃላ . . .  ጃላ . . .!» ይላል አንድ ሸካራ ድምጽ እንደብራቅ ጮሆ፡፡
ጋሻው ሀናን ለቆ ዞር አለ፡፡
የበናው ወጣት ቁራጭ ቁርበቱን እንዳገለደመ በግራ እጁ ቅቤ የጠጣ በርኮታ፣ በቀኝ ክንዱ የእባብ መርዝ የተለወሰ ቀስቱን እንዳነገበ በኩራት ቆሟል፡፡
ሀና የዓለሟ ፍፃሜ የሆነ መሠላት፡፡
የጋሻው ፊት እንደ በና ፀሐይ አበራ፣ ቅንድቦቹ ሽቅብ ተነሥተው ፀጉሩ ውስጥ ተወሸቁ፡፡ ዓይኖቹ ከመበልጠጣቸው የተነሣ ወልቀው የሚወድቁ እንክብሎች መሰሉ፡፡ ልክ እንደበና አሞሮች ክንፉን ዘረጋ «ሃይ ሃይ ጃል» ብሎ አጸፋውን መለሰ ድምጹ በበና ግዛት ውስጥ አስተጋባ፡
አሞሮቹ ግራ ገባቸው፡፡
ሮጦ አቀፈው የበናውን ወጣት፡፡
እሱም ቀስትና በርኮታውን ቁልቁል ለቀቃቸው፣ ሳሩ ውስጥ ሰጠሙ፡፡
የበናው ወጣት ፈነደቀ ፣ጋሻው ቀልቡን ሳተ «የክፍለ ዘመኑን ፎቶ አገኘህ» እያለች ደመነፍሱ ደስታውን አበዛችለት፡፡
ሀና ራሷን ጠዘጠዛት፣ እያዞራት ነው፡፡
የበናው ወጣት እግሩ ሥር ያስቀመጠውን ቅል ከሳሩ ውስጥ አወጣና ለጋሻው ሰጠው፡፡
ጋሻው አላቅማማም ግጥም አድርጎት ጠጣ፣ ዞሮ ሀናን ያናግራታል «ሀኒ ነይ ወዲህ፣ ይህ ጃላዬ ነው። ተዋወቂው፡፡ በበናዎች ቋንቋ ጃላ ማለት ጓደኛዬ ማለት ነው፡፡ እንዴት ያለ ወዳጄ መሰለሽ . . . » እያለ ቅሉን ይሰጣል «ቅመሺው!»
ጎንጨት ታደርገዋለች፡፡ ቆመጠጣት ቀና ብላ አየችው፡፡
«ዋጭው  ምንም  አይልሽም፣  የማሽላ  ቦርዴ  ነው፣  ጨቃ ይባላል»
ነጭ ነገር ተፋች፡፡
የበናው ወጣት ሳቀ . . .
ጋሻው የበነዋ ጉብል ባሳደረችበት ብሩህ ተስፋ ተነቃቅቷል፡፡ ያለውን ገንዘብ አሟጦ፣ ከሚያውቃቸው ሁሉ ተበድሮ፣ ካነሰውም ንብረቱን በሙሉ ሽጦ፣ ተጨማሪ ፎቶ ግራፎችን ከወሎ፣ ትግራይና ሐረር ማንሣት አለበት፡፡ ከነዚህ መካከል መርጦ በሚልከው በአንዱ ማሸነፉ አይቀርም! ካሸነፈ ሽልማቱ የሃናን ዳሌ የመሰለ ዋንጫ አይደለም፡፡
በአወዳዳሪው  ድርጅት  ስፖንሰር  አድራጊነት  ዓለም  አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ኢግዚቢሽን እንዲያዘጋጅ እድል ይሰጠዋል፡፡ የዕድሜውን አጋማሽ ለሚክል ጊዜ የሰበሰባቸው ፎቶ ግራፎች ቀን  ወጣላቸው  ማለት  ነው፡፡  ተወዳጅ  የሆኑት በጨረታ ይቸበቸባሉ። ያልተሸጡትም ቢያንስ የሀገሪቱን ወርቃማ ባህል፣  ጀግንነት፣ ውበትና ማንነት ለዓለም ሕዝብ በጣፋጭ ለዛቸው ይሰብካሉ።
በኢግዚቢሽኑ የሚያገኘውን ክብር፣ ቱጃር የሚያደርገው ረብጣ ዶላር፣ በቀጣይ ዘመኑ የሚኖረውን የሙያ መሣሪያዎች፣ ያሠራር ደረጃና፣ የአሸናፊነት ሌሎች ፀጋዎች ሁሉ ታዩት፡፡ የጨበጣቸው ያህል እየቋመጠ፣ በቁሙ እያለመ ሳለ ጀምበር በስተ ምሥራቅ እርቃኗን ብቅ አለችለት፡፡ የመጨረሻው ፎቶ ሆና  በካሜራው ጠቀሳት፡፡
ወዲያው   የተከራያት   መኪናን   በመጣችበት   ፍጥነት እያስወነጨፈ ወደ አዲስ አበባ መመለስ ጀመሩ...
ለሊቱን ሙሉ በበናዎች የእሳት ዳር ጨዋታ ሲዝናና ያደረው ጋሻው፣ እጎኑ እንቅልፍ እየጣለ የሚያነሳት ሃናን እረሳ፡፡ ሃሳቡን ከመሪው ጋር እየጠመዘዘ፣ ምኞቱን ከነዳጅ መስጫው ጋር እየተጫነ ያልማል፡፡
እሷ  የሁለት  ዓመት  ምኞትዋ  መና  እንደማይቀር  እርግጠኛ ሆናለች፡፡ አልፎ አልፎ የሽርደዳ ሚመስው ፈገግታዋን ብልጭ አያረገች ትመለከተዋለች፡፡
እሱ እዚህ የለም፡፡ በሃሳብ ጠፍቷል፡፡
ሁለቱን የአሸናፊነት ጥማት ያቃጠላቸውን ተጓዦች የያዘችው መኪና የሶዶ፣ የሻሸመኔ፣ የዝዋይ አየርን ሰንጥቃ ሞጆ ደረሰች፡፡
ተፋላሚዎቹ  የደብረዘይት  ከተማን  ከሩቅ  ሲመለከቱ  ከሃሳብ ጎሬያቸው በመውጣት ተያዩ። አንዳቸው በሌላኛው ዓይን ውስጥ እንግዳ ነገርን አስተዋሉና ተሳሳቁ፡፡
ሁለቱም ድክም ብሏቸዋል፡፡ ማረፍ ይፈልጋሉ፣ ደብረዘይት ምቹ ናት፡፡ ከመኪናው ወርደው ቡና ጠጡ፡፡
«ሳሎኑ ተደፍሯል፡፡ የጉዞ  እቅዶቹ ተካፋይ ሆኛለሁ፣ የስቱዲዮ በር ቀላል ነው ፡፡
የመኝታ ቤቱ ቁልፍ ከተከፈተ አልጋ አለ፣ እዛ ላይ ከወደቅን አለቀ! ይወደኛል፡፡ ይህ ደግሞ ከባድ አይደለም ጊዜ ብቻ ያስፈልገዋል አንጂ. . . » የጣቷን  ጥፍር  በጥርሷ እየከረከመች እራሷን አረጋጋች፡፡
አዲስ አበባ ሲገቡ መሽቷል፡፡ ቤቷ በር ላይ አደረሳት። ጉንጩን ስማው ወረደች፡፡ እንደ እርጥብ ስጋ ቀዘቀዘው፡፡
* * *
ወራት እንዳአቃጠላቸው ፊልሞች ላይመለሱ ጋዩ። በቁርጠኝነት የዘመተበት ውድድር ካሰበው በላይ መስዋት አስከፍሎታል፡፡ የነበረውን ገንዘብ አሟጧል፡፡ ያችኑ ጥቂት ቁሳቁስ ሸጧል፣ የተበደራቸውንም ብሮች በተባለው ጊዜ ባለመመለሱ ቅሬታን አትርፎ መንገድ አጥቷል፡፡
አሁን ጠባቧ ስቱዲዮ ውስጥ፣ ብረት እንደታጠረበት አቦሽማኔ ይንቆራጠጣል፡፡ ከካናዳ ቶሮንቶ የተላከው የተወዳዳሪዎች ውጤት ማስታወቂያ መጽሔት እንደታሸገ ደርሶታል። ኢንቨሎፑን የሚከፍትበት አቅም አጥቶ ይሽከረከራል፡፡
በርግጥ  ኢትዮጵያን  ከዳር  እስከ  ዳር  አካልሎ  ብርቅዬ አእዋፍቷን፣ ድንቅ የመልካ ምድር አቀማመጧን፣ አስገራሚ ቅርሶቿን፣ ታሪካዊ መስህቦቿን ሁሉ ደረጃውን በጠበቀ ብቃት አንስቷል፡፡
አቅሙ የፈቀደውን ሁሉ ቢያደርግም፣ የማሸነፍ ሚስጥሩ የሚፈታው አቅም የፈቀደውን ሁሉ በማድረግ ሳይሆን ጉዳዩ ሊያስከፍል የሚገባውን ዋጋ መክፈል በመቻል ብቻ መሆኑን ማወቁ አስጨንቆታል፡፡
የታሸገው የውጤት ማሳወቂያ ኢንቨሎፕ ውስጥ ያ መፅሔት አለ፡፡ የመፅሄቱ ፊተኛ ሽፋን ላይ ያሸናፊው ፎቶ ይኖራል፡፡ እዚህ አሸናፊ ቦታ ላይ የበናዋ ጉብል ከሌለች ጋሻው ያከትምለታል! በቀጣዩ ጊዜ ስራውን በአግባቡ የሚያከናውንበት የመንቀሳቀሻ አቅም ያጣል፣ ይሰደዳል! አበዳሪዎቹ የቀረውን ካሜራና አንዳንድ ቁሳቁስም ይነጥቁት ይሆናል . . .
በዚህም አለ በዚያ በቀላሉ ለማያንሰራራበት የሞራል ውድቀት፣ የስሜት ስብራት፣ ብሎም መሰረታዊ ፍላጎቶችን ማሟላት የማይችልበት የድህነት ማጥ ውስጥ ይዘፈቃል፡፡
ጭንቀቱን የሚጋራው አጣ፡፡ ላቡ ችፍ አለ በፊቱ ላይ፡፡ በህይወት ዘመኑ የዛሬውን ያህል ጠንካራ ውጥረት ገጥሞት አያውቅም፡፡ አድርጎ የማያውቀወን ቤተአምልኮ ጎራ ማለት አማረው፡፡ እዛ ሄዶ ኢንቨሎፑን ሊከፍት አሰበ፡፡ የበናዋ ጉብል በሚፈልገው ቦታ ከሌለችስ ? እግዚኦ በሉልኝ ! ልል ነው? በራሱ ላይ ዘበተ፡፡
«ቀድሞውንም በዚህች ደሃ ሀገር ውስጥ እየኖርኩ፣ የፎቶ ግራፍ ጥበቡ የመጠቀበት ዓለም ላይ ካሉ ባለሙያዎች ጋር  መወዳደር አልፎ፣ ተርፎም ለማሸነፍ መጎምጀቴ እንዴት
አልፎ፣ ተርፎም ለማሸነፍ መጎምጀቴ እንዴት ያለ ቅዠት ነበር ?» አለ ለራሱ፡፡
ሀይሌ ገብረ ስላሴ በአዕምሮው ተከሰተ፣ የምፀት ፈገግታውን እንደ ካሜራው ፍላሽ ብልጭ አደረገበት፡፡ ዞሮ ፈለገው፣ ድንቅ ፎቶውን በስቱዲዮ ሰቅሏል፡፡ እግሩ  ስር ወድቆ ጭንቀቱን ሊያካፍለው ዳዳውና ፎቶው ፊት ቆመ፡-
«ባላሸንፍስ?»  ጠየቀው፡፡
«ትሸነፋለሃ! »
«መሸነፍ ምንድን ነው?»
«መታገልና ተረትቶ መውደቅ!»
«ማሸነፍስ?»
«ከውድቀት መነሳት!»
«በቃ?»
«አልበቃም»
«ሌላ ማሸነፍ አለ ?»
«አዎ?»
«እባክህ ንገረኝ »
«በውድቀትህ ውስጥ ባለህበት ጊዜ ፣ይህን ውድቀትክን በማሸነፍ እንደምትተካው በፍፁም እምነት ማመን»
«ማመን ብቻ?»
«አሂሂ . . .  ውጤቱ አስኪመጣ ደጋግሞ መሞከር ያስፈልጋል . . .  ይኸውልህ ምን መሠለህ . . . »
እንዳያብድ ሰጋ! ቀልቡን ሰብሰብ  አድርጎ ወደ ኢንቨሎፑ አመራ፡፡
ግድግዳውን ያጣበቡት ፎቶ ግራፎች፣ መደርደሪያው ላይ የተሰቀሉት ካሜራና ሌንሶች ሸምቅቅ እንዳሉ ኢንቨሎፑ ያመጣውን መልዕክት የሚጠባበቁ መስለው።
መንቆራጠጡን ቆም አደረገና አፈፍ አደረገው ኢንቨሎፑን፡፡ ይከብዳል፡፡ በፍጥነት ሊሸረክተው ቆነጠጠ፡፡ አይ! አይ!» ካሜራና ሌንሶቹ ሲንጫጩ ተሰማው፡፡
ፎቶ ሲያድን «ሰላይ!» ተብሎ የታሰረና የተንገላታበት ወቅት፣ በሌሊት ሲማስን በማጅራት መቺ የተዘረፈበትን፣ ጫካ ለጫካ ሲያስስ ከአውሬ መንጋጋ ለጥቂት ያመለጠበትን፣ ገንዘብ እያጠረው የተራበበትን፣ አዕምሮው ጥበቡ ላይ ተጣብቆ ገላው ያደፈበት ልብሱ የመነቸከበትን፣ ጊዜያት አስታወሰ፡፡
የአሸናፊት ጎዳናን የማይሽር የመንፈስ ደዌ  አድርጎ ቆጠረው! ለአመታት የታተረለት አሸናፊነትን ደጋግሞ ረገመው፡፡
የማይቀርለትን ጽዋ ለመጎንጨት ኢንቨሎፑን አነሳ፣ ጠበቅ አድርጎ ከያዘው በኋላ ጥርሱን ነክሶ አይኑን እንደጨፈነ ስቦ አወጣው፡፡ እንደበረደው ህንፃ አገጩ ተርገበገበ፣ ችፍ ያሉት ላቦቹ ተድበልብለው ወደቁ . . .
እንደጨፈነ መጽሔቱን ወደ ኢንቨሎፑ ሊመልሰው አሰበ፡፡ አላደረገውም! ዓይኑን ገለጠው። ከበናዋ ጉብል ጋር ተፋጠጡ! ፊቷ ላይ ታሪክ ይነበባል፡፡ ቁጣ፣ ድፍረት፣ ግርምት! ጋሻው አፈገፈገ የስቱዲዮ ግድግዳ አገደው፡፡ ህልም እንዳይሆን ሰጋ፡፡
መጽሔቱን ወደ ዓይኑ አስጠጋ፣ ሮኬቶቿ አነጣጡሩበት፣ በቀይ አፈር የታሸው ጥምዝ ፀጉሯ፣ የአንገት ቀለበቷ፣ ሁሉም
አሉ፡፡  በእጁ  ዳበሳት  አልደነበረችም፡፡  እቅፍ  አደረጋት፡፡  ሰላም ሰጠችው፡፡
«አላልኩህም»  እያለች ጮኸች ደመነፍሱ «በል ሳማት»
አዘዘችው፡፡
መጽሔቱን ሳመው፡፡ የስቱዲዮ በር ተበረገደ፡፡ አቅሉን ስቶ ወጣ፣ አስፋልት አቋረጠ፣ ታክሲ ያዘ፣ ርቆ ወረደ በተለያዩ ቅያሶች እያሰባበረ ገስግሶ እነ ሃና ሳሎን፣ በሃና ፊት ተገኘ፡፡
ሃና ጆሮ የሚበጥስ ጩኸት አሰማች፡፡ እናቷ ተንደርድረው ገቡ፡፡
መጽሔቱን እያሳየች የሆነው ሁሉ አነበነበችላቸው፡፡
ከቁብ ሳይቆጥሯት ገርምመዋት ወጡ፡፡
መጽሔቱን ገለጠችው፡፡ የግሪክ እመቤት!
ጋሻው ከጥይት ያመለጠ መሰለው፡፡
አሁንም ገለጠችው፣ የአርመን ኮረዳ ፡፡
ሃና ደነዘዘች፡፡ ገለጠችው የሩስኪ ውብ፡፡ ገለጠችው የህንድ…
የበናዋ ጉብል ናፈቀችው፡፡ መጽሔቱን ከሃና ቀማትና ወደ ሽፋኑ መለሰው፣ ሮኬቶቿን ወደረችበት። መጽሔቱን ሳመው፣ ፆታዊ ፍቅር ተፀነሰበት፡፡
«አገባታለሁ! » ሲል ተናገረ፡፡
«ምን»
«ሚስቴ አደርጋታለሁ!»
«ም . . .  ምን አልክ ጋሻዬ? » “እቺ ናት ሚሰቴ፣ አ ገ ባ ታ ለ ሁ”
«እውነት የምትለውን ታደርገዋለህ? አንተእኮ… እኔ…» የምትናገረው ጠፋት፡፡ «ይሆናል የኔ ጌታ? በመካከላችሁ ያለውን ሰፊ የባሕል ፣ የአኗኗር፣ የስልጣኔ፣ ልዩነት አላስተዋልከውም? ይህን ያህል የተራራቀ ልዩነት ያላቸው ሰዎች በትዳር ሊጣመሩ ይችላሉ? ጋሻዬ? ይቻላል ጋሻዬ?. . . »
ሀይሌ ገብረስላሴ ፈገግ አለ፡፡ ያ ህያው ምስል በጋሻው ሕሊና ደግሞ ተከሰተ፡፡ ጋሻውም እሩቅ እያለመ፣ እሩቅ እያሰበ አብሮት ፈገግ አለ፡፡
ሃና ይህን የመሰለው በረከት ተቋዳሽ ባለመሆኗ ከልቡ አዘነላት፡፡ በጓደኝነት ስሜት ጠልቆ መረመራት፣ ጉድለቷን አስተዋለ፡፡ ከሕይወት ፍልስፍናው ይበልጥ ሊያካፍላት፣ እምነቱን ሊተክልባት ወሰነ። «ይሄውልሽ ሃንዬ. . . ጉዳዮችኮ ቀላል ወይም ከባድ ስለሆኑ አይደለም የሚሳኩልን፣ ልናሳካቸው በቆራጥነት ስንወስንና ያላማቋረጥ ስንጥር ብቻ ነው የሚሳካልን፡፡» የግል እምነቱን አሰረፀባት፡፡
ምንም እንኳን ጋሻውንና ያልጨበጠችውን ዓለማቀፋዊ ዝናን፣ ተስፋ አድርጋ የቶማስን ንፁህ ወዳጅነት ብትረግጥም፣ መልሳ ልታገኘውና እስከ መጨረሻውም በፍቅሩ ውስጥ ልትሆን እንደምትችል አመነች፡፡ ልታደርገውም ወሰነች፡፡
ወዲያው በአይነ ህሊናዋ እንዲህ ይታያት ጀመር።
የበና ማኅበረሰብ ገላቸው በልብስ ተሸፍኖ። በምሽት፣ መስክ ላይ በሚያነዱት እሳት ዙሪያ ተሰባስበው፣ በርኮታቸው ላይ ቁጢጥ እንዳሉ፣ አረቄያቸውን እየተጎነጩ ሲጨዋወቱ . . .
ጨረቃ ፍልቅልቅ ብላ ቁልቁል ስታስተውላቸው...
እሷ እና ቶማስ ጎን ለጎን እንደተቀመጡ፣ እሳቱን እየሞቁ በሹክሹክታ ሲያወጉ. . .
የበናዋ ጉብል   ጠይሙ ፊቷን በፈገግታ አስጊጣ፣ በዘመናዊ የቆዳ ጃኬት የተሸፈኑ ውድር ሮኬቶችዋን በማስቀደም  ወደ ጋሻው
ስትርብ . . .
ጋሻውም በርኮታው ላይ ጉብ እንዳለ ፣በነበልባሉ ውስጥ አሻግሮ እየተመለከታት በነደደ ስሜት ሲጠብቃት. . .
ጨረቃም እየተቅለሰለች ደመናው እቅፍ ውስጥ ስትሸሸግ . . .

Saturday, 14 June 2014 12:20

የጸሐፍት ጥግ

ጭንቅላቴን ባዶ ለማድረግ መፃፍ አለብኝ፡፡ ያለዚያ አቅሌን እስታለሁ፡፡
ሎርድ ባይረን
በመፃፍ ካልተነፈስክ፣ በመፃፍ ካልጮህክ ወይም ካልዘመርክ አትፃፍ፡፡ ምክንያቱም ባህላችን ለፅሁፍ ቦታ የለውም፡፡  
አናይስ ኒን
ከሌላ ፀሃፊ ባለሁለት ቃላት ሃረግ ከምሰርቅ ሙሉ ባንክ ዘርፌ ብያዝ እመርጣለሁ፡፡
ጃክ ስሚዝ
ፅሁፍ ከዝምታ ጋር የሚደረግ ትግል ነው፡፡
ካርሎስ ፉንቴስ
ህትመት የሰውን አዕምሮ ለጨረታ ማውጣት ነው፡፡
ኤሚሊ ዲኪንሰን
የደራሲ ሁለቱ እጅግ ማራኪ ጥንካሬዎች፣ አዳዲስ ነገሮችን የተለመዱ ማድረግና የተለመዱትን አዲስ ማድረግ ናቸው፡፡
ሳሙኤል ጆንሰን
ለመፃፍ የተገደድክበትን ምክንያት እወቀው፡፡ ስሩን በልብህ ውስጥ ማሰራጨቱንም አረጋግጥ። መፃፍ ብትከለከል ብቸኛ አማራጭህ ሞት እንደሆነ ለራስህ ተናዘዝ፡፡
ሬይነር ማርያ
ጥሩ ልቦለድ የዋና ገፀ ባህሪውን እውነት ሲነግረን፣ ቀሽም ልቦለድ የደራሲውን እውነት ይነግረናል፡፡
ጂ.ኬ.ቼስቴርቶን
በአንድ ሰው አዕምሮ ውስጥ በሺዎች የሚቆጠሩ ሃሳቦች ይኖሩታል፡፡ ያ ሰው ብዕሩን አንስቶ እስኪፅፋቸው ድረስ ግን እኒያ ሃሳቦች መኖራቸውን አያውቅም፡፡
ዊሊያም ሜክፒስ ታክሬይ
በእያንዳንዱ ጭንቅላት ውስጥ ያለውን የትራፊክ መጨናነቅ የሚያስወግዱ መፃህፍት መፃፍ እፈልጋለሁ፡፡
ጆን አፕዳይክ
ሰዎች በደምስሮቼ ውስጥ ቀለም፣ በትየባ ማሽኔ ቁልፎች ላይም ደም ማግኘታቸው አይቀርም፡፡
ቴሪ ጉይሌሜትስ
መፃህፍቱ ራሳቸው እንዲወለዱ ፈለጉ እንጂ እኔ አልፈጠርኳቸውም፡፡ ወደ እኔ መጥተው “እንዲህና እንዲያ ሆነን ካልተፃፍን” ብለው ወትውተውኝ ነው፡፡
ሳሙኤል በትለር

ጀምስ ጆይስ (1882-1941)
ይሄ አየርላንዳዊ የሥነ-ፅሁፍ ሰው ከ20ኛው ክፍለ ዘመን እጅግ ዝነኛ ደራሲያን መካከል በግንባር ቀደምትነት ተጠቃሽ ነው፡፡ እ.ኤ.አ በ1907 ዓ.ም “Chamber Music” የተሰኘ 36 ግጥሞችን ያካተተ መድበል ያሳተመ ሲሆን ከ 8 ዓመት በኋላ የመጀመሪያ ረዥም ልብ-ወለዱን ለህትመት አበቃ - “Dubliners” በሚል ርዕስ።
ከሁለት ዓመት በኋላ ደግሞ እንደወረደ ስልት (stream of consciousness) የአተራረክ ዘይቤ በመጠቀም የፃፈውን “A portrait of the Artist as a young Man” የተሰኘ ልብ-ወለዱን አሳተመ፡፡ ጆይስ ከዚህ በመቀጠል ዓለም አቀፍ ዕውቅና ያስገኘለትን “Ulysses” ነው ለንባብ  ያበቃው፡፡ የመጨረሻ ሥራው “Finnegan’s wake” በስነ-ፅሁፉ ዓለም ቀዝቃዛ አቀባበል በማግኘቱ ጆይስን ክፉኛ አስከፋው፡፡ አብዛኛውን ህይወቱን በገንዘብ ችግር ያሳለፈው ይሄ ዝነኛ ደራሲ፣ እስከ ዕድሜው የመጨረሻ ዓመታት ገደማ ድረስ ከስራው ምንም ገቢ አላገኘም ነበር፡፡
የጄምስ ጆይስ የአፃፃፍ ልማድ ከብዙዎቹ ደራስያን የተለየ ነበር፡፡ በቀን ምን ያህል ቃላት ወይም ገፆች እፅፋለሁ የሚለው ጉዳይ እምብዛም አሳስቦት አያውቅም፡፡ አንዲት ዓረፍተ ነገር ብቻ በመፃፍ ቀኑን  ሊያሳልፍ ይችላል፡፡ አንድ ወዳጁ “ደህና ፃፍኩ የምትለው ምን ያህል ስትፅፍ ነው?” ሲል ላቀረበለት ጥያቄ “ሦስት አረፍተ ነገሮች” በማለት መልሷል፡፡


ቭላድሚር ናቦኮቭ (1899-1977)
ትውልደ ሩሲያ አሜሪካዊ ደራሲው ቭላድሚር ናቦኮቭ፤ በረዥም ልብ-ወለድ ፀሃፊነቱ ይበልጥ ቢታወቅም ገጣሚና ሃያሲም ጭምር ነው፡፡ በከፍተኛ ፈጠራ የተሞላው አፃፃፉ እንደ 20ኛው ክፍለ ዘመን ታላቅ የሥነ-ፅሁፍ ሰውነቱ ከፍተኛ ተወዳጅነትን አትርፎለታል፡፡ ናቦኮቭ እ.ኤ.አ በ1955 ለንባብ በበቃው “Lolita” የተሰኘ ረዥም ልብ-ወለዱ ይበልጥ የሚታወቅ ሲሆን Pale Fire እና Ada የተሰኙ ተወዳጅነትን ያተረፉ ረዥም ልብ-ወለዶችንም ፅፏል፡፡ ሌሎች አያሌ ልብወለዶችን በእንግሊዝኛና በሩስያኛም የፃፈ ሲሆን፤ በርካታ የኢ-ልብወለድ ሥራዎችም አሉት፡፡
ቭላድሚር ናቦኮቭ የፅሁፍ ስራውን የሚያከናውነው ቁጭ ብሎ ወይም እንደ አንዳንድ ፀሃፍት ተጋድሞ ሳይሆን ቆሞ ነው፡፡ ለመፃፊያነት የሚጠቀመውም የተለመደውን ወረቀት አይደለም። በኢንዴክስ ካርዶች ነው የሚፅፈው፡፡ ይሄ ደግሞ ለትዕይንቶች ቅደም ተከተል ሳይጨነቅ እንዲፅፍ ነፃነት ይሰጠዋል፡፡ በኋላ የካርዶቹን ቅደም ተከተል እንደፈለገ ሊያስተካክል ይችላል፡፡ ደራሲው Ada የተሰኘውን ረዥም ልብ-ወለዱን ሲፅፍ ከ2ሺ በላይ ካርዶችን ተጠቅሟል፡፡


ጆይስ ካሮል ኦትስ
እ.ኤ.አ በ1938 የተወለደችው አሜሪካዊቷ ደራሲ ኦትነስ፤ በተለያዩ ዘውጎች በመፃፍ ትታወቃለች፡፡ አጭር ልብ-ወለዶች፣ ግጥሞች፣ ተውኔቶች፣ የሰሉ ወጎችና ረዥም ልብወለዶችን ትፅፋለች፡፡ ሶስት ተከታታይ (trilogy) ረዥም ልብ ወለዶችን የፃፈች ሲሆን በ1967 A Garden of Delights፣ በ1968 Expensive People እና በ1969 Them በሚል ለንባብ በቅተዋል፡፡
ከእነዚህም ውስጥ የመጨረሻው (Them ማለት ነው) በ1970 ዓ.ም የናሽናል ቡክ አዋርድ ተሸላሚ ሆኖላታል፡፡ ኦትስ ሌሎች በርካታ ሽልማቶችንም አሸንፋለች፡፡
የፈጠራ ሥራዋን የምትሰራበት የተወሰነ መደበኛ ሰዓት ባይኖራትም፣ ጠዋት ከቁርስ በፊት መፃፍ እንደምትመርጥ ትናገራለች፡፡ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የመጀመሪያ፣ ሁለተኛና ሶስተኛ ድግሪዋን የሰራችው ኦትስ፤ የበዩኒቨርሲቲ ፈጠራ አፃፃፍ የምታስተምር ስትሆን ክፍል ከመግባቷ በፊት ለአንድ ሰዓት ወይም ለ45 ደቂቃ ትፅፋለች፡፡ ክፍል በሌላት ጊዜ ደግሞ ለሰዓታት ስትፅፍ ቆይታ ቁርሷን ከሰዓት በኋላ በ8 ወይም በ9 ሰዓት ትመገባለች፡፡

      የእስራኤል ፕሬዚዳንት፣ ጠ/ሚንስትር፣ የገንዘብ ሚ/ር እና የኢኮኖሚ ሚ/ር በዝርዝሩ ውስጥ ተካተዋል
ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ ታዋቂ ድምጻዊት ኢስተር ራዳ፣ ‘ዘ ጀሩሳሌም ፖስት’ ጋዜጣ የአመቱ የዓለማችን ተጽዕኖ ፈጣሪ አይሁዳውያን ብሎ ከመረጣቸው 50 ታዋቂ ግለሰቦች መካከል አንዷ ሆነች፡፡
በሶል፣ በአር ኤንድ ቢ እና በፋንክ ስልቶች የተቃኙና የኢትዮ-ጃዝ ቃና ያላቸው ሙዚቃዎችን የምትጫወተውና “የእስራኤል የሶል ሙዚቃ ንግስት” በመባል የምትጠራዋ ኢስተር ራዳ፣ በእስራኤል ብቻም ሳይሆን በመላ አለም በርካታ አድናቂዎችን ማፍራት የቻለች ድምጻዊት መሆኗን ‘ዘ ጀሩሳሌም ፖስት’ ባለፈው ሰኞ ይፋ ባደረገው መረጃ መስክሮላታል፡፡
ጋዜጣው ተስፋ ከሚጣልባቸውና ከፍተኛ ስኬት ካስመዘገቡ የዘመኑ ተጠቃሽ ቤተ እስራኤላውያን አርቲስቶች ተርታ ትሰለፋለች ያላት ይህቺ ድምጻዊት፣ በተለያዩ ጊዜያት በአውሮፓና በሰሜን አሜሪካ ስኬታማ የሙዚቃ ኮንሰርቶችን ማቅረቧንና፣ ኢትዮጵያዊ ቅኝት ያላቸውን ሙዚቃዎች እንደምትጫወትም ገልጧል፡፡
በሙዚቃው ዘርፍ ከፍተኛ ተወዳጅነትን ማፍራትና ለኤምቲቪ አውሮፓ የሙዚቃ ሽልማት እስከመታጨት የደረሰችው ኢስተር ራዳ፣ ‘ኪሮት’ እና ‘ስቲል ዎኪንግ’ን በመሳሰሉ ፊልሞች፣ ሙዚቃዊ ቲያትሮችና ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማዎች ላይ በተዋናይነት በመስራት ድንቅ የትወና ክህሎቷን አስመስክራለች፡፡
በተለያዩ የአለም ክፍሎች የሚኖሩ ፖለቲከኞች፣ ተመራማሪዎች፣ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች፣ ስራ ፈጣሪዎች፣ ቢሊየነሮች፣ አርቲስቶችና በሌሎች ሙያዎች ላይ ተሰማርተው ውጤታማ መሆን የቻሉ ግለሰቦችን በዘንድሮው የአመቱ 50 የአለማችን ተጽዕኖ ፈጣሪ አይሁዳውያን ዝርዝር ውስጥ ያካተተው ዘ ጀሩሳሌም ፖስት፤ ከእነዚህም ውስጥ ኢስተር ራዳን ጨምሮ 15 ያህሉ ሴቶች መሆናቸውን ይፋ አድርጓል፡፡
ካቻምና በእስራኤል ጠ/ሚንስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ፣ አምና ደግሞ በገንዘብ ሚንስትሩ የር ላፒድ ተይዞ የነበረውን የዚህ  ዝርዝር መሪነት፣ ዘንድሮ የአሜሪካ ትሬዠሪ ጸሃፊ የሆኑት ጃክ ሊው ተረክበውታል፡፡ በአገሪቱ ኢኮኖሚ ውስጥ ቁልፍ ሚናን በሚጫወተው በዚህ ዘርፍ ውስጥ ጉልህ ሚና እየተጫወቱ የሚገኙት እኒህ ሰው፣ በፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ አስተዳደር ውስጥ ተጽዕኖ መፍጠር የቻሉ ተሰሚ ሰው እንደሆኑ ጋዜጣው ዘግቧል፡፡
በተጽዕኖ ፈጣሪነት ሁለተኛውን ደረጃ የያዙት አሜሪካዊቷ ቤተ እስራኤላዊ ጃኔት የለን ሲሆኑ፣ የአሜሪካን ተቀማጭ ገንዘብ ተቋም እንዲመሩ በመመረጥ በአገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያዋ ሴት ናቸው፡፡ እሳቸውን ተከትለው በዝርዝሩ የተካተቱት፣ ቤኒያሚን ኔታኒያሁ (የእስራኤል ጠ/ሚንስትር) እና ሽሞን ፔሬዝ (የእስራኤል ፕሬዚዳንት) ናቸው፡፡
አቪግዶር ሊበርማን (የእስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር)፣ የር ላፒድ (የእስራኤል የገንዘብ ሚንስትር) እና ናፋታሊ ቤኔትም (የእስራኤል የኢኮኖሚ ሚንስትር)፣ በዘንድሮው ተጽዕኖ ፈጣሪ ቤተ እስራኤላውያን ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱ ታዋቂና በአለም አቀፍ ደረጃ ተጽዕኖ መፍጠር የቻሉ ግለሰቦች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡

ወላጆች ለልጆች እግር መበላሸት ተጠያቂ ናቸው ተባለ
         በቅርቡ የተካሄደ ጥናት፤ በዓለም ላይ 4ሚ. ያህል ህፃናት ልካቸው ያልሆነ በመጫማት እንደሚሰቃዩ ይጠቁማል፡፡ ለዚህ ደግሞ ተጠያቂዎቹ ወላጆች ናቸው ይላል፡፡
የልጆቻቸውን እግሮች ልካቸው ያልሆነ ጠባብ ጫማ ውስጥ እንዲሰቃዩ የሚፈቅዱ ወላጆች፤ ለልጆቻቸው የዘላለም ችግር እያስቀመጡላቸው እንደሆነ ማወቅ አለባቸው ብሏል ጥናቱ፡፡ ጠባሳ፣ እብጠት፣ የጣት ጥፍር ወደ ውስጥ ማደግ… የአጭር ጊዜ ችግሮች ሲሆኑ የረዥም ጊዜ ችግሮች ደግሞ የእግር መንጋደድ ለምሳሌ የጣት መቆልመም እንዲሁም የጉልበትና የቅርጽ መበላሸት እያለ ዝርዝሩ ይቀጥላል፡፡
ወላጆች ለልጆቻቸው ጥርስ ብዙ እንክብካቤ የሚያደርጉትን ያህል ለእግሮቻቸውም ሊያስቡላቸውና ሊጠነቀቁላቸው ይገባል ይላሉ፤ የእግር ጤናና እንክብካቤ ባለሙያዎች፡፡ ለመሆኑ 4ሚ. ህፃናት ለምንድነው ልካቸው ባልሆነ ጫማ የሚሰቃዩት? በቸልተኝነት? በገንዘብ እጥረት? በአመቺነትና ፋሽን በመሆኑ? ሁሉም ሰበብ ይሆናሉ ይላሉ ብለዋል በግላስጐው ካሌዶንያን ዩኒቨርሲቲ፣ በእግር ጤናና እንክብካቤ ዙሪያ ሌክቸር የሰጡት ዶ/ር ጐርዶን ዋት፡፡
የህፃናት እግሮች በዕድሜያቸው የመጀመያዎቹ አራት ዓመታት በፍጥነት የሚያድጉ ቢሆንም  የእግራቸው አጥንቶች፣ ጡንቻዎችና መገጣጠምያዎች እንደ አዋቂ እግር ለመጠንከር ግን እስከ 18 ዓመት ድረስ ሊወስድባቸው ይችላል የሚሉት ባለሙያዎቹ፤ የታዳጊዎችም ሆነ የህፃናት እግሮች በቂ ትኩረትና እንክብካቤ እንደሚሹ ያሳስባሉ፡፡  በጥናቱ እንደተጠቆመው፤ ከ10 ወላጆች አንዱ ልጆቹ ለእግራቸው የሚያንሳቸውን ጫማ አሁንም ድረስ እንደሚያደርጉ ሲናገር፣ ገሚሶቹ ወላጆች ደግሞ፤ ልጆቻቸው “ጫማው እግራችንን አሳመመን” ብለው እስኪጨቀጭቋቸው ድረስ አዲስ ጫማ እንደማይገዙላቸው ታውቋል፡፡
የእግር ህክምና ባለሙያዎች እንደሚሉት፤ ብዙ ሰዎች ለልጆቻቸው እግር ጥንቃቄ የማያደርጉት ጠባብ ጫማ መጫማት የሚያስከትለውን ችግር ስለማይረዱት ነው፡፡ ለዚህ ጥናት ቃለ መጠይቅ ከተደረገላቸው ወላጆች ውስጥ 40 በመቶ ብቻ ናቸው የልጆቻቸው ጫማ ልካቸው እንደሆነና ምቾት እንዳለው ለማረጋገጥ የሚተጉት ተብሏል፡፡
ልጆች ጫማ በተገዛላቸው ቁጥር እግራቸው መለካት እንዳለበት የሚያሳስቡት ባለሙያዎቹ፤ ወላጆች ጫማው ላይ የሰፈረውን ቁጥር ብቻ አይተው መግዛት እንደሌለባቸው ይመክራሉ፡፡

Saturday, 14 June 2014 12:06

የቸኮሌት ነገር!

የደም ግፊትን ይቀንሳል
በኮኮዋ ውስጥ የሚገኙት ፍላቫኖልስ የተባሉት ንጥረ ነገሮች የደም ግፊት የሚቀንሱ መድሃኒቶችን ሥራ እንደሚሰሩ ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡ ፍላቫኖልስ ሰውነታችን ናይትረስ ኦክሳይድ እንዲያመርት በማድረግ ለደም ስሮች መከፈት እገዛ ያደርጋሉ፡፡
የአውስትራሊያ ተመራማሪዎች፤ ኮኮዋ ዘወትር መጠቀም የሰዎችን የደም ግፊት ዝቅ እንደሚያደርግ በጥናታቸው ያረጋገጡ ሲሆን 1 በመቶ ያህሉ ግን ቸኮሌትን ከመጠን በላይ በመመገብ ለሆድ ህመም መጋለጣቸውን በጥናት ወረቀታቸው ላይ አስፍረዋል።
የጉበት ጉዳትን ይከላከላል
ቸኮሌት ለደም ግፊት ያለው ጠቀሜታ የሚመነጨው በውስጡ ካለው ከፍተኛ የፍላቫኖል ይዘት  ነው፡፡ በጉበት ቬይኖች ከፍተኛ የደም ግፊት መከሰት ከጉበት ጉዳት ወይም ሥር ከሰደደ የጉበት በሽታ ጋር እንደሚገናኝ ይታመናል፡፡ ቀደም ሲል የተደረገ ጥናት እንደሚጠቁመው፤ ጥቁር ቸኮሌት መብላት በጉበት ውስጥ ያለውን የደም ዝውውር ያሻሽለዋል፡፡ ይኼው የቸኮሌት ዓይነት የጉበት ጉዳትን መከላከል ይችል እንደሆነ ለማረጋገጥ በአሁኑ ወቅት ጥናቶች እየተካሄዱ እንደሆነ ታውቋል፡፡
ለልብ ጤንነት ይጠቅማል
የደም ግፊትን ዝቅ በማድረግ፣ የደም ስሮችን በመክፈትና፣ ብግነትን በመቀነስ ከፍተኛ ሚና የሚጫወተው ቸኮሌት፤ የልባችንን ጤንነት በመጠበቅ ረገድም ጉልህ አስተዋጽኦ ያበረክታል። የልብ በሽታንና ስትሮክንም ይከላከላል፡፡ ከ114ሺ በላይ በሆኑ ሰዎች ላይ በተካሄደው ጥናት፤ ብዙ ቸኮሌት የሚመገቡ ሰዎች እጅግ አነስተኛ ከሚመገቡት ይልቅ በልብ በሽታ የመያዝ ዕድላቸው 37 በመቶ፣ ለስትሮክ የመጋለጥ ዕድላቸው ደግሞ 29 በመቶ እንደቀነሰ ተረጋግጧል፡፡
ሸንቃጣ ያደርጋል
ከ1ሺ በሚበልጡ  ሰዎች ላይ በተደረገ ጥናት እንደተረጋገጠው፤ ቸኮሌት መብላት የሚያዘወትሩ ሰዎች ሸንቃጣ የመሆን ዕድላቸው ከፍተኛ ነው፡፡
ለጥናቱ የተመረጡት ሰዎች “በሳምንት ስንት ጊዜ ቸኮሌት ትመገባለህ/ትመገቢያለሽ?” የሚል ጥያቄ የቀረበላቸው ሲሆን የጥናት ውጤታቸውን በ “አርካይቭስ ኦፍ ኢንተርናል ሜዲሲን” ያሳተሙት ተመራማሪዎች፤ በሳምንት ውስጥ ደጋግመው ቸኮሌት የሚበሉ ሰዎች አልፎ አልፎ ከሚበሉት የበለጠ ሸንቃጣ እንደሆኑ አረጋግጠዋል ፡፡
ብልህና ብሩህ ያደርጋል
በ”ኒው ኢንግላንድ ጆርናል ኦፍ ሜዲሲን” የወጣ አንድ ጥናት፤ ቸኮሌት በብዛት የሚጠቀሙ ህዝቦች ያላት አገር፣ ከሌሎች የበለጠ የኖቤል ሽልማት አሸናፊዎች እንደሚኖራት አመልክቷል፡፡ ቸኮሌት አዘውትሮ መብላት ብልህና ብሩህ ያደርጋል ማለት ነው፡፡ ለዚህም በምሳሌነት የተጠቀሰችው ስዊዘርላንድ ናት፡፡
ስዊዘርላንዶች ቸኮሌት በብዛት በመመገብ የሚታወቁ ሲሆን ብዙ የኖቤል ተሸላሚዎች እንዳሏቸውም ተገልጿል፡፡ የእንግሊዝ ተመራማሪዎች እንደሚሉት፤ በእንግሊዝ የኖቤል ተሸላሚዎችን ለማብዛት እያንዳንዱ ሰው በዓመት 2 ኪ.ግ ቸኮሌት መብላት ይኖርበታል፡፡

ጤናንና ህይወትን ለመታደግ ነው ተብሏል
ሲጋራ ማጨስ ለከፍተኛ የጤና አደጋ፣ ባስ ሲልም ለህልፈት እንደሚዳርግ ማንም ሊክድ አይችልም። እንዲያም ሆኖ ከወደ አየርላንድ የተሰማው አዲስ እገዳ ክፉኛ ያስደነገጠው ከአጫሾች ይልቅ የትምባሆ ኩባንያዎችን ነው። ሰሞኑን አየርላንድ ማንኛውም ሲጋራ ስያሜ፣ የንግድ ምልክትና አርማ እንዳይኖረው የሚያግድ ህግ  አውጥታለች፡፡ እገዳው ሲጋራዎች ላይ ብቻ ግን አይደለም፤ የሲጋራ ፓኮዎችም ያለምንም ፅሁፍና ምልክት ለገበያ እንዲቀርቡ ህጉ ያስገድዳል። አዲሱ ህግ የትምባሆ ኩባንያዎችን ቢያስከፋም የአየርላንድ የጤና ሚኒስትር ጄምስ ሬይሊ፤ እገዳው የብዙዎችን ህይወት ለመታደግ ያግዛል ብለዋል፡፡
የምርት ስያሜ፣ የንግድ ምልክትና አርማ ያለው ሲጋራ ለሸማቶች እንዳይቀርብ የሚያግድ ህግ በማጽደቅ አየርላንድ በአውሮፓ የመጀመሪያዋ አገር ናት ተብሏል፡፡
አውስትራሊያ ተመሳሳይ እገዳ በሲጋራ ላይ በመጣል ከዓለም የመጀመሪያዋ አገር ስትሆን ኒውዚላንዶች ደግሞ በረቂቅ ህጉ ላይ እየተከራከሩ እንደሆነ ታውቋል፡፡ እንግሊዝን ጨምሮ ሌሎች የአውሮፓ አገራት እገዳው በህግ የመውጣቱን አስፈላጊነት ገና እያጤኑት ነው ተብሏል፡፡
የአየርላንድ ጤና ሚኒስትር በሰጡት መግለጫ፤ “የህጉ ዓላማ የሲጋራ ፓኮዎች ለሸማቾች ያላቸውን ማራኪነት በመቀነስ፣ በጤና ላይ የሚያደርሱትን አደጋ ማጉላት ነው፡፡ ፓኬቶች ሰዎችን በተለይ ህፃናትን የማሳሳት አቅማቸውን በመቀነስ የማጨስ ጐጂነትን እንዲገነዘቡ እናደርጋለን” ብለዋል፡፡
የትምባሆ ኩባንያዎች ግን እገዳውን አጥብቀው ተቃውመዋል፡፡ የትምባሆ ምርቶችን ስያሜና አርማ አልባ አድርጐ ማቅረብ፣ ሃሰተኛ የሲጃራ ምርቶችን የሚያመርቱ ወንጀለኞችን የሚያግዝና የሚያበረታታ ነው ብለዋል - ኩባንያዎቹ፡፡
ቤንሰን ኤንድ ሄጅስ እና ደንሂል በሚሉ ስያሜዎች የሚታወቁት ሲጋራዎች ባለቤት የሆነው የብሪቲሽ አሜሪካን ቶባኮ (BAT) ቃል አቀባይ እንደተናገሩት፤ የአየርላንድ ካቢኔ ረቂቅ ህጉን ማጽደቁ አሳዝኗቸዋል።
“ምንም ፅሁፍ ያልሰፈረበት ሌጣ ፓኬት፣ ታዳጊዎች ሲጋራ እንዳይጀምሩ ወይም አጫሾች ማጨስ እንዲያቆሙ ስለማድረጉ ተዓማኒ ማስረጃ የለም” ሲል ተሟግቷል  ተቋሙ፡፡
በቅርብ ዓመታት ሲጋራ ማጨስ በህብረተሰቡ ላይ የጋረጠውን አደጋ ለመቅረፍ የሚያስችል ውይይት ያደረገችው አየርላንድ፤ እ.ኤ.አ በ2004 ዓ.ም በስራ አካባቢ ሲጋራ ማጨስን ሙሉ በሙሉ የሚያግድ ህግ በማውጣት በዓለም የመጀመርያው አገር ሆናለች፡፡ በሥራ አካባቢ ሲጋራ ማጨስ የሚከለክለው ህግ መሸታ ቤቶችንና ክለቦችንም እንዳካተተ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ እንዲያም ሆኖ ታዲያ የህጉ ተፈፃሚነት 97 በመቶ እንደተሳካ ተገልጿል፡፡

Saturday, 14 June 2014 12:04

የኢትዮጵያ ታሪክ

...በዚያም ወራት ደጃች ብሩ፤ ጭልጋ አርባ አምባ ታስሮ ሳለ፣ ሚሽቱ ወይዘሮ የውብዳር ከእልፍኝ አሽከሮቿ አንዱን መልምላ ውሽማ አበጅታ ነበረ፡፡ ይህን ነገር ደጃች ብሩ በሰማ ጊዜ አዘነ፡፡ በበገና እንዲህ ብሎ አለቀሰ፡፡ ...
“መከራን በሰው ላይ እንዲያ ሳቀለው፣
ምንኛ ከባድ ነው እኔ ብይዘው፡፡
መከራ ሲመጣ አይነግርም አዋጅ፣
ሲገሠግሥ አድሮ ቀን ይጥላል እንጅ፡፡
ዘሃው ሰለሰለ ሸማኔው ተቆጣ፣
እስተወዲያው ድረስ መጠቅለያ ታጣ፡፡
የኔታም አይመጡ እኔም አልመለስ፣
ዋ ቢቸና ቀረ እስተወዲያው ድረስ፡፡
ከእልፍኝ ሰው አይግባ ሚሽቴን ሰው አይያት አይሉም አይሉም፣
ፈረሱን ሰው አይጫነው፣ በቅዬን ሰው አይጫነው አይሉም አይሉም፣
ጠጁ ቀጠነብኝ፣ ሥጋው ጎፈየብኝ አይሉም አይሉም፣
ቀን የጣለ ለታ፣ የጨነቀ ለታ፣ ይደረጋል ሁሉም። አለ፡፡
የደጃች ብሩ ግጥም ብዙ ነው፡፡ በሰራው ክፋት ብድሩን ከፈለ፡፡ በዘመኑ ጎጃምን ሲገዛ ያደረገው ክፋት ተጽፎ አያልቅም፡፡ ሚሽቱ ወይዘሮ የውብዳር ቤተክርስቲያን ልትሳለም በምትወጣበት ቀን አስቀድሞ ሰው የገባ እንደሆነ የዱላ በረዶ ይወርድበት ነበር፡፡ በደረቤ በየወረዳው ፲ ፲ (አሥር አሥር) እንስራ ጉንዳን ለምስጥ ማጥፊያ ብሎ ደሃውን አስጨንቆት ነበረ፡፡ ያንን ጊዜ ባላገር ጉንዳን በሣምባ ሥጋ እየተሰለበ በእንስራ ውስጥ እየከተተ ወደ ሶማ አምባ ሲወስድ ጆሮውንና ትክሻውን እየነከሰ አስቸገረው፡፡ የዚህ ጊዜ በለቅሶ ሲአንጎራጉር እንዲህ አለ፡፡
ከመከራው ሁሉ የጉንዳኑ ባሰ፣
የተሸካሚውን ጆሮና ትክሻ እየተናከሰ፡፡ አለ፡፡
ደግሞ የሴት ብልት ጠጉር የበቅሎ ቁርበት ይበጃል ብሎ ፭፻ ጉንዲ ጠጉር በሚዛን አምጡ ብሎ በየወረዳው ጥሎ ደኃውን አስለቀሰው፡፡ በሚዛን ሳይሞላለት ጊዜ የራሱን ጠጉር እየጨመረ ቢሰጥ እምቢ እያለ ወርቅ ተገላገለው፡፡
ያን ጊዜ የሴት ዘመድ የሌለው ተቸግሮ ነበረ፡፡ ደግሞ አፄ ቴዎድሮስ እንዳይሰብረው ብሎ ሶማን ሊያሰራ ፴ ጎበዝ ግንድ ተሸክሞ ሲወጣ፣ ከጠባብ ቦታ ላይ ተጨናንቆ ግንዱ ወንጥሎት ገደል ይዞት ገባና አለቀ፡፡ ይኸን ደጃች ብሩ በሰማ ጊዜ ገበሬ ምንኛ ተዋዳጅ ነው፡፡ አንድነት ወርዶ አለቀ ወይ ብሎ ቀለደ፡፡ አለሚገባ እጁን  እግሩን የቆረጠው ሰውም ብዙ ነው፡፡
ይህን ሁሉ ክፋት ክርስቶስ መዝኖ ጊዜው ሲደርስ፣ በአጼ ቴዎድሮስ እጅ አግብቶ ሚሽቱን ለጠብደል ማላገጫ አድርጎ ሲአስለቅሰው ኖረ። የደጃች ብሩን ልቅሶ አጼ ቴዎድሮስ በሰማ ጊዜ ሎሌዎች በድለዋል አሉና ልቅጣዎ ብሎ ላከበት። ደጃች ብሩም ለጊዜው ኀዘን አብርትቶ ነበረና መንግሥትዎን ያሰንብትልኝ፡፡ ቃሉ ደረሰኝ፡፡ ግን የጮሁለት ሰው አለና የዚያን ቁርጥ ሳውቅ ይሁን አለ፡፡
መልክተኛው ከመድረሱ ውሽማዋን መብረቅ ገደለው፡፡ ደጃች ብሩም ክርስቶስ ሰማኝ፡፡ ፍርዱን ፈረደ፡፡ ባላጋራየ ሞተ ብሎ ላከ፡፡ አጼ ቴዎድሮስም ሰምቶ ተደነቀ፡፡ ለካስ ደጃች ብሩ አጥብቀው አዝነዋል፡፡ ክርስቶስም ሰማቸው፤ በኔም ቢአዝኑ ያደርሱብኛል ብሎ ፈተህ አምጣልኝ አለ፡፡
ከታሰረበት ፈትቶ ወደ አጼ ቴዎድሮስ እጅ ሊነሣ ሲኸድ፣ ያው ጋኔኑ ጥንተ ትቢቱ አልለቀው ብሎ ተከናንቦ ሎሚ ታህል ደንግያ በትከሻው ይዞ ሊታረቅ መጣ፡፡ አጼ ቴዎድሮስም ክንንቡንና የድንጋይቱን ማነስ አይቶ ተበሳጭቶ፣ ትቢትዎ አለቀቀዎምሳ ቢለው፣ ክንብንቤን እንደሆነ የጭልጋ በረሃ  ጠጉሬን ጨርሶት ባፍር ነው አለ፡፡ አጼ ቴዎድሮስም ከአብራጃው አገር መቅደላ ይቆዩ፡፡ እኔ ልፈታዎ ነበረ፡፡ ነገረ ክርስቶስ ማቆያ በትቢት ምክንያት አመጣብዎ፡፡ ፈቃዱ ሲሆን ይፈታሉ አለው፡፡  
ምንጭ - (አለቃ ተክለኢየሱስ፣ የኢትዮጵያ ታሪክ፤ ሐተታ (በሥርግው ገላው (ዶ/ር))