Administrator

Administrator

 ባለፉት 6 ወራት ሀብታቸውን ካስመዘገቡ 41 ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች ውስጥ ትክክለኛ ሆኖ የተገኘው አንዱ ብቻ ነው
መታሰቢያ ካሣዬ
ባለፈው  የፈረንጆች 2023  በኢትዮጵያ የሙስና ወንጀሎች በእጅጉ  መጨመራቸውንና   የመንግሥት ስልጣንን ያለከልካይ ለግል ጥቅም ማዋል መባባሱን  ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል አስታወቀ።  አገሪቱ በ2023 በሙስና ነክ ወንጀሎች መንሰራፋት ልኬት 37  ነጥብ ከ100 ተሰጥቷት ከዓለም በ98ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ተቋሙ  ይፋ አድርጓል።
የ180 የዓለም አገራትን  የሙስና ነክ ወንጀሎች  በየዓመቱ  እየመዘነ ደረጃ የሚያወጣው ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል  ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው የ2023 ሙሉ ዓመት ሪፖርት፣ ኢትዮጵያ በመመዘኛዎቹ 37 ከ100 ነጥብ በማግኘት 98ኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን አስታውቋል፡፡ አገሪቱ በፈረንጆቹ  2022 ዓ.ም በሙስና ነክ ወንጀሎች መንሰራፋት ልኬት 38 ነጥብ ከ100 ተሰጥቷት ከዓለም 94ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣ እንደነበር ተቋሙ አስታውሷል።
በተቋሙ መለኪያ  ዓለም አቀፍ አማካይ የሙስና ውጤት 43 ነጥብ ሲሆን፤ ኢትዮጵያ ያገኘችው 37 ነጥብ  ከአማካይ በታች በስድስት ነጥብ ዝቅ ያለ መሆኑንም ተቋሙ በሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡ በትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል ነጥብ አሰጣጥ መሰረት፤ 100 ማለት ከሙስና ነጻ ማለት ሲሆን ወደ ዜሮ እየቀነሰ ሲሄድ የሙስና ወንጀሎች መጨመራቸውን አመላካች ነው።
ተቋሙ የሚፈትሻቸው የሙስና ዓይነቶች ጉቦ ፣ የመንግሥት ስልጣንን ያለከልካይ ለግል ጥቅም ማዋል፣ የመንግስት አካላት በመንግስት ዘርፍ ሙስናን የመቆጣጠር ችሎታ፣ በመንግስት ተቋማት ለሙስና አጋላጭ የሆኑ አሰራሮችን መተግበር፣ በጀትን ማዞር ፣ የመንግስት ባለስልጣናት ሃብታቸውንና ሊፈጠሩ የሚችሉ የጥቅም ግጭቶችን ከማሳወቅ አንጻር፣ የሙስና ጉዳዮችን ለሚያጋልጡ አካላት የህግ ከለላ መኖር እንዲሁም በሕዝባዊና መንግስታዊ ጉዳዮች ላይ የመረጃ ማግኘት መብትን ያካትታሉ።
የኢትዮጵያ ፌደራል ሥነ ምግባር እና ጸረ ሙስና ኮሚሽን  ሰሞኑን ይፋ ባደረገው መረጃ መሰረት፤ ባለፉት ስድስት ወራት  ሀብታቸውን ለኮሚሽኑ ካስመዘገቡ 41 ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናትና  አመራሮች መካከል ትክክለኛ ሆኖ የተገኘው አንዱ ብቻ መሆኑን ማስታወቁ ይታወሳል፡፡

-ድምጻዊ ዳዊት ጽጌ-
በአንጋፋዎቹ የአገራችን ድምፃውያን አሰፋ አባተ፣ ጥላሁን ገሰሰ እና እሳቱ ተሰማ ከዘመናት በፊት የተቀነቀኑና ከአድማጭ ጆሮ እርቀው የኖሩ ሦስት ተወዳጅ ሙዚቃዎች በወጣቱ ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ ዳግም ተቀንቅነው፣ “የዘመን ቃናዎች ፩” በሚል ስያሜ የሙዚቃ ቪዲዮዎች እንደተሰራላቸው የተገለጸ ሲሆን፤ ትላንትና አርብ ጥር 24 ቀን 2016 ዓ.ም ሥራዎቹ በራሱ ዳዊት ፅጌ ዩቲዩብ እንደሚለቀቁ ተነግሯል፡፡
“የዘመን ቃናዎች ፩” የሙዚቃ ቪዲዮዎችን አስመልክቶ ከትናንት በስቲያ ሐሙስ  ረፋዱ ላይ ድምፃዊ ዳዊት ፅጌና አንጋፋው የሙዚቃ አቀናባሪ አበጋዙ ክብረወርቅ ሺዎታን ጨምሮ ሌሎች በሙዚቃ ሥራዎቹ የተሳተፉ ባለሙያዎችና የቀድሞ አርቲስቶች ቤተሰቦች  በተገኙበት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ራስ መኮንን አዳራሽ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል፡፡
ጋዜጣዊ መግለጫው በጥያቄና መልስ፤ በማብራሪያና አስተያየት የታጀበና ከወትሮው በተለየ መልኩ ቁምነገር የሚያስጨብጥና ጥበብ ጥበብ የሚሸት እንደነበር ታዳሚዎች ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ መድረኩን በጥበብና በዕውቀት የመራው የመድረኩ ሞገስ  ተዋናይ ግሩም ዘነበ የአንበሳውን ድርሻ እንደሚወስድ ብዙዎች መሥክረዋል፡፡
 


ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ የራሱን ዘፈኖችና አልበም ከመሥራት ይልቅ ለምን የነባር አርቲስቶችን ሙዚቃዎች በድጋሚ ለማቀንቀን እንደመረጠና ዓላማውንም ሲያስረዳ፤ “ትውልድ የራሱን ቀለም አስቀምጦ ማለፍ አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ሌላውም እንዲሁ እንዲያደርግ እመክራለሁ፡፡ የዘመን ቃናዎች ቀደምት አርቲስቶችን የማክበር መንገድ--- መድረክ  መፍጠር ነው ዓላማው፡፡” ብሏል፡፡
የራሱንም ሙሉ አልበም ሰርቶ በማጠናቀቅ ላይ እንደሆነ የጠቆመው ድምጻዊው፤ በቅርቡ ለአድማጭ ጆሮ እንደሚደርስም በይፋ ቃል ገብቷል፡፡
አንጋፋው የሙዚቃ ሰው አበጋዝ ክብረወርቅ ሺዎታ የሙዚቃዎቹን ዳግም ማቀናበር አስመልክቶ ሲናገር፤ “እነዚህን ሥራዎች የተቀበልኩበት ምክንያት ከዚህ ቀደም የአስቴር አወቀንና የጥላሁን ገሰሰን ሥራዎች ተቀብዬ በድጋሚ ስለሰራሁ ነው፡፡ ሦስቱም ዳዊት ፅጌ የተጫወታቸው ሙዚቃዎች መሰረታዊው ጉዳይ ሳይነካ ወይም ሳይለወጥ ነው በድጋሚ የተቀናበረው፤ እኔ ብዙ የጨመርኩት ነገር የለም” ብሏል - ትህትና በተጫነው ድምፀት፡፡
በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ከታደሙት ብዙዎቹ ግን በዚህ ትህትና በእጅጉ በተጫነው አስተያየቱ ጨርሶ አይስማሙም፡፡ ለዚህ ደግሞ በመግለጫው መጨረሻ ላይ ታዳሚው የተጋበዘውን ዳግም የተቀነቀነና የተቀናበረ ሥራ ይጠቅሳሉ፡፡ ልዩነቱ በግልጽ የሚታይ ነው ይላሉ - አስተያየት ሰጪዎች፡፡
የሙዚቃ ቪዲዮዎቹ የተቀረፁት ከትላንት በስቲያ ጋዜጣዊ መግለጫው በተሰጠበት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ራስ መኮንን አዳራሽ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡ ይሄ ደግሞ ግጥምጥሞሽ ሳይሆን በዕቅድ ታስቦበትና ታልሞበት የተከወነ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ከሰሩ አይቀር እንዲህ ነው - ጥንቅቅ አድርጎ፡፡
የመድረኩ አጋፋሪ አርቲስት ግሩም ዘነበ በበኩሉ፤ የዘመን ቃናዎች ፩ የተሰራበትን ምክንያት  ሲያብራራ፤ ከዚህ ቀደም የነበሩ አርቲስቶች ለኢትዮጵያ ሙዚቃ ለከፈሉት መስዋዕትነት ዋጋ ለመስጠትና ለማክበር የተሰራ የሙዚቃ ስብስብ መሆኑን በአፅንኦት የገለፀ ሲሆን፤ ሌላው ምክንያት ደግሞ እነዚህን ሙዚቃዎች ሌላ ከፍታ በመጨመር አቀናብሮ ለዘመኑ  ጆሮ በሚጣጣም መልኩ ለአድማጭ ለማቅረብ ነውም ብሏል፡፡
የዘመን ቃናዎች ቀጣይ ክፍሎች ወደፊትም እንደሚወጡ በመግለጫው ላይ የተጠቆመ ሲሆን፤ ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ በዚህ ጉዳይ ላይ በሰነዘረው አስተያየት፤ “ቀጣዮቹን ክፍሎች እኔም ላልጫወታቸው እችላለሁ፤ ግን ብዙ ሥራዎች አሉ፤ በቀጣይ  የሚወጡ፡፡” ሲል ጠቁሟል፡፡
“የዘመን ቃናዎች ፩” የሙዚቃ ቪዲዮዎች የህግና የሞራል ግዴታዎችን በአግባቡ ተወጥተው መሰራታቸውም በመግለጫው ላይ ተደጋግሞ ተጠቅሷል፡፡ ተወዳጁ ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ በጋዜጣዊ መግለጫው መደምደሚያ ላይ ለአርቲስቶቹ ቤተሰቦች በሙሉ ምስጋናውን አቅርቧል፡፡ “የእናንተ ፈቃድ ባይኖር ኖሮ ሙዚቃዎቹን መሥራት አንችልም ነበር” ብሏል - ዳዊት ፅጌ፡፡


ድምፃዊው በሙዚቃ ስራዎቹ ላይ ለተሳተፉት ባለሙያዎችም ምስጋናውን ከመድረክ አቅርቧል - በይፋ፡


የጋዜጣዊ መግለጫውን ኹነት ያዘጋጀው የተለያዩ ኤቨንቶችን በማዘጋጀትና በመምራት የሚታወቀው አንጋፋው የህትመትና ማስታወቂያ ድርጅት ኢምር አድቨርታይዚንግ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Sunday, 04 February 2024 00:00

ሦስት መዓዘን

ምዕራፍ 1
-ኪሩቤል ሳሙኤል -
የሚተነፍሰው ትንፋሽ ከዛፎቹ ቅጠሎች ጋር እየተጋጨ ደግሞ ደጋግሞ ይሰማዋል፡፡ ትንፋሹ ከአፍንጫው ሲወጣ ጥሎት ላይመለስ እየኮበለለ ነው የሚመስለው፡፡ በጣም ደክሞታል፡፡ ወደ የት እየሄደ እንደሆነ የሚያውቀው ታሪክ የለም፡፡ በዚህ ጥቅጥቅ ያለ ጫካ ውስጥ የሚተነፍስና የሰው ፍጥረት የሆነው እሱ ብቻ ነው፡፡ እህል ባልጎበኘው ሆዱ ለግማሽ ቀን ያህል ነው በነዚህ ዛፎች መካከል መልስ ፍለጋ ሲኳትን የከረመው፡፡ ሆኖም ሁሉም ነገሮች ምንምን ብቻ ነው እያስረዱት ያሉት፡፡
ድንገት…
ካለበት አካባቢ በቅርብ ርቀት ድንገት አንድ ድምፅ ሰማ፡፡ የተቻለው ድረስ ድምፁን ወደ ሰማበት ቦታ በሀይል እየተራመደ ተመለከተ፤ ምንም ነገር የለም፡፡ አሁንም ሳያቋርጥ መራመዱን ቀጠለበት፡፡
በመንገዱም ላይ እያለ ያለምንም ተስፋ የፈጠረውን ፈጣሪውን በህሊናው ውስጥ ቅርፅ አበጅቶለት፣ ሊፀልይለትና አንዳች ተዓምር እንዲሰራለት ሊለምነው ተመኘ፤ ሆኖም ምኞቱ ሙሉ አልነበረም፡፡ ምኞቱ ውስጥ እውቀት የለበትም፣ ሀሳብ የለበትም፤ ስሜት የለበትም፡፡ ድካምን ለመካድ ከሚደረግ የአዕምሮ ውስጥ ጨዋታ ውጭ ይህ ሰው አላማ ብሎ ሊያስቀምጠው የሚችለው የህይወት ስርዓት አብሮት የለም፡፡ ብቻውን ነው፡፡
ሆኖም ይህ የተዘበራረቀ ስሜት ብዙም ሳይቆይ ሰብሳቢ የህይወት ገጠመኝ ይዞለት መጣ፡፡ ከርቀት አንዲት ደሳሳ ቤት ከወደ ፊቷ አጎንብሳ በዛፎች መካከል ተሰፍታ ተመለከተ፡፡ ማመን አቃተው፡፡ እንደምንም እየተንደረደረ ሄዶ የቤቱ በር ጋር ቆመ፡፡ ምን ማድረግ እንዳለበት ግራ ገባው፡፡ ዝም ብሎ እንዳይገባ እሱ ራሱ ያልተረዳው ህግ መጥቶ ድፍረቱ ላይ ተከመረበት፡፡ እዛው በሩ ላይ ተገትሮ አንድ እሱን የመሰለ ፍጥረት ከቤቱ ውስጥ እስኪወጣ ድረስ ቆሞ እንዳይጠብቅ፣ በምንም አይነት ታሪክ ትዕግስት መስጠት የማይችለው ረሀብ በሆዱ ውስጥ የአመፃ ድምፁን እያስተጋባበት ነበር፡፡ ህይወት በሁለት የተስፋ ገመዶች ተወጥራ ይህን ሰው የተምታታ ምስሎችን ብቻ በጭንቅላቱ እንዲፈለፍል እያስገደዱት ነው፡፡
አልቻለም፡፡ ረሀቡን አልቻለውም፡፡ ወደቤቱ ተጠግቶ የጨለማ ጥቀርሻ የተቀባውን የቆርቆሮ በር ዘመም አድርጎ ከፈተው፡፡ ቅጥሩ የተጣሰበት ይመስል በቤቱ ውስጥ ተደብቆ ተቀምጦ የነበረው የጨለማ ፀዳል ሲረበሽ ታወቀው፡፡ ካጠገቡ የመብራት ማብሪያና ማጥፊያ አግኝቶ መብራቱን ተጫነው፡፡ ክፍሉ ላይ ብርሀን ሰለጠነበት፡፡ የብርሀኑ ሰበብ የሆነው አምፖል ግን የት ጋ እንዳለ ለማየት አልቻለም፡፡
ክፍሉ ባዶ አይደለም፡፡ በውስጡ አንድ በላዩ ላይ በሸረሪት ድር ተጀቡኖ የመጻሕፍት ክምር ያለበት ጠረጴዛ፣  የእንጨት ወንበር፣ በግድግዳው ላይ የተለያዩ የተለጣጠፉ ፎቶዎች፣ በፎቶዎቹ ላይ የአቧራ ቂጣ ተለጥፎባቸው፣ ከቤቱ ሰጎጥ ስር ደግሞ አንድ ተለቅ ያለ በእንጨት የተበጀ ሳጥን ይዟል፡፡
ይህ ሰው በቅድሚያ ትኩረቱን የት ላይ ማድረግ እንዳለበት በቆመበት ትንሽ ካሰላሰለ በኋላ በቅድሚያ በግድግዳው ላይ ወዳለው የፎቶግራፎች ሰልፍ ጋር ሄዶ ቆመ፡፡ በላያቸው ላይ ያለውን ቆሻሻ በእጁ ካፀዳ በኋላ በተቻለው ጥረት አጥርቶ ለመመልከት ቀረብ ብሎ መመልከት ጀመረ፡፡ በመጀመሪያ የተገናኘው ከራሱ ፎቶ ጋር ነው፡፡ ግራ ገባው፡፡ እንዴት ሆኖ የእሱ ፎቶ እዚህ ለምድር የተሰወረ ደሳሳ ጎጆ ውስጥ ሊገኝ እንደቻለ ማመን አቃተው፡፡ በፍጥነት ሌሎች ፎቶዎችን እያፀዳ መመልከት ውስጥ ገባ…የራሱ ብዙ ፎቶዎች፣ ከአንዲት ሴት ጋርና አብሯቸው ደግሞ አንድ ወንድ ህፃን ልጅ ይዘው፣ በሌላ ቦታም የራሱ ፎቶ የወታደር ልብስ ለብሶ ከሌላ ሴት ጋር የተነሳው፣ በሌላ ቦታ መጀመሪያ ያየው ህፃን ልጅ አደግ ብሎ ብቻቸውን የተነሱት ፎቶና በከፊልም ቢሆን ከዚህ ቀደም ያለው ህይወቱን የሚናገርበት የፎቶ ክምር ተመልክቶ ነፍሱ ደርቃ ቀረች፡፡
ብዙ ነገር ተረጋግቶ ማሰብ ይችል ነበር፡፡ ሆኖም አሁንም ሊመለከታቸው የሚገቡ የቤት እቃዎች ባሉበት ሆነው እየጠበቁት እንደሆነ ሲረዳ፣ፊቱን አዙሮ መጻሕፍቶቹ ላይ ትኩረቱን አደረገ፡፡ በመጻሕፍቱ ላይ ያለውን የሸሪት ድር አንስቶ መመልከት ውስጥ ገባ፡፡ አብዛኞቹ በእጅ ፅሁፍ የተፃፉ ድርሳናት ይታያሉ፡፡ ከዛም ባለፈ የብራና ጥቅሎችም አልፎ አልፎ ይታያሉ፡፡
ድርሳናቱንና ጥቅሎቹን ለማንበብ ጊዜ አልሰጠም፡፡ ዞሮ ወደ እንጨት ሳጥኑ ቀርቦ ለመክፈት ሙከራ አደረገ፡፡ ሳጥኑ ተለቅ ባለ ቁልፍ የተከረቸመ ነው፡፡ አሁኑኑ ሳጥኑን ከፍቶ ማየት እንዳለበት ተገነዘበ፡፡ ጎጆውን ለቆ ወጥቶ ጋኑን የሚሰብርበትን ድንጋይ ማፈላለግ ጀመረ፡፡ ፍለጋ ላይም እያለ ጥቃቅን በትውስታ ውስጥ የሚንፀባረቁ ምስሎች ያለ እሱ ፈቃድ ድንገት እየመጡ ብልጭ ድርግም ይሉበታል፡፡
ከግድግዳው ላይ ተለጥፎ ያየው ህፃን ልጅ መልክ ድንገት ብልጭ ብሎ ይታየዋል…አብሮት ሲስቅ…አብሮት ሲሮጥ…አብሮት ከሶፋ ላይ ተጋድመው መፅሐፍ ሲያነብለት….እነዚህ ሶስት ምስሎች ልክ እንደ ልብስ መስፊያ የሲንጀር ባህሪይ እየተመላለሱ ጭንቅላቱን ይተከትኩት ጀመር፡፡ ሆኖም ምንም ሊያደርገው የሚችለው ትዝታ አይደለም፡፡ የራሱ ልጅ ይሁን የሌላ የሚያውቀው እውቀት ባዶ ነው፡፡ ሆኖም ከጭንቅላቱ ስውር ስፍራ ውስጥ አስቀምጦት እንደነበር ግን መጠርጠር ውስጥ ገብቷል፡፡
ተለቅ ያለ ድንጋይ አጋጠመው፡፡
በፍጥነት ወደ ሳጥኑ ጎጆው አመራ፡፡ በጎጆው ውስጥ ሰርጎ በጋኑ ላይ ድንጋዩን ያመላልስበት ጀመር፡፡ በሳጥኑ ውስጥ ምግብ ቢያገኝ በወደደ ነበር፡፡ የራበው ሰው የሚያደምጠው በጆሮው ነው እንዲል ካልሂል ጅብራን፣ ይህም ሰው ቀስ እያለ እያጨለመው ያለውን ድካሙን የሚያሸንፍበትን መሳሪያ ብቻ ነው የሚፈልገው፡፡ ምግብ፡፡
ከብዙ ድብደባ በኋላ ጋኑ እጅ ሰጥቶ ተከፈተ፡፡ ቀስ ብሎ ከፈተው፡፡ ባየው ነገር በጣም ደንግጦ በፍጥነት ወደ ኋላው አፈገፈገ፡፡ ክፍሉ እጅግ ነፍስን በሚያጎመዝዝ ሽታ ታወደ፡፡ ደንግጦ ለጥቂት ደቂቃዎች ከወደቀበት ሆኖ በሳጥኑ ላይ ሲያፈጥበት ከቆየ በኋላ፣ያየው ነገር እውነት መሆኑን ለማረጋገጥ በቀስታ መልሶ ተጠጋው፡፡ ደግሞም ሲመለከተው ነገርየው ራሱ ነው፡፡
ነገርየው… በሳጥኑ ውስጥ እየተመለከተው ያለው  ራሱን ነው፤ ራቁቱን እጥፍጥፍ ብሎ ተኝቶ በመበስበስ ላይ ያለውን የራሱን አስክሬን ነው ያየው….
      

"ኤልዛቤል?"
ጥያቄው ከእንቅልፏ አባነናት፡፡
"አቤት…"
"የምጠይቅሽን ጥያቄ በጥንቃቄ ለመመለስ ሞክሪ? አለበለዚያ ለሚደርስብሽ ስቃይ ተጠያቂ ማንንም እንዳታደርጊ፡፡ ሁሉም ውሳኔ ያንቺ ነው፡፡ ተግባባን?"
"አዎ…" አለች ኤልዛቤል፤ በጨርቅ የተሸፈኑት አይኖቿ ላይ የእንባ ድፍድፍ እያመረተች፡፡
"ስንት ሆናችሁ ነው ወደዚህ ቦታ የመጣችሁት?"
"አልገባኝም…እኛ እነማን ነን? "
ይህን እንደተናገረች ድንገት አንዳች የኤሌክትሪክ ንዝረት ሰውነቷን አነዘረው፡፡ በሀይል ጮኸች፡፡ አለቀሰች፡፡ ጠያቂው በተረጋጋ መንፈስ ጥያቄውን ቀጠለ፡፡
"ስንት ሆናችሁ ነው የመጣችሁት?"
ኤልዛቤል ትንፋሽ ሰብስባ ለማሰብ ሞከረች፡፡ እነዚህ ሰዎች ያለምንም ርህራሄ እያሰቃዩዋት እንደሚሰነብቱ እንዲሁ ገባት፡፡ እያሰቃያት ያለው ሰው ስለ ማን እና ስለ ምን እየጠየቃት እንደሆነ ልታውቅ አልቻለችም፡፡ አሁን ላይ ሆና ተረጋግታ አስባ ልትደርስበት የሚቻላት ታሪክ ከኋላዋ ሊታያት አይችልም፡፡ ማምለጥ ብቻ እንዳለባት ነው ህሊናዋ እየደጋገመ እየነገራት ያለው፡፡ ይህን እያሰበች ያለችበት ወቅት ላይ ድንገት የኤሌክትሪኩ ንዝረት መጥቶ አንድ ጊዜ በሀይል አስጮሀት፡፡
"እሺ ታገሰኝ…" አለችው ንዴትና እልህ በተቀላቀለበት አንደበት፡፡
"ስንት ሆናችሁ ነው የመጣችሁት?" ጠያቂው ድምፅ ላይ መጠነኛ የድል አድራጊነት ስሜት ይደመጥበት ጀምሯል፡፡
"አራት ነን…" መለሰች ኤልዛቤል፡፡
"ለምንድን ነው የመጣችሁት? አላማችሁ ምን ነበር?"
"መረጃ ይዞ ለመውጣት ብቻ ነው የመጣነው፡፡" ኤልዛቤል በጥንቃቄ ጥያቄዎቹን ማድመጥ እንዳለባት እየገባት ነው፡፡ ጥያቄው እስካለ ድረስ መልስ ስፍራዋን ፈልጋ መክተሟ ግድ ነው፡፡
"ምን አይነት መረጃ ነው መሰብሰብ የፈለጋችሁት?"
"የማህበራችሁን አጠቃላይ አላማ…ከተቻለ ሙሉ ማኒፌስቶዋችሁን ይዘን ለመውጣት ነው የተላክነው፡፡"
ድንገት ፀጥታ ሰፈነ፡፡ በድን ዝምታ ውስጥ ሆና ኤልዛቤል የጠያቂዋን ትንፋሽ ለማድመጥ ሞከረች፡፡ ጠያቂው በፍጥነት በመተንፈስ ላይ ነው፡፡ ትልቅ ሀላፊነት ይዞ ወደ እሷ እንደመጣ ገባት፡፡ የሚፈልገውን መረጃ ካላገኘ አለቃው በሰላም እንደማይቀበለው አውቃለች፡፡ ስለዚህ ከራሷ ውጭ የዚህንም ሰው ህይወት መታደግ እንዳለባት ነው እየገባት ያለው፡፡ ፍርሀቱን መጠቀም እንዳለባት ገባት፣ ስጋቱ ድረስ ሄዳ የልቡን አድምጣለት ከአለቃው ይልቅ እሷ ደህነቱ ሆና የመገኘት ሀላፊነት አለባት፡፡ በዛ ውስጥ ነው መዳን የምትችለው፡፡ በንቃት ውስጥ ሆና የጠያቂውን ቃላት መጠበቅ ጀመረች፡፡
"እንዴት እንደተያዥስ ታስታውሻለሽ?"
"ምንም አይነት ትውስታ የለኝም፡፡ ሰውነቴ በጣም ደክሟል፡፡ በትክክል ላስብ አልችልም፡፡ በዚህ ስቃይ ውስጥ ማንስ ትላንቱን ማስታወስ ይችላል፡፡ እንደምታየኝ ነኝ፡፡ አቅም የለኝም፡፡ እንደፈለክ ብታደርገኝ ራሴን የምከላከልበት መንገድ የለም…እንደፈለክ ልታደርገኝ ትችላለህ…እሱን ደግሞ ጠንቅቀህ ታውቀዋለህ፡፡ እንደፈለክ…."
ይህን ተናግራ ፀጥ አለች፡፡ የልብ ትርታው ጋር የነፍሷን ጆሮዎች ላከቻቸው፡፡ በሀይል እየደለቁ ናቸው፡፡ ምራቁን ሲውጥ እያንዳንዱን የጉሮሮውን ክርክር በማድመጥ ደረሰችበት፡፡ "እንደፈለክ ማድረግ ትችላለህ…" እያለች ደጋግማ ቃላቶቹን የተጠቀመችው የወሲብ ከፍታውን ለማናር ብቻ ነበር፡፡ ለዚህ ሰው ጉልበትና ወንድነቱን ሰጥታዋለች፡፡ ከዚህች ደቂቃ አንስቶ እስረኛው ሳትሆን የወሲብ መገልገያ ቁሱ እንደሆነች አድርጎ ማሰብ እንደሚጀምር ታውቃለች፡፡ አውቃ ነው ይህን ያደረገችው፡፡ ጠያቂው ጉሮሮውን ጠራርጎ ጠየቃት…
"እስካሁን ለምን እንዳልተገደልሽ ታውቂያለሽ?"
"አዎ…በምሰራበት የስለላ ድርጅት ውስጥ ቁልፍ ሰው ከሚባሉት ሰዎች ውስጥ ስለሆንኩ፣ የእውቀት ስፋቴ ከየትኛውም የድርጅታችን ሰራተኞች በላይ ከፍ ስለሚያደርገኝ እና ተፈላጊ ስላደረገኝ፣ ቆንጆ ስለሆንኩ፣ ያየኝ በሙሉ ስለሚመኘኝ….ለዛ ይመስለኛል ሞት ወዳጆቼን መቀማት ችሎ የኔ ደጅ ጋር መድረስ ያቃተው፣ የሚወዱኝም የሚጠሉኝም በእኩል አይን ነው የሚያዩኝ…ሁሉም የሚወዱኝ የሚያከብሩኝ ሰው ነኝ፡፡ ያልሞትኩት ኤልዛቤል ስለሆንኩ ነው፡፡"
 ያ ፀጥታ ተመልሶ መጣ፡፡ የጠያቂው ነፍስ ጋር ቀረብ ብላ ልታደምጥ ሞከረች፡፡ ትንፋሹ በሀይል ጨምሯል፡፡ መረቧ ውስጥ እያስገባችው እንደሆነ እየተረዳች ነው፡፡ ጊዜ ማባከን አልፈለገችም፡፡
"ይቅርታ…እኔን ከመግደልህ በፊት አንድ ጥያቄ ብቻ ልጠይቅህ?"
ጠያቂው ጥቂት ካንገራገረ በኋላ ፈቀደላት፡፡
"ትኩር ብለህ ስታየኝ አምራለሁ? ሌሎች ሰዎች ታምሪያለሽ እያሉ ያቆዩኝ ዘመኔን ከመርገሜ በፊት ይሄን ብቻ መልስልኝ….አምራለሁ…?"
ጠያቂው በቀስታ ሲጠጋት ተሰማት፡፡ ወደ ፊቷ እየተጠጋ መሆኑን ከርቀት እየጋለ በሚመጣው እስትንፋሹ ገባት፡፡ አንገቷ ስር ገብቶ ሲተነፍስ ተሰማት፡፡ ጊዜ ማባከን አልፈለገችም፤ አንገቷን በሀይል ወደ ጎን ስባ በሀይል መንጋጋው ስር በጭንቅላቷ አጎነችው፡፡ እዛው ታፋዋ ስር ወደቀላት፡፡
ኤልዛቤል…
ለመኖር ያላት እድል በደቂቃዎች ውስጥ እንደሚወሰን ደርሳበታለች፡፡
ነፃነቷ ታፋዋ ላይ ተጋድሞ እየጠበቃት ነው፡፡
                                     
የዘካሪያስ አይኖች ተገለጡ፡፡ አለመሞቱን ያወቀው ያኔ ነው፡፡ ተበሳጨ፡፡ እንዴት አድርጎ እንደዳነ ለማስታወስ ጊዜ አላገኘም፡፡ የአንዲት ሴት ድምፅ ሊሰደድ ያለው ሀሳቡን ስባ አሁኑ ላይ መለሰበት፡፡
"ወንድም ዘካሪያስ ….እንኳን ወደ ሰው ልጆች መንደር በሰላም ተመለስክ?"
የልጅቷን መልክ ለማየት ሲዞር አንገቱ ላይ የተሰማው ህመም አላዞር አለው፡፡ ልጅቱ ይህን ተመልክታ አጠገቡ መጥታ ቆመች፡፡ ዘካሪያስ አተኩሮ ተመለከታት፡፡ ያውቃታል፡፡ አዘውትሮ ቡናውን የሚጠጣበት ካፌ ውስጥ አስተናጋጅ ሆና ያውቃታል፡፡
"አስታወስከኝ?" አለችው ስስ ፈገግታ ለአይኑ እየሰጠችው፡፡
"አውቅሻለሁ…የት ነኝ ያለሁት?"
"ለጊዜው ምንም አይነት እውቀት ባልሰጥህ ደስ ይለኛል፡፡"
"ለምን አዳንሺኝ…ማነሽ አንቺ?"
"ራስህን ነው ያዳንከው ወንድም ዘካሪያስ፡፡ እኔ ምንም ያደረኩልህ ነገር የለም፡፡ ለማንኛውም አሁን ላይ በጣም የምትፈለግ ሰው ነህ፡፡ በኔም ሆነ በብዙዎች፡፡ በጣም የሚያስቅህ ነገር ምን ልሁን ብዬ እንደሆነ እንጃ በሁለት የተለያዩ ግለሰቦች ነው ተቀጥሬ ስከታተልህ የከረምኩት፡፡ አሁን ግን ግራ የገባኝ ለየትኛቸው አሳልፌ ልስጥህ የሚለው ሀሳብ ነው፡፡ እ….ምን ይሻላል ትላለህ?"
ዘካሪያስ በፍርሀት ነው እያያት ያለው፡፡ በመሰረታዊነት ለአመታት እያፈላለገው ያለ ሰው እንዳለ ያውቃል፡፡ ሆኖም ስለ ሁለተኛው ሰው ደግሞ የሚያውቀው ነገር የለም፡፡
"ስለ ምን እያወራሽ እንደሆነ ላውቅ አልቻልኩም፡፡ እኔ ሰላማዊ ሰው ነኝ፡፡ በማንም ላይ ጉዳት አድርሼ አላውቅም፡፡ እስከዛሬም ባለው ህይወቴ አንድም ጠላት ተነስቶብኝ አያውቅም…."
የለበጣ ሳቅ እየሳቀች አጠገቡ ተጠግታው ተቀመጠች፡፡
"እርግጠኛ ነህ ዘኪ? የምሬን ነው… ስለምታወራው ነገር በጣም እርግጠኛ መሆን አለብህ፡፡ ይሄን ያልኩህ ዋነኛው ምክንያት፣ አንተን አስሼ እንዳገኝህ የሚፈልጉ ሰዎች ከለመድኩት ወጣ ባለ ከፍተኛ ገንዘብ ነው የተደራደሩኝ፡፡ እና ሳሰላስለው ይሄ ሰው ማን ቢሆን ነው በዚህን ያህል ደረጃ እየተፈለገ ያለው ብዬ ነገሮችን እንድመረምር ሆንኩኝ፡፡
ከዛም ስላንተ ማጥናት ጀመርኩኝ፡፡ በጥንታዊ የአስማት ጥበቦች ላይ እውቀት ያለህ ሰው እንደሆንክ፣ ሚስትህ እንደሞተችብህ፣ አሁን ላይ የት እንዳለች የማታውቃት አንዲት ሴት ልጅ እንዳለችህ፣ የልቤ የምትላቸውጓደኞች እንደሌሉህ፣ ያላሳተምከው ሚስጥረ ራዛኤል የሚል መፅሐፍ እንደፃፍክ፣ ከዛም ባለፈ ማንም እጅ ላይ የሌለ… የመላው ሁለንታን ሚስጥር የሚያትት…ከምድር ሆድ እቃ ውስጥ ያሉትን ማዕድናት አስሶ የሚጠቁም የብራና ጥቅል ለብቻህ ደብቀህ እንደምትኖር እና አሁን ላይ የማልገልፅልህን የህይወትህን ክፍል በደንብ አድርጌ ደረስኩበት፡፡ "
"እና ምን ውሳኔ ላይ ደረሽ?" ዘካሪያስ ረጋ ብሎ ጠየቃት፡፡
"ማን እያሳደደህ እንደሆነ እንደምታውቅ አውቃለሁ፡፡ ማወቅ የምፈልገው ግን ለምን የምትለዋን ነው፡፡ ለምንድን ነው የሚፈልጉህ…? በዚህ ሀሳብ ላይ ያንተን እውቀት ሳትዋሽ ከነገርከኝ ነፃነትህን ምናልባት ልሰጥህ እችላለሁ፡፡"
የዚያን ሰዓት ላይ ነው ዘካርያስ ከተኛበት አልጋ ጋር የጥፍንግ እንደታሰረ የተረዳው፡፡
"የምፈለገው ለእውቀቴ ነው፡፡ በሰው ልጅ አይን ታይቶ የማይተረጎም እውቀትን ከነፍሴ ከትቤ በሚስጥራዊው እውቀት ውስጥ የምመላለስ ሰው ነኝ፡፡ ህይወቴ ሚስጥር ነው፡፡ እውቀቴ ሚስጥር ነው፡፡ እምነቴ ሚስጥር ነው፡፡ እዚህ እሳቤ ድረስ እንዳስብ ያደረገኝም ሀሳብ በራሱ ሚስጥር ነው፡፡ ምንም ልነግርሽ የምችለው እውነት የለም፡፡ ለማንም አሳልፈሽ ብትሰጪኝ መልሴ ተመሳሳይ ነው፡፡ የልቤን ተረድቶ መልስ ወደሚያሻኝ ስፍራ የሚሰደኝ ሞት ነበር …እሱንም አንቺ ቀድመሽ ቀማሺኝ፡፡  ከቻልሽ መልሰሽ ግደይኝ? አሁን በጭንቅላቴ ውስጥ የከመርኩት እውቀት እያሰቃየ እንደበረዶ አሟሙቶ በስቃይ ሳይጨርሰኝ በፊት አንቺው ግደይኝ?
”ራሱን ሊገድል ከሚሻ ልብ ውስጥ ምንም አይነት ተስፋ አትፈልጊ፡፡ የምታስፈራሪኝ እየመሰለሽ ከሆነ ደግመሽ ማሰብ ይጠበቅብሻል፡፡ ብለምንሽ …ውለታ ብጠይቅሽ፣ የምጠይቅሽ አንድ ነገርን ብቻ ነው፡፡ ግደይኝ እና እኔንም ሆነ ይህችን ምስኪን ሀገር ታደጊያት፡፡ "
ልጅቷ አሁንም ፈገግ ብላ ስታየው ከቆየች በኋላ ከተቀመጠችበት አልጋ ላይ ተነስታ በጠረጴዛ ላይ ያስቀመጠችውን ስልክ አንስታ የዘካርያስን አይኖች በጥናት እያየች ደወለች፡፡ ስልኩ ተነሳ፡፡
"መምጣት ትችላላችሁ--" ይህን ተናግራ ከዘካሪያስ አይኖች ተሰወረች፡፡

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የባህል ማዕከል በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የሁሉም ዩኒቨርስቲዎች ባህል ማዕከላት የሚሳተፉበትና የፊታችን ሰኞ ጥር 27 ቀን 2016 ዓ.ም የሚከፈት አገራዊ ፌስቲቫል ማዘጋጀቱ ተገለፀ፡፡
ፌስቲቫሉ ለተከታታይ ሦስት ቀናት  የሚቆይ ሲሆን፤ መክፈቻው ሰኞ ከአመሻሹ 11 ሰዓት እስከ ምሽቱ 2 ሰዓት ድረስ በዩኒቨርስቲው የፋውንቴይን መናፈሻ አውድ ፊት ለፊት ለዚሁ ዓላማ ታስቦ በተዘጋጀ መድረክ ላይ በልዩ ልዩ ዝግጅቶች እንደደመቀ የሚቆይ ነው ተብሏል፡፡
 “ከዚህ በኋላም ዩኒቨርስቲዎች በየተራ ሃላፊነት ወስደው የሚያዘጋጁት ክብረ-በዓል ሆኖ ይቀጥላል፡፡ በሂደትም ምስራቅ አፍሪካን፣ አፍሪካን፣ ሌሎች አህጉራትን… ደረጃ በደረጃ እያካተተ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚከበር “ኢንተርናሽናል ፌስቲቫል” እንዲሆን ለማስቻል ታቅዷል” ብሏል፤ የባህል ማዕከሉ ከትላንት በስቲያ ሃሙስ ባሰራጨው መግለጫ፡፡
“ይህ ሲሆን የአገራችን ዓይነተ- ብዙ ባህላዊ እሴቶች፣ ኪነጥበባዊና ሥነጥበባዊ የፈጠራ ውጤቶች፣ ብሎም ደግሞ አገራዊ የቱሪስት መስህቦች በማስተዋወቅ ረገድ የሚጫወታቸው የገፅታ ግንባታ ሚናዎች በዓይነትም፣ በይዘትም፣ በቅርፅም እጅግ በርካታ እንደሚሆኑ ይታመናል” ብሏል የባህል ማዕከሉ፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የባህል ማእከል በኢትዮጵያ ዩኒቨርስቲዎች ታሪክ አንጋፋውና ግንባር ቀደሙ እንደመሆኑ መጠን፣ አገራዊ ሃላፊነቱም የዚያኑ ያህል እጅግ በጣም ከባድ እንደሆነ እናምናለን ያለው ማእከሉ፤ ይህንኑ እምነታችንን መሰረት በማድረግም የሁሉንም ዩኒቨርስቲዎች የባህል ማዕከል ያቀናጀ “አገር - አቀፍ የዩኒቨርስቲዎች ባህል ማዕከላት ጥምረት”ን ለመመስረት የሚያስችለውን የፈር - ቀዳጅነት ሚና ሲጫወት ቆይቷል ብሏል፡፡
“በውጤቱም እነሆ ዛሬ በዓይነቱም ሆነ በግብሩ የመጀመሪያ በሆነው ታላቅ አገራዊ ፌስቲቫል ላይ በአንድነት ለመታደም ጫፍ ላይ ደርሰናል” ብሏል ማዕከሉ በመግለጫው፡፡



የካቲት
ወይ ስትገባ
ወይ ስትወጣ
ባታንጎዳጉድ፤ መሬት ትጨነቅ ነበር!
የአንድ ንጉሥ አገር በጣም ሥቃይና ዕንባ በዛበት፡፡ ይኸውም በአንድ ሰብል በሚያጠፋና ሰው በሚገድል አውሬ ምክንያት ነበር፡፡ ንጉሡ መላ ፍለጋ ብዙ አውጥተው አውርደው ሲያበቁ፤ በመጨረሻ “ይህን አውሬ ገድሎ ወይም እስከ ህይወቱ አጥምዶ አገሬን ከሥቃይ ላወጣ ሰው ከፍተኛ ሽልማት እሰጣለሁ” አሉ፡፡ ሆኖም አውሬው እጅግ ግዙፍ በመሆኑ ሰው ሁሉ ወደ ጫካው መሄድ ፈራ፡፡ ንጉሡ የበለጠ ህዝቡን ለማበረታታት ብለው ከሽልማቱ በተጨማሪ ሴት ልጃቸውን እንደሚድሩለት አሳወቀ፡፡
በዚያ አገር የሚኖሩ የአንድ ደሀ ሰው ሁለት ወንዶች ልጆች ነበሩ፡፡ መጥተው ለንጉሡ አውሬውን እንደሚገድሉ ተናገሩ፡፡ ታላቅዬው ብልጥና ጉልበተኛ ሲሆን የሚመራው በምኞት ነበር፡፡ ታናሽዬው ደግሞ ሁሉ ነገሩ የዋህና ገር ነበረና በልበ-ቀናነቱ ብቻ ይመራ ነበር፡፡ ንጉሡ፤
“እንግዲህ አውሬውን ለማግኘታችሁ እርግጠኛ እንድንሆን ወደ ጫካው ከሁለት አቅጣጫ ግቡ” አሉ፡፡ በዚህ መሰረት ታላቅዬው በምዕራብ በኩል ገባ፡፡ ታናሽዬው ደግሞ በምሥራቅ፡፡
ታናሽዬው ትንሽ  መንገድ እንደሄደ አንድ ጥቁር ጦር የያዘ አጭር ሰው ድንገት ከጫካው ብቅ ብሎ፤
“እንካ ይሄንን ጦር ያዝ፡፡ ምክንያቱም ልብህ ንፁህ ነው፡፡ በዚህ ጦር አውሬውን ሳትፈራ ልትወጋው ትችላለህ፡፡ ምንም ጉዳት አያደርስብህም አይዞህ” አለና ሰጠው፡፡
ታናሽ ወንድም የተሰጠውን ጦር አንግቦ አመስግኖ መንገዱን ቀጠለ፡፡ ልበ - ሙሉ ሆነ፡፡ ጥቂትም ሳይጓዝ አውሬው ብቅ አለ፡፡ ገና ጦሩን ወድሮ እንደቆመ አመለኛው አውሬ ከፍርሃት በመነጨ ጭካኔ የዕውር የድንብሩን መጥቶ ጦሩ ላይ ተንደርድሮ ተሰካበት፡፡ ጦሩ ልቡ ላይ ተሰካና ሁለት ላይ ከፈለው፡፡ ታናሽ ወንድም የአውሬውን ሬሣ ተሸክሞ ለንጉሡ ሊያስረክብ መንገዱን ቀጠለ፡፡
በአንፃሩ ታላቅ ወንድሙ በሄደበት በተቃራኒው አቅጣጫ ሰዎች ሁሉ የሚዝናኑበት አንድ መሸታ ቤት አለ፡፡ ታላቅ ወንድም እዚህ መሸታ ቤት ሊገባ አሰበና “አውሬው እንደሆነ ከዚህ ጫካ ወጥቶ አይሄድም፡፡ ለምን ለድፍረት እንዲሆነኝ ጥቂት እህል ውሃ አልልም?” ብሎ ገባና ጥቂት መጠጥ ጠጣ፡፡
ከመሸታ ቤቱ ሲወጣ ታናሽ ወንድሙ አውሬውን ተሸክሞ ሲመጣ አየው፡፡ እቡይና እኩይ ልቡ ሸር አሳሰበውና፤
“ና ወንድም ዓለም አረፍ በልና ወይን ጠጣ” አለው፡፡ ምንም ተንኮል ያልጠረጠረው ታናሽ ወንድም፣ ግብዣውን ተቀብሎ ሲጠጣ ቆየ፡፡ ያ አጭር ሰውዬ ጦር እንደሰጠውና አውሬውን እንደገደለው ነገረው፡፡ ሲመሻሽ አብረው መንገድ ጀመሩ፡፡ ከጅረቱ ላይ ካለው ድልድይ አጠገብ ሲደርሱ ድቅድቅ ጨለማ ሆነ፡፡
ታላቅዬው ታናሽዬው እንዲቀድም ይነግረውና ግማሽ ድልድዩን አብረው ይሄዳሉ፡፡ ጥቂት ካደባ በኋላ ከኋላው ክፉኛ ይመታዋል፡፡ በዚህም የታናሽ ወንድም ህይወት ያልፋል፡፡
ቀጥሎም፤ ታናሽ ወንድሙን ድልድይ ሥር ቀብሮ፣ የአውሬውን ሬሳ ይዞ ወደ ንጉሡ ይሄዳል፡፡ ንጉሡም ተደስተው ልጃቸውን ይድሩለታል፡፡
ታናሽ ወንድሙ እስከመጨረሻው ሳይመጣ ቀረ፡፡ ታላቅ ፈጠን ብሎ፤
“ምናልባት ታናሽ ወንድሜን አውሬው በልቶት ይሆናል፡፡” ሲል ዋሸ፡፡ ሰው ሁሉ ግን አመነው፡፡
ሆኖም በዓለም ላይ ምንም ነገር ተሸሽጎ አይቀርምና፤ ከዓመታት በኋላ አንድ እረኛ ከብቶቹን ከዚያ ድልድይ ላይ እየነዳ ሳለ ታች አሸዋው ላይ አንድ ነጭ፤ የሚያበራ፣ ረዥም - አጥንት አየና ለጥሩምባ መሣሪያ ቢሆነኝ ብሎ ወርዶ ወሰደው፡፡ ከዚያም እየፋቀ በጥሩምባ ቅርጽ ሰራው፡፡ ሊነፋው ገና ወደ አፉ እንዳስጠጋው ግን አንድ ተዓምር ተከሰተ፤
“እረኛ ሆይ እረኛ ሆይ፤ የምትጫወተው
በእኔ አጥንት እኮ ነው፡፡
ተመትቼ ሞቼ በገዛ ወንድሜ
የገደልኩት አውሬ ተወስዷል በስሜ፡፡
ከውሃው አጠገብ አካሌን ቀበረ
ለንጉሡ ሴት ልጅ በተንኮል ተዳረ”
ሲል አጥንቱ ዘመረ፡፡ እረኛው በመገረም “ይሄን ጉድ ለንጉሥ ማሳየት አለብኝ” ብሎ ወደ ንጉሱ ሄደ፡፡ ቀርቦም አጥንቱን አሳየ፡፡ አጥንቷ እሱ ሳይናገር በፊት መዘመር ጀመረች፡፡ ንጉሱ ነገሩ ገባቸው፡፡ ቦታው ድረስ ጋሻ ጃግሬ ልከው አስቆፍረው የታናሽዬውን ሬሳ አወጡ፡፡ በቦታውም ታላቅ ወንድሙ ተገድሎ እንዲቀበር ትዕዛዝ ሰጡ፡፡
***
በብልጥነትና በጉልበተኛነት የሰሩት ተንኮል ውሎ አድሮ ከመጋለጥ አያመልጥም፡፡ በልበ - ቀናነት የተሰራ ሥራ ግን ለብዙዎች ጠቀሜታው ሰፊ ነው፡፡ ግዙፉን አውሬ በንፁህ ልቡ ሊዋጋ የሄደው ልጅ ቀንቶት ያገኘውን ድል፤ በተንኮልና በዕቡይነት የነጠቀው ቀማኛው ታላቅ ወንድም ምንም ሳይቆይ ተጋልጧል፡፡ አውሬው ብዙ ጥፋት ያደረሰ ነበረና ከፍርሃቱ በመነጨ ጭካኔው ያልተወረወረ ጦር ላይ መሰካቱም “ደም ያሰከረው” እንዲሉ መሆኑ ነው፡፡ የታናሽ ውንድሙን ሞት በአውሬው ያሳበበው ታላቅ ወንድሙ የሰራው ግፍ ሳያንስ ውሸት መጨመሩ ሁለተኛ ጥፋት ነው፡፡
ምርጫንም ሆነ ድርድርን በልበ - ቅንነት ማካሄድ አንድ በጎ እርምጃ ነው፡፡ አፈ-ቅቤ ልበ-ጩቤ የሆነ አካሄድ ግን ማንንም ወደፊት አያራምድም፡፡ ዕውነቱን ገልጦ የሚወጣ ተዓምረኛ ጥሩምባ ከምድርም ይፍለቅ ከሰማይም ይዝነብ ብቅ የሚልበት ቀን እንዳለ ልብ ብሎ፤ እጅን ከግፍ አፍን ከቅጥፈት መሰብሰብ ወቅታዊው ብልህነት ነው፡፡ በሰፈሩት ቁና መሰፈር እንደማይቀር አለማስተዋል ከባድ እርግማን ነው፡፡ በድፍረት አሻፈረኝ ብለው ዘራፍ ካሉም “ሥጋ ሲመጣ ዳንኪራ፣ ዕዳ ሲመጣ ኩብለላ” መሆኑን ከወዲህ ለመገመት አያዳግትም፡፡
ለውጥን ቀስ በቀስ እንደሚገነባ ጥብቅ ካብ ማሰብ እንጂ በነቶሎ ቶሎ ቤት አሰራር ልናመጣው እንደማይቻል፣ ከተቻለም እንደማያዛልቅ መረዳት ለሀገራችን እጅግ ጠቃሚ መነሻ ይሆናል፡፡ ይህን መሰረት ያልያዘ ሂደት ውሎ አድሮ “የተማመኑበት ቢላዋ በጉበት ይሰበራል” ዓይነት እንደሚሆን ልብ ማለት ደግ ነገር ነው፡፡
በወርሃ የካቲት በኢትዮጵያ አያሌ እንቅስቃሴዎች እየፈሉ እንደነበሩ ሁሉ ወራቸው ሲገባ የሀሳብ፣ የዕውቀት፣ የለውጥ ንፋስ መንፈሱ ያለ ነው፡፡ ከየካቲት 23 እስከ መሬት ላራሹ፣ ከየካቲት 12 እስከ የካቲት 11 ብዙ አይተናል፡፡
ዛሬም ብዙ እንሰማለን፤ የተጨበጠም ያልተጨበጠም፡፡ ሁሉም ምን እንዳዘለ ጊዜ ያሳየናል፡፡ ለውጥ የጊዜ ልጅ ነው፡፡ “የካቲት ወይ ስትገባ ወይ ስትወጣ - ባታንጎዳጉድ፣ መሬት ትጨነቅ ነበር” የሚለው የሰሜኖች ተረት እንዲሁ አልተተረተም፡፡

ባለ አራት ኮከቡ ዘጠነኛው ኃይሌ ሆቴል ወላይታ በዛሬው ዕለት አገልግሎት መስጠት መጀመሩን አብስሯል፡፡ ሆቴሉ  ትልቁን ዳሞታ ተራራን ተንተርሶ  በኮረብታማዋ ወላይታ ሶዶ ከተማ እምብርት ላይ የተገነባ ነው።

 ሆቴሉ ተሰርቶ ለመጠናቀቅ አራት ዓመታትን የፈጀ ሲሆን፤ እስካሁን 1 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር ወጥቶበታል ብሏል፤ በሆቴሉ ዳሞታ አዳራሽ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጠው ሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ።

 ሆቴሉ 107 ዘመናዊ የማረፊያ አልጋዎች፣ ከ15-600 ሰው የመያዝ አቅም ያላቸው 7 የስብሰባ አዳራሾች፣  የጤናና የውበት መጠበቂያ -  የጂም የሳውና የስቲም ባዝና የማሳጅ አገልግሎት  እንዲሁም የወላይታ ህዝብ የምግብ ሜኑን ጨምሮ የተለያዩ የሐገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ምግቦችን የያዙ ሦስት ዘመናዊ ሬስቶራንቶች የለስላሳና የአልኮል መጠጦች አገልግሎት የሚሰጡ ሁለት ባሮችን በውስጡ ይዟል።

በአሁኑ ወቅት ለ160 ሰዎች የስራ እድል የፈጠረ ሲሆን፤ በሙሉ አቅሙ ስራ ሲጀምር ለ300 ሰዎች ቋሚ የስራ እድል እንደሚፈጥር ተገልጿል።

  "አንድ ኢንቨስተር  ኢንቨስት ሊያደርግ ሲነሳ መጀመሪያ የሚያየው የአካባቢው ህዝብና መንግስት ምን ያህል ቀና ናቸው የሚለውን ነው" ያለው ሐይሌ፤ የወላይታ ህዝብ ላሳየው ቅንነትና ትብብር አመስግኗል። ሆቴሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ዋና መቀመጫ ለሆነችውና በፈጣን  እድገት ላይ ለምትገኘው ወላይታ ሶዶ ከተማም ሆነ ለነዋሪዎቿ ድምቀት  ብሎም የስራ እድል ይዞ የመጣ የህዝብ ሐብት ነው  ያለው ሐይሌ፤ ለቱሪዝም ፍሰትና ለኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ጉልህ ሚና ይጫወታልም ብሏል።

ከ14 ዓመት በፊት በሐዋሳ ከተማ የተጀመረው የሐይሌ ሪዞርት፣ ዛሬ ላይ በተመሳሳይ የአገልግሎት ጥራት 9ኛ ሆቴሉን በወላይታ እያስመረቀ ሲሆን፤ በቀጣይ በጅማ በደብረ ብርሃንና በሻሸመኔ ሐይሌ ሆቴሎችና ሪዞርቶች ተከፍተው ስራ ይጀምራሉ ተብሏል።

 ኃይሌ በአካባቢው በተፈጠረ አለመረጋጋት የሻሸመኔና  በዝዋይ ያሉት ሆቴሎቹ ውድመት እንዳሳዘነው ገልፆ፣ ምንም እንኳን መንግስት  ካሳ ባይከፍለውም (እንዲከፍለኝ እጠብቃለሁ ብሏል)፤ሆቴሎቹ ግን መገንባትና ስራ መስራት ስላለባቸው የዝዋዩ ስራ ላይ ሲሆን የሻሸመኔው ግን እንደገና ፈርሶ በአዲስ መልክ እየተገነባ ስለመሆኑ አብራርቷል። በወላይታው የሆቴሉ ግንባታ ላይ የግብአት እጥረት ከፍተኛ  ተግዳሮት እንደነበረ ኃይሌ ተናግሯል። በዘጠኙም ኃይሌ ሆቴሎችና ሪዞርቶች በአጠቃላይ  1ሺ 800 ሰዎች ተቀጥረው እየሰሩ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ኢትዮ ቴሌኮም በዘንድሮው መንፈቅ ዓመት 42.86 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ገቢ ማግኘቱንና አጠቃላይ የደንበኞቹ ብዛት 74.6 ሚሊዮን መድረሱን አስታውቋል፡፡
ኩባንያው ይህን ያስታወቀው ሰሞኑን  በስካይ ላይት ሆቴል የ2016 በጀት ዓመት የመጀመሪያ መንፈቅ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርቱን ለመገናኛ ብዙኃን ባቀረበበት ወቅት ሲሆን፤ ሪፖርቱ ከሐምሌ 2015 እስከ ታህሳስ 2016 በጀት ዓመት ያለውን የሥራ አፈጻጸም የሚገልጽ መሆኑ ታውቋል፡፡  
በመንፈቅ አመቱ አጠቃላይ የደንበኞቹ  ብዛት 74.6 ሚሊዮን መድረሱን የጠቆመው ኩባንያው፤ ይህም  ከባለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት አንጻር የ4.7  ሚሊዮን ወይም የ6.7% እድገት ማሳየቱን እንዲሁም ከእቅድ አንጻር የ98.3% ውጤት መመዝገቡን አመልክቷል፡፡
በአገልግሎት አይነት ሲታይ የሞባይል ድምፅ ደንበኞች ብዛት 71.7 ሚሊዮን፣ የሞባይል ዳታና ኢንተርኔት ተጠቃሚዎች 36.4 ሚሊዮን፣ የመደበኛ ብሮድ ባንድ 688.3 ሺህ እንዲሁም የመደበኛ ስልክ ደንበኞች 834 ሺህ ሲሆኑ፤ የቴሌኮም ስርጸት (teledensity) መጠን 68.5% ማድረስ ተችሏል ብሏል፤ኢትዮ ቴሌኮም፡፡


”የደንበኞችን ቁጥር ለማሳደግ የተቻለው፣ ተሞክሯቸውን ለማሻሻል እንዲሁም ተደራሽነትን ለማስፋት፤ ተጨማሪ የሞባይልና የመደበኛ ኔትዎርክ ማስፋፊያ ሥራዎች በመሰራታቸው፣ተጨማሪ የአገልግሎት መስጫ ማዕከላትና የምርትና አገልግሎት አጋሮች በማካተት አዳዲስ ምርትና አገልግሎቶች ለገበያ በመቅረባቸው፣ የ5ጂ አገልግሎት በአዲስ አበባና በተወሰኑ የክልል ከተሞች እንዲሁም የደንበኞችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ወቅታዊነትን የተላበሱ 114 (64 አዳዲስ እና 50 ነባር) የሀገር ውስጥና የዓለም አቀፍ ምርትና አገልግሎቶችን በማሻሻል ለደንበኞች በመቅረባቸው ነው፡፡” ብሏል፤ ኩባንያው በመግለጫው፡፡ የአገልግሎት ጥራትን እንዲሁም የኔትወርክ ሽፋንና አቅምን ከማሳደግ አንጻር የኔትወርክ ማስፋፊያ የፕሮጀክት ሥራዎች በመከናወን ላይ ሲሆኑ ወሳኝ ተልዕኮ ላላቸው (Mission Critical)፣ በተመሳሳይ ወቅት(real time) መከናወን ለሚያስፈልጋቸው አገልግሎቶች እና internet of things የመሳሰሉ ቴክኖሎጂዎች በተግባር እውን እንዲሆኑ የሚያስችለውን 5G የሞባይል ቴክኖሎጂ አገልግሎት በተወሰኑ ከተሞች ለገበያ ማቅረቡንም አመልክቷል፡፡


 በግማሽ ዓመቱ በተደረገ የኔትወርክ ማስፋፊያ በ3G 678.2 ሺህ፣ በ4G 1.1 ሚሊየን እና በ5G 148.2 ሺህ በድምሩ 1.9 ሚሊየን ተጨማሪ ደንበኛ የሚያስተናግድ አቅም መፈጠሩን የጠቆመው ኩባንያው፤ በዚህም አጠቃላይ የሞባይል ኔትወርክ ደንበኛ ማስተናገድ አቅሙን 81 ሚሊየን ለማድረስ እንደቻለ ነው የገለጸው፡፡


በመንፈቅ አመቱ ከተሰሩ  የሞባይል ማስፋፊያዎች መካከል ለገጠር ቀበሌዎች የሚውል በ10 ክልሎች፣ ለ41 ወረዳዎች፣ 229 ሺህ ደንበኞችን ማስተናገድ የሚችሉ 41 የሞባይል ጣቢያዎች ተተክለው አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን እንዲሁም  በገጠር አካባቢ ባሉ 92 ነባር ጣቢያዎች ላይ የ3G ማስፋፊያ ስራዎች ተከናውነው አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉን አስታውቋል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም፤ የአገልግሎት አድማሱን በማስፋት፣ ቀጣይነት ያለው የደንበኞቹን አቅም ያገናዘበ አዳዲስና የተሻሻሉ ምርትና አገልግሎቶችን በማቅረብ እንዲሁም የተለያዩ የሞባይል ፋይናንስና የዲጂታል አገልግሎቶችን በማቅረብ በመንፈቅ ዓመቱ 42.86 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ገቢ በማግኘት የእቅዱን 98% ማሳካቱን አስታውቆ፤ ይህም ካለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ8.86 ቢሊዮን ብር ወይም የ26% ብልጫ እንዳለው ጠቁሟል፡፡ ”የተገኘው ገቢ በአገልግሎት አይነት ሲታይ፤ የድምጽ አገልግሎት 41.8% ድርሻ ሲኖረው፣ ዳታና ኢንተርኔት 25.7%፣ ዓለም አቀፍ ገቢ 9.3%፣ እሴት የሚጨምሩ አገልግሎቶች 8.7%፣ የቴሌኮም አገልግሎት መጠቀሚያ መሳሪያዎች ሽያጭ 5%፣ ቴሌብር 2.5%፣ የመሰረተ ልማት ኪራይ 1.1%፣ እንዲሁም ሌሎች አገልግሎቶች 5.9% ድርሻ አላቸው፡፡” ብሏል፤ የኩባንያው መግለጫ፡፡
 የውጭ ምንዛሪ ከሚያስገኙ አገልግሎቶች 84.7 ሚ. ዶላር መገኘቱንና ይህም የእቅዱን 109% ያሳካ መሆኑን ኢትዮ ቴሌኮም አስታውቋል፡፡
 የቴሌብር አገልግሎት ከ41 ሚሊዮን በላይ ደንበኞችን በማፍራት የዕቅዱን 104% ማሳካቱን በመግለጫው ያመለከተው ኩባንያው፤  የግብይት መጠኑን  910.7 ቢሊዮን ብር በማድረስ አመርቂ ውጤት ማስመዝገቡን ጠቁሟል፡፡  የቴሌብር አገልግሎት ከተጀመረ አንስቶም በአጠቃላይ 1.7 ትሪሊየን ብር በኢኮኖሚው ላይ እያንቀሳቀሰ እንደሚገኝ አክሎ ገልጧል፡፡


በግማሽ ዓመቱ ከዲጂታል ኢትዮጵያ ግንባታ ጋር በተያያዘ 602 መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት የአገልግሎት የክፍያ ስርዓታቸውን ከቴሌ ብር ጋር እንዲያስተሳስሩ  መደረጉንም ኩባንያው በመግለጫው አመልክቷል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም በመንፈቅ ዓመቱ ያጋጠሙትንም ተግዳሮቶች የዘረዘረ ሲሆን፤ በተለያዩ የሀገሪቱ  ክፍል ባጋጠመው የፀጥታ ችግር ምክንያት የአገልግሎት መቋረጥ፣በኔትዎርክ ሀብት ላይ የሚደርሱ አደጋዎች እንዲሁም የፋይበርና የኮፐር መስመሮች ስርቆትና መቆራረጥ፣ቴሌኮም ማጭበርበር፣ የግንባታ ስራ ግብአቶች እጥረት፣ የገበያ አለመረጋጋትና የሃይል አቅርቦት መቆራረጥ በዋናነት የሚጠቀሱ ተግዳሮቶች መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡




የዘንድሮ የአፍሪካ እግር ኳስ ዋንጫ ይፋዊ ስፖንሰር ነው

የሞባይል ቴክኖሎጂ ብራንዶች አምራቹ ቴክኖ ሞባይል፤ ሰሞኑን ስፓርክ 20 ፕሮ ፕላስ (Spark 20 Pro+) የተሰኘ አዲስ ስማርት ሞባይሉን ያስተዋወቀ ሲሆን፤ ምርቱ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተራቀቀ፣ እጅግ ከፍተኛ የካሜራ ጥራትና የፕሮሰሰር አቅም እንዲሁም ለረጅም ጊዜ መቆየት የሚችል ባትሪ፣ ማራኪ ቅርጽና ውበት ያለው የመጨረሻው የቴክኖሎጂ ውጤት መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ኩባንያው ደንበኞች የላቀ የአገልግሎት ተሞክሮ እንዲኖራቸው የሚያስችለውን አዲስ  የስማርት ሞባይል ስልክ ሞዴሉን  በአዲስ አበባ ፍሬንድሽፕ ፓርክ በደማቅ መርሃ ግብር  አስተዋውቋል።

ቴክኖ ሞባይል አዲሱን ስፓርክ ፕሮ ፕላስ ሞዴል ባስተዋወቀበት ልዩ ዝግጅት የመንግስት ባለስልጣናት፣ የቴክኖ ሞባይል ኢትዮጵያ ከፍተኛ አመራሮች፣ የኢትዮጵያ አንጋፋ የእግር ተጫዋቾችና አመራሮች እንዲሁም የስፖርቱ ቤተሰብ የታደሙ ሲሆን፤ በኢትዮጵያ የስፖርቱ ዘርፍ እድገትና የአፍሪካ እግር ኳስ ዋንጫ ተሳትፎ እውን እንዲሆን ከፍተኛ ሚና የነበራቸውን የቀድሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጫዋቾች፣ አሰልጣኞችና የስፖርት ጋዜጠኞችን የማመስገኛ መርሃ ግበር ያካተተም ነበር። በስፖርቱ አለም ተወዳጅ ከሚባሉት ዝግጅቶች አንዱ የሆነውን የአፍሪካ ዋንጫ የእግር ኳስ ውድድር ይፋዊ ስፖንሰር የሆነው ቴክኖ ሞባይል፤ ይህን አዲሱን የሞባይል ሞዴል ከዚሁ የአህጉራዊ ስፖርት መርሀ ግብር ጋር በማስተሳሰር ቴክኖሎጂና ስፖርቱን ያጣመረ የማስተዋወቅ ልዩ ልዩ እንቅስቃሴዎችን በተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት እያከናወነ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

አዲሱ ስፓርክ 20 ፕሮ ፕላስ ሞዴል፤ በ108 ሜጋ ፒክስል አልትራ ሴንሴቲቭ (ultra-sensitive) የካሜራ ጥራት የተገጠመለት ሲሆን፤ በኤ.አይ (AI) ሲስተም በመታገዝ በየትኛውም አይነት የብርሀን መጠን በምሽት ሆነ በቀን ጥርት ያሉ ፎቶዎችን ማንሳት የሚያስችል ሲሆን፤ በከፍተኛ ፍጥነት የተለያዩ መተግበሪያዎችን ያለ እንክን እንዲያስተናግድ የሚያስችለው (G99 ultra boost) የተሰኘ ፕሮሰሰር ያለው መሆኑና 6.78 ኢንች አሞሌድ ስክሪን በ120Hz ሪፍሬሽ ሬት የሆነው ስፓርክ 20 ፕሮ ፕላስ ሲጠቀሙበት ያለምንም እንከን በቅልጥፍና አንዲያገለግል ያደርገዋል ተብሏል። የሞዴሉንም የመያዝ አቅሙን በመጨመር 256 ጂቢ ሚሞሪ በ16 ጂቢ ራም ጋር የቀረበ ሲሆን፤ 5000 mAh አቅም ያለው ባትሪ ከ33W ሱፐር ቻርጅንግ ሲስተም እንዳለውና በአጭር ጊዜ 100% ባትሪ ቻርጅ ማድረግ አቅም ያለው የስልክ ሞዴል ነው- ብሏል ኩባንያው ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ፡፡

በዚህ በምረቃ ወቅት ንግግር ያደረጉት የቴክኖ ሞባይል ኢትዮጵያ ብራንድ ማኔጀር አቶ ኤሊክ ኋንግ፤ ‘’ይህ በላቀ ቴክኖሎጂ በልዩ መልክ የተመረተውን አዲሱ spark 20 pro+ በዚህ አህጉራዊ ውድድር ወቅት በማስተዋወቃችን ኩራት ይሰማናል። በኢትዮጵያ ብሎም በአፍሪካ እየጨመረ የመጣውን የቴክኖሎጂ ፍላጎት አለም ከደረሰበት የስማርት ስልክ ቴክኖሎጂ ጋር በማጣመር፣ የአህጉሪቷን እድገት ለማፋጠን ለሚደረገው ርብርብ የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ እንደሚሆን አንጠራጠርም። ከዚም በተጨማሪ ድርጅታችን ቴክኖ ሞባይል ተወዳጅ የሆነውን አዲሱን ስፓርክ (spark 20 pro+) ስልክ ከማስተዋወቅ ባለፈ የብዙ እግር ኳስ ከዋክብት መፍለቅያ በሆነችው አፍሪካ የ2024ቱን የአፍሪካ የእግር ኳስ ዋንጫ ይፋዊ ስፖንሰር በመሆኑ ደስታችን ላቅ ያለ ነው።’’ ብለዋል።

· ዲሞክራሲ የሚፈተንበት ዓመት ነው ተብሏል
· በመላው ዓለም 4 ቢሊዮን ህዝብ ድምፁን ይሰጣል
· ከ60 በላይ አገራት ውስጥ ምርጫ ያካሂዳል
· በዓመቱ መጨረሻ ዲሞክራሲ መቀጠሉ አጠራጥሯል


የአንድ ወር ዕድሜ ብቻ ያስቆጠረው የፈረንጆች 2024 ዓ.ም በዓለማችን በታሪክ እጅግ በርካታ ምርጫዎች የሚካሄድበት ዓመት ነው። ምርጫ ብቻ ግን አይደለም። ተቃውሞ፣ ጦርነት፣ አምባገነንነት፣ ሥርዓት አልበኝነት አክራሪነት ወዘተ ዓለምን እንዳያናውጣት ተሰግቷል።  መረጃዎች እንደሚጠቀሙት በ2024 ዓ.ም ከ60 በላይ አገራት ውስጥ ምርጫዎች የሚካሄዱ ሲሆን፤ የዓለምን ግማሽ የሚወክል (4 ቢሊዮን ገደማ) ህዝብ ወደ ምርጫ ጣቢያ በማምራት፣ ለፕሬዚዳንታዊ፣ ለፓርላማና ለአካባቢያዊ ምርጫ ድምጹን ይሰጣል፡፡
ዘንድሮ የሚካሄዱ የዓለማችን ምርጫዎች ከግዙፉ የህንድ የበርካታ ቀናት የህግ አውጭ ምርጫዎች (በዓለም ላይ ትልቁ) እስከ የኢንዶኔዥያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ (የዓለም ትልቁ የአንድ ቀን ምርጫ) እንዲሁም ትን የሰሜን ሜቆዶኒያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንደሚደርስ ተጠቁሟል።
ኢኮኖሚስት ኢንተለጀንስ ዩኒቲ እንደሚለው፤ የ2024 ምርጫ በዓለማችን ሦስተኛ ዲሞክሲያዊ አገር በሆነችው አይስላንድ የሚካሄደውን ነፃና ፍትሃዊ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫም ያካትታል፡፡ ከነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ጋር እምብዛም ትውውቅ በሌለበት ሰሜን ኮሪያም ምርጫ ይደረጋል፡፡
ባንግላዲሽ 2024ን የተቀበለችው ለዓመቱ የመጀመሪያው የሆነውን አብይ ምርጫ በማድረግ ሲሆን፣ በውጤቱም ሼክ ሃሲና ለአራተኛ ተከታታይ የሥልጣን ዘመን በጠ/ሚኒስትርነት ተመርጠዋል፡፡ ችግሩ ግን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ምርጫው ነፃና ፍትሃዊ አይደለም በሚል ቅሬታ ራሳቸውን ማግለላቸው ተዘግቧል፡፡
ራስዋን በምታስተዳድረው የታይዋን ደሴት ደግሞ ባለፈው ጥር 13 ቀን 2024 ዓ.ም ለአገሪቱ ወሳኝ የሆነው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ተካሂዷል፡፡ ደሴቷን በሃይል ወደ ግዛቴ እጠቀልላሁ የሚለው የቻይና መንግስት ማስፈራሪያ በምርጫው ላይ ቁጥር ጥላውን ማጥላቱ አልቀረም፡፡  በምርጫውም የገዢው  ዲሞክራቲክ ተራማጅ ፓርቲ እጩ ሆነው የቀረቡት ላይ ቺንግ ቴቱ አሸንፈዋል፡፡ የእሳቸው ድል ግን ለቻይና አስደሳችና ተወዳጅ አልሆነም። እንደውም በታይዋንና በቻይና መካከል ያለውን ውጥረት እንዳያባብሰው ነው የተፈራው።
በመጪው የካቲት ደግሞ ኢንዶኔዥያ 277 ሚ. ህዝብ ባለቤት የሆነችው አዲስ ፕሬዚዳንት ለመምረጥ ተዘጋጅታለች፡፡ በዚሁ ወር ፓኪስታን የፓርላማ ምርጫ (የህግ አውጪዎች) የምታደርግ ሲሆን በዚህ መሃል ግን የተቃዋሚ መሪና የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ኢምራን ክሃን “የመንግስት ምስጢር አሾልከዋል” በሚል ተከሰው አሁንም በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ እሳቸው ግን ክሱን እንዳልፈፀሙ ይሞግታሉ፡፡
በመጋቢት ወር እንዲሁ ሩሲያውያን ፕሬዚዳንታቸውን ይመርጣሉ፡፡ ታዛቢዎች ግን በሥልጣን ላይ ያሉት ቭላድሚር ፑቲን በእርግጠኝነት እንደሚያሸንፉ ከወዲሁ ተንብየዋል፡፡ ለዚህም ምክንያቱም የምርጫው ሂደትና የመንግስት  መገናኛ ብዙሃን በቁጥጥራቸው ሥር መሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡
“ፑቲን ምንም ዓይነት እውነተኛ ተቃዋሚ ሊኖራቸው አይችልም” የሚሉት የአውሮፓ ተሃድሶ ማዕከል ባልደረባ ኢያን ቦንድ፤ “እሳቸውን የሚደግፍ ድምፅ መሰጠቱን ለማረጋገጥ የሚያስፈልጉት ሁሉም የአስተዳደር ማሽኖች በቁጥጥራቸው ሥር ናቸው፤ እናም ቢያንስ እስከ 2030 ድረስ፣ ሌላ ስድስት ዓመት ፑቲን አብረውን ይዘልቃሉ” ብለዋል፡፡ በዚያ ላይ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ በእስር ቤት ነው የሚገኙት።
የዓለም ትልቋ ዲሞክራሲ በምትባለዋ ህንድ ደግሞ በሚያዚያና ግንቦት ወር የፓርላማ ምርጫዎች ይደረጋሉ፤ ጃናታ በቢሃራቲያ ፓርቲ (BIP)፤ በጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ሥር፡፡ አንጋፋው ህንዳዊ የፖለቲካ ጋዜጠኛ ፑሽ ሳራፍ፤ ተቃዋሚዎች በምርጫው ለማሸነፍ እንደሚታገሉ ያምናል፡፡ ነገር ግን በአንድነት ከቆሙ ነው ይላል፡፡
ህብረት ካልጠፋና በአንድነት ካልታገሉ ግን ጠንካራ አደረጃጀት ያለውን የጠ/ሚኒስትሩን ፓርቲ የማሸነፍ ዕድል አይኖራቸውም-ብሏል (አንጋፋው ጋዜጠኛ)። ሰሜን 2 ቀን 2024 ዓ.ም ደግሞ በሜክሲኮ ፕሬዚንታዊ ምርጫ ይካሄል። ይህም ለአገሪቱ አዲስ ምዕራፍ የሚያበስር ነው ተብሏል፡፡ “ምክንያቱም ለመጀመሪያ ጊዜ ሴት ሜክሲኮን ልትመራ የምትችልበት እድል በመፈጠሩ ነው፡፡” ይላል-የሜክሲኮው የህዝብ አስተያየት ተንታኝ ፓትሪኮ ሞሬሎስ፡፡ የሜክሲኮ ገዢ ፓርቲ የቀድሞዋን የሜክሲኮ ሲቲ ከንቲባ ክላውድያ ሼይባምን በእጩነት መርጧል፡፡
ከግማሽ ቢሊዮን በላይ ህዝብ የሚወክለው የአውሮፓ ህብረትም የፓርላማ ምርጫ በሰኔ ወር እንደሚካሄድ ተጠቁሟል። የህዝብ አስተያየት እንደሚጠቁመው፤ ፈረንሳይን፣ ጀርመንንና ጣሊያንን ጨምሮ በበርካታ አገራት ውስጥ ለቀኝ ክንፍ ህዝበኛ ፓርቲዎች እንደገና ድጋፉ እያደረገ መጥቷል፡፡
“የቀኝ አክራሪ ወገኖች በአውሮፓ ምርጫ ጥሩ ቦታ ይኖራቸዋል፡፡ ይሄ ማለት ግን የአውሮፓን ፓርላማ እስከመምራት ድረስ አይደለም፤ የአውሮፓን ፓርላማ የሚመራ ማንኛውም ሰው ግን እነሱ የሚናገሩትንና የሚሰሩትን ከግምት ውስጥ ማስገባት ይኖርበታል፡፡” ሲሉ በለንደን ኪንግስ ኮሌጅ የዓለማቀፍ ፖለቲካ ፕሮፌሰር የሆኑት አናንድ ሜኖን ለቪኦኤ ተናግረዋል፡፡
ብሪታን በበኩሏ ከ2024 መጨረሻ በፊት ምርጫ ለማካሄድ ዕቅድ ይዛለች፡፡ የተቃዋሚው የሌበር ፓርቲ መሪ ኬይር ስታርመር፣ ለ14 ዓመታት የዘለቀውንና አምስት የተለያዩ ጠ/ሚኒስትሮች የተፈራረቁበትን የኮንሰርቫቲቭ አገዛዝን ከአመራርነት ለመግታት አልመዋል ምርጫውን በማሸነፍ፡፡
“ሁሉን ነገር የብሬክዚት ጦርነት ተቆጣጥሮት ነበር፤ ከዚያ ደግሞ ኮቪድ -19 ወረርሽኝ መጣ፤ አሁን የኑሮ ውድነት ቀውስ ውስጥ ገብተናል፡፡ የመንግስት አለመረጋጋት አጋጥሞና …. አለመረጋጋት ራሱ የፖለቲካ ጉዳይ ሆኗል” ብለዋል፤ ፕሮፌሰር ሜኖን፡፡
አሜሪካ ደግሞ በህዳር 2024 ዓ.ም በእጅጉ የሚጠበቀውንና በውዝግብ የተሞላውን ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ታካሂዳች፡፡ አሜሪካውያን ፕሬዚዳንታቸውን ከዲሞክራቱ ጆ ባይደን ወይም ከሪፐብሊካኑ ዶናድ ትራምፕ አንዱን እንደሚመርጡ ይጠበቃል፡፡ የጆ-ባይደን አስተዳደር ግን እስከ ምርጫው የሚያደርሰው አይመስልም። የብዙዎቹ ስጋትና ቀድሞወን ፕሬዚዳንት እስር ቤት በመወርወር ከምርጫው እንዳያስወጡት ነው። ሂደቱን ደግሞ ጀምረውታል። የፖለቲካ ተንታኞች ዓመቱ የምርጫ የመሆኑን ያህል ዲሞክራሲም የሚፈተንበት ነው የሚሉት ወደው አይደለም።
በ2024 የሚካሄዱ ምርጫዎች፣ ምርጫ በሚያካሂዱ አገራት ብቻ ሳይሆን ምርጫ በማያካሂዱም አገራት ላይ ተፅዕኖ ሊያሳድሩ እንደሚችሉ ሜኖን ይናገራሉ፡፡
“አዎ፤ ሁሉም ፖለቲካ አካባቢያዊ ነው፤ ነገር ግን ዓለማቀፋዊ አዝማሚያዎችም አሉ፡፡ ለምሳሌ የስደተኞች ጉዳይ (ኢሚግሬሽን) በዓለም ላይ በሚደረጉ በርካታ ምርጫዎች ላይ በብዛት ይገለጣል፡፡ በአውሮፓ ምርጫ ይገለፃል፤ በብሪታንያ ምርጫም ይገለጣል” ብለዋል፤ ሜሞን በሰጡት ፖለቲካዊ ትንተና፡፡
“እውን ዴሞክራሲ በአደጋ ላይ ነው?!”
ምንም እንኳን በ2024 በመላው ዓለም በ64 አገራት ምርጫ ቢካሄድም፤ ዲሞክራሲም የሚፈተንበት ዓመት ነው ይላሉ የፖለቲካ ተንታኞች፡፡ የዴሞክራሲ መገለጫ የሆነው ምርጫ በሚካሄድበት በዚህ ዓመት “ዴሞክራሲ በአደጋ ላይ ነው” የሚለው አነጋገር ተቃርኖ ግን አይደለም። ዓመቱን በምርጫ የጀመረችው ባንግላዲሽ፤ ጠ/ሚኒስትሯን ለ4ኛ ጊዜ የመረጠችው ተቃዋሚ ፓርቲዎች ራሳቸውን ከምርጫ ባገለሉበት ሁኔታ ነው ከምርጫው ቀደም ብላ የተቃዋሚ አባላትን፡፡
ሌላው ቀርቶ በዴሞክራሲ ብዙም የማትታማውና ለቀረው ዓለም አርአያ የነበረችው አሜሪካ፣ በዘንድሮ ምርጫ “ዴሞክራሲ በአደጋ ላይ ነው” እያለች ነው፡፡ የዴሞክራቱ እጩ ጆን ባይደንና የሪፐብሊኩ ዶናድ ትራምፕ እርስ በእርስ “የዴሞክራሲ ስጋት” በሚል እየተወራረፉ ነው፡፡ ሰሞኑን ፕሬዚዳንት ባይደን በምርጫ ቅስቀሳ ላይ “Democracy is on the ballot” ሲሉ ለደጋፊዎቻቸው ተናግረዋል፡፡ የኖቤል የሰላም ተሸላሚና የምርምር ጋዜጠኛ ማሪያ ሬሳ በቅርቡ እንደተናገሩት፤ “ዲሞክራሲ መኖሩን ወይም መሞቱን በ2024 መገባደጃ ላይ እናውቃለን፡፡”


Page 9 of 695