Administrator

Administrator

“ዕጣው ያልደረሰኝ… ለበጐ ነው”

    የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባለፈው መጋቢት አጋማሽ ላይ 30ሺ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለከተማዋ ነዋሪዎች በዕጣ ማስረከቡን አብስሮናል፡፡ እውነትም የአፍሪካ መዲና የሆነችውና ከ4 ሚሊዮን ህዝብ በላይ ይኖርባታል ተብሎ የሚገመትባት አዲስ አበባ፤ ፈርጀ ብዙ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች እየተካሄደባት የምትገኝ ከተማ ናት፡፡ የከተማው አስተዳደር ከአስር ዓመት በፊት የጀመረው የኮንዶሚኒየም የመኖሪያ ቤቶች ግንባታ አሁን 10ኛ ዙር ላይ ሲሆን 136ሺ ቤቶችም ለነዋሪዎች ተላልፈዋል ተብሏል፡፡
የኮንዶሚኒየም ቤቶች ግንባታ በመሰረቱ የድሃውን ህብረተሰብ የመኖሪያ ቤት ችግር ይቀርፋል በሚል ዓላማ የተወጠነ ፕሮጀክት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በተጨባጭ ግን በሀገሪቱ በፈጣን ሁኔታ እየገሰገሰ ባለው የኢኮኖሚ ዕድገት ምክንያት ፍላጎትና አቅርቦቱን ማጣጣም ባለመቻሉ፣ የመኖሪያ ቤቶቹን እየተጠቀመ ያለው ድሃው የህብረተሰብ ክፍል ሳይሆን መካከለኛ ገቢና ከዚያ በላይ የተሻለ ገቢ የሚያገኘው የህብረተሰብ ክፍል ነው። ለዚህ መቼም ሳይንሳዊ ትንተና የሚያስፈልገው አይመስለኝም። በየኮንዶሚኒየሙ የተሰቀሉ የቴሌቪዥን ሳህኖች፤ በየፎቁ ስር ተጨናንቀው የቆሙ መኪናዎችና የኮንዶሚኒየም ቤቶች ከፍተኛ የኪራይ ዋጋ በቂ ምስክሮች ናቸው፡፡
ቤቶቹን ድሆች እጣው ደርሷቸው ያከራዩት… ወይም ባለእድሉ ነዋሪ ራሱ ይኑርበት ዜጎች ወጥተው የሚገቡበት ታዛ መገኘቱ በራሱ እሰየው ያስብላል፡፡
ነገር ግን ከ1997 ዓ.ም ጀምሮ እጣ ወጥቶላቸው መኖሪያ ቤታቸውን በአቅም ማነስ ምክንያት መረከብ ያልቻሉ ዜጎች ቁጥር እየተበራከተ መምጣትና እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የቁጠባ ባህልን ማዳበር እንዲችል ለማበረታታት የከተማ ቤቶች ልማት ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በደረሱት ስምምነት መሰረት፣ ባንኩ ለኮንዶሚኒየም ቤቶች መገንቢያ የሚሆን 1ቢሊዮን ብር ለአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ጽ/ቤት በብድር መልክ እንዲሰጥ መወሰናቸው ይታወሳል፡፡
መንግስት በጥናት ደረስኩበት ባለው መሰረት፤ በተጨባጭ የመኖሪያ ቤት ችግር ያለበት ድሃው የህብረተሰብ ክፍል እጣው በወጣለት ወቅት የሚጠየቀውን ቅድሚያ ክፍያ ማሟላት አለመቻሉን ታሳቢ በማድረግ፣ የ1997 ዓ.ም ተመዝጋቢዎችን ዳግም በመጥራት እንዲሁም አዲስ ተመዝጋቢዎችን አካቶ በሰኔ ወር 2005 ዓ.ም ላይ ባካሄደው ምዝገባ፣ ከ900ሺ በላይ ቤት ፈላጊ የከተማዋ ነዋሪዎችን እንደ አቅማቸው በ10/90፤ በ20/80 እና በ40/60 መርሀ ግብር ከፋፍሎ ወደ ቁጠባ ማስገባቱ ይታወቃል፡፡
ይሄን ተከትሎም 135 ሺህ የሚደርሱ የ1997 ዓ.ም ተመዝጋቢዎች፣ የእድሉ ቅድሚያ ተጠቃሚ እንዲሆኑ አድርጓል፡፡ ከ21 ወራት ቁጠባና ቆይታ በኋላም ባለፈው መጋቢት 13 ቀን 2007 ዓ.ም ቢያንስ ለ16 ወራት የቆጠቡ ነዋሪዎች በእጣው ተካትተው፣ 35ሺ የሚደርሱ የከተማዋ ነዋሪዎችን የቤት ባለ እድል ማድረጉን አስታውቋል፡፡ መቼም እጣው ደርሶት ያልተደሰተ፤ ያልፈነደቀ ያለመኖሩን ያህል፣ 16 ወራት መቆጠብ ባለመቻሉ ከእጣው የተገለለና ቆጥቦ እንኳን ቢሆን እጣው ያልወጣለትና ያላዘነ ሰው ይኖራል ብዬ አልገምትም፡፡ ሆኖም ግን ይህ ደስታና ሁካታ በብርሃን ፍጥነት ወደ ሀዘንና ተስፋ ማጣት ሲቀየር፣ በአንጻሩ እጣው ያልወጣለት ደግሞ “እሰየው ለበጎ ነው… እጣው የዘለለኝ” ሲል ከሳምንት ያልበለጠ ጊዜ ብቻ ነው የወሰደበት፡፡
ለምን ይሆን አትሉም?
ምክንያቱማ የቤቶች ልማት ፕሮጀክት ጽ/ቤት ስለቤቶቹ ማስተላለፍ በበተነው ብሮሸር ላይ የተቀመጠው የቤቶቹ ሂሳብ አከፋፈል መመሪያ፣ የከተማ ልማት ሚኒስቴር በወቅቱ ተፈፃሚ ይሆናል ብሎ ቃል ከገባበት መመሪያ ጋር ተጻራሪ ሆኖ በመገኘቱ ነው፡፡ የከተማ ልማት ሚኒስትሩ በወቅቱ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ መንግስት ዜጎችን የመኖሪያ ቤት እንዲኖራቸው ለማድረግ በ1997 ዓ.ም የጀመረው የኮንዶሚኒየም ቤቶች ግንባታ በሚፈለገው ፍጥነት እየተጓዘ አለመሆኑ አንድ ጉዳይ ሆኖ፣ እጣው የወጣላቸው ባለእድለኞች ግን ቤቱን እንዲረከቡ ጥሪ በሚደረግበት ሰዓት አብዛኛው የህብረተሰብ ክፍል በይበልጥም ድሃው ለቅድምያ ክፍያ የሚሆን ገንዘብ ማግኘት ከባድ ፈተና እንደሆነበት መንግስት መረዳቱን ጠቁመው አዲስ የተዘረጋው በየወሩ የመቆጠብ አሰራር ወርሃዊ ቁጠባውን እንዲያከናውንና እጣው በወጣለት ጊዜም ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መኖሪያ ቤቱን እንዲረከብ በማድረግ የአስተማማኝ ኑሮ ዋስትና እንዲያገኝ ያግዛል በማለት መናገራቸው አይዘነጋም፡፡
ሚኒስትሩ ይህን ቃል ሲናገሩ፤ እያንዳንዱ ቤት ፈላጊ የእድሉ ተጠቃሚ እንዲሆን ቢያንስ በየወሩ እንዲቆጥብ የተተመነበትን ሂሳብ በአግባቡ ከቆጠበ፣ እጣው በደረሰው ወቅት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ቤቱን ተረክቦ ኑሮውን ይጀምራል ማለታቸው እንደሆነ የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ ይገነዘባል፡፡ ነገር ግን ለ10ኛ ዙር ባለ እድለኞች የቀረበላቸው መመሪያ ግን ዱብ እዳ ነገር ነው፡፡ የቤቶች ልማት ፕሮጀክት በቅርቡ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ አሁን የተገነቡት ቤቶች ዋጋ የልደታ መልሶ ማልማት ፕሮጀክት ግንባታ ሲካሄድ የተፈጠረውን የዋጋ ልዩነት ታሳቢ በማድረግ፣ ከዚህ ቀደም ቤቶቹን ለመገንባት ይፈጃል የተባለው ተመን የ20 በመቶ የጭማሪ ማሻሻያ እንደተደረገበት አስታውቋል፡፡ ልብ በሉ! እንግዲህ ቤቶቹን የሚገነባው አካል በተፈጠረበት የዋጋ ንረት መሰረት የ20 በመቶ ጭማሪ ሲያደርግ የከተማው ነዋሪውም ከሚያገኘው ገቢ ላይ በንጽጽር የዚያኑ ያህል የዋጋ ንረት ይገጥመዋል ማለት ነው፡፡
ሆኖም የቤቶች ልማት ፕሮጀክት ከሁለት ዓመት በፊት ሚኒስትሩ የተናገሩትንና ተግባራዊ ይሆናል ብለው ቃል የገቡትን ውሳኔ ወደ ጐን በመተው፣ ስለ እድለኞች የመኖሪያ ቤት ርክክብ በሚያስረዳው መመሪያ ላይ በቀረበው የዋጋ ትመና መሰረት፤ ለ10/90 ቤቶች በካሬ ሜትር 1ሺ 910 ብር፤ ለ20/80 ስቱዲዮ 2ሺ 483 ብር፤ ለ20/80 ባለ አንድ መኝታ ቤት 3ሺ 438 ብር፤ ለ20/80 ባለ ሁለት መኝታ ቤት 4ሺ 394 ብር እና ለ20/80 ባለ ሶስት መኝታ ቤት 4ሺ 776 ብር መጨመሩ ታውቋል፡፡ ከዚህ ሌላ የ10/90 ባለዕድለኞች 10 በመቶ ቅድሚያ ክፍያ መክፈል ሲጠበቅባቸው፤ የ20/80 የጋራ መኖሪያ ቤት ባለእድለኞች ደግሞ የ20 በመቶ ቅድሚያ ክፍያ መክፈል ይኖርባቸዋል ይላል፡፡ እንደ ቤቶቹ አይነትና ስፋት እያንዳንዱ ባለ እድለኛ ቅድሚያ ክፍያ እንዲከፍል የቀረበለት ተመንና ከሁለት ወር የእፎይታ ጊዜያት በኋላ በ15 ዓመት ተከፍሎ የሚጠናቀቅ የወርሃዊ ክፍያ ተመን ጭንቅላት አስይዞ የሚያስጮህ፤ የሚያስበረግግ ምናልባትም እንደ እብድ በየጎዳናው ላይ ለብቻ እያወሩ እንዲጓዙ የሚያደርግ ነው፡፡ ለዚህ ነው አንዳንዱ ነዋሪ እጣው “እንኳንም አልደረሰኝ!!” ያለው፡፡
እንደ ማሳያ ለማቅረብ ያህል፣ ባለ ሁለት መኝታ ቤት የደረሰው ባለ እድለኛ አለ እንበል፡፡ አፍ ሞልቶ በእርግጠኝነት ይኖራል ማለት አስቸጋሪ ስለሚሆን ብቻ ዝም ብለን አለ እንበል፡፡ ታዲያ ይህ ሰው ለባለሁለት መኝታ ቤት የሚከፍለው ጠቅላላ ክፍያ ብር 317068 ይሆናል፡፡ በመመሪያው መሰረት፣ 20 ከመቶ ቅድሚያ ክፍያ መክፈል ስላለበት 21 ወራት እንኳን ቆጥቧል ቢባል (560 ብር x 21 ወራት = 11,760 ብር) ይመጣል ማለት ነው፡፡ ይህ ባለ እድለኛ 51,653 ብር ገደማ ለቅድሚያ ክፍያ አቅርቦ ከንግድ ባንክ ጋር መዋዋል ይጠበቅበታል፡፡ አሁን ይሄ ብር ከየት ይመጣል? ኧረ በምን ስሌት ይሆን ከሁለት ወር የእፎይታ ጊዜ በኋላ በየወሩ 2,700 ብር ከፍሎ በ15 ዓመት ውስጥ እዳውን የሚያጠናቅቀው? ምግብ አይበላም? የትራንስፖርት ወጪ የለበትም? ለልጆች የትምህርት ቤት ክፍያ አይከፍልም? እንደው በደፈናው ቤቱ ይድረሰው እንጂ ከባሌም ከቦሌም ብሎ ይክፈል በሚል የኢኮኖሚክስ መርህን በሚጥስ ስሌት ተዘጋጅቶ የቀረበ መመሪያ ነው የሚመስለው፡፡ ይሄ በእውነቱ “መንግስት አበደ እንዴ?” ያሰኛል፡፡ ግን መንግስት ቢያብድ ምን ይሆን የሚደረገው? መንግስት የኑሮውን ሁኔታና ክብደት መረዳት ይከብደው ይሆን እንዴ? የተማረ ኢኮኖሚስት ጠፍቶ ነው ወይስ የፖለቲካ ደባና ሴራ እየተካሄደ ነው? ለነገሩ ይህቺ ከተማ ለድሆች ፊቷን ካዞረች ሰነባብታለች፡፡
አንዳንዱ ሰው እኮ በአምላክ ተዓምር ካልሆነ በቀር፣ ልጆቹን እንዴት እያሳደገ እንደሆነ ማሰብ ሁሉ ይከብዳል፡፡ በዘመናዊ የሽፍን መኪና የምትመላለሱ የፖለቲካ አመራሮቻችን፤ መንግስት በአነስተኛ ክፍያ ቤት እየሰጣችሁ የምትኖሩ ባለስልጣኖቻችን፤ ልጆቻችሁን የተሻለ ት/ቤት የምታስተምሩ አለቆቻችን… እስኪ ለአንድ ወር እንኳን የእኛን የድሃዎቹን የአኗኗር ዘይቤ ኑና ተቋደሱ!!
መንግስትና አገሪቷን እየመራ ያለው ኢህአዴግ፣ በምርጫ ዋዜማ በእርግጥም ይህን አይነት የፖለቲካ ኪሳራ የሚያከናንብ ድርጊት አምኖበት ይሆን የፈጸመውን? እስኪ እውነት እንነጋገር ከተባለ መንግስት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለቤቶች መስሪያ የተበደረውን 1 ቢሊዮን ብር ለማስመለስ ዋስትና ማቅረብ ይሳነዋል? የትኛውስ ኢትዮጵያዊ ነው የባንክ እዳውን መከፈል ሳይችል ቤቱ ውስጥ መኖር የሚችለው? እውነት ንግድ ባንክ እዳቸውን ያልከፈሉ ዜጎችን መኖሪያ ቤት በሃራጅ ሸጦ ብሩን ማስመለስ ያቅተዋል?
ኢህአዴግ ትላልቅ ሃገራዊ ፕሮጀክቶችን እየመራ፣ እነዚህን ጥቃቅን የሆኑ፣ ነገር ግን ህዝብን የሚያማርሩ ስህተቶችን እንዴት ይፈጽማል?  በአፋጣኝ መፍትሄ የሚሻ ጉዳይ ነው፡፡ የሰለጠኑ አገራት አመራሮች እኮ ስህተት ተፈጽሞ ሲገኝ በይፋ ህዝባቸውን ይቅርታ ጠይቀው የእርምት እርምጃ ይወስዳሉ፡፡ እኔማ አንዳንዴ መንግስትንና ህዝብን የማቃቃር ተልእኮ ያነገቡ ጸረ ሰላም፤ ጸረ ዲሞክራሲና ፀረ ልማት ሀይሎች በመዋቅሩ ውስጥ እንዳይኖሩ እሰጋለሁ፡፡ ኢህአዴግ ሆይ፤ አሁንም የእርምት እርምጃ ለመውሰድ ጊዜው አልረፈደም። ኧረ ጎበዝ ልብ እንበል!

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ኢጣሊያዊ የማፊያ መሪ (የዘራፊ፣ የመንታፊና ገዳይ ቡድን መሪ) መሞቻው ጊዜ ደርሶ ኖሮ የልጅ ልጁን ጠራው፡፡ ከዚያም፤
“የልጅ ልጄ ያስጠራሁህ ለዋዛ አይደለም፡፡ በደንብ አዳምጠኝ”
“እሺ አያቴ፡፡ ምን ልትለኝ ፈልገሃል?”
“እንግዲህ መሞቻዬ ተቃርቧል”
“አያቴ፣ ለምን እንዲህ ትላለህ?”
 “በጣም ደህና እኮ ነህ?” ምንም የህመም ምልክት እንኳ አይታይብህም
“አይመስለኝም፡፡ ድምፄ ከመክሰሙ በፊት ብታዳምጠኝ መልካም ነው፡፡”
“እሺ አያቴ አዳምጥሃለሁ”
“አየህ እኔ ምን ጊዜም እንድታስታውሰኝ ስለምፈልግ አንድ ስጦታ ልሰጥህ እፈልጋለሁ”
“አያቴ ምንም ስጦታ ባትሰጠኝም አልረሳህም”
“በጭራሽ፡፡ የሰንሰል ቅጠልም ቢሆን ሰው ለሰው ስጦታ የሚሰጠው እንዲያስታውሰው ይጠቅመዋል፡፡ ስለዚህ ኮልት 45 ሽጉጤን እሰጥሃለሁ፡፡ ዘራፊ፣ መንታፊና የገዳይ ቡድን አባል የሆንኩትን አያትህን ምን ጊዜም የምታስታውሰኝ በዚህ ሽጉጥ ይሆናል” አለ፡፡
ይሄኔ የልጅ ልጁ፤
“ግን አያቴ፣ እኔ ሽጉጥ፣ ጠመንጃ፣ ጦር ጋሻ አልወድም፡፡ ምን ያደርግልኛል? እኔ የማፊያ ቡድን አባል አልሆንም፡፡  ይልቅስ ዕውነት የምትወደኝ ከሆን ሮሌክስ ሰዓትህን ትተህልኝ ሂድ፡፡ ውድ ሰዓትህ ሁልጊዜ አንተን የስታውሰኛል፡፡”
አያትዬው ድምፁ እየተንተባተበና እየተጎተተ መጣ፣
“የልጅ .. ል…ጄ…. በደ…ምብ አድምጠኝ የ… ቤታ…ችንን… ን.ግ.ድ.የምትመራው አንድ…ቀን አን…ተ  ነ.ህ… ከዚያ ቆንጆ ..ሚ..ስ..ት…ታገባ…ለህ፡፡ ብዙ … ገንዘብ ..  ይኖ.. ርሃል፡፡ ትልቅ ቪላ.. ቤ..ት ይኖር…ሃል፡፡ ምናል…ባ…ት..ም.. አንድ ሁለት ባምቢኖ (ልጆች) ይኖሩሃል፡፡
… እና ከዕለ… ታት አንድ ቀን … ሥ…ራ ውለህ ወደ ቤት … ስትመጣ ሚስትህ … ከሌላ ወንድ ጋር ተኝታ ልታገኛት ትችላለህ…  ያን ጊዜ ምን ታደርጋለህ? … የእኔን ሮሌክስ ሰዓት እያሳየህ “በቃችሁ ሰዓቱ ደርሷል!” ትላቸዋለህ?
ይልቅ መሳሪያዬን ተረከብ!” አለውና ድምፁ መሰማት አቆመ፡፡
*            *           *
ሁሉም ጉዳይ የየራሱ ማስፈፀሚያ አለው፡፡ የሀገራችን አንዳች የሚያህል ችግር አባትና ልጅ፣ ትውልድና ትውልዱ አለመጣጣሙ ነው፡፡ የአንዱ ፍላጎት ከሌላው ፍላጎት ጋር አለመመጋገቡ ነው፡፡ ለማንኛውም እያንዳንዱ ትውልድ የየራሱን ጣዕም ማበጀቱ እጅግ ወሳኝ ነገር ነው፡፡ የየራሱ ጣዕም የሌለው ትውልድ ለአገር አይበጅም፡፡ ስፖርት የሚያዘወትር፤ ትግል የሚወድ፣ አለ፡፡ ባንፃሩ ማጭበርበርን እንደኑሮ ዘዴ የለመደ፣ በመፈክር አገር እገዛለሁ ብሎ የሚያስብ፤ እርስ በርስ መጠላለፍን እንደፖለቲካ ካባ የደረበ ወዘተ ብዙ ዓይነት ትውልድ አይተናል፡፡
ሁሉም እኔ ልክ ነኝ ስለሚል ተው አይሆንም ማለት አዳጋች ነው፡፡ አቋሙ ታሪክ እስኪሆን በትዕግስት እንድንጠብቅ እንገደዳለን፡፡
ሌላው ችግራችን ስም-ልጠፋ ነው - በክፋት፡፡ (Branding) በዚህ ጉዳይ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ያለንን መስማት ጥሩ ነው፡-
“አንድ ተረት ልንገርህ፡፡ አንዲት እናት ልጇ አይናፋር ኖሮባት ከጓዳ አልወጣ አለ፡፡ “ወጣ በል!”  ተብሎ ከጓደኞቹ ጋር መቀላቀል ቢፈልግም አልቻለም፡፡ ግን የልጆቹን ሁሉ ስም አጥንቷል፡፡ እዚያ አካባቢ የሚነገረውን ስለሚሰማ ሁሉን ያውቃል፡፡ እቤት ይገባና ለእናቱ “በደሻ እንዲህ ሲል አፍንጮ እንዲህ ብሎ መለሰለት … ቀዮ ግን …” እያለ ይነግራታል፡፡ እናቱ ስትመልስለት “ያንተስ ስም ማነው?” ስትለው “እኔማ … እኔማ ስም የለኝም” አላት፡፡ “እንግዲያው ሂድ… ሂድ መንገዱን አቋርጥ፡፡ ልክ ስታቋርጥ ስም ያወጡልሃል፡፡ ያኔ ትነግረኛለህ፡፡” አለችው፤ ይባላል፡፡
መንገዱን ማቋረጥ የሀሳብ ትግል ይሆናል፡፡ የአቋም መለወጥ ሊሆን ይችላል። የሀሳብ ልዩነትን ግልፅ ሆኖ ማሳየት ሊሆን ይችላል፡፡ በማንኛውም የትኛውንም አዲስ መንገድ አቋርጠን እንሂድ ብንል አዲስ ስም እንደሚወጣልን ጥርጥር የለውም፡፡ ያየናቸው መንግስታት ሁሉ ለጠላቶቻቸው ስም ሳያወጡ አልኖሩም፡፡ ንፁሃን ዜጎችን ጭምር ስም ያወጡላቸዋል፡፡ ይሄ ደግ ዜጋ መንግስትን እንዳያምንና እንዲጠራጠር ያደርገዋል፡፡ ጥርጣሬ ካለ ዕድገት የለም፡፡ ልማት የለም፡፡ ወደፊት መራመድ የለም! ስለዚህ ለትንሽ ለትልቁ መንገድ አቋራጭ፤ ስም ማውጣቱን ትተን ለምን ከቤቱ ወጥቶ መንገድ አቋረጠ? ብለን መጠየቅ ያባት ነው!
ለውጥ ባየን ቁጥር ግትር ብለን አልቀበልም ማለት ጅልነት ነው፡፡ ለውጥ ባየን ቁጥር አብረን ዘራፍ ማለትም ጅልነት ነው፡፡ እኔ ምን አገባኝ ብሎ በምንግዴ መጓዝና መንግሥት ተለወጠ  አልተለወጠ፣ አይሞቀኝ አይበርደኝ ማለት የባሰ ጅልነት ነው! እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው ማለት እንደማያዋጣን ከልብ አውቀን ከተጓዝን አያሌ ነገሮችን ወደቀናው ነገ እንዲያመሩ ለማድረግ እንችላለን፡፡ ለዳግማይ ትንሣዔም እንበቃለን! መልካም በዓል!




አሸባሪው ቡድን ‘አይኤስአይኤስ’ ስደተኛ ኢትዮጵያዊያንን ገደለ
የሟች ቤተሰቦች ሐዘን ተቀምጠዋል - በኢንተርኔት ፎቶና ቪዲዮ አይተው


በሊቢያ የአሸባሪው ቡድን ‘አይኤስአይኤስ’ ታጣቂዎች፣ ’30 ኢትዮጵያዊያን ክርስትያኖችን ገድለናል’ ብለው በቪዲዮ የተቀረፀ አሰቃቂ የጭካኔ ግድያ ያሰራጩት በሳምንቱ መጨረሻ ላይ ነው። በደቡብ አፍሪካ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ላይ በደረሰው ዘረኛ ጥቃት ማግስት፣ በሊቢያ ሲቪል ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ላይ የተፈፀመው የአሸባሪ ቡድን ዘግናኝ ግድያ፤ የኢትዮጵያውያን ሐዘንና ቁጭት አክብዶታል።
በኢንተርኔት የተሰራጨው ቪዲዮና ፎቶ፣ የሟቾቹን ማንነት ወዲያውኑ ለማወቅና ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውን ለማረጋገጥ ለብዙዎች አስቸጋሪ ቢሆንም፣ ለቤተሰቦች ግን አጠራጣሪ አልነበረም። ወላጆችና ቤተሰብ፣ ወንድምና እህት፣ ጎረቤትና ወዳጆች ሁሉ ውስጥን በሚያደማ ቅፅበታዊ ሐዘን ነው የተመቱት።  
በአዲስ አበባ የኢያሱ ይኩኖአምላክ እና የባልቻ በለጠ ቤተሰቦች ድንገተኛ መርዶ የደረሳቸው እሁድ እለት ነው። በሰላሳዎቹ ዕድሜ ላይ የነበሩት ኢያሱና ባልቻ በአንድ ሰፈር ውስጥ ያደጉ ጎረቤታሞች ናቸው - በቀድሞው ወረዳ 21 ቀበሌ 25፤ በአሁኑ ወረዳ 10። የሟቾቹ ቤተሰቦች መኖሪያ ቤት አጠገብ ለአጠገብ ስለሆነ ለቅሶውም አንድ ላይ ነው፡፡
ኢያሱና ባልቻ የዛሬ ሁለት ወር ገደማ ወደ ሊቢያ የሄዱት አንድ ላይ እንደሆነ የገለፀልን የኢያሱ ወንድም፤ የሊቢያውን የግድያ ወሬ የሰማው እሁድ ዕለት ነው - ስልክ ተደውሎ። የደወለለት ሰው፣ “የናንተ ሰፈር ልጆች ሊታረዱ ሲሉ የሚያሳይ ፎቶ በፌስቡክ ተለጥፏል” ብሎ ሲነግረው፤ በደንጋጤ “እነማን ናቸው?” ብሎ ጠየቀ። “የወንድሜን ስም ጨምሮ ነገረኝ፤ የወንድሜን ስም አያውቅም ነበር” ይላል የኢያሱ ወንድም።
“የኔ ፌስቡክ ስለማይሰራ ጓደኛዬ ጋር ሄጄ አየሁ። በደንብ ስላልታየኝ እንደገና ከምሽቱ አራት ሰአት ስንከፍት ወንድሜን ተንበርክኮ አየሁት። ባልቻን ደግሞ ቀይ ቱታ ካደረጉት መሀል ለየሁት፡፡ ለእናቴ ከመንገሬ በፊት ለሩቅ ዘመዶች ለመናገር እያሰብኩ እያለ እነሱ ቀድመው ሰምተው ለቅሶ ላይ አገኘኋቸው” ብሏል የኢያሱ ወንድም።
ኢያሱ ኳታር ሰርቶ የተወሰነ ገንዘብ ይዞ ስለመጣ የባልቻንም ወጪ ሸፍኖለት ነው አብረው የሄዱት። ከኢትዮጵያ ወጥተው በሱዳን ጉዞ የጀመሩት ከሁለት ወር በፊት ነው። “ሱዳን እያሉ በስልክ እንገናኝ ነበር። ገንዘብ ሲያስፈልጋቸው እልክላቸው ነበር” የሚለው የኢያሱ ወንድም፤ “ወደ ሊቢያ ከተሻገሩ በኋላ ግን ስልክ ቁጥር እሰጥሃለሁ ቢለኝም አንገናኝም ነበር” ብሏል።  
 

 ሶስት ኢትዮጵያውያን በጥቃቱ ህይወታቸው አልፏል
- ብዙዎች ንብረታቸውን ተዘርፈዋል፣ በእሳት ተለብልበዋል
“ስደተኞችን በጉያችን ይዘን የምናባብልበት ጊዜ ማብቃት አለበት!” - የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ልጅ
“ስደተኞች ጓዛቸውን ጠቅልለው ወደመጡበት መመለስ አለባቸው!” - የዙሉ ንጉስ ዝዌሊቲኒ  
    ከሶስት ሳምንታት በፊት...
እትብታችን በተቀበረባት አፈር ላይ የሌሎች አገራት ዜጎች ተደላድለው ተቀመጡ፣ የዕለት እንጀራችንን ነጠቁ፣ ሃብት አፈሩ በሚል ሰበብ የተበሳጩ ደቡብ አፍሪካውያን ጎበዛዝት፣ በቁጣ ነድደው ወደ አደባባይ ወጡ። ቆንጨራቸውን ይዘው፣ ከላይ እስከ ታች ታጥቀው፣ ደም ሊያፈስሱ ተንደረደሩ፡፡
ለአመታት ጊዜ እየጠበቀ ሲፈነዳ የቆየውና ከወራት በፊት በሶዌቶ ዳግም የተቀሰቀሰው የጥላቻ መንፈስ ያደረባቸው እነዚህ ደቡብ አፍሪካውያን፣ በኢስፒንጎና ቻትስዎርዝ ከተሞች የሚገኙ የውጭ ዜጎችን ሱቆችና ግሮሰሪዎች በእሳት አነደዱ፡፡ ከእሳት የተረፉትም ዘረፉ፡፡
ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ፤ ጥፋቱን ለማስቆም የፓርላማ አባላትንና ሚኒስትሮችን የያዘ ግብረ ሃይል አቋቁመው እየሰሩ እንደሚገኙ ቢያስታውቁም፤ ይህ ነው የሚባል ለውጥ አልታየም፡፡ የአገሪቱ ፖሊስ ይህንን የጥፋት እሳት ለመግታት ደፋ ቀና ሲል ቢሰነብትም አልተሳካለትም፡፡ ቁጣና ጥፋቱ በያቅጣጫው መሰራጨቱን ቀጠለ፡፡ ወደ ክዋማኩታ... ወደ ኡምላዚ... ወደ ሌሎች የደቡብ አፍሪካ ከተሞች ተዛመተ፡፡ አገሬው ስደተኛውን እያሳደደ ማጥቃቱን ገፋበት፡፡ ሰርቼ ሰው እሆናለሁ ያሉ በሺዎች የሚቆጠሩ የሌሎች አፍሪካ አገራት ስደተኞች፣ ከጥፋቱ ለማምለጥ በየአቅጣጫው ተበተኑ፡፡ ላባቸውን አፍሰው ያፈሩትን ሃብትና ንብረት ታግለው ለማዳን የደፈሩ ጥቂቶችም፣ ከሞት ጋር ተፋጠጡ፡፡
የአገሪቱ ፖሊስ ግን፣ ራሳቸውን ከጥቃት ለመከላከል በቡድን የተንቀሳቀሱትን እነዚሁ ስደተኞች ሊያግዛቸው አልፈለገም፡፡ ይልቁንም ባለፈው ረቡዕ በአስለቃሽ ጭስ በተናቸው፡፡
ባለፈው ሳምንት አርብ፣ ምሽት ላይ...
የውጭ አገራት ስደተኞችን ለማጥቃት የወጡት ደቡብ አፍሪካውያን፣ ፊታቸውን ከደርባን በስተ ደቡብ ወደምትገኘው ኡማልዚ ከተማ አዞሩ፡፡ በከተማዋ የሚገኙ የስደተኞች ሱቆችን በእሳት አቀጣጠሉ፡፡ በሱቆቻቸው ውስጥ እያሉ በድንገተኛው የእሳት ወላፈን ከተለበለቡት የውጭ አገራት ስደተኞች መካከል፣ ሁለቱ ወንድማማች ኢትዮጵያውያን ነበሩ፡፡ አንደኛው በደረሰበት ቃጠሎ ለሞት ተዳርጓል፡፡
የያዝነው ሳምንትም በደቡብ አፍሪካ ለሚገኙ ስደተኞች የመከራ ሆኖ ቀጥሏል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ ምሽት...
ይባስ ብሎም የአገሪቱ መሪ ጃኮብ ዙማ ወንድ ልጅ፣ የውጭ አገራት ዜጎችን በጉያችን ይዘን የምናባብልበት ጊዜ ማብቃት አለበት ሲል አፍ አውጥቶ በመናገር ጥፋቱን የባሰ የሚያቀጣጥል ድርጊት ፈጸመ፡፡ የፕሬዚዳንቱ ልጅ ይሄን ባለባት ምሽት፣ አገሬው ለባሰ ጥፋት ታጥቆ ተነሳ፡፡ የደቡብ አፍሪካዋ የወደብ ከተማ ደርባን ጎዳናዎች፣ ስደተኞችን ለማጥፋት ቆርጠው በተነሱ፣ እሳትና ስለት በታጠቁ ዜጎች ተጥለቀለቁ፡፡ በከተማዋ ጥፋት ሆነ፡፡
በርካቶች ራሳቸውን ከሞት ለማዳን ድቅድቁን ጨለማ እየሰነጠቁ፣ እግራቸው የመራቸውን አቅጣጫ ተከትለው ሮጡ፡፡ አሶሼትድ ፕሬስ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፤ ከሁለት ሺህ በላይ ስደተኞች በፖሊስ ጊዚያዊ መጠለያ ካምፖች፣ በስታዲየሞችና በተለያዩ የመንግስት ተቋማት ተጠለሉ፡፡
በዚህ የጥፋት ዘመቻ፣ ሰሞኑን ብቻ የ14 አመት ዕድሜ ያለውን ብላቴና ጨምሮ ሁለት የውጭ አገራት ዜጎችና 3 ደቡብ አፍሪካውያን ለህልፈተ ህይወት ተዳርገዋል፡፡ ፖሊስም በዚህ የጥፋት ዘመቻ ተካፍለዋል ያላቸውን 74 ያህል ሰዎች በቁጥጥር ውስጥ ማዋሉን አስታውቋል፡፡
በደቡብ አፍሪካ የኢትዮጵውያን ኮሚኒቲ መሪ ኤፍሬም መስቀሌን ጠቅሶ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ባለፈው ማክሰኞ እንደዘገበው፣ ባለፈው አርብ ሱቁ በእሳት የጋየበትን ግለሰብ ጨምሮ 3 ኢትዮጵያውያን በጥቃቱ ህይወታቸው አልፏል፡፡
ይህንን የዘረኝነትና የጥፋት ዘመቻ ለመቃወም ያለመና 10 ሺህ ያህል ሰዎች የተሳተፉበት ሰልፍ በደርባን ከተማ ተካሂዷል። ማላዊ ባለፈው ረቡዕ በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ዜጎቿን ለማውጣት መዘጋጀቷን ስትገልጽ፣ ሞዛምቢክም በበኩሏ፤ ከደቡብ አፍሪካ በሚያዋስናት ድንበር አካባቢ የስደተኞች መሸጋገሪያ ካምፕ ማዘጋጀቷን አስታውቃለች፡፡
እ.ኤ.አ በ2008 ሶዌቶ ውስጥ በተቀሰቀሰ ተመሳሳይ ጥቃት፣ ከ62 በላይ የሌሎች አገራት ዜጎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ከሰሞኑ የተከሰተውን ጥፋት ያቀጣጠለው ዝዌሊቲኒ የተባሉ የዙሉ ንጉስ የተናገሩት ንግግር ነው እንደተባለ ጠቁሟል፡፡
እኒሁ ተሰሚነት ያላቸው ንጉስ ባለፈው ወር ስደተኞች ወደየአገራቸው መመለስ አለባቸው ብለው ተናግረዋል በሚል ወቀሳ እየቀረበባቸው እንደሆነ ዘገባው ገልጾ፣ ይሄም ሆኖ ንጉሱ ግን እንዲህ ብለው አለመናገራቸውን በመግለጽ፣ ወቀሳውን ማጣጣላቸውን አክሎ አስታውቋል።
በተለይም ኢትዮጵያውያንና ሶማሊያውያንን ታላሚ አድርጎ የተጀመረው የዘረኝነት ጥቃት፣ አሁን ወደ ሁሉም የአፍሪካ አገራት ስደተኞች መስፋፋቱን የዘገበው ቪኦኤ፤ አገሬው የስደተኞቹን ንብረት በመዝረፍና በእሳት በማጋየት እንዲሁም በጭካኔ በመደብደብ ተግባሩ እንደገፋበት አመልክቷል፡፡
የደቡብ አፍሪካ መንግስት ጥቃቱን ያወገዘ ሲሆን ባለፈው ማክሰኞ የተለያዩ ሚኒስትሮች ንግግር አድርገዋል፡፡ የአገሪቱ ፖሊስ ሚኒስትር ናቲ ንህሌኮ፣ጥቃቱ አፍሪካውያን የራስ ላይ ጥላቻቸውን ያንጸባረቁበት መንገድ ነው ማለታቸውን News24.ዘግቧል፡፡
“አንዳንዶቻችን የውጭ ዜጎች ጥላቻ ነው ብለን ለማሰብ ተቸግረናል፡፡ የተወሰነ የፖለቲካ ችግርን የሚወክልም ይመስለኛል፡፡ የአውስትራሊያ ዜጎች በመንገድ ላይ ሲሳደዱ አታዬም፤ እንግሊዞች መንገድ ላይ ሲሳደዱ አታዩም፡፡” ብለዋል የፖሊስ ሃላፊው፡፡
እሳቸው እንዲህ ይበሉ እንጂ ፓኪስታኖችና ባንግላዲሾች ጥቃት እንደተፈጸመባቸው የሚያመለክቱ ዘገባዎች አሉ፡፡
የመከላከያ ሚኒስትሩ ኖሲቪዌ ማፒሳ-ንኳኩላ በበኩላቸው፤ “የውጭ ዜጎች በመሆናቸው ብቻ ንጹሃን ላይ ጥቃት ከሚፈጽሙ ወገኖች ጋር ደቡብ አፍሪካውያን መተባበር የለባቸውም” ብለዋል፡፡

ኤምባሲው በጥቃቱ ማዘኑን ገልጿል
“ኢትዮጵያውያን ለደቡብ አፍሪካ ህዝብ ሲያደርጉ የነበረውን ድጋፍ አሁን መጠቀሚያ ሊያደርጉት አይገባም”  -  (የፕሬዚዳንቱ ልጅ)
“ከደቡብ አፍሪካ አመራሮች ጋር እየተገናኘን ችግሩን ለመፍታት እየሰራን ነው”  - (ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም፤ የውጭ ጉዳይ ሚ/ር)

ሰሞኑን በደቡብ አፍሪካ በሚገኙ ኢትዮጵያውያን ላይ እየተወሰደ ያለው የጥቃት እርምጃ ተባብሶ የቀጠለ ሲሆን በርካታ ኢትዮጵያውን ስደተኞች የጥቃቱ ሰለባ እየሆኑ መምጣታቸውን ምንጮች ጠቆሙ፡፡ ድርጊቱን የሚቃወሙ ሰላማዊ ሰልፎች እየተካሄዱ ሲሆን ጥቃቱ አሁንም እልባት አለማግኘቱንና ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ስደተኞች በከፍተኛ ስጋት ላይ እንደሆኑ እነዚሁ ምንጮች ገልፀዋል፡፡
እስከአሁን የሶስት ኢትዮጵያውያንን ህይወት የቀጠፈውና የብዙዎችን ሰርቶ የመኖር ተስፋ ያጨለመው የሰሞኑ የደቡብ አፍሪካ ጥቃት፣ አድማሱን እያሰፋና እየተባባሰ ሄዷል የሚሉት ኢትዮጵያውያኑ፤ ጥቃቱ እንዳይፈፀም የሚያደርግና ስጋታችንን የሚቀንስ ምንም አይነት እርምጃ በአገሪቱ መንግሥትም እየተወሰደ አይደለም ብለዋል፡፡ የአገራችን መንግስት ለጉዳዩ የሰጠው ትኩረት አነስተኛ ነው ሲሉ ወቅሰዋል፡፡
የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ ልጅ ኤድዋርድ ዙማ፤ ጥቃቱን አስመልክቶ በሰጠው ቃለ ምልልስ፤ እርምጃው አግባብ መሆኑን ጠቁሞ ጥቃቱ መወሰድ ያለበት በአፍሪካውያን ላይ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ያለምንም ህጋዊ ሰነድ በደቡብ አፍሪካ እየኖሩ ባሉ የውጪ ዜጎች ላይ ጭምር ነው። እነሱን በማባበል ጊዜ ማጥፋት አያስፈልግም፡፡ ቀደም ሲል ስለአደረጉልን ድጋፍ እናመሰግናለን፡፡ ያንን ድጋፋቸውን ግን ለአሁን መጠቀሚያ ማድረግ አይችሉም” ብሏል፡፡
“በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ የውጪ አገር ዜጎች በሙሉ ወደሚመለከተው የመንግስት አካል ሄደው መመዝገብ አለባቸው፤ ምን እናውቃለን… ISISን ወይም አልሻባብን እየረዱ ሊሆኑ ይችላሉ” ሲልም የፕሬዚዳንቱ ልጅ ተናግሯል፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ በበኩላቸው፤ በስደተኞቹ ላይ የተፈፀመውን ጥቃቅ አውግዘው “በችግራችን ወቅት ነፃነታችንን እንድናገኝ የእርዳታ እጃቸውን ዘረጉልን እንጂ አላሳደዱንም፤ ይህንንም ማስታወስ ይገባናል” ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም፣ የደቡብ አፍሪካውን ጥቃት አስመልክተው ሲናገሩ፤ በደቡብ አፍሪካ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሙሉ ጊዜውን ለጉዳዩ ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው ከአገሪቱ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትርና ከሌሎች የደቡብ አፍሪካ አመራሮች ጋር ተገናኝተው ችግሩን ለመቅረፍ እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ “ሚኒስትሯ በሁኔታው በጣም እንዳዘኑና እንዳፈሩበት ነግረውናል” ያሉት ዶ/ር ቴዎድሮስ፤ ኢትዮጵያ ለደቡብ አፍሪካውያን ቤታቸው ነች፤ በነፃነት ትግላችን ወቅት ያደረጋችሁልንን ድጋፍ አንረሳውም፤ የተቻለንን ሁሉ እናደርጋለን” ብለውናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡
እንደ ኢትዮጵያውያኑ ሁሉ ዜጎቻቸው የሰሞኑ ጥቃት ኢላማ የሆኑባቸው የዚምባቢዌና ማላዊ መንግስታት፣ በአገሪቱ እየተካሄደ ያለውን ጥቃት በማውገዝ ድርጊቱ እንዲቆም የሚጠይቅ ደብዳቤ ለአገሪቱ ኤምባሲ አስገብተዋል፡፡ በማላዊም በዚህ ጉዳይ የተሰባሰበ ቡድን የማላዊ ዜጎች የደቡብ አፍሪካ ምርቶችን ከመግዛት እንዲቆጠቡና በደቡብ አፍሪካ አየር መንገድ እንዳይጠቀሙ ጠይቋል፡፡  
በሌላ በኩለ፤በኢትዮጵያ የደቡብ አፍሪካ ኢምባሲ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ፣ የአገሪቱ ፖሊስ ዜጎቹንና የውጭ አገራት ዜጎችን ደህንነት ለመጠበቅና ጥቃትና ዝርፊያ የሚፈጽሙ ህገወጦችን በቁጥጥር ስር ለማዋል እየሰራ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡ የአገሪቱ መንግስት በውጭ አገራት ዜጎች ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት ለማስቆምና ጸጥታን ለማስፈን የተቀናጀ ርብርብ እያደረገ እንደሚገኝም ጠቁሟል፡፡ ይህም ሆኖ ከችግሩ ስፋት አንጻር የበለጠ የተቀናጀና ዘላቂነት ያለው ስራ መስራት የሚገባ መሆኑ ስለታመነበት አዲስ አቅጣጫ እየተቀየሰ መሆኑንም ገልጧል፡፡
ደቡብ አፍሪካውያን በታሪክ አጋጣሚ ከአገራቸው ወጥተው በኢትዮጵያና በሌሎች የአፍሪካ አገራት ይኖሩ እንደነበር ያስታወሰው መግለጫው፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ለደቡብ አፍሪካ የነጻነትና የአመራር ንቅናቄዎች ያደረገውን ድጋፍ ዛሬም በክብር እናስታውሰዋለን ብሏል፡፡
የሁለቱ አገራት ታሪካዊ ትስስር ለወደፊትም ይቀጥላል፤ ለአፍሪካ ልማት እውን መሆን የጀመርነው የጋራ ጥረትም ተጠናክሮ ይቀጥላል ያለው ኢምባሲው፣ በጥቃቱ ህይወታቸውን ላጡ ዜጎች ቤተሰቦች የተሰማውን ሃዘን ገልጾ፣ የቆሰሉትም በቶሎ እንዲያገግሙ ያለውን መልካም ምኞት ገልጧል፡፡

የአለም ባንክ ቡድን አባል የሆነው ኢንተርናሽናል ፋይናንስ ኮርፖሬሽን (IFC) ተቀማጭነቱ በኢትዮጵያ ለሆነው አፍሪፍሎራ ግሩፕ የተባለ የአበባ አምራች ኩባንያ ማስፋፊያ የሚውል የ90 ሚሊዮን ፓውንድ (2ቢ.880ሚ. ብር ገደማ) የገንዘብ ብድር ሊሰጥ መሆኑን አስታወቀ፡፡
ከ9ሺህ በላይ ሰራተኞች ያሉት አፍሪፍሎራ ከአለም ባንክ በሚያገኘው የገንዘብ ብድር የአበባ ምርቱን 60 በመቶ ለማሳደግ፣ ውሃን መልሶ ለመጠቀም የሚያስችል ቴክኖሎጂ ለመገንባት፣ የፈጠረውን የስራ ዕድል ከ50 በመቶ በላይ ለማሳደግና ሌሎች የማስፋፊያ ስራዎችን ለማከናወን እንደሚያውለው ተቋሙ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
አፍሪፍሎራ በአበባ ምርት ዘርፍ የስራ ዕድል በመፍጠር በኢትዮጵያ ቀዳሚው እንደሆነ የጠቆመው የኢንተርናሽናል ፋይናንስ ኮርፖሬሽን መግለጫ፣ በቀጣይም አለማቀፍ የአካባቢና የማህበራዊ ዘላቂነት መስፈርቶችን ባሟላ መልኩ ምርቱን ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝ ጠቁሟል፡፡
በዝዋይ አካባቢ በሚገኘው የኩባንያው ዋና እርሻ እስከ 40 ሺህ የሚደርሱ ሰዎችን በቀጥታ፣ ከ100 ሺህ በላይ የሚሆኑትን ደግሞ በተዘዋዋሪ ተጠቃሚ እያደረገ  ሲሆን ትምህርት ቤቶችን፣ ሆስፒታልና ስቴዲየም በመገንባት ማህበራዊ ሃላፊነቱን እየተወጣ እንደሚገኝም አስታውቋል፡፡
ኢንተርናሽናል ፋይናንስ ኮርፖሬሽን ባለፈው የፈረንጆች የበጀት አመት ከሰሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገራት ለሚከናወኑ የግብርና ቢዝነስ ፕሮጀክቶች 686 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉንም መግለጫው አክሎ አስታውቋል፡፡

ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማት ተዘጋጅቷል
ዕጣ የደረሰው በዱባይ የንግድ ትርኢት ይሳተፋል

ታላቱ ሩጫ በኢትዮጵያ ከኢስት አፍሪካ ቦትሊንግ ኩባንያ (ኮካኮላ) ጋር በመተባበር ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ ሲያካሂድ የነበረውን የኮካኮላ የጎዳና ላይ ውድድር በ “ዳሳኒ የጎዳና ሩጫ” መተካቱን አስታወቀ፡፡ በቅርቡ በሚካሄድ የጐዳና ሩጫ ላይ ላሸነፉ ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማት ተዘጋጅቷል ተብሏል፡፡
የሩጫው አዘጋጆች ከትናንት በስቲያ በሰጡት መግለጫ፤ ዳሳኒ ውሃ ዓለም አቀፍ የጥራት ደረጃ ያለው የኮካኮላ ምርት መሆኑን ጠቅሰው፣ ውድድሩ ከስም ለውጥ በስተቀር አራት ዓመት ሲካሄድ ከቆየው ውድድር ጋር ተመሳሳይ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
ከዚህ ቀደም ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ 15ሺህ ተሳታፊዎች የተሳተፉበት ትልቅ የጐዳና ላይ ውድድር ማካሄዱን ጠቅሰው ዘንድሮ በሁለቱም ፆታ በሚካሄደው ውድድር 18ሺ ያህል ራጮች ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡
በመጪው ሰኔ 7 በዳያስፖራ አደባባይ ለሚካሄደው ውድድር ሰኞ ሚያዝያ 12 ቀን ምዝገባ እንደሚጀመር ጠቅሰው ሩጫውም 7.5 ኪ.ሜ ለጤና ሯጮች፣ 15 ኪ.ሜ ደግሞ ለአትሌቶች እንደሚሸፍን የተገለፀ ሲሆን አሸናፊዎች እስካሁን በኢትዮጵያ ታሪክ ለሯጮች ተሰጥቶ የማያውቅ የገንዘብና የቁሳቁስ ሽልማት እንደሚሸለሙ አስታውቀዋል፡፡
በወንድና በሴት ምድብ ተከፍሎ በሚካሄደው ውድድር፤ ከ1ኛ እስከ 10ኛ ለሚወጡ ተወዳዳሪዎች 285 ሺህ ብር የተዘጋጀ ሲሆን በሁለቱም ፆታ 1ኛ የሚወጣ 60ሺ ብር፣ 2ኛ 30 ሺህ ብር፣ 3ኛ 20,500 ብር እንደሚሸለም ታውቋል፡፡ በውድድሩ ለሚሳተፉ ተወዳዳሪዎች በ2008 በዱባይ በሚካሄደው የንግድ ትርዒት ለመሳተፍ የሚያስችል የዕጣ ዕድሎች የተዘጋጁ ሲሆን ዕጣው የደረሰው ተወዳዳሪ የደርሶ መልስ ቲኬትና የሁለት ቀን ወጪ እንደሚሸፈንለት ተጠቁሟል፡፡ የላፕቶፕና የሞባይል ቀፎ ዕጣ ዕድሎችም እንደተዘጋጁ ታውቋል፡፡

ሲኒማ ቤቱ ህገወጥ የንግድ አሰራርን ይከተላል ተብሏል

የንግድ ውድድርና የሸማቾች ጥበቃ ባለስልጣን አቃቤ ህግ፤ በሴባስቶፖል ኢንተርቴይንመንት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ላይ ክስ መሰረተ። ክሱ የተመሰረተውና የታየው ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ረፋድ ላይ በባለስልጣኑ አስተዳደር ችሎት ሲሆን የባለስልጣኑ አቃቤ ህግ ሴባስቶፖል በፈጸመው ፀረ ውድድር  የንግድ አሰራር ምክንያት ክሱ እንደተመሰረተበት በክስ ቻርጁ አመልክቷል፡፡
ሴባስቶፖል ክስ የተመሰረተበት ኤግዚቢሽን ማዕከል በሚገኘው ሲኒማ ቤቱ አዳዲስ ፊልሞችን ለማሳየት የሚመጡ ፕሮዲዩሰሮችን ፊልሞቻቸው የሚታዩት ኢዮሃ ሲኒማ ላለማሳየት የሚስማሙ ከሆነ ብቻ እንደሆነ በመግለፅና በፊልም ፕሮዲዩሰሮች ላይ ጫና በማሳደር ተገቢ ያልሆነ የንግድ አሰራር እያካሄደ በመሆኑ ነው ይላል የክስ ቻርጁ፡፡
የሴባስቶፖል ኢንተርቴይንመንት ድርጊት በአቅራቢያው የሚገኘው ኢዮሃ ሲኒማ በገበያው የፊልም አቅርቦት እንዳያገኝና ተወዳዳሪ ሆኖ እንዳይቀጥል ብሎም ከገበያ እንዲወጣ የሚያደርግ ፀረ-ውድድር የንግድ አሰራር እንደሆነ በክስ ቻርጁ ያተተው የባለስልጣኑ አቃቤ ህግ፤ ድርጊቱም የፌደራል የንግድ ውድድርና የሸማቾችን አሰራር መብት አዋጅን የሚቃረን በመሆኑ ይህን የሚያደርግበት ምክንያት ምን እንደሆነ ተከሳሹ ድርጅት መልስ ይዞ ለሚያዚያ 8 እንዲቀርብ ቀጠሮ የሰጠ ቢሆንም በዕለቱ የሴባስቶፖል ሲኒማ ባለቤት አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ “ጊዜው አጥሮኛል” በሚል ምክንያት መልሱን ይዞ አልቀረበም፡፡ በእለቱ ተሰይሞ የነበረው የባለስልጣኑ አስተዳደር ችሎት፤ ተከሳሹ ድርጅት መልሱን ይዞ እንዲቀርብ ለሰኔ 1 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
የኢዮሃ ሲኒማ ባለቤትና ዋና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ አዩ ዓለሙ፤ ሴባስቶፖል ባደረሰባቸው ጫና ላለፉት ሁለት ዓመታት በፊልም እጥረት ከፍተኛ ኪሳራ እንደደረሰባቸው ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል። “እስከዛሬም ሲኒማ ቤቱን ያልዘጋነው በአንዳንድ ደፋርና የመጣው ይምጣ ብለው ፊልማቸውን ኢዮሃ በሚያስገቡ ፕሮዲዩሰሮች ብርታት ነው” ያሉት ሥራ አስኪያጇ ጉዳዩ እዚህ ደረጃ ላይ እንዳይደርስ ላለፉት ሁለት ዓመታት ቢታገሱም እንዳልተሳካ ገልፀዋል፡፡
የሴባስቶፖል ሲኒማ ባለቤት አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመን ለማነጋገር በተደጋጋሚ ብንደውልም ስልኩ ባለመነሳቱ ሃሳባቸውን ለማካተት አልቻልንም፡፡

በማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ ትኩረት በማድረግ በየሳምንቱ ቅዳሜ ለንባብ የምትበቃው “ፍቱን” መጽሄት ከህትመት ታገደች፡፡ በአገሪቱ የሚገኙ የግልም ሆነ የመንግስት ማተሚያ ቤቶች መፅሔቷን እንዳያትሙ ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡
የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ባስተላለፈው መልዕክት የመፅሄቷን አሳታሚ አቶ ፍቃዱ በርታን ለጥያቄ ቢፈልጓቸውም ሊያገኟቸው አለመቻላቸውን ጠቁሟል፡፡ አሳታሚዎቹ፤ ከመንግስት ደረሰኞች ጋር ተመሳሳይ የሆኑ ደረሰኞችን በማሳተም ህገወጥ ስራ ሲሰሩ ተደርሶባቸዋል ያለው የባለስልጣኑ መግለጫ፤ በዚህ ምክንያትም መፅሄቷ ከህትመት ውጪ እንድትሆን ለማድረግ የሚያስችል የፍርድ ቤት ማገጃ ማውጣታቸውንና የትኛውም ማተሚያ ቤት መፅሄቷን ከማተም እንዲቆጠብ አሳስበዋል፡፡
“ፍቱን” መፅሄት በማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ አተኩራ በየሳምንቱ ቅዳሜ ለንባብ የምትበቃ መፅሔት ነበረች፡፡

ተመላሽ ኢትዮጵውያኑ በማቆያ ውስጥ ተቀምጠው ክትትል እየተደረገባቸው ነው
የበሽታው ምልክት የታየባቸው ሰዎች ወደ አገር ውስጥ አይገቡም ተብሏል፡፡
በሽታው ወደ አገር ውስጥ ቢገባ ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር የሚያስችሉ ሁኔታዎች ተመቻችተዋል፡፡

በምዕራብ አፍሪካ አገራት በድንገት ተከስቶ ለሺዎች ሞት ምክንያት የሆነውና ዓለምን ስጋት ላይ የጣለው የኢቦላ በሽታ አሁንም ሥጋት መሆኑ አላበቃም። በበሽታው ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖች ለመርዳት በሽታው ወደተከሰተባቸው አገራት ሄደው ለወራት የቆዩት ኢትዮጵያውያን ኮንትራታቸው በመጠናቀቁ ወደ አገራቸው እየተመለሱ ነው፡፡ ተመላሽ ኢትዮጵያውያኑ ለኢቦላ ክትትልና ቁጥጥር በተዘጋጁት የማቆያ ማዕከላት ውስጥ ሆነው ክትትል እየተደረገባቸው እንደሆነ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡
ሚኒስቴር መ/ቤቱ ኢቦላን አስመልክቶ ባዘጋጀው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲቲዩት ምክትል ዳይሬክተር ዶክተር ዳዲ ጂማ እንደተናገሩት፤ ኢቦላ የዓለም ስጋትነቱ እንደቀጠለ መሆኑን ጠቁመው የስጋቱ መጠን ቀደም ብሎ ከነበረው የተለየ አለመሆኑንና ኢትዮጵያ እስከአሁን ድረስ ከበሽታው ነፃ መሆኗ መረጋገጡን ገልፀዋል፡፡ በሽታው በአገሪቱ ቢከሰት እንኳን ለመቆጣጠርና ለመከላከል የሚያስችል በቂ ዝግጅት መደረጉን የጠቆሙት ምክትል ዳይሬክተሩ፤ በሽታውን በቀላሉና በፍጥነት ለመለየት የሚያስችሉ ዘመናዊ መሳሪያዎች ግዥ መፈፀሙንም ገልፀዋል፡፡
በኢቦላ ወደተጠቁ አገራት በተለያዩ መንግስታዊ ባልሆኑ ተቋማት አማካኝነት ለስራ የሄዱ ኢትዮጵያውያን የሥራ ኮንትራታቸውን አጠናቀው ወደአገራቸው እየተመለሱ መሆኑን የተናገሩት ዶ/ር ዳዲ፤ እነዚህ ተመላሽ ኢትዮጵያውያን ለሥራ በቆዩባቸው ጊዜያት ለበሽታው ሊጋለጡ የሚችሉበት አጋጣሚ ሰፊ በመሆኑ ተመላሾቹ በኢቦላ ክትትል ማዕከል ውስጥ እንዲቆዩ በማድረግ ክተትልና ጥበቃ እየተደረገላቸው መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የበሽታው ምልክት የታየባቸው ደግሞ ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ በመግታት እዚያው ባሉበት ቦታ ላይ ክትትልና ምርመራ እንደሚደረግላቸው ጠቁመው በዚህም በሽታው ወደ አገር ውስጥ እንዳይገባ ከፍተኛ ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በበሽታው ወደተጠቁ አገራት በመንግስት የተላኩ በጎ ፈቃደኛ ባለሙያዎችም በቅርቡ የቆይታ ጊዜያቸውን አጠናቀው እንደሚመለሱና በእነሱም ላይ ተመሳሳይ ክትትል እንደሚደረግ ዶ/ር ዳዲ ጨምረው ገልፀዋል፡፡