Administrator

Administrator

Saturday, 28 September 2013 13:28

ዴንጌሣት

ዴንጌሣት - የልጅ እሳት
ዴንጌሣት - የልጅ መብራት…
የባህል ችቦ መቀነት
ከዘመን ዘመን ማብሰሪያ፣የመስቀል ብርሃን “ኬር” በሥራት፡፡
“በእሳት አትጫወት” ይላል አበሻ ልጁን ሲያሳድግ
ዴንጌሣትን ባያውቀው ነው፤ የጉራጌን ባህልና ወግ
ገና በጥንስስ በጭሱ፣ መስቀልን እንደሚታደግ
በችቦ ማህል ተወልዶ፣ ንግዱን እንደሚያንቦገቡግ
በእሳት አልፎ እሳት ሲሆን
አላየውም ጉራጌውን
ዴንጌሣት ነው የዚህ እርከን!
ጉራጌ የላቡን ሠርቶ
ዓመቱን በንግዱ ገፍቶ
በፍቅሩ ልጆቹን አይቶ
የለማው በፊናው ለፍቶ
የተገፋውም ተገፍቶ፤
ላንደኛው አዱኛ በርቶ
ያንዱ መክሊቱ ከስቶ
ያም ሆኖ በቀኑ ተግቶ
መስቀሉን በዕድሜው አብርቶ
የልጅ - እሳት፣ የዴንጋ - እሳት፤ ለምለም ጨረር ይዞ መጥቶ
ይሄው በመስቀል ወር ጥቢ፣ ኬር! ይላል የዓመቱን ንጋት
ኬር! ይላል የዓመቱን ብሥራት
ፍሬው በስሎ፣ ቅርሱ ሲያብብ፤ ማየት ነው ያገሬው ኩራት
ዴንጌሣት የልጆች ምትሃት
ጐርፍ ላይ የሚሄድ እሳት
ዓመቱን እንደብጤቱ፣ ሰው መቼም አቅሙን ለክቶ
እንደየርምጃው ነውና፣ የሚሄድ ብርሃን አይቶ
እንደዘመን እንደ ዓመሉ…ነግዶም አርሶም አምርቶ
ወይ ጀግኖ አሊያም ፈርቶ
ወይ ሸሽቶ ወይ ዝቶ ኮርቶ
ወይ ተኮራርፎ ወይ ታርቆ
ወይ ከስሮ ወይ አንሰራርቶ
አትርፎ ወይ “ፓሪ” ወጥቶ
በጋን እንደበጋ ፀሐይ፣ ክረምትን እንደዶፍ ዝናብ
ሁሉን ችሎ ሁሉን አዝሎ፣ ሁሉን የንግድ አጀብ ወጀብ
ተቀብሎ ታግሎ፣ ጥሎ፤
አቀርቅሮ ቀና ብሎ
የተስፋ ጐሁን በችቦ፣ ቀዶ በዴንጌሣት ፍካት
በዝናብ ውጋገን እሳት
የመስቀል ደመራ ዜማ
ያውዳመት ሆታ ዋዜማ
የልጆች ርችት ማማ
አገር ሲታጠር በአበባ
የኮከቦች ሳቅ ሲተባ
የማይሞት የማይነቀል
ኗሪ የጉራጌ ባህል፤
እንደህፃን ፍልቅልቅ ፊት፣ እነደመስክ ብርሃን ወለል፤
መስከረም ወር ፍንትው ሲል፣
ገጠር ከተማውን ዳብሶ፣ ዴንጌሣት ዙሪያ ይሞላል!
ዴንጌሣት የፍቅር እሳት
የልጅ መቅሰስ ያዋቂ እራት
ነግ እንዲያበራ ይህ ልማድ፣ መስቀል - ወፍ እንድትዘምረው
ምራቅ የዋጥን፣ ልማድ ያቀፍን፤
አሻግረን እንለኩሰው
ለአገር ልጅ እናስረክበው
ጐዶሏችንን እንሰብስብ፣ ሙሉማ አለ በጃችን
ዘለዓለምን ለማሸነፍ፣ ብርሃን ነው መሣሪያዎችን !
ሁሌም ዴንጌሣት ለማየት፣ አሁን ያለን እንበቃለን፡፡
ይህን የልጆች ህብር እሳት፣ እጅ በእጅ እንለኩሰው
ወትሮም በእፍኝ ጭራሮ ነው፣ አገር - ምድሩ የሚበራው
ባህል የሚኖር እንዲህ ነው፣ ትውልድ የሚጫር በዚህ ነው!
አገር ማለት ዴንጌሣት ነው!
ኬር እንሁን ኬር እናርገው!
የጉራጌ ብርሃን ህልም፣ እዚህ ጋ ነው ትርጉም ያለው፡፡
ዴንጌሣት የልጅ አገር ነው፤
አገር ማለት ዴንጌሣት ነው፡፡
መስከረም 14/2006
(ለዴንጌሣት በዓልና ባህሉን ለሚያከብሩ)

 

ላለፉት 12 ዓመታት ኢትዮጵያን በርዕሰ ብሔርነት የመሩትና በሚቀጥለው ሳምንት ስልጣን የሚያሥረክቡት ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስን የሚዘክር የፎቶግራፍ አውደርእይ ባለፈው ረቡዕ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ትያትር ቀረበ፡፡ አውደርዕዩ ፕሬዚዳንቱ በስልጣን ላይ ሳሉ ያከናወኗቸውን ተግባራት እንደሚያስቃኝ “ታሪኳ ኤቨንት ኦርጋናይዘር” አስታውቋል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን የቅርስ ጥበቃና የቤተመጻሕፍት ወመዘክርና ቱሪዝም መምርያ፤ በፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ሊወገዱ የነበሩ ሦስት ጥንታዊ የብራና መጻሕፍትን ተረከበ፡፡ እንደ መምሪያው ገለፃ፤ ከቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ጊዜ ጀምሮ በቬርባል ሲገላበጡ ቆይተው ለመወገድ በዝግጅት ላይ የነበሩት የብራና መፃሕፍት የተገኙት በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አባል ጥቆማ ነው፡፡ መጻሕፍቱ በፖሊስ ኮሚሽን ግምጃ ቤት እንደሚገኙ በጠቆሙን መሰረት ተጻጽፈን ባለፈው ሰኞ መጻሕፍቱን ተረክበናል ብለዋል - የመምርያው ሃላፊ መምህር ሰለሞን ቶልቻ፡፡ የተገኙት የብራና መጽሐፍት እያንዳንዳቸው ከ200 ገጽ በላይ ሲሆኑ፤ መፃሕፍቶቹም ድርሳነ ኡራኤል፣ ድርሳነ ማህየዊ እና ድርሳነ ሚካኤል ናቸው፡፡ መምርያቸው ተመሳሳይ ሥራዎችን እየሰራ መሆኑን ሃላፊው ገልፀዋል፡፡

ደቂቀ ኤልያስ፣ ማህበረ ቅዱሳን፣ ተሀድሶ … እርስበርስ ይናከሳሉ

ወሃቢያ፣ ሰለፊያ፣ አህበሽ … አንዱ ሌላውን እየወነጀለ ይናጫሉ

የአዲሱን አመት አዝማሚያ ታዝበን እንደሆነ፣ እንደአምናው ዘንድሮም “ከሃይማኖት ጣጣዎች” በቀላሉ እንደማንላቀቅ ያስታውቃል። ግን ብዙም አሳሳቢ የሆነብን አይመስልም። ከአወሊያ ትምህርት ቤት እና ከእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ምርጫ ጋር ተያይዞ ባለፉት ሁለት አመታት እየተባባሰ የመጣው ችግር ስጋት ቢፈጥርብንም፣ የአደጋው መጠንና ስፋት ያን ያህልም በግልፅ አልታየንም። ወይም ለማየት አልፈለግንም። ለምሳሌ፣ “ነብይ ኤልያስ ዓለምን ሊፋረድ በእሳት ሰረገላ መጥቷል” በማለት እነ ጀማነሽ ሰለሞን በሚያካሂዱት ስብከት ላይ የተፈጠረው ውዝግብ ብዙም አላስጨነቀንም። “መስቀል ከሰማይ ወረደ” ተብሎ በተጀመረው እንቅስቃሴ ዙሪያ የተከሰተው እንካሰላንቲያ ያን ያህልም አያሳስበንም። ነገር ግን፣ በጊዜ ካላሰብንባቸውና መፍትሄ ካላበጀንላቸው፣ ክፉ መዘዝ ማስከተላቸው አይቀርም።

የዛሬ ፅሁፌም፣ “ደቂቀ ኤልያስ፣ ማህበረ ቅዱሳን፣ ተሀድሶ…” በሚሉ ጎራዎች እየተለኮሱ የሚቀጣጠሉ የሃይማኖት ጣጣዎች ላይ ያተኮረ ነው። የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ተከታይ መሆናቸውን በሚገልፁት በእነዚህ ጎራዎች መካከል የተጧጧፈው የውግዘትና የውንጀላ ውርጅብኝ ይዘገንናል። በከፊል እየቀነጨብኩ አቀርብላችኋለሁ። የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ መሆናቸውን የሚናገሩ ሰዎችም ውስጥ፣ ወሃቢያ፣ ሰለፊያ፣ አህበሽ… በሚሉ ጎራዎች ተቧደነው፣ አንዱ በሌላው ላይ የሚያዘንቡት የውግዘትና የውንጀላ ዶፍ ያሰቅቃል። ትችቶቻቸው እንደ እሬት የመረሩ፣ ክርክሮቻቸውም እንደ እሳት የሚጋረፉ መሆናቸው አይደለም የሚያስፈራው። በሰዎች መካከል የሚደረግ የሃሳብ ክርክርትና ትችት ከልኩ አያልፍም። “ካልደረሰብህ ጫፉን አትንካ” የሚባል የመብትና የነፃነት ድንበር ይበጅለታላ። የሃይማኖት ተከራካሪዎች ግን፣ የሃሳብ አለመግባባትን የፍፃሜ ጦርነት ያስመስሉታል። ለዚያውም ጦርነቱ “ተራ የሰዎች ግጭት” አይደለም። ፈጣሪና ሰይጣን የሚፋለሙበት ጦርነት ነው! ተሸፋፍኖ የቆየውና አስፈሪው የሃይማኖት ጣጣም፣ በዚህ ምናባዊ የፈጣሪና የሰይጣን ጦርነት አማካኝነት በግልፅ መታየት ይጀምራል። እንዴት ቢባል፤ …በጦርነቱ መሃል፣ የሰው ልጅ ከእንሰሳትና ከእፀዋት የተሻለ ክብር አይሰጠውም።

በቃ፣ እንደ አህያ ጭነው የሚነዱት የጋማ ከብት፣ እንደ ቀርከሃ መልእክት የሚያስተላልፉበት ቱቦ ሆኖ ያርፈዋል። የሰው አእምሮ ጥልቅና ረቂቅ እውነቶችን የማወቅ አቅሙ ኢምንት ነው ተብሎ ሲሰበክ አልሰማችሁም? የጊዜያዊ ስሜትና የብልጭልጭ ነገሮች እስረኛ ስለሆነ ለራሱ የሚበጀውንና የሚጠቅመውን ነገር አጥርቶ መለየት አይችልም፤ ያለ እረኛ ተስፋ የለውም ተብሎ ሲሰበክስ አላደመጣችሁም? “ሰውማ ምን አቅም አለው? ደካማና ከንቱ ፍጡር!” የሚል ፅሁፍስ አላነበባችሁም? ብዙውን ጊዜ በሃይማኖት ስብከት ውስጥ፣ የሰውን ልጅ የሚገልፁት እንደ ምርኮኛ ወይም እንደ ባሪያ አድርገው ነው። ሁሉንም አለመግባባትና ውዝግብ፣ “የፈጣሪና የሰይጣን ጦርነት” ሆኖ የሚታያቸውም በዚህ ምክንያት ይመስለኛል። አንደኛ ነገር፤ የሰው ልጅ፣ በአእምሮው አገናዝቦ እውነትንና ሃሰትን የማወቅ አቅም የሌለው ቀልበ ቢስ ፍጡር ከሆነ፣ የፈጣሪን ወይም የሰይጣንን ቃል በጭፍን ተቀብሎ ከማመን ውጭ ምንም ማድረግ አይችልም።

ሁለተኛ፤ የሰው ልጅ፣ በአእምሮው አመዛዝኖ ጥሩና መጥፎውን ለይቶ የመምረጥና የመወሰን አቅም የሌለው ዱካ ቢስ ፍጡር ከሆነም፣ የፈጣሪ ወይም የሰይጣንን መመሪያዎች በታዛዥነት ከመከተል ውጭ አማራጭ አይኖረውም። ሦስተኛ ነገር፤ ሰው ሲባል በጥቅሉ፣ እውነትን አገናዝቦ በማወቅና መልካምነትን አመዛዝኖ በመምረጥ ስኬታማ ሕይወትን የመቀዳጀት አቅም የሌለው፣ ጎደሎና መናኛ፣ ደካማና ክብረ ቢስ ፍጡር ከሆነ፣ እጣፈንታው ምን ሊሆን ይችላል? የሰይጣንን ቃል ተቀብሎ በተላላኪነት የሚያገለግል ምርኮኛ ወይም የፈጣሪን ቃል ተቀብሎ በታዛዥነት የሚያገለግል ባሪያ! አሃ፤ ከአህያና ከቀርከሃ የተሻለ ክብር ለሌለው ፍጡር፣ መብትና ነፃነት ማክበር የሚባል ነገር ሊነሳ አይችልማ። “የሰይጣን መብትና ነፃነት” ብሎ ነገር ይኖራል እንዴ? “ሰይጣን ለሚጋልበው አህያስ”፣ መብትና ነፃነቱን እናከብርለታለን? አያችሁ! የሃይማኖት ክርክር ድንበር የለሽ ነው። ልክ ሊበጅለት አይችልም። አንደኛው ጎራ ሌላኛውን፣ “የሰይጣን መሳሪያ!” እያለ ሲያወግዝ በጣም ሊያሳስበን የሚገባውም በዚህ ምክንያት ነው። “አንተ የዲያብሎስ መልእክተኛ! አንቺ የአውሬው ቅጥረኛ!” እየተባባሉ መወነጃጀል ሲበራከት፣ መስጋት አለብን። ውዝግባቸውን በጣም አለዘብኩት መሰለኝ።

ቃል በቃል ክርክራቸውንና ንግግራቸውን ባቀርብ ይሻላል። በሌላ ጊዜ፣ “ወሃቢያ፣ ሰለፊያ፣ አህበሽ…” በሚል የሚወራወሩትን ውንጀላና ውግዘትን ለማሳየት መሞከሬ ባይቀርም፣ ለዛሬ ግን ከላይ እንደጠቀስኩት “ደቂቀ ኤልያስ፣ ማህበረ ቅዱሳን፣ ተሃድሶ…” በሚለው ዙሪያ ላይ ነው የማተኩረው። ነብይ ኤልያስ አለምን ሊፋረድ በእሳት ሰረገላ መጥቷል በማለት የሚሰብኩት እነ ጀማነሽ ሰለሞን፣ “ማህበረ ሥላሴ ደቂቀ ኤልያስ” በማለት ራሳቸውን ሰይመው ያሰራጩትን ፅሁፍ በመጥቀስ ልጀምር። “እነሆ ለዘመናት የተጠበቀው ትንቢት ተፈጽሞላት፣ ኢትዮጵያ ዓለምን በተዋህዶ የምትገዛበት ሰአት ላይ ቆመን ይህንን ታላቅ አስፈሪ የቅዱስ ኤልያስ ምስጢር ስናውጅላችሁ በታላቅ ደስታና ሐሴት ነው። … ዓለማችንን እየገዛ ካለው አውሬ ይታደገን ዘንድ ቅዱስ ኤልያስን የላከልን… የኢትዮጵያ አምላክ ልዑል እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን። … ይህ ጹሑፍ ለአመጸኞች የሚያቃጥላቸው… እንደመብረቅ የሚያስደነግጣቸው ሊቋቋሙት የማይቻላቸው እሳት ነው” ጽሑፉ ከፈጣሪ እንጂ ከሰዎች የመነጨ እንዳልሆነ በመግለጽ አንባቢዎችን ሲያስጠነቅቅም፣ “…ከልዑል መለኮታዊ መንበር የታዘዘና የተላለፈ ኃይለ ቃል ነው። ስለዚህ ማንም ቢሆን በትህትና… የቅዱስ ኤልያስን መርህ መከተል ይገባዋል” ይላል።

ለምን? ፅሁፉ ምላሽ ይኖረዋል። ቅዱስ ኤልያስ ሁሉንም ነገር ሊያፀዳ በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ ይዞና ሌሎችንም አሰልፎ ነው በእሳት ሰረገላ የመጣው። የሆነ ሆኖ፣ “ማኅበረ ሥላሴ ዘደቂቀ ኤልያስ” ጳጉሜ 1 ቀን ያሰራጨው ጽሑፍ በዚህ ማስጠንቀቂያ ወደ ዋና ፍሬ ነገሮች ይቀጥላል። በቤተክርስትያኗ ስም ላይ፣ “ኦርቶዶክስ” የሚለው ቃል በሰይጣን ተንኮል የተጨመረ ስለሆነ መወገድ እንዳለበት የሚገልፀው ይሄው ፅሁፍ፣ የሰንበት በዓል መከበር ያለበት በቅዳሜ እለት እንጂ በእሁድ መሆን እንደሌለበት ያሳስባል። የሰንበት ትምህርት ቤቶች እና ማህበረ ቅዱሳን የተሰኙት ተቋማትም የሰይጣን ስራዎች ስለሆኑ መፍረስ እንዳለባቸው ፅሁፉ ያስጠነቅቃል። ቤተክርስትያኗ በአለም አብያተ ክርስትያናት ማህበር ውስጥ በመግባት በሰይጣንና በአውሬው ሴራ ውስጥ ተካፋይ ሆናለች በማለት እያወገዘም፣ ከማህበሩ እንድትወጣ ያሳስባል። እንግዲህ አስቡት። ነብይ ኤልያስ በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ ይዞ በእሳት ሰረገላ እንደመጣ “ደቂቀ ኤልያስ” ነግረውናል። እውነት መሆኑን አምነን እንድንቀበልም ይጠብቃሉ።

ለምን? የሰው አእምሮ በራሱ አቅም እውነትን የማወቅ አቅም የለውም። ስለዚህ የፈጣሪን ቃል ተቀብሎ ማመን የግድ ነው። “ከፈጣሪ የመነጨ ቃል” ሲባል፣ በሌላ አነጋገር ከእነ ጀማነሽ የሰማነውና ያነበብነው ቃል ማለት ነው። የነሱን ቃል አምነን ካልተቀበልን፣ የሰይጣንን ቃል የምንከተል ርጉማን እንሆናለን። “እሁድን ሳይሆን ቅዳሜን አክብሩ፣ ያኛው ማህበር ይበተን፣ ከዚያኛው ውጡ…” የሚሉ መመሪያዎችን ሲያቀርቡም፣ “ለምን አላማና በምን መነሻ? ጥቅሙና ጉዳቱስ? በምን መመዘኛ?” ብሎ መመራመርና መፈተሽ አይኖርብንም፤ በሰው አቅም አይቻልማ። ከአቅመ ቢሱ የሰው ልጅ ሳይሆን ከፈጣሪ የመነጨ መመሪያ ስለሆነ በታዛዥነትና በትህትና መከተል ይገባል ብለዋል ደቂቀ ኤልያስ። በሌላ አነጋገር፣ በደቂቀ ኤልያስ የተሰራጨውንና ያነበብነውን መመሪያ በታዛዥነት መከተል ይጠበቅብናል ማለት ነው። እነሱ የነገሩንን በእምነት ለመቀበል እና መመሪያቸውንም በታዛዥነት ለመከተል ፈቃደኛ ያልሆነ ሰውስ? በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ ተብሎ በፅሁፉ ውስጥ የተጠቀሰው ነገር፣ ለእንዲህ አይነቱ “የሰይጣን አገልጋይ አመፀኛ ሰው” መፍትሄ ይሆናል በሚል ሃሳብ ይመስላል። በጭካኔ ጭፍጨፋ ፈፅማለች ተብላ የምትጠቀሰው “ዮዲት ጉዲት”፣ ቤተ መቅደስ ላይ ተሹመው ይሳለቁ የነበሩትን ካህናት ከመጻህፍቶቻቸው ጋር ቤተ መቅደሳቸውን ያፈራረሰችና ያጠፋች ቅደስት ሴት ናት በማለት ያደንቋታል - ደቂቀ ኤልያስ። እንዲህ አይነቱ ውዳሴ አስገራሚ ሊሆንባችሁ ይቻላል። ነገር ግን፣ “የምንነግራችሁን ነገር በጭፍን አምናችሁ ተቀበሉ።

የምሰጣችሁን መመሪያ በታዛዥነት ተከትላችሁ ፈፅሙ” ብሎ የሚጀምር ስብከት፣ ዞሮ ዞሮ አፈናን፣ ጭካኔንና እልቂትን ወደ ማወደስ ማምራቱ አይቀሬ ነው። በዚህ ካልተስማማችሁ፣ ይህን ጥያቄ መልሱልኝ። ዮዲት፣ ከሃይማኖት ወጥተዋል ወይም አፈንግጠዋል ያለቻቸውን ሰዎች ከነንብረታቸው ካጠፋቻቸው፣ እንዴት ቅድስት ተብላ ትወደሳለች? ድርጊቷ እንደ ወንጀል ሳይሆን እንደፅድቅ ተቆጥሮ በአድናቆት ሲሞገስ ምን ትላላችሁ? ነውጠኛነት ነው። ደቂቀ ኤልያስ ባሰራጩት ነውጠኛ ፅሁፍ ላይ ከየአቅጣጫው በርካታ ትችቶችና ወቀሳዎች፣ ከዚያም አልፎ ውግዘቶችና ውንጀላዎች መሰንዘራቸው ላይገርም ይችላል። አሳዛኙ ነገር፣ አብዛኛው ትችትና ውግዘት የተሰነዘረው “በፅሁፉ ነውጠኛነት” ላይ አይደልም። መምህር ምህረተአብ አሰፋ፣ ደቂቀ ኤልያስን ባወገዙበት ስብከታቸው፣ ነብይ ኤልያስን እንዲህ ሲሉ በአድናቆት ገልፀውታል - “በቂሶም ወንዝ 450 የባዕድ ነቢያትን ያሳረደ፣ ስለ እግዚአብሄር ክብር የቆመ ነብዩ ኤልያስ!”።

እንግዲህ በተሳሳተ መንገድ ይሰብካሉ የሚባሉትን ሰዎች ማስገደል ለሙገሳ የሚያበቃ ከሆነ፣ ከሃይማኖት አፈንግጠዋል ያለቻቸውን ካህናት በመግደሏና ንብረታቸውን በማውደሟ፣ “ቅድስት ዮዲት” ብትባል ምን ይገርማል? ለማንኛውም፣ በ“ደቂቀ ኤልያስ” ከተሰራጨው ነውጠኛ ፅሑፍ ጥቂት ልጨምርና፣ መምህር ምህረተአብ፣ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት እንዲሁም በማህበረ ቅዱሳን መፅሄት ወደ ታተሙ ምላሾች ልሻገር። “ኦርቶዶክስ” የሚለው ስያሜ ከሰይጣን ተንኮል የመጣ ነው በማለት የውግዘት ውርጅብኝ የሚያዘንበው የደቂቀ ኤልያስ ፅሑፍ፤ “…በግሪክ ቋንቋ መዝገበ ቃላት ውስጥ፣ ‘ቀጥተኛ ሃይማኖት’ የሚል ፍቺ ቢሰጠውም፣ በዓለም ሕብረተሰብእ ዘንድ ግን ‘አክራሪ፣ አውቃለሁ ባይ፣ ጊዜው ያለፈበት፣ የቆየ’ … የሚል አሉታዊ ትርጉም ያለው ቃል ነው” ይላል። “…ኦርቶዶክስ የሚለው ስያሜ ለቤተ ክርስቲያናችን መቼ፣ እንዴት፣ በእነማን፣ ለምን አላማ ሊሰጣት ቻለ የሚሉትን መጠይቆች ስንመረምር… በቤተክርስቲያን ላይ ሰይጣን የቀመመው መርዛማ ተንኮል፣ አውሬው ያቀናበረው ስውር ደባ መኖሩን እናስተውላለን። …የሮም መናፍቃን ለራሳቸው ‘ካቶሊክ’ (ማለትም አንዲት፣ ሐዋርያዊት፣ ዓለምአቀፋዊት ቤተ ክርስቲያን) የሚል ስያሜ ወስደው፣ ከእነሱ የተለዩትን ምስራቅ አውሮፓውያንን ለመንቀፍ የተጠቀሙበት ስያሜ መሆኑን እናስተውላለን።

…ኦርቶዶክስ የመናፍቃን ስያሜ ነው። እመቤታችንን የሰው እንጂ የአምላክ እናት አይደለችም በሚለው የንስጥሮስ… መንገድ፣ ክርስቶስ ሁለት ባህርይ ነው ብለው ክደው፣ ንጹሐን ኢትዮጵያውያንን እነ ቅዱስ ዲዮስቆሮስን ያሳደዱ የምስራቅ አውሮፓ፣ የግሪክ፣ የሩስያ… መናፍቃን ስያሜ ነው። ታዲያ… እኛ [ላይ እንዴት] ኦርቶዶክስ የሚል ስያሜ ሊለጠፍብን ቻለ ቢሉ፣ ጠላታችን ዲያብሎስ በአውሬው ላይ አድሮ የቤተ ክርስቲያንን መሪዎች በቁጥጥሩ ስር ለማድረግ የተጠቀመው ረቂቅ ተንኮል መሆኑን እናስተውላለን። …አውሬው፣ እረኞችን ከተኩላ፣ ስንዴን ከእንክርዳድ ለመቀላቀልና ብዙዎችን ግራ አጋብቶ ለማጥመድ ባዋቀረው ተንኮል፣ ቤተክርስቲያን ኦርቶዶክስ በሚል ስያሜ ስትጠራ ኖራለች” በደቂቀ ኤልያስ የተሰራጨው ፅሑፍ፣ አብዛኛውን ነገር የሚያወግዘው፣ “የሰይጣን መርዝ፣ የዲያብሎስ ተንኮል፣ የአውሬው ሴራ”… የሚሉ ውንጀላዎችን በማዥጎድጎድ ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ ማህበር እንዲሁም የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ማህበር የተቋቋሙት፣ በሰይጣንና በአውሬው ተንኮል ነው በማለት ይኮንናቸዋል። “ቤተክርስቲያን፣ ከልዑል እግዚአብሔር ያገኘችውን፣ ከነቢያን ከሐዋርያት የተረከበችውን ንጹህ ቃለ እግዚአብሔር በጥንቃቄ አዘጋጅታ ልጆችዋን መመገብ ሲገባት፣ መርዛማ ጥርጥር ከሚነዙ መናፍቃን ጋር መጽሐፍ ቅዱስን ለመጻፍ ማኅበር መግባትዋ፣ ለብዙዎች ማሰናከያ ወጥመድ ሆኑዋል።

… መናፍቃንን ገስጸ የሰው ልጆችን ሁሉ ወደ ተዋህዶ እቅፍ እንዲገቡ ማድረግ ሲገባት፣ በገንዘብ ፍቅር ላይ የተመሰረተ ወዳጅነት ከመናፍቃን ጋር መመስረቷ፣ ለብዙዎች መውደቅና በአውሬው መማረክ ምክንያት ሆኗል” አለምን የሚገዛ አውሬ፣ የዓለም መንግስታትንና የቤተክርስቲያን መሪዎችን ለመቆጣጠር “የረቀቁ ተንኮላዊ ስልቶችን” እንደሚጠቀም የሚያትተው የደቂቀ ኤልያስ ፅሁፍ፣ ማህበረ ቅዱሳን እና የሰንበት ትምህርት ቤቶች በሰይጣን ተንኮል ለአውሬው ስውር አላማ የተቋቋሙ ናቸው ሲል ያወግዛል። እግዚአብሄር ስድስት ቀናትን ሠርቶ ያረፈባት ሰባተኛዋ ቀን ቅዳሜ ሰንበት ተብላ እንድትከበር እንዳዘዘ ጽሑፉ ጠቅሶ፣ በቅዳሜ ፋንታ እሁድ (የፀሐይ ቀን) ሰንበት ተብሎ እንዲከበር የተደረገው የፀሐይ አምልኮን በመከተል ነው ይላል። ደቂቀ ኤልያስ ያሰራጩት ፅሁፍ እንደሚተርከው ከሆነ፣ ሰይጣን ያልሰራው ነገር የለም። ቅዱስ ኤልያስም ሁሉንም ነገር ሊያፀዳ በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ ይዞ ሌሎችንም አሰልፎ መጥቷል ይላል። የሰይጣን መልእክተኞች፣ የዲያብሎስ ታዛዥ፣ የአውሬው አገልጋይ በማለት ያወገዟቸውን ነገሮች ለማጥፋት መሆኑ ነው። እንግዲህ፣ ከዚህ በኋላ የሚቀረን፣ ደቂቀ ኤልያስ ላይ የተሰነዘረውን ትችት ማቅረብ ነው። ትችት ብቻ ሳይሆን ውግዘትና ውንጀላ ጭምር ነው የዘነበባቸው - ደቂቀ ኤልያስም በተራቸው “የሰይጣንን ቃል የሚሰሙ፣ በሰይጣን ቅናት የሚመሩ፣ ሰይጣናዊ ስውር አላማ የያዙ፤ ቤተክርስትያንን ለማጥፋት የሚያሴሩ ጠላቶች” ተብለው ተኮንነዋል። ለሳምንት እናቆየው።

“መመሪያን ማውጣት የፓርላማ ስልጣን ነው”

ከምክትል ኮሚሽነር ግርማ ካሳ የሰማነው፤ ስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ዕውቅና ቢያገኝም የመኪና ላይ ቅስቀሳ፣የበራሪ ወረቀት መበተን፣ ፖስተር መለጠፍና ፊርማ ማሰባሰብን በተመለከተ ከልዩ አካል ፍቃድ ያስፈልጋል የሚል ነው፡፡ ከልዩ አካል ይባል እንጂ ልዩ አካሉ ማን እንደሆነ ግን አልነገሩንም፡፡ ፍቃድ ሳይኖራችሁ የመኪና ቅስቀሳና የመሳሰሉትን ማድረግ ህገወጥ ስለሆነ እርምጃ እንወስዳለን ብለውናል፡፡ ግን በቃል ነው የነገሩን፤ ዶክመንቱን አሳይተውናል፤ ኮፒ አድርገው ሊሰጡን ግን አልቻሉም፡፡ መመሪያ ሲወጣ ለሚመለከታቸው አካላት ማሳወቅ አለባቸው፡፡ መመሪያውን በማተም ፓርቲዎችንም ህብረተሰቡንም ማሳወቅ ይገባቸዋል፡፡ እነሱ የፈለጉት ግን የእኛን እንቅስቃሴና የምናደርገውን ዝግጅት ማነፍነፍ ነው፤ የሚሳተፉ ሰዎችን ማንነትና መፈክሮቻችንን ማወቅ ይፈልጋሉ፡፡ እንደዚህ አይነት ህጎች የአዋጅና የህገመንግስት ጉዳይ ስለሆኑ የአዲስ አበባ መስተዳደር ይቅርና መንግስትም ማውጣት አይችልም፤ ፓርላማ ቀርቦ መፅደቅ አለበት፡፡ አዲሱን መመሪያ በተመለከተ ምርጫ ቦርድም ሄደን “ ስለመመሪያው ታውቃላችሁ?” ብለን ጠይቀናቸው እንደማያውቁ ነግረውናል፡፡ እነሱም ተገርመዋል፤ “እኛም ትክክል እንዳልሆነ ተረድተናል።

ስለዚህ መመሪያ የአዲስ አበባ መስተዳደር ጠይቀን ያገኘነው መልስ፤ “የአዲስ አበባ ካቢኔ ወስኖ ከንቲባው ስላልፈረመበትና ማተሚያ ቤት ስላልገባ ኮፒ ልንሰጣችሁ አንችልም” የሚል ነው፡፡ በጎን ግን ለክፍለ ከተሞችና ለፖሊሶች ተሰጥቷል፡፡ የፅህፈት ቤት ሃላፊው መጀመሪያ ስንሄድ ይህንን ጉዳይ እየተነጋገርበት ነው አሉ ለሁለተኛ ጊዜ ስንሄድ ደግሞ መመሪያው የሚወጣው ለኩባንያዎችና ለንግድ ድርጅቶች እንጂ ለፖለቲካ ፓርቲዎች አይደለም አሉን፡፡ ፖሊስ እንዲህ እያለን ነው ስንላቸው ደግሞ ሃላፊው፤ “ግዴለም እኔ ከከንቲባውም ሆነ ከአዲስ አበባ ፖሊስ ሃላፊዎች ጋር ተነጋግሬያለሁ” ብሎ ነበር፡፡ “ችግር ከተፈጠረ አስታውቁን” አለ፡፡ ችግሩ ግን ይህንን ፖሊሶች፣ ክፍለከተሞችና ደህንነቶች አላወቁም ነበር፤ ስለዚህ ሰሞኑን ቅስቀሳ ስናደርግ ሶስት መኪኖች ታስረዋል፡፡ ቅስቀሳ ሲያደርጉ የነበሩ ሰላሳ አባላቶቻችንም ታስረው ነው የተለቀቁት፡፡ ከ9 ሰዓት እስከ 11ሰዓት ታስረው ነበር፡፡ ይህ የህግ መፃረር ብቻ ሳይሆን ከህዝቡ ጋር እንዳንገናኝና ሃሳባችንን እንዳናሳውቅ እየተደረግን ነው፡፡ የመድብለ ፓርቲ ስርዓት ይቁም እንደማለት ነው፡፡ ይሄን ሰላማዊ ሰልፍ ለመስከረም 19 ቀን 2006 ዓ.ም ለማድረግ አሳውቀን ነበር፤ ነገር ግን እኛ ሰልፉን ለማድረግ ያሰብነው በመስቀል አደባባይ ነበር፡፡ መስተዳደሩ ቅድሚያ የምንሰጠው ለልማት ነው በማለት መስቀል አደባባይን እንድንቀይርና ሌላ አማራጭ ቦታዎችን እንድንነግራቸው ጠየቁን፡፡ እኛም ኢትዮ - ኩባ ፓርክ፣አራት ኪሎ፣ስድስት ኪሎና ቴዎድሮስ አደባባይን እንደ አማራጭ አቀረብን፡፡ እነሱ ግን ይህንን አንፈቅድም በማለት በራሳቸው ፈቃድ ጃንሜዳ ብለው ወሰኑ፡፡ ይሄም ብቻ ሳይሆን ከቢሮአችሁ ተነሱና በዚህ መንገድ አድርጋችሁ ብለው ሰዓታችንን እና መነሻ ቦታችንን ወስነው ነገሩን፡፡ ጃንሜዳ አንደኛ ለትራንስፖርት አይመችም፤ ሜዳው ረግረግ ነው፡፡ ቦታው የንግድና የመኖሪያ ቤቶች በስፋት የሚገኙበት ነው፡፡ አዋጅ አንቀፅ 7 ንዑስ አንቀፅ 2፤ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ከማህበራዊ እንቅስቃሴዎች፣ ከት/ቤቶች፣ ከሆስፒታሎችና ከመኖሪያ አካባቢ 100 ሜትር መራቅ አለበት ይላል፡፡ ከወታደራዊ ካምፕ ደግሞ 500 ሜትር መራቅ እንዳለበት ህጉ ያዛል፡፡ ለእኛ የወሰኑልን ቦታ ግን በአጥር የሚገናኙ ሆስፒታል እና የጦር ካምፕ ያሉበት ነው፡፡ ያቀረብናቸውን አማራጮች ከልክለውን ይሄንን ቦታ ተጠቀሙ ብለውናል፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ የአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር “አዲሱ መመሪያ በመውጣቱ ምንም አይመጣም” አዲስ መመሪያ መውጣቱን ሰምቻለሁ ግን ከቁም ነገር አልቆጥረውም፡፡ ምክንያቱም የህገመንግስቱ አንቀፅ 9/1፤ “ይህ ህገመንግስት የአገሪቷ የበላይ ነው፤ ከዚህ ውጪ የሆነ ልማዳዊ አሰራር አዋጅም ደንብም የባለስልጣን መመሪያም ተቀባይነት የለውም” ነው የሚለው፡፡ ይሄንን ቢያደርጉም ባያደርጉም ተቀባይነት ስለሌለው እኔ እንደ ቁም ነገር አልቆጥረውም፡፡ እየሰራ ያለው መመሪያው ሳይሆን ጉልበት ነው፡፡ እኛ ለእሁድ ሰላማዊ ሰልፍ ስንዘጋጅ ቅዳሜ ይሄንን ቢሮ ገብተው ዘረፉ፡፡ አራት መቶ የምንሆን ሰላማዊ ሰልፍ አስተባባሪዎች ነበርን፡፡ ከየአቅጣጫው የሚመጡት ሰልፈኞች ከእኛ ጋር እንዳይገናኙ፡፡ በመኪናና በፖሊስ መንገዱን ዘጉት፡፡ እኛም ወደ መስቀል አደባባይ እንዳንሄድ አገዱን፡፡ እናም እዛው ጋ ትንሽ ንግግር አድርገን ሰላማዊ ሰልፉ ሳይካሄድ ተመለስን፡፡ የዚህ አይነት አገዛዝ ባህሪው ይሄ እንደሆነ ሁላችንም እናውቃለን፡፡ ስለዚህ የእኛ ሰላማዊ ትግል ይቀጥላል፤ በበለጠ መልኩም ይጠናከራል፡፡ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ ሰላማዊ ሰልፍ ለማካሄድ ስንዘጋጅ በህግ ያደረጉትና የከለከሉን ነገር የለም፤ በጉልበት ግን ቢሮአችን ገብተው የሚፈልጉትን ወስደውብናል፡፡ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር “አዲስ የወጣ መመሪያ የለም” ያወጣነው መመሪያ የለም፤ ክልሎች አዋጆችን ለማስፈፀም የራሳቸውን ስነስርዓት ማስፈፀሚያ ያወጣሉ፡፡ እኛም በ1983 ዓ.ም ሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባን ለማካሄድ የተደነገገውን አዋጅ መተግበር የሚያስችል የአሰራር ስርዓት ነው ያወጣነው፡፡ አዋጁ እንዴት ይተገበራል ለሚለው የሚያገለግል እንጂ ሌላ የወጣ ነገር የለም። ሰነዱ ገና ህትመት ላይ ያለ ነገር ነው፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንደማንኛውም ጊዜ ሰላማዊ ሰልፉን በየት አካባቢና እንዴት እንደሚያደርጉ ያሳውቃሉ። ይሄም ቦታው ላይ ችግር እንዳይፈጠር፣ በነዋሪዎችና በትራፊክ እንቅስቃሴዎች ላይ መጨናነቅ እንዳይከሰትና ሰልፈኛው አስፈላጊው ጥበቃ ተደርጎለት በሰላማዊ ሁኔታ ወደመጣበት እንዲመለስ ለማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ እነዚህን ጫናዎች ለማቅለል ነው ማሳወቅ የሚያስፈልገው። ከዚህ ቀደም ሰማያዊ ፓርቲ ከአንድም ሁለት ጊዜ ጠይቆ ተፈቅዶለታል። መጠቀም ያለመጠቀም የፓርቲው ጉዳይ ነው፡፡ ከዛ ውጪ እንደ ከተማ መስተዳደር፣ እንደ መንግስትም ሊደረግላቸው የሚገባውን ነገር ሁሉ እያደረግን ነው፡፡ ነገር ግን የደጋፊ ቁጥር ሲያንስና ደጋፊ ሲጠፋ፣ የእናቴ ቀሚስ ጠለፈኝ የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ ጃንሜዳን የሚያክል ቦታ ተፈቅዶላቸው ሳይጠቀሙበት “መንግስት እገዛ አላደረገልንም፤ ከለከለን” የሚሉም አሉ፡፡ በጃንሜዳ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ይደረጋሉ፤ የጦር ካምፕ አለ ብለው እንደሰበብ አቅርበዋል፡፡ እነሱም በአማራጭነት ባቀረቡዋቸው ቦታዎች በሙሉ ትምህርት ቤትና የሃይማኖት ተቋማት አሉ፡፡ ጃንሜዳ ምናልባት ትንሽ ቅርበት ያለው ለጦር ካምፕ ነው፤ እሱም ቢሆን 500 ሜትር ርቀት አለው፡፡ ስለዚህ እነሱ ከመረጡት ቦታ የተሻለ ነው፡፡ አቶ አሰግድ ጌታቸው የአዲስ አበባ መስተዳደር ከንቲባ ፅ/ቤት እና የካቢኔ ሃላፊ “ፖሊስ ሰላማዊ ሰልፍ መፍቀድና መከልከል አይችልም” ሰላማዊ ሰልፍና ፖሊስ የሚገናኙት ከከተማችን ሰላምና ፀጥታ ጥበቃ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ዜጎችም ሆነ ማንኛውም ሰው ሰላሙንና ፀጥታውን ማስከበር አለበት፡፡ ይሄንን እንደተልዕኮ በዋነኛነት የተሸከመው የፖሊስ ሃይል ነው፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ ህጋዊና ሰላማዊ ሆኖ እንዲካሄድ፣ በሰልፎኞች ላይ አደጋ እንዳይደርስና በመልካም ግንኙነት እንዲጠናቀቅ ፖሊስ የፀጥታ ሃይል ያስከብራል፡፡ አስቀድሞ በተቀመጠለት ቦታ ፣ጊዜና አቅጣጫ መከናወኑን ይከታተላል፡፡ ፖሊስ አዲስ ያወጣው መመሪያ የለም፡፡ መስተዳድሩ አዲስ ያወጣው የሰላማዊ ሰልፍ አፈፃፀም ስነስርዓት አለ፤ እኛም ደርሶናል፡፡ ፖሊስ ሰላማዊ ሰልፍ መፍቀድና መከልከል አይችልም፡፡ ይሄ ጥያቄ የሚቀርብለት ለአስተዳደሩ ነው፡፡ አስተዳደሩ ሲፈቅድ ለፖሊስና ለሚመለከተው አካላት ያሳውቃል፡፡ ፖሊስ ፀጥታውን ያስከብራል፡፡ የሰላማዊ ሰልፍ አድራጊዎች መብት ሲጠበቅ የሌላውም መጠበቅ አለበት፡፡ እኛ ፈቃጁ ክፍል ፈቅጃለው ካለን ጊዜ ጀምሮ ዝግጁ ሆነን ሰላምና ፀጥታን ለማስከበር እንቀሳቀሳለን፡፡ የከተማችን መንገዶች በልማት ተይዘዋል። ዋናው የከተማው መንገድ ግንባታ ላይ ነው፤ በሙሉ አቅም እየሰራ አይደለም፤ ስለዚህ መጨናነቁ ይጨምራል። ሰላማዊ ሰልፍ ሲጨመርበት ደግሞ ይብሳል፡፡ የልማት ተግባር እንዳይስተጓጎል እንዴት ነው መሆን ያለበት የሚለውን አስተዳደሩ ነው የሚጨርሰው። እኛ ግን ፀጥታን እናስከብራለን፡፡ በዚህ ከተማ ማናቸውም ጉዳዮች ሲካሄዱ ፖሊስ ሰላማቸውን ይጠብቃል፡፡ ይሄ ማለት ጉዳዩ ወይም ባለቤቱ ፖሊስ ነው ማለት አይደለም፡፡ የአፍሪካ ህብረት ሲካሄድ ፖሊስ ፀጥታ ያስከብራል እንጂ ባለቤት ወይም ፈቃጅ አይደለም፡፡ ከሰላማዊ ሰልፍ ጋር በተያያዘም ከተለያዩ አቅጣጫዎች መታየት ስላለባቸው ፍቃድ መስጠት የአስተዳደሩ ጉዳይ ነው፡፡ የፀጥታው ጉዳይ ነው የእኛ፡፡ በአስተዳደር እና በፖሊስ በኩል እስካሁን ችግር የለም፡፡ እስካሁን አስተዳደሩ የፈቀደውን ፖሊስ ከልክሎ አያውቅም፤ ባሳለፍነው ሳምንት ሰማያዊ ፓርቲ ጃንሜዳ ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚያደርግ ተነገረን፡፡ እኛ በቂ ሃይል አዘጋጅተን ስንጠብቅ ጃንሜዳ ግን መምጣት አልቻሉም፤ እንደውም ባልተፈቀደላቸውና አሁን በልማት ላይ ወደሚገኘው መስቀል አደባባይ ባነራቸውን ይዘው ሄዱ፤ ይሄ የጠያቂው ስህተት እንጂ የፖሊስ ችግር አልነበረም። ፖሊስ እንደውም ከዚህም ወጣ ብሎ በተቻለ መጠን ሃላፊዎችን በማግኘት የተፈቀደላችሁ ደብዳቤ ደርሶናል፤ እናንተን የመጠበቅ ሃላፊነት አለብን፤ ይሄንን ደግሞ ማድረግ የምንችለው ተራርቀን ሳይሆን ተቀራርበን ነው፤ የሚያስተባብሩ አካላት ስጡን፤ እኛም ሰው እንስጣችሁ፤ እየተመካከርን የሚያስቸግሩ ነገሮችን እያስተካከልን በጋራ እንስራ ብለን ነበር፡፡ ይህንን እንደ ተራ ነገር ነው ያዩት። አንዳንዴ እንደ ዜጋ ማሰብ ጥሩ ነው፤ ልማት ይካሄዳል ሲባል “ለእኔ ሲባል ካልቆመ ወይም ካልተደናቀፈ” እንዴት ይባላል? ሰልፉ ሊካሄድ የነበረው ለአገር እድገት ይጠቅማል ተብሎ አይደለም እንዴ? በርካታዎቹ ሰልፎች በሰላም የሚጠናቀቁ ናቸው። ፖሊስ እነዚህን ያመሰግናል ከተወሰነ ወራት በፊት ሰማያዊ ፓርቲ፤ ሰላማዊ ሰልፍ ሲያካሂድ፣ ከሃይማኖት አክራሪነት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን (ብዙ ጊዜ አንዋር መስጊድ ላይ ሲስተጋቡ የነበሩ) አንፀባርቋል፡፡ ያ መሆን ነበረበት ወይ? እኛ በመታገሳችን በሰውም ሆነ በንብረት ላይ ጉዳት ሳይደርስ ለጠናቀቅ ችሏል፡፡ አሁንም ቢሆን የተፈቀደላቸው ቦታ ጃንሜዳ ነውና እሱን ተጠቀሙ ብንልም ይሄንን ማድረግ አልቻሉም፡፡ አንዋር መስጊድ እኮ ፖሊስ ጉዳት እየደረሰበት እንኳን ለአብዛኛው ህዝብ ስንል “ቻለው” ብለነው ብዙ ጊዜያቶችን አልፏል። ተቃዋሚዎች ደግሞ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ችግራቸውን ይፍቱ፤ ፖሊስን አይመለከተውም፡፡ ፖሊስ የሚቆመው ዜጎች በሰላምና በነፃነት በአገራቸው ላይ እንዲንቀሳቀሱ ለማድረግ ነው፡፡ ለዚህም ንቃተ ህሊናውን የሚያሳድጉ ስልጠናዎች ይሰጣሉ። በፖሊስ ላይ የሚታዩ ችግሮች ዝም ብለው የሚመጡ አይደሉም፡፡ ከልምድና ከትምህርት ማነስ የሚመጡ ናቸው፡፡ ፖሊስ የህብረተሰቡ አካል እንጂ ልዩ ፍጡር አይደለም፡፡ ከሌላው ፈጠን ብሎ ቀድሞ መገኘት አለበት። ፖሊስ የህብረተሰቡ አካል እንደመሆኑ ስህተት ሲሰራ ህዝቡ እያረመው ነው እዚህ የደረሰው፡፡ የሃይል እርምጃ እንዲወስድ ታዝዞ እንኳን፣ እርምጃውን ሳይወስድ ችግሩ የሚፈታበት ሁኔታ አለ፡፡ ዋና ኮሚሽነር ይደጐ ስዩም፤ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር

ፕሬዚዳንቱ አልሰሩም የሚባለውን ይቃወማሉ

                               ባለፈው ሳምንት እትማችን ተሰናባቹ ፕሬዚዳንት አቶ ግርማ ወ/ጊዮርጊስ በስልጣን ዘመናቸው ምን ስኬቶችና ውድቀቶች ነበሯቸው በሚል የተለያዩ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትን፣ ምሁራንና የፕሬዚዳንቱን አማካሪ አነጋግረን ሰፋ ያሉ አስተያየቶችን ማስነበባችን ይታወሳል፡፡ አስተያየቱን ያነበቡትና ለ20 ዓመታት በታክሲ ሹፌርነት የሰሩት አቶ ወርቁ አማረ፤ ፕሬዚዳንቱ በስልጣን ዘመናቸው የሰው ችግር ለመፍታት የተጉ ስለመሆናቸው የአይን ምስክር ነኝ በማለት ለጋዜጣችን ቃለ ምልልስ ለመስጠት ፈቃደኛ ሆነዋል፡፡ የቀድሞው የታክሲ አሽከርካሪዎች ማህበር መስራችና ፕሬዚዳንት የነበሩት አቶ ወርቁ፤ ማህበሩን ለስምንት ዓመታት መርተዋል፡፡ በአሁኑ ሰዓት ከታክሲ ሹፌርነት ወጥተው በመስክ መኪና ሹፌርነት እየሰሩ ሲሆን የማህበሩ ፕሬዚዳንት በነበሩበት ወቅት ፕሬዚዳንት ግርማ፤ የታክሲ ሹፌሮችን የ154 ሚሊዮን ብር ዕዳ እንዴት እንዳሰረዙላቸው ተናግረዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ከአቶ ወርቁ አማረ ጋር በፕሬዚዳንት ግርማና ተያያዥ ጉዳዮች ዙርያ ያደረገችው ቃለምልልስ እንዲህ ቀርቧል:-

አቶ ወርቁ አማረ፤ የቀድሞ ታክሲ ሹፌሮች ማህበር ፕሬዚዳንት

እስቲ ስለ ፕሬዚዳንት ግርማ መናገር የፈለጉትን ነገር ይነገሩን… የዛሬ ሳምንት በወጣው ጋዜጣችሁ ላይ ፕሬዚዳንቱ ስኬታማ ናቸው አይደሉም በሚል ርዕስ የተለያዩ አካላትን አነጋግራችሁ ያወጣችሁት ዘገባ ነው አስተያየት እንድሰጥ የገፋፋኝ፡፡ እኔ የታክሲ ሹፌሮችን ወክዬ በምሰራበት ጊዜ የሰሩት ሥራ የማደንቀው ስለሆነ እሱን መግለጽ እፈልጋለሁ። ባለፈው ሳምንት አማካሪያቸው አቶ አሰፋ ከሲቶ የሰጡትን አስተያየትም አደንቃለሁ፡፡ ፕሬዚዳንቱ ምን ነበር የሰሩት? እንደነገርኩሽ ቤተ-መንግስት የገባሁት የህዝብን ጉዳይ ይዤ ነበር፡፡ በወቅቱ ታክሲ ሹፌሮች ላይ አንድ ደንብ ወጥቶ እዳ ተቆልሎባቸው ነበር፡፡ ዕዳው ወደ 154 ሚሊዮን ብር ገደማ ነው፡፡ ታክሲ ሹፌሩ በባለንብረቶች ከሚደረግበት ጫና በተጨማሪ ደንቡ ጫና ፈጥሮበት ነበር፡፡ በ1990 ዓ.ም የወጣው ደንብ፣ መንጃ ፈቃድ እስከማስቀማት ይደርስ ነበር። አንድ ሹፌር ጥፋት ሲያጠፋ የመጀመሪያው መጥሪያ መቶ ብር ከሆነ፣ ሁለተኛው 150 ይሆናል፣ ከዚያ 250፣ 300 እያለ… እስከነወለዱ እየጨመረ፣ ሹፌሮች መክፈል እስከማይደርሱበት ደረጃ ደረሰ። ብዙዎቹ ታክሲ ሹፌሮች መንጃ ፈቃዳቸውን ተነጥቀው ከጫወታው ውጭ ከሆኑ በኋላ፣ የሙያው ባለቤት ያልሆኑት በዘልማድ እየገቡና እያሽከረከሩ፣ በሰው ህይወትና በንብረት ላይ ብዙ አደጋ ይደርስ ጀመር፡፡ ባለሙያና ባለሙያ ያልሆነውን መለየትም የሚያዳግትበት ሁኔታ ተፈጠረ፡፡ በቀጥታ ወደ ፕሬዚዳንቱ ነው የሄዳችሁት ወይስ በተዋረድ ያሉ የከተማ አስተዳደር ሃላፊዎችን አነጋግራችኋል? ወይ ጉድ ምን ያላየነው ችግር፣ ምን ያላንኳኳነው በር ነበርና! በተለይ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ያላየነው ፈተና የለም፤ ግን ሃላፊዎችን ለማነጋገር ዕድሉን አላገኘንም፡፡

እናም ብዙ ተንከራተናል፡፡ አዋጁ የወጣው በ1990 ዓ.ም ነው ብለዋል። በወቅቱ ፕሬዚዳንት ግርማ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት አልነበሩም፡፡ መቼ ነው ቤተ-መንግስት የገባችሁት? እውነት ነው፡፡ በወቅቱ ፕሬዚዳንት ነጋሶ ነበሩ፤ ደንቡ ሲወጣ ማለቴ ነው፡፡ እኛ ግን እስከ 1997 ዓ.ም ድረስ ትግላችንን ቀጥለን ምንም ምላሽ ሳናገኝ ተስፋ የቆረጥንበት ወቅት ነበረ፡፡ እንዳልኩሽ ብዙ ውጣ ውረድ አይተናል፡፡ ከዚያም እግዜር ፈቅዶ በ1997 ግንቦት ውስጥ ቤተ-መንግስት ገባን፡፡ ጥያቄያችሁ ደንቡን ለማስቀየር ነው ወይስ …? አንደኛ ደንቡ እንዲሻሻል ነበር ትግላችን፡፡ ሌላው በታክሲ ሹፌሮች ላይ የተቆለለው 154 ሚሊዮን ብር ዕዳ እንዲሰረዝ ነበር፡፡ ገንዘቡን ሹፌሮች እንዲከፍሉ ተወስኖ መንጃ ፈቃድ ሲቀሙ ግማሹ ቤተሰቡን በትኖ ጠፋ፣ ግማሹ ሌላ የማያውቀው ስራ ውስጥ ገባ፡፡ ራሳቸውን የጣሉ ሁሉ ነበሩ፡፡ ታዲያ ይሄ ነገር እስከየት ድረስ ነው የሚሄደው የሚለው ነገር ያሳስበን ነበርና በማህበሩ በኩል ከፍተኛ እንቅስቃሴ ማድረግ ጀመርን፡፡ ብዙ በሮችን አንኳኩተናል፤ ብዙ ውጣ ውረድ ደርሶብናል ብለዋል፡፡ ሄዳችሁ ምላሽ ከነፈጓችሁ መ/ቤቶች ጥቂቱን በስም መጥቀስ ይችላሉ? ለምሳሌ ሰራተኛ ማህበር ኮንፌዴሬሽን፣ የትራንስፖርት ቢሮዎች… ብቻ ብዙ ብዙ ቢሮዎች ሄደን መልስ ባለማግኘታችን ተስፋ ቆርጠን ነበር፡፡ ለፕሬዚዳንቱ አቤቱታ የማቅረቡ ሀሳብ እንዴት መጣ? እንዳልኩሽ ተስፋ ቆረጥንና ቁጭ አልን፤ ነገር ግን ቁጭ ብዬ ሳስብ አንድ ነገር በአዕምሮዬ መጣ። ለባልደረቦቼ “ለምን ለመጨረሻ ጊዜ ፕሬዚዳንት ግርማን እንደምንም ብለን አናናግራቸውም?” ስላቸው፣ እንደ እብድ ነበር የቆጠሩኝ፡፡ “እንኳን እሳቸዉ ጋ ሊያደርሱን የሚመለከታቸውስ መች ምላሽ ሰጡን?” በማለት ተቃወሙኝ፡፡ ጤንነቴን ሁሉ ነበር የተጠራጠሩት፡፡

እኔ በራሴ ተስፋ አድርጌ ወደ ቢሯቸው ስልክ ደወልኩ፡፡ ፀሀፊያቸው “ይህን ጉዳይ አዲስ አበባ መስተዳድር እንጂ ፕሬዚዳንቱ አያዩም” የሚል ምላሽ ሰጠችኝ፡፡ “ግዴለም እኛ ብዙ ውጣ ውረድ እና እንግልት ስለደረሰብን ለፕሬዚዳንቱ መልዕክቱን ይንገሩልንና፣ የሚራሩልንና የሚያነጋግሩን ከሆነ እሰየው፤ አልችልም ካሉም ይሄም አንድ መልስ ነው” አልኳት። የፕሬዚዳንቱ ቢሮ (የቤተመንግስት) ስልክ ነበረዎት? ዶ/ር ነጋሶ ስለማውቃቸው እርሳቸው እንዲያገናኙኝ ጥረት አደርግ ነበር፡፡ እናም ዶ/ር ነጋሶ የቢሮ አቸውን ስልክ ሰጡኝና ወደ ቤተ-መንግስት ደወልኩ፡፡ ከዚያስ? ከዚያማ መልዕክቱ ደረሳቸው፣ ግዴለም ቀጠሮ ያዙላቸውና ያነጋግሩኝ አሉ፡፡ በዶ/ር ነጋሶ በኩል ነው ይሄ የሆነው፡፡ ሰኞ ደወልን፡፡ እሮብ ለእኛ ተደውሎ “አርብ ቀን መጥተው ያነጋግሩኝ ብለዋል፡፡” የሚል ምላሽ አገኘን፡፡ ይታይሽ … አንድ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ነው ይሄ የሆነው፡፡ በዚያው ቀጠሮ መሰረት ብሔራዊ ቤተ-መንግስት ገባን፡፡ ስንት ሆናችሁ ገባችሁ? ከእርስዎ ጋር እነ ማን ነበሩ? ከእኔ ጋር ሶስት ሆነን ነው የገባነው፡፡ እኔ፣ አንድ ጠንካራና ለህዝብ ተቆርቋሪ የሆነ አቶ ትዕግስቱ ስብሀት የተባለ ሰው እንዲሁም መለሰ ወጂ የተባለ ግለሰብ ሆነን ነው የገባነው፡፡ ስንት ሆነን እንደምንመጣ ተጠይቀን ሶስት ነን ብለን ነበር፡፡ ፕሬዚዳንቱ አቀባበላቸው እንዴት ነበር? አቀባበላቸው ከምነግርሽ በላይ አስደናቂ ነበር። እድሜና ሰውነታቸው ሳይከብዳቸው፣ በሀበሻ የእንግዳ አቀባበል ስነ-ስርዓት ከመቀመጫቸው ብድግ ብለው ነው የተቀበሉን፡፡

ችግራችሁን ከተናገራችሁ በኋላ ፕሬዚዳንቱ ምን አደረጉ? አሁኑኑ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ደውዬ እነግራቸዋለሁ፡፡ አንድ መፍትሄ እንዲሰጡ አደርጋለሁ አሉን፡፡ በቀጥታ ለአቶ አባይ ተክሌ ደውለው ጉዳዩን አሳወቁልን፡፡ በወቅቱ ክቡር አቶ አባይ ተክሌ በፓርላማ የሰብአዊ መብት ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ይመስሉኛል፡፡ ሀላፊነታቸውን በትክክል አላስታውስም፡፡ አምባሳደር ካሳ ገ/ህይወትም ነበሩ፡፡ ሁኔታው ወደዚያ ተመራና እኛን ጠርተው አነጋገሩን፡፡ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ነው የተጠራችሁት? አዎ! የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ገባንና አነጋገሩን፡፡ ያለንን ማስረጃ ከተቀበሉን በኋላ የአዲስ አበባ መስተዳድር የስራ ሀላፊዎችን ጠርተው አነጋገሩ። በወቅቱ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አቶ አርከበ እቁባይም በነበሩበት ይመስለኛል ያነጋገሯቸው። ከዚያም ባላሰብነው ሁኔታ ስብሰባ ተጠራን፡፡ ይህ ጥሪ የተላለፈው በሬዲዮ በመሆኑ የማህበሩ አባላት አንሄድም አሉ፡፡ ከዚያም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ የአዲስ አበባ ታክሲ ማህበር አባላትን ለስብሰባ እንደሚፈልጋቸው በሚዲያ እንደገና እንዲነገር ተደረገ፡፡ ይሄኔ አባላቱ ግልብጥ ብለው መጡ፡፡ የአዲስ አበባ ታክሲ ባለንብረት ማህበሮችም በስብሰባው ላይ ነበሩ። አቶ አርከበ እቁባይና ሌሎች የካቢኔ አባላትም ተገኝተዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ዋና ስራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ፈለቀ ይመርም ነበሩ። በእሳቸው አማካኝነት ስብሰባው ተከፈተና “ይህ እድል ሊገኝ የቻለው የአዲስ አበባ ታክሲ ሹፌሮች ማህበር ባደረገው ከፍተኛ እንቅስቃሴ ከፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ጋር በተደረገ ውይይት በመሆኑ፣ የማህበሩ ፕሬዚዳንት አቶ ወርቁ አማረ ወደ መድረክ መጥተው ንግግር ያድርጉ” ተብዬ ተጋበዝኩና ንግግር አደረግሁ፡፡ አቶ አርከበ በንግግሬ ተገርመው ነበር፡፡

ከስብሰባው ምን ውጤት ተገኘ? ጉዳዩ ለካቢኔ ቀርቦ ውይይት ይደረግበት እንኳን ሳይባል በቀጥታ “ምህረት ተደርጐላችኋል” ተብሎ ደስታ በደስታ ሆንን፡፡ ይታይሽ … ወደ 154 ሚሊዮን ብር ገደማ የታክሲ ሹፌሮች እዳ ተሰረዘልን፡፡ ከመሀላችን በህግ መተላለፍ ጉዳያቸው የተያዘ ነበሩ፡፡ ጉዳያቸው ትንሽ እንዲቆይ ተደረገና ሌላው ተሰረዘ፡፡ በሂደት የእነዛም ሰዎች ጉዳይ አልቆ ተሰረዘላቸው፡፡ ለውዝፍ እዳ የዳረጋችሁ ደንብ እንዴት ሆነ? አንቀጿ አሁንም በስራ ላይ ናት፤ እየሰራች ነው፡፡ ታክሲ ሹፌሮች ክስ ሲኖርባቸው በ48 ሰዓት ውስጥ እየከፈሉ ነው የሚሰሩት፡፡ አሁን እርስዎ ምን እየሰሩ ነው? ከታክሲ ሹፌርነት ወጣሁና መነሀሪያ ገባሁ፣ የአገር አቋራጭ ሹፌር ሆንኩኝ፣ ከዚያ ለቅቄ ዶሎ ኦዶ ውስጥ ለአንድ የውጭ ዜጋ ሹፌር ሆኜ ነው የምሰራው፣ የመስክ መኪና ሹፌር ነኝ፡፡ ታዲያ አሁን አዲስ አበባ እንዴት መጡ? ከአለቃዬ ጋር ለስራ ነው የመጣሁት፡፡ በዚህ አጋጣሚ አዲስ አድማስን አገኘሁና ሳነብ “ፕሬዚዳንቱ ሰርተዋል አልሰሩም” የሚል የጦፈ ክርክር አየሁ። አማካሪያቸው አቶ አሰፋ ከሲቶ፤ ፕሬዚዳንት ግርማን በደንብ ገልፀዋቸዋል፡፡ እኔም ይህን አጋጣሚ ተጠቅሜ የሰሩልንን ቁም ነገር፣ ያመጡልንን ትልቅ መፍትሄ መናገር ፈለግሁኝ፡፡

ከፕሬዚዳንቱ ቀጥሎ አቶ አርከበ እቁባይን ማመስገን እፈልጋለሁ፡፡ በጣም ቅን ሰው ናቸው፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳንም ማመስገን እፈልጋለሁ። ፕሬዚዳንቱን ገብተን እንድናናግር ሁኔታዎችን አመቻችተውልናል። ዶ/ር ነጋሶ ፕሬዚዳንት በነበሩ ጊዜ ልታናግሯቸው አልሞከራችሁም? እውነት ለመናገር በጣም ጥረት አድርገናል። በተለይ እኔ በጣም ጥረት አድርጌ ነበር፤ አልተሳካም። በእርሳቸው ጊዜ አልሆነልንም። ግን ፕሬዚዳንት ግርማን እንድናገኝ ላደረጉት ጥረት አሁንም አመሰግናቸዋለሁ፡፡ ለነገሩ የእኛ ፍላጐት ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔር ፈቃድም ስለሆነ ነው የተሳካልን ብዬ ነው የማምነው። በሌላ በኩል የአዲስ አበባ ታክሲ ሹፌሮች ማህበር ም/ሊቀመንበር የነበረው አቶ ትዕግስቱ ስብሀት፤ ጠንካራ ሰው ነው፤ ለህዝቡ ብዙ ደም የሰጠና የታገለ ሰው ነው፡፡ በጣም ላመሰግነው እወዳለሁ፡፡ አቶ ኑረዲን ዲታሞም ሊመሰገኑ ይገባል። ማህበሩን መቼ መሰረቱት? እስከመቼስ መሩት? ማህበሩ አሁን በምን ሁኔታ ላይ ይገኛል? በ1991 ዓ.ም ጥቅምት ወር ላይ ተመስርቶ መጋቢት ወር ላይ እውቅና አገኘ፡፡ በነገራችን ላይ ማህበሩን ለማቋቋም ያነሳሳኝ፣ በባለንብረቶች በኩል የነበረብን ከፍተኛ ጫና ነው፡፡

በማህበር ስንደራጅ የተሻለ አቅም ፈጥረን፣ ጫና እንቀንሳለን በሚል ነበር የመሰረትነው፡፡ ማህበሩ እንዳይመሰረትና እንቅስቃሴ እንዳናደርግ ጭምር ባለንብረቶቹ ከፍተኛ እንቅፋት ሲፈጥሩብን ነበር፡፡ ፍ/ቤት እስከመከሰስ ሁሉ ደርሰን ነበር፡፡ እንቅፋቶቹ ምን አይነት ናቸው? ለምሳሌ ህገ-ወጥ ማህበር ነው በሚል የተሳሳተ መረጃ ያሰራጩ ነበር፡፡ እኛ እንቅስቃሴያችን በህጉ ዙሪያ፣ በአገልግሎት ሰጪውና በተገልጋዩ መሀል ያለውን ክፍተት ለማጥበብ ጭምር ነበር። በባለንብረቶች የሚደርስብንን ተፅዕኖዎች መቀነስ የሚለው እንዳለ ሆኖ ማለቴ ነው። በዋናነት ከላይ የፀደቀው ደንብ ሲወጣ፣ ህግ አውጭዎች እኛን ማወያየት ነበረባቸው፡፡ ይህን ጥያቄ በማህበራችን በኩል እናቅርብ የሚልም ሀሳብ ይዘን ነበር የተንቀሳቀስነው፡፡ ለምን ቢባል? በጊዜው የተጋበዙትና ለውይይት የተጠሩት የባለንብረቶች ማህበር አመራሮች ናቸው፡፡ ነገር ግን የስራውና ደንቡ የወጣበት ጉዳይ ባለቤት አሽከርካሪዎች ነን፡፡ አሁን እርስዎ ከታክሲ ስራ ውጭ ነዎት፡፡ አሁን ያለውን ሁኔታ እንዴት ያዩታል? በአሁኑ ሰዓት የታክሲ ሹፌር መብትና ግዴታውን ያወቀ አልመሰለኝም፡፡ በአቋራጭ ለመክበር አቆራርጦ መጫን እና በመሳሰሉት ሹፌርና ረዳት ሲመሳጠሩ አያለሁ፡፡ ህዝብ መከበር አለበት፤ እኔም ስሰራ ህግና ደንብን ተከትዬ፣ ህዝብ አከብሬ ነው የኖርኩት፡፡ ስንት አመት ታክሲ ላይ ሰሩ? ለ20 ዓመታት ሰርቼያለሁ፡፡ እንዴት በ20 አመት ውስጥ የራስዎ ታክሲ አልገዙም? እንደነገርኩሽ ህግና ስርዓትን ጠብቄ እሰራ ስለነበር፣ የማገኘው ገንዘብ ቤተሰብ ከማስተዳደር አልፎ ታክሲ ሊያስገዛ የሚችል አልነበረም፡፡ በ20 ዓመት የስራዎ ዘመን ውስጥ በርካት ገጠመኝዎች እንደሚኖርዎት እገምታለሁ፡፡ አንድ ሁለቱን ቢነግሩኝ … ከ1980 ዓ.ም ጀምሮ ነው ታክሲ መስራት የጀመርኩት፡፡ ማህበሩን ከ1991-1998 መርቻለሁ። ማሽከርከር ያቆምኩት 2000 ዓ.ም ነው፡፡ በሃያ አመት ውስጥ ታክሲ ላይ ምን የማያጋጥም አለ? የታክሲ ስራ ትልቅ መድረክ አይደለም እንዴ? አንዴ የማይረሳኝ አንድ ተሳፋሪ ከአቅም በላይ ጠጥቷል እና ወራጅ አለኝ፡፡ ከኔ ወንበር ኋላ ነው የተቀመጠው፡፡

በስካር አንደበት “ወራጅ አለ” ብሎኝ እስካቆምለት እድል ሳይሰጠኝ እኔና ጋቢና የተቀመጡት ሰዎች ላይ አስመለሰብን፡፡ ይህን አልረሳውም፡፡ ሌላ ጊዜ አንዲት ሴት መሳሪያ አውጥታ አስፈራራችኝ። የተከለከለ ቦታ ላይ አልቆምም ስላልኩኝ “የሰው ማንነት ሳታውቅ” ብላ ማጅራቴን ልትለኝ ነበር፡፡ በሽጉጥ ተመትቶ የሞተ ሹፌር አውቃለሁ፤ ፓስተር ማዞሪያ ላይ፡፡ በርካታ ገጠመኝ አለ፡፡ አንድ ሹፌር ወይም ረዳት 12 ተሳፋሪ ጭነው ሲሄዱትንሽ ጥፋት ቢፈጽሙ ከተሳፋሪዎች አንዱ እንኳን ሹፌሩና ረዳቱ ከጥፋታቸው እንዲማሩ የሚያደርግ አስተያየት ሲሰጥ አጋጥሞኝ አያውቅም፡፡ አንድ ተሳፋሪ ቢበደል 12ቱም ሹፌሩና ረዳቱ ላይ ሲረባረቡ ይታያል፡፡ በአጠቃላይ ስራው አስቸጋሪ ነው እያሉኝ ነው? ስራው ሳይሆን የተለያየ ሰውና የተለያየ ባህሪ ማስተናገዳችን ነው አስቸጋሪው፡፡ ሙያው ክቡር ነው፡፡ ሰው ድንጋይ ተሸክሞም ኑሮውን ይመራል እኮ። ስራ ያው ስራ ነው፡፡ በ20 ዓመት የታክሲ ሹፌርነትዎ አደጋ አድርሰው፣ ሰው ገጭተው ያውቃሉ? አንድ ጊዜ አጋጥሞኛል፡፡ አዲስ ከተማ አካባቢ ሰው ገጭቼ ነበር፡፡ ጥፋተኛው ግን እግረኛው ነበር፡፡ መሀል አስፓልት ላይ ከእግረኛ መንገድ አራት ሜትር ከዘጠና ገብቶ ነው የተገጨው፡፡ ነገር ግን ህጉ ሰው ገጭተሽ ጥፋተኛም ባትሆኚ በነፃ አይለቅሽም፡፡ ሰውየው ሞተ ወይስ ተረፈ? ሰውየው ሞተ፡፡ እኔም ማግኘት የሚገባኝን ቅጣት አግኝቻለሁ፡፡ ልጆች አለዎት? አዎ አራት ልጆች አሉኝ፡፡ እነሱን ለማስተማር ደፋ ቀና እያልኩ ነው፤ ይመስገነው፡፡

             ከዕለታት በአንዱ ዝናባማ ቀን አንድ ሰው በአንዲት ቀጭን መንገድ እየሄደ ነበር። ዝናቡ ብዙ የዘነበ ስለሆነ አካባቢውን ሁሉ አጨቅይቶታል፡፡ በተለይ ያቺ ቀጭን መንገድ፤ ለአንድ ጊዜ የምታሳልፍ ሲሆን እጅግ አድርጋ ጭቃ በጭቃ ከመሆኗና በጣም ከመሟለጧ የተነሳ፤ የረገጡትን እግር ሁሉ ታዳልጣለች፡፡ ሰውየው በጣም ይቸኩል እንጂ በጥንቃቄ መራመድ እንዳለበት ገብቶታል፡፡ ከኋላው ያለ አንድ ሰው ከኋላው እየተከተለ ነው፡፡ እንግዲህ ተከታትለው እየሄዱ ነው፡፡ የመጀመሪያው ሰውዬ ጥቂት እንደተራመደ፤አዳለጠውና ዘጭ አለ፡፡ ወድቆ ጭቃው ላይ አረፈ፡፡ እንደ እልህም እንደቁጭትም ያዘውና፤ “እቺን ይወዳል?!” አለ፡፡

ሆኖም፤ እንደምንም ተሟሙቶ ተነሳ፡፡ ተስተካከለና እንደገና ለመራመድ ሞከረ፡፡ እንደገና ወደቀ፡፡ ሙሉ በሙሉ ጅው ብሎ ነው ከጭቃው የተደባለቀው፡፡ አሁንም፤ “እቺን ይወዳል?!” አለና እንደምንም መሬት ቧጦ ተነሳ፡፡ ከኋላው ለማለፍ የፈለገው ሰውዬ ትዕግስቱ እያለቀ መጥቷል፡፡ ወድቆ የተነሳው ሰው ለሶስተኛ ጊዜ ሙከራ ለማድረግ ሲራመድ፤አሁንማ ከስሩ ያለው ጭቃ ጭራሽ ላቁጧልና ባንድ ጊዜ አዳልጦት ዘጭ አደረገው፡፡ ለሶስተኛ ጊዜ፤ “እቺን ይወዳል?!” አለ ጮክና ቆጣ ብሎ፡፡ ይሄኔ ከኋላ ሆኖ ይህንን እየሠማ ትርዒቱን የሚያስተውለው፤ ለማለፍ የሚፈልገው ሰውዬ ተናደደና፤ “ስማ የእኔ ወንድም፤አንተ ከወደድከው ተንደባለልበት! ለእኔ መንገድ ልቀቅልኝ!” አለው፡፡

                                                    * * *

በማንኛውም የህይወት እንቅስቃሴ ውስጥ መውደቅም ሆነ ማዳለጥ ያለ ነው። መነሳት አንድ የጠንካራ ሰው ነገር ነው፡፡ ደግሞ መውደቅ ፣ሆኖም እዚያው ቦታ ላይ መውደቅ አሳዛኝ ነው፡፡ ቀጭንና አዳላጭ የሆኑ የትግል መንገዶች ብዙ ናቸው፡፡ መሳለጫ እየመሰሉ የማያሳልፉ መኖራቸውን ያልተገነዘበ ታጋይ፣ ደጋግሞ መውደቅ አይቀርለትም! እንግሊዙ የታሪክ ተመራማሪ ስለፈረንሳይ የንጉስ ናፖሊዮን ሶስተኛው እንዲህ ሲል ፅፏል፡- “የአንድ አገር መሪ አደገኛ ነገር ነው ብዬ የማስበው የታሪክ ተማሪ መሆኑን ነው። እንደታሪክ ተማሪዎች ሁሉ መሪውም ካለፈው ስህተቱ የተማረው እንዴት አዲስ ስህተት እንደሚሰራ ነው!” ይላል፡፡ ለእኔ ብለህ ስማ ነው፡፡ ገጣሚው፣ፈላስፋውና ሃያሲው ሳሙኤል ቴይለር ኮልሪጅ፤ ደግሞ፤ “ሰዎች ከታሪክ ለመማር ቢችሉ ኖሮ፤እንዴት ያለ ትምህርት ባገኙ! ሆኖም አንድን ነገር ሙጭጭ ብሎ ከመውደድና በይዞታነት የያዝነው ፓርቲ ዐይናችንን ከማሳወሩ የተነሳ፤ ልምድ የሚያበራልን ማሾ ያለፍነውን ማዕበል ብቻ ይሆናል” ይለናል፡፡ ለእኔ ብለህ ስማ ነው ጐበዝ!

ሔገል የባለው ጀርመናዊ ፈላስፋ በበኩሉ፤ “ልምድና ታሪክ የሚያስተምሩን አንድ ነገር አለ፡፡ ይሄውም ህዝቦችና መንግሥታት ከታሪክ በፍፁም እንደማይማሩ ነው፡፡ አሊያም ደግሞ ከታሪክ ባገኙት ትምህርት መሠረት ምንም እርምጃ አለመውሰዳቸው ነው፤ ይለናል፡፡ ለእኔ ብለህ ስማ ነው ጐበዝ! “ህይወት ሰዎች ሲሞቱ አስቂኝ መሆኗን የማታቆመውን ያህል፤ ሰዎች ሲስቁም ህይወት ኮስታራ መሆኗን አታቆምም፡፡” በርናርድ ሾው ነው ይሄን ያለው፡፡ ዕውነቱን ነው፡፡ የዛሬው መስቀል ደመራ በየትም ወደቀ በየት፤ ከላይ የጠቀስናቸው ጥቅሶች የበዓሉ ስጦታ ይሁኑ! “ትላንትና ማታ ቤትህ ስትገባ እንቅፋት የመታህ ድንጋይ ዛሬ ማታም ከደገመህ፤ ድንጋዩ አንተው ነህ!” - የምንለው ዓመቱን በፍቅር፣ ሰላምና በብርሃን እንድንገፋው ነው! መልካም የመስቀል በዓል! ”

የአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፤ ባለፈው ረቡዕ ለሦስት ሰዓታት በፖሊስ ጣቢያ ታስረው መፈታታቸው ተገለፀ፡፡ ዶ/ር ነጋሶ፤ ፓርቲው ነገ ያካሂዳል ተብሎ ለሚጠበቀው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ እንዲያደርጉ ካሰማራቸው አባላት ጋር በተያያዘ ታስረው እንደነበር ታውቋል፡፡ ባለፈው ረቡዕ የሰላማዊ ሰልፍ ቅስቅሳ ሲያደርጉ የነበሩ 14 የፓርቲው አባላት “የቅስቀሳ ፈቃድ የላችሁም” ተብለው በፖሊስ መያዛቸውን የገለፀው ፓርቲው፤ የአንድነት ልሳን ጋዜጣ ፎቶግራፍ አንሺም በራሪ ወረቀት ሲቀበሉ የነበሩ ሰዎችን ያለፍላጐታቸው ፎቶግራፍ አንስቷል፤ ተሳድቧል በሚል ክስ እንደቀረበበት አስታውቋል፡፡ ዶ/ር ነጋሶ የሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ እንዲደረግ ለአባላቱ የስምሪት ደብዳቤ በመፈረማቸው፣ ድርጊቱ የተፈፀመው እሳቸው በሰጡት አመራር እንደሆነ በፖሊስ ተገልፆላቸው ጉዳዩ እስኪጣራ መታሰራቸውን ነው ፓርቲው የገለፀው፡፡ ከሶስት ሰዓት እስር በኋላም ፎቶግራፈሩ በዋስ ሲለቀቅ ዶ/ር ነጋሶ በነፃ እንደተለቀቁ ታውቋል፡፡

የክብር ዶ/ር ጥላሁን ገሰሰ መታሰቢያ ዝግጅት በመጪው አርብ ከቀኑ 8 ሰዓት እንደሚቀርብ የኢትዮጽያ ብሔራዊ ትያትር አስታወቀ፡፡ በትያትር ቤቱ በሚቀርበው የሙዚቃ ዝግጅት፣ ከኢትዮጵያውያን አርቲስቶች በተጨማሪ ከሱዳን የመጣ የሙዚቃ ቡድን ጣዕመ ዜማዎችን በነፃ ለታዳሚዎች ያቀርባሉ፡፡ ዝግጅቱ የሚቀርብበት ዕለት ዐርብ መስከረም 17 የከያኒው የልደት ቀን እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በሌላም በኩል የኢትዮጵያ ብሔራዊ ትያትር ባለፈው ዓመት ክረምት “በመሠረታዊ የቴአትር ጥበብ” ዘርፍ ያሠለጠናቸውን ተማሪዎች ዛሬ ከጧቱ 3 ሰአት እንደሚያስመርቅ አስታወቀ። 60 ለሚሆኑ ተመራቂዎች ሥልጠናውን በትያትር ዝግጅት ጌትነት እንየው፣ በጽሑፈ-ተውኔት ተስፋዬ ገብረማርያም እንዲሁም በትወና ሳሙኤል ተስፋዬና መሠረት ሕይወት ሥልጠናውን እንደሠጡ ለማወቅ ተችሏል፡፡

“የፍቅር ኬምስትሪ” ተመረቀ፤ “የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ገመና” ለንባብ በቃ

በቶሌራ ፍቅሩ ገምታ የተፃፈው “Raayyaa Dhugaa” የተሰኘ የኦሮምኛ ረዥም ልቦለድና የሙሉጌታ ጌቱ “ሰይጣን አሳስቶኝ” የአማርኛ የግጥም መድበል ዛሬ እና ሰኞ በፑሽኪን አዳራሽ እንደሚመረቁ ተገለፀ፡፡ ዛሬ ከቀኑ 8 ሰዓት በማዕከሉ ፑሽኪን አዳራሽ የሚመረቀው የቶሌራ ፍቅሩ ገምታ የኦሮምኛ ረዥም ልብወለድ፣ በኦሮሞ ሕዝብ ማህበራዊ እውነታ ላይ ተንተርሶ የተፃፈ ሲሆን የምረቃ ሥነስርዓቱን የሩስያ ሳይንስና ባህል ማእከል ከኢትዮጵያ ደራስያን ማሕበር እና ከኦሮሞ ደራስያን ማህበር ጋር እንዳዘጋጁት ለማወቅ ተችሏል፡፡

ደራሲው ካሁን ቀደም ‘Immimman Hadhaa’ የተሰኘ ሌላ መጽሐፍ አዘጋጅተው አሳትመዋል፡፡ “ሰይጣን አሳስቶኝ” የተሰኘው የግጥም መድበልም እንዲሁ የፊታችን ሰኞ ምሽት በ11፡30 በማዕከሉ የሚመረቅ ሲሆን የመፅሃፉ ገጣሚ አቶ ሙሉጌታ ጌቱ፣ የባሕል ማእከሉና የኢትዮጵያ ደራስያን ማሕበር አባል ናቸው፡፡ በሌላም በኩል በብርሃኔ ንጉሤ የተዘጋጀው “የፍቅር ኬምስትሪ ሴቶችን የመማረክ ጥበብ” የተሰኘው መጽሐፍ፣ከትላንት በስቲያ ምሽት ተመረቀ፡፡ የመፅሃፉ አዘጋጅ “ኢትዮፒካሊንክ” የተባለው የሬዲዮ ፕሮግራም መስራችና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ብርሐኔ ንጉሴ ሲሆን በ250 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ፣ በ55 ብር እንደሚሸጥ ለማወቅ ተችሏል። በተማሪዎች አንደበት ተነገሩ የተባሉ እውነታዎችን ያካተተና በሄለን መልካሙ የተዘጋጀ “የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ገመና” የተሰኘ መጽሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ 134 ገፆች ያሉት መጽሐፍ፣ ለገበያ የቀረበው በ35 ብር ነው፡፡