Administrator

Administrator

          ባለፉት አስርት ዓመታት በልብ በሽታ ሳቢያ የሚጠፋው የሰዎች ህይወት በከፍተኛ መጠን እየቀነሰ መምጣቱ ተገለፀ፡፡ በከፊል አውሮፓ በቀዳሚ ገዳይነቱ ይታወቅ የነበረው የልብ በሽታ በሰዎች ህይወት ላይ ሲያደርስ የቆየው የሞት አደጋ በከፍተኛ ደረጃ እንደቀነሰ በቅርቡ የወጣ ጥናት ጠቆመ፡፡ በምስራቅ አውሮፓ አገራት ግን የልብ በሽታ በግንባር ቀደም ገዳይነቱ እንደቀጠለ ጥናቱ አመልክቷል፡፡
“European Heart Journal” ላይ የወጣ ሪፖርት እንደሚጠቁመው ደግሞ ዴንማርክን በመሳሰሉ አንዳንድ አገሮች በአሁኑ ሰዓት የልብ በሽታን ተክቶ ካንሰር ትልቁ ገዳይ በሽታ እየሆነ መጥቷል ተብሏል፡፡
በከፊል አውሮፓ የልብ ህመም ገዳይነት የቀነሰው ከአኗኗር ዘይቤ መሻሻል ጋር ተያይዞ ነው ያለው ጥናቱ፤ በዋናነት የሲጋራ ማጨስ መቀነስና የተሻሻሉ ህክምናዎች ተጠቅሰዋል፡፡
የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የጥናት ትንተና እንደሚያሳየው፤ በአስር አውሮፓ አገራት ወንዶችን በከፍተኛ ደረጃ ለሞት እየዳረገ ያለው ከልብ ህመም ይልቅ ካንሰር ነው፡፡ በዴንማርክ ደግሞ ካንሰር የልብ ህመምን ቦታ ተክቶ በከፍተኛ ደረጃ ህልፈት እያስከተለ የሚገኘው በሴቶች ህይወት ላይ ነው ይላል፤ የጥናት ውጤቱ፡፡
ምስራቅ አውሮፓውያን ግን ከአቻዎቻቸው በእጅጉ ወደ ኋላ እንደቀሩ የጠቆመው ጥናቱ፤ በአንዳንድ የምስራቅ አውሮፓ አገሮች የልብ በሽታ አሁንም ከፍተኛ የሞት አደጋ እያስከተለ ነው ብሏል።
ከተመራማሪዎቹ አንዱ የሆኑት ዶ/ር ማይክ ራይነር ለቢቢሲ ሲናገሩ፤ “በልብ በሽታ የሚከሰተው አጠቃላይ የሞት መጠን እየቀነሰ ነው፤ በአንዳንድ አገራት ከሌሎች አገራት ፈጣን ነው፤ አሁንም ግን በአውሮፓ ትልቁ ገዳይ ነው” ብለዋል፡፡
የብሪቲሽ ኸርት ፋውንዴሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሲመን ጊሌስፒ በበኩላቸው፤ “በልብ ህመም በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሞቱ የነበሩ በርካታ ሰዎች ቁጥር በመላው አውሮፓ መቀነሱ መልካም ዜና ነው” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

የስዕል ተሰጥኦ ከዘረመል ጋር ግንኙነት አለው ተብሏል

ህጻናት በአራት አመት እድሜያቸው ላይ ሆነው የሚስሏቸው ስዕሎች አጠቃላይ ሁኔታና የስዕል ችሎታቸው፣ በቀጣይ የህይወት ዘመናቸው የሚኖራቸውን አእምሯዊ ብቃት በተወሰነ መልኩ የሚያመላክት እንደሆነ በጥናት መረጋገጡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ለንደን ውስጥ በሚገኘው ኪንግስ ኮሌጅ የሥነ አዕምሮ ተቋም ተመራማሪዎች በጥናታቸው ያካተቷቸውን 7ሺህ 752 ጥንድ መንታ ህጻናት፣ የአንዲትን ህጻን ፎቶግራፍ በወረቀት ላይ እንዲስሉ በማድረግ የህጻናቱን የስዕል ችሎታ የገመገሙ ሲሆን የስዕሎቹ ውጤትም ህጻናቱ ከአስር አመታት በኋላ የሚኖራቸውን አእምሯዊ ብቃት እንደሚያመላክት ማረጋገጣቸውን ተናግረዋል፡፡
በአይን የተመለከቱትን ነገር በወረቀት ላይ በስዕል መልክ ማስፈር መቻል ለሰው ልጆች የተሰጠ ልዩ ክህሎት ነው ያሉት የተመራማሪዎች ቡድኑ መሪ ዶ/ር ሮዚላንድ አርደን፤ የስዕል ችሎታ የሰዎችን መረጃን በአእምሮ የማቆርና በተፈለገው ጊዜ የማውጣትና የማሰብ ብቃት የሚያመለክት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የስዕል ችሎታ ህጻናት ሲያድጉ የሚኖራቸውን አእምሯዊ ብቃት የሚያመለክት ቢሆንም፣ ይህ ችሎታ አእምሯዊ ብቃትን የሚወስን አለመሆኑን የገለጹት ዶ/ር አርደን፤ አእምሯዊ ብቃትን የሚወስኑ ሌሎች ተፈጥሯዊና አካባቢያዊ ምክንያቶች እንደሆኑም ተናግረዋል፡፡
“በስዕል ችሎታና በአእምሯዊ ብቃት መካከል ያለው ግንኙነት የተወሰነ በመሆኑ፣ ወላጆች የልጆቻቸው የስዕል ችሎታ አነስተኛ በመሆኑ ሊሰጉ አይገባም” ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
ተመራማሪዎቹ ከዚህ በተጨማሪም፣ ጥናት ያደረጉባቸው መንታ ህጻናት የሳሏቸውን ስዕሎች በመገምገም፣ የስዕል ችሎታ በዘር የሚተላለፍ መሆን አለመሆኑን ለማጥናት የሞከሩ ሲሆን፣ በዚህም የስዕል ችሎታ ከዘረመል ጋር ግንኙነት እንዳለው ድምዳሜ ላይ ደርሰዋል፡፡

ጉዲፈቻ የሚለው ቃል ከኦሮምኛ ቋንቋ በቀጥታ ወደ አማርኛ የተወሰደ ሲሆን ፍቺውም ከሌላ አብራክ የተገኘን ልጅ ከሌላ ሰው የተወለደ መሆኑን አምኖና ተቀብሎ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መብቱን ጠብቆ እንደ ገዛ ልጅ አድርጎ ማሳደግ ማለት ነው፡፡
ጉዲፈቻ ለሚለው ቃል የእንግሊዝኛ አቻው “adoption” ሲሆን አመጣጡም ‘ad-optare’ ከሚል የላቲን ቃል ነው፡፡ ትርጉሙም “መምረጥ” የሚል ነው፡፡ ይህም ጉዲፈቻ በጉዲፈቻ አድራጊው ምርጫ ብቻ የሚከናወን መሆኑን አመላካች ነው፡፡ ጉዲፈቻ አድራጊው በነጻ ፈቃዱ ከሌላ አብራክ የተገኘን ልጅ ለማሳደግና ለመጠበቅ እንዲሁም ለእድገቱ አስፈላጊ የሆኑትን ማናቸውም እንክብካቤዎች ለማድረግ ወስኖ የሚወስደው እርምጃ ሲሆን ይሄም ልጁ የጉዲፈቻ አድራጊውን ቤተሰብ ስም፣ ንብረትና ህይወት እንዲካፈል የሚያደርግ መብት ያጐናጽፈዋል፡፡ ከአብራኩ ክፋይ የተገኘው ልጅ ያለው ማንኛውም መብት ይኖረዋል፡፡
በአጠቃላይ ጉዲፈቻ አንድ ሰው ቀደም ሲል የነበረውን ቤተሰባዊ የደም ትስስር በከፊልም ሆነ ሙሉ በሙሉ በአዲስ ቤተሰባዊ ትስስር የሚተካ ወይም የሚለውጥ ማህበራዊ ተቋም ነው ሊባል ይችላል፡፡
ጉዲፈቻ ከጥንት ጀምሮ በተለያዩ የዓለም ማህበረሰቦች ዘንድ በአንድ ወይም በሌላ መልኩ ሲከናወን የቆየ ሥርዓት ነው፡፡ ለዚህም በአይሁድና በክርስትና ሃይማኖቶች ታሪክ ውስጥ የሚጠቀሰው የነቢዩ ሙሴ ጉዲፈቻ እንደ አብነት ሊነሳ ይችላል፡፡ በህንድ፣ በግብፅና በሮማውያን ዘንድ የዘር ግንዳቸው መቀጠል ባልቻለበት ሁኔታ የቤተሰብ ስም እንዲቀጥል ጉዲፈቻን እንደመሳሪያ ይጠቀሙበት ነበር፡፡ በእስልምና ህግ የሚተዳደሩ አገሮች የሚጠቀሙበት “የጉዲፈቻ” ሥርዓት ከዚህ በመጠኑ ለየት ይላል፡፡ ካፍላህ በመባል የሚታወቀው ይሄ የጉዲፈቻ ሥርዓት ከኢንዶኔዥያና ቱኒዚያ በስተቀር በእስልምና ሃይማኖት ተከታይ አገራት በሙሉ  በስፋት ይተገበራል፡፡ ካፍላህ የተፈጥሮ ወላጆቻቸው ወይም ቤተሰቦቻቸው ሊያሳድጓቸው ላልቻሉ ልጆች የተፈጠረ አማራጭ የእንክብካቤ መንገድ ሲሆን በህጉ መሰረት ካፍላህ አድራጊዎች ልጆቹን ለዘለቄታው ወስደው እንደራሳቸው ልጆች የማሳደግ ግዴታ አለባቸው፡፡ ሆኖም ልጆቹ ማንነታቸውን ይዘው ማደግ አለባቸው ተብሎ ስለሚታመን የካፍላህ አድራጊዎችን የቤተሰብ ስም እንዲጠቀሙ የማይፈቀድ ሲሆን ንብረት የመውረስ መብትም የላቸውም፡፡
በጥንቱ ዘመን ጉዲፈቻ የልጆችን ሳይሆን የጉዲፈቻ አድራጊዎችን ጥቅም መሰረት በማድረግ ነበር የሚከናወነው፡፡ ጉዲፈቻ የዘር ሀረግን በቀጣይነት ለማረጋገጥ፣ በወንድ ጉዲፈቻ ተደራጊ ልጅ አማካይነት ፖለቲካዊ፣ ሃይማኖታዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞችን ለማስጠበቅ እንዲሁም በገበሬዎች አካባቢ ተጨማሪ አጋዥ ሐይል ለማግኘት ጭምር ሲተገበር ቆይቷል፡፡ የጉዲፈቻ ተደራጊዎች የእድሜ ክልልም በአብዛኛው ከ10 ዓመት በላይ ነበር፡፡
በአብዛኛው የዓለም ክፍል ሲተገበር የቆየው የጉዲፈቻ ሥርዓት በመካከለኛው ዘመን ላይ በተለይ በአውሮፓ አገራት ወደ መጥፋት ደረጃ ደርሶ ነበር፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ደግሞ ከክርስትና ሃይማኖት መስፋፋት ጋር ተያይዞ የቤተሰብ ተቋም የደም ትስስር መለያ ባህሪ ስለተሰጠው ነው፡፡
ጉዲፈቻ ዳግም እንደ ሥርዓት ያንሰራራው በፈረንሳይ ቡርዥዋ አብዮት ማግስት በነገሰው ነፃ አስተሳሰብና ዘመናዊ ፍልስፍና ተፅዕኖ ሲሆን እ.ኤ.አ በ1804 በወጣው የፈረንሳይ ፍትሀብሔር ህግ ላይ ጉዲፈቻ በተወሰኑ ሁኔታዎች እንዲደረግ ተፈቅዶ ነበር፡፡
ይህን የፈረንሳይ ተሞክሮ ተከትሎ በ19ኛው ክፍለ ዘመን ማብቂያ ላይ ጉዲፈቻ በአውሮፓ አገራት እንደ አዲስ የህግ ማዕቀፍ እውቅና አግኝቷል፡፡ በእንግሊዝ ጉዲፈቻ ለመጀመሪያ ጊዜ ሕጋዊ ማዕቀፍ ያገኘው እ.ኤ.አ በ1926 “Children Act of 1926” (የ1926 የህፃናት ድንጋጌ) በሚል ሕግ ሲሆን በአሜሪካ በማሳቹስቴት ግዛት ደግሞ “The Massachusetts Adoption of Children Act” (የማሳቹሴትስ የህፃናት ጉዲፈቻ ድንጋጌ) በሚል በወጣው የጉዲፈቻ ህግ ዕውቅና አግኝቷል፡፡ በወቅቱ ህግ ጉዲፈቻ ተደራጊው ከሁለቱም ቤተሰቡ ማለትም ከቀድሞ ቤተሰቡና ከጉዲፈቻ አድራጊዎቹ ዝምድናውን ይዞ የሚቆይ ሲሆን ከሁለቱም የመውረስ መብት ነበረው፡፡ እነዚህ በአሜሪካና በእንግሊዝ የወጡት የጉዲፈቻ ድንጋጌዎች የመጀመሪያዎቹ ዘመናዊ የጉዲፈቻ ህጎች ተብለው ይታወቃሉ፡፡
የአሜሪካው የማሳቹሴትስ የጉዲፈቻ ድንጋጌ፣ ለቀጣዩ የጉዲፈቻ ህግ መበልጸግ የማእዘን ድንጋይ የጣለ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ህጉ ለመጀመሪያ ጊዜ የጉዲፈቻ ውል በፍርድ ቤት እንዲጸድቅ የደነገገ ሲሆን ፍ/ቤቱም ውሳኔውን ከማስተላለፉ በፊት የሚመለከታቸው አካላት ለጉዲፈቻው ፈቃድ መስጠታቸውንና ውሳኔው የልጁን ደህንነት የሚያስጠብቅ መሆኑን ማረጋገጥ እንዳለበት ይገልፃል፡፡ ፍ/ቤቱ ጉዲፈቻ  አድራጊዎቹ ለህፃኑ ተስማሚ መሆናቸውን በቅድሚያ ማረጋገጥ እንዳለበትም ህጉ ያስቀምጣል፡፡
በሃያኛው ክፍለ ዘመን መግቢያ ላይ ከአዳዲስ የጉዲፈቻ ህጐች መውጣት ጋር ተያይዞ የጉዲፈቻ አላማና ግብ ከጉዲፈቻ አድራጊው ጥቅሞች ተላቅቆ የህፃናትን ደህንነትና ጥቅም የሚያስጠብቅ እየሆነ መጣ፡፡ ጉዲፈቻ መንግስታት የተጣሉ፣ ቤተሰብ የሌላቸው/የማይንከባከባቸው ወይም ከጋብቻ ውጭ የተወለዱ ልጆችን የሚንከባከቡበትና ደህንነታቸውን የሚያስጠብቁበት ተቋም ለመሆንም በቃ። ይሄን ተከትሎም የጉዲፈቻ ተቋም የሚያስከትለው ህጋዊ ውጤትም ተቀይሯል፡፡ በፊት ጉዲፈቻ ተደራጊው ከቀድሞ ቤተሰቡ ጋር ያለውን ግንኙነት ሙሉ ለሙሉ የማያቋርጥ ሲሆን ይህም ከፊል ጉዲፈቻ /weak or simple adoption/ በመባል ይታወቃል፡፡ አሁን በተሻሻለው የጉዲፈቻ ህጋዊ ሥርዓት ግን ጉዲፈቻ ተደራጊው ከቀድሞ ቤተሰብ ጋር ያለውን ግንኙነት ሙሉ በሙሉ ያቋርጣል፡፡ ይህም ሙሉ ጉዲፈቻ / ‘strong’ or ‘full’ adoption/ በሚል የሚታወቅ ሲሆን የህፃናትን ደህንነት ከማስጠበቅ አንፃር ተቀባይነቱ እየጨመረ መጥቷል፡፡
በአውሮፓና በአሜሪካ የጉዲፈቻ መርህ “የህፃናትን ደህንነት ማስጠበቅ ነው” የሚለው አስተሳሰብ እየጠነከረ የመጣው ከመጀመሪያው የዓለም ጦርነት በኋላ ሲሆን ለዚህም ምክንያቱ በርካታ ልጆች ያለቤተሰብና አሳዳጊ በመቅረታቸውና ከጋብቻ ውጪ የሚወለዱ ልጆች በመበራከታቸው ነበር፡፡ ጉዲፈቻ አድራጊዎች በአብዛኛው ባለትዳር ጥንዶች ቢሆኑም በርካታ ያላገቡ (ወንደላጤ ወይም ሴተላጤ) ግለሰቦችም ልጆችን በጉዲፈቻ ወስደው ያሳድጋሉ፡፡
ሰዎች በተለያዩ ምክንያቶች የጉዲፈቻ ልጅ ሊፈልጉ ይችላሉ፡፡ ብዙዎች የአብራካቸውን ክፋይ ማግኘት ባለመቻላቸው (የማይወልዱ በመሆናቸው) የጉዲፈቻ ልጅ ሲያሳድጉ፣ ሌሎች ደግሞ አዲስ አባል ቤተሰባቸው ውስጥ ለመጨመር ሲሉ የጉዲፈቻ ልጅ ይወስዳሉ፡፡ አሳዳጊ ለሌለው ልጅ መኖሪያ ቤት ለመስጠትና ቤተሰብ እንዲኖረው ለማድረግም የጉዲፈቻ ልጅ የሚወስዱ ቁጥራቸው ቀላል አይደለም፡፡
ህፃናቱም በተለያዩ ምክንያቶች በጉዲፈቻ የሚያሳድጓቸው ቤተሰቦች የሚፈልጉበት ሁኔታ አለ። አንዳንዶቹ ወላጆቻቸውን በሞት በማጣታቸው ሊሆን ይችላል፡፡ ወላጆች ቢኖሩም በህመም ወይም በሌላ የግል ችግር ማሳደግ አቅቷቸው በጉዲፈቻ የሚሰጡበት ሁኔታም አለ፡፡ ሌሎች ደግሞ ተፈጥሯዊ ወላጆቻቸው ጥለዋቸው በጉዲፈቻ የሚሳድጋቸው ቤተሰብ ሊፈልጉ ይችላሉ፡፡
ፍላጐት ሳይኖራቸው የወለዱ ወላጆችን ማንነትን የሚያጋልጥ አለመሆኑ እንዲሁም የልጆችን ደህንነት የሚያስጠብቅ መሆኑ በህፃናት ሥነልቦናና ዕድገት ላይ በተደረጉ ጥናቶች መደገፉ ለጉዲፈቻ ከፍተኛ ተቀባይነት ማግኘት ምክንያት ሆኗል፡፡
በአሜሪካ “የጉዲፈቻና አስተማማኝ ቤተሰቦች ድንጋጌ” (Adoption and Safe Families Act 1997) መውጣት ጋር ተያይዞ የህፃናትን ጥቅም ይበልጥ ሊያስጠብቅ የሚችለው ዘላቂ የሆነ አያያዝ ነው የሚለው ይበልጥ እየታመነበት መጥቷል፡፡ ቀደም ሲል ልጆችን በተቻለ መጠን “ከቤተሰብ ጋር መቀላቀል” የሚለው መርህ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት የቆየ ሲሆን በዚህም ሳቢያ ልጆች ለረዥም ጊዜ በማሳደጊያ (ፎስተር ኬር) ውስጥ እንዲቆዩ ይደረግ ነበር - አሳዳጊ ቤተሰብ እስኪመጣ፡፡ ይሄ ደግሞ መንግስትን ለከፍተኛ ወጪ የሚዳርግ ከመሆኑም በላይ ልጆችን ከቤተሰብ ለመቀላቀል የሚደረገው ሙከራ በአብዛኛው እንደማይሳካ ተሞክሮዎች ያሳያሉ፡፡ አሁንም ቢሆን ልጆችን ከቤተሰብ ጋር መቀላቀል የሚለው መፍትሄ ቅድምያ የሚሰጠው ቢሆንም ህፃናት በማሳደጊያ ውስጥ ለረዥም ጊዜ መቆየታቸው በደህንነታቸው ላይ  አሉታዊ ተፅዕኖ እንዳለው ጥናቶች ይጠቆማሉ፡፡
የአሜሪካ የጉዲፈቻ ህግ ይሄን ለማስታረቅ የጊዜ ገደብ አስቀምጧል፡፡ ልጁ በተወሰነ የጊዜ ገደብ ውስጥ ከቤተሰቡ ጋር መቀላቀል ካልቻለ የወላጅነት መብት እንዲቋረጥ በቤተሰብ ላይ ክስ ተመስርቶ፣ ልጁ በጉዲፈቻ ሊመደብ እንደሚችል ህጉ ይደነግጋል፡፡ አሁን በአሜሪካ ተመራጩ የህፃናት እንክብካቤ መንገድ ጉዲፈቻ ሲሆን ለልጆች ዘላቂ መፍትሄ የሚሰጥ አማራጭ የእንክብካቤ መንገድ መሆኑ ይበልጥ እየታመነበት መጥቷል፡፡    
በኢትዮጵያ ጉዲፈቻ በትክክል መቼ እንደተጀመረ የሚጠቁም ጥናት ባይገኝም ከ1800 ክፍለ ዘመን መጀመርያ አንስቶ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች በባህላዊ መንገድ ይካሄድ እንደነበር ይገመታል፡፡ በተለይ በኦሮሞ ብሄረሰብ ዘንድ ይተገበር እንደነበርም ይነገራል፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ የህግ ማዕቀፍ የተበጀለት በ1952 ዓ.ም በወጣው የፍትሐብሄር ህግ ሲሆን በዚህ ህግ ስለ ድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ በግልፅ የተቀመጠ ነገር ባለመኖሩ፣ በፍትሐብሄር ህግ ውስጥ ያለውን የቤተሰብ ህግ ክፍል ከኢ.ፌ.ዲ.ሪ ህገ-መንግስት ጋር አጣጥሞ ማሻሻል አስፈልጓል፡፡ በዚህም መሰረት የተሻሻለ የቤተሰብ ህግ በአዋጅ ቁ፣ 213/92 ከ1992 ዓ.ም ጀምሮ ፀንቶ በስራ ላይ ውሏል፡፡   
ምንጭ - የጉዲፈቻ አሠራር በኢትዮጵያ
በወ/ሮ ረሂላ አባስ

ወጪው የኮሌጅ ክፍያን አያካትትም

በአሜሪካ ወላጆች አንድን ልጅ ከተወለደበት ጊዜ አንስቶ 18 አመት እስኪሞላው ድረስ በወጉ ተንከባክቦ ለማሳደግ የኮሌጅ ክፍያን ሳይጨምር ግማሽ ሚሊዮን  ዶላር ያህል ወጪ እንደሚጠይቃቸው ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
አሜሪካውያን ወላጆች አንድን ልጅ ለማሳደግ ወጪ የሚያደርጉት ገንዘብ እንደገቢያቸው መጠን የሚለያይ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፤ አነስተኛ ገቢ ያላቸው የአገሪቱ ወላጆች ከ145 ሺህ በላይ፣ መካከለኛ ገቢ ያላቸው ከ245 ሺህ በላይ፣ ከፍተኛ ገቢ ያላቸው ደግሞ 455 ሺህ ያህል ዶላር ወጪ እንደሚያደርጉ ገልጿል፡፡
ወጪዎቹ የተሰሉት ወላጆች ለቤት፣ ለምግብ፣ ለትራንስፖርት፣ ለአልባሳት፣ ለጤና፣ ለትምህርትና ለሌሎች ጥቃቅን ጉዳዮች የሚከፈሉ ገንዘቦችን መሰረት በማድረግ ሲሆን ባለፉት አመታት ለጤናና ለልጆች እንክብካቤ የሚወጣው ወጪ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱን ዘገባው አስረድቷል፡፡
በአገሪቱ እየናረ የመጣው የትራንስፖርትና የምግብ ዋጋ ለአሜሪካውያን ወላጆች ከፍተኛ ጫና እየፈጠረ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ ባለፉት አስር አመታት የነዳጅ ዋጋ በእጥፍ መጨመሩንና የምግብ ዋጋም ባለፉት ስድስት አመታት ከ13 በመቶ በላይ ጭማሪ ማሳየቱን አመልክቷል፡፡

ከ162 አገራት ‘ከግጭት ነጻ’ የሆኑት 11 ብቻ ናቸው ተባለ

ግጭት ባሉባቸው የዓለም አካባቢዎች ጦርነትን የማስቆምና ዓለምን ሁሉም ሰው ያለስቃይና ያለጦርነት ፍርሃት የሚኖርባት ሰላማዊ ስፍራ የማድረግ ዓላማ ያለው ዓለምአቀፍ የሰላም ጉባኤ በመጪው መስከረም መጀመሪያ በደቡብ ኮሪያ ሴኡል ከተማ እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ ለአዲስ አድማስ አስታወቁ፡፡
የኡራጋይ፣ የኖርዌይና የኮስታ ሪካን ፕሬዚዳንቶች ጨምሮ የተለያዩ የአለም አገራት መሪዎችና የሃይማኖት ተቋማት መሪዎች እንደሚሳተፉበት የሚጠበቀውን ይህን አለማቀፍ የሰላም ጉባኤ የሚያዘጋጀው፣ “ሄቨንሊ ካልቸር፣ ዎርልድ ፒስ፣ ሪስቶሬሽን ኦፍ ላይት” (HWPL) የተባለ የሰላም ባህልን በማህበረሰቦችና በዓለም አቀፍ ደረጃ በማጎልበት ጦርነትን ለማስቆም የሚሰራ መንግስታዊ ያልሆነ ዓለም አቀፍ ተቋም ነው፡፡
በመላው ዓለም በሃይማኖቶች መካከል ያሉ አለመግባባቶች ትላልቅ ግጭቶችን እንዳስከተሉ ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መግለጫ የጠቆመው ተቋሙ፤ ሰላምን ለመፍጠር አስቀድሞ በሃይማኖቶች መካከል ሰላምና መግባባት ማስፈን የሚል ተልዕኮ እንዳለው አስታውቋል። ከመላው ዓለም ከ40 አገራት የተወከሉ ተሳታፊዎች በሚገኙበት የሴኡሉ ታሪካዊ የሰላም ጉባኤ ግጭቶችን በማስቆም ላይ ያተኮሩ ውይይቶች፣ ባህላዊ ትርኢቶችና የሰላም የእግር ጉዞ እንደሚደረጉ ይጠበቃል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ በፊሊፒንስ በሃይማኖት ልዩነቶች በግጭት በምትታመሰው ዛምቦዋንጋ ከተማ ተጨባጭ የሰላም መፍትሄ ለማምጣት ያለመ ዓለም አቀፍ የሰላም ጉዞ ማካሄዱን ተቋሙ አክሎ ገልጿል። ባለፈው ነሐሴ 5 ለ3 ቀናት ተጀምሮ በተካሄደው 13ኛው የሰላም ጉዞ በዛምቦአኛ ከተማ በሚንዳናኦ ደሴት የፊሊፕንስ መንግስት ከፍተኛ አመራሮችና የሃይማኖት መሪዎችን ጨምሮ 12ሺ የሚገመት ህዝብ የተሳተፈበት የሰላም የእግር ጉዞ የተካሄደ ሲሆን 300 የፊሊፒንስ ፖሊሶች የተካፈሉበት የሰላም ፎረም መካሄዱን ተቋሙ በመግለጫው ጠቁሟል። የተቋሙ ፕሬዚዳንት ሚ/ር ሊ፤ 3ሺ ለሚደርሱ ተማሪዎች ሰላም ላይ ያተኮረ ትምህርት እንደሰጡም ለማወቅ ተችሏል፡፡ የሰላም ልኡኩ ከዚህ ቀደምም ወደ ፊሊፒንስ ተጉዞ እንደነበር ያስታወሰው ተቋሙ፤ የካቶሊክና የሙስሊም ሃይማኖት ተወካዮችን አገናኝቶ የወንድማማችነት ስምምነት በማፈራረም በሚንዳናኦ ከ40 ዓመት በላይ የዘለቀውን የሁለቱን ሃይማኖቶች ግጭት እንዳስቆመ ጠቁሟል፡፡ የሰላም  ተቋሙ በመላው ዓለም ከሚገኙ 81 አገራትና ከ321 ከወጣቶች ጋር ትስስር ካላቸው ድርጅቶች ጋር በትብብር እንደሚሰራ ታውቋል፡፡
በሌላ በኩል፣ ‘ኢንስቲቲዩት ፎር ኢኮኖሚክስ ኤንድ ፒስ” የተባለ ዓለማቀፍ ተቋም በሰራው ጥናት፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት በአለም ዙሪያ ከሚገኙ 162 አገራት ‘ከግጭት ነጻ’ የሆኑት 11 ብቻ እንደነበሩ በጥናት ማረጋገጡን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡በዘንድሮው የፈረንጆች አመት ከተለያዩ የአገር ውስጥም ሆነ የውጭ ግጭቶች የጸዱ ተብለው በጥናቱ የተለዩት አገራት ስዊዘርላንድ፣ ጃፓን፣ ኳታር፣ ሞሪሺየስ፣ ኡራጓይ፣ ቺሊ፣ ቦትስዋና፣ ኮስታ ሪካ፣ ቬትናም፣ ፓናማ እና ብራዚል ናቸው፡፡
እ.ኤ.አ ከ2007 ጀምሮ ባሉት አመታት የዓለማችን ሰላም ከጊዜ ወደጊዜ እየከፋ መምጣቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ጥናቱ ከተሰራባቸው 162 አገራት ግጭት የሌለባቸው 11 ብቻ ሆነው መገኘታቸውም ለዚህ አለማቀፍ ችግር ማሳያ ነው ብሏል፡፡
ምንም እንኳን አስራ አንዱ አገራት በ2013 ከግጭት ነጻ እንደሆኑ በጥናቱ ቢረጋገጥም፣ አገራቱ ለግጭት ሊዳርጓቸው ከሚችሉ ሌሎች ችግሮች ነጻ አይደሉም ያለው ዘገባው፣ ለአብነትም በብራዚልና በኮስታ ሪካ የአገር ውስጥ ግጭቶች ችግር እጅግ በጣም አነስተኛ ቢሆንም፣ የአገራቱ ዜጎች አነስተኛ የጦር መሳሪያዎችን የማግኘት እድላቸው ከፍተኛ በመሆኑ ሃይል የተቀላቀለባቸው ተቃውሞዎች የመካሄዳቸው እድል በአሳሳቢ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱን አስረድቷል፡፡
ጥናቱ በተሰራበት ወቅት ሰላማዊ የነበረችው ብራዚል ከወራት በፊት ባስተናገደችው የዓለም የእግር ኳስ ዋንጫ ውድድር ሳቢያ በተቀሰቀሰባት የህዝብ አመጽ የተነሳ በቀጣዩ አመት ይወጣል ተብሎ በሚጠበቀው የ2014 ከግጭት ነጻ አገራት ዝርዝር ውስጥ እንደማትኖር ዘገባው ገልጿል፡፡
አንድ አገር ከግጭት ነጻ ለመባል፣ ተቋሙ ያወጣቸውን የግጭት መለኪያ መስፈርቶችን በሙሉ ማሟላት እንደሚገባውና በአገሩ የግዛት ክልል ውስጥ በሁለት የታጠቁ ሃይሎች መካከል (ቢያንስ አንዱ መንግስት መሆን አለበት) በተፈጠረ ግጭት በአመት ውስጥ ከ25 በላይ የሞት አደጋ ያልተከሰተበት መሆን አለበት፡፡ በድንበር አካባቢም ግጭት መኖር የለበትም፡፡
አሜሪካ ተቋሙ ባወጣው የሰላማዊነት ደረጃ 101ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ዘገባው ጨምሮ ገልጿል፡፡

ኢራናዊቷ የሂሳብ ባለሙያ ፕሮፌሰር ሜርያም ሚርዛካኒ፤ አለማቀፉ የሂሳብ ህብረት የሚሰጠውንና ከኖቤል ሽልማት ጋር የሚስተካከለውን የፊልድስ ሜዳል ሽልማት መቀበሏን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በየአራት አመቱ በአለማቀፍ ደረጃ የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ የሂሳብ ተመራማሪዎች የሚሰጠውን ይህን ሽልማት በመውሰድ የመጀመሪያዋ የሆነችው ፕሮፌሰር ሚርዛካኒ፤ ትኩረቷን በጂኦሜትሪ ላይ በማድረግ፣ ሬማን ሰርፌስስ ከተባሉ ቅርጾች ጋር የተያያዘና ውስብስብ ሂሳባዊ ቀመር የሚጠይቅ የምርምር ውጤት ይፋ በማድረጓ ለሽልማት እንደበቃች ዘገባው ገልጿል፡፡
የአንደኛና የሁለተኛ እንዲሁም የከፍተኛ ትምህርቷን በቴህራን የተከታተለችው ሚርዛካኒ፤ ወደ አሜሪካ በማቅናት የፒኤችዲ ትምህርቷን በሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ የተከታተለች ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅትም ካሊፎርኒያ በሚገኘው ስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ በመምህርነትና በተመራማሪነት እየሰራች ትገኛለች፡፡ 

አመታዊ የማስታወቂያ ገቢው 50 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል
ለስኬቱ የአንበሳውን ድርሻ የምትወስደው አንዲት ሴት ናት ተብሏል
ከአስርት አመታት በፊት በይዘትም ሆነ በአቀራረብ ጥራቱን ያልጠበቀና ደረቅ ፕሮፓጋንዳ የነበረው የቻይና የማስታወቂያ ዘርፍ፣ በከፍተኛ ፍጥነት በማደግ በአመት 50 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ወደሚያስገኝ ዘመናዊ የማስታወቂያ ኢንዱስትሪነት መሸጋገሩንና፣ በዘንድሮው የዓለም የማስታወቂያ ገበያ ሁለተኛውን ደረጃ መያዙን ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
የቻይና የማስታወቂያ ኢንዱስትሪ በአሁኑ ወቅት ከአውሮፓና ከሌሎች የአለም አገራት ታላላቅ የማስታወቂያ ኩባንያዎች ጋር ተፎካካሪ እንደሆነና በአትራፊነት የሚጠቀስ መሆኑን የጠቆመው ሲኤንኤን፣ ኢንዱስትሪው ከነበሩበት ችግሮች ተላቆ ዘመናዊ አደረጃጀትና አሰራር እንዲይዝ በማድረግ በኩል የአንበሳውን ድርሻ የምትወስደው ቻይናዊቷ የማስታወቂያ ባለሙያና ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሺናን ቹዋንግ እንደሆነች ገልጿል፡፡
በማስታወቂያው ዘርፍ ከ30 አመታት በላይ እንደቆየች የተነገረላት ቹዋንግ፤ በአሁኑ ወቅት በዘርፉ በአለማቀፍ ደረጃ ስማቸው ጎልቶ ከሚጠቀሱ የማስታወቂያ ድርጅቶች አንዱ የሆነውንና ትርፋማውን “ኦጊልቪ ኤንድ ማተር ግሬተር ቻይና” የተባለ የአገሪቱ ኩባንያ በዋና ስራ አስፈጻሚነት ከመምራት ባሻገር የቻይናን የማስታወቂያ ኢንዱስትሪ በአመት ከ50 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ የሚያገኝበት ደረጃ ላይ ያደረሰች ብርቱ ሴት መሆኗን ዘገባው ይጠቁማል፡፡
ቹዋንግ በማስታወቂያው ዘርፍ በቆየችባቸው አመታት በአገር አቀፍ ደረጃ ተቋማዊና የአሰራር ለውጥ በመፍጠር ረገድ ሰፋፊ ስራዎችን አከናውናለች ያለው ዘገባው፤ አሁን ዋና በስራ አስፈጻሚነት በምትመራው ኩባንያ፤ አለማቀፍ የጥራት ደረጃዎችን የጠበቁ ማስታወቂያዎችን በመስራት ትልቅ ስኬት መጎናጸፍ መቻሏን አመልክቷል፡፡
ኩባንያው በቴክኖሎጂ የታገዙና ፈጠራ የታከለባቸውን አለማቀፍ የምርትና የአገልግሎት እንዲሁም የቅስቀሳ ማስታወቂያዎች በብዛት በመስራት ላይ እንደሚገኝ ጠቁሞ፣ ኩባንያው ለኮካ ኮላ በሰራው ማስታወቂያ የ “ኬንስ ግራንድ ፕሪክስ”ን ሽልማት ለመቀበል መብቃቱንም አስታውሷል፡፡

          አዲስ አበባ ለወደፊት በኢንቨስትመንት ዘርፍ ተመራጭ የሆኑ የአፍሪካ 10 ቀዳሚ አገራት በሚል ግሎባል ኢኮኖሚ ዎች በቅርቡ ባወጣው ሪፖርት ውስጥ መካተቷን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ተቋሙ በአህጉሪቱ በቀጣይ ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻዎች ይሆናሉ ባላቸው ከተሞች ዝርዝር ውስጥ ከአዲስ አበባ በተጨማሪ ኢባዳንና ካኖ የተባሉትን የናይጀሪያ ከተሞች፣ የቡርኪናፋሶዋን ኡጋዱጉ፣ የሴኔጋሏን ዳካር፣ የኬንያዋን ናይሮቢ፣ የኮትዲቯሯን አቢጃኒን፣ የሱዳኗን ካርቱም፣ የአንጎላዋን ሉዋንዳና የታንዛንያዋን ዳሬ ሰላም ማካተቱን ሚኒስቴሩ በድረገጹ ያወጣው መረጃ ያሳያል፡፡
ተጨባጭ የኢንቨስትመንት አማራጭ ያለባቸው ከተሞች በቀጣዮቹ ሁለት አስርት አመታት  በእጥፍ ያህል እንደሚያድጉ የተነበየው የተቋሙ ሪፖርት፣ እነዚህ ከተሞች ወደሌሎች አገራት የመስፋፋት ጥረት በማድረግ ላይ የሚገኙ የንግድ ተቋማት ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ እንደሚሆኑም አመልክቷል፡፡
በእነዚህ ከተሞች የሚካሄደውን የመሰረተ ልማት አውታሮች የማስፋፋት እንቅስቃሴ በተፋጠነ ሁኔታ አጠናክሮ መቀጠል ይገባል ያለው ሪፖርቱ፣ የመሰረተ ልማት አውታሮች መስፋፋት በአህጉሪቱ እድገትን ለማፋጠን ቁልፍ ሚና እንደሚጫወትና ማህበረሰቡን ያቀፈ ዘላቂ እድገት ለማስመዝገብ ወሳኝ እንደሆነ ጨምሮ ገልጧል፡፡ 

አለማቀፍ የቡና ገበያንና ተጠቃሚነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው

ኢትዮጵያ በመጪዎቹ አስራ ሁለት ወራት ለውጭ ገበያ ከምታቀርበው የቡና ምርት የምታገኘው ገቢ በ25 በመቶ እድገት ያሳያል ተብሎ እንደሚጠበቅ ብሉምበርግ ዘገበ፡፡
በቡና ምርትና በአቅራቢነት ከአለም ቀዳሚ በሆነችው ብራዚል በተከሰተው ድርቅ ምክንያት በአለም የቡና ገበያ ላይ የዋጋ ጭማሪ ይፈጠራል ተብሎ እንደሚጠበቅ የገለጸው ዘገባው፣ ኢትዮጵያም በተያዘው የፈረንጆች አመት ለውጭ ገበያ ከምታቀርበው የቡና ምርት 900 ሚሊዮን  ዶላር ያህል ገቢ ታገኛለች ተብሎ እንደሚጠበቅ ዘገባው አመልክቷል፡፡
የኢትዮጵያ ቡና ላኪዎች ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ አለምሰገድ አሰፋን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ የአለም ገበያ የቡና አቅርቦት እጥረት የሚቀጥል ከሆነ በኢትዮጵያ የምርት ገበያ አማካይነት ለገበያ በሚቀርበው የአረቢካ ቡና ዋጋ ላይ በፓውንድ የ2 ዶላር ጭማሪ ሊገኝ ይችላል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ኢትዮጵያ እስካለፈው ሃምሌ ወር መጀመሪያ በነበሩት 12 ወራት ለውጭ ገበያ ካቀረበችው ቡና 719 ሚሊዮን ዶላር ማግኘቷን ያስታወሰው ዘገባው፣ ይህም ከአንድ አመት በፊት ከነበረው ጋር ሲነጻጸር የ3 ነጥብ 7 በመቶ ብልጫ እንዳለው ጠቅሷል። በተመሳሳይ ጊዜ ለውጭ ገበያ ባቀረበችው የቡና ምርት መጠን ላይ የ4 ነጥብ 1 በመቶ ቅናሽ መታየቱንም አመልክቷል፡፡
በዚህ አመት በአገሪቱ 500 ሺህ ቶን ቡና ይመረታል ተብሎ እንደሚጠበቅና፣ ከዚህ ውስጥም ግማሽ ያህሉ ወደተለያዩ አገራት ገበያ የሚላክ እንደሚሆንም ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡
የኢትዮጵያ ቡና ላኪዎች ማህበር ከተለያዩ የአለም አገራት አዳዲስ የቡና ምርት ገዢዎችን ለመሳብና አገሪቱ በአለማቀፉ የቡና ገበያ ውስጥ ያላትን ድርሻ ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝም አስታውቋል፡፡ ወርልድ ቡሊቲን በበኩሉ፤ ከአፍሪካ ቀዳሚዋ የቡና አምራች የሆነችው ኢትዮጵያ ለአለም ገበያ የምታቀርበውን የቡና ምርት የንግድ ምልክት በማውጣት የበለጠ በገበያው ውስጥ ተወዳዳሪ ለማድረግ በአለማቀፍ ደረጃ ታዋቂ ከሆኑ ቡና ገዢ ኩባንያዎች ጋር እየሰራች መሆኗን ዘግቧል፡፡
ከኩባንያዎቹ ጋር የተጀመረው ስራ ህገወጥ የቡና ንግድንና አላግባብ የሚጣል የቡና ዋጋ ተመንን የመከላከል እንዲሁም የአገሪቱን የቡና የንግድ ምልክቶች በመጠቀም ትርፋማነትን የማሳደግ ዓላማ ያለው ነው ተብሏል፡፡
በአገሪቱ በቡና ልማት ውስጥ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ተሳትፎ የሚያደርጉ 15 ሚሊዮን ዜጎች እንዳሉ የጠቆመው ዘገባው፣ እነዚህ ዜጎች ከሽያጩ የሚያገኙት ገቢ ከ10 በመቶ በታች እንደሆነና የተቀረውን የሚወስዱት በአለማቀፍ ደረጃ የሚገኙ ነጋዴዎችና አከፋፋዮች መሆናቸውን ገልጧል፡፡
እስካሁን ድረስ 34 አገራት በደቡብና በምስራቅ ኢትዮጵያ የሚመረቱ የቡና ዝርያዎች መለያዎችንና የንግድ ምልክቶችን ተቀብለው ለገበያ እያቀረቡ እንደሚገኙ ገልጾ፣ በቀጣይም በአውስትራሊያና በብራዚል ተመሳሳይ ስራ ለመስራት እንቅስቃሴ መጀመሩን አስረድቷል፡፡

       የብሄራዊ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን የስማርት ቴክኖሎጂ ውጤት የሆኑ የኤሌክትሪክ ቆጣሪዎችን አምርቶ ለኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ማቅረብ የጀመረ ሲሆን ቴክኖሎጂው በሃገር ውስጥ መሰራቱ የሃገር ደህንነትን ለማስጠበቅ ከፍተኛ ፋይዳ አለው ተብሏል፡፡
ከውጭ በከፍተኛ ምንዛሬ የሚገቡትን ቆጣሪዎች ሙሉ ለሙሉ እንደሚያስቀር የተነገረለት የኤሌክትሪክ ቆጣሪ “አይቲ ፕላስ ስማርት ኢነርጂ ሜትር” በመባል የሚታወቅ ሲሆን እስካሁን ከሚሰራበት ቴክኖሎጂ በተሻለ ሁኔታ መስራት የሚችሉ የተለያዩ አገልግሎቶችን ያካተተት ነው ተብሏል፡፡
የብኢኮ ም/ዋና ዳይሬክተር ብርጋዴር ጄነራል ጠና ቁርንዲ ከትናንት በስቲያ ከስራ ባልደረቦቻቸው ጋር በሒልተን ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንዳስታወቁት፤ ቆጣሪው የወደፊቱን የቴክኖሎጂ እድገት እያንዳንዱ ቆጣሪ ያለሰው ንክኪ ከዋና ማዕከል ጣቢያ ጋር በርቀት መቆጣጠሪያ እየተገናኘ የሚሰራበት በመሆኑ በኃይል አቅርቦት ላይ ያነጣጠሩ ሃገራዊ የደህንነት ስጋቶችን መቆጣጠርና መከላከል ያስችላል ብለዋል።
ደህንነትን ያስጠብቃል የተባለው የኤሌክትሪክ ቆጣሪው፤ ከንድፉ እስከ ምርት ድረስ በብረታ ብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን እና በስሩ ባሉት ተቋማት የተፈበረከ ሲሆን የፕላስቲክ ክፍሉ በኢትዮ ፕላስቲክ ኢንዱስትሪ፣ የብረታ ብረት ክፍሉ ደግሞ በብረታ ብረትና ፋብሪኬሽን ኢንዱስትሪ እንዲሁም የተለያዩ ምርቶች በህብረት ማኑፋክቸሪንግ ማሽን ግንባታ ኢንዱስትሪ የተመረተ ነው ተብሏል፡፡ ፋብሪካው ሙሉ ለሙሉ ወደ ስራ ሲገባም በቀን 1200 ቆጣሪዎችን የማምረት አቅም አለው ተብሏል፡፡
የኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያ ሲስተም ለጦርነት ጥቃት እንደሚውል ይታወቃል ያሉት ምክትል ዳይሬክተሩ፤ ብ/ጄነራል ጠና ቴክኖሎጂው ሙሉ ለሙሉ የሃገር ውስጥ መሆኑ በኃይል ላይ አነጣጥሮ የሚፈፀም የጦር ጥቃትን በቀላሉ ለመቆጣጠር እንደሚያስችል ገልፀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋየር ቢዝነስ ስራ አስፈፃሚ አቶ ቢትወደድ ገ/አሊፍ በበኩላቸው፤ “ቴክኖሎጂው በደንበኛውና በአገልግሎት አቅራቢው መካከል ጥብቅ ቁርኝትን ይፈጥራል፤ ቆጣሪ አንባቢነትን አስቀርቶም ደንበኞች የራሳቸውን ሂሳብ አውቀው በቢል መልክ እንዲከፈሉ ያስችላል” ብለዋል፡፡ ቆጣሪ አንባቢነት ቢቀርም የሚፈናቀል ሰራተኛ አይኖርም፤ ሌሎች ስራዎች ይሰጣቸዋል ሲሉ ኃላፊው ጨምረው ገልፀዋል፡፡
አዲሱ ስማርት ቆጣሪ በርቀት መቆጣጠሪያ የሚታገዝ በመሆኑም አደጋ ሲያጋጥም በቀላሉ ለዋና ማዕከል መልዕክት ስለሚያስተላልፍ ኃይል በመቀነስ መቆጣጠር ያስችላል፤ ቆጣሪው ንክኪ ሲደረግበት በቀጥታ ለማዕከሉ መረጃ ያቀብላል ተብሏል፡፡
ኢብኮ አንዱን ቆጣሪ በ2500 ብር ለኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የሚያቀርብ መሆኑ የተጠቆመ ሲሆን ቆጣሪው በቅርቡ አገልግሎት ላይ እንደሚውል ተገልጿል፡፡