Administrator

Administrator

   ሞሓ የለስላሳ መጠጦች ፋብሪካ፣ ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል አንድ ሚሊዮን ብር ግምት ያለው ሁለተኛ አምቡላንስ በዕርዳታ ሰጠ፡፡ ርክክቡ የተከናወነው መንግሥት ለመቄዶንያ በነፃ በሰጠውና አያት ኮንዶሚኒየም አጠገብ በሚገኘው 30ሺ ካ.ሜ ቦታ ላይ ሲሆን በስፍራው 5 ብሎክ ቤቶች ተሰርተው ኮተቤ የነበሩ 350 ተረጂዎች ገብተውበታል፡፡
በአያት ኮንዶሚኒየም አጠገብ የሚሰራው የመቄዶንያ አረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል፤ ከ300 ሚሊዮን ብር በላይ የሚፈጅ ስለሆነ፣ የኮንስትራክሽን ድርጅቶች ኤክስካቫተር፣ ሎደር፣ ሚክሰር፣ ሲኖትራክ፣ የመሳሰሉትን ለተወሰነ ሰዓት ወይም ለአንድ ቀን ይዘው በመምጣት በሕዝብ ድጋፍ የሚሰራው ማዕከል ግንባታ አካል እንዲሆኑ መቄዶንያ ጠይቋል፡፡
“አገር በቀሉ መቄዶንያ እስካሁን እየተንቀሳቀሰ ያለውና አዲሱ ማዕከልም የሚሰራው በኢትዮጵያውያን በጎ አድራጎት ስለሆነ ለማዕከሉ ግንባታ ገረጋንቲ፣ የምግብ ማብሰያ እንጨት (የቤት ፍራሽ) ብሎኬት፣ አሸዋ፣ ጠጠር፣ ሚስማር፣ ቆርቆሮ የመሳሰሉትና የሙያ እገዛም በጣም ስለሚያስፈልገን፣ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ወደ ማዕከሉ መጥተው በመጎብኘትና የጎደለውን በማሟላት፣በማዕከሉ ግንባታ አሻራቸውን እንዲያሳርፉ እንጠይቃለን” ብሏል፡፡
“ይበል ኢንዱስትሪያል፤ለመቶ ሰዎች በነፃ በብረት ተገጣጣሚ ቤት እየሰራ ነው፡፡ ቤቱን፣ በ3 ወር ሰርተው እንደሚያስረክቡን ነግረውናል፡፡ የአንቡላንስ ርክክብ ስነ ስርዓቱ የተከናወነበትን 4 ድንኳኖች በነፃ የሰጠን ልዩ የድንኳን ሽያጭና አከራይ ድርጅት ነው፡፡ ሌሎችም ያላቸውን ለአረጋውያኑ እንዲለግሱ እንጠይቃለን፡፡ ዳይፐር፣ ሞዴስ፣ ቅባት … ያስፈልገናል፡፡ በማዕከሉ ያሉት ብዙዎቹ የአዕምሮ ሕሙማን ናቸው፡፡ ሞዴስና ዳይፐር ሲታሰርላቸው ይቀዳሉ፣ አውልቀውም ይጥላሉ፡፡
 ያገለገሉ የቤት ዕቃዎች፣ ፖፖ፣ መዘፍዘፊያ፣ የሚገፋ ወንበር (ዊል ቸር) አልጋ፣ ፍራሽ፣ … በጣም ስለሚያስፈልጉን፣በተረጂዎቹ ስም እንጠይቃለን” ሲል ማዕከሉ ተማፅኗል፡፡
የአንቡላንሱን ቁልፍ ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል መስራችና ማኔጂንግ ዳይሬክተር ለአቶ ቢኒያም በለጠ ያስረከቡት የሞሓ ለስላሳ መጠጦች ፋብሪካ የማርኬቲንግ ኃላፊ አቶ ማሩ ሞላ፤ባዩት ነገር ከልብ መደሰታቸውን ገልጸው ወደፊትም አስፈላጊ በሆነው ነገር ሁሉ ከማዕከሉ ጎን እንደሚቆሙ እንዲያረጋግጡ መልዕክት እንደተሰጣቸው ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት መቄዶንያ፤ ምንም ጧሪና ደጋፊ ለሌላቸው ከአንድ ሺህ በላይ አረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን ምግብ፣ ልብስ፣ መጠለያ፣ ሕክምናና የቤተሰብ ፍቅር እየሰጠ እንክብካቤና ድጋፍ እያደረገ መሆኑን የገለፁት አቶ ቢኒያም፤በዕለቱ በስጦታ የተረከበው ሁለተኛ አንቡላንስ፣ በጎዳና ላይ የወቀዱትን ወገኖች ለማንሳትና ያሉትንም ተረጂዎች ወደ ሆስፒታል ለማድረስ ትልቅ እገዛ እንደሚያደርግ ጠቅሰው፣ለፋብሪካውና ለባለቤቱ ለሼሕ መሐመድ አላሙዲ ከፍተኛ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

ፈረንጆች Good News and Bad News የሚሉት አላቸው፡፡ ደግ ወሬና ክፉ ወሬ
እንደማለት ነው፡፡ ይኸንን የተንተራሰ የአንድ ሀኪምና የታካሚው ንግግር የዛሬ ተረታችን ነው፡፡
እነሆ፡-
ሐኪም - እንኳን ደህና መጣህ ወዳጄ፡፡
ታካሚ - እንኳን ደህና ቆዩኝ ሐኪም፡፡
ሐኪም - ዛሬ፤ደግም ክፉም ወሬ ይዤ ነው የጠበቅሁህ፡፡
ታካሚ - ግዴለም ሐኪም፤ከክፉው ወሬ ይጀምሩልኝ፡፡
ሐኪም - መልካም፡፡ ግን ቅር እንዳይልህ፡፡
ታካሚ - በጭራሽ ቅር አልሰኝም፡፡
ሐኪም - እንግዲያው ልንገርህ፡፡ እህትህ በጠና ታማ፣ኮማ ገብታ፣እያጣጣረች ናት፡፡
ታካሚ - ይሁን እግዜር ካመጣው ምን ይደረጋል? ሌላስ?
ሐኪም - ወንድምህ ውሃ ውስጥ ሰጥሞ፣አሁን አምቡላንስ ተልኮለት እየመጣ ነው፡፡
ታካሚ - እግዚሀር ፈርዶበት ነው እንጂ ዋና ይችላልኮ! ሌላስ የሚነግሩኝ አለ?
ሐኪም - አዎ፡፡
ታካሚ - ቶሎ ቶሎ ይንገሩኝ ሐኪም!
ሐኪም - ባለቤትህ ልፈታው ነው ብላ ነግራኛለች፡፡
ታካሚ - ይሁን እንግዲህ ካመጣው ምን ይደረጋል! ሌላ አለ የሚነግሩኝ?
ሐኪም - ዛሬ በህይወት ሆነህ አንተን ማግኘቴ ገርሞኛል፡፡ ምክንያቱም ማታ ቤትህ መቃጠሉን
ሰምቻለሁ፡፡
ታካሚ - አዎ፤ ውጪ ነው ያደርኩት፡፡ ሌላስ  ምን የሚጨምሩልኝ ክፉ ወሬ አለ?
ሐኪም - ክፉውን ወሬ ጨርሻለሁ፤የቀረኝ ደጉ ወሬ ነው፡፡
ታካሚ - (በጣም ተጣድፎ) ሐኪም፤እሱን በደምብ ይንገሩኝ!
ሐኪም - አልዛይመር የሚባል በሽታ ይዞሃል፡፡
ታካሚ - ምን ማለት ነው?
ሐኪም - የማይድን በሽታ ነው፡፡ ማስታወስ የአለመቻል በሽታ ነው!
ታካሚ - ሐኪም፤በጣም ጨካኝ ነዎት፡፡ ይሄንን ነው ደግ ወሬ ብለው የሚነግሩኝ?
ሐኪም - ለምን መሰለህ እንድታውቅ ያደረኩህ?
ታካሚ - ለምንድነው ሐኪም?
ሐኪም - ምክንያቱም አሁን ከእኔ ስትለይ ያልኩህን ሁሉ ትረሳዋለህ፡፡ ለዚህ ነው ደግ ወሬ ነው
ያልኩህ!
***
የመከራና ችግሮቻችን መብዛት መርሳትን (አልዛይመርን) እንዳንመኝ ቢያደርገን መልካም ነበር፡፡
የበሽታችንን ስር ካላወቅን ሌላ በሽታ በራችንን ማንኳኳቱ አይቀሬ ነው፡፡ በሩ ሲንኳኳ ካላደመጥን
ደሞ ሌላ በሽታ አከልንበት ማለት ነው፡፡ “ሌባ!----ሌባ!” እያልን እንጮሃለን! በአደባባይ “እናሳየዋለን” እንላለን፤አንይዘውም፡፡ የጠራራ ፀሃይ ስርቆሽ፣ “የአየር ጊዜ መግዛትና” ፖሊሱ ዞር ብሎ እንዲቆይ ማድረግ፣ ፀሃይ የሞቀው እውነት ነው፡፡ ሌባውም አይያዝም፤ ፖሊሱም አይጠየቅም - መርካቶ ጉያዋ ብዙ ቢሆንም አደባባይዋ ግን ይህን ያሳየናል፡፡ የሞባይል ሌብነት፣አንድ ሌባ እንዳለው፤“የሥራ ፈጠራ እኮ ነው!” እንደ አራዶች አባባል፤ “ልማታዊ ሌብነት” መሆኑ ነው፡፡ የሴት ቦርሳ ምንተፋ ተጧጡፏል! የማን ያለህ እንበል? “በኃይለስላሴ አምላክ!” ይባል የነበረው ቀረ እንጂ ትንሽ ፋታ ይሰጥ ነበር፡፡ በ”ሕግ አምላክ”፣ ዛሬ እንኳን ወጣቱ የመንግሥት ሠራተኛም አያውቀው!
“ያባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ” የተሻለ መርህ ቃል (motto) ነው:: ቀን በቀን ከባንክ ጋር ተመሳጥሮ ከሚመዘበረው ገንዘብ አንስቶ በመሬት መልክ አገር እስከ መሸጥ ያለውን “የገበያ ውጣ-ውረድ”፣ በዓለም አቀፉ የገበያ ሥርዓት ወይስ በግሎባላይዜሽን እቅፍ ውስጥ እንደመድበው?
የታላላቅ ባለስልጣናት ወገናዊነት፣ እስከ ሰባት ቤት የኢ-ፍትሐዊ ሀብት ክፍፍል፣ የህዝብ ሀብት
ምዝበራ እንጂ የልማት ቀፎ ውስጥ የሚቀፈቀፍ የማር እንጀራ ሊባል ነው እንዴ?
ማ ባለስልጣን የማ ንግድ ድርጅት “ሼር ሆልደር” እንደሆነ ሳናውቅ ነው እንዴ ስለ ሙስና የምናወራው? የጦር አበጋዝ የንግድ ተቋራጭ የሚሆንበት አገር፣እዚሁ አኛ ዘንድ ካልሆነ የሮማ ነገስታትን ታሪክ አናመጣ?ስንቱን እንርሳ? በስንቱ “አልዛይመር” ይያዘን? ወይስ በተቋም ደረጃ የሚያም “አልዛይመር” ይኑረን?
ነገረ ስራችን ሁሉ ጥሩ ታቅዶ ነበር፡፡ ጥሩ ሥራ አመራር ተመድቦ ነበር - ታዲያ ምን ያደርጋል?
“የአፈፃፀም ችግር አለ” ይባላል፡፡ እስከ መቼ? “የአፃፀም ችግርን የሚያይ አገር አቀፍ ኮሚሽን”
ይቋቋም እንዴ? የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ከኮሌጅነት እስከ ዩኒቨርሲቲነት በሸፍጥ እስከመሰየም
ድረስ ከፍተኛ ሙስና ውስጥ ሲዘፈቅ ስናይ፣ እንዲህ በይፋ ምንም ሳያሟላ የተመረቀ ተማሪ ማስረጃ
አቅርብ ሲባል፤ እስከ መፋጠጥ ሲደርስ፣ ያስተማረው ዩኒቨርሲቲ እንዴት እንደተቀበለው ግራ  እስከመጋባት ሲደርስ ስናስተውል፤ “እዚህ አገር ስንቱን እንርሳ?” “በስንቱ አልዛይመር ይያዘን?”
ያሰኛል፡፡
በእውነት አገራችን እድገት ካላት፣የእድገቷ ታማሚ ናት ወይም ምርኮኛ ናት!
የቤቶች አስተዳደር ጣጣ ችግር ዛሬም ችግር ነው፡፡ ገቢዎችና ተገልጋዩ ነጋዴ ህብረተሰብ ዛሬም እንዳልተማመኑ፣ዛሬም እንዳልተዋደዱ ናቸው፡፡ የአደጉ አገሮችን የገቢዎች አስተዳደር ሥርዓት እንመኛለን፡፡ ግን በምን አንጀት? በማን ትከሻ? በምን እምነት?
የሰብዓዊ መብት ችግርና የመልካም አስተዳደር ጉድለት፣ይተሳሰር ዘንድ መከራችንን ስናይ ሰንብተናል፡፡ ግጭትን ባልተመጣጠነ ኃይል መፍታት የመልካም አስተዳደር የሁሉ-የሁሌ-ፍቱን  መድሐኒት (Panacea) አድርገን መውሰዱ በውል መጤን አለበት፡፡ ፍርድ ቤቶች ከሹማዊና ወገናዊ ሥርዓት መፅዳት አለባቸው፡፡ ስህተታችንን ስንሰማ አለመደናገር ቁልፍ ነገር ነው፡፡ በርትቶ ማረም ነው መድሐኒቱ! ችግሮቻችን አያሌ ናቸው፡፡ አልዛይመርም ቢይዘን አንረሳቸውም፡፡ ከሁሉም የሚልቀው “ችግር የለብንም፡፡ ይሄን ያህል ፐርሰንት አድገናል! የዓለም ባንክ ይሄን ይሄን ብሎናል፡፡” የሚለው ነገር ነው፡፡ “ይሄን አውጀናል፤ይሄን በጀት በጅተናል፤በሚቀጥሉት ይሄን ያህል አመታት ጉድ እናያለን” የሚለው ምኞትና ተስፋም፣ ዜጐች ብዙ ፍሬ እንድንጠብቅ ልባችንን ያንጠለጥለናል፡፡ “መሬት የያዘው የቱ ነው?” ማለታችን ግን አይቀርም፡፡ “የማያስተኛ ነገር ነግረውን ተኝተው አደሩ” የምንለው ያኔ ነው!

   በጋሻው መርሻ የተዘጋጀው በዕውቁ የቀዶ ጥገና ሃኪምና ፖለቲከኛ ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ህይወት ላይ የሚያጠነጥነው “አንፀባራቂው ኮከብ፣ ፕ/ር አስራት ወልደየስ” የተሰኘ መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ ፀሐፊው ለመፅሀፉ የሚውሉ ግብአቶችን ለማሰባሰብ ሶስት ዓመት፣ መረጃዎቹን አጠናቅሮ ወደፅሁፍ ለመቀየር አንድ ዓመት ከሁለት ወራት እንደፈጀበት ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ ፕ/ሩ ከልጅነት ህይወታቸው ጀምሮ ስለትምህርታቸው፣ ስራቸው፣ በእስር ላይ በነበሩበት ጊዜ ስላደረጓቸው… ክርክሮች እስከ ዕድሜያቸው ፍፃሜ ድረስ ያለውን ህይወት በመፅሀፉ ለመዳሰስ ሞክሯል፡፡ ፀሐፊው ስለፕሮፌሰሩ ሙሉ ምስል ለማግኘት  ወዳጆቻቸውን፣ የስራ ባልደረቦችን ቤተሰባቸውን ያነጋገረ ሲሆን በተለያዩ ጊዜያት  የሰጧቸውን ቃለ ምልልሶች፤ የውጭና የአገር ውስጥ ሚዲያዎች ስለእሳቸው ያወጧቸውን ዘገባዎች መጠቀሙን ጠቁሟል፡፡ በ260 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ81 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

     በየዓመቱ የሚካሄደውና ዘንድሮ ለአራተኛ ጊዜ “New Trends in Art Education in Ethiopia” በሚል ርዕስ የተዘጋጀው የኪነ ጥበብ ጉባኤ ባለፈው ረቡዕና ሀሙስ ተካሄደ፡፡ ጉባኤው በዋናነት በኪነ ጥበቡ ላይ የሚታዩ ችግሮችን፣ የፖሊሲ ክፍተቶችንና መሰል ጉዳዮችን በጥናት አስደግፎ መፍትሄ ማፈላለግ ላይ እንደሚያተኩር የጉባኤው አዘጋጅ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቴአትር ጥበባት ት/ቤት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ እሸቱ ተናግረዋል፡፡ ለጉባኤው ጥናቶች እንዲቀርቡ ት/ ቤቱ ከሁለት ወራት በፊት ባደረገው ጥሪ በርካታ ጥናቶች መግባታቸውን ሃላፊው ጠቁመው ከነዚህ ውስጥ ውሃ የሚያነሱና ጥልቀት ያላቸው 15 ያህል ጥናቶች ተመርጠው መቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ ከጥናቶቹ መካከል በረዳት ፕሮፌሰር በቀለ መኮንን የቀረበው “የሥነ ጥበብ ሁለንተናዊ ጉዞ
ከየወቅቱ ጥያቄዎች አንፃር”፣ በዓለም ፀሐይ ለማ የቀረበው “የከፍተኛ ትምህርት ተቋም የጥበብ ትምህርቶች ማስተማሪያ ዘዴ (ፔዳ ጎጂ) በቴአትር ትምህርቶች ላይ ያለው ሚና” እና በምስጋናው ዓለሙ የቀረበው “በኢትዮጵያ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ቴአትር የማስተማር ፈተናዎች” የሚሉት ይገኙበታል፡፡ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፣ ተ/ፕሮፌሰር ተስፋዬ ገሰሰ አርቲስት ፍቃዱ ከበደ ወግና ፅሁፍ በማቅረብ ተሳትፈዋል፡፡፡ በአምስት ኪሎ ቴአትር ጥበባት ት/ቤት አዳራሽ በተካሄደው በዚህ ጉባኤ ላይ በኪነ-ጥበቡ ላይ ያሉትን ፈተናዎች ለመቅረፍና የትምህርት ፖሊሲው ለዘርፉ ሊሰጠው በሚገባው ትኩረት ላይ ውይይቶች እንደተካሄዱም ታውቋል፡፡

    በዶ/ር ሱባህ ኤ የሱፍ በእንግሊዝኛ የተሰናዳው “Sharing Costss Nothing” ሰሞኑን ለገበያ የዋለ ሲሆን በተለያዩ የጤና ጉዳዮች ላይ እንደሚያጠነጥን ታውቋል፡፡ መፅሀፉ በዋናነት ህብረተሰቡ በተደጋጋሚ  የሚያያቸው ነገር ግን ትኩረት ሰጥቶ ወደ ህክምና የማይመጣባቸው እንደ ስቅታ፣ ነስር፣ የመንገድ ጉዞ ህመም፣ የከፍታ በሽታ (Mountain Sikness)፣ ሀንግ ኦቨር፣ እና በጎጂ የጤና ልማዶች ላይ አተኩሮ የተዘጋጀ ነው፡፡ መፅሀፉ ለአገር ውስጥ በ45 ብር ፣ ለውጭ አገራት በ10 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡

    የገጣሚ መብራቱ መሀመድ “ሽሽት” የተሰኘ የግጥም መድበል ዛሬ ከ9፡30 ጀምሮ በሀገር ፍቅር ቴአትር ይመረቃል፡፡ በመፅሀፉ ውስጥ የተካተቱት ግጥሞች በዋናነነት ሰው ከሀገሩ፣ ከህሊናው፣ ከፖለቲካ፣ ከዓለም፣ ከፍቅር፣ ከእውነት፣ ከጥበብና ከፈጣሪው ይሸሻል ወይ?
ቢሸሽስ የት ይደርሳል፣ ማንስ ነው መጠጊያው? በሚሉት ጉዳዮች ላይ ያጠነጥናሉ ተብሏል። በምርቃት ሥነ ስርዓቱ ላይ ወጣትና አንጋፋ ገጣሚያን ስራዎቻቸውን የሚያቀርቡ ሲሆን ከመፅሀፉ የተመረጡ ግጥሞች ለታዳሚው ይቀርባሉ ተብሏል፡፡ በ83 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ30 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

የኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ብሔራዊ ማህበርና መስከረም ፕሮሞሽን በመተባበር ያዘጋጁት “አገር አቀፍ ተጓዥ የንግድ ትርኢትና ባዛር” ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ተከፈተ፡፡ “አካል ጉዳተኞችን ማሳተፍ የህዳሴው አካል ነው” በሚል መርህ የመጀመሪያውን የንግድ ትርኢትና ባዛር ሜክሲኮ አደባባይ የከፈተው ማህበሩ፤ በተለያዩ የክልል ከተሞች ለ1 ዓመት እንደሚቀጥል አስታውቋል፡፡
ከተቋቋመ 23 ዓመታትን ያስቆጠረውና በአገር አቀፍ ደረጃ 16ሺህ አባላት ያሉት ማህበሩ፤ የአካል ጉዳተኞችን መብት ለማስከበርና በሁሉም ዘርፍ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማስቻል ጥረት ሲያደርግ መቆየቱን አስታውሶ፤ አካል ጉዳተኞች አካል ጉዳተኝነታቸው ሳይገድባቸው የሚያመርቷቸውን ምርቶች ከገዢ ጋር ለማገናኘትና ለማበረታታት ባዛሩ መዘጋጀቱን የማህበሩ ሃላፊዎች ባለፈው ረቡዕ በመክፈቻ ስነ-ስርዓቱ ላይ ተናግረዋል፡፡
በንግድ ትርኢትና ባዛሩ ላይ አካል ጉዳተኖች ያመረቷቸው ቆዳና የቆዳ ውጤቶች፣ የእጅ ስራዎች፣ ቦርሳዎች፣ ቀበቶዎች፣ የሶፋ ጨርቆች፣ የህትመትና የማስታወቂያ ስራዎችና ሌሎችም እቃዎች ለእይታና ለሽያጭ እንደሚቀርቡ ተገልጿል፡፡

በምግብ ማብሰል ሙያ አለማቀፍ እውቅናን ያተረፈው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ሼፍ ማርከስ ሳሙኤልሰን፤“ፌስቱፌስ አፍሪካ; የተባለው የፓን-አፍሪካን ሚዲያ ተቋም ለሚያዘጋጀው አመታዊው የ“ፌስ ሊስት” ሽልማት በ“ግሎባል አምባሳደር አዋርድ” ዘርፍ ለሽልማት መመረጡን ተቋሙ ባወጣው መግለጫ አስታወቀ፡፡
ተቋሙ በተሰማሩበት የሙያ መስክ የላቀ ተግባር ለፈጸሙ፣ ለወጣቱ ትውልድ አዲስ መንገድን ለከፈቱና የፓን-አፍሪካኒዝምን በጎ ገጽታ  በተመለከተ በሚደረጉ ውይይቶች ተጽዕኖ ለፈጠሩ ጀግኖች በየአመቱ የሚሰጠው የ“ፌስ ሊስት” ሽልማት ዘንድሮም ለ5ኛ ጊዜ በመጪው ሃምሌ ወር መጀመሪያ ላይ ኒውዮርክ ሲቲ ውስጥ በሚካሄድ ስነስርዓት ለሼፍ ማርከስ ሳሙኤልሰንና ለሌሎች አራት ታዋቂ ግለሰቦች ይበረከታል ተብሏል፡፡
በኢትዮጵያ ተወልዶ በስዊድን ያደገውና በአሁኑ ሰዓት ነዋሪነቱ በኒውዮርክ ሲቲ የሆነው ሼፍ ሳሙኤልሰን፤በሙያው አለማቀፍ ዝናን እንዳተረፈ የገለጸው ተቋሙ፣ሬድ ሮስተር የተባለ የራሱን ሬስቶራንት ከፍቶ ትርፋማ ቢዝነስ እያከናወነ እንደሚገኝና በኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ ለሁለት ጊዚያት ያህል የ3 ኮከብ ደረጃ የተሰጠው በእድሜው ትንሹ ሼፍ መሆኑን ጠቁሟል፡፡
በዋይት ሃውስ ለኦባማ በኣለ ሲመት በተዘጋጀ የክብር የእራት ስነስርዓት ላይ በተጋባዥነት ምግብ በማብሰል የሚታወቀው ሼፍ ሳሙኤልሰን፣ ለጥቁር አፍሪካውያን የስኬት ተምሳሌት መሆኑንና በሙያው የተለያዩ ታላላቅ ሽልማቶችን ማግኘቱንም መግለጫው አስታውቋል፡፡
ለ2016 የ“ፌስ ሊስት” ሽልማት የተመረጡት ሌሎቹ ዝነኞች፣ የግራሚ ተሸላሚው ድምጻዊ ዋይክሌፍ ዣን፣ ዋይቴከር ግሩፕ የተባለው ኩባንያ ፕሬዚዳንት ሮዛ ዋይቴከር፣ የታዋቂው ኢሰንስ መጽሄት ዋና አዘጋጅ የሆነቺው ቫኔሳ ዲ ሊካ እና የኩራሞ ካፒታል ኩባንያ መስራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዋሌ አዲኦሱን መሆናቸውንም ተቋሙ አስታውቋል፡፡


   የኡጋንዳው ፕሬዚዳንት ዮሪ ሙሴቬኒ በመፈንቅለ መንግስት ስልጣኔን ለመቀማት ሲያሴሩ ደርሼባቸዋለሁ ያሏቸውን 30 ያህል የአገሪቱ ከፍተኛ የጦር መሪዎችና ባለስልጣናት ማሳሰራቸውን ተከትሎ በአገሪቱ ውጥረት መንገሱ ተዘገበ፡፡
ከአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር በመተባበር በስልጣን ላይ ያለውን መንግስት ለመጣል አሲረዋል የተባሉት የጦር መሪዎችና ባለስልጣናቱ፣ ባለፈው ሳምንት መታሰራቸውን ያስታወሰው አሶሼትድ ፕሬስ፤ ይህን ተከትሎም ድርጊቱን የተቃወሙ ታጣቂዎች በመንግስት ፖሊሶች ላይ ተኩስ መክፈታቸውንና ውጥረት መንገሱን ገልጧል፡፡
የአገሪቱ ፖሊስ ከመፈንቅለ መንግስት ሴራው ጋር ንክኪ አላቸው ያላቸውን በርካታ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትንና ደጋፊዎችን ማሰር መቀጠሉን የጠቀሰው ዘገባው፤ 12 ያህል የተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊ ታጣቂዎች፣ ኡጋንዳ ፒዩፕልስ ኮንግረስ የተባለው ፓርቲ አባል የሆኑትንና በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉትን ዳን ኦላ ኦዲያ የተባሉ ግለሰብ ለማስለቀቅ፣ባለፈው እሁድ በፖሊስ ላይ ተኩስ በመክፈት ብጥብጥ መፍጠራቸውን ጠቁሟል፡፡  
ባለፈው የካቲት ወር በተካሄደው የአገሪቱ ምርጫ የሙሴቬኒ ተፎካካሪ ሆነው የቀረቡትና የምርጫውን ውጤት በመቃወም ብጥብጥ አስነስተዋል በሚል ወደ ወህኒ የተወረወሩት ፎረም ፎር ቼንጅ የተባለው ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ዶ/ር ኪዛ ቢሲጂ፤ባለፈው ረቡዕ በአገር ክህደት ተከሰው በናካዋ ከተማ ፍርድ ቤት በቀረቡበት ወቅት፣ በአካባቢው ከፍተኛ ውጥረት ነግሶ እንደነበር ዘገባው አመልክቷል፡፡
መፈንቅለ መንግስቱን የጠነሰሱት ኪዛ ቢሲጄ የተባሉ የአንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር እንደሆኑ መነገሩን የጠቆመው ዘገባው፣ ግለሰቡ በአገር ክህደት ከተከሰሱት ቢሲጂ ጋር የጠበቀ ወዳጅነት እንዳላቸው ገልጾ፣ ቢሲጂ በመንፈንቅለ መንግስቱ ሴራ እጃቸው ሊኖርበት እንደሚችል መጠርጠሩን አስታውቋል፡፡
ቪኦኤ በበኩሉ፤ የአገሪቱ መንግስት ባለስልጣናቱን በመፈንቅለ መንግስት ሴራ ጠርጥሮ ማሰሩ በቀጣይም ከፍተኛ ብጥብጥ ሊፈጥርና አገሪቱን ወደ ከፋ ቀውስ ሊከታት እንደሚችል እየተነገረ እንደሚገኝ ዘግቧል፡፡

  ታዋቂው ማይክሮሶፍት ኩባንያ፣ሊንክዲን የተባለውን ዝነኛ የማህበራዊ ድረገጽ በ26.2 ቢሊዮን ዶላር ለመግዛት ስምምነት ላይ መድረሱን እንዳስታወቀ ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ኩባንያው በታሪኩ ከፍተኛውን ግዢ የሚፈጽምበት ነው በተባለው በዚህ ስምምነት ወደ ማህበራዊ ድረገጽ አለም በይፋ ይቀላቀላል ያለው ዘገባው፤ ማይክሮሶስፍት ሊንክዲንን መግዛቱ ከፌስቡክና ከጎግል ጋር ለሚያደርገው የቴክኖሎጂ ፉክክር ትልቅ አቅም ይፈጥርለታል መባሉንም ገልጧል፡፡
በቢዝነስ ላይ በተሰማሩ ተጠቃሚዎች ዘንድ የሚዘወተረው ሊንክዲን የማህበራዊ ድረገጽ፤ከ400 ሚሊዮን በላይ ተጠቃሚዎች እንዳሉት የጠቆመው ዘገባው፣ ማይክሮሶፍት ግዢውን እስከ መጪው ጥር ወር ድረስ አጠናቅቆ ሊንከዲንን በእጁ ያስገባል ተብሎ እንደሚጠበቅም አስታውቋል፡፡
የሊንክዲን ተጠቃሚዎች ቁጥር ባለፉት አመታት በአማካይ በ19 በመቶ እድገት በማሳየት፣ 433 ሚሊዮን ያህል መድረሱን የጠቆመው ሮይተርስ፤ በትርፋማነቱም እንደማይታማና በማይክሮሶፍት ባለቤትነት ስር መተዳደሩ የበለጠ ውጤታማ ያደርገዋል ተብሎ እንደሚታመን አስረድቷል፡፡
ማይክሮሶፍት ከአምስት አመታት በፊት ስካይፒን በ8.5 ቢሊዮን ዶላር፣ የኖኪያ የሞባይል ቀፎ አምራችነትንም በ7.2 ቢሊዮን ዶላር መግዛቱን ያስታወሰው ዘገባው፤ሁለቱ ግዢዎች በታሪኩ ከፍተኛ ወጪ ያወጣባቸው ተብለው ተመዝግበው እንደነበርም ገልጧል፡፡