Administrator

Administrator

Saturday, 11 October 2014 13:25

የቀጨኔ ልጆች ምን ይላሉ?

       ዛሬም “ቡዳ በልቶት ነው” ከማለት አልተላቀቅንም!

            ከፒያሳ በ2.8 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው ቀጨኔ፤ በአዲስ አበባ ከተማ ከሚገኙ ሰፈሮች ውስጥ አንዱ ነው፡፡ ከሰሜን ሸዋ ተነስተው በአካባቢው የሰፈሩት የቀጨኔ ነዋሪዎች ከእስራኤል እንደመጡ ይነገራል፡፡ የአካባቢው ሰዎች በእጅ ሙያ በተለይ በሸክላ ስራና በሽመና የተሰማሩ በመሆናቸው “ቡዳ” በሚል አሉታዊ ተፅዕኖ የሚያሳድር ስያሜ የሚጠሩ ሲሆን “የቀጨኔ ሰዎች ሌሊት ወደ ጅብ በመቀየር ሰው ይበላሉ” የሚለው አመለካከትም ሙሉ በሙሉ አለመቀየሩን የሰፈሩ ነዋሪዎች በቅሬታ ይገልፃሉ፡፡ የህብረተሰቡ አመለካከት ከቀድሞው እየተሻሻለ መምጣቱን ባይክዱም ችግሮቹ ግን አሁንም እንዳሉ ነው ነዋሪዎች የሚናገሩት፡፡

በቀጨኔ ተወልዶ ያደገው ሰለሞን አስፋው እንደሚለው፤ የአካባቢው ሰዎች በሚደርስባቸው ጫና የተነሳ አብዛኛውን ጊዜ ሰፈራቸው ቀጨኔ እንደሆነ አይናገሩም፡፡ ሲጠየቁ ወይም መናገር የግድ ከሆነባቸው ሾላ ወይም አዲሱ ገበያ ገባ ብሎ በማለት ነው የሚመልሱት፡፡ ሰፈሬ ቀጨኔ ነው ብሎ መናገር ለብዙ ሰው “እኔ ቡዳ ነኝ” እንደማለት ነው የሚቆጠረው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ታክሲ ውስጥ ስለቀጨኔ ሲወሩ የምሰማቸው ነገሮች በጣም ይገርሙኛል፤ ሁሉም የሚያወሩት ራሳቸው በቀጥታ ያጋጠማቸውን ሳይሆን አንዱ ሰው ከሌላ ሰው ሰምቶ የነገራቸውን ነው፡፡ “ሰው በቡዳ ተበልቶ” የሚለው ወሬ መቆሚያ የለውም፡፡ ሁልጊዜ ይወራል፡፡ መቼም ሰው እንደዚህ “በቡዳ እየተበላና እየሞተ” የሟች ቤተሰቦች የሆነ ነገር ማለታቸው አይቀርም ነበር፡፡ ነገሩ ወንጀል ስለሆነም ይፋ ይሆን ነበር ይላል ሰለሞን፡፡

አንድን ህዝብ “ሰው ትበላለህ” ብሎ መናገር ራሱ ትልቅ ወንጀል ነው፡፡ በየቦታው የምትሰሚው ነገር ላይ ክርክር ብታነሺ ውሉ ያልተገኘለት ክር እንደመምዘዝ ስለሚሆን ዝም እላለሁ፡፡ የሚያድጉ ትንንሽ ልጆች በማንነታቸው እንዳያፍሩና ለተፅዕኖ እንዳይበገሩ ግን የተቻለንን ሁሉ እንሰራለን፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሰዎች “ከቀጨኔ” ብለው ሬዲዮ ላይ ጥያቄ ሲመልሱ ወይም ዘፈን ሲመርጡ በጣም ደስ ይለኛል፤ ምክንያቱም ሰፈሩን መጥራት እየተለመደ እንዲመጣ ያደርገዋል፡፡ ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡ ሰለሞንን ጨምሮ ያነጋገርኳቸው ዳዊት ጥላሁንና ሰላማዊት ወንድምአገኘሁ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን እዚያው ሰፈራቸው በሚገኘው “ቀጨኔ ደብረሰላም” ትምህርት ቤት በመማራቸው የተለየ ነገር ሳያዩ ነበር ያደጉት፡፡ ፈተናዎችን መጋፈጥ የጀመሩት ወደ ሁለተኛ ደረጃ አልፈው ሌላ ትምህርት ቤት ሲመደቡ ነው፡፡ ሰላማዊት የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ገጠመኟን እንዲህ ታወጋለች፡- “ኤለመንተሪ የራሳችን ማህበረሰብ የሰራው ትምህርት ቤት ውስጥ ስለተማርን ጓደኝነታችን ከማህበረሰባችን ሰው ጋ ነበር፡፡ እኔ ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መነን ነበር የተመደብኩት፡፡ ክፍል ውስጥ ከአንድ የሰፈሬ ልጅና ከሌላ ሰፈር ልጅ ጋር ነበር የምንቀመጠው፡፡

ከልጅቷ ጋር በጣም ጥሩ ቅርበት ነበረን፡፡ የቀጨኔ ልጆች መሆናችንን ስታውቅ ግን ወዲያው ተቀየረች፣ ከኛ ጋር ምግብ መብላት አቆመች፣ ለሌሎችም ነግራ ሁሉም እንዲያገሉን አደረገች፡፡ እንዲያም ሆኖ እኔ ሰፈሬን ደብቄ አላውቅም፤ መናገር ባለብኝ ቦታ ሁሉ የቀጨኔ ልጅ እንደሆንኩ እናገራለሁ፡፡ ነገር ግን ሌላው ሰው ስለኛ ማህበረሰብ የሚያወራውን ነገር ስትሰሚ በውስጥሽ ጥያቄ ይፈጠራል ትላለች፡፡ የሆነ ጊዜ ላይ እናትና አባቴ ጅብ ሆነው ሲቀየሩ ለማየት ቁጭ ብዬ አድር ነበር፡፡ እኔ ወደ ጅብ የምቀየረው ሳድግ ነው እንዴ ብዬ ራሴንም እጠይቅ ነበር፡፡ እናትና አባቴ ግን ሌሊት ተነስተው ቤተክርስቲያን ሲሄዱ ነበር የማየው፡፡” አንድ ጊዜ አንድ ሰው ማታ ሰክሮና ተፈነካክቶ ጉድጓድ ውስጥ እግሮቹን ጅብ ለኮፍ ለኮፍ አድርጓቸው፣ ጠዋት ላይ በህይወት ይገኝና ሀኪም ቤት ይወሰዳል፡፡ የሀኪም ቤቱ ሰራተኞች “የት ነው የተገኘው?” ብለው ይጠይቃሉ፡፡ ቀጨኔ ጉድጓድ ውስጥ መሆኑ ሲነገራቸው፤ “አይ እዚያማ ሰዎቹ ራሳቸው ጅቦች ናቸው፤ ራሳቸው በልተውት ነው” አሉ ይባላል፡፡ የሚወራው ነገር የሚፈጥረው ጫና እጅግ ከባድ ነው፡፡ ለምሳሌ እኔ የሽመና ሙያ አውቃለሁ፤ ከዚያ አልፎም ዲዛይነር ነኝ፡፡ የሆነ ወቅት ላይ “ዲዛይነር” ብዬ ራሴን ማስተዋወቅ ስጀምር፣ የተወሰኑ ሰዎች ግርግር ፈጥረውብኝ ነበር፡፡ ምክንያቱም እዚያው ጉድጓድ ውስጥ ሆኜ ሽመናውን እንድሰራ እንጂ እንዳድግ አይፈለግም፡፡

ይህን ግርግር የፈጠሩት ሰዎች ደግሞ ሙያውን በትክክል ጠንቅቆ የሚያውቀው ሰው የሰራውን ስራ በማይረባ ዋጋ ገዝተው፣ ደህና ስምና ሱቅ ስላላቸው በውድ ዋጋ የሚሸጡ ናቸው፡፡ በጣም የሚገርመኝ እኛ ሰፈር ጅብ ሞቶ ቢገኝ ሰዎች መጥተው አይኑን፣ ቅንድቡን፣ ጆሮውን… ቆራርጠው ይወስዳሉ፤ ምን ይሰራላችኋል ስትያቸው፤ “የቡዳ መድሃኒት ነው” ይሉሻል፡፡ ሰዎች ወደኛ ሰፈር ሲመጡ እንደ ነጭ ሽንኩርት አይነት ለቡዳ መከላከያ ነው ብለው የሚያምኑበትን ነገር ደብቀው ይይዛሉ፡፡ በሚወራው ወሬ ምክንያትም የቤት ኪራይ ርካሽ ስለሆነ፣ የኛ ማህበረሰብ ያልሆኑ ተከራዮች፤ ልጆቻቸው አንገት ላይ የቡዳ መከላከያ የሚሉትን ነገር ያስራሉ፡፡ የኛን ሸማ ለብሰው፣ በኛ ሸክላ አብስለው በልተው፣ የሚያወሩት ነገር ምን እንደሆነ ሳስበው ግራ ይገባኛል ብላለች - ሰላማዊት፡፡ የከፍተኛ ትምህርቱን ለመማር አዲሱ ገበያ ተመድቦ እንደነበር የሚናገረው ዳዊት፤ ከተለያዩ የከተማዋ ክፍሎች በሚመጡ ተማሪዎች የሚወራው ወሬ የተሳሳተ ስለነበር ከቀጨኔ ነው የመጣሁት አልልም ነበር ብሏል፡፡ “ሰው ወደ እኛ ሰፈር እንደሚመጣ ሲታወቅ እንዳትሄድ ወይም ተጠንቀቅ ይባላል፡፡

በቅርብ ጊዜ የክፍለሀገር ልጅ የሆነች የጓደኛዬ ባለቤት እኛ ጋ መምጣት ፈልጋ፣ ወንድሟ ‹እዚያ ሰፈር ከሄድሽ አበቃልሽ፤ በህይወት አትመለሽም› ብሏት እንደነበር አጫውታናለች፤ ቤታችን አድራ ስትሄድም በሚወራው ነገር ግራ እንደተጋባች ነግራን ነበር ብሏል፡፡ አብዛኛው የቀጨኔ ነዋሪ የተሰማራበትን የእጅ ሙያ ሥራ በተመለከተ ሦስቱም ወጣቶች በሰጡኝ አስተያየት፤ የቀጨኔ ሰዎች የራሳቸውን ምርቶች አደባባይ አውጥተው ለመሸጥ ያለባቸው ጫና ከፍተኛ በመሆኑ የስራቸው ውጤት ተጠቃሚ አይደሉም፡፡ የሥራው ተጠቃሚዎች ለሸማ ስራ ከዋሉት ነገሮች አንዳቸውንም እንኳ የማያውቁ ሌሎች ሰዎች ናቸው፡፡ የቀጨኔ ሰው እዚያው ሰፈሩ አፈር ላይ ሆኖ የሰራውንና በተለያዩ ጫናዎች ምክንያት ራሱ ይዞት የማይወጣውን ምርት ተቀብለው፣ በከተማዋ ባሉ ሱቆች መሸጥ የሚችሉ ናቸው እየተጠቀሙ ያሉት፡፡ ማህበረሰቡ ተፅዕኖውን ሰብሮ ለመውጣት አልቻለም፡፡ በታሪኩም ከቦታ ቦታ ሲሳደድ የመጣ በመሆኑ፣ ፍራቻው እስካሁን ከውስጡ አልወጣም፤ ብለዋል፡፡ በቅርቡ በህብረት ስራ ተደራጅተው እንዲሰሩ በመንግስት ተወስኗል፡፡ በዚህ አጋጣሚ “ራስ አገዝ የሴቶች ድርጅት” ሴቶችን ቀጨኔ እያመጡ የሸክላ አሰራር እንዲሰለጥኑ በማድረጋቸው ምስጋና ይገባቸዋል ይላሉ - ወጣቶቹ፡፡ ዳዊት እንደሚለው፤ “ቡዳ” የሚለው ቃል በጊዜ ሂደት ትርጉሙን እየለወጠ መጣ እንጂ አዋቂ ጠቢብ ማለት ነበር፡፡ በነገራችን ላይ የመጀመሪያው ሸክለኛ፣ የሰውን ልጅ በጭቃ የሰራው እግዚአብሔር ነው፤ እሱንስ ምን ሊሉት ይሆን? ዳዊትና ጓደኞቹ ይጠይቃሉ፡፡

(አንጋቻ ፉር ይጠብጥቲ ቤቶ ጦት ኤያተኩሺ)
ከዕለታት አንድ ቀን አንድን ዲታ የገጠር ሰው አውቶብስ መናኸሪያ አካባቢ ሌቦች አይተው ገንዘቡን ከኪሱ

ሊወስዱ ያንዣብቡበታል፡፡ ሰውዬው በጣም ደክሞታል፡፡ በአቅራቢያው ወደሚገኝ ቤተክርስቲያን ሄዶ ጥቂት

አረፍ ማለት ይሻና ወደዚያው ቤተክርስቲያን ሄዶ ጥቂት አረፍ ማለት ይሻና ወደዚያው ያመራል፡፡
ሌቦቹም ባገኙት አጋጣሚ ብሩን ሊመነትፉት “እንከተለው፣ እንከተለው” ተባብለው ማንዣበባቸውን ይቀጥላሉ፡፡
ሌቦቹ ሰውዬውን ከግራ ከቀኝ ከበው ሲከተሉት ፖሊስ ጠርጥሮ እነሱን እየተከተላቸው ኖሯል፡፡
ሰውዬው ቤተክርስቲያን ገባ፡፡
ሌቦቹም ተከትለውት ገቡ፡፡
ሰውዬው ሳር ላይ ጋደም አለ፡፡ ሌቦቹም ዙሪያውን ተጋደሙ፡፡
አፍታም ሳይቆይ ሰውዬው እንቅልፍ ድብን አድርጎ ወሰደው፡፡
ሌቦቹ በጣም ቀርበው ደረት ኪሱ ያለውን ገንዘብ ለማውጣት ሲሞክሩ ፖሊሶቹ ወደሌቦቹ መጡ፡፡
ከሌቦቹ አንደኛው ፖሊሶች እንደደረሱባቸው በመገንዘብ፣ ከኪሱ ምላጭ አውጥቶ ሰውዬውን መላጨት ጀመረ፡፡
አንደኛው ፖሊስ - “ምንድነው? ምን እያደረጋችሁ ነው?” ሲል ጠየቀ፡፡
አንደኛው ሌባ - “አይ ጓደኛችን ነው፡፡ ደክሞት ጋደም ብሎ ነው፡፡ ፀጉሩ በጣም ስላደገ ላጩኝ ብሎን ነው፡፡

ድንገት እንቅልፍ ወሰደው፡፡”
ፖሊሱም፤
“ደህና፡፡ ቀጥሉ” ብሎ ሄደ፡፡
ሌቦቹ፤
“ስለጥንቃቄህ እናመሰግናለን” አሉት፡፡
ሌቦቹም ከራሱ ላይ ፀጉሩን፣ ከደረት ኪሱ ብሩን፣ ላጭተው ሲያበቁ ተነስተው ይሄዳሉ፡፡
ሰውዬው ከሰዓታት በኋላ ከእንቅልፉ ይነቃል፡፡
የሰላም እንቅልፍ በመተኛቱ፤
“ተመስገን” እያለ ደረቱ ላይ ሲያማትብ፤ ደረት ኪሱ ቅልል አለበት፡፡ እጁን ኪሱ ከቶ ቢያይ ብሩ የለም፡፡
“ወይኔ ብሬ! ብሬን ዘረፉኝ!” እያለ በሁለት እጁ ጭንቅላቱን ይዞ ሊጮህ ሲሞክር የራስ ፀጉሩ የለም፡፡
ይሄኔ ጥቂት አሰብ አድርጎ ፀጉር - አልባ መሆኑን በደንብ ሲገነዘብ፤
“እፎይ! ለካ እኔ አይደለሁም!” ብሎ ተፅናንቶ መንገዱን ቀጠለ፡፡
                                     *       *          *
በቁም ከሚላጩ ሌቦች ይሰውረን!
መቼም ቢሆን መች ማንነታችንን ከሚያስዘነጋ አደጋ ይጠብቀን፡፡ ህልውናችንን ጥያቄ ውስጥ ከሚያስገባ ሁኔታ ያድነን፡፡ የቱንም ያህል ብናንቀላፋ፣ የቱንም ያህል ቸልተኛ ብንሆን፣ የቱንም ያህል ግብዝ ብንሆን፤ “እፎይ! እኔ አይደለሁም!” ከማለት ያውጣን፡፡
በሀገራችን ከተከሰቱ ችግሮች አንዱ “እኔን እስከደገፈ ድረስ አምነዋለሁ” የማለት አባዜ ነው፡፡ ሌብነቱን ያበዛው፣ እምነቱን ያቀጨጨው፣ በቀላሉ ማታለልን ያበረታታው፤ “ከታላላቅ ባለሥልጣናት ጋር የዋለ አጭበርባሪ ሊሆን አይችልም” ብሎ ማለትን እጅግ ያጎለበተው ሰውን የማመን ባህል ነው፡፡ ማመናችንን እንመርምር! ሀገራችን ችግር በገጠማት ቁጥር ከመራወጥና ይይዙት ይጨብጡትን ከማጣት፣ ተገዶም ከመንገድ ከመውጣት አስቀድሞ “ያቀድነው ባይሳካስ፣ ያልጠበቅነው ነገር ቢከሰትስ?” ብሎ ራስን መጠየቅ ትልቅነት ነው፡፡ ማናቸውም ችግር ራስን ለማዘጋጀት ይጠቅማልና ያቀድኩትን በችኮላ እፈፅማለሁ ብሎ መሯሯጥም “ሲሮጡ የታጠቁት ሲሮጡ ይፈታል መሆኑን ቀድሞ ማውጠንጠን ነው፡፡
ባልታዛር ግሬሺያን የተባለ ፈላስፋ፤ እንዲህ ይለናል፡-
“ታላላቅ ችሎታ ያላቸው ሰዎች ቸኩለው እርምጃ ከመውሰድ ይቆጠባሉ፡፡ ምነው መውጣት አንድ ጉዳይ ውስጥ ቸኩሎ እጅን ካስገቡ በኋላ፤ ያ ከመግባት ይልቅ የከበደ ነውና፡፡ አንዳች አዲስ ነገር ሲከሰት ፍርድህን ይፈታተንሃል፡፡ በአሸናፊነት መውጣት ከሚጠይቅህ አቅም ይልቅ፤ ቸኩሎ ከመወሰን መቆጠብ ትንሽ ጉልበት ነው የሚጠይቀው፡፡ አንድ ኃላፊነትና ግዴታ ሌላ ኃላፊነትና ግዴታን እንደሚወልድ አትርሳ፡፡ ያ እየተጫነህ ስትመጣ ወደ መንኮታኮት እጅግ ተቃረብክ ማለት ነው፡፡”ይሄ ለእኛ ትልቅ ተሞክሮ ሊሆነን ይገባል፡፡ በሩቅ ከለየላቸው ጠላቶች ይልቅ በውስጣችን ያሉትን መጠንቀቅም አንዱ መርሀችን ሊሆን ይገባል፡- “ለሰለሰ ብለህ እባብ ትታጠቃለህ ወይ?” የሚለው የትግሪኛ ተረት ይሄንን ጠቅልሎ ያስቀምጥልናል፡፡
በሀገራችን፣ የፖሊተካ፣ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ንፍቀ-ክበብ ውስጥ ብርቱ ቦታ ሊሰጠው የሚገባ ነገር አደብ መግዛትና ሆደ-ሰፊ መሆን ነው፡፡ በቀላሉና በትንሹ ነገር ሁሉ ቱግ ማለት፣ ሲያሸንፉ ከልኩ በላይ ዘራፍ ማለት፣ ሲሸነፉ መድረሻ ማጣትና ዓለም ጨለመች ማለት፤ ለክፉ ይዳርጋል፡፡ “ላናድህ ያለ እሳት ሲጭር እሳት ፍለጋ አትሂድ፡፡ ማገዶውን አርጥብ” እንዲል መፅሐፈ - ተረት፤ በብስለት እንጂ በጉልበት ለውጥ እንደማናመጣ ልብ እንበል፡፡ ዛሬ ላደርገው ያሰብኩትን ነገር በቀጣዩ ዓመት ባደርገውስ? ብሎ ቆም ብሎ ማሰብ “የቸኮለች አፍሳ ለቀመች” ከመባል ያድነናል፡፡ ብዙ በችኮላ የተከናወኑ እንቅስቃሴዎች ሽባ አድርገው ሊያስቀሩን እንደሚችሉ ያስወረዱ አብዮቶች (abortive revolutions) ታሪክ ይነግረናል፡፡ ለማናቸውም፤ ግዴታችን የሆኑትን ነገሮች ለይተን እንደግዴታነታቸው መቀበል፣ ኃላፊነት የሚጠይቁትን ጉዳዮች እንደኃላፊነት አጥብቆ ይዞ መወጣት፣ አሌ የማይባልና ተጠያቂነትን የተሸከመ ተግባር ነው፡፡ ለሀገር ዕድገትና ለህዝብ ጥቅም ሲባል፤ መሪና ተመሪ፣ ገዢና ተገዢ፣ አለቃና ምንዝር፣ ሥልጣን ላይ ያለፓርቲና ተቃዋሚ … ሹመኛና ሿሚ፤… ሁሉም ሁነኛ ኃላፊነትና ግዴታውን ጠንቅቆ ማወቅ አለበት፡፡ ምነው ቢሉ፤ “ድመት አይጥ እነዲይዝ ተብሎ ችቦ አይበራለትምና!” 

               በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ በፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ተጠርቶ የተካሔደው ስብሰባ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን ወቅታዊ ኹኔታ የማይገልጽ፣ መዋቅሩን ያልጠበቀ እና ጽ/ቤታቸው የማያውቀው መኾኑን በመግለጽ ተቃወሙ፡፡ ‹‹የቤተ ክርስቲያንን አስተዳደራዊ አስተሳሰብ ማበልጸግ›› በሚል ርእስ ከትላንት በስቲያ በመንበረ ፓትርያርኩ አዳራሽ የግማሽ ቀን ስብሰባ በተደረገበት ወቅት፣ የፓትርያርክ አቡነ ማትያስን የመግቢያ ንግግር ተከትለው የተናገሩት ዋና ሥራ አስኪያጁ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ÷ ‹‹አኹን ወደ ስብሰባው ስገባ ነው መልእክቱን የሰማኹት፤ አጀንዳውም ከመቅረቡ በፊት ከቋሚ ሲኖዶሱ ወይም ከእኔ ጋራ ምክክር አልተደረገበትም፤›› በማለት ስብሰባው ከመዋቅሩና ከዕውቅናቸው ውጭ የተጠራ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ የፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ባስተላለፈው የቃል ትእዛዝ መጠራቱ በተገለጸው በዚኹ ስብሰባ÷ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የመምሪያዎች ዋናና ምክትል ሓላፊዎች፣ የድርጅቶች ዋናና ምክትል ሥራ አስኪያጆች፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአስተዳደር ሓላፊዎች፣ የዋና ክፍሎችና የክፍሎች ሓላፊዎች፣ የክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ዋናና ምክትል ሥራ አስኪያጆች መሳተፋቸው ተገልጧል፡፡

በ2001 ዓ.ም. በቅ/ሲኖዶስ ውሳኔ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የመልካም አስተዳደር እንቅስቃሴ መጠናከሩን ተከትሎ የቀድሞው ፓትርያርክ መዋቅሩን ሳይከተሉና ከቅ/ሲኖዶሱ ጋራ ሳይመክሩ ወስደዋቸው ነበር ያሏቸውን ርምጃዎች በመቃወም በወቅቱ የአሜሪካ ሊቀ ጳጳስ የነበሩት የአኹኑ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በብዙኃን መገናኛ የሰጡት መግለጫ በማስረጃነት ተይዞ እንደሚገኝ ያስታወሱት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ ‹‹ቅዱስነትዎም በምትካቸው ሲቀመጡ መዋቅሩን ሊጠብቁ ይገባል፤ መዋቅሩን ሳይከተሉና ከሚመለከተው አካል ጋራ ሳይመክሩ የሚሠሩት ሥራ ቤተ ክርስቲያኒቱን አደጋ ላይ የሚጥል ነው፤›› እንዳሏቸው ተመልክቷል፡፡

ዋና ሥራ አስኪያጁ ‹‹ውድቀት እንዳይደረስብዎ አማካሪዎችዎ ሊያዝንልዎ ይገባል፤›› ማለታቸውን የገለጹት የስብሰባው ተሳታፊዎች አያይዘውም ‹‹ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በአማካሪዎቻቸው ምክንያት ከዕድሜያቸው ዐሥር ዓመት አሳጥረዋል፤ እርስዎም በአማካሪዎችዎ የተነሣ ዕድሜዎ እንዳያጥር ያስቡበት፤›› ሲሉ መምከራቸውን ጠቁመዋል፡፡ ውይይቱን በሰብሳቢነት የመሩት ፓትርያርኩ በበኩላቸው፤ በሥራ የሚያግዛቸው ባለማግኘታቸውና ብቻቸውን በመኾናቸው›› ስብሰባውን ወደ ታች ወርደው ለመጥራት እንደተገደዱ አስረድተዋል፡፡ ፓትርያርኩ ባቀረቡት በጽሑፍ የተደገፈ ገለጻ÷ በቤተ ክህነቱ የመልካም አስተዳደር ዕጦቶች እንዳሉ፣ በሙሰኝነት፣ በዘረኝነትና በአድሏዊነት የሚገለጹ የብልሹ አሠራር ሒደቶች እንደሚታዩ ዘርዝረዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ስም የሚደራጁ ማኅበራትና ግለሰቦች፣ ሕግና ደንብ እየጣሱ መዋቅሯን እየተፈታተኗት እንደሆነና ከመዋቅራዊ ቁጥጥር ውጭ የሚንቀሳቀስ ሀብትና ንብረት እያካበቱ በመኾኑ አካሔዳቸው ለአንዲት ቤተ ክርስቲያን ጥንካሬና ህልውና ፍጹም አደጋ እንደኾነ አብራርተዋል፡፡

መልካም አስተዳደርን ከማስፈን አንጻር ኹሉም የሥራ ሓላፊዎች ራሳቸውን በመፈተሽና በማጽዳት ችግሩን በዘላቂነት ለማስወገድ በሚደረግ ጥረት የድርሻቸውን እንዲወጡ ያሳሰቡት ፓትርያርኩ፤ የማኅበራት አካሔድ ሥርዓት መያዝ እንዳለበት ጠቁመው ተገቢ ያልሆነውን አካሄድ ኹሉም ሊቃወመው ይገባል ብለዋል፡፡ ‹‹አማካሪዎቼ ዓላማዬን የሚጋሩና የሚያስፈፅሙልኝ ሰዎች ናቸው፤›› ያሉት አቡነ ማትያስ፤ ‹‹አኹንም የምቀጥልበት መኾኑን አሳውቃለኹ›› ብለዋል፡፡ ‹‹ብቻዬን ነኝ፤ በሥራም አልታገዝኹም›› ለሚለው የፓትርያርኩ ንግግር ‹‹ቅዱስነትዎ አዝዘው ምን ያልተፈጸመ ነገር አለ?›› በሚል ምላሽ የሰጡት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ ‹‹ያልተፈጸመ ነገር ካለ ለጉባኤው በይፋ ይገለጽ›› ሲሉ ጠይቀዋቸዋል፡፡ የመልካም አስተዳደር ችግርና የችግሩ መገለጫዎች በርግጥም እንዳሉ ያልሸሸጉት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ መምሪያዎችና ድርጅቶች የበጀት ዓመቱን ዕቅድ በማውጣት፣ የክንውን ሪፖርት በአስተዳደር ጉባኤ በወቅቱ እንዲያቀርቡ፣ ድክመቶች እንዲስተካከሉና ጠንካራ ጎኖች ታቅበው እንዲቀጥሉ መደረጉን በመግለጽ በፓትርያርኩ ጽሑፍ የቀረቡትን መረጃዎች ወቅታዊነት ሞግተዋል፡፡

በልማት ተግባራትና በሠራተኛ አያያዝ ባለፈው በጀት ዓመት የተፈጸሙ ተግባራትን የዘረዘሩት የጽ/ቤቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም መለሰ በበኩላቸው፤ ቀጣይነት ባላቸውና በጥናት በተደገፉ የመልካም አስተዳደር ማሻሻያዎች የሚቀርቡ ቅሬታዎችና የተጉላሉ ባለጉዳዮች አለመኖራቸውን የገለጹ ሲሆን፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን የፋይናንስ ሥርዐት ዘመናዊው ለማድረግ ዝግጅቱ መጠናቀቁን ጠቁመው የፓትርያርኩን መረጃዎች አግባብነት እንደጠየቁ ታውቋል፡፡ አንድ የስብሰባው ተሳታፊ “አንድ ጣታችንን ወደሌላው ስንጠቁም ሦስቱ ወደኛ እንደሚያመለክት አንዘንጋ” በማለት ፓትርያርኩ ከሙስናና ብልሹ አሠራር ጋር በተያያዘ በዙሪያቸው ስላሉ አማካሪዎችም እንዲያስቡበት ጠቁመዋቸዋል፡፡መንግሥት የሲቪል ማኅበራትን የሚከታተለው ሕግ አውጥቶና ተቋም መሥርቶ መኾኑን፣ በሕጉ የሚተዳደር አብሮ እንደሚጓዝና አልፈልግም ያለ እንደሚወጣ የተናገሩት አቡነ ማቴዎስ፤ ቤተ ክርስቲያን ግን መንፈሳውያን ማኅበራት የሚቋቋሙበት ሕግ እንዳላወጣችና የምታቅፍበት መዋቅር እንዳልዘረጋች ገልጸዋል፡፡

በአገልግሎት ላይ ያሉትን መንፈሳውያን ማኅበራት በሕገ ወጥነትና በመዋቅር ባለመታዘዝ ለመጠየቅ በቅድሚያ ሕጉ ወጥቶ በሥራ ላይ ማዋሉ መቅደም እንዳለበት አስገንዝበዋል፡፡ “ለኢትዮጵያ በረሓ ወርደው፣ ብረት አንሥተው የታገሉትና ዋጋ የከፈሉት ኹሉም ሕዝቦች ናቸው፤ ሕገ መንግሥት ለኹሉም እኩል ነው፤ ለእገሌ ሚኒስትር እናገራለኹ፤ ለእገሌ ደኅንነት እደውላለኹ እያሉ አያስፈራሩን፤›› በማለት ዋና ሥራ አስኪያጁ ፓትርያርኩን እንዳሳሰቧቸው የስብሰባው ተሳታፊዎች ተናግረዋል፡፡ አቡነ ማትያስ ቀደም ሲል ከቋሚ ሲኖዶሱ ጋራ ሳይመክሩ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአድባራትና ገዳማት አለቆች ጋራ ባደረጉት ስብሰባ፤ ሊቃነ ጳጳሳቱን ማዘለፋቸውን የጠቀሱት አቡነ ማቴዎስ በዚኽም ኹሉም አባቶች ቅሬታ እንደተሰማቸውና እንዳዘኑባቸው ተናግረዋል፡፡ ፓትርያርኩ ዓመቱን በሙሉ በየደረጃው እቀጥልበታለኹ ባሉት ስብሰባ÷ አጀንዳዎች መዋቅር ሳይጠብቁ፣ ጥናት ሳይደረግባቸውና ሳይብላሉ ውይይቱ ለሚዲያዎች ክፍት መደረጉ ቤተ ክርስቲያኒቷን ለአጉል ትችት ያጋልጣታል ሲሉ ተሳታፊዎች አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

             የኢትዮጵያ፣ የግብጽና የሱዳን የውሃ ሚኒስትሮችና ባለሙያዎች የሚሳተፉበትና በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ የሚመክረው ሁለተኛው ዙር የሶስትዮሽ የቴክኒክ ውይይት፣ በመጪው ሃሙስና አርብ በካይሮ እንደሚቀጥል የግብጹ አሃራም ድረገጽ ዘገበ፡፡የግብጹን የውሃና የመስኖ ሚኒስትር ሆሳም አልሞሃዚን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በውይይቱ ላይ የሚሳተፉት 12 የአገራቱ ባለሙያዎች፣ ግድቡ በግብጽና በሱዳን ላይ የሚያደርሰውን ማህበራዊ፣ አካባቢያዊና የውሃ ተጽእኖዎች በተመለከተ ተጨማሪ ጥናት የሚያደርግ አለማቀፍ አማካሪ ኩባንያ ይመርጣሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ሚኒስትሩ ከትናንት በስቲያ በሰጡት መግለጫ እንዳሉት፣ ለሁለት ቀናት በሚካሄደው ውይይት ሶስቱ አገራት የግድቡን ተጽዕኖ በተመለከተ ያገኟቸውን አዳዲስ የጥናት ውጤቶች አቅርበው ይወያዩባቸዋል፡፡አገራቱ ባለፈው ነሃሴ በግድቡ ተጽዕኖዎች ዙሪያ የሚሰሩ ተጨማሪ ጥናቶችን በስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ መስማማታቸውንና የመጀመሪያው ዙር የሶስትዮሽ ውይይት ባለፈው መስከረም 10 ቀን በአዲስ አበባ መካሄዱ ያስታወሰው ዘገባው፣ በውይይቱ የተገኘው ውጤትም በአገራቱ መካከል የተጀመረው ድርድር ወደተሻለ ደረጃ እየተሸጋገረ መሆኑን የሚያመላክት እንደሆነም አክሎ ገልጧል፡፡

           ባለፈው ሳምንት በተካሄደው 41ኛው የበርሊን ማራቶን የ31 ዓመቱ ኬንያዊ ዴኒስ ኪሜቶ ርቀቱን ከ2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች በታች በመግባት የመጀመርያው ሰው ተብሎ ተደነቀ፡፡ ማራቶን መሮጥ ከጀመረ ገና የ5 ዓመታት ልምድ ያለው  ዴኒስ ኪሜቶ፤ ያስመዘገበው አዲስ የማራቶን ክብረወሰን 2 ሰዓት ከ02 ደቂቃዎች ከ57 ሴኮንዶች ነው፡፡ በ2013 እኤአ ላይ በሌላው ኬንያዊ ዊልሰን ኪፕሳንግ ተይዞ ከነበረው ሪከርድ ላይ 26 ሰከንዶችን አሻሽሏል፡፡   ከ2 ሰዓት ከ4 ደቂቃዎች በታች በመግባት የመጀመርያው ሰው የነበረው በ2008 እኤአ ላይ ኃይሌ ገብረስላሴ ነበር፡፡
በ41ኛው በርሊን ማራቶን ላይ ዴኒስ ኪሜቶ በሪከርድ ሰዓት ሲያሸንፍ የተሳትፎ እና የስፖንሰር ክፍያዎችን ሳይጨምር እስከ  154ሺ ዶላር ክፍያ ማግኘቱን የዘገበው ዴይሊ ኔሽን ነው፡፡ በውድድሩ አሸናፊነት 40ሺ ዶላር፤ ከ2 ሰዓት 4 ደቂቃዎች በታች ስለገባ የ30ሺ ዶላር ቦነስ እንዲሁም ለሪከርዱ 50ሺ ዶላር ተከፍሎታል፡፡ ከወር በኋላ በሚደረገው የኒውዮርክ ማራቶን ላይ ከሚሳተፈው የቀድሞ ሪኮርድ ባለቤት እና የልምምድ አጋሩ ዊልሰን ኪፕሳንግ ጋር ለማራቶን ሊግ የ500ሺ ዶላር ሽልማትም ይፎካከራል፡፡ ዊልሰን ኪፕሳንግ በኒውዮርክ ማራቶን ካላሸነፈ ኪሜቶ የማራቶን ሊጉን በመሪነት ማጠናቀቁ የማይቀር ይሆናል፡፡ እንደኬንያው ዴይሊ ኔሽን ጋዜጣ ዘገባ በኤልዶሬት ከሰፈር ሰዎች ጋር ውድድሩን ትመለከት የነበረችው ካሮሊን ቼፕኩሪር የተባለች ሚስቱ ሪከርዱን በሰበረበት ወቅት ከደስታ ብዛት ራሷን ስታለች፡፡በማራቶን ስኬቱ ያገኘውን ሃብት በትውልድ አገሩ ትምህርት ቤት በመገንባት እና ወጣት የቤተሰቡ አባላት ከፍተኛ ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ እደግፍበታለሁ ብሏል፡፡ከዴኒስ ኪሜቶ አዲስ የዓለም ማራቶን ሪከርድ በኋላ ርቀቱ ከ2 ሰዓት በታች ይገባል የሚለው አጀንዳም  በይበልጥ ማነጋገር ጀምሯል፡፡ በዚሁ ጉዳይ ላይ አስተያየት የተጠየቀው ዴኒስ ኪሜቶ የራሱን ሪከርድ የማሻሻል አቅም እንዳለው ተናግሮ፤  በሚቀጥለው ውድድር 2 ሰዓት ከ1 ደቂቃ ልገባ እችላለሁ ብሏል፡፡ በበርካታ ጥናቶች በተሰሩ ትንታኔዎች 42.195 ኪሎሜትሮች (26 ማይሎች እና 385 ያርዶች) የሆነውን የማራቶን ርቀት ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት  እስከ 30 ዓመታት ሊፈጅ ይችላል ተብሎ ነበር፡፡ ሰሞኑን ግን ቢያንስ በ10 ቢበዛ በ15 ዓመታት ውስጥ ሊሳካ እንደሚችል በተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ተገልጿል፡፡
ይህን አስደናቂ የስፖርት ውጤት እንደሚያሳኩ ግምት ያገኙት ሁለቱ የምስራቅ አፍሪካ አገራት ኬንያና ኢትዮጵያ ቢሆኑም ግምቱ ወደ ኬንያ አጋድሏል፡፡በተያያዘ በ41ኛው የበርሊን ማራቶን በወንዶች ምድብ ለሶስትኛ ተከታታይ ጊዜ የዓለም ማራቶን ሪከርድ በኬንያ አትሌቶች ሲሰበር በውድድር አይነቱ ከኢትዮጵያውያን ያላቸው ብልጫ በጋሃድ ተረጋግጧል፡፡ በሴቶች ግን ኢትዮጵያውያን እንደሚሻሉ የበርሊን ማራቶን አመልክቷል፡፡ በሴቶች  ያሸነፈችው ትርፌ ፀጋዬ በ2 ሰዓት ከ20 ደቂቃዎች ከ18 ሰከንዶች ሲሆን ፈይሴ ታደሰ በ9 ሰከንዶች ዘግይታ ሁለተኛ ታደለች በቀለ እና አበበች አፈወርቅ አራተኛ እና አምስተኛ ደረጃ በማግኘት የተሻለ ውጤት አስመዝግበዋል፡፡ በራድክሊፍ በለንደን ማራቶን የተመዘገበው ክብረወሰን 10 ዓመት ሆኖታል፡፡ ይህ ሪከርዷ 2 ሰዓት ከ15 ደቂቃዎች ከ25 ሰኮንዶች ነው፡፡
ዴኒስ ኪሜቶ ማነው?
በ14 ዓመቱ ትምህርቱን ያቋረጠው ዴኒስ ኪሜቶ አዘውትሮ አትሌቲክስን በቴሌቭዥን ይመለከት ነበር፡፡ በተለይ በ10ሺ ሜትር ኃይሌ ገብረስላሴና ፖል ቴርጋት በሲድኒ ኦሎምፒክ የነበራቸው ትንቅንቅ ወደ ስፖርቱ በደንብ አተኩሮ ለመግባት ምክንያት ሆኖታል፡፡ ከዚያ በፊት ግን ገበሬ እና እረኛ ነበር፡፡በግብርናው  ድንች እና በቆሎ እያመረተ የሚተዳደር ሰው ነበር፡፡ ከአምስት አመት በፊት አንድ የቺካጎ ትሪቡን ጋዜጠኛ ወደ ማራቶን እንዲገባ ከመከረው በኋላ ግን ግብርናውን ትቶ በሳምንት እስከ 250 ኪሎሜትሮች በመሮጥ በከፍተኛ ትጋት ይለማመድ ነበር፡፡ የሚመገበው ደግሞ ጓሮ ያፈራውን ፍራፍሬ እና አታክልቶችን ብቻ ነው፡፡ ዴኒስ ኪሜቶ የማራቶን ስልጠናውን በመደበኛነት የሚያከናውነው ከኤልዶሬት ወጣ በምትገኝ ካፓንግኡቱኒ በተባለች የገጠር ከተማ ነው፡፡ ከ2008 እኤአ ጀምሮ  አብረው ልምምድ የሚሰሩት ደግሞ የማራቶንን የምንግዜም ፈጣን ሰዓት በ2ኛ እና በ3ኛ ደረጃ የያዙት ኬንያውያኑ ጂኦፍሪ ሙታይ እና ዊልሰን ኪፕሳንግ ናቸው፡፡ የእነዚህ ሶስቱ አትሌቶች ማራቶንን መሮጫ አማካይ ሰዓት 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ07 ሰከንዶች ነው፡፡ ዴኒስ ኬሚቶ ከ2012 ጀምሮ የማራቶን ሊግ አካል የሆኑ እና ሌሎች ትልልቅ ውድድሮችን ሮጧል፡፡ በ2012 በበርሊን ማራቶን ሁለተኛ ነበር፡፡ በ20014 የቦስተንን ማራቶንን አቋርጦ ወጥቷል፡፡ በ2013 የቶኪዮና የቺካጎ ማራቶኖች አሸንፏል፡፡ እንዲሁም ዘንድሮ የበርሊን ማራቶንን በሪከርድ ሰዓት በማሸነፍ በአጭር ግዜ የተሳካለት ዓለም አቀፍ ማራቶኒስት ሆኗል፡፡
ከ2 ሰዓት በታች የት እና መቼ?
ማራቶን ከ2 ሰዓት በታች ይገባባቸዋል ተብለው የተጠበቁ ውድድሮች የበርሊን እና የለንደን ማራቶኖች ናቸው፡፡ በተለይ የበርሊን ማራቶን ለውድድሩ አዳዲስ ሪከርዶች በተደጋጋሚ የሚመዘገቡበት አመቺ መድረክ ሆኖ  ቀጥሏል፡፡ ባለፉት 11 ዓመታት 6  የዓለም ማራቶን ሪከርዶች በበርሊን ማራቶን ተሰብረዋል፡፡ በተለይ ያለፉት አምስት የማራቶን  ሪከርዶች ደግሞ የኬንያ እና የኢትዮጵያ አትሌቶች የተፈራረቁባቸው ናቸው ፡፡ በ2003 እኤአ ላይ ኬንያዊው ፖል ቴርጋት በ2 ሰዓት ከ04 ደቂቃዎች ከ55 ሴኮንዶች፤ በ2007 በ2 ሰዓት ከ04 ደቂቃዎች ከ26 ሴኮንዶችና በ2008 እኤአ 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ59 ሴኮንዶች በኢትዮጵያዊው ኃይሌ ገብረስላሴ በርሊን ላይ የተመዘገቡ የሪከርድ ሰዓቶች ነበሩ፡፡ ከዚያ በኋላ ኬንያውያን የሪከርድ መዝገቡን ተቆጣጥረውታል፡፡ በ2011 እኤአ በ2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ38 ሴኮንዶች  ፓትሪክ ማኩ፤ በ2013 እኤአ 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ23 ሴኮንዶች  ዊልሰን ኪፕሳንግ እንዲሁም በ2014 እኤአ በ2 ሰዓት ከ02 ደቂቃዎች ከ57 ሴኮንዶች ዴኒስ ኪሜቶ ናቸው፡፡ መረጃዎች  እንደሚያመለክቱት ባለፉት 30 ዓመታት ከተመዘገቡ የማራቶን ሪከርዶች ስምንቱ በበርሊን ማራቶን  የተገኙ ናቸው፡፡ አራቱ በቺካጎና በለንደን አራት ሪከርዶች እንዲሁም  በሮተርዳም 3 የዓለም ማራቶን ሪኮርዶች ተመዝግበዋል፡፡
የዓለም ማራቶን ሪከርድ በአይኤኤኤፍ እውቅና ተሰጥቶት መፅደቅ የጀመረው በ2004 እኤአ ነው፡፡ ስለዚህም ባለፈው ሳምንት በዴኒስ ኪሜቶ የተመዘገበው በአይኤኤፍ የሚታወቅ እውቅና የሚያገኝ የዓለም ማራቶን ሪኮርድ ይሆናል፡፡ ከዚያን በፊት ክብረወሰኑ ይመዘገብ የነበረው ምርጥ ሰዓት እየተባለ ነበር፡፡ በ1908 እኤአ ላይ የተመዘገበው የመጀመርያው የማራቶን ምርጥ ሰዓት  2 ሰዓት ከ55 ደቂቃዎች ከ18 ሴኮንዶች ሲሆን ከዚያን በኋላ እስከ ዴኒስ ኪሜቶ ክብረወሰን ድረስ ከ45 በላይ የማራቶን ክብረወሰኖች ተመዝግበዋል፡፡
የማራቶን ሪከርድ በ1900  2፡40 ፤ በ1920ዎቹ 2፡32፤ በ1950ዎቹ 2፡15፤ በ1960ዎቹ 2፡08 ነበር፡፡ ከ1999 እኤአ ወዲህ በ3 ደቂቃዎች ተሻሽሎ 2፡05 ደረሰ፡፡ ከ2004 እኤአ ጀምሮ 2፡04 እና 2፡03 እያለ ቀጥሏል፡፡  ከ10 ዓመታት በፊት ከ2 ሰዓት 5 ደቂቃዎች በታች ማራቶን የሚገቡ ሁለት አትሌቶች ነበሩ፡፡ ባለንበት ጊዜ ግን በዚያ  ሰዓት የሚገቡት ከ35 በላይ ናቸው፡፡ ከ2 ሰዓት ከ06 ደቂቃዎች በታች የሚገቡ ከ50 በላይ ማራቶኒስቶች ይገኛሉ፡፡ በ2013 እኤአ ላይ ከ2 ሰዓት ከ10 ደቂቃዎች በታች ከገቡ 149 አትሌቶች 80ዎቹ የኬንያ ሲሆኑ የኢትዮጵያ 47 ናቸው፡፡
ብዙዎቹ የሁለቱ አገራት አትሌቶች በመጀመርያ ውድድራቸው ከ2 ሰዓት 4 ደቂቃዎች ውስጥ የሚገቡት 20 ደርሰዋል፡፡
ስፖርት ሳይንቲስት በድረገፁ በሰራው ትንተና የማራቶን ርቀትን ከ2 ሰዓት በታች የሚገባ አትሌትን ለማግኘት ከ35 እሰከ 40 ዓመታት እንደሚፈጅ ገምቶ ነበር፡፡ ይህ እንዲሆን ደግሞ በየዓመቱ የማራቶን ሪከርድ ሰዓት በአማካይ በ15 ሰከንዶች እየተሻሻለ መቀጠል አለበት የሚል ድምዳሜ ላይም ደርሷል፡፡በርግጥ የማራቶን ሪከርድ ሰዓትን ከ20 ሰከንዶች በላይ ማሻሻል ትልቅ የማራቶኒስት ስኬት ነው፡፡
ከዴኒስ ኪሜቶ አዲስ የማራቶን ሪከርድ በኋላ ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት 157 ሴኮንዶች ይቀራሉ፡፡ እነዚህን ሴኮንዶች በማራገፍ ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት በርካታ ሁኔታዎች ወሳኝ ይሆናሉ፡፡ በመጀመርያ ደረጃ የማራቶኑን ርቀት ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት የሚችሉት አትሌቶች ኬንያዊ ወይንም ኢትዮጵያ ዜገነት ያላቸው መሆኑ ይጠበቃል፡፡ ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት የሚችል አትሌት በሰዓት 13.1 ማይሎችን መሸፈን ይጠበቅበታል፤ ይህ ብቃት ያላቸው የሁለቱ አገራት አትሌቶች ብቻ መሆናቸውን ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡
ከእነዚህ ሁለት የምስራቅ አፍሪካ አገራት የሚወጣ አትሌት ከ7ሺ እስከ 8ሺ ጫማ ከፍተኛ አልቲትዩድ ባለበት አገር መኖሩ፤ ከ4ሺ ጫማዎች በታች ባለ ስፍራ  ልምምዱን መስራቱ ለሚያስፈልገው ብቃት አስፋላጊ ነው፡፡ ከዚያም አትሌቱ  ከባህር ጠለል በታች ዝቅተኛ በሚባል አገር ውድድሩን ማድረጉ ከ2 ሰዓት በታች የመገባቱን ሁኔታ ያጠናክረዋል፡፡
በሌላ በኩል ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት እንደ ዩሴያን ቦልት አይነት የላቀ ብቃት ያለው አትሌት መፈጠሩም ትረጉም ይኖረዋል፡፡ ከዩሴያን ቦልት በፊት መቶ ሜትርን በ9.6 ሰከንዶች ለመሸፈን ይቅርና በ9.7 ሰከንዶች አይገባም ይባል ነበር፡፡ በአጠቃላይ የሰው ልጅ በሚችለው ብቃት ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት  የስልጠና ሳይንስ እና ቴክኖሎጂም ለውጥ ይፈጥራል፡፡ 40 አመት በፊት የነበረው ስልጠና አሁን በከፍተኛ ደረጃ ማደጉ እንደ አጋዥ ምክንያት ሊጠቀስ የሚችል ነው፡፡አዲዳስ ለማራቶን ሯጮች የሚሰራቸው የመሮጫ ጫማዎች ለሪከርድ ሰዓቶች መመቸታቸው ሌላው አስተዋፅኦ ነው፡፡ ባለፈው ሳምንት እንኳን ዴኒስ ኪሜቶ ለሰበረው ሪከርድ አዲዮስቡስት የተባለው መሮጫ ጫማ ጠቅሞታል ተብሏል፡፡ ሌላው ኬንያዊ ፓትሪክ ማኩ ከ2 አመት በፊት ሪከርድ ያስመዘገበው በዚሁ መሮጫ ጫማ የነበረ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ የማራቶንን የምንግዜም ፈጣን ሰዓት ያስመዘገቡት አራት የኬንያ አትሌቶች እና ኃይሌ ገብረስላሴ ጨምሮ የሚጠቀሙት አዲዮስቡስት መሆኑ ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት የሚደረገውን ጥረት የአዲዳስ ምርት ሊያግዘው እንደሚችል እምነት አሳድሯል፡፡  አሯሯጮችም የሚያከናውኑት የቡድን ስራ ምክንያት እንደሚሆንም ተጠቅሷል፡፡ አሯሯጮቹ  ሙሉ ለሙሉ ማራቶን ቢሮጡ ሪከርዶች እና ፈጣን ሰዓት የማስመዝገብ ብቃት አላቸው፡፡ በ2011 እኤአ ላይ የኃይሌን ሪከርድ የነጠቀው ፓትሪክ ማኩ በፊት አሯሯጩ እንደነበር ይታወቃል፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች ብራዚል በሪዮዴጄኔሮ ከተማ ከምታዘጋጀው 30ኛው ኦሎምፒያድ በፊት አዲሱ የዴኒስ ኪሜቶ የማራቶን ሪከርድ ሊሰበር እንደሚችል ይገልፃሉ፡፡ ከ2 ሰዓት በታች የሚገባ አትሌት ደግሞ ከ10 እስከ 15 ዓመታት ጊዜ ውስጥ ይገኛል እየተባለ ነው፡፡
እነማን ታጭተዋል ኬንያዎች፤ ቀነኒሳ እና ሌሎች
ከሶስትና አራት የውድድር ዘመናት በፊት ከ2 ሰዓት ከ5 ደቂቃ በታች ከሚገቡ 10 አትሌቶች ሰባቱ እድሜያቸው በአማካይ 24 የሆኑ ነበሩ፡፡ ባለፉት አምስት አመታት የታየው ግን ሪከርድ የመስበር እድል ያላቸው በእድሜያቸው በሰል ያሉ አትሌቶች ናቸው፡፡ በ2011 እኤአ ላይ የኃይሌን ሪከርድ የሰበረው ፓትሪክ ማኩ 29፤ አምና የፓትሪክ ማኩን ሪከርድ ያሻሻለው ሌላው ኬንያዊ ዊልሰን ኪፕሳንግ 31 ዓመታቸው ነበር፡፡ በ2007 እና በ2008 እኤአ በቅደም ተከተል ለሁለት ጊዜ ሪኮርዶቹን የሰበረው ኃይሌ ገብረስላሴ በ34 እና 35 አመት እድሜው ነበር፡፡
እንደኦልአትሌቲክስ ድረገፅ ስታስቲካዊ መረጃ እና ደረጃ በረጅም ርቀት የአትሌቲክስ ውድድሮች ኬንያውያን በወንዶች ምድበ ከፍተኛ ብልጫ ሲኖራቸው ኢትዮጵያውያን በሴቶች ምድብ ይሻላሉ፡፡ በ2012 እና በ2013 ከተመዘገቡ የማራቶን ፈጣን ሰዓቶች ኬንያውያን በወንዶች ምድብ ሲበዙ በሴቶች ኢትዮጵያውያን ይበዛሉ፡፡  በአሁኑ ጊዜ በ2 ሰዓት ከ03 ደቂቃዎች ከ23 ሰከንዶች እስከ 2 ሰዓት ከ4 ዲቃዎች ከ05 ሰከንዶች የተመዘገቡ አራት ፈጣን ሰዓቶች የኬንያውያን ናቸው፡፡ ኢትዮጵያን ከእነዚህ ፈጣን ሰዓቶች በመቀጠል የተመዘገቡትን አምስት ፈጣን ሰዓቶች አስመዝግበዋል፡፡ ብዙዎቹ የኢትዮጵያ አትሌቶች ከኬንያውያን አንፃር ብልጫ ያላቸው ትልልቅ ማራቶኖችን ደጋግሞ በማሸነፍ እንጅ ምርጥ ሰዓት በማስመዝገብ አይደለም፡፡ በማራቶን ሪከርዶች ታሪክ 90 በመቶው ድርሻ በኬንያ እና ኢትዮጵያ አትሌቶች የተመዘገበ መሆኑ ከእንግዲህ ለሚመዘገቡ የማራቶን ሪከርዶች ዋና እጩ ተደርገዋል፡፡
ከ2 ሰዓት በታች ማራቶንን ለመግባት ወይንም አዲስ የማራቶን ክብረወሰን ለማስመዝገብ ቅድሚያ ግምት ካገኙ አትሌቶች የመጀመርያው ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ በፓሪስ የመጀመርያ ማራቶኑን በመሮጥ 2 ሰዓት ከ05 ደቂቃዎችች ከ03 ሰከንዶች አስመዝግቦ የቦታውን ክብረወሰን ያሻሻለው የ31 ዓመቱ ቀነኒሳ በቀለ ማራቶን ልዕልቷን ወደ ኢትዮጵያ ይመልሳል ተብሎ በብዙ ሚዲያዎች ግምት ተሰጥቶታል፡፡ ቀነኒሳ በርሊን ላይ ከሮጠ ለሪከርዱ እድል ይኖረዋልም ተብሏል፡፡ ከቀነኒሳ ባሻገር ግምቱ ወደ ኬንያውያን አትሌቶች በብዛት ያጋደለ ነው፡፡
ከሳምንት በፊት በበርሊን ማራቶን ሁለተኛው የዓለም ፈጣን ሰዓ ያስመዘገበው ሌላው ኬንያዊ ጄፍሪ ሙታይ ግንባር ቀደም ግምቱን በመውሰድ ይጠቀሳል፡፡
በቆጂእና አካዳሚዎቻችን  የኬንያን ብልጫ እንዲመልሱ
የዓለም ምርጥ ማራቶኒስቶች ከሁለቱ የምስራቅ አፍሪካ አገራት ከኬንያ እና ከኢትዮጵያ እየወጡ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ በቆጂ የምትባለዋ የክልል ከተማ በኬንያ ኤልዶሬት እና ኢቴን የተባሉ ከተማዎች ማራቶኒስቶችን በማውጣት በመላው ዓለም የሚስተካከላቸው የለም፡፡ ኦሮምያ ክልል አርሲ ውስጥ የምትገኘው የበቆጂ ገጠር ከተማ የትልልቅ የዓለም ማራቶኒስቶች መፍለቂያ በመሆኗ በየጊዜው ከፍተኛ ትኩረት እያገኘች በመላው ዓለም በሚሰራጩ ሚዲያዎች ተዳስሳለች፡፡ የበቆጂ ለጥ ያለ መልክዓ ምድር እና ተስማሚ  እና ተስማሚ አየር ንብረት  በርካታ የውጭ አገር አትሌቶችን እየሳበም ነው፡፡  ከወራት በፊት አንድ የቱርክ ጋዜጠኛ የበቆጂ ከተማን በመጎብኘት ያቀረበው ዘገባ ያቀረበው አሃዛዊ መረጃ የሚያስገርም ነው፡፡  17ሺ ነዋሪዎች ያሏት የበቆጂ ከተማ በረጅም ርቀት የአትሌቲክስ ውድድሮች ታሪክ ከፍተኛውን ውጤት ያስመዘገቡ የዓለም ምርጥ አትሌቶች መገኛ ስትሆን፤ 7 የኦሎምፒክ ሻምፒዮኖችን አፍርታለች፡፡ ቀነኒሳ በቀለ እና ታናሽ ወንድሙ ታሪኩ በቀለ፤ ደራርቱ ቱሉ እና የእህቷ ልጆች የሆኑት የዲባባ እህትማማቾች፤ ፋጡማ ሮባ እና ቲኪ ገላና ትውልዳቸው ከበቆጂ መሆኑን የዘረዘረው የቱርኩ ጋዜጠኛ፤ የበቆጂ ሯጮች ባለፉት 20 ዓመታት በዓለም አትሌቲክስ 16 ሜዳልያዎች 10 የወርቅ፤ ከ30 በላይ የዓለም ሻምፒዮና ሜዳልያዎችን መሰብሰባቸውን ጠቅሷል፡፡ የበቆጂን አትሌቶች ስኬት በንፅፅር ሲያስቀምጠው 17ሺ ህዝብ ያላት የገጠር ከተማዋ በኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያዎቿ ብዛት 1.2 ቢሊዮን ህዝብ ካላት ህንድ ትበልጣለች፤ 247 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ኢንዶኔዥያ በሁሉም ኦሎምፒኮች በሁሉም ውድድሮች ባላት ተሳትፎ ካገኘችው የሜዳልያ ስብስብ በእጥፍ የሚል የሜዳልያ ስብስብም ካላት አሳይቷል፡፡ የዲባባ እህትማማቾች በኦሎምፒክ መድረክ ያገኟቸው የወርቅ ሜዳልያዎች ብዛት 22 ሚሊዮን ህዝብ ካላት ሲሪያ እና 28 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ሳውዲ አረቢያ በድምር የሰበሰቡትን እንደሚበልጥ አመልክቶም ጥሩነሽ ዲባባ የሰበሰበችውን የወርቅ ሜዳልያ ብዛት 179 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ፓኪስታን አለማግኘቷን አውስቷል፡፡  አሁን በዓለም የጎዳና ሩጫዎች እና ማራቶኖች ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገቡ ያሉ አትሌቶች ከበቆጂ የተገኙ መሆናቸው የከተማዋን የማራቶን ሯጮች መፍለቂያነት ያረጋግጣል፡፡ ስለዚህም የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽንና የኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ኮሚቴ በዚህች ከተማ በስፋት አትሌቶችን ለማፍራት መንቀሳቀሳቸው ማራቶን ልዕልቷን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ ወሳኝ ተግባር ይሆናል፡፡ እንደበቆጂ ሁሉ ኬንያም ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጮቿንና ማራቶኒስቶቿን የምታገኝባቸው ሁለት ልዩ አካባቢዎች ኤልዶሬት እና ኢቴን የተባሉት የገጠር ከተሞች ናቸው፡፡ በተለይ ኢቴን ከቅርብ አመታት ወዲህ የማራቶን ሯጮች መገኛ ብቻ ሳይሆን የዓለም ማራቶን ሯጮች መናሐርያ መሆንም ጀምራለች፡፡   ከሁለት ዓመት በፊት የኬንያ ምርጥ ማራቶን ሯጮች በሚፈልቁባት ኢቴን የተባለችው ከተማ በለንደን ማራቶን አዘጋጆች የሚደገፍ የማሰልጠኛ ትራክ ተሰርቶ ስራ ጀምሯል ባለፉት አምስት አመታት በርካታ የእንግሊዝ እና የአውሮፓ ሯጮች ከተማዋን መቀመጫቸው በማድረግ ትልልቅ የልምምድ ፕሮግራሞችን ያከናወናሉ፡፡ አንዳንድ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በማንኛውም ወቅት በዚህች ኢቴን በተባለች ከተማ ቢያንስ እስከ 30 የውጭ አገር ሯጮች ይሰራሉ፡፡
በአጠቃላይ የኢትዮጵያን አትሌቲክስ የሚመሩ ተቋማት በስፖርቱ ከፍተኛ ስኬትን ማግኘት፤ በኬንያ የተወሰደውን ብልጫ ለማስተካከል እንዲሁም በሪከርድ ሰዓቶች ውጤቱን የሚያጅብ ትውልድ ለመፍጠር በትጋት መንቀሳቀስ ይገባቸዋል፡፡ ለዚህም በአገሪቱ የተለያዩ ክልሎች ያሉ አዳዲስ አካዳሚዎች በሙሉ ራእይ እና አቅም መስራታቸው ግድ ይላል፡፡ የኢትዮጵያ ወጣቶች ስፖርት አካዳሚ በተለይ ለአትሌተክስ ስፖርት ውጤታማነት ጉልህ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው በተግባራዊ እንቅስቃሴዎች መታየቱ ይጠበቃል፡፡ ታዳጊዎች ጥቅም ይኖረዋል፡፡ ከአካዳሚዎቹ በ2016 ሪዮዲጂኔሮ እስከምታስተናግደው 31ኛው ኦሎምፒያድ ድረስ ምርጥ ወጣት አትሌቶችን በማፍራት የኢትዮጵያን አትሌቲክስ ከኬንያ እጅግ ወደኋላ እየራቀ የመጣበትን ሁኔታ መለወጥ  ይጠበቃል፡፡ አካዳሚዎቹ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ እድገት እና እንቅስቃሴን በሙሉ ፍላጎት በመከታተል በብሩህ ራዕይ የሚሰሩ ብቁ ባለሙያዎች ኖሯቸው መስራት አለባቸው፡፡ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተሠሩት አካዳሚዎች ከመሠረተ ልማት ግንባታው ባሻገር ወደተግባራዊ ስልጠና መግባት ይጠበቅባቸዋል፡፡ የአርሲ አካዳሚዎች የአትሌቶች መገኛ ለሀገራቸው በቆጂ እና በአርሲም ከተማ አሰላ ሁለት አካዳሚዎች በስፖርት ሚኒስትር ተገንብተዋል፡፡ ከ600 በላይ ታዳጊ አትሌቶችን ሲያሰለጥኑ የቆዩ ናቸው፡፡ እነዚህ ታዳጊ አትሌቶች የኬንያን የበላይነት ለመስተካከል ትኩረት ተሰጥቶ ከተሰራባቸው ስኬታማ ለመሆን አይቸግርም፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ማራቶን ልዕልቷ ተብሎ ሲዘመር የኖረው የበላይነት ማራቶን ሃራምቤ ተብሎ በኬንያውያን የበላይነት ይቀጥላል፡፡

እየጮሁ ማውራትና መጨቃጨቅ ተከልክሏል
በሞባይል ወደ ውጭ አገራት መደወል አይፈቀድም
የሞባይል ባለቤት መሆን የሚችሉት ከፍተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙ ብቻ ናቸው

የሞባይል ስልክ ተጠቃሚዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ በሚገኝባት ደቡብ ኮሪያ፣ በተጠቃሚዎች ላይ የሚታየውን የስነ-ምግባር ጉድለት ለመቅረፍ ሲባል አዲስ የአጠቃቀም መመሪያ መውጣቱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ዮንሃፕ የተባለውን የደቡብ ኮሪያ የዜና ተቋም ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በአገሪቱ የሞባይል ተጠቃሚዎች ላይ ከሚታዩ የስነ-ምግባር ጉድለቶች መካከል፣ ሰው በተሰበሰበባቸው አካባቢዎች ጮክ ብሎ ማውራትና መጨቃጨቅ ይገኙባቸዋል፡፡አዲሱ የአገሪቱ የሞባይል አጠቃቀም የስነ-ምግባር መመሪያ እንደሚለው፣ ተጠቃሚዎች ህዝብ በተሰበሰበባቸው አካባቢዎች ድምጻቸውን ቀነስ አድርገው በትህትና መነጋገር ይኖርባቸዋል፡፡በሞባይል ስልክ የሚደረጉ አላስፈላጊ ጭቅጭቆችን ለማስወገድ ሲባልም፣ የተደወለላቸው ሰዎች ጥሪያቸውን ሲመልሱ፣ ለደዋያቸው ማንነታቸውን ማስተዋወቅ ይጠበቅባቸዋል፡፡
 የደዋያቸውን ማንነት እንዳወቁ መግለጽም ይገባቸዋል፡፡ ይህም ደዋዩ ራሱን ለማስተዋወቅ ጊዜ እንዳይፈጅ ያግዘዋል ተብሏል፡፡
እ.ኤ.አ በ2008 የሞባይል ስልክ አገልግሎት ተጠቃሚ በሆነችው ደቡብ ኮሪያ፣ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ቁጥር ከ2 ቢሊዮን በላይ እንደደረሰ የጠቆመው ዘገባው፣ ይህም ሆኖ ግን አሁንም ድረስ አለማቀፍ ጥሪዎችን ማድረግ ክልክል ነው፡፡
የሞባይል ስልክ ባለቤት መሆን የሚችሉትም፣ በከፍተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ የማህበረሰብ ክፍሎች ብቻ ናቸው ብሏል፡፡

አብዛኞቹ የአገሪቱ ባለስልጣናት ፖሊሲ ሲያወጡ ጠንቋይ ያማክራሉ
የታይላንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ፕራዩዝ ቻኖቻ፣ ወደ ጠንቋዮች ጎራ ብሎ የመጪውን ጊዜ ዕጣ ፋንታ በተመለከተ የሚሰጡትን ትንቢትና ምክር መስማት ክፋት የለውም፤ ጥንቆላም ራሱን የቻለ ጥበብ ነው ሲሉ መናገራቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
“ጠንቋዮች የሚነግሩኝን ትንቢት ልብ ብዬ እሰማለሁ፡፡ ምክራቸውንም እቀበላለሁ፡፡ እንዲያውም በቅርቡ በአገሪቱ ከሚገኙ መገናኛ ብዙሃን ጋር ግጭት ውስጥ ልገባ እንደምችል አስጠንቅቀውኛል” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ መገናኛ ብዙሃን መሪያችን ጠንቋይ ቤት ይሄዳሉ ሲሉ ያሰራጩት ዘገባም ትክክለኛ እንደሆነ አረጋግጠዋል፡፡
ቻኖቻ በመገናኛ ብዙሃን ስለጠንቋይ አማኝነቴ የሰማችሁት ትክክል ነው ሲሉ ባለፈው ማክሰኞ መናገራቸውን የገለጸው ዘገባው፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠላቶቻቸው ካሰሩባቸው ድግምትና አስማት ለመንጻት ሲሉ፣ ከእግር እስከ ራሳቸው ጠበል መጠመቃቸውን በወሩ መጀመሪያ ላይ በይፋ መናገራቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
የአገሪቱን የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ታክሲን ሺንዋትራን ጨምሮ በርካታ ደንበኞችን ወዳፈራው ኢት የተባለ የማይናማር ታዋቂ ጠንቋይ በመሄድ ምክር ይሰማሉ መባሉን ያስተባበሉት ቻኖቻ፣ ይሄም ሆኖ ግን ወደ ጠንቋዩ የመሄድ ፍላጎት እንዳላቸው አልደበቁም፡፡
ከአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናትና ፖለቲከኞች አብዛኞቹ፣ የፖሊሲ ለውጥ ለማድረግ ሲያስቡ ወደ ጠንቋዮች ሄደው፣ “ይበጃል፣ አይበጅም?” ብለው የማማከር ልማድ እንዳላቸው የጠቆመው ሮይተርስ፣  ታይላንድ ወደዘመናዊነት እየተሸጋገረች ያለች አገር ብትሆንም፣ ለረጅም ዘመናት የዘለቀው ጥንቆላና መሰል የባዕድ አምልኮ አሁንም ድረስ በስፋት እንደሚከናወንባት አመልክቷል፡፡

ውድ እግዚአብሔር፡-
ወንድሜ ቶሎ ቶሎ ሽንቱን ይሸናል፡፡ እኔ ግን አይመጣብኝም፡፡ ለእኔ ብዙ ያልሰጠኸኝ አልቆብህ ነው?
ናቲ- የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ኤሊዬ ሞታብኛለች፡፡ ጓሮአችንም ቀብረናታል፡፡ አሁን ካንተ ጋር ናት እንዴ ?
ከሆነች ሰላጣ በጣም ትወዳለች እሺ፡፡
ዴቭ- የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ትልቅ ስሆን ቅርጫት ኳስ መጫወት እፈልጋለሁ፡፡ በደንብ መጫወት እንድችል ቆዳዬን ጥቁር አድርግልኝ፡፡ ቁመቴንም በጣም አርዝምልኝ፡፡
አሌክስ- የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ወዳንተ ስፀልይ ደስ ይልሃል አይደል? እኔም ደስ ይለኛል፡፡
ጄሪ- የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
የሰንበት ት/ቤት አስተማሪዬ አንተ ሁልጊዜ እንደምትወደኝ ነግራኛለች፡፡ እውነቷን ነው? ትላንት ሳራ ላይ ያንን ነገር ካደረኩም በኋላ ትወደኛለህ? አውቀኸዋል አይደል?! በጣም አዝናለሁ፤ አሁንም ብትወደኝ ግን ደስ ይለኛል፡፡
ቤቲ - የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
አያቴ ልትሞትብኝ ነው፡፡ አንተ እንደምትፈልጋት ነግራኛለች፤ እኔ ግን እዚህ አብራኝ እንድትሆን እፈልጋለሁ፡፡ሌላ የፈለግኸውን ሰው መውሰድ ትችላለህ፡፡
ለእኔ ያለችኝ እሷ ብቻ ናት፡፡ እባክህን ከህመሟ ድና አብራኝ እንድትሆን አድርጋት፡፡
ጆኒ- የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ለምንድነው እባብና ሸረሪቶችን የፈጠርከው? በጣም እኮ ነው የምፈራቸው፡፡
ጄሪ- የ6 ዓመት ህፃን

         በአዲስ አበባ በየዓመቱ የሚካሄደው የአውሮፓ ፊልም ፌስቲቫል ትላንት ዕለት ምሽት በ12 ሰዓት በጣልያን የባህል ማዕከል The Great Beautiful በተሰኘው የጣልያን ፊልም ተከፈተ፡፡
ለ15 ቀናት በሚዘልቀው የፊልም ፌስቲቫል ላይ የ15 አውሮፓ አገራት ፊልሞች ለተመልካች የሚቀርቡ ሲሆን የጣልያን ባህል ማዕከልን ጨምሮ በገተ ኢንስቲቲዩትና በአልያንስ ኢትዮ ፍራንሴስ ፊልሞቹ እንደሚታዩ ታውቋል፡፡
ሁሉም ፊልሞች በነፃ ለተመልካች የሚቀርቡ ሲሆን በእንግሊዝኛ ቋንቋ ወይም በእንግሊዝኛ ትርጉም (subtitles) እንደተዘጋጁም ለማወቅ ተችሏል፡፡ የፊልም ፌስቲቫሉ ጥቅምት 7 ቀን 2007 ዓ.ም The Selfish Giant በተሰኘው የእንግሊዝ ፊልም እንደሚጠናቀቅም ታውቋል፡፡

Monday, 06 October 2014 08:41

“መረቅ” ነገ ይመረቃል

በደራሲ አዳም ረታ የተጻፈው “መረቅ” የረጅም ልቦለድ መጽሃፍ፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ የደራሲው አድናቂዎችና የጥበብ ቤተሰቦች በተገኙበት ነገ ጧት በሃገር ፍቅር ቲያትር አዳራሽ ይመረቃል፡፡
ለረጅም አመታት በውጭ አገራት የኖረው ደራሲ አዳም በሚገኝበት በሚከናወነው የምረቃ ስነ-ስርዓት ላይ፣ የተለያዩ ስነ-ጽሁፋዊ ዝግጅቶች የሚቀርቡ ሲሆን፣ ስለደራሲው ስራዎችም ማብራሪያ ይሰጣል፡፡
ለደራሲው ስምንተኛ ስራው የሆነውና 600 ገጾች ያሉት “መረቅ”፣ በሶስት ዋና ዋና ክፍሎች የተዋቀረ ሲሆን የመሸጫ ዋጋውም  120 ብር ነው፡፡