Administrator

Administrator

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለአለማችን የአቪየሽን ኢንዱስትሪ ፈታኝ የነበረውን የበጀት አመት ክብረ ወሰን ባስመዘገበ ስኬት ማጠናቀቁን አስታወቀ፡፡
አየር መንገዱ ከትናንት በስቲያ በፌስቡክ ድረገጹ ላይ ባስነበበው መረጃ እንዳለው፣ አመታዊ ገቢውን አምና ከነበረበት 21 በመቶ በማሳደግ፣ በአመቱ 46 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር አድርሷል፡፡ ተሳፋሪዎችን የማመላለስ አቅሙን በ17 በመቶ ከፍ ማድረጉንና ከተሳፋሪዎች የሚያገኘውን ገቢ በ16 በመቶ ማሳደጉንም አስታውቋል፡፡
እጅግ ዘመናዊ እንደሆነ የሚነገርለትን ቦይንግ 787 ድሪምላይነር አውሮፕላን ጨምሮ፣ 13 አዳዲስ አውሮፕላኖችን ገዝቶ ወደ አገር ውስጥ ማስገባቱን የገለጸው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ 9 አዳዲስ መዳረሻዎች በረራ መጀመሩንም ተናግሯል፡፡

ለአዲስ አበባ ከተማ የቀላል ባቡር ፕሮጀክት 41 ባቡሮችን ለመስራት ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ስምምነት የፈጸመውና ካለፈው ግንቦት ወር ጀምሮ ስራውን በማከናወን ላይ የሚገኘው ‘ቻይና ሲ ኤን አር ቻንግቹን ሬልዌይ ቪሄክልስ’ የተባለው የቻይና ባቡር አምራች ኩባንያ የመጀመሪያውን ባቡር ሰርቶ ማጠናቀቁን አስታወቀ፡፡
የኩባንያው ዋና ስራ አስኪያጅ ሊዩ ጋንግ፣ ባቡሩ በሰዓት 70 ኪሎሜትሮች የመጓዝ አቅም እንዳለው፣ ነጭና አረንጓዴ ቀለም እንዳለው እንዲሁም ለተሳፋሪዎች ምቹ በሆነና የጸሃይ ብርሃንን ለመከላከል በሚያስችል መልኩ ዲዛይን መደረጉን ለቻይናው የዜና ወኪል ዥንዋ ተናግረዋል፡፡“በመጪው መስከረም ወር 50 ኢትዮጵያውያን የባቡር አሽከርካሪዎችንና የጥገና ሰራተኞችን ወደ ኩባንያችን በማስመጣት አስፈላጊውን ስልጠና ለመስጠት እየተዘጋጀን ነው” ያሉት ስራ አስኪያጁ፣ ኩባንያው ሁሉንም ባቡሮች በታሰበው የጥራት ደረጃ ሰርቶ ለማጠናቀቅና በተቀመጠው ጊዜ ለማስረከብ እየሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል፡፡የመገጣጠም ስራው ሙሉ ለሙሉ የተጠናቀቀው የመጀመሪያው ባቡር፣ በቻይና የሰሜን ምስራቅ ግዛት ጂሊን ውስጥ በምትገኘውና የኩባንያው መቀመጫ በሆነችው ቻንግቹን ከተማ ባለፈው ማክሰኞ የተሳካ የሙከራ ጉዞ እንዳደረገ ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት የባቡር ስራውን ለኩባንያው የሰጠው ባለፈው ግንቦት ወር መሆኑን ያስታወሰው ዘገባው፣ ኩባንያው እስከ መጪው ጥር ወር ሁሉንም ባቡሮች አጠናቆ ለማስረከብ ተዋውሎ በመስራት ላይ እንደሚገኝ አስረድቷል፡፡
የከተማ ባቡር ትራንስፖርት በአፍሪካ አህጉር በጅማሬ ላይ ያለ ዘርፍ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፣ ከደቡብ አፍሪካ በስተቀር በሌሎች አገራት እምብዛም አለመስፋፋቱንና ይህም ለቻይና የባቡር አምራች ኩባንያዎች ከፍተኛ የገበያ ዕድል የሚፈጥር እንደሆነ አመልክቷል፡፡
በአህጉሪቱ ቀላል የከተማ ባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት የተዘረጋባቸው አገራት አልጀሪያ፣ ግብጽ፣ ሞሮኮና ቱኒዚያ እንደሆኑ የጠቀሰው ዘገባው፤ የምድር ውስጥ የባቡር መስመር ያለባቸው የአፍሪካ ከተሞች ደግሞ ካይሮና አልጀርስ ብቻ መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡

       በአለማቀፍ ደረጃ ዘመናዊ የባንክ ክፍያ ስርዓቶችን በመዘርጋት የሚታወቀው ቢፒሲ ባንኪንግ ቴክኖሎጂስ የተባለ ኩባንያ፣ በኢትዮጵያ ‘ስማርትቪስታ’ የተሰኘ ዘመናዊ የባንክ ክፍያ ስርዓት ሊዘረጋ መሆኑን ባንክስ ቢዝነስ ሪቪው ድረ-ገጽ ትናንት ዘገበ፡፡የ “ስማርትቪስታ” የተባለውን የክፍያ ስርዓት የመዘርጋት ሃላፊነቱን በአገሪቱ የሚገኙ ሁሉም ባንኮች በጋራ ከመሰረቱት የኢትዮጵያ ባንኮች ጥምረት የተረከበውና ተቀማጭነቱ በስዊዘርላንድ የሆነው ቢፒሲ ባንኪንግ ቴክኖሎጂስ፣ በአገሪቱ ሊዘረጋው ያቀደው የክፍያ ስርዓት ዘመናዊና ለአጠቃቀም ምቹ መሆኑ ተመራጭ እንዳደረገው ገልጿል፡፡
የኢትዮጵያ ባንኮች ጥምረት አዲሱን የክፍያ ስርዓት ለመዘርጋት ያቀደው፣ ሁሉንም የአገሪቱ ባንኮች በአንድ የገንዘብ ዝውውር ማዕከል አማካይነት ለማስተሳሰርና ደንበኞች የተለያዩ የባንክ አገልግሎቶችን በኤቲኤም፣ በፖይንት ኦፍ ሴል ዲቫይስ፣ በሞባይልና በኢንተርኔት አማካይነት እንዲያገኙ ለማስቻል በማሰብ እንደሆነ ዘገባው አስረድቷል፡፡
ኩባንያው በቀጣይም “ስማርትቪስታ” በተሰኘው ዘመናዊ የክፍያ ስርዓት አማካይነት የአገሪቱ ባንኮች ቪዛ ካርድንና ማስተር ካርድን በመሳሰሉ የመክፈያ ካርድ አሰራሮች አለማቀፍ ክፍያዎችን መፈጸም የሚችሉበትን አሰራር እንደሚዘረጋ ተነግሯል፡፡
የቢፒሲ ባንኪንግ ቴክኖሎጂስ የአፍሪካ ቅርንጫፍ ስራ አስኪያጅ ዳሪል በርግ፣ መሰል ፕሮጀክቶችን በመላው አለም በስኬታማ መንገድ በማከናወን የካበተ ልምድ ያለው ኩባንያው፣ በኢትዮጵያም የዘመኑ ቴክኖሎጂ የደረሰበትን ጠንካራና የተሻሻለ የክፍያ መሰረተ ልማት እንደሚዘረጋ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡  የኢትዮጵያ ባንኮች ጥምረት ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ብዙነህ በቀለ በበኩላቸው፣ ጥምረቱ በባንኮች ውስጥ የሚከናወነውን የክፍያ አሰራር ሂደት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማገዝ በበለጠ ሁኔታ የተቀላጠፈ፣ ግልጽነት ያለውና ደህንነቱ የተጠበቀ የማድረግ ዓላማ ይዞ በመስራት ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡
“በአገሪቱ ዘመናዊ የባንክ ክፍያ ስርዓት ለመዘርጋት የያዝነውን እቅድ ተግባራዊ ለማድረግ፣ በዘርፉ በአለማቀፍ ደረጃ የሚሰሩ ኩባንያዎችንና የክፍያ ስርዓቶችን የመገምገም ስራ በስፋት ከተከናወነ በኋላ፣ ወቅታዊውንና የወደፊቱን ዘርፈ-ብዙ ፍላጎታችንን የሚያሟላው “ስማርትቪስታ” በመሆኑ ልንመርጠው ችለናል” ብለዋል አቶ ብዙነህ፡ቢፒሲ ባንኪንግ ቴክኖሎጂስ በአሁኑ ወቅት በ45 የተለያዩ የአለም አገራት ለሚገኙ 126 ደንበኞቹ በዘርፉ አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፣ የኢትዮጵያ ባንኮች ጥምረትም እ.ኤ.አ በ2011 በብሄራዊ ባንክና በአገሪቱ በሚገኙ ሁሉም ባንኮች ያቋቋሙትና ለፋይናንስ ተቋማት ብሄራዊ የክፍያ ስርዓት ለመዘርጋት ያለመ አክስዮን ማህበር መሆኑን አስታውቋል፡፡



          ከሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ በህግ ሙያ የተመረቀችውና በአሜሪካ በአካል ጉዳተኞች መብት ተሟጋችነት በመስራት ላይ የምትገኘው፣ ማየትና መስማት የተሳናት ትውልደ ኢትዮጵያዊት የህግ ጠበቃ ሃቤን ግርማ፣ በአካል ጉዳተኞች ላይ መድልኦ ይፈጽማል ስትል ስክሪፕድ የተባለውን ታዋቂ የአሜሪካ የድረገጽ ኩባንያ መክሰሷ ተዘገበ፡፡ ቢዝነስ ኢንሳይደር ድረገጽ ባለፈው ሳምንት እንደዘገበው፤ ዲጂታል መረጃዎችን ለአንባብያን በስፋት በማቅረብ የሚታወቀው ስክሪፕድ የተባለው ኩባንያ፣ የሚከተለው አሰራር ማየት የተሳናቸው አንባቢዎችን ፍላጎት ያላሟላና መድልኦ የሚፈጥር ነው በማለት ነው ሃቤን በኩባንያው ላይ ክስ የመሰረተችው፡፡ የ26 አመቷ ጠበቃ ሃቤን ግርማ፤ ‘ናሽናል ፌደሬሽን ኦፍ ዘ ብላይንድ’ እና ‘ብላይንድ ቬርሞንት ማዘር ሄዲ ቪነስ’ የተባሉትን የአሜሪካ የአይነስውራን መብቶች ተሟጋች ተቋማት በመወከል በስክሪፕድ ላይ በመሰረተችው ክስ፣ ኩባንያው የድረገጽ አገልግሎቶቹ ሆን ብሎ ለአይነስውራን አንባብያን ተደራሽ እንዳይሆኑ በማድረግ፣ የአገሪቱን የአካል ጉዳተኞች ህግ በሚጥስ መልኩ ያልተገባ ድርጊት ፈጽሟል ብላለች፡፡

ስክሪፕድ ከ40 ሚሊዮን በላይ በሚሆኑ የተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ ያጠናከራቸውን መረጃዎች በድረገጹና በአፕሊኪሽኖቹ አማካይነት ለደንበኞቹ 8 ነጥብ 99 የአሜሪካ ዶላር ወርሃዊ ክፍያ በማስከፈል የሚያሰራጭ ሲሆን በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ የሚጽፉ ደንበኞቹን ስራዎች በድረገጽ አማካይነት ታትመው ለንባብ እንዲበቁ በማድረግ፣ በአለማቀፍ ዙሪያ ሰፊ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ የሚገኝ ኩባንያ መሆኑን ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡ስትወለድ ጀምሮ ማየትና መስማት የተሳናት ሃቤን፤ ትምህርቷን የተከታተለችው በአሜሪካ ሲሆን የመጀመሪያ ዲግሪዋን ከሊዊስ ኤንድ ክላርክ ኮሌጅ ተቀብላለች፡፡ ከሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲም በህግ የሁለተኛ ዲግሪ ይዛለች፡፡ በአሁኑ ወቅትም በበርክሌይ የአካል ጉዳተኝነት መብት ተሟጋች ጠበቃ በመሆን እያገለገለች ትገኛለች፡፡የቢዝነስ ኢንሳይደር ድረገጽ ‘የ2013 እጅግ አስደማሚ 20 ምርጥ የሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች’ በሚል ባለፈው አመት ከመረጣቸው ተጠቃሽ ተማሪዎች መካከል ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ ሃቤን ግርማ አንዷ እንደነበረች ዘገባው አስታውሷል፡፡

Saturday, 30 August 2014 10:30

ጋዛ - ከእንባ ወደ እልልታ…

           ለሰባት ሳምንታት የማያባራ የሮኬት ድብደባ ሲወርድባት የዘለቀች፣ 490 ያህል ጨቅላዎቿን ጨምሮ 2 ሺህ 142 ዜጎቿን በሞት የተነጠቀች፣ አይሆኑ ሆና የፈራረሰችው ጋዛ፤ ከከረመባት መከራና ስቃይ ለጥቂት ጊዜም ቢሆን እፎይ አለች፡፡ ባለፈው ማክሰኞ አመሻሽ ላይ፣ ተረኛውን ሮኬት በፍርሃት እየተርበተበቱ የሚጠብቁት የጋዛ ሰዎች፤ ያልጠበቁትን ከወደ ካይሮ ሲደገስ የሰነበተ አንዳች በጎ ነገር አደመጡ፡፡ የፍልስጤሙ ፕሬዚደንት ማሃሙድ አባስ ከወደ ዌስት ባንክ ይፋ ያደረጉት መረጃ፣ እርግጥም ጧት ማታ በሮኬት ድብደባ አሳር መከራዋን ስታይ ለነበረችው የፈራረሰችው ጋዛ ትልቅ የምስራች ነበር፡፡ ፕሬዚዳንቱ እስራኤል በፍልስጤም የቀረበውን የተኩስ አቁም ስምምነት በጄ ብላ መቀበሏን ማብሰራቸውን፣ ሃማስም የድል ብስራት ዜናውን ለጋዛ ነዋሪዎች በአጭር የጽሁፍ መልዕክት ማድረሱን ተከትሎ፣ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ፍልስጤማውያን በጋዛ ጎዳናዎችና በአደባባዮች ወጥተው ደስታቸውን ገለጹ፡፡ ጣቶቻቸውን ከፍ አድርገው በማውጣት የ v ምልክት አሳይተዋል - “ድል ለፍልስጤም ሆነ!” ለማለት፡፡ የሃማሱ ምክትል መሪ ሞሱአ አቡ ማርዙክም ቢሆኑ፣ እስራኤል የቀረበላትን የተኩስ አቁም ስምምነት ሃሳብ መቀበሏ፣ ለሃማስ ትልቅ ድል ነው ብለዋል፡፡ የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር የመካከለኛው ምስራቅ አገራት ቃል አቀባይ ኦፊር ጌንዴልማን በበኩላቸው፤ አገሪቱ በጋዛ ስታደርገው የነበረው ወታደራዊ ዘመቻ በድል መጠናቀቁን ነው የሚናገሩት፡፡

ሃማስ ከዚህ ቀደም በግብጽ ቀርቦለት አሻፈረኝ ያለውን የሰላም ሃሳብ ነው መልሶ የተቀበለው ይላሉ ቃል አቀባዩ፡፡ በግጭቱ 69 ያህል ዜጎቿን ያጣችው እስራኤል የመንግስት ቃል አቀባይ የሆኑት ማርክ ሬጌቭ በበኩላቸው፣ ሃማስ ባለፈው ሃምሌ ወር አጋማሽ ላይ የቀረበለትን የሰላም ስምምነት ሃሳብ በወቅቱ ቢቀበል ኖሮ፣ ይሄ ሁሉ ደም መፋሰስ ባልኖረ ነበር በማለት ተጠያቂነቱን ወደ ሃማስ አድርገዋል፡፡ ስምምነቱን እውን ለማድረግ ደፋ ቀና ሲሉ ለቆዩት ለግብጽ፣ ለኳታርና ለአሜሪካ ምስጋና ይግባቸውና፣ አሁን ደም አፋሳሹ የሁለቱ አገራት ግጭት ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን ጋብ ብሎ የሚቆይበት ሁነኛ የተኩስ አቁም ስምምነት በሁለቱ ሃይሎች መካከል እንዲደረስ አስችለዋል፡፡ የአልጀዚራው ዘጋቢ አንድሪው ሲሞንስ ከጋዛ በላከው ዘገባ እንዳለው፣ በሁለቱ ሃይሎች መካከል የተደረሰው ስምምነት፣ እስራኤል የዘጋቻቸውን የጋዛ መግቢያዎች በአፋጣኝ እንድትከፍትና በሂደትም በጋዛ ሰርጥ አካባቢ የጣለችውን የእንቅስቃሴ ገደብ እንድታነሳ የሚያደርግ ነው፡፡ በእስራኤልና በፍልስጤም መካከል ተጀምሮ የተቋረጠው ውይይትም በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ እንደሚቀጥል ዘግቧል፡፡ሃማስ በቀጣይ በጋዛ ውስጥ የአየር ማረፊያና የባህር ወደብ ማቋቋም ይገባኛል፣ ፍልስጤማውያን እስረኞችም መፈታት ይኖርባቸዋል እያለ ሲሆን እስራኤልም የጋዛን ነዋሪዎች ሙሉ ለሙሉ ትጥቅ ማስፈታት እፈልጋለሁ እያለች ነው፡፡ እንዲህ እና እንዲያ ያሉ ከግራና ቀኝ የሚነሱ ጥያቄዎች፣ በሁለቱ ሃይሎች መካከል ይካሄዳል በተባለው ቀጣይ ውይይት እልባት ያገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡

ስምምነቱ ጋዛን ከግብጽ ጋር የሚያዋስነው 9 ማይል የሚረዝመው የራፋህ ድንበር እንዲከፈት፣ የጋዛ ድንበሮች በፍልስጤም ሃይሎች ቁጥጥር ውስጥ እንዲሆኑና የመልሶ ግንባታ ስራውን የመምራት ሃላፊነቱንም የፍልስጤም መንግስት እንዲወስድ የሚያደርግ ሲሆን፣ እስራኤልም በጋዛ ውስጥ ያላትን የደህንነት እንቅስቃሴ አሁን ካለበት 300 ሜትር ክልል ወደ 100 ሜትር እንድትቀንስ፣ ከአየርና ከምድር የምትሰነዝረውን ወታደራዊ ጥቃት እንድታቆም የሚያስችል ነው ተብሏል፡፡ በሁለቱ ሃይሎች መካከል የተደረሰው ይህ ስምምነት እንደሚለው፣ የፍልስጤም መንግስት የጋዛን ድንበር ከሃማስ ሃይሎች ተረክቦ የመቆጣጠር ሃላፊነቱን ይወስዳል፤ እስራአልም ከጋዛ ድንበር በሶስት ማይል ርቀት ገድባው የነበረውን የአሳ ማስገር ስራ ወደ ስድስት ማይል ማስፋት ይጠበቅባታል፡፡ ስምምነቱ በጋዛ ሰማይ ላይ የሰላም አየር መንፈስ ለመጀመሩ ማሳያ ነው ቢባልም ታዲያ፣ የማህበረሰብ መሪዎች ግን፣ ህዝቡ ወደቤቱ እንዳይመለስ እየመከሩ ነው ተብሏል፡፡ ጋዛ አሁንም ገና ከስጋት አልወጣችም የሚል አመለካከትም በብዙዎች ዘንድ ይንጸባረቃል፡፡

የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን፤ አገሬን ብላክቤሪ በተባለው ዘመናዊ ስማርት ፎን የሞባይል ቀፎዬ ብቻ በወጉ ማስተዳደር እችላለሁ ማለታቸውን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡ ዴቪድ ካሜሩን ባሉበት ቦታ ሆነው አገሪቱን የማስተዳደር ስራቸውን በሞባይላቸው አማካይነት በአግባቡ ማከናወን እንደሚችሉ መናገራቸውን የገለጸው ዘገባው፤ በየትኛውም የአለም ጫፍ ላይ ብሆን ብላክቤሪ ሞባይሌን ከእጄ ስለማላወጣት፣ በእሷ አማካይነት ከአስተዳደር ጋር በተያያዘ መስራት የሚገባኝን ነገር ሁሉ ሳላጓድል ማከናወን አያቅተኝም ማለታቸውን አስረድቷል፡፡ ብላክቤሪ ስማርት ፎን መረጃን በማስተላለፍ ረገድ ደህንነቱ የተረጋገጠ ነው ተብሎ ስለሚታሰብ፣ የሞባይል ቀፎው የዴቪድ ካሜሩን ቀዳሚ ምርጫ መሆኑን የጠቆመው ዘ ጋርዲያን፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የብላክቤሪ የረጅም ጊዜ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጽዋል፡፡ “ካለፉት ጥቂት አመታት አንስቼ፣ የበአል ቀናትን በመሳሰሉ ስራ ላይ በማልገኝባቸው ጊዜያት አገር የማስተዳደር ስራዬን ሳከናውን የቆየሁት በዚህች ዘመናዊ ብላክቤሪ የሞባይል ቀፎዬ ነው” በማለት በግልጽ ተናግረዋል ብሏል ዘገባው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሁለት አመታት በፊት በአፕል አይፓዶች ላይ በሚጫኑ አፕሊኬሽኖች በመጠቀም የአገሪቱን የኢኮኖሚ መረጃ ለማወቅ ሙከራ ማድረጋቸውንና በዚህም፣ አጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት፣ የባንኮችን የብድር አሰጣጥ አሰራር፣ የስራ ዕድሎችን፣ የንብረት ዋጋ ተመኖችን፣ የምርጫ ውጤቶችን የመሳሰሉ መረጃዎችን በፍጥነት ማግኘት እንደቻሉ፤ ከዚያ ጊዜ ጀምሮም ቴክኖሎጂ ያለውን እገዛ ማጤናቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡

“አትሌት የሆንኩት ባለማወቅ ካዳበርኩት አቅም ነው” አትሌት ወርቁ ቢቂላ ወርቁ ቢቂላ በጣም ታዋቂና አይረሴ የሚያሰኙ በርካታ የአትሌቲክስ ገጠመኞች ያሉት ታዋቂ አትሌት ነው፡፡ በኢትዮጵያ የዘመን ቀመር ከ1976 ጀምሮ እስከ ፈረንጆቹ 2002 ድረስ በተለያዩ ዓለም አቀፍ የውድድር መድረኮች የአገሩን ባንዲራ በድል አውለብልቧል፡፡ ከጀግናው አትሌት ሻለቃ ሃይሌ ገ/ስላሴ ጋር በተለያዩ የአለም የሩጫ ትራኮች ላይ ጥሩ የቡድን ስራ በመስራት ለድል በቅተዋል፡፡ በአርሲ ክ/ሀገር ሰሬ ወረዳ አርብ ገበያ የተወለደው አትሌት ወርቁ ቢቂላ፣ የጐልደን ሊግ አሸናፊም ነበር፡፡ በጐልደን ሊግ ካስመዘገበው ስኬት በኋላ አዲዳስ ኩባንያ ጋር የማስታወቂያ ውል በመፈራረም ለሶስት አመታት ማስታወቂያ ሰርቷል፡፡ በግምት 48 ዓመት እንደሆነው የሚናገረው አትሌት ወርቁ በአሁኑ ሰዓት በዱከም ከተማ ትልቅ ሆቴልና ትልቅ የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ት/ቤት ከፍቶ ኢንቨስትመንት ላይ ተሰማርቷል፡፡

ለህንፃ ግንባታ በዝግጅት ላይ እንደሆነም ተናግሯል፡፡ ከሩጫ አጀማመሩ፣ ከስኬቶቹ፣ ከቢዝነስ ስራውና ከግል ህይወቱ ጋር በተገናኘ ዱከም በሚገኘው ሆቴሉ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ጋር ቆይታ አድርጓል፡፡ እስኪ ስለአስተዳደግህ አጫውተኝ… እኔ እንግዲህ ገጠር ነው የተወለድኩት፤ የአርሶ አደር ልጅ ነኝ፡፡ እንደማንኛውም የገጠር ልጅ በእርሻ በከብት ጥበቃ ቤተሰቤን እያገለገልኩ፣ ከዚያው ጎን ለጎን ትምህርት እየተማርኩ ነው ያደግሁት፡፡ ያው ገጠር ውስጥ ስትኖሪ በግብርና ህይወት ውስጥ ብዙ ውጣ ውረዶች አሉ፡፡ እነዚያን ውጣ ውረዶች በፅናት ማለፌ አሁን ላለሁበት ህይወት መሰረት ጥሎልኛል፡፡ ብዙ ጊዜ ስለአትሌቶች ሲነሳ አርሲ ትጠቀሳለች፡፡ ብዙዎቹ ሩጫ ለመድን የሚሉት የመኖሪያ ቤታቸውና ት/ቤታቸው ሩቅ በመሆኑ እየሮጡ ስለሚሄዱ ነው፡፡ የአንተ ሯጭነት መነሻው ከዚህ ይለያል? በእርግጥ እኔ የተማርኩበት ት/ቤት ከቤቴ ብዙ አይርቅም ነበር፡፡

ግፋ ቢል በእግር የ20 ደቂቃ መንገድ ነው፡፡ እሷን በሩጫ በአምስት ደቂቃ ፉት ነው የምላት፡፡ ከቤቴ ሲደወል ተነስቼ እንኳን ሮጬ እደርሳለሁ፡፡ ትልቁ እኔን ለሯጭነት ያበቃኝ ጉዳይ ከብት እረኝነት ላይ እያለሁ አንድ አመፀኛ ወይፈን ነበረኝ፡፡ ይህ ወይፈን አውድማ ላይ እህል ሲወቃ በጄ ብሎ አይወቃም፡፡ ጥጋበኛ ነው፡፡ ሳሩ ለምለም ነው፤ እንደልቡ ይበላል፡፡ ውቂያ ውስጥ ግባ ስትይው ይፈረጥጣል፡፡ በዚህን ጊዜ ጭራውን ይዤ አብረን እንሮጣለን፡፡ ይገርምሻል እኛ የምንኖርበት አካባቢ ሜዳማ ነው፤ ያንን ሁሉ ሜዳ ጭራውን ይዤ አብሬው እሮጣለሁ፡፡ ለምን አብረኸው ትሮጣለህ? አሃ! ወይፈኑ ሮጦ ሮጦ ሲደክምና ሲያለከልክ ይዤው እመለስና ወደ ውቂያው እከተዋለሁ፡፡ ይሄን በየጊዜው ስለማደርግ ለካ ሳላውቀው አቅም አዳብሬ ኖሯል፡፡ በሌላ በኩል እህል እነግድ ነበር፡፡ እህል ለመሸመት የምንሄድበት ገበያ የአራት ሰዓት መንገድ ሲሆን ስንመለስ አራት ሰዓት በድምሩ በቀን የስምንት ሰዓት መንገድ እጓዛለሁ ማለት ነው፡፡ በዚህ በዚህ የአካል ብቃቴ እየዳበረ መጣ፡፡ ይህ የሆነው ሳላውቀው ነው፡፡ ስራዬ ብለህ ሩጫ የጀመርከው እንዴትና መቼ ነበር? ሩጫ የጀመርኩት ት/ቤት እያለሁ ነው፡፡ በስፖርት ክፍለ ጊዜ እንሮጣለን፡፡ እንዳልኩሽ እኔ ከዚያ በሬ ጋር ስሮጥ፣ ገበያ በቀን ስምንት ሰዓት ስጓዝ፣ ሳላውቀው ሯጭ ሆኛለሁ፡፡ በማወቅና ባለማወቅ ነው ስፖርት የሚሰራው ብሏል ኃይልሻ (ኃይሌ ገ/ሥላሴ ለማለት ነው) ከዚያ በስፖርት ክፍለ ጊዜ ሩጫ ስንወዳደር ማን ይቻለኝ! 1500 ሜትርና 800 ሜትር አንደኛ፣ ከት/ቤቶች ጋር ስወዳደር አንደኛ፤ በአርሲ ክ/ሃገር በ1500 እና 800 ሜትር አንደኛ እየሆንኩ ማንም ሊደርስብኝ አልቻለም፡፡

በዚያን ጊዜ የሙዚቃ ክፍለጊዜም ነበረን፤ ሙዚቃም ስፖርትም ማርክ ነበረው፡፡ ዘፈን በድምፄ ስለማልችል ማርክ ሊያመልጠኝ ሆነ፡፡ ዋሽንት መፈለግ አለብኝ ብዬ ተነሳሁ፡፡ በሸምበቆ እሰራለሁ፤ እበሳለሁ፣ አልተሳካም፡፡ ብዙ ስቃይ አየሁ፡፡ የዋሽንት አሰራሩ ችግር ለካስ የራሴው ነው፡፡ በኋላ አንድ የብረት ዋሽንት በአንድ ብር ገዛሁ፡፡ ድምፅ ማውጣት ጀመረች፡፡ በእሷ ቀስ በቀስ ስለማመድ ዋሽንት መንፋት ቻልኩ፡፡ የሙዚቃ ማርኬን ማግኘት ቻልኩኝ ማለት ነው፡፡ በሁለቱም መስኮች ተሳትፎዬ አደገ፡፡ ያኔ ወረዳችን ስፌ ወረዳ ይባል ነበር፤ አሁን ጦሳ ወረዳ ተብሎ ተቀይሯል፡፡ ያኔ በወረዳችን መጥተው ሲያወዳድሩ አንደኛ እወጣ ጀመር፡፡ ልጁ በሙዚቃውም በስፖርቱም ጠንካራ ነው በማለት ካምፕ አስገቡኝ፡፡ መቼ ነው ይህ የሆነው? በ1976 ዓ.ም አካባቢ ነው፡፡ ካምፕ ከገባን በኋላ መማር፣ መሰልጠን ጀመርን፡፡ እዚያም ማሸነፍ ሆነ ስራዬ፡፡ መጨረሻ ላይ ፍስሃ የሚባል ሰው “ጐበዝ አትሌት ስለሆንክ ኢንስፔክተር ትዕዛዙ ውብሸት ከሚባል አሰልጣኝ ጋር ላስተውዋቅህ” አለኝ፡፡ በትልቅ ደረጃ ላይ የሚገኝ ሰው ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም መሬት ሸልመውታል፡፡ በወቅቱ የወጣቶችና ስፖርት ክፍል ኃላፊ ነበር፡፡ እኔ ደግሞ ፈርቼ እምቢ አልኩኝ፡፡ በኋላ ትዕዛዙ ራሱ ተዋወቀኝና “ምን መሆን ትፈልጋለህ?” ብሎ ጠየቀኝ “እኔ በህይወቴ መሆን የምመኘው ፖሊስ ነው፤ ፖሊሶችን በጣም እወዳለሁ” አልኩት፡፡ ለምን ነበር የምትወዳቸው? ይሄ ጃምቦ የሚመስል ትልቅ ኮፍያቸውን ሲያደርጉ በጣም ደስ ይሉኛል፡፡ እናም በወር 30 ብር ደሞዝ ላግኝ እንጂ ምንም አልፈልግም አልኩኝ፡፡

ለካስ ቤት ኪራይ አለ፣ ምግብ አለ፣ መታመም አለ፤ ያንን 30 ብር ምን ላደርገው ነበር እያልኩ አሁን ሳስብ ያስቀኛል፡፡ በቃ ትዕዛዙ “በቃ በርታ፤ ስፖርትህን አታቋርጥ፤ በደንብ ስራ” አለኝ፡፡ ከዚያስ? ከዚያማ በ1979 የሰራዊቱ የስፖርት በዓል በአዲስ አበባ ይካሄድ ነበር፡፡ ትዕዛዙ ያኔ ተመልምሎ አርሲ ሄዷል፡፡ እኔ ገና ሰሬ ወረዳ ውስጥ ነበርኩኝ፤ እድሜዬም ገና ነበር፤ በዚህ በአገር አቀፍ የስፖርት በዓል ላይ እሱ አርሲን ወክሎ ሄዶ ነበር፡፡ ስድስት ወር ያህል ቀድሞ አዲስ አበባ ገብቷል፡፡ በስፖርቱ ለመሳተፍ ግዳጃቸውን ፈፅመው የተመለሱ አንድ ሺህ ሰራዊት፣ እንደገና ከዚያው አካባቢ የተመለሱ ስድስት መቶ ተሳታፊዎች ነበሩ፡፡ “ከ1600 ሰራዊት የሚበልጥ፣ ከእነሱ ሁሉ አንደኛ የሚወጣ ወርቁ ቢቂላ የሚባል አትሌት አመጣለሁ” አለ፡፡ “እንዲህ የምትለው ከስልጠና ለመሸሽ ነው፤ እሱ ከተሸነፈ አንተ ትባረራለህ” አሉት፡፡ “ግዴላችሁም ልባረር” አለና እኔ ጋ መምጫ ብር አጥቶ፣ ከጓደኞቹ አንድ አንድ ብር ለቃቅሞ በ10 ብር እኔ ጋ መጣ፡፡ ካምፕ መጥቶ “ወርቁን ፈልጉልኝ” አለ፤ ገና እንዳገኘሁት “በል ልብስህን ያዝና ተነሳ” አለኝ፤ “ለምን?” ስለው “ፖሊስ ላደርግህ ነው” አለኝ፡፡ ያኔ ምን እንደተሰማህ ታስታውሳለህ? በደንብ እንጂ! ቀላል አስታውሳለሁ! ማመን አቃተኝ፤ የምይዝ የምጨብጠውን አጣሁ፡፡ ካምፕ ውስጥ መንግስት የሰጠኝን ልብስ በሙሉ ፀጋዬ ለሚባል ጓደኛዬ “ከመጣሁ መጣሁ፣ ካልመጣሁ የት እንደሄደ አላውቅም ብለህ ልብሱን ብቻ አስረክብልኝ” አልኩት፡፡

ተመልሰህ ወደ ካምፕ የመምጣት ሃሳብ ነበረህ እንዴ? አይ… ምናልባት በጤና ምርመራ ወይም ሌሎች መስፈርቶችን ላላሟላና ልመለስ እችላለሁ በሚል ጥርጣሬ ነው፡፡ ከዚያ ወደ አዲስ አበባ መምጫ ብር ከየት ይምጣ! በሌሊት ዶሮ ሲጮህ ተነሳንና እናቴ ቤት ጅማታ ሎዴ ጉዞ ጀመርን፡፡ ምክንያቱም 20 ብር ያስፈልገናል፡፡ መንገዱ አራት ሰዓት ያስኬዳል፤ ገደላገደል አለው፤ አስቸጋሪ መንገድ ነው፡፡ አንዲት ሸራ ጫማ ነበረችኝ፡፡ እሱ ደግሞ መንግስት የሰጠው ቆዳ ጫማ ነበረው፡፡ ያ ፖሊስ ቤት የተሰጠው ጫማ እንዳይቆሽሽና በአስቸጋሪ መንገድ እንዳይቀደድ አወለቀና የእኔን ሸራ ሰጥቼው፣ እኔ በእግሬ ሆኜ ጉዟችንን ቀጠልን፡፡ እሾሁ፣ ድንጋዩ እግሬን እየጋጠኝ፣ አይደረስ የለም ጠዋት አንድ ሰዓት አካባቢ ደረስን፡፡ ብሩን አገኘህ? እህቴ በወቅቱ ቡና ትነግድ ነበር፡፡ ከእሷ ወሰድኩ፡፡ ትንሽ አረፍንና በሁሩታ በኢተያ አድርገን አዲስ አበባ ገባን፡፡ ከዚያ ማሰልጠኛ ገባሁ፤ ጥቂት እንደቆየን ማጣሪያ ውድድር ተባለ፡፡ ኢንስፔክተር ትዕዛዙ እንደነገርኩሽ፣ ቀልጣፋና ተግባቢ በመሆኑ፣ ምልመላ ፖሊሶችም ሆኑ ኃላፊዎቹ ይወዱታል፡፡ ማጣሪያ ሲባል ተጠራጠረኝ፤ ምክንያቱም “እሱ ከተሸነፈ ትባረራለህ” ተብሏል፡፡ ያኔ ፖሊስ ቤት የመግባት እድል ጠባብና ከባድ ነበር፡፡ እኔ ላይ ጥርጣሬ ሲያድርበት ለማጣሪያ የሚወዳደሩትን ጠዋት ከባድ ልምምድ ሰጥቶ አደከማቸው፡፡ ከሰዓት ማጣሪያው ሆነ፡፡ ባለስልጣኑ ሁሉ ወጣ፣ ሰራዊቱ ተደረደረ፣ ሜዳዋ ጠባብ ስለነበረች ለ1500 ሜትር ስምንት ዙር ነው የምትሮጪው፡፡ ሲጀመር ፈትለክ ብዬ ወጣሁና ደርቤ ደርቤ አንደኛ ወጣሁ፡፡ ጭብጨባው ቀለጠ፤ ያኔ ትዕዛዙን “ሼባው” ነው የሚሉት፣ “የሼባው ልጅ አንደኛ” እያሉ ጮሁ፡፡ አሸነፍኩ፡፡ የመጣንበት የትራንስፖርት ታስቦ ተሰጠን፡፡ ደስታ በደስታ ሆንን እልሻለሁ፡፡ አንተ ግን ያን ጊዜ ያሸነፍከው በሙስና ነው ማለት? እንዴት? ምክንያቱም ከሰዓት በኋላ ማጣሪያው እንደሚካሄድ ሲያውቅ ትዕዛዙ ስልጣኑን ተጠቅሞ ተፎካካሪዎችህን በልምምድ ስላደከማቸው ነው ያሸነፍከው (ሳ…ቅ) በእውነት እልሻለሁ፤ በልምምድ ባይደክሙም እምቅ ጉልበት ስለነበረኝ አሸንፋቸው ነበር፡፡ በእርግጠኝነት ነው የምነግርሽ በዚያን ወቅት እንደ ንፋስ ነበር የምበረው፡፡ እሺ ከማጣሪያው በኋላ ምን ሆነ? ከዚያማ ኦሜድላ ስፖርት ገባን፡፡

የጤና ምርመራ አደረግን፡፡ በምርመራው ወቅት ሲያዩኝ “ስፖርተኛ ነህ አይደል?” አሉኝ፤ “አዎ” አልኳቸው፡፡ “በቃ አንተ የሰራዊታችንን ስም ታስጠራለህ፤ ሰራዊታችንን ብቻ ሳይሆን ለአገራችንም ትልቅ ነገር ታደርጋለህ፤ በርታ ውጤት እንጠብቃለን” አሉኝ፡፡ በቃ ፖሊስ ሰራዊት ውስጥ መግባቴን አረጋገጥኩኝ፡፡ በፕሮፌሽናል ደረጃ ለመጀመሪያ ጊዜ የሮጥክበትን መድረክ እስኪ አስታውሰኝ ከዚያ በፊት ልነግርሽ የምፈልገው ትዕዛዙ ቀድሞ ስድስት ወር ስልጠና ገብቶ ስለነበር ስልጠናውን ጨርሶ ወጣ፤ እኛ ገና ስድስት ወር ይቀረናል፡፡ ስለዚሀ አርሲ ሆኖ በመደወል “አትሌት ወርቁ ቢቂላ ጎበዝ እና ጠቃሚ በመሆኑ ወደ አርሲ እንዲዛወርልን” በማለት ጥያቄ አቀረበ፡፡ ወዲያው ስልጠናው እንደተጠናቀቀ ሃላፊው “ወደ አርሲ ይዛወር” ብለው ፈቀዱ፡፡ የዚያኔ የደርግ ዘመን ጦርነት ስለነበረ ወይ ወደ አንዱ ግንባር ዘምቼ ሞቼና ተረስቼ እቀር ነበር፤ አሊያም አካል ጉዳተኛም ሆኜ ልኖር እችል ነበር፡፡ በትዕዛዙ ምክንያት ወደ አርሲ ሄጄ የፖሊስ አትሌት ሆኜ ቀጠልኩኝ፡፡ የትምህርትህስ ጉዳይ? ትምህርት እስከ 8ኛ ነበር የተማርኩት፡፡ አርሲ ፖሊስ ስገባ ትዕዛዙ የማታ ተማር አለኝ፡፡ እኔ ደግሞ “እንዴት አድርጌ እማራለሁ” አልኩት፤ ምክንያቱም ገና ከፖሊስ ስልጠና ስትወጪ ጥበቃ ነው የምትሰሪው፡፡ “ጥበቃ ሰርቼ፣ ሩጫ ሮጬ እንዴት ትምህርት ማታ እማራለሁ” አልኩት፡፡ “ጥበቃውን ከእኔ ጋር አንድ ሽፍት እናደርግና የአንተንም አደር እየጠበቅሁ እረዳሃለሁ፤ አንተ ብቻ ትምህርትህን ቀጥል” አለኝ፡፡ አሰላ ጭላሎ ት/ቤት እስከ 11ኛ ክፍል ትምህርቴን ተከታተልኩኝ፡፡ አግደው ወልዴ የሚባል የጥበቃ ኃላፊ ነበር “አይዞህ አንተን አሳድገን አንድ ነገር ላይ እናደርስሃለን ይለኝ” ነበር፡፡ ብቻ ድጋፋቸው በጣም አበረታታኝ፡፡ ትዕዛዙ ደግሞ አሰላ ቤተሰብ ስለነበረው ወንድሙ ቤት እንድቀመጥ አድርጐ ከምግብ ጀምሮ በእንክብካቤ ያኖረኝ ጀመር፡፡ ሁሉን ነገር ትቼ ሩጫዬ ላይ አተኮርኩኝ፤ ከዚያ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ፕሮጀክት ስለነበረ፤ እዛ ገባሁ፡፡ እዚያ በሶስት ወር ሶስት መቶ ብር ይሰጡናል፡፡

የፖሊስ ደሞዝ ደግሞ 137 ብር ነበረ፡፡ በቃ ሃብታም ሆንን፡፡ ሶስት መቶ ብር ብዙ ነው ያን ጊዜ፡፡ እኔ፤ ሃይሌ ገ/ሥላሴና ሌሎች አትሌቶች ከዚህ ፕሮጀክት ነው የወጣነው፡፡ የፖሊስ አትሌቶችም ሆነን በአየር መንገድም ታቅፈን ነበር፡፡ በዚህ መልኩ ስንሰለጥን ከቆየን በኋላ በ1983 ዓ.ም ኢህአዴግ ገባ፡፡ በወቅቱ ስፖርቱም ሁሉም ብትንትኑ ወጣ፡፡ የለውጡ ሂደት ሲረጋጋ የስፖርቱ ሂደት መቀጠል አለበት ብለው ኢህአዴጎች ስፖርቱን መልሰው አቋቋሙት፡፡ ተበትናችሁ በነበረበት ሰዓት ምን እየሰራህ አሳለፍክ? ይገርምሻል፤ ተበትነንም እኔ ስፖርት መስራቴንና ሩጫ መሮጤን አላቆምኩም፡፡ እናቴም በሶና የተለያዩ ምግቦች እየላከችልኝ፣ ትእዛዙ ውብሸትም እየረዳኝ ልምምዴን ቀጥዬ ነበር፡፡ ከለውጡ በኋላ የመጀመሪያ ፕሮፌሽናል ውድድሬን ያደረግሁት ሃዋሳ ላይ ነበር፡፡ ውድድሩ የ21 ኪ.ሜትር (ግማሽ ማራቶን) ነበረ፡፡ በመሰረቱ የእኔ የሩጫ ዘርፍ አጭር ርቀት ነበር፤ 800፣1500 እና 5000 ሜትር ላይ ነው የምሮጠው፡፡ ሃዋሳ ላይ ስሄድ ትእዛዙ “ታሸንፋላችሁ አይዟችሁ” አለንና ተወዳደርን፡፡ ፊሽካ ተነፋ፡፡ እኔ 21 ኪ.ሜትር ርቀት ተወዳድሬ አላውቅም፤ ግን ሸክሽኬ ሸክሽኬ አፈትልኬ ስወጣ፣ ትዕዛዙ ሳይክል ተከራይቶ ይከተለን ነበር፡፡ በምልክት “አይዞህ” አልኩት፡፡ ይገርምሻል ትዕዛዙ ሰው ሲሞት እንኳን አያለቅስም፡፡ በቁም እያለ መርዳት ያለበትን ይረዳል፣ ያስታምማል፤ ያንን አልፎ ከሞተ “ምንም ማድረግ አይቻልም” ባይ ነው፡፡ “አይዞህ አሸንፋለሁ” የሚለውን ምልክት ስሰጠው አለቀሰ፡፡ አንደኛ ወጥቼ አሸነፍኩኝ፡፡ ከዚያ ፖሊስ ኦሜድላ መግባት አለብህ አለ፡፡ አሰላ ፖሊስ ደግሞ አንለቀውም አሉ፡፡ “ከኦሜድላ ሁለት ወታደር እንሰጣችኋለን፤ ወርቁን ስጡን” አሉ፤ ከዚያ በሁለት ፖሊስ ተቀይሬ ኦሜድላ ገባሁ እልሻለሁ፡፡ የኦሜድላ ፖሊስ ቆይታህ ምን ይመስል ነበር? ኦሜድላ ደግሞ ሃይለኛ ሃይለኛ ልጆች ነበሩ፡፡ ያኔ ሃይልሻ (ኃይሌ ገ/ሥላሴ) ብሄራዊ ቡድን ገብቶ ነበር፡፡

“እባክህ ብቻዬን ሆኛለሁ፤ ቶሎ ወደ ብሄራዊ መጥተህ ተረዳድተን እንስራ” ይለኝ ነበር፡፡ ኦሜድላ እያለሁ ብሄራዊ ቡድን እንድገባ ትዕዛዙ በጎን ጥረት ጀመረ፡፡ እሱ ይጥራል፤ እኔ በውጤት እያሸነፍኩ እደግፈዋለሁ፡፡ ከዚያ ኢትዮጵያ ሻምፒዮን ውድድር ተደረገ፡፡ በአምስት ሺህ አንደኛ ወጣሁ፤ በ10 ሺህ ሁለተኛ ወጣሁ፡፡ 10ሺውን አሸንፌያለሁ ስል አንዱ አንገቱ ብቻ ቀድሞኝ ሁለተኛ አልወጣ መሰለሽ፡፡ ተበሳጭቼ ልሞት! እንደ ኃይሌና ፖልቴርጋት አገባብ ማለት ነው? ትክክል፡፡ እንደዚያ አይነት መሸነፍ ነው የተሸነፍኩት፡፡ ገርባ በትቻ የሚባል የአምቦ ውሃ ልጅ ነው ያሸነፈኝ፡፡ ከዚያ ብሄራዊ ቡድን ገባሁ፤ ይህ እንግዲህ በ1984 ዓ.ም መሆኑ ነው፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ውጭ አገር የተወዳደርከው የት ነው? ውጤትህስ? ቦስተን የዓለም አገር አቋራጭ (Cross Country) ውድድር ላይ ተሳተፍኩና በጣም የሚያስቅ ውጤት አመጣሁ፡፡ 90ኛ ወጣሁ (በጣም እየሳቀ…) በረዶው እስከ ቅልጥምሽ ይደርሳል፡፡ እኔ በእንደዚህ አይነት አየር ላይ ተወዳድሬም እንዲህ አይነት የአየር ንብረት አይቼም አላውቅም፡፡ ሃይልሻም አልቀናውም፡፡ ወደኔው አካባቢ ነው ውጤቱ፡፡ ያኔጥሩ የነበረው ፊጣ ባይሳ ነው፡፡ ደራርቱም ጥሩ ነበረች፡፡ ሃይሌ ገ/ሥላሴ 100 ሺህ ብር እንደ ሸለመህ ሰምቻለሁ፡፡ ለምን ነበር የሸለመህ? በፈረንጆቹ 1994 አካባቢ ይመስለኛል፡፡ ከሃይልሻ ጋር አብረን ሮጠናል፤ ማናጀራችንም አንድ ነበር፡፡ በወቅቱ በነበረው ውድድር ሃይሌ ሪከርድ መስበር አላሰበም፡፡ እኔ አፌ ላይ መጣብኝና “ሃይልሻ አብሬህ ልሂድና ልወዳደር ሪከርድ እንሰብራከን አልኩት፡፡ ውድድሩ ሆላንድ ሄንግሎ ውስጥ ነበር፡፡

“ያንተ ውድድር ጣሊያን ሮም ውስጥ ነው፤ ሄንግሎ ውስጥ ሆቴልም የለህም አልተያዘልህም” አሉኝ፡፡ “እኔ ምንም አልፈልግም፤ ሆቴል ብቻ ያዙልኝ፤ ገንዘብም ምንም አልፈልግም፤ ግን ሪከርድ እንሰብራለን” አልኩት፡፡ ተሳካ ታዲያ? ሃይሌ ያኔ እንዳሁኑ ፈረንጅ አልሆነም፤ እንግሊዝኛ ትንሽ ትንሽ ይችል ነበር፤ ለማናጀሩ ሃሳቤን ነገረው፤ እኛ እንግሊዝኛ “Yes” እና “No” ብቻ ነበር የምንችለው፤ እርግጥ የሚናገሩት ይገባናል፤ መመለስ ላይ ነው ችግሩ (ሳ…ቅ) ሄድን ተወዳደርን፤ አሪፍ የቡድን ስራ ሰራን፤ ሪከርድ ሰበርን፡፡ ውድድሩ የ10 ሺህ ሜትር ነበር፤ ሃይሌ ሪከርድ ሰበረ፡፡ ብር የለም የተባልኩት ሰውዬ ማናጀሩ ተደስቶ 5ሺህ ዶላር ለቀቀብኝ፡፡ መቶ ሺህ ብር ተሰጠኝ ማለት ነው፡፡ የሚገርምሽ በሶስተኛው ቀን ሮም ላይ ውድድር አለኝ አላልኩሽም፡፡ ሮም ላይ እሱ ሆላንድ ሄንግሎ ያስመዘገበው ሪከርድ ተሰበረበት፤ ተናደድኩ፤ አበድኩ በቃ ምን ልበልሽ … ሪከርዱ ስለተሰበረ ነው? አዎ … እኔ ባለሁበት እንዴት ይሰበራል ብዬ ነዋ! እኔ ሶስተኛ ወጣሁ፤ የእኔ ውጤት በእለቱ በአምስት ሺህ ሜትር ከዓለም አራተኛ ሆኖ ተመዘገበ ሃይሌ በሩጫው አልተሳተፈም፡፡ እዚያው ሆላንድ ቀረ፤ ግን በቴሌቪዥን ውድድሩን ይመለከት ነበር፡፡ በጣም ተደሰተ፤ ሆላንድ ስገባ “ዝነኛ ሆንክ ኮንግራ” አለኝ፡፡ “በቃ ሌላ ጊዜ ሪከርዱን እንሰብራለን” አለኝ “እሺ እንሰብራለን” ተባብለን ወዲያው ስዊዘርላንድ ዙሪክ ላይ ሪከርድ ሰበርን፡፡ ተዓምር ሰራን፡፡ ከዚህ ሁሉ ድል በኋላ ነው ሃይልሽ 100ሺህ ብር የሰጠኝ፡፡ ጎልደን ሊግ ላይም ተወዳድረሃል ሲባል ሰምቻለሁ … በዚሁ በ1994 ዓ.ም ለአትላንታ ኦሎምፒክ ሚኒማ ለማምጣት ልሞክር ብዬ ነበር የገባሁት፡፡ እኔ፤ ዳንኤል ከመን፤ ፖልቱርጋርና ሌሎችም ነበሩ፡፡ እነዚህ ሰዎች ትልቅ ደረጃ ላይ ያሉ ሯጮች ናቸው፤ በ10ሺህ ሜትር ነው፡፡

እኔ ለሚኒማ ነው የሮጥኩት፡፡ ሩጫው ተጀመረ፤ እጅብ ብለን እንሮጣለን፤ የሚመራውን እግር እግር ስከተል ስምንት መቶ ሜትር ላይ ስደርስ ተለይቼው ወጣሁ፡፡ ጎልደን ሊግ ትልቅ ውድድር ነው፤ ወርቅ ከሚያስገኙ ሰባት ውድድሮች አንዱ ጀርመን ስቱትጋርት ውስጥ አንዱን ማርቼሊስ ከሃይሌ ጋር የበላው እስማኤል ኩሪ የተባለ ሯጭም አለ፡፡ ዳንኤል ኮመንን ደረብኩት እና በዚህ ጎልደን ሊግ አንደኛ ወጣሁ፤ ጩኽት ቀጠለ… ምን ልበልሽ… በዚህ ውድድር አሸናፊነትህ የተነሳ በጥሩ ብር ከአዲዳስ ኩባንያም ጋር ለማስታወቂያ መፈራረምህን ሰምቻለሁ እውነት ነው? እውነት ነው፤ ከውድድሩም ከማናጀሬም ጥሩ ገንዘብ አግኝቼያለሁ፡፡ በተጨማሪም ከአዲዳስ ኩባንያ ጋር ለሶስት ዓመት ማስታወቂያ ተፈራርሜ ነበር፡፡ ጫማ ብትይ ልብስ እስካሁን የምለብሰው የአዲዳስን ምርቶች ነው፡፡ ምን ያህል ዶላር ነበር በዓመት የተፈራረምከው? እነሱ ምን ያህል እንክፈልህ አሉኝ፤ 25 ሺህ ዶላር በዓመት አልኳቸው፤ የኩባንያው ኃላፊ “Is it enough?” አለኝ “Yes it is enough” አልኩት በኋላ “It is no not enough” አለኝ “so how much” አልኩት “60 ሺህ ዶላር እንከፍላለን” አለኝ፡፡ “በሶስት ዓመት 180 ሺህ ዶላር ታገኛለህ፤ በዚህ ተስማምተህ ፈርም” አሉኝ፤ ፈረምኩ፡፡

ፈረንጅ አሪፍ ነው፤ ሌላው ቢሆን እኛ ምን አገባን ብለው በ25 ሺህ ያስፈርሙኝ ነበር፡፡ የሩጫ ጫማህን የሰቀልከው መቼ ነው? ማራቶን ፓሪስ ላይ ከሮጥኩ በኋላ 8ኛ ወጣሁ፡፡ በእርግጥ የመጀመሪዬ እንደመሆኑ በዚያው መቀጠል ነበረብኝ ግን ብዙ ዓመት ስለሮጥኩ ከአገር ቤት ጀምሮ ቆይ ትንሽ ልረፍ አልኩኝ፡፡ በቃ በዛው አቆምኩኝ፤ ወቅቱ በፈረንጅ 2002 ዓ.ም አካባቢ ይመስለኛል፡፡ ብዙ አትሌቶች እና ታዋቂ ሰዎች ስኬት ላይ ሲደርሱ ህንፃም ሆቴልም የሚሰሩት በትውልድ አካባቢያቸው ነው፡፡ አንተ ሆቴል የከፈትከው ዱከም ከተማ ነው እንዴት ነው? አንድ ጓደኛ አለኝ ብርሃኔ ሚደቅሳ ይባላል፤ የሆለታ ልጅ ነው፤ ብዙ ነገሮችን የሚያማክረኝ እሱ ነበር፤ ከውድድር ስመለስ ላዝናናህ አየር ቀይር ብሎኝ ዱከም ይዞኝ መጣ፡፡ ድሮም አካባቢውን እወደው ነበር፡፡ ነገር ግን እኔ ሃሳቤ አዲስ አበባ ውስጥ ክትፎ ቤት ለመክፈት ነበር፡፡ ብርሃኑ ያልኩሽ ጓደኛዬ ለምን እዚህ (ዱከም) ሆቴል አትከፍትም አለኝ፡፡ በል ቶሎ ደላላ ፈልግና ቦታ ይፈለግ አልኩት፤ መጀመሪያ ቤት ሂድና ከባለቤትህ ጋር ተማከር አለኝ፤ ግዴለም አሳውቃታለሁ ትስማማለች አልኩት፡፡ በኋላ አሁን ሆቴሉ ያረፈበትን ቦታ ገዛሁ፡፡ ለካ ያኔ በነፃ ሁሉ ማግኘት እችል ነበር፤ ቦታ እየገዛሁ እየገዛሁ አስፋፋሁ እስኪ ስለቤተሰብህ ንገረኝ? ጥሩ ትዳርና ቤተሰብ አለኝ፡፡ አራት ልጆች አሉኝ፡፡ የመጀመሪያው ልጄ የ17 ዓመት ልጅና የ10ኛ ክፍል ተማሪ ነው፡፡ አንደኛው ወደ ስምንት አልፏል፤ ሴትም ልጅ አለችኝ፤ የመጨረሻው ህፃን የሁለት ዓመት ነው፤ ልጆቼ ጥሩና ጨዋ ናቸው፡፡

አሁን ጤናህ እንዴት ነው? ጤናዬ ጥሩ ነው፤ ደስተኛ ሆኜ ነው የምኖረው፡፡ ለስፖርት ፍቅር ላላቸው የአቅሜን እደጉማለሁ፡፡ መርዳት ያለብኝን እረዳለሁ፡፡ ቢዝነስ ላይ ነኝ፤ በጣም በጥሩ ሁኔታ ነው የምኖረው፡፡ የእሬቻ በዓል ከደብረዘይት ቀጥሎ አንተ ሆቴል ውስጥ በድምቀት ይከበራል ይባላል፡፡ እውነት ነው? የእሬቻ በዓል ጊዜ መጥተሸ ብታይ ጉድ ነው የምትይው፡፡ አካባቢው በሰው ይሞላል፤ የሙዚቃ ባንድ አለ፤ የከተማው ሰው ይመጣል፤ የአገር ሽማግሌዎች፣ የገዳ ስርዓት መሪዎች ሳይቀሩ ይታደማሉ፡፡ በልዩ ድምቀት ይከበራል፡፡ በቀጣይም የመስቀል በዓል በዋለ በቀጣዩ እሁድ ይካሄዳል፤ በጣም አስደሳች በዓል ነው፡፡ አባ ገዳ ሆነህ ልትሾም ነው ሲባል ሰምቻለሁ ሰምተሽ ይሆናል፡፡ እሱን ከአካባቢው የአገር ሽማግሌዎችና ከስርዓቱ መሪዎች ብትጠይቂ ይሻላል፡፡ አሁን እሱን ለመናገር ጊዜው አይደለም፤ የሚሆነውን አብረን እናየዋለን፡፡ በተረፈ በሁሉ ነገር ደግፎ አይዞህ ብሎ መንገዱን ምቹና ቀና ላደረገልኝ ኢንስፔክተር ትዕዛዙ ውብሸት ታላቅ አክብሮትና ፍቅር አለኝ፤ ዘመኑ ይባረክ እላለሁ፡፡ ሻለቃ ሃይሌ ገ/ሥላሴንም አመሰግናለሁ፤ ሃይልሻ ጠንካራና ምሳሌ የሚሆን ሰው ነው፡፡ በተረፈ ለሁላችንም እድሜና ጤና ይስጠን፡፡ አገራችንን ከክፉ ይጠብቅልን እላለሁ፤ አመሰግናለሁ፡፡

          ለአመታት ያላቋረጠው የአገራችን የፖለቲካ ድራማ፣ ዛሬም ከአዙሪት የመላቀቅ ምልክት አይታይበትም። ሰሞኑን በስፋት የተሰራጩ ሁለት ወሬዎችን ብቻ እንመልከት። አንደኛው ወሬ፣ በኢህአዴግ ባለስልጣናት ላይ ያተኮረ ነው። ሌላኛው ደግሞ በግል ጋዜጦችና መፅሔቶች ላይ ያነጣጠረ።
በእርግጥ ወሬዎቹ እንደ ትኩስ “ዜና” ቢሰራጩም፣ አዲስ “መረጃ” አይደሉም። ከነጭራሹ የመረጃ ሽራፊ እንኳ የላቸውም። “የግል ጋዜጦችና መፅሔቶች፣ ከተለያዩ የውጭ ሃይሎች ወይም ከተቃዋሚ ፓርቲዎች የገንዘብ ድጋፍ ያገኛሉ” እየተባለ በመንግስት ሚዲያ ሲነገር ሰምታችሁ አታውቁም? በተደጋጋሚ ተወርቷል። ከሰሞኑም እንደገና ተከልሶ እንደ አዲስ ሲወራ ሰንብቷል። ግን፣ የትኛው ጋዜጣና መፅሔት መቼ፣ ምን ያህል ገንዘብ ከማን እንደተቀበለ በግልፅ አይልተጠቀሰም። ተጠቅሶም አያውቅም። ተጨባጭና ግልፅ መረጃ ይቅርና፣ ጠቋሚ መረጃ እንኳ ለማቅረብ አልተሞከረም። ጭፍን ውንጀላ ብቻ!
ሁሉም የግል ጋዜጦችና መፅሔቶች ከነውር ንፁህ ናቸው ማለቴ አይደለም። አንዳንዶቹ ንፁህ ላይሆኑ ይችላሉ። ነገር ግን፣ “ነውር ይፈፅማሉ፣ የተቃዋሚ ፓርቲ ልሳን ናቸው” በማለት ያለ አንዳች መረጃ በተደጋጋሚ ወሬ ማሰራጨት ግን፣ ከተራ የስም ማጥፋት ወይም የስም ማጉደፍ ዘመቻ አይለይም። ታዲያ ለምን የመንግስት ሚዲያና የኢህአዴግ ደጋፊዎች ይህን መረጃ አልባ ወሬ ያሰራጫሉ? ያው... ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ለማሳጣትና ለማብጠልጠል፣ እንዲሁም ዜጎችንና ጋዜጠኞችን ለማስፈራራት እስካገለገለ ድረስ፣ የሃሰት ወሬ ማሰራጨት ችግር የለውም - ለጭፍን የገዢ ፓርቲ ደጋፊዎች።
ሁለተኛው ወሬም እንዲሁ ያለ ምንም ተጨባጭ መረጃ ነው የተሰራጨው - በጭፍን ተቃዋሚዎች። “በርካታ የኢህአዴግ መሪዎችና ባለስልጣናት በአለማቀፍ የወንጀል ፍርድ ቤት (አይሲሲ) ተከሰሱ” የሚለው ወሬ እንደካሁን በፊቱ ባለፉት ቀናትም በብዛት ተሰራጭቷል። ወሬው ሲሰራጭ፣ “እስቲ በፍርድ ቤቱ (በአይሲሲ) ድረገፅ ላይ መረጃ ካለ ለማየት እንሞክር” የሚል ሰው አልተገኘም።
በፍርድ ቤቱ አሰራር፣ ከክስ በፊት መደበኛ ምርመራ ይካሄዳል። ከመደበኛ ምርመራ በፊት ደግሞ መነሻ ፍተሻ አለ። በተለያዩ አገራት፣ በርካታ መንግስታትና ባለስልጣናትን እንዲሁም ታጣቂ ድርጅቶችንና እንደ ኢራቅ አሸባሪዎች የመሳሰሉ ቡድኖችን በተመለከተ ምርመራና ፍተሻ እያካሄደ እንደሆነ አይሲስ በድረ ገፁ ይዘረዝራል። ግን፣ በአገራቱ ዝርዝር ውስጥ የኢትዮጵያ ስም አልተጠቀሰም። እና ለምን፣ ወሬው ያለ መረጃ ተሰራጨ? ያው... ገዢውን ፓርቲ ለማጥላላት፣ ለማንቋሸሽ እስካገለገለ ድረስ ችግር የለውም።
በየጎራው የተቧደኑት ጭፍን ፊታውራሪዎችና ቲፎዞዎች፤ በየፊናቸው የሚያሰራጩት የወሬ አይነት ይለያያል። ነገር ግን፣ በባሕሪያቸው በጣም ተመሳሳይ ናቸው። “ተቀናቃኝ ወገንን ለመወንጀል የሚያገለግል እስከሆነ ድረስ፤ ተጨባጭ መረጃ ሳያስፈልግ ማንኛውንም ወሬ ማሰራጨት ይቻላል” በሚለው ሃሳብ ይስማማሉ። ዛሬ የሚያሰራጩት ወሬ፣ ውሎ አድሮ ሃሰት እንደሆነ ቢታወቅ እንኳ፣ ያን ያህልም አያሳስባቸውም። “የሃሰት ወሬ የተሰራጨው ለበጎ አላማ ስለሆነ አያስነውርም” ብለው ያስባሉ። ምን አይነት በጎ አላማ? “ለአገር እድገትና ልማት፣ የአገርን ክብር ለመጠበቅና የአገርን ገፅታ ለማሳመር፣ የድሃውና የሰፊውን ሕዝብ ጥቅም ለማስከበር” ሲባል ነው ወሬው የተሰራጨው በማለት ማመካኛ ያቀርባሉ። “ለብሔር ብሔረሰብና ለባህል በመቆርቆር፣ ለሃይማኖት ቀናኢነትን ለማሳየትና የአምላክን ትዕዛዝ ለማስፈፀም በማሰብ ነው ወሬው የተሰራጨው” በማለትም ራሳቸውን ያሳምናሉ።

በነሱ ቤት፣ ለበጎ አላማ የሃሰት ወሬ ማሰራጨት መደበኛ የሕይወት ዘይቤ ነው።
በአሳዛኙ ነገር ምን መሰላችሁ? የበጎ ነገሮች ሁሉ ምንጭ የሆነውን ነገር እየናዱት ነው - ማለትም እውነትን ዋጋ እያሳጡ የእውነትን ክብር እያረከሱ ናቸው። በፖለቲካ ጉዳይ ውስጥ ስለ “እውነት” መነጋገር፣ ከንቱ “ቲዎሪ” ሊመስል ይችላል። ስለሚመስልም ነው፣ ከአመት አመት እየተደናበርን ከአዙሪት መውጣት ያቃተን። ዋናውን ቁልፍ ችላ ብለን ከተውነው፣ እንዴት ብለን መንገዳችንና መድረሻችን እናውቃለን። ለ“እውነት” ታላቅ ክብር የማይሰጥ ባህል ውስጥ፣ መቼም ቢሆን በጎ ለውጥ ሊፈጠር አይችልም። ለእውነት ክብር ከሌለን እንዴት ልንግባባ እንችላለን? ተቀናቃኛችን፣ የቱንም ያህል አስተማማኝ መረጃ ቢያቀርብ፣ ከመጤፍ አንቆጥረውም። በተቃራኒው፣ ምንም መረጃ ሳይኖረን ተቀናቃኛችንን የሚያሳጣ ወሬ እናወራለን - በዙሪያችን የተሰባሰቡ ቲፎዞዎች በጭፍን እንደሚያጨበጭቡልንና ወሬውን እንደሚያራግቡልን እርግጠኛ ነን። ለነገሩ፣ ትክክለኛ መረጃ ሰብስበን ብናቀርብን፣ ተቀናቃኛችንና ቲፎዞዎች፣ ለሴኮንድ ያህል የመስማት ፈቃደኛ አይሆኑም። አልቧልታ እየነዙና እየተቀባበሉ ያስተጋባሉ እንጂ።

“መውጪያ የሌለው አዙሪት” ይሉሃል ይሄ ነው። ታዲያ ይሄ በጎ ነው? በየጎራችን “ለበጎ አላማ” በማሰብ የምናሰራጨው አሉባልታ፣ እንደምታዩት የመጨረሻ ግቡ “ፋታ የለሽ መናቆር” እንደሆነ ተመልከቱ።
ለዚህም ነው፤ በአገራችንም ስለ ኢትዮጵያና ስለ ኢትዮጵያውያን ቀን ከሌት እያወራን መወዛገባችን፣ ክረምት ከበጋ እየተናቆርን መጠማመዳችን፣ መሻኮታችንና መጠላለፋችን ሊያስገርመን የማይገባው። በእርግጥ፣ አብዛኞቹ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች ስለ ኢትዮጵያ እየተናገሩ የሚወዛገቡትና የሚናቆሩት ለምን እንደሆነ ብትጠይቋቸው፣ መልሳቸው ተመሳሳይ ነው። በየጎራቸው ለአገሪቱ በጎ ለውጥ ለማምጣት እየተጣጣሩ እንደሆነ ይነግሯችኋል። አብዛኞቹ ምሁራንና ዜጎች ስለ አገራቸው እየፃፉ የሚከራከሩት ወይም የሚሰዳደቡትስ? በየፊናቸው “በቀና መንፈስ መልካም ለውጥን ስለምንመኝ ነው” ይሏችኋል። ምን ዋጋ አለው? ለእውነት ክብር ባለመስጠት፣ የ“በጎ” ነገሮች ጠላት ሆነን እናርፈዋለን።
በፖለቲካ ጉዳዮች ውስጥ መጠቀስ ከሚገባቸው በጎ አላማዎች መካከል አንዱ፣ “ነፃነት” የሚባለው ነገር ነው - በራስህ አእምሮ የመጠቀም፣ የራስህን ኑሮ የመምራት፣ የራስህን ሕይወት የማጣጣም ነፃነት። በጥንታዊው የግሪክና የሮም የስልጣኔ ዘመናት፤ እንዲሁም በሬነሰንስ እና በኢንላይትመንት ዘመናት፣ የፖለቲካ ነፃነትና ብልፅግና ከሳይንስና ከእውቀት ጋር በጣምራ የተስፋፉት አለምክንያት አይደለም - እነዚህ ሁሉ የሚመነጩት “እውነት”ን ከማክበር ነው። የነፃነት ተቃራኒ ምንድነው ቢባል፣ በቅድሚያ የሚጠቀሱት፣ አፈናና ጭፍን ፕሮፓጋንዳ ናቸው። አሃ፣ ከመነሻው አፈናና ጭፍንነት የሚስፋፋው ለምን ሆነና? ሰዎች፣ “እውነት”ን እንዳያውቁ ወይም “ሃሰትን” እንዲቀበሉ ማድረግ ነው። በሌላ አነጋገር፣ ለእውነት ከፍተኛ ክብር የሌለው ሰውም ሆነ ፖለቲከኛ፣ ገዢም ፓርቲ ሆነ ተቃዋሚ፣ ለነፃነትም ትልቅ ክብር ሊኖረው አይችልም። እንዲያውም፤ የአቅሙን ያህል አፈናንና ጭፍንነትን የማስፈን ዝንባሌ ይኖረዋል። የትኛውም ወገን ቢያሸንፍ ለውጥ የለውም። ለምሳሌ፣ የሙስሊም ወንድማማቾችና ሆስኒ ሙባረክ፣ የሶሪያ አክራሪዎች እና በሽር አልአሳድ፣ ... የሚጣሉት አንዱ አምባገነን አፋኝ ሌላኛው የነፃነት ታጋይ ስለሆነ አይደለም። የሰዎችን ሃሳብና ንግግር ሙሉ ለሙሉ ለመቆጣጠር፣ ማለትም ተቀናቃኝ የሌለው አፋኝ ለመሆን ነው። ጉልበት ያለውና ስልጣን የያዘ አፋኝ ፓርቲ፣ ግድያ፣ እስር፣ ወከባ፣ ፕሮፓጋንዳ ይፈፅማል። ለጊዜው ስልጣን ያልያዘና ጉልበት የሌለው ፓርቲ ደግሞ ቢያንስ ቢያንስ በአልቧልታ የማሸማቀቅ፣ ስም የማጥፋት፣ በጭፍን የመፈረጅ ዘመቻ ያካሂዳል። ማለቂያ የለሹ አዙሪት የዚህ ውጤት ነው።    
በአገራችን ኢህአዴግና ተቃዋሚዎች በሁለት ጎራ ስለ ኢኮኖሚ እድገትና ስለ ድህነት የሚያካሂዱትን ውዝግብ በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል።  “የኢትዮጵያ ዋነኛ መገለጫ... የሞት አፋፍ ላይ መሆኗ ነው” በማለት ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ የተናገሩ ጊዜ የተፈጠረውን ውዝግብ ታስታውሱ ይሆናል። ኢትዮጵያ በድህነት ተዳክማ በልመና የምትንገታገትና የሕልውና አደጋ የተጋረጠባት መሆኗን ጠቅሰው፤ “እርዳታ ባይገኝ ስንት ሚሊዮን ሕዝብ ያልቃል? እርዳታ እንደልብ ቢገኝ እንኳ፣ ረሃብተኛው እጅግ ብዙ ሲሆን እርዳታ ማጓጓዝ ራሱ ትልቅ ፈተና ይሆናል። ከጥፋት ለመዳን መሮጥ አለብን። መፍጠን አለብን፤ ሴንስ ኦፍ ኧርጀንሲ ያስፈልጋል” የሚል ሃሳብ ነው የተናገሩት ጠ/ሚ መለስ። ይሄ ለብዙ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የሚዋጥላቸው አልነበረም።
የዜጎች ድህነት እጅግ አስከፊ ከመሆኑ የተነሳ አገሪቱ የገደል አፋፍ ላይ መድረሷ እውነት ቢሆንም፤ ብዙዎቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች “እውነት ብለሃል” በማለት ስምምነታቸውን አልገለፁም። “አዎ አገሬው አደጋ ላይ ነው። ግን፣ መልካም ለውጥ ለማምጣት ገዢው ፓርቲ በብቃት አልሰራም። አገሪቱን ለማሳደግ የሃሳብና የተግባር ብቃት የለህም” ብለው መከራከር ይችሉ ነበር። ግን፤ አላደረጉም። እንዲያውም፤ “ምንም አዲስ የተፈጠረ ነገር ሳይኖር መዓት ማውራት ምንድነው? ኢህአዴግ የአገርን ክብር ደፈረ፤ የአገርን ስም አጠፋ...” በማለት ገዢውን ፓርቲ አብጠልጥለውታል።
አሁን ነገሩ የተገላቢጦሽ ሆኗል። በገዢው ፓርቲ ዘንድ፣ ስለ ድህነት ማውራት፣ የአገርን ገፅታ እንደማበላሸት እየተቆጠረ መጥቷል። ተቃዋሚዎች ስለ ድህነት ሲያወሩ... ገዢው ፓርቲ “አዎ ትክክል ነው። አገራችን ድሃ ነች። ባለፉት አስር አመታት ኢኮኖሚው ከእጥፍ በላይ ቢያድግም፤ አሁንም እጅግ ድሃ ነን። ለዚህም ነው በፈጣን የኢኮኖሚ እድገት መቀጠል አለብን የምንለው” ብሎ ማስረዳት ይችላል። ግን አያደርገውም። አገሪቱ እጅጉን የበለፀገች ያስመስላል፤ ስለ ድህነት የሚያወሩትንም “ፀለምተኛ፣ ፅንፈኛ፣ ከሃዲ” በሚል እየፈረጀ ይሳደባል፤ ያስፈራራል።
ተቃዋሚዎችም፤ “አዎ፣ የኢኮኖሚ እድገት እየታየ ነው። ነገር ግን፤ አሁንም ከ13 ሚሊዮን በላይ ተረጂዎች አሉ። በማምረቻ ኢንዱስትሪ መስክ ለውጥ እየታየ አይደለም። በቂ የስራ እድል እየተፈጠረ አይደለም። መንግስት እየገነነና የግል ኢንቨስትመንት ወደ ኋላ እየቀረ ነው። የያዝከው አቅጣጫ አያዛልቅም” ብለው ማስረዳት ይችላሉ። ግን አያደርጉትም። ገዢውን ፓርቲ ለማንቋሸሽ፣ ለመሳደብ፣ በጭፍን ለመፈረጅ ይቸኩላሉ።
እናማ ሁለቱም ጎራዎች፤ ገዢው ፓርም ተቃዋሚ ፓርቲዎችም በጭፍን ስሜታዊነት ይቀጥላሉ - አንዱ ሌላውን ለማሳጣት።
ግን በጋራ የሚጠሉት ደግሞ አለ - ሚዛናዊ የሆኑ ሰዎችን። እርስ በርስ ለመናቆር ችግር የለባቸውም - ቁንፅል እውነትና ያገጠጠ ሰበብ አለላቸው። ኢህአዴግ የኢኮኖሚ እድገት እየተመዘገበ ነው ሲል እውነት ነው - የአሪቱን ድህነት እየሸፋፈነ። ተቃዋሚዎች፣ ስለ ድህነትና ችግር የሚናገሩት ነገር እውነት ነው - ስለ ኢኮኖሚ እድገት እየዘነጉ። “እንዴት የህዝቡን ድህነት ትክዳለህ?”፣ “እንዴት የኢኮኖሚ እድገቱን ትክዳለህ?” እየተባባሉ ይናቆራሉ።
“ድህነትም አለ፤ የኢኮኖሚ እድገትም አለ” ብሎ እውነት የሚናገር ሲመጣ ለሁለቱም አይጥማቸውም። ኢህአዴግ የመንግስት ስልጣን ስለያዘ፤ ማስፈራራት፣ ማዋከብና ማሰር ይችላል።
 ተቃዋሚዎች ደግሞ፣ ስልጣን እስኪይዙ ድረስ፣ ስም ማጥፋት፣ ማንቋሸሽና መሳደብ ይችላሉ። ጨዋታው በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ፤ የትኛውም ወገን ቢያሸንፍ ብዙም ለውጥ አያመጣም።

በመኩሪያ መሸሻ የተዘጋጀው “ከቤተ መንግስት ደሴ የብላታ    ወ/ማሪያም መዘክር” የሚል መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ።
ማመልከቻና ደብዳቤ በአይነቱ ይገለጥበታል የተባለው መፅሀፉ፤ ብላቴን ጌታ ወ/ማሪያም አየለ ከ1912 ዓ.ም እስከ 1925 ድረስ በቁም እጅ ፅሁፋቸው በማስታወሻነት የከተቡት እንደሆነና ስለማዕድን፣ ስለፀጥታ፣ ስለ አውሮፕላን ግዢ፣ ስለ ጋምቤላ ወሰን፣ ስለ ጣና ባህር ልኬትና ግደባ፣ ስለ ጉምሩክ እቃዎችና መሰል ጉዳዮችን የያዘ መሆኑን አዘጋጁ በመፅሀፉ መግቢያ ላይ ገልጸዋል፡፡ 200 ገጾች ያሉት መፅሀፉ፤ በ35.50 ለሽያጭ ቀርቧል፡፡

በወጣት ገጣምያን የተጠነሰሰው “ግጥምን በጃዝ” ባለፈው ረቡዕ ምሽት የ3ኛ ዓመት ክብረ በዓሉን  በብሄራዊ ቴአትር አዳራሽ በተለያዩ የጥበብ ዝግጅቶች አከበረ፡፡ በክብረ በዓሉ ምሽት ግጥሞች፣ ሙዚቃዊ ተውኔት፣ዲስኩሮችና የእውቅና የሽልማት ስነስርአቶች ተካሂደዋል፡፡
በዋቢ ሸበሌ ሆቴል ተጀምሮ ወደ ራስ ሆቴል የተዛወረው “ግጥምን በጃዝ”፤ በኪነ-ጥበብ አፍቃሪያን ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነትን ያተረፈ ፕሮግራም ነው፡፡ በምሽቱ የጥበብ ዝግጅት ላይ ጸሀፌ ተውኔትና ገጣሚ ጌትነት እንየው፣ ገጣሚ ነቢይ መኮንን፣ አርቲስት ግሩም ዘነበ፣ ገጣሚ አበባው መላኩ፣ ምህረት ደበበ፣ በረከት በላይነህ፣ ምስራቅ ተረፈና ሌሎችም የጥበብ ስራዎቻቸውን ለታዳሚው ያቀረቡ ሲሆን አዳራሹ ገና በጊዜ ጢም ብሎ ሞልቶ ነበር፡፡