Administrator

Administrator

Tuesday, 20 February 2024 00:00

"ዶቃ" አሸነፈ !!

በቅድስት ይልማ ተዘጋጅቶ በማህደር አሰፋ ፕሮዲዩስ የተደረገው ዶቃ ልብ አንጠልጣይ ፊልም "Los Angeles”ከተማ ውስጥ በተዘጋጀው በፓን አፍሪካን ፊልም ፌስቲቫል ላይ ተሳትፎ በ" Audience Choice Awards” አሸናፊ መሆን ችሏል::

በአፍሪካዊያን የጥበብ ስራዎች ላይ ትኩረትን ያደረገው ፓን አፍሪካ ፊልም ፌስቲቫል ከ32 ዓመታት በፊት የተመሰረተ ነው።

ቅድስት ይልማ ከአሁን ቀደም "ረቡኒ" ፣ "ታዛ" ፊልሞችንና "እረኛዬ" ድራማን ጨምሮ ከአስር በላይ ስራዎችን ለተደራሲያን ማቅረቧ ይታወሳል::


• በአማራ ክልል ትራክተር እንጂ ጥይት አያስፈልግም

• ይቅርታም ብለን ካሣም ከፍለን ቢሆን፣ እንታረቅ እንስማማ

• በምርጫ የሰጣችሁንን ሥልጣን በምርጫ ውሰዱት

-ሪፖርታዥ-

በትላንትናው ዕለት ከአማራ ክልል ተወካዮች ጋር በጽ/ቤታቸው የተወያዩት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፤ በአማራና በኦሮምያ ክልል ነፍጥ አንግበው ከሚንቀሳቀሱ ወገኖች ጋር በጠረጴዛ ዙሪያ በመወያየት ሰላም ለማምጣት እንደሚፈልጉ ተናገሩ፡፡

አዲሱ ምክትል ጠ/ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህና የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳደር አረጋ ከበደ በተገኙበት በተካሄደው በዚህ ውይይት ላይ ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ፣ ለሃይማኖት መሪዎችና ለአገር ሽማግሌዎች ባስተላለፉት ጥሪ፤ ”እባካችሁ በሰላማዊ መንገድ ገብቶ መነጋገር የሚፈልግ ሰው ካለ --ከየሰፈሩ አምጡ አወያዩና ይቅርታም ብለን ካሳም ካስፈለገ ካሳ ከፍለን እንታረቅ፤ እንስማማ፡፡” ብለዋል፡፡

“ሰው መግደልና መዝረፍ የትም አያደርስም፤ መክራችሁ የሚመለስ ሰው ካለ በመመለስ እርዱን፤እኛ የምንፈልገው ሰላም ነው” ሲሉ ጠ/ሚኒስትሩ ለአማራ ክልል ተወካዮች መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

ከአማራ ክልል የተለያዩ ዞኖች ተወክለው በውይይቱ ላይ የታደሙ ተሳታፊዎች በክልሉ የሰላምና ጸጥታ ጉዳይ፣ በመሰረተ ልማቶች ችግር፣ በግብርና ግብአቶች አለመሟላት፣ በመልካም አስተዳደር እጦትና በሌሎችም ዙሪያ ጥያቄዎችና አስተያየቶችን ሰንዝረዋል፡፡

ከተወካዮቹ ለተሰነዘሩት ጥያቄዎችና አስተያየቶች ምላሽና ማብራሪያ የሰጡት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፤ ስለ ታጣቂዎች፣ ስለ አማራ ተወላጆች የሥልጣን ድርሻ፣ ስለ ሃይማኖትና መንግስት ሚና፣ ስለ አንድነት ቤተ መንግሥት ፒኮክ ጉዳይ፣ ስለ ልማትና ሌሎች ሰፊ ጉዳዮች ተናግረዋል፡፡

የአማራ ተወላጆች ባለፉት 5 ዓመታት በአዲስ አበባ ላይ ያገኙት የሥልጣን ድርሻ ባለፉት 30 ዓመታት ኖሯቸው እንደማያውቅ የገለጹት ጠ/ሚኒስትሩ፤ ከለውጡ በኋላ የትኛውም ሥልጣን ለሁሉም ክፍት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

“ድሮ የአዲስ አበባ የሥልጣን ድርሻን በተመለከተ 25 ፐርሰንት ለኦህዴድ፣ 25 ፐርሰንት ለብአዴን፣ 25 ፐርሰንት ለህወኃት እና 25 ፐርሰንት ለደህዴን ነበር” ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ የፈለገ ቢያብጥ በአዲስ አበባ ላይ የአማራ የሥልጣን ድርሻ 25 ፐርሰንት ብቻ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

“ዛሬ ግን ካላጋነንኩት አማራ በአዲስ አበባ ላይ ከ33–35 ፐርሰንት የሥልጣን ድርሻ አለው” ብለዋል፡፡

ከምክትል ጠ/ሚኒስትር ጀምሮ ደህንነት፣ መከላከያ፣ ውጭ ጉዳይ፣ አየር መንገድና ብዙ ተቋማት በአማራ ተወላጆች ሥልጣን ሥር መሆናቸውንም ጠ/ሚኒስትሩ አብራርተዋል፡፡

የመንግሥት ሥልጣንን አስመልክቶ ያብራሩት ጠ/ሚኒስትሩ፤ “ሥልጣን በምርጫ ነው የሰጣችሁን፤ ስትፈልጉ በምርጫ ውሰዱት፤ ከኛ የተሻለ ካገኛችሁ ምረጡ፤ደሞ ታዩታላችሁ በምርጫ ህዝብ ሲወስን እንዴት እንደምናከብር፤ ጊዜው ሲመጣ ታዩታላችሁ” ብለዋል፡፡

ሥልጣን በአፈሙዝ ግን በፍጹም አይሞከርም ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ ፤ “እኛ ወታደሮች ነን፤ የአድዋ አርበኞች ልጆች ነን፤ ማንም በጉልበት ሊያሸማቅቀን አይችልም” ሲሉ ተናግረዋል፡፡



በአማራና ኦሮምያ ክልል ነፍጥ አንግበው የሚንቀሳቀሱ ወገኖችን በተመለከተ ጠ/ሚኒስትሩ ሲናገሩ፤ “የኛ ፍላጎት በአማራ ክልል ያለውም ሸኔ በኦሮምያ ያለውም ሸኔ ህዝብ ከማገድ፣ ከማገት፣ ከመግደል፣ ከመጥለፍና ከመዝረፍ ወጥቶ በሰላማዊ መንገድ ተነጋግሮ፣ ትጥቁን አስቀምጦ፣ ምርጫ ተወዳድሮ በሃሳብ አሸንፎ፣ እነሱ እዚህ መጥተው (ሥልጣን ላይ) እኛ እዚያ ብንቀመጥ ምንም ችግር የለብንም፡፡” ብለዋል፡፡

በአማራ ክልል ጥይት አያስፈልግም፤ ትራክተር ነው የሚያስፈልገው ያሉት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ፤ እኛ ከናንተ ጋር በፍቅር ብቻ ነው መኖር የምንፈልገው፤ ከዚህ የተለየ አጀንዳ የለንም ብለዋል፡፡

ጠ/ሚኒስትሩ ከአማራ ክልል የተለያዩ ዞኖች ከተወከሉ ተሳታፊዎች ጋር ያደረጉትን ውይይት ሲቋጩ፤ “በትብብር እንሥራ፤ በምክክር እንስራ፤ አንናናቅ፤ እንተባበር፤ የሚሻለው እሱ ነው፤ከዚያ ውጭ ያለው ሃሳብ ጥፋት ነው፡፡” የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

87ኛውን የካቲት 12 የሰማዕታት መታሰቢያ ቀንን በማስመልከት በሰማእታት ሀዉልት የአበባ ጉንጉን አኑረናል።
ዘላለማዊ ክብር ለጀግኖች ሰማእታት!
የ87ኛው የየካቲት 12 የሰማዕታት መታሰቢያ ቀንን ለማሰብ ነው የአበባ ጉንጉን ያኖሩት።
ከንቲባ አዳነች በዚህ ወቅት ባደረጉት ንግግር፤ኢትዮጵያ የዛሬ መልክና ቅርፅ የያዘችው የቀደምት አባቶቻችን በከፈሉት በደምና አጥንት ዋጋ ነው ብለዋል ።
ልጅ ዳንኤል ጆቴ መስፍን በበኩላቸው፤ ከ87 ዓመት በፊት በፋሽስት ጣሊያን በግፍ በተፈፀመው ጭፍጨፋ ሕይወት ያጡ ሰማዕታትን ስናስብ፤ የባለፈውን ታሪክ ብቻ በመዘከር ሳይሆን ያሁኑ ትውልድ ከጀግኖች አባቶች እንዲማር ለማድረግ ጭምር ነው ሲሉ ተናግረዋል ።

• የአበባ ዘርፉ ከ50 ሺ በላይ የሥራ ዕድል ፈጥሯል
• ኢትዮጵያ የዓለም 4ኛዋ ትልቋ የአበባ አምራች ናት
• የፍቅረኛሞች ቀን ለአበባ አምራቾች የውጥረት ጊዜ ነው


ባለፈው ረቡዕ ፌብሯሪ 14 ቀን 2024 ዓ.ም በመላው ዓለም የቅዱስ ቫላንታይን ቀን (የፍቅረኛሞች ቀን) ተከብሮ ውሏል- በፅጌረዳ አበባና በሌሎች የፍቅር መግለጫ ስጦታዎች ደምቆና ፈክቶ። በአበባ ምርትና ሽያጭ ላይ ላሉ ወገኖች ግን ከበዓሉ ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ አንስቶ ያሉ ጊዜያትን ጨምሮ በውጥረት የተሞላ ነው- የአበባ ምርቶች በብዛት ለገበያ የሚቀርቡበት ወቅት በመሆኑ፡፡ በአዲስ አበባ ዳርቻ ላይ ለሚገኘው የጋሊካ አበባ ኩባንያም ከዚህ የተለየ አይደለም - ወቅቱ፡፡ ይህን ባለፈው ረቡዕ  በሰፊው የጋሊካ የአበባ እርሻ ግቢ ውስጥ በአካል ተገኝቶ የቃኘው የፈረንሳዩ የቴሌቪዥን ጣቢያ ፍራንስ 24 ነው፡፡ የጣቢያው ዘገባ እንደሚያመለክተው፣ በዕለቱ ከጠዋቱ 1 ሰዓት ላይ 300 የሚሆኑ የኩባንያው ሠራተኞች በእርሻው ሥፍራ ላይ ደርሰው ነበር፡፡  
በየዓመቱ የኩባንያው 8 ሄክታር የቤት ውስጥ ማልሚያ (ግሪንሃውስ)፣ በመላው ዓለም የሚላኩ 5 ሚሊዮን ገደማ የፅጌረዳ አበቦችን እንደሚያመርት ዘገባው ይጠቁማል፡፡
የቅዱስ ቫላንታይን ቀን መቃረቢያ ጊዜያት ግን ከዓመቱ  ሁሉ እጅጉን ሥራ የሚበዛበት ወቅት ነው። ዛሬ ብቻ (ባለፈው ረቡዕ ማለት ነው) ከ20ሺ በላይ አበቦች ይሰበሰባሉ- ብሏል ዘገባው፡፡
“እዚህ ኡደቱ 80 ቀናት ገደማ ነው” ሲል ያስረዳው  የእርሻው ስራ አስኪያጅ አቶ ግዛቸው ወንድሙ፤ “ፅጌረዳዎቹን የዛሬ 80 ቀን ከተከልካቸው ዛሬ ደርሰው ታገኛቸዋለህ። እናም በተለይ አንዳንዶቹ የፅጌረዳ ዓይነቶች እንዲደርሱ ለማዘጋጀት እንሞክራለን፤ በዋናነት ቀያይ ጽጌረዳዎቹን፡፡ እኛ ሁልጊዜም ከሚፈለገው ያነሰ ነው የምናመርተው።” ብለዋል።
ባለፉት 12 ዓመታት በኢትዮጵያ የአበባ ምርት በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉን የጠቆመው ፍራንስ 24፤ እ.ኤ.አ በ2013 ዓ.ም ኢትዮጵያ ከምንም ተነስታ 212 ሚ.ዶላር የሚገመት 2 ቢሊዮን ቶን አበባ ለውጭ ገበያ መላኳን ያስታውሳል።
ይኼም አሃዝ ኢትዮጵያን የዓለም አራተኛዋ ትልቋ የአበባ አምራች ሲያደርጋት፤ በአፍሪካ ደግሞ ከኬንያ ቀጥሎ በሁለተኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧታል- ይላል ዘገባው።
50ሺ የሥራ ዕድሎች
ምንም እንኳ አብዛኞቹ የአበባ ኩባንያዎች በውጭ ዜጎች ባለቤትነት የተያዙ ቢሆኑም፣ የኢትዮጵያ የአበባ ዘርፍ ከ50ሺ በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የሥራ ዕድል የፈጠረ ሲሆን፤ ከ70 በመቶ የሚልቁት ሠራተኞች ደግሞ ሴቶች ናቸው።
“የምኖረው እዚሁ ጎረቤት ነው፤ ነገር ግን የራሴ መሬት የለኝም። እዚህ  ለመሥራትና በቆጠብኩት ገንዘብ የራሴን ንግድ ለመጀመር ነው ያቀድኩት።” ትላለች፤ በጋሊካ እርሻ ላይ ከሚሰሩት አንዷ የሆነችው ብርቱካን ሚልኬሳ፤ ለፍራንስ 24 ቴሌቪዥን።
“እዚህ በመሥራታችን ትልቅ ጥቅም አለን። ለምሳሌ፡- በየቀኑ ምሳችንን በነጻ እንመገባለን።” ስትልም አክላለች-ብርቱካን።
የኢትዮጵያ አበባ ገበሬዎች ጥብቅ የስነ-ምግባር መመሪያ የሚከተሉ ሲሆን፤ እጅግ ውድድር በበዛበት ገበያ ውስጥ እንደሚሰሩም ይገነዘባሉ።
በጋሊካ እያንዳንዱ ፅጌረዳ በጥንቃቄ ይመረጣል፤ ይደረደራል፤ ከዚያም  ይታሸጋል።
“ወደ መዳረሻቸው ከመላካቸው በፊት ፅጌረዳዎቹ ይታሸጋሉ፤ ውሃ ይጠጣሉ፤ ከዚያም በቀዝቃዛ ክፍል ውስጥ ለአንድ ሌሊት ይቀመጣሉ።” ሲል የጋሊካ ባለቤት ስቲፌን ሞቲየር አስረድቷል፡፡
እርሻው ከ60 በላይ የፅጌረዳ ዝርያዎችን ያመርታል። አዲስ ዲቃላ ቀለማት ሲፈጠሩ ልዩ ስሞች ይወጣላቸዋል።
“የተለያዩ አገራት የተለያዩ ዓይነት ፅጌረዳዎችን ይፈልጋሉ። ይኄኛው ምናልባት ወደ ጃፓን ወይም ደቡብ አፍሪካ ይላካል” አለ ስቴፋን ወደ ነጭ ፅጌረዳ እየጠቆመ፤ “የተቀሩት በተለይም ቀይ ፅጌረዳዎቹ ደግሞ  ወደ ፈረንሳይ ይላካሉ።”
በመጨረሻም አበቦቹን ለመውሰድ ትልቅ መኪና ይመጣል። ከዚያም አበቦቹ በአውሮፕላን ተጭነው በቀጥታ በዓለም ዙሪያ ወደሚገኙ የአበባ መሸጫ ሱቆች በሰዓታቸው ይደርሳሉ - ለፍቅረኛሞች ቀን!!

ፖርቹጋል ገናና በነበረችበት ወቅት የነበሩ የአንድ ንጉሥ አፈ-ታሪክ አለ፡፡
ለዘመናት በወራሪነት የኖሩ ንጉሥ፣ በምርኮ የያዙዋቸውን አገሮች አቀናለሁ እያሉ ብዙ ብር ያፈሱባቸዋል፡፡ ከዚያም በዓመት አንድ ጊዜ ህዝቡን ሰብስበው፤
“ዕድሜ ለእኔ በሉ ነፃ አወጣኋችሁ” ይላሉ፡፡ህዝቡ በጭብጨባ ስለንግግራቸውና ስለቸርነታቸው ያለውን አድናቆት ይገልፃል፡፡
ቀጥለውም ንጉሡ፤ “ዛሬ በገዛ ደግነቴ፤ ለሀገራችሁ ዕድገት፣ ለህዝባችሁ ደህንነት ስል አንድ ተጨማሪ በጎ-አድራጎት እፈፅማለሁ፡፡ ይኸውም፤ ነፃ የወጣችሁበትን ቀን በዓመት አንድ ቀን ታከብሩ ዘንድ ፈቅጄላችኋለሁ፡፡”
ህዝቡ በጭብጨባ አድናቆቱን ይገልፃል፡፡፡
ከዚያ እንደተለመደው፤
“ጥያቄ ካላችሁ መጠየቅ ትችላላችሁ” ይላሉ፡፡
ከሰው መካከል በተራ በተራ እየተነሱ ተወካዮች ጥያቄ ይጠይቃሉ፡፡ የህፃናቱ ተወካይ፤ “ንጉሥ ሆይ! መዋዕለ - ህፃናት ይሰራላችኋል ከተባልን ብዙ ዓመት አለፈን፡፡ በጦርነቱ እናት አባታቸውን ያጡ አያሌ ህፃናት የሚኖሩበት አላገኙም፡፡”
ቀጥሎ የወጣቱ ተወካይ ይነሳል፡፡
“ንጉሥ ሆይ! ከሁሉም በጦርነቱ የተጎዳው ወጣቱ ነው፡፡ ወጣቱ የሚያነብበት ቤተ -መፃሕፍት፣ የሚዝናናበት ኳስ ሜዳ፣ የሚወያይበት አዳራሽ የለውም፡፡ ስለዚህ የእርሶን እርዳታና ረድኤት እንሻለን” ንጉሥ- “መልካም፡፡ የእናንተም በጣም አሳሳቢ ጉዳይ ነው፡፡ በቀጣይ የተያዘ ስለሆነ ይፈፀማል” አሉ፡፡
በተከታታይ የሴቶች ተወካይ፣ የሽማግሌ ተወካይ፣ የሠራተኛ ተወካይ፣ የተማሪ ተወካይ ወዘተ…. ጥያቄያቸውን አቀረቡ፡፡
ንጉሡም “በቀጣይ ተይዟል” ሲሉ መለሱ፡፡
በመጨረሻም የምርኮኞቹ ወታደሮች ተወካይ፤
“ንጉሥ ሆይ! ከሁሉም የተጎዳን እኛ ወታደሮች ነን፡፡ ይኸው ያለ ጦርነት ተቀምጠን ስንትና ስንት ዓመት  ተሰቃየን፡፡ ወይ ከእንግዲህ ጦርነት የለምና ተበተኑ በሉን፡፡ አለበለዚያ ደግሞ በአስቸኳይ ጦርነት ይፈጠርልንና በቶሎ ተግባር ላይ እንሰማራ፡፡ ንጉሥ ሆይ! ቃታ እንስብበታለን ያልነው ጣታችን ለስልሶ የወርቅ ቀለበት ማሰሪያ ሆነ፡፡ ለሬዲዮ መገናኛ የተሠጠን መሳሪያ የሙዚቃ ማዳመጫ ሆኖ ሰነበተ፡፡ ስንት ዳገት ቁልቁለት ይወጣል ይወርዳል፤ የት ይደርሳል የተባለው ሰውነታችን በተጠረገ መንገድ መምነሽነሽ፤ በሚሞቅ አልጋ ላይ መተኛት የሁልጊዜ ፀባዩ ሆነ፡፡ ምቾት በዛ ንጉሥ ሆይ? ያ በሥልጠና ላይ የተነገረን ጦርነት የታለ?  እንደ-ምጽዓት ቀን ራቀብን’ኮ፡፡ ኧረ አንድ መላ ይፈጠርልን ንጉስ ሆይ!” ሲል ተማጠነ፡፡
ንጉሡም፤ “እኔም ይህን ችግራችሁን በጣም አስቤበታለሁ፡፡ ሥቃያችሁ ያሰቃየኛል፡፡ ህመማችሁ ያመኛል፡፡ ስለዚህም የናንተ ጉዳይ ከማንም በፊት በቀዳሚነት በቀጣይ ተይዟል” አሉ፡፡
እኒያ ንጉሥ ከዚያን ጊዜ አንስቶ እስከ እለተ - ሞታቸው ድረስ መጠሪያ ስማቸው “ንጉሥ በቀጣይ” የሚል ሆነ፡፡
አገራቸውም፤ ከዓመት ዓመት ጦርነት በቀጣይ እያስተናገደች፤ አያሌ ቅኝ-ግዛቶቿን እስክታጣ ድረስ ስትዋጋ ኖረች፡፡
***
ህዝቦችን በተስፋ ብቻ በማሰር ለመሰንበት  የሚሞክር እንደ ፖርቹጋሉ ንጉሥ ያለ መሪ፤ ህዝቦቹ የለበጣ የሚገዙለት፤ በሀሳዊ-ጭብጨባ እንዲገበዝ የሚያደርጉት ነው፡፡ ከቶውንም ምርኮኞቹን ነፃ እንዳወጣቸው ማሰቡና፤ እንዲያስቡም ለማስገደድ መሞከሩ፤ ጊዜያዊ የአሸናፊነት ስሜትን እንጂ ዘላቂ ሥርዓትን ለመገንባት የሚፈይደው ነገር አይኖርም፡፡
ህዝብ የተታለለ ሲመስል የእድር አለቃውም፣ የቀበሌ ሹሙም፣ የቢሮ ኃላፊውም፣ የቢሮክራሲ አባ-ወራውም፣ የፖለቲካ ፓርቲ መሪውም…. አዕምሮውን ሰብሰብ አድርጎ፣ ማናቸውንም ዕርምጃ ከመውሰዱ በፊት ሁለት ሶስቴ አስቦ፤ ከምወስደው እርምጃ ጠቀሜታና ህዝቡ ከሚያገኘው ፋይዳ የትኛው ሚዛን ይደፋል? ብሎ ሁኔታዎችን ማውጠንጠን እጅግ ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ የገባሁት የተስፋ ቃል ከታጠፈ ካፌ የሚወጣው ሁሉ ወደ አለመታመን ማምራቱ አይቀርም ብሎ የማያስብ የበላይ፤ የኮቴውን ድምፅ ያህል እንኳ የሚታወስ ፍሬ የሌለው ነው፡፡
የኒውዚላንድ ህዝቦች ሲተርቱ “አሮጌ ቃል - ኪዳን ወደ ኋላ ይቀራል” እንደሚሉት፤ በአዲስ ቃል-ኪዳን ወይም እንደ ፖርቹጋሉ የአፈ -ታሪክ ንጉስ በቀጣይ ቃል-ኪዳን ይተካል ብንል፤ ጊዜን መሸጋገራችን እንጂ ረብ ያለው ድርጊት አልፈፀምንም፡፡
ጆርጅ ፓድሞር የተባለው ትሬኒዳዳዊ የምርጫ ተወዳዳሪ “አፍሪካውያን በቃል--ኪዳን በመተማመን ረዥም ጊዜ ኖረዋል፡፡ አሁን ማየት የሚፈልጉት ጥቂት ተጨባጭ ተግባራትን ብቻ ነው፡፡ አንገታቸው ላይ የሎሌነት ሰንሰለት አጥልቀውም ስለ “ዲሞክራሲ” እና ስለ “ነፃነት” የሚሰበኩ ሃይማኖት አከል ውዳሴዎችን ማዳመጥ ደክሟቸዋል፤ ታክቷቸዋል” ያለው በከንቱ አይደለም፡፡ የብዙ ፖለቲካዊ ቀውሶች መንስዔዎች የታጠፉ ቃሎች ናቸው፡፡
ሌት ተቀን አውጥተን አውርደን፣ አዋቂ ጠይቀን፤ የውጪ አጥኚ አሰማርተን ይሄን ችግር በቅርቡ እንፈታዋለን ብለን ስናበቃ፣ መልሰን በቅርቡ ያልነውን ላልተወሰነ ጊዜ አሸጋግረነዋል ካልን፣ ከቃል ማጠፍ የማይተናነስ ተግባር ፈፅመናልና ችግሩን አዘገየነው እንጂ የመፍታት ሙከራ አላደረግንም፡፡ የሚዋዥቀውን ወይም ትርጉም ባለው መልኩ ለውጥ ያልታየበትን ኢኮኖሚ፣ አድጓል ተመንድጓል፣ነገ ደግሞ የእጥፍ-እጥፍ ያድጋል ብለን ቃል-ብንገባ፣ በኑሮ ውድነቱ ሳቢያ ሰልፍ አስመርሮኛል የሚለውን ሰው በቅጡ ማሳመን የሚቻል አይሆንም፡፡ ነባራዊውም ሆነ ህሊናዊው ሁኔታ የማያግዙት ሙግት፤ አፍአዊ እንጂ ልባዊ ብሎም ተግባራዊ ለመሆን ይሳነዋል፡፡
የላይኛው እንዳፈተተው ሲናገር የታችኛው ለማስተጋባት የበለጠ መጮሁ አግባብ ያለው ሥርዓት በሚመስልበት፣ እንደ ውሃ በመሬት ስበት ኃይል ከላይ ወደታች እንደሚወርድ የዕዝ-ሠንሠለት የተዋቀረ በሚመስል አካሄድ ውስጥ፤ “አሳታፊ ዲሞክራሲ”፣ “የውድድር ኢኮኖሚ”፣ “ልማት-ተኮር ራዕይ”፣ “ፍትሕ-ርትዕ የሰፈነበት ማህበራዊ መርሕ” እያልን ብናንቆለጳጵሰው፤ ለስልት እንጂ ለስሌት አያግዘንም፡፡  ዞሮ ዞሮ  ከላይ ወደታች የሚወርድ አንድ አሸንዳ ውስጥ ያለ ፍሰት የመሰለ ፖለቲካዊ ሥርዓት፤ “ታላቅየው ሲመቸው፣ ታናሽየው ሳይድህ በእግሩ ይሄዳል” እንደሚባለው ያለ ነው፡፡

እውነቱ ማውጣት፣ ተጎጂዎችን መካስና የወንጀለኞችን ተጠያቂነት ማረጋገጥ እንደሚገባ ተገልጿል። የሚዲያ ባለሙያዎች  አገራዊ መግባባቱን ሊያሣኩትም ሊያፈርሱትም ይችላሉ ተብሏል
የሽግግር ፍትህ ሂደቱ በማህበረሰቡ መሃከል የሚኖረውን ስንጥቅ የሚደፍን መሆን አለበት።
በኢትዮጵያ በቅርቡ  ተግባራዊ መደረግ ይጀምራል ተብሎ የሚጠበቀው የሽግግር ፍትሕ፤ የሕግ የበላይነትን ለማስፈን ፤ ግጭትን ወደእርቅ ለመለወጥና ዘላቂ ሰላም ለማስፈን የሚያስችል ለማድረግ ቁርጠኝነት ሊኖር እንደሚገባና ሂደቱ በገለልተኛ ወገን ሊከናወን እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት አስታወቀ ምክር ቤቱ  “ ለሽግግር ፍትህ ስኬት የሚዲያ ሚና በኢትዮጵያ “  በሚል ርዕስ ትናንት ለሚዲያ ባለሙያዎች  ባዘጋጀው ውይይት ላይ በቀረበው ጥናታዊ ፅሁፍ እንደተገለፀው የተድበሰበሰ የፍትህ ስርዓት የሽግግር ፍትሁን ሊያሣካ አይችልም ተብሏል። ለሠላም ሲባል ብቻ ፍትህን ጨፍልቆ እርቅ እንዲፈጸም  ማድረግ ተጠያቂነትን እንደማያረጋግጥና ነገ ተመሣሣይ ጥፋቶች ላለመፈጸማቸው ዋስትና አይሰጥም ተብሏል ።
ይህ ሁኔታዎች ሰዎች ጥፋት ፈጽመው ከተጠያቂነት ማምለጥ እንደሚችሉና ያለመጠየቅ ዕድሎች እንዳሉ  አመላካች እንደሆነም ተገልጿል። ይህ አሰራር እንደማያወጣና ውጤት እንደሌለው  በ2009 ያደረግነው ጥቅል የምህረት አሰጣጥ ስርአቶች ጥሩ ማሣያዎች ናቸው ተብሏል። ለሽግግር ፍትህ ሂደቱ  የተለያዩ አማራጮችን ለማየት እንደተሞከረ የተናገሩት ጥናታዊ ፅሁፍ አቅራቢው አቶ ዘላለም   ሁሉን አቀፍ  አፕሮች የተባለው መንገድ የተሻለ መሆኑንና ይህ መንገድ የዜጎችን እውነቱን የማወቅ መብት የሚያከብር ፣ የሕግ የበላይነትን የሚያስከብርና ወንጀለኞች ለፍትህ እንዲቀርቡ የሚያደርግ ተጎጂዎችን የሚክስና ዘላቂ ሰላም የሚያሰፍን መንገድ ነው ።
ይህ መንገድ እውነት ማውጣትን ካሣንና እርቅን አጠቃሎ የያዘ ሁሉን አቀፍ መንገድ ነው ብለዋል።

በመንግስት ተቋማቱ ጫና አገልግሎቱን ለማቆም ተገደናል - የማዕከሉ መስራች
“ከገባነው ውል ያጎደልነው የለም” - አዲስ አበባ ጤና ቢሮ እና ምንሊክ ሆስፒታል


ከሁለት ዓመት በፊት በኢትዮጵያዊቷ ዲያስፖራ ትዕግስት አበበ፣ በአዲስ አበባ ጤና ቢሮና በዳግማዊ ምንሊክ ሆስፒታል ትብብር ለኩላሊት ታማሚዎች ነፃ የኩላሊት እጥበት አገልግሎት መስጠት የጀመረው የአብ ሜዲካል ሴንተርና ሪሀብሊቴሽን ሊሚትድ አገልግሎት መስጠት በማቆሙ ህይወታቸው ለአደጋ መጋለጡን ችግር ላይ መውደቃቸውን ታካሚዎች ለአዲስ ድማስ ገለፁ።
ህይወታችንን ለማቆየት ትግል ላይ በነበርንት ወቅት አብ የኩላሊት እጥበት ማዕከል ተከፍቶ እፎይ አልን ስንል  “የግብአት እጥረት አጋጥሟል” በሚል ማዕከሉ አገልግሎት መስጠት ካቆመ ሶስት ሳምንት አልፎታል ያሉት ታካሚዎች፤ ግማሾቻችን ወደ ልመናና ወዳጅ ዘመድ ማስቸገር፣ ከፊሎቻችን የቀረችንን ጥሪት ወደ መሸጥ፣ ይህን ያልቻልን ፊታችን ከተደቀነው ሞት ጋር መፋጠጥ ዕጣ ፈንታችን ሆኗል ሲሉ አማርረዋል።
“ወዳጅ ዘመድ የሚደግፈን ወደ ግል የኩላሊት እጥበት ማዕከል አገልግሎት ፍለጋ ስንሄድ፣ ከምኒልክ ከመጣችሁ አናስተናግድም የሚል ተግዳሮት እየገጠመን ነው” ሲሉ ከወጣት እስከ ዛውንት የእድሜ ክልል የሚገኙ የማዕከሉ ተጠቃሚ ታካሚዎች ለአዲስ አድማስ ገልጸው፤ የሚመለከተው የመንግስት አካል አስቸኳይ መፍትሄ ይስጠን ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል። በዳግማዊ ምንሊክ ሆስፒታል ገቢ ውስጥ የሚገኘውና በአንድ ጊዜ 30 ታካሚዎችን የማስተናገድ አቅም ያለው ማዕከሉ፤ ላለፉት ሁለት ዓመታት ለ120 ታካሚዎች ነፃ የኩላሊት እጥበት አገልግሎት ሲሰጥ እንደነበር የሚገልፁት የማዕከሉ መሥራች ትዕግስት አበበ፤ ለማዕከሉ ታካሚዎች፤ አገልግሎት  መስጠት ካቆመ ሦስት ሳምንታት ማስቆጠሩንና በዚህ ሳቢያ ከሞት ጋር ትንቅንቅ የገጠሙ ታካሚዎች እንዳሉ ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል።
“ሳይንሱ የሚያዘው አንድ ኩላሊት እጥበት የጀመረ ታካሚ በሳምንት ሶስት ቀን ዲያሊሲስ ማድረግ እንዳለበት ነው ያሉት ታካሚዎቹ፤ “ይህ ማዕከል ከመከፈቱ በፊት በግል የኩላሊት እጥበት ማዕከላት አገልግሎት ለማግኘት በወር እስከ 40ሺህ ብር ለመክፈል ቤት ንብረት ከመሸጥም ባለፈ ወዳጅ ዘመድ እያስቸገርን፤  የሌለን  ደግሞ ጎዳና ወጥተን እየለመንን ነበር” ብለዋል።
ማዕከሉ ምን ችግር ገጠመው በሚል ትላንት ረፋድ ወደ ምንሊክ ሆስፒታል አቅንተን የማዕከሉ መስራች  ትውልደ ኢትዮጵያዊቷን ትዕግስት አበበን ጠይቀን  ታካሚዎቹ በነፃ በሰጡን ምላሽ፤  ላለፉት 2 ዓመታት 120 ታካሚዎች በነጻ ኩላሊታቸውን በሳምንት ሶስት ቀን  እንዲታጠቡ  በማድረግ መቆየታቸውን ይናገራሉ።  ኑሯቸውን ለረጅም ዓመታት በአትላንታ ጆርጂያ ያደረጉት የማዕከሉ መስራች ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ የጤና ባለሙያ፤ በዚሁ የህክምና ዘርፍ መቆየታቸውን ገልፀው፣ ለ19 ዓመታት በሜዲካል ሚሽን ትሪፕ ወደ አገራቸው እየመጡ እያገለገሉ ይመለሱ እንደነበር፣ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ ዲያስፖራው ማህበራሰብ ባለው አቅምና ሙያ ሀገሩን እንዲደግፍ ባደረጉት ጥሪ መሰረት፣ በፐብሊክ ፕራይቬት ፓርትነርሽፕ ይህን ማዕከል በመክፈት ወገንን ለማገልገል ሙያቸውን ይዘው እንደመጡ ይናገራሉ።
ከዚም በኋላ በክብርት ከንቲባዋ አዳነች አበቤ ትብብር ጉዳዩ ተቀላጥፎ ከሁለት ዓመት በፊት በ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን ዶላር ማዕከሉ ደረጃውን ጠብቆ መከፈቱን 60 ያህል ሰራተኞች መቅጠሩንና አዲስ አበባ ጤና ቢሮና ዳግማዊ ምንሊክ ሆስፒታል አስፈላጊውን ድጋፍ ባለማድረጋቸው ህክምና አሰጣጡ መስተጓጎሉን የገለፁት የማዕከሉ መስራች ትዕግስት አበበ፤ ማዕከሉ በቀን እስከ 120 ታካሚዎችን የማስተናገድ አቅም ያለው ሆኖ በድንገተኛ የሚመጡ አራትና አምስት ታካሚዎችን በሳምንት እየተቀበለ ሲያክም እንደቆየ አብራርተዋል።
ይሁን እንጂ ህክምና መስጠት ስንጀምር የነበረው የታካሚዎቹ የአላቂ እቃ ዋጋ በአራት እጥፍና ከዚያ በላይ በመጨመሩ ከአቅም በላይ ሆኖብን ከ4 ወር  በፊት ማዕከሉ አገልግሎት መስጠት አቁሞ እንደነበር ገልጸዋል። ከዚያ በኋላ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በጉዳዩ ገብቶ ረጅም ሂደት ወስደን የገዛነውን የህክምና እቃ የአውሮፕላን ተከፍሎ መምጣቱን ተናግረዋል። እንደ ማዕከሉ መስራች ገለፃ፤ ሀገራችንንና ወገናችንን ለማገልገል ካለን ጥልቅ ፍላጎት አንፃር በኩላሊት እጥበት ሥራ በጣም አስፈላጊውንና ዋናውን እቃ (አሲድ) እዚሁ አገራችን ማምረት ጀምረን፣ እንኳን ለማዕከላችን ለሌሎች ሆስፒታሎችም በጣም በቅናሽ ዋጋ ማቅረብ ጀምረናል፤ ዋናው ችግራችን ግን ወዲህ ነው ብለዋል።
“የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጥሪ ተቀብለን ስንመጣ ከተደላደለና ከሞቀ ኑሯችን ወጥተን ነው” የሚሉት ሃላፊዋ፣ በስምምነታችን መሰረት ከተማ መስተዳድሩ የጤና ቢሮ ሃላፊዎችንና ምንሊክ ሆስፒታል መስተዳድሮችን ይህን አድርጉልን ይሁን አሟሉልን ስንል  ከአራት ወር በፊት  በ90 ቀናት ውስጥ “ጓዛችሁን ጠቅልላችሁ ውጡ” የሚል ከአንድ ትልቅ የጤና ቢሮ ሃላፊ የማይጠበቅ ምላሽ ሰጥተውናል ብለዋል።
ወ/ሮ ትዕግስት አክለውም፤ ይህን ስራ ከጀመርንበት ከአንደኛው  ቀን ጀምሮ በሁለቱ ተቋማት ሃላፊዎች እየተበደልን ወገን ለማገልገል ብንታገስም፣ አሁን ግን በደረሰብን ጫና አገልግሎት መስጠት አቁመን ለ10 ዓመት የተፈራረምነውን ውል፣ በሁለት ዓመቱ ላይ ለማቋረጥ ደብዳቤ ፅፈናል ሲሉ ለምንሊክ ሆስፒታል የፃፉትን የውል ማቋረጫ ደብዳቤ በዋቢነት አቅርበዋል።
“እኛ ወደ መንግስት ሆስፒታል ገብተን ለመስራት የፈለግነው ጉዳዩ የጋራ በመሆኑ የበለጠ መንግስት ሥራችንን ያሳልጣልናል፤ የመጣነው ሀገርን ለማገዝ ነው በሚል ነው ያሉት ሃላፊዋ፣ ነገር ግን በአንዱ ስንለው በሌላው፣ አንዱን ስንፈታ ሌላ ጉዳይ እየታሰረብን በቀን 240 ሰው ማከም ስንችል 120 ሰው ላይ ተቸክለን ቀርተናል ብለዋል።” መሥራቿ  ለአዲስ አድማስ የገጠማቸውን ተግዳሮት ሲያስረዱ።
“ከዚህ ግቢ ጓዛችሁን ጠቅላላችሁ” ውጡ ለሚባለውም ነገር ይህ ማዕከል ሲቋቋም ጠቅላይ ሚኒስትሩ  የቀድሞዋ የጤና ሚኒስትር ዶ/ር ሊያ ታደሰና ከንቲባዋ አዳነች አቤቤ የደከሙበትና ወገንን የሚያገለግል ማዕከል እንደመሆኑ፣ በህግና በስነስርዓት እንደገባነው ሁሉ አዲስ አበባ ጤና ቢሮና ዳግማዊ ምንሊክ ሆስፒታል ያጠፋነው ያጎደልነው ካለ ገልጸውልን፣ የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት አውቀው በህግና በስርዓት ለመልቀቅ ዝግጁ ነን፣ ለሀገራችንና ለወገናችን ለመድረስ ብዙ ጥረናል፤ ከዚህ በላይ ምንም ማድረግ አንችልም” ብለዋል።
መግባታቸውን ዙሪያ ያነጋገርናቸው የዳግማዊ ምንሊክ ኮምፕረኸንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር ተከተል ጥላሁን፣ ሶስቱ ወገኖች ማለትም የአብ የህክምና ማዕከል፣ ዳግማዊ ምንሊክ ኮምፕረኸንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታልና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ በመንግስት የግል አጋርነት ወይም (ፐብሊክ ፕራይቬት ፓርትነርሽፕ) አማካኝነት ወደ ስራ መግባታቸውን አስታውሰው፤ ሶስቱም አካላት በውልና በህግ የተቀመጠ ግዴታና ሀላፊነት እንዳለባቸው ገልፀዋል፡፡
ዶ/ር ተከተል የሶቱን ተዋዋይ ወገኖች ሀላፊነት ሲገልፁም፤ ዳግማዊ ምኒሊክ ሆስፒታል የአብ የህክምና ማዕከል ለታካሚዎች የሚሰጠው ህክምና ጥራቱንና ደረጃውን የጠበቀ መሆኑን መቆጣጠርና ማረጋገጥ አንዱ ሃላፊነቱ ሲሆን፤ ሁለተኛው የአብ ሜዲካል ሴንተር ለሚሰጠው አገልግሎት የህክምና  ባለሙያዎችን ማቅረብና የአብ ለሚሰጠው አገልግሎት ለሚጠይቀው ክፍያ በውሉ መሰረት ክፍያው በተጠየቀ 3 የስራ ቀናት  ውስጥ ክፍያ መፈፀም እንዲሁም የድጋፍ ደብዳቤ መፃፍና የመሳሰሉት ዋና ዋናዎች ናቸው ብለዋል። ዶ/ር ተከተል አክለውም የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ በዋናነት የአብ ሜዲካል ሴንተር የድጋፍ ደብዳቤ ሲጠይቀው ህጋዊነቱንና አስፈላጊነቱን አጣርቶ ደብዳቤ መፃፍና ማዕከሉ ከቀረጥ ነፃ እቃዎችን እንዲያስገባ ለሚመለከተው አካል የድጋፍ ደብዳቤ መፃፍ በማዕከሉ የሚሰጠው አገልግሎት ሳይቆራረጥ እንዲሰጥ ማገዝ ነው ይላሉ፡፡
ማዕከሉ ምን ያህል ታካሚዎችን እያገለገለ ነበር ለሚለው ጥያቄ ሲመልሱ፤ እኛ የምናውቀው ለሚያገኙት አገልግሎት ክፍያ የምንፈፅምላቸው 104 ናቸው ያሉት ስራ አስኪያጁ፤ ማዕከሉ 120 ናቸው ቢልም 16ቱን ግን አናውቅም ብለዋል፡፡ የአብ ሜዲካል ሴንተር በነፃ ህክምና እሰጣለሁ ቢልም ለታካሚዎች የአገልግሎት ክፍያ ለማዕከሉ የሚከፍለውና ለህክምና ባለሙያዎች ደሞዝ የሚከፍለው ዳግማዊ ምንሊክ ሆስፒታል ነው ብለዋል፡፡ ይህም በውሉ ላይ የተቀመጠና በማስረጃ የሚረጋገጥ ነው ይላሉ፡፡ ከአራት ወር በፊት በግብአት እጥረት ለምን ህክምና ተቆራረጠ የአብ የህክምና ማከል ለጠየቀው የዋጋ ማሻሻያ ለምን ምላሽ አልተሰጠም በሚል ላቀረብነው ጥያቄ ዶ/ር ተከተል ሲመልሱም፤ ለኩላሊት ስንፈት ታካሚዎች ለአንድ ጊዜ አገልግሎት 800 ብር፣ ዘላቂ የኩላሊት ስንፈት ላጋጠማቸው ደግሞ ለአንድ ጊዜ አገልግሎ 1080 (አንድ ሺህ ሰማኒያ ብር) ለማዕከሉ እንከፍል ነበር ያሉት ዶ/ር ተከተል ሆኖም ማዕከሉ የዋጋ ማሻሻያ  ለከተማ አስተዳደሩ ፋይናንስ ተመርቶ ከዚያም የከተማ አስተዳደሩ ካቢኔ አይቶት ሌሎች የዲያሊስስ አገልግሎ የሚሰጡት እንደነ ጳውሎስ ሆስፒታል ያሉ ማዕከላት ያለው ዋጋ ታይቶና የዋጋ ማሻሻያ ጥናት ተደርጎ የሚፀድቅ እንጂ ማዕከሉ ዛሬ ማሻሻያ አድርጉ ስላለ በእኛ ስልጣን የምናሻሽለው አይደለም ካሉ በኋላ፤ “ሆኖም ይህንን ማሻሻያ አስጠንተን እናሻሽላለን እስከዛ ስራው ይቀጥል የሚል ደብዳቤ ብንፅፍም ማዕከሉ ደብዳቤያችንን ውድቅ አድርጎት ከሶስት ሳምንት በፊ የህክምና አገልግሎቱ ተቋርጧል” ብለዋል፡፡
ከዚህ በፊት የህክምና አገልግሎቱ በዋናነት የተቋረጠውም የአብ የህክምና ማዕከል በውሉ መሰረት ስራ ሲጀምር ቢያንስ ከ3-6 ወር የሚበቃ የህክምና ግብአት ስቶክ እንዲይዝ ውል የገባ ቢሆንም አንድም ቀን መጠባበቂያ ስቶክ ይዞ ባለማወቁ ነው ያሉት ዶ/ር ተከተል ይህን ሁሉ ታግሰን ብንቆም ማዕከሉ ግን የግድ ውል ይቋረጥ በማለት አሻፈረኝ ብሏል ብለዋል፡፡
እስካሁን ከውላችን ያጎደልነው የለም ያት ዶ/ር ተከተል፤ የውሃ ቧንቧ ተሰበረ ራውተር ተሰረቀና ሌሎች ቅሬታዎች ማዕከሉ ቢያነሳም የምን ቀበለው የራውተሩን መሰረቅ ነው ያሉ ሲሆን የሆስፒሉ ጥበቃ አውትሶርስ ተደርጎ በጥበቃ ኤጀንሲ የሚሰራ ሲሆን ከዚህም ቀደም የሆስፒታሉ ሌሎች እቃዎች እየጠፉ የጥበቃ ኤጀንሲው እየገዛ እንዲተካ እንደሚደረግና የማዕከሉንም ራውተር የጥበቃ ኤጀንሲው ገዝቶ ለመተካት በሂደት ላይ መሆኑን ተናግረዋል።  ከዚህ ቀደምም ስራው እንዳይቋረጥና አገልግሎቱ እንዲቀጥል ማዕከሉ ከውጪ ገዝቶ ያመጣውን የህክምና ግብአት የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ከውሉ ውጪ 3 ሚ ብር የአውሮፕላን ከፍሎ ግብአቱ መግባቱንና ህክምና እንዲቀጥል ማድረጉን ጤና ቢሮው ከገባው ውል አንዱንም አላማጉደሉን የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ሀላፊ ዶ/ር ዮሃንስ ጫላ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

ሲንቄ ባንከ አ.ማ ከተለያዩ ስምንት ተቋማት ጋር አብሮ ለመስራት የሚያስችለውን የመግባቢያ ሰነድ ዛሬ የካቲት 7 ቀን 2016 ዓ.ም በባንኩ ዋና መስሪያ ቤት ተፈራርሟል፡፡ ባንኩ ከተቋማቱ ጋር ከተፈራረማቸው የመግባቢያ ሰነዶች በተጨማሪ የ50 ሚሊዮን ብር የኢንቨስትመንት ስምምነት ከኢትዮጵያ የነዋይ ዋስትና ሰነዶች ልውውጥ ጋር ተፈራርሟል፡፡ ከባንኩ ጋር የመግባቢያ ስምምነት የተፈራረሙት ተቋማት፣ ጨፌ ኦሮሚያ፣ የኢትዮጵያ መድን ድርጅት፣ የኢትዮጵያ ስራ አመራር  ኢኒስቲትዩት፣  የኦሮሚያ ጤና ቢሮ፣ የኦሮሚያ ኢንደስትሪ  ፓርኮች ኮርፖሬሽን ፣ቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ እና የኦሮሚያ ሴቶችና ህጻናት ጉዳይ ቢሮ ናቸው፡፡

የዳሸን ባንክ ባለአክሲዮኖች ባካሄዱት 30ኛው መደበኛ ጉባኤ የተመረጠውና የምርጫውም ውጤት በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የፀደቀለት አዲሱ የዳሸን ባንክ ቦርድ ባደረገው የመጀመሪያ ጉባኤ ላይ ባለፉት ሶስት ዓመታት ባንኩን በዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀ-መንበርነት ያገለገሉትን አቶ ዱላ መኮንንን በድጋሚ በዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀ-መንበርነት መርጧል፡፡   አዲሱ ቦርድ የካቲት 5 ቀን 2016 ዓ.ም በሸራተን አዲስ ሆቴል ባካሄደው ጉባኤ፣ ለቀጣይ ሶስት አመታት ዳሸን ባንክን በዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀ-መንበርነት እንዲያገለግሉ በድጋሚ የመረጣቸው አቶ ዱላ መኮንን፤ በአሁኑ ወቅት የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ የማዕድን ዘርፍ ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚ ሆነው በማገልገል ላይ ይገኛሉ፡፡   አዲሱ ሊቀመንበር አቶ ዱላ መኮንን የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በኤሌክትሪካል ኢንጅነሪንግ፣ እንዲሁም የማስተርስ ዲግሪያቸውንም በቢዝነስ አስተዳደር ከዚሁ ዩኒቨርሲቲ አግኝተዋል፡፡ በአግሪካልቸራል ምህንድስናም ዲፕሎማ አላቸው፡፡
 አዲስ የተመረጡት የቦርድ አባላት እና ባንኩን ላለፉት ሶስት ዓመታት ያገለገሉት የቦርድ አባላት የስራ ርክክብ ያደረጉ ሲሆን ንዑስ ኮሚቴዎችንም አዋቅረዋል፡፡ ባንኩ አዲስ ለተመረጡት የቦርድ አባላት አጠቃላይ የስራ እንቅስቃሴውን አስመልክቶ ገለፃ ሰጥቷል፡፡

የንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ታህሣሥ 18 ቀን 2ዐ16 ዓ. ም. የባንኩን ባለአክሲዮኖች 24ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በብሔራዊ ባንክ አመቻችነትና ታዛቢነት ባደረገው ምርጫ የተመረጡት የቦርድ አባላት ዝርዝር ጥር 24 ቀን 2ዐ16 ዓ. ም. በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ፀድቋል፡፡ በዚህም መሠረት አዲሱ ቦርድ ባንኩን የማስተዳደር ተግባሩን ከጥር 27 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ ሙሉ በሙሉ ተረክቧል፡፡
አዲሱ ቦርድ ባንኩ ያለበትን ከፍተኛ ተግዳሮት በመገንዘብ ፈጥኖ ወደ ሥራ በመግባት የራሱን አመራር እና የንዑስ ኮሚቴዎችን ድልድል በማካሄድ አቶ ሺሰማ ሸዋነካን በሊቀመንበርነት እንዲሁም ዶ/ር ወንድሙ ተክሌን በምክትል ሊቀመንበርነት መርጧል፡፡ በቀጣይም ቦርዱ፣ ባንኩ ያለበት አሁናዊ ሁኔታ ጊዜ የማይሰጥና ቀን ከሌት መስራትን እንደሚጠይቅ ከግንዛቤ በማስገባት የባንኩን ስምና ዝና  ወደነበረበት መመለስን እንዲሁም የባንኩን ዘለቄታዊ ጥቅም ማስጠበቅን ዋነኛ ግቡ ያደረገውን የባንኩን የመልሶ ማደራጃ የዘጠና ቀናት ዕቅድ (90 days Turnaround Plan) ተልሟል፡፡ ቦርዱ ከባንኩ የማኔጅመንት አባላት እስከዋና ክፍል ኃላፊ ድረስ  ካሉት የሥራ ኃላፊዎችም ጋር ትውውቅና ውይይት አካሂዷል፡፡ ቦርዱ በተጨማሪም እንደ ባንክ እንዲሰሩ ባሰባቸው ዝርዝር ጉዳዮች ላይ ማብራሪያ ሰጥቷል፡፡ በዚህም ቦርዱ የተለመውን የመልሶ ማደራጃ ዕቅድ ይፋ በማድረግ የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች በተረጋጋ መንፈስና በጥንቃቄ ሥራቸውን እንዲያከናውኑ መመሪያ አስተላልፏል፡፡ የቦርዱ ንዑሳን ኰሚቴዎችም ጊዜ ሳይሰጡ ከባንኩ የማኔጅመንት አባላት ጋር በቀረቡ ሪፖርቶችና በቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ውይይት አካሂደዋል፤ አቅጣጫም አስቀምጠዋል፡፡
አዲሱ ቦርድ የካቲት 6 ቀን 2ዐ16 ዓ. ም. ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዢ ከክቡር አቶ ማሞ ምህረቱ፣ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ምክትል ገዢ ከክቡር አቶ ሰሎሞን ደስታ እና ከሌሎች የባንኩ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ጋር ትውውቅ አድርጓል፡፡
በስብሰባውም ክቡር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዢ አዲሱ ቦርድ ከፊቱ የተደቀኑትን ተግዳሮቶች ግዙፍነት በአፅንዖት አስገንዝበው ሃላፊነቱን በልዩ ቁርጠኝነት እና በከፍተኛ የሃላፊነት ስሜት እና ፍጹም ታማኝነት እንዲወጣ በአፅንዖት አሳስበው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የአዲሱን ቦርድ የስራ አፈፃፀም በቅርበት እንደሚከታተልና እንደሚገመግም የባንኩ ገዢ በስብሰባው ላይ ጨምረው አስታውቀዋል፡፡  
በዋነኛነት ክቡር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዢ ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ በባንክ ሴክተር ቀደምት እና ጠንካራ ከሆኑት ባንኮች መካከል የሚመደብ መሆኑን አስታውሰው በቀጣይም አዲሱ ቦርድ ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ወደነበረበት ደረጃ በሚያደርገው ጉዞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ከጐኑ በመሆን በቅርበት ሁሉን አቀፍ ድጋፍ እንደሚሰጠው የባንኩ ገዢ አረጋግጠዋል፡፡
አዲሱ ቦርድ፤ የንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ከፍተኛ ተግዳሮት በገጠመው በዚህ ወቅት ከጐኑ በመሆን ፈተናዎቹን በስኬት እንዲወጣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እያደረገለት ለቆየው እና ወደፊትም ለሚቀጥለው ሁሉ አቀፍ ድጋፍ፣ ክትትልና ቁጥጥር ከፍተኛ አክብሮቱን እና ላቅ ያለ ምስጋናውን በባንኩ ማህበረሰብ ስም ማቅረብ ይወዳል፡፡

Page 6 of 695