Administrator

Administrator

  በመላው አሜሪካ ያሉ ተማሪዎች ባርነት በ19ኛው ክፍለ ዘመን የተወገደ ችግር መሆኑን ይማራሉ፡፡ ይሁንና በሚያሳዝን መልኩ፣ ከ150 ዓመታት በኋላ ዛሬም ችግሩ ሥር እንደሰደደ መሆኑን እንረዳለን፡፡ በእርግጥ ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውር በሚል ስሙንና መልኩን የቀየረ ቢሆንም፤ በአሜሪካና በመላው ዓለም አስከፊና የሰው ልጆችን መሠረታዊ ክብር የሚያዋርድ ወንጀል ሆኗል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ ጃንዋሪ 2015 ብሔራዊ የባርነትና የህገወጥ የሰዎች ዝውውር የሚወገዝበት ወር እንዲሆን አውጀዋል፡፡ አሜሪካ ህገ ወጥ አዘዋዋሪዎችን ለህግ የምታቀርብ ሲሆን፤ የችግሩ ሰለባዎችንም ከችግሩ እንዲያገግሙና መልሰው እንዲቋቋሙ ትረዳለች፡፡ ከዚህም በተጨማሪ መንግሥታችን የጤና ባለሙያዎች፣ የበረራ ሠራተኞችና ሌሎች በግሉ ዘርፍ የተሠማሩ ባለሙያዎች የህገወጥ ዝውውር ሰለባዎችን በተሻለ መልኩ መለየትና መርዳት የሚችሉበትን ሥርዓት ዘርግቷል፡፡
አሜሪካ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ አጋሮችና የሃይማኖት ተቋማት ጋር በመሥራት ህገወጥ የሰዎች ዝውውርን በማስወገድ ዙሪያ የሚደረጉ ጥረቶችን ትደግፋለች፡፡ በዚህ ረገድ የህገ ወጥ ዝውውር ሰለባዎችን ለመጠበቅ፣ ወንጀሉን ለመከላከልና አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ አዳዲስ አሠራሮችን በመደገፍና ተጎጂዎችን አቋቁሞ ራሳቸውን እንዲችሉ በማድረግ ዙሪያ ከእነዚህ አጋር ድርጅቶች ጋር እንሠራለን፡፡
ዘመናዊ ባርነት በዓለማችን ላይ በየትኛውም ሥፍራ ሊከሰት የሚችል በመሆኑ መንግሥታት፣ የንግድ ድርጅቶችና ደንበኞቻቸው ችግሩን የመከላከል የጋራ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ ዓለም አቀፉ የሥራ ድርጅት (ILO) ከ20 ሚሊዮን በላይ ሰዎችን በማሠማራት፣ ህገወጦች 150 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ህገ ወጥ አሠራር ትርፍ እንደሚያገኙ በሪፖርቱ አመልክቷል፡፡  
ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውርን በአቅርቦት ሰንሰለት ላይ መግታት የሸማቾችንም የነቃ ተሳትፎና የግሉን ዘርፍ መሪዎች አጋርነት የሚጠይቅ ነው፡፡ ፕሬዚዳንት ኦባማ፡-“እያንዳንዱ ዜጋ ችግሩን በማጋለጥና የሚለብሰው ልብስ፣ የሚበላው ምግብና ማናቸውም ለሽያጭ የሚቀርቡለት ሸቀጦች ከጉልበት ብዝበዛ በፀዳ መንገድ መመረታቸውን ማረጋገጥ ይችላል” ሲሉ አሳስበዋል፡፡ የንግድና ለትርፍ ያልተቋቋሙ ድርጅቶች መሪዎችም የአቅርቦት ሰንሰለቶቻቸው ከጉልበት ብዝበዛ መፅዳታቸውን በማረጋገጥ ባርነትንና ግዞትን መከላከል እንደሚችሉም ጠቁመዋል፡፡
የአሜሪካ መንግሥት ህገወጥ የሰዎች ዝውውርን በአሜሪካም ሆነ በዓለም ዙሪያ ከምንጩ ለማድረቅ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ በኢትዮጵያም የአሜሪካ መንግሥት፣ ከወርልድ ቪዥንና ከሜኖናይት የኢኮኖሚ ዕድገት አጋሮች ጋር በመተባበር “የህፃናት ጉልበት ብዝበዛን ለመዋጋት የተቀናጁ ኢትዮጵያውያን” በተሰኘ ፕሮጀክት በኩል ለጉልበት ብዝበዛና ለህገ ወጥ ዝውውር ተጋላጭ የሆኑ ወጣቶች ሰፋ ያለ የትምህርት ዕድል እንዲያገኙ በማስቻል ከፍተኛ እንቅስቃሴ አድርጓል፡፡ በተጨማሪም ፕሮጀክቱ ለህገ ወጥ ዝውውር ሊጋለጡ ይችላሉ ለተባሉ ህፃናት ቤተሰቦችም ድጋፍ ያደርጋል፡፡ ከአንድ ወር በፊት ከሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳዮች ሚኒስትር ክቡር አቶ አብዱልፋታህ አብዱላሂ ሐሰን ጋር በመሆን ወደ ደቡብ ኢትዮጵያ በተጓዝኩበት ወቅት ፕሮጀክቱ ህገ ወጥ ዝውውርን ከመዋጋት አኳያ እያበረከተ ያለውን ከፍተኛ አስተዋፅዖ ለማወቅ ችያለሁ፡፡ ባየሁትም አኩሪ ሥራ የተደነቅሁ ሲሆን፤ኢትዮጵያና አሜሪካ አስከፊ የሆነውን የህፃናት ጉልበት ብዝበዛን በጋራ በመዋጋት ያሳዩት ቁርጠኝነት በአርአያነት የሚጠቀስ እንደሆነም ተረድቻለሁ፡፡
በሌላም በኩል የአሜሪካ መንግሥት የህገወጥ ዝውውርን ችግር ከምንጩ ለማድረቅ ከዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት(IOM) ጋር በመተባበር “የማህበረሰብ ውይይት” የተሰኘ ፕሮግራም ያዘጋጃል፡፡ ፕሮግራሙ በኢትዮጵያ በታችኛው የማህበረሰብ ክፍል ህገ ወጥ ዝውውርን በመከላከል ላይ ያተኮረ ፕሮጀክት በማካሄድ ላይ ይገኛል፡፡ ይህ የማህበረሰብ ውይይት ፕሮግራም እያንዳንዱ ማህበረሰብ አባላቱና ነዋሪዎች ለችግሩ እንዳይጋለጡ በማስተማር የህገወጥ ዝውውር ሰለባዎች እንዳይሆኑ ያስችላቸዋል፡፡ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውርና ዘመናዊ ባርነት በአሜሪካና ኢትዮጵያን ጨምሮ በዓለም ዙሪያ በሚገኙ አጋር ሀገራት የተንሰራፋና ከፍተኛ ተፅዕኖ በማሳደር ላይ ያለ ችግር ሆኗል፡፡ ይሁንና ቀጣይነት ባላቸው የተቀናጁ ጥረቶች ህገወጥ አዘዋዋሪዎችን በመዋጋት ብቻ ሳይሆን ችግሩንም ከምንጩ በማድረቅ ተጨባጭነት ያለው ለውጥ ማምጣት እንደምንችል እንተማመናለን፡፡

አንድ አፈ-ታሪክ እንዲህ ይላል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ውብ ልዕልት ነበረች አሉ - ሁሉም የሚያደንቃት ናት፡፡ ግን ማንም ላግባሽ ያላት የለም፡፡ ንጉሡ አባቷ ተስፋ በመቁረጥ አፖሎ የተባለው አምላክ ዘንድ ሄደና አማከረው፡፡ አፖሎም፤ ሳይክ (Psyche) ልዕልቲቱ ወደ ተራራ መውጣት አለባት፡፡ የሐዘን ልብስም ትልበስ፡፡ እዚያም ብቻዋን ትተው፡፡ ቀኑ ከመንጋቱ በፊት አንድ እባብ ይመጣል፡፡ ያገኛታል፡፡ ያገባታልም፡፡”
ንጉሱ ታዘዘው፡፡ ሌሊቱን ሙሉ ልዕልቲቱ ባሏን ልታይ ስትጠብቅ ቆየች፡፡
የሞት ያህል በሚያስፈራ ሁኔታ ውስጥ በአሰቃቂ ቅዝቃዜ በድና መጠበቋን ቀጠለች! በመጨረሻ እንቅልፍ ወሰዳት፡፡
ስትነቃ በአንዳች ቆንጆ ቤተ መንግስት ውስጥ ንግሥት ሆና ራሷን አገኘች! በየማታው ባሏ ይመጣል፡፡ ኢሮስ ይባላል፡፡ ይገናኛታል (ፍቅር ይሰራሉ)፡፡ ግን አንድ ቃል ኪዳን አስገብቷታል፡- “ሳይክ፤ የምትፈልጊውን ሁሉ አደርግልሻለሁ፡፡ ግን ፊቴን መልኬን አታይም፡፡ ሳታይኝ ሙሉ በሙሉ ልታምኚኝ! ይገባል፡፡” ወጣቷ ያላትን ፈፅማ ለረዥም ጊዜ በደስታ ኖረች፡፡
ምቾት አላት፡፡ መወደድ አላት፡፡ ደስተኛ ናት፡፡ በየማታው ከሚጎበኛት ሰው ጋር ፍቅር ይዟታል! ግን አንዳንዴ ከእባብ ጋር የተጋባች የተጋባች ይመስላታል! አንድ ጧት ማለዳ ላይ፤ ባሏ ተኝቶ ሳለ ፋኖሱን ለኮሰችና ባሏን ኢሮስን መልኩን አየችው፡፡ ወደር የሌለው ቁንጅና ያለው ወንድ ነው፡፡ ከጎና ተኝቷል፡፡ የፋኖሱ ብርሃን ቀሰቀሰው፡፡
ያፈቀራት ሴት፤ አንድዬ አደራውን አለማክበሯን አይቶ ኢሮስ ላንዴም ለሁሌም ተሰወረ፡፡ ልዕልቲቱ ባለ በሌለ ኃይሏ ፍቅረኛዋን ዳግም ለመመለስ ስትፍረመረም አፍሮዳይት የተባለች የባሏን እናት አግኝታ ጥፋቷን አምና ለመነቻት፡፡ ከእንግዲህ ብዙ ልትፈፅማቸው የሚገቡ ነገሮች እንዳሉ አውቃ፣ ተቀብላ ልትኖር ቃል ገባች፡፡
ምራቷ ግን በልዕልት ውበት ቅናት ይዟት ኖሮ፤ የሁለቱን ፍቅረኞች ዳግም መገናኘት ለመቀልበስ/ ለማነቀፍ ያልፈነቀለችው ድንጋይ አልነበረም፡፡ ልዕልት ሳይክ፤ በተቀበለችው የቤት ስራ መሰረት አንድ ሳጥን ከፈተች፡፡ ለካ ያ ሳጥን ከባድ እንቅልፍ የሚያስወስድ አስማታዊ ሚስጥር ኖሮታል፡፡ ድብን አድርጎ እንቅልፍ ወሰዳት፡፡
መቼም ሳይደግስ አይጣላምና ኢሮስ ደግሞ ከባድ ፍቅር ይዞት ኖሮ እጅግ አድርጐ ተፀፅቷል፡፡ እንደምንም ብሎ ወደ ቤተመንግስቱ ህንፃ ገብቶ ሚስቱን በቀስቱ ጫፍ ጭሮ ቀሰቀሳት፡፡ “በማወቅ ጉጉትሽ ምክንያት ሞት አፋፍ ደርሰሽ ተመለስሽ” አላት፡፡ ዕውቀት ስር መጠለል ሽተሽ ግንኙነታችንን ገሥሠሽ አጠፋሽ! ቃልኪዳንሽን ሰበርሽ! ሆኖም በፍቅር ዓለም ምንም ነገር ለዘለዓለም አይጠፋም፡፡
ባልና ሚስቱ በዚህ ዕምነት ተይዘው/ተጠርንፈው ወደ ዚዑስ ሄዱ፡፡ ፍቅራቸው ከእንግዲህ እንዳይጠፋ ለመኑ፡፡ ዚዑስ ከብዙ ክርክርና ሙግት በኋላ የአፍሮዳይትን ምክር አገኘ፡፡ ከዚያን ቀን ወዲህ ሳይክ (የአንጎላችን አላዋቂ (unconscious) ግን አመክኖአዊ ወገን) እና ኢሮስ (ፍቅር) በደስታና በተድላ ለዘለዓለም ኖሩ!”
በዚህ ታሪክ መሰረት፤ “ይህንን የማይቀበሉና አስማታዊና ሚስጥራዊ ለሆነው የሰው - ልጅ ግንኙነት ማብራሪያ ለማግኘት የሚሹ ሁሉ፤ እንደሳይክ የህይወትን ምርጥ ክፍል ያጣሉ!” የሚባለው ለዚህ ነው፡፡
ሳይክ፤ በሆዷ እንዲህ አለች፡-
“አንድ ቀን ቤተ መንግሥት ውስጥ እነቃለሁ! የምፈልገው አንድ ነገር፤ ጊዜ ብቻ ነው!”
*          *          *
በዓለማዊው ህይወታችን ሳያዩ ማመን ከባድ ነው፡፡ ባሌ እባብ ሊሆን ይችላል ብሎ መኖርም ከባድ ነው! እርግጥ፤ “አንድ ቀን ቤተ መንግሥት ውስጥ እነቃለሁ” ብሎ ማሰብ ይቻላል፡፡ ግን ድካም አለበት፡፡ በቀስት ተጭሮ እንደመንቃት ቀላል አይደለም፡፡ ቃልኪዳንን መጠበቁን ይጠይቃል፡፡ ለማወቅ ጉጉት ለከት ማበጀትም ይፈታተናል፡፡ በልጦ መገኘትን ጠንቅቆ መቻል እንደው ያለጥረት የሚገኝ፣ ክብሪት እንደመጫርም የቀለለ፣ የዘፈቀደ ነገር አይደለም፡፡ በሀገራችን ተፎካካሪን በልጦ መገኘት እጅግ አዳጋች፣ የቋጥኛማ ተራራ ያህል የማይዘለቅ ችግር ሆኖ ከቆየ ሰነባብቷል፡፡ አንድ ፀሃፊ እንዳለው፤ “እያንዳንዱ ሰው ትንሽ ትንሽ ዘውድ በኪሱ ይዞ ስለሚዞር “ውይይቱም፣ ድርድሩም፣ ፉክክሩም ሌላውን በማጥፋት ወይም በመጥለፍ ላይ የተመሰረተ ይሆንና ጤናማ ጉዞ አይሆንም፡፡ ጥንትም እንደዚያው ነበር፤ አሁንም ቅኝቱን አልቀየረም፡፡ በዚህ ቅኝት ላይ የመከፋፈል ዜማ ሲጨመርበት ለባላንጣ ሲሳይ የመሆን አባዜ ይከተላል፡፡ ማ ለምን ይህን አደረገ? ምን እየተጠቀመብኝ ነው? ብሎ ማሰብ ያባት ነው!
ተፈጥሮውን ማሳየት የሚበጀው / የሚያዋጣው አንዳንዴ ብቻ ነው፡፡ ከተቻለ ቃናውን ዝቅ ማድረግ መማር አለብህ… ስትጀምር ብዙ ሳትጮህ መጀመር ነው፤ አዋጪው፡፡ የውድድር ዘዴ! “ከጥበብ ሁሉ ከባዱ ደደብነትህን መቼ እንደምትጠቀምበት ማወቅ ነው!” ይላሉ አዋቂ ፀሀፍት፡፡ ብዙ ከመንጫጫት፣ ሰብሰብ ብሎ የማሰብ፣ የማስተዋል ክህሎት ሊኖር ይገባል፡፡ ከተመክሮ ሁሉ ጥንቃቄን የሚፈልግ ተመክሮ የትግል ተመክሮ ነው፡፡ አምስት ዓመት ሙሉ ጊዜ ኖሮ በቂ ዝግጅት ማጣት አንድም ንዝህላልነት፣ አንድም አቅለ-ቢስ መሆን ነው ከማለት በስተቀር ምን ትርጓሜ ይኖረዋል? ራስን ለክፍፍል ማጋለጥ፣ የራስን ችግር ራስ አለመፍታት፣ የተፎካካሪን ስልትና ስትራቴጂ አለማስላት፣ የህዝብንና የሀገርን ፍላጐት አለማስቀደም፣ የመንገዶችን ኮረኮንችና ሊሾነት አለመለየት አባዜዎች ሁሌ እንደተፈታተኑን አሉ፡፡ ጠንካራነትን ብቻ ሳይሆን ደካማነትንም መገንዘብ ብልህነት ነው፡፡
”ደካማ ከሆንክ በማታሸንፈው ጦርነት ውስጥ ለክብርህ ብለህ አትዋጋ፡፡ ይልቁንም ማፈግፈግን እወቅ፡፡ ማፈግፈግ ጊዜ መግዛት ነው፡፡ ማገገሚያ ነው፡፡ ቁስልህን ማከሚያና ባላንጣህን ማዳከሚያ ነው፡፡ ቁልፉ ነገር ማፈግፈግን የኅይል ማፍሪያ መሳሪያ ማድረጉ ነው!”
ጉዞን በረዥሙ ማቀድ ሌላው የብልህነት ስልት ነው፡፡ “ዛሬ ካልተሳካ ሞቼ እገኛለሁ” ማለት ቢያንስ የዋህነት ነው! አጓጉል ፍዘትም ስስ ብልት መስጠት ነው፡፡ ፖለቲካ ማመዛዘንን፣ ጊዜ-መግዛትንና ፍጥነትን መሰረት የሚያደርግ “ሸቃባ ሚዛን” ነው ይባላል፡፡ ይሄን ልብ ማለት ግድ ነው፡፡ “ታሪክ ባሸናፊዎች የሚፃፍ ተረት ነው!” የሚባለውንም አለመርሳት ነው፡፡
ታዲያ ፀጋዬ ገ/መድህን በሼክስፒሩ ሐምሌት እንደሚለን፡-
“…ፈጥነህ ጠብ ውስጥ አትስጠም
አንዴ ከገባህበት ግን እጅህ ከባላንጣህ ይቅደም”
የሚለውን ሳንዘነጋ ነው፡፡ ሁሉም መስዋእትነት ይጠይቃል፡፡ መስዋእትነት እንደ ዴሞክራሲ ሁሉ ገጠመኝ አይደለም፡፡ ቀድመው መሰረትና እሳቤ የሚያበጁለት ነው፡፡
“አንተኛም ካላችሁ እንገንድሰው
መኝታ እንደሆነ ቀርቷል ካንድ ሰው!” እያልን የምናላዝንበትም ከቶ አይደለም፡፡ ሂደት ነው፡፡ መቀጠል አለበት፡፡ ዝምታ እንኳ መስዋእትነት የሚጠይቅበት ጊዜ አለ፡፡ ትግል በጥበብ የተሞላ መንገድ ነው! ካልበሰሉ በድፍረት ብቻ የሚወጡት የወጣት ስሜታዊነት ዘመቻ መሆኑ ቀርቷል፡፡ እንደ ፋሽን በወረት የሚያሸበርቁበት የገና ዛፍም አይደለም፡፡ ከጀመሩ በኋላ “ፉርሽ ባትሉኝ!” የሚባልበት ጨዋታም አይደለም! “ሰይ ብል ባንከረባብት” እያሉ ያሹትን የሚያጭዱበት ቁማርም መሆን የለበትም! “አርፋ ስጠኝ”፣ “አቫንስ ስጠኝ” እያሉ የሚጠባበቁበት አይደለም፡፡ ትግል መሰረቱ የፖለቲካ ክህሎት ነው፡፡ ያልተነገረ ያልተሰማ ነገር የለም፡፡ ከአንጃ እስከ ዋና መስመር፣ ከቀኝና ግራ መንገደኛ እስከ አምስተኛ-ረድፈኛ፣ ከውጪ ወራሪ እስከ ውስጥ ቦርቧሪ፣ ከአናርኪስት እስከ ዘውድ-ናፋቂ፣ ከገንጣይ-አስገንጣይ እስከ በታኝ-ከፋፋይ፣ ከጠባብ እስከ ትምክህተኛ፣ ከአኢወማ እስከ ሊግ፣ ከአንጋፋው ፎረም እስከ ብላቴናው ፎረም…” ስርዝ የኔ ድልዝ ያንተ፣ እመጫት የሷ፣ ሆያ-ሆዬ የሰፊው ህዝብ ስንባባል በኖርንበት አገር ትግል “ሁለት አንድ ዐይናዎች ተጋብተው ሁለት ዐይን ያለው ልጅ ወለዱ፡፡ ምነው ቢሉ፣ አንዱን ከእናቱ አንዱን ከአባቱ!” ብለው የሚገላገሉት አይደለም!? “ዋና የማይችል ባህር አይግባ፤ ትግል የማይችል ልፊያ አይውደድ” የሚባለው ተወዶ አይደለም፡፡ እሙናዊውን ዓለም እናጢን! ሁሌ ልጅ አንሁት - ልብ-እንግዛ!!


መንግስት መሰረተቢስ ውንጀላ ነው በሚል ያጣጥለዋል
የኢትዮጵያ መንግስት በአገሪቱ የግል ሚዲያ ላይ የሚያደርገው የተራቀቀ ጫና፣ ሚዲያዎቹ በመጪው ግንቦት ወር የሚካሄደውን ምርጫ በተመለከተ በሚሰሩት ዘገባ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ ምህዳሩን እያጠበበባቸው ነው ሲል ሂዩማን ራይትስ ዎች ገለጸ፡፡
መንግስት የግሉን ሚዲያ እንደ አንድ የታመነ የመረጃና የትንተና ምንጭ ሳይሆን እንደ ስጋት በመቁጠር የተጠና ጫና ያደርስበታል ያሉት የሂውማን ራይት ዎች የአፍሪካ ምክትል ዳይሬክተር ሌስሊ ሌፍኮው ሚዲያው በመጪው ምርጫ ቁልፍ ሚና መጫወት ቢኖርበትም፣ በአንጻሩ ግን በርካታ የአገሪቱ ጋዜጠኞች ምርጫን በተመለከተ በሚያቀርቡት ዘገባ ለእስር እንዳረጋለን የሚል ስጋት እንዳደረባቸው ገልጸዋል፡፡
መንግስት በአገሪቱ የግል ሚዲያ ላይ የሚያደርገው ጫና እየተባባሰ በመምጣቱ ባለፈው አመት ብቻ ስድስት የግል የህትመት ውጤቶች ተዘግተዋል፤ በ22 ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮችና አሳታሚዎች ላይ የወንጀል ክስ ተመስርቶባቸዋል፤ ከ30 በላይ ጋዜጠኞችም እስራትን በመፍራት አገራቸውን ጥለው ተሰደዋል ብሏል ሂዩማን ራይትስ ዎች ከትናንት በስቲያ ባወጣው ሪፖርት፡፡
“ጋዜጠኝነት ወንጀል አይደለም፣ የመገናኛ ብዙሃን ነጻነት ጥሰት በኢትዮጵያ” የሚል ርዕስ ያለው  ሪፖርቱ፣ የኢትዮጵያ መንግስት ላለፉት አራት አመታት ነጻ ዘገባን የሚያቀጭጩ ተግባራትን ሲፈጽም እንደቆየ ጠቅሶ፣ በእነዚህ አመታትም ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብታቸውን በመጠቀማቸው 19 ጋዜጠኞች መታሰራቸውንና 60 ያህሉም መሰደዳቸውን ገልጿል፡፡
ሂውማን ራይትስ ዎች በስደትና በአገራቸው የሚገኙ ከ70 በላይ ጋዜጠኞችን አነጋግሬ ያዘጋጀሁት ነው ባለው በዚህ ሪፖርቱ፣ በአገሪቱ አብዛኞቹ የህትመትና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች በመንግስት ቁጥጥር ስር እንደሚገኙ ጠቁሞ፣ ጥቂት የግል የህትመት ውጤቶችም እንዳይዘጉ በመስጋት ፖለቲካዊ ጉዳዮችን ሲዘግቡ በአብዛኛው በራሳቸው ላይ ሳንሱር እንደሚያደርጉ ጠቁሟል፡፡መንግስት በበኩሉ፤ ሂዩማን ራይትስ ዎች የሚያወጣቸው የነፃነትና መብት ጥሰትን የተመለከተ ሪፖርቶች መሰረተ ቢስ እንደሆነ በመግለፅ በተደጋጋሚ ማጣጣሉ ይታወቃል፡፡

           በኢትዮጵያ ተግባራዊ በመደረግ ላይ የሚገኙት የታክስ ፖሊሲዎችና ህጎች ከወቅታዊ አለማቀፍና አገራዊ ሁኔታዎች ጋር ተገናዝበው መሻሻል እንደሚገባቸው የፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ (የማህበራዊ ጥናት መድረክ) ጥናት  አመለከተ፡፡በመድረኩ አዘጋጅነት “የኢትዮጵያ የታክስ ፖሊሲና ህጐች ቅኝት” በሚል ርዕስ መድረኩ ያቀረበው ጥናታዊ ፅሁፍ እንደጠቆመው፤ የአገሪቱ የገቢ ግብርና የቫት ህጎች ከአስር አመት በላይ ያስቆጠሩ ቢሆኑም ጉልህ የማሻሻያ ለውጥ አልተደረገባቸውም፡፡ ከወር ደሞዝ ታክስ የማይከፈልበት 150 ብር ወይም ከአመት ገቢ 1800 ብር እንዲሆን ከአመታት በፊት የወጣው ህግ ከብር የመግዛት አቅም መሸርሸርና ከዋጋ ንረት ጋር ተያይዞ ከመጡ ለውጦች ጋር ተገናዝቦ አልተሻሻለም፡፡ አላግባብ ከፍተኛ የታክስ ክፍያ የተጣለባቸው ድርጅቶች ጉዳያቸው እንዲመረመር አቤቱታ ማቅረብ ከፈለጉ፣ በቅድሚያ ግማሽ ያህሉን ክፍያ እንዲፈፅሙ እንደሚገደዱና ለአቤቱታቸው ምላሽ ለማግኘት ረጅም ጊዜ እንደሚንገላቱ የጠቆመው ጥናቱ፤ ብዙውን ጊዜም የሚያገኙት ውሳኔ ፍትሀዊ  እንዳልሆነ ይነገራል ብሏል፡፡ የታክስ ኦዲትን አስመልክቶም የታክስ ኦዲት የሚደረገው ከ4 እና ከ5 አመት በኋላ ስለሆነ የተጠራቀመ የታክስ እዳ እንዲከፍሉ የሚወሰንባቸው ድርጅቶች ከፍተኛ ወለድም ጭምር እንደሚጫንባቸው ጥናቱ ገልጿል፡፡የንግድ ድርጅቶች የ‹‹ሀ›› ምድብ፣ የ‹‹ለ›› ምድብ በሚል የሚፈረጁበት አመታዊ የሽያጭ ገቢ  በዋጋ ንረት ሳቢያ የብር የመግዛት አቅም ተሸርሽሮ ሽያጫቸው ላይ ጭማሪ ቢያሳይም ህጉ ግን እንዳልተሻሻለም በጥናቱ ተጠቅሷል፡፡የ‹‹ሐ›› ምድብ ተብለው በሚፈረጁትና አመታዊ ሽያጫቸው እስከ 100 ሺህ ብር  በሆኑ ድርጅቶች ላይ የሚደረገው የታክስ ክፍያ አወሳሰንም ውስብስብና በግምት ላይ የተመሰረተ ነው ብሏል፡፡
ብዛት ያላቸው መመሪያዎች በስራ ላይ መዋላቸው በታክስ ከፋዩና አንዳንድ ጊዜም በግብር ሰብሳቢ መስሪያ ቤቱ ባለሙያዎች ግራ አጋቢ እንደሚሆኑ ያመለከተው ጥናቱ፤ በተለያዩ የግብር መሰብሰቢያ ቢሮዎች ወጥ የሆነ መረጃ ያለመኖር እንዲሁም  ባለሙያዎችም መረጃዎቹን የሚረዱበት አግባብ ወጥ አለመሆኑ እንዲሁም በህጉ ላይ የተቀመጠውና በተግባር የሚታየው የተለያዩ መሆናቸው እንደችግር ተጠቅሰዋል፡፡ጥናቱ በታክስ ፖሊሲና ህጎች ዙሪያ መሻሻል ያለባቸውን ነገሮች ያስቀመጠ ሲሆን በአጠቃላይ ግን በአገር ውስጥና በአለም አቀፍ ደረጃ ያሉ ለውጦችን ግምት ውስጥ ማስገባት እንደሚኖርበት ተጠቁሟል፡፡
 “ፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ” (የማህበራዊ ጥናት መድረክ) በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ጥናትና ምርምር እንዲሁም ሕዝባዊ ውይይቶችን የሚያካሂድ መንግስታዊ ያልሆነ አገር በቀል ድርጅት ነው፡፡

ተደጋጋሚ የቅጥር ማስታወቂያ ባወጣም ሠራተኛ ማግኘት አልቻልኩም ብሏል
በአመራር ደረጃ ላይ ያሉ ሠራተኞች የአመለካከትና የአቅም ችግር እንዳለባቸውም ገልጿል

   የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በያዝነው አመት ካጋጠሙት ችግሮች ሁሉ እጅግ የከፋው በርካታ ሠራተኞች በየጊዜው ከሥራ መልቀቃቸው መሆኑንን በመጠቆም ይህም በሚፈልገው መጠን ለመሥራት እንዳይችል እንቅፋት እንደሆነበት ተገለፀ፡፡ የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል፤ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከትናንት በስቲያ ባቀረቡት የስድስት ወራት እቅድ አፈፃፀም ሪፖርት ላይ እንደገለፁት፤ በበጀት ዓመቱ የተለያዩ ችግሮች የገጠሙአቸው ቢሆንም በጐላ መልኩ የሚጠቀሰው ግን በርካታ ሠራተኞች በየጊዜው መልቀቃቸው እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ ከሥራቸው በለቀቁ ሠራተኞች ምትክ ለመቅጠርና ክፍት የሥራ ቦታዎች ለማሟላት የቅጥር ማስታወቂያ በተደጋጋሚ ቢወጣም በሚፈለገው መጠንና ጊዜ የሰው ኃይል ከገበያው ለማግኘት አለመቻሉን ገልፀዋል፡፡ ችግሩን ለመቅረፍ ከፍተኛ ጥረት በመደረግ ላይ መሆኑን የገለፁት ሚኒስትሩ፤ ተደጋጋሚ የሥራ ማስታወቂያዎችን ማውጣትና ያሉት ሰራተኞች በተቻለ መጠን ስራዎችን በማካካስ እንዲሰሩ ማድረግ እየተወሰዱ ካሉት እርምጃዎች ተጠቃሽ እንደሆኑም ገልፀዋል፡፡ የሥራ ተቋራጮች
በውላችን መሰረት የግንባታውን ሥራ በተቀመጠው ጊዜ ያለማስኬድ ችግር አለባቸው ያሉት ሚኒስትሩ፤ የስራ ተቋራጮቹ በገቡት ውል መሰረት ስራዎቹን እንዲያከናውኑ ኃላፊነት እንዳለባቸው የማስገንዘብ ስራ እየሰሩ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡ ሚኒስቴር መ/ቤቱ በዋናነት ከኮንስትራክሽን ፕሮጀክቶች አፈፃፀም መጓተት ጋር በተያያዘ የተመደበለትን በጀት በተሟላ መልኩ መጠቀም አለመቻሉን ሚኒስትሩ በሪፖርታቸው ላይ ገልፀዋል፡፡

“የስዕል ስራዎቿን ለእይታ በማብቃታችን ኩራት ይሰማናል”
                           - የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ
 
ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ ሰዓሊ ጁሊ ምህረቱ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በአለማቀፍ ደረጃ የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ የስነ-ጥበባት ባለሙያዎች በየአመቱ የሚሰጠውን የ2015 የስነ-ጥበባት ሜዳሊያን ተቀበለች፡፡ኢትዮ- አሜሪካዊቷ ሰዓሊ ጁሊ ምህረቱ በአለማቀፍ ደረጃ እውቅና በተሰጠው የስነ-ጥበብ ስራዋ እና ባህላዊ ዲፕሎማሲን በማጠናከር ረገድ በፈጠረችው ተጽዕኖ ለዚህ ሽልማት መብቃቷን የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቱ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡የመስሪያ ቤቱ ቃል አቀባይ ለአርት ኒውስ ድረገጽ እንደተናገሩት፣ ሰዓሊዋ በሙያዋ ላሳየችው ጉልህ ቁርጠኝነት እንዲሁም አርት ኢን ኢምባሲስ በተሰኘው ፕሮግራምና በአለማቀፍ የባህል ልውውጥ መስክ ላበረከተችው አስተዋጽኦ እውቅና ለመስጠት፣ የዘንድሮውን ሽልማት ከተቀበሉት 7 ሰዓሊያን አንዷ ተደርጋ ተመርጣለች፡፡እ.ኤ.አ በ1970 በአዲስ አበባ የተወለደችው ሰዓሊ ጁሊ ምህረቱ፤ በተለያዩ የውጭ አገር ዩኒቨርሲቲዎች የስነጥበባት ትምህርቶችን የተከታተለች ሲሆን፣ በአለማቀፍ ደረጃ በተዘጋጁ በርካታ የግልና የጋራ የስዕል አውደ ርዕዮች ላይ ስራዎቿን ለእይታ በማብቃትና የታላላቅ ሽልማቶች አሸናፊ በመሆን ትታወቃለች፡፡ በአሁኑ ሰዓትም ነዋሪነቷ በአሜሪካ ኒውዮርክ ነው፡፡የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጆን ኬሪ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ የጁሊ ምህረቱን ስዕሎች በተመለከተ በሰጡት አስተያየት፣ በተለያዩ አገራት በሚገኙ ኤምባሲዎቻችን ለእይታ ያበቃናቸው የጁሊ ስዕሎች እጅግ ማራኪ ናቸው፣ በስራዎቿ ኩራት ይሰማናል ብለዋል፡፡ ላበረከተችው አስተዋጽኦም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

•    በኢትዮጵያ ቅርንጫፍ ስትተዳደር ቆይታለች
ከሀያኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ አንስቶ የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን አካል የነበረችው የኤርትራ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሰሞኑን  በራሷ እንድትተዳደር የተወሰነ ሲሆን  አባ መንግስተአብ ተስፋማሪያም የመጀመሪያው የኤርትራ ሊቀጳጳስ ሆነው ተሾሙ፡፡ ኤርትራ ከኢትዮጵያ ከተነጠለች በኋላም የኤርትራ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን  በአዲስ አበባ ቅርንጫፍና በአንድ የጳጳስ ጉባኤ ስር ስትተዳደር የቆየች ቢሆንም ሰሞኑን ከቫቲካን የወጣ መረጃ፤ የሮማ ካቶሊካዊት ቤ/ክርስትያን አቡን ጳጳስ ፍራንሲስ የኤርትራ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን በአስመራ ቅርንጫፍ ራሷን ችላ እንድትተዳደር መወሰናቸውንና አባ መንግስተአብ ተስፋማሪያምን ሊቀጳጳስ አድርገው መሾማቸውን ጠቁሟል፡፡
የኤርትራ የመጀመሪያው የካቶሊክ ሊቀጳጳስ ሆነው የተሾሙት የአስመራ  ሀገረስብከት ጳጳስ  የነበሩት አባ መንግስተአብ ተስፋማርያም፤ ኤርትራ የ23ኛ አመት የነፃነት በአሏን ስታከብር “ወንድምህ የት ነው” በሚል ርዕስ በወቅታዊ የኤርትራ ሁኔታ ላይ በተለይ የወጣቶችን ስደት የተመለከተ  ሀተታና ጥያቄዎችን የያዘ ሰነድ ለፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ካስረከቡ አራት ጳጳሳት  አንዱ ነበሩ፡፡የጳጳሱን መሾም ተከትሎም የኤርትራ መንግስት ደጋፊ በሆኑ ድረገፆች አቡነ መንግስተአብ ተስፋማርያምን የሚያጥላሉ አስተያየቶች እየተሰነዘሩ ይገኛሉ፡፡ ኢትዮጵያና በኤርትራ የተደረገውን ጦርነት ተከትሎ  የሁለቱ አገራት ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያናት ስብሰባዎቻቸውን በኢትዮጵያም ሆነ በኤርትራ ሊያደርጉ ባለመቻላቸው በሮም ሲያካሂዱ መቆየታቸው ታውቋል፡፡

የደቡብ አፍሪካው ስታንዳርድ ባንክ በመጪው መጋቢት ወር መጨረሻ በኢትዮጵያ ተወካይ ቢሮ
ሊከፍት መሆኑን ቬንቸርስ አፍሪካ ድረገጽ ዘገበ፡፡የአገሪቱ የፋይናንስ ህግ የውጭ አገራት ባንኮች በመስኩ እንዳይሰሩ የሚከለክል እንደመሆኑ፣ ባንኩ ኢትዮጵያ የሚከፍተው ተወካይ መስሪያ ቤት የገንዘብ ብድርና ቁጠባን የመሳሰሉ ስራዎችን እንደማያከናውን የስታንዳርድ ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት ጣይቱ ወንድወሰንን ጠቅሶ ዘገባው ገልጿል፡፡በአዲስ አበባ የሚከፈተው ቢሮ ስታንዳርድ ባንክ በአገሪቱ ከሚገኙ ኩባንያዎች ጋር መልካም የስራ ግንኙነት ለመፍጠር የሚያስችሉ ስራዎችና የገበያ ጥናቶች የሚከናወንበት እንደሚሆን የገለጸው ዘገባው፤ የቢሮው መከፈት ባንኩ በኢትዮጵያ የኢንቨስትመንት ስራዎችን ለማከናወን ፍላጎት ላላቸው ደንበኞቹ የማማከር አገልግሎት ለመስጠት እንደሚያግዘውም አስረድቷል፡፡

    በአምስት አመቱ የጣሊያን ወረራ ወቅት በውስጥ አርበኛነታቸው የሚታወቁትን ወ/ሮ የሸዋረገድ ገድሌን የህይወት ታሪክ የሚዘክረው መፅሐፍ ዛሬ ከቀኑ 7፡30 ጀምሮ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተመዛግብትና ቤተ መጽሐፍት ኤጀንሲ (ወመዘክር) አዳራሽ ይመረቃል፡፡ “ሸዋረገድ ገድሌ፤ የአኩሪ ገድላት ባለቤት” በሚል ርዕስ የታተመው መጽሃፍ፤ ከ1878-1942 ስለኖሩትና በጣሊያን ወረራ ወቅት በዱር በገደሉ ላሉ አርበኞች  መረጃዎችን በማቀበል ታላቅ ገድል ስለፈፀሙት እናት አርበኛ ይተርካል፡፡ የመፅሐፉ ፀሐፊ ደራሲ ሺበሺ ለማ ሲሆኑ መጽሐፉን ያሳተሙት የአርበኛዋ የወንድም ልጅ ዶ/ር ክፍሌ ማርቆስ ገድሌ መሆናቸው ታውቋል፡፡ መፅሐፉ ለአገር ውስጥ በ70ብር፣ ለውጭ በ25 ዶላር ለገበያ የቀረበ ሲሆን በዛሬው የምረቃ ስነስርአት ላይ የቀድሞ ፕሬዚዳንት አቶ ግርማ ወ/ጊዮርጊስ እና ሌተናል ጃገማ ኬሎ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡

አርቲስት ደበበ እሸቱ ብቸኛው የህይወት ዘመን ተሸላሚ እጩ ሆኗል
በመጪው የካቲት የሚያካሂደውና በኢትዮ ፊልምስ ባለቤትነት የሚመራው የጉማ ፊልም ሽልማት ምርጥ አምስቶች ከትናንት በስቲያ በሃርመኒ ሆቴል ይፋ ሆኑ፡፡ በህይወት ዘመን ተሸላሚነት አርቲስት ደበበ እሸቱ ብቸኛ እጩ መሆኑም ተገልጿል፡፡ በዕለቱ በ17 ዘርፎች በዳኞችና በተመልካች የተመረጡ አምስት አምስት እጩዎች የታወቁ ሲሆን ዘርፎቹም በምርጥ የተማሪ አጭር ፊልም፣ በምርጥ ድምፅ፣ በምርጥ ሙዚቃ፣ በምርጥ ስኮር፣ በምርጥ ሜክአፕ፣ በምርጥ የፊልም ጽሑፍ፣ በምርጥ ቅንብር፣ በምርጥ ሲኒማቶግራፊ፣ በምርጥ ተስፋ የተጣለባት ህፃን ተዋናይት፣ በምርጥ ተስፋ የተጣለበት ህፃን ተዋናይ፣ በምርጥ ረዳት ሴት ተዋናዮች፣ በምርጥ ረዳት ወንድ ተዋናይ፣ በምርጥ ሴት ተዋናይት፣ በምርጥ ወንድ ተዋናይ፣ በምርጥ የተመልካች ምርጫ፣ በምርጥ ዳይሬክተርና በምርጥ ፊልም ጐራ በሚል ተከፋፍለዋል፡፡ መቶ ዳኞች በተሳተፉበት በዚህ ምርጫ ምርጥ አምስቶቹ የታወቁ ሲሆን በቀጣይ ከአንድ እስከ ሦስት የሚወጡት ተለይተው፣ የካቲት 16 ቀን 2007 ዓ.ም ደማቅ የሽልማት ስነ ስርዓት እንደሚካሄድ የኢትዮ ፊልም መስራችና ስራ አስኪያጅ ዮናስ ብርሃነ መዋ ለጋዜጠኞች ተናግሯል፡፡ ፕሮግራሙን ሙሉ በሙሉ ስፖንሰር ያደረገው በደሌ ቢራ ነው፡፡