Administrator

Administrator

Monday, 11 March 2024 10:32

ያ ዕለት ይናፍቀኛል !

“የዘመናት መድረክ ላይ ረዥሙን የታሪክ ጉዞ ተጉዘው ለሰው ልጆች ተስፋንና ጥበብን ይዘው ለትውልድ በመተላለፍ እንደ ውርስ የተሰጡ ቅርሶች መጻሕፍት ናቸው”  ሻምበል አፈወርቅ ዮሐንስ።
ስለ መጻሕፍት፣ ስለ ንባብ አዲሱ ባህላችን  ላወጋችሁ ነው። መጻሕፍትን በመላው አገራችን አዳርሰው የንባብ ባህልን የህዝብ ቋሚ ባህል  ለማድረግ፣ የኢትዮጵያ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻሕፍት ኤጀንሲ  በአያሌው እየተንቀሳቀሰ ነው። በዚህም እንቅስቃሴው 337916  መጻሕፍትን፣ ከ60 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ ለ590 ተቋማት ሰጥቷል። ተቋማቱ  ዩኒቨርሲቲዎች ፣ የህዝብ ቤተ መጻሕፍት፣ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችና ማረምያ ቤቶች ናቸው። መጻሕፍትም እንዴት መነበብ እንዳለባቸው ደራሲያንን ፣ ገጣሚያንን፣ የዩኒቨርስቲ መምህራንን በመጋበዝ፣ ለታዳሚዎች ልምዳቸውን እንዲያጋሩ ያደርጋል። በየክልሉ ለሚገኙ የህዝብ ቤተ መጻሕፍት ሰራተኞች ሙያዊ ስልጠና ይሰጣል። በመዲናችን ለሚገኙ መጻሕፍት ነጋዴዎች ትራንስፖርት በማመቻቸት፣ በተጋባዝዋ ከተማ የመጻሕፍት አውደ ርእይ ያዘጋጃል። በዚህም ከየከተሞቹ ባህል፣ ስፖርት ቢሮ ጋር በመቀናጀት ህዝብ አውደ ርእዩ ላይ እንዲሳተፍ ያደርጋል።
ኤጀንሲው ወሳኝ የሆኑ ዶክሜንቶችን ኦርጂናሌውን ፣ አልያም ፎቶ ኮፒዎች በማቅረብ የራሱን የዘመናት እንቅስቃሴዎች በአውደ ርእዩ ላይ ያቀርባል። በቅርቡ በአርባምንጭ ከታዩ ዶክሜንቶች መካከል አቶ ታደሰ ታቼ የተባሉ አርቆ አሳቢ ከ70 አመታት በፊት፣ በ1946 ዓ.ም በወቅቱ አገሪቱን ሲመራ ለነበረው መንግስት የጻፉት ደብዳቤ ለትእይንት ቀርቦ ነበር ፡፡ አቶ ታደሰ፤ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ አምስት ፣ አምስት ብር ቢያዋጣ እንዴት የአባይን ወንዝ መገደብ እንደሚቻል ይገልጹና፣ እርሳቸው ይህንኑ መዋጮ በወር 5 ብር በአመት 200 ብር ለመለገስ ቃል ይገባሉ። ይህ ሃሳብ ይሆን ለእነ አቶ መለስ ዜናዊ፣ ከሰባ አመታት በኋላ የህዳሴውን ግድብ መሰረት ለመጣል ያስቻላቸው ? ስል አውጠንጥኛለሁ።
 እዚያው በጉባኤው ላይ የከተሞቹ ከፍተኛ ሀላፊዎች፣ ታዳሚዎች በተገኙበት ትዕይንቱ ይጎበኛል። የከተማዋ ነዋሪዎች ይታደማሉ። በዚህም የማንበብ ፍቅር ያላቸው በደስታ የፈለጉትንና ገበያው ያቀረበላቸውን መጻሕፍት ሲሸምቱ ይስተዋላሉ።  
በቅርቡ በአገራችን “ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል!” የሚሉት ብሂል በተደጋጋሚ በመገናኛ ብዙሃን ይደመጣል። አባባሉ ሊያከራክር ቢችልም ከማንበብ የተሻለ ሰውን ሙሉ ሊያድርገው የሚችል ሙያ የለም ማለት እንችላለን። አዎን ልጆቻችንን ዩኒቨርስቲ ልከን የአንድ ሙያ ባለቤት ማድረግ እንችላለን። የህክምና ዶክተሮች ፣ ኢንጂነሮች ፣ ኢኮኖሚስቶች ወዘተ ማድረግ ይቻላል። ዓለምን በምልአት እንዲያዩዋት ግን መጻሕፍት ማንበብን ልንጨምርበት ይገባል። በዚህ ጉዳይ ላይ በእንድ ወቅት ከዶክተር ተወልደ ብርሃን ጋር ስንጨዋወት፤ “ማንኛውም ሰው የራሱ የእኔ የሚለው  ሙያ ሊኖረው ይገባል። በሙያው ላይ ዓለምን በምልአት ለማየት ታሪክንና ሥነ ጹሑፍን ሙያው ላይ ማከል አለበት። ይህንን ካደረገ ሥነ ጹሑፍ የወደፊቱን ሲያመላክቱት ፣ ታሪክ ደግሞ በሙያው ላይ ባለፈው ዘመን ምን እንደተሰራ ያሳውቁታል” ብሎኛል።
የኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት እና ቤተ መዛግብት እንድታደም ጠርቶኝ በድሬዳዋ ፣ አርባምንጭ ፣ ወላይታ ሶዶ፣ዱራሜ እና ዲላ ከተሞች  ላይ ተገኝቼ፣ የመጻሕፍት ንባብ ልምዴን ለታዳሚው አጋርቻለሁ። በዚህም የሚገርመኝ አይነት ገጠመኞችም በህይወቴ ውስጥ ተከስተዋል። ከማስታውሰው አንዱ  ድሬዳዋ ማረሚያ ቤቶች ተገኝቼ ልምዴን ያጋራሁበት እለት ነው። በእለቱ አንድ ታራሚ በእርማቱ ወቅት ምን ማድረግ እንዳለበት፣ ጊዜውን እንዴት መጠቀም እንደሚገባው ካነበብኩት እንዳጋራ ጥናቴ  እዚህ ላይ እንዳተኩር አቶ ያሬድ ተፈራ ነገረኝ። አቶ ያሬድ፣ ከቤተ መዛግብቱ ከፍተኛ ሀላፊዎች መካከል አንዱ ነው። እኔም ህይወቱ በእስር ቤት 100% የተቀየረ አንባቢ የማስታውሰው ማልኮም ኤክስን ነው።(1925 - 1965)  ኤክስ ጥቁር አሜሪካዊ ነው፣ ትምህርቱን ከዝቅተኛ ክፍል ነው ያቋረጠው። ዘመኑ በፈጠረበት ተጽእኖ አስፈሪ ወመኔ ሆነ። አንድ በታደለበት ቀን እስር ቤት ገባ። ያቺ ቀን ዳግም ልደቱ ሆነች ፣ ያቺን እለት ቢያልፋት ኖሮ በቀጣዩ ቀን ሟች ነበር። ምክንያቱም አንድ ነጭ ሰውዬ ሚስቴን አባልጎብኛል ብሎ ሊገድለው እርሱ በታሰረ የእለቱ እለት ጠመንጃ ገዝቶ ነበር። ኤክስ በእለቱ በመታሰሩ ሟችና ገዳይ ሳይገናኙ ቀረ። ከዚያ በኋላ የማልኮም ኤክስ ህይወት በእስር ቤት በመጻሕፍት ንባብ ታንጻ መቶ በመቶ ተቀየረች። ይህንን ላወጋቸው እራሴን አዘጋጀሁ ፤ አንድ ቅር ያለኝ ነገር ይህ ታሪክ የአንድ ሩቅ አገር የሚገኝ ጥቁር ልጅ ታሪክ ቢሆንም፣ ለአበሻ ምናብ ይርቅ ይሆን?  እያልኩኝ በቅጡ አውጠነጠንኩ። እንደ መታደል የዚህ እለት የኢትዮጵያ ህዝባዊ ደሞክራሲያዊ ሪፕብሊክ፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ጓድ ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ ተጋባዥ ስለነበሩ ጎን ለጎን ስንቀመጥ፣ ከቁም እንቅልፌ ባነንኩ። ማውራት ያለብኝ ስለ ማልኮም ኤክስ ሳይሆን ስለ ጓድ  ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ ነው አልኩኝ። ልብ አድርጉልኝ፤ እኒህ ሰው በኢህዲሪ ዘመን ከፍተኛ ባለሥልጣን ነበሩ። ስርአቱ ሲፈርስ በእነ መንግስቱ ኃይለማሪያም ፋይል በተመሰረተባቸው ክስ የመጀመሪያ ተከሳሽ ናቸው። የክስ ሂደቱን እንደማስታውሰው  ሞት ተፈረደባቸው ፣ በሂደት ወደ ዕድሜ ይፍታህ ተቃለለላቸው፡፡ ከሁለት አስርት አመታት በኋላ በምህረት ተለቀቁ። ይህንን የመሰለ ጮማ ወሬ እንደዋዛ ካለፍኩት ድንቅ የመድረክ ሰው አይደለም አልኩት ለራሴ። አቶ ያሬድንም ሆነ ጓድ ፍቅረ ሥላሴን ሳላስፈቅድ ለታራሚው እጥር ምጥን ያለች አይን ገላጭ ንግግር አደረኩ። ንግግሬን ስቋጭ ሞቅ ያለ ጭብጨባ ተከተልኝ።
አልዋሽም፤ የጓድ ፍቅረ ሥላሴ ጽናታቸውን ከልብ አደንቃለሁ። ፌዎዶር  ዶስቶዬቭስኪ የተባለ አንጋፋ ሩሲያዊ ደራሲ፣ ደራሲ ለመሆን ለሚሹ ወገኖች ተጠይቆ ሲናገር፤ “ሞት ይፈረድብህ፤ በዚህ ስትጨነቅ በእድሜ ይፍታህ ይቃለልልህ ፣ ይህም ሲያስጨንቅህ በነፃ  ትለቀቃለህ፤ የዚያን ጊዜ ደራሲ ትሆናለህ” ይላል። ይህንን መራር  መንገድ ጓድ ፍቅረ ሥላሴ በጽናት ሲያልፉበት ባይ ነው ማድነቄ። ከዚያ በኋላ በእኔ እና በፍቅረ ሥላሴ መካከል ወዳጅነታችን ስር ሰዶ አዲስ አበባ ተገናኝተን መጻሕፍት ተቻችረናል። አገር ውስጥ እስካሁን ያልተነበበው መጽሐፋቸው ፤”እኔና አብዮቱ” እጄ ላይ አለ። ሌሎች የተጠናቀቁ ሥራዎች እንዳላቸው አውግተውኛል።  አንድ ቀን ያነበብኩላቸውን እዳስሰዋለሁ።
እንዲህ እይነቱ ጉዞ በተጋባዥ እንግዶች የሚወደድ ነው። እኔ ከተጋበዝኩ ስለምጓጓ እነማን አብረውን እንደሚጓዙ አስቀድሜ እጠይቃለሁ። አንዳንዴ የተነፋፈቅን ወዳጆች የምንገናኝበት ጊዜ አለ። አዲስ አበባ እንደሁ የምታገናኘን ቀብር ላይ ነው። “ተዋናይ እገሌ አረፈ!” ከተባለ ቀብር ላይ እንገናኛለን።
 ስለዚህ በህይወት ተገናኝቶ  እንዲህ አይነቱ አጋጣሚ ላይ መገናኘት  በጣም ተወዳጅ ነው።
የቀድሞው የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሥነ ጽሁፍ መምህር የነበረው መሰረት አበጀ፣ ዲላ እንግዳ ሆነን ሄደን የሆድ የሆዳችንን ስንጨዋወት፣ የካቲት ወር የተወለደበት ቀን እንደሆን ነገረን። የሚገርመው ወጣቶቹ ይህንን መረጃ ወደ ተግባር ቀይረው ምሽቱን 60ኛ ዓመት የልደት በዓሉን አከበርንለት። እርሱም በወጣቶቹ ድርጊት ልቡ ተነክቶ  ይህንን የመከባበርና የመዋደድ ባህልን  መጪው ትውልድ ላይ ማስታዋሉ እንዳስደሰትው አወጋን።
ዲላ ዩኒቨርስቲ ለወጣቶች የንባብ ልምዱን ሲያጋራ፣ የመግለጽ አቅሙ፣ የመመሰጥ ባህሪው ፣ ልክ እንደ ተዋጣላት ተዋናይ መድረክ ጠቦት ያደረገው ገላጻ ግሩም ነበር፡፡ ከእኔ ጋር በግል ስንጨዋወት፤ “ይህ የኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት እና ቤተ መዛግብት የሚሰራው ሥራ እጅግ የሚያስመሰግነው ነው። ቢያድለን ይህንን ተግባር መከወን ያለባቸው ትምህርት ሚኒስቴር እና ዩኒቨርስቲዎቹ ነበሩ፡፡ አልሆነም። አሁን ልብ ብዬ ሳስተውል ማንበብ በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ ሞቷል። ኤጀንሲው ለመጻሕፍት ንባብ ዳግማዊ ትንሳኤ እያደረገለት  ነው። ደሞ እየተዋጣላቸው ነው። ታያለህ፤ ህዝቡ ተማሪው በታላቅ ፍቅር ሲቀበላቸው?! ሥራውም ግዴታቸውም ነው።እነርሱም ደስ ብሏቸው እየተወጡት ነው” ያለኝን አልዘነጋውም። መምህር መሰረት አበጀ ዘንድሮ የ62 ዓመት ጎልማሳ ነው ።
ለዲላ ከተማ ነዋሪዎች ንግግር እንዳደርግ የተመረጥኩት እኔ ነበርኩ። የጌዲዮ ህዝብ ከምግብ ሥጋ እንደሚወድ አውቃለሁ። በርካታ አዝናኝ ቀልዶች ተነግረውበታል፡፡ የተወሰኑትን አውቃቸዋለሁ። በነገራችን ላይ ሥጋ መብላት በመላው ህዝባችን እንደሚወደድ አውቃለሁ። የጌዲዮ ከሁላችንም ይልቃል ለማለት ነው። የቆየ ቢሆንም አንድ ጥናት ሲገልጽ፤ አመታዊ ፍጆታችን 6% ነው።አምሮታችን 94% መሆኑ ነው። በአለማችን ከፍተኛ ሥጋ ተመጋቢ ህዝብ፣ የቻይና ህዝብ ነው። የአመት ፍጆታቸው 60% ነው።
ወደ ጌዲዮ እንመለስ፡፡ አንዷን ቀልድ እነሆ። ዲላ ከተማ ውስጥ  ከሰአት በኋላ ሙቀት ያይላል። አንዱ  ብልሁ አስተማሪ ጥቁር ሰሌዳው ላይ በቅጡ የተቀለበ ሰንጋ ሳለ እና አንዴ በደንብ አጨብጭቦ ተማሪዎቹ ትኩረት እንደሰጡት፤ “ልጆች ከሻኛ ላይ ልቁረጥ? ወይንስ ከሽንጥ ላይ ?!” አሉዋቸው።
ልጆቹን በታላቅ ጉጉት፣ የአምሮት ምራቅ አፋቸውን እየሞላው፤ “ ከሻኛ ቁረጥ ፣ ከሽንጥ ቁረጥ ! “ እያሉ እንደ ምርጫቸው ተንጫጩ ። መምህሩም ተማሪዎች እስኪነቁ እንጫጩዋቸው። ከልብ መንቃታቸውን ካስተዋሉ በኋላ ወደ እለታዊ ትምህርት ገቡ። እኔም ወጌን በስጋ ወግ አሟሟቅሁት። ወዳጆቼም ሆኑ የቤተ መዛግብቱ ሀላፊዎች፣ ታዳሚው ህዝብ  “ምን ሊያወራ ነው ?” በሚል ስሜት ተደንቀው ሲከታተሉኝ አስታውሳለሁ። እኔም ሥጋ በበላ አንጀት ትንሽ መጻሕፍት ማንበቡ፣ አስተዋይና አርቆ አሳቢ እንደሚያደርግ፣ ጭብጤን ሳስይዝ፣ ሞቅ ያለ የጭብጨባ ሽልማት ተቸረኝ፡፡
ድሬዳዋ ፣እርባምንጭ፣ ጬንቻና ዲላ ማረሚያ ቤቶች የተለያዩ ገጠመኞች አሉን። የዲላው ልብ የሚነካ ነበር። የማረሚያ ቤቱ ከፍተኛ ሀላፊ ኮማንደር እንስት ናቸው። በሁለት ነገር አስታውሳቸዋለሁ። አንደኛ ከልክ በላይ ግዙፍ ቁመናቸው ሲሆን ፣ ሁለተኛው ልብ የሚነካው ንግግራቸው ትውስ ይለኛል፡፡ “ማረሚያ ቤታችንን የእውነት ማረሚያ እንዲሆን መጥታችሁ አስተዋፅኦ ስላደረጋችሁልን ከልብ አመሰግናለሁ። ሌሎች አካላት ህግን ከማስከበር ውጪ እንዴት ሊያስቡን አልቻሉም ? እናንተ በራሳችሁ ፍቃድ  ስላሰባችሁን ከልብ! ከልብ! እናመሰግናችኋለን !” አሉ ፤ትክዝ ብለው።የጬንቻው ማረሚያ ቤት የሚደንቅ ነው። እንግዳ አቀባበሉን ብሔራዊ በአል ነበር ያደረጉት።ታራሚዎቹ የክት ልብሳቸውን ለብሰው  ደማቅና ውብ በሆነ ስሜት፤ “እንኳን ደህና መጣችሁ!”ብለው ተቀበሉን። በቆይታ አስተዳደሩም በአገር አቀፍ ደረጃ የተሸለመ የማረሚያ ቤቶቻችን አምባሳደር እንደሆነ ተገንዝበናል፡፡ ረዳት ኮሚሽነር አጥናፉ አሰፋ ቦቃ ለማንም የማይከብዱ ድንቅ መኮንን ናቸው። ከባልደረቦቻቸው ጋር ባደረጉት ድንቅ አመራር፣ ጬንቻ ማረሚያ ተቋም የድንቅ ዜጎች መፈጠሪያ ማእከል አድረገውታል። አብረውኝ ከተጓዙ ጓደኞቼ ጋር ስንጨዋወት፤ “ይህ ማረሚያ ቤት ጬንቻ እንደ እንዱ የቱሪስት መስህብ ልትጠቀምበት ይገባል“ ማለታቸውን አስታውሳለሁ። በርግጥም የሚጎበኝ ተቋም ነው።ጬንቻ የታዋቂው ፖለቲከኛና ደራሲ አሰፋ ጫቦ የትውልድ ስፍራ ነች። አሰፋ በአንደበቱ ም በብእሩም አንስቶ አይጠግባትም። ይህንን የሚያውቁት የፖለቲካ ተጻራሪዎቹ፣ ጬንቻን በዘመኑ ከጣሩት ልማት ተቋዳሽ ሳያደርጓት አለፉ። የማጣጣል ብእር ተስፋዬ ገብረአብም፣ በጬንቻ ላይ መዞባታል። የሚገርመው አሰፋም አርፎ የፖለቲካ ድርጅትም ታሪክ ከሆነ በኋላ፣ ዘንድሮ ተነቃቅታ በዘመንዋ የአስፓልት መንገድ ለመስራት ተፍተፍ ስትል አስተዋልኳት። የመንግስትም ሆነ የግል ባንኮች ተከትፈውባት፣ ሞቅ ደመቅ እያለች ነው። “አንድን የስድስት አመት ህጻን ያሰብከውን ጉዳይ ለማብራራት ካልቻልክ  ጉዳዩን አንተም አላወቅኸውም “ ይላል አልበርታይን አነስታይን። ንባብን ለመጀመሪ ደረጃ ተማሪዎች በጣም አቅልለን ማቅረብ። ለሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ትንሽ ከፍ አድርጎ መግለጽ ፣ ጥልቀቱን ጨምሮ ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ማውሳት በሂደት እየበሰልንበት መጣን ።
መሥሪያ ቤቱ የሁሉንም ደራሲዎች ሥራ ሸምቶ፣ ተረታ ተረቱን ለአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ፣ የጠቅላላ እውቀቱን ለመምህራኑ ሸምቶ ሰጥቷል። ለሁለተኛ ደረጃና ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ከልብ ወለዱም፣ ከግጥሙም  ከፍልስፍናውም  እያደረገ ሲለግስ የአይን ምስክሮች ነን።
ሌላው አስተዋጽኦ ለገጠር ቤተ መጻሕፍት የሚያደርገው ልግስና የሚደነቅ ሆኖ አግኝቼዋለሁ። ጋሞ ውስጥ ኤዞ በተባለ ገጠር ውስጥ በዶክተር ታደሰ ወልዴ ስም በተሰየመው ቤተ መጻሕፍት ምረቃ ላይ ተገኝቼ በጉዳዩ ላይ ከእንድ ወዳጄ ጋር ስናወጋ፤ “በህይወት ዘመናቸው መጽሐፍ ምን እንደሆን አይተው የማያውቁ ወገኖቻችን እንዳሉ ታውቃለህ ?!” ሲል ያነሳልኝ ጥያቄ የማልዘነጋው ነው። ከአመታት በፊት ገጠር ውስጥ አንድ ማለዳ እለት መደብ ላይ ጋደም ብዬ አንድ መጽሐፍ አነባለሁ ። ይህንን ልብ ብላ ታስተውል የነበረች አዛውንቷ አክስቴ፣ ወ/ሮ ወዘንቴ ወጋ፤ “ ምንድነው የያዝከው ?” አለቺኝ። መጽሐፍ እንደሆነ ነገርኳት። መጽሐፍ ምን እንደሆነ ጠየቀችኝ ፤ዝግ ባለ ሁኔታ መጽሐፍ ምን እንደሆነ አስረዳኋትና ከልብ ተደነቀች ። በወቅቱ 100 አመት ይሞላት ነበር ። በዚህ አንድ ምእተ ዓመት ባስቆጠረ እድሜዋ፣ መጽሐፍ ስትመለከት ይህ  የመጀመሪያዋ ነበር።
በዚህ ነው የኢትዮጵያ ቤተ መዛግብት እና ቤተ መጻሕፍት ጥበቡን አይቶ የማያውቅ እንዲያውቀው ፣ ያወቀው ከህጻናት እስከ አዋቂው  እንዲፈትሽና ውስጡን እንዲያይ የሚያደርገውን ጥረት ይበል ልለው የወደደድኩት፡፡
ይህ ከላይ በቁጥር ያሰፈርኩት መረጃ ኤጀንሲው ከ2011 ዓ.ም እስከ 2015 ዓ.ም ያከናወነው ሲሆን፤ 2016 ዓ.ም የመጀመሪያ መንፈቅ አመት ተካቶበታል፡፡ ኤጀንሲው 82 ዓመታት ባስቆጠረ የስራ ልምዱ፣ አገልግሎቱ በአዲስ አበባና አካባቢው ነበር። ባለፉት አምስት አመታት በኢትዮጵያ ቆዳ ስፋት ልክ ባደረገው ጥረት፤ “ የሚያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል” እንዲሉት እየሆነ ነው።
ተቋሙ፤የኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት እና ቤተ መዛግብት ወመዘክር በሚል ስያሜ በ1934 ዓም የተመሰረተ ነው። ወደ ኋላ ሄዶ በማንበብ ባህሪዬ እንደመረመርኩት፤ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ለወመዘክር የተለያዩ መንግስታትም ሆነ ትቋማት መጻሕፍት በልግስና ሲቸሩ፣ ንጉሰ ነገስቱ በአካል ተገኝተው መቀበላቸውን ማንበቤን አስታውሳለሁ። በዚህም በበርካታ የዓለም ቋንቋዎች አያሌ የመጻሕፍት ክምችት እንደሚኖረው እገምታለሁ። እራሳቸው አፄ ኃይለ ሥላሴ በቤተ መጻሕፍቱ በመገኘት እንደሚያነቡና በወቅቱ ከነበሩ ምሁራን ጋር በነጻነት ሲወያዩ ማየቱን ወዳጄ ኃይለ መለኮት መዋዕል አጫውቶኛል። ይህ ታላቅ የጥበብ ቤት ሲጠራኝ  በታላቅ ደስታ ነው  ከጎናቸው  የምቆመው። ይህን የተቀደሰ እንቅስቃሴያቸውን አብዝቼ ስለምወደውም  የሚጠሩኝን  ቀን እናፍቃለሁ፡፡
***
ከአዘጋጁ፡-
 ደራሲና ጋዜጠኛ ዘነበ ወላ ከ6 በላይ መጻሕፍትን ለንባብ አብቅቷል፡፡ ከጥበባዊና ወጋዊ ጸሃፊነቱ ባሻገርም የህይወት ታሪኮችን (ባዮግራፊስ) በመጻፍም ይታወቃል፡፡ ዘነበ ወላ አርታኢም ነው፡፡ ደራሲውን በኢሜይል አድራሻው፡ This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ማግኘት ይቻላል፡፡

ዱሮ ኪዩባን ከባቲስታን አምባገነናዊ አገዛዝ ነፃ ለማውጣት እነ ካስትሮና እነ ቼጉቬራ የትጥቅ ትግል ላይ በነበሩበት ዘመን (እ.ኤ.አ በ1950ዎቹ በ1990ዎቹ ውስጥ ) ይነገር የነበረ አንድ ወግ ነበር። አሁን ወደ አፈ-ታሪክነት ሳይለወጥ አልቀረም። የጥንት ተማሪዎች።
“ፋኖ ተሰማራ ፋኖ ተሰማ
እንደ ሆቺሚኒ እንደ ቼጉቬራ” ኢያሱ ይዘምሩለት የነበረ እንቅስቃሴ ማለት ነው።
ወጉ እንዲህ ነው።
 የኪውባው መሪ የነበሩት ፊደል ካስትሮ፣ የባቲስታን አገዛዝ ሊዋጋ ኃይል ሊያደራጅ ወደ ሜክሲኮ ይሄዳል። እዚያም አርጀንቲና የተወለደውንና ኋላ የኪውባ አብዮተኛ የሆነውን ቼ ጉ ቬራን ያገኛል። ሁለቱ ከአንድ ጠንካራ የኪውባ ተዋጊ ወታደር ጋር ጫካ ውስጥ ይመሽጋሉ። የትጥቅ ትግሉን በማፋፋም ላይ ናቸው። ከድጡ ወደ ማጡ እንዲሉ ከስፔይን ተገላግሎ በአሜሪካ እጅ መውደቅን ለመታገል እየጣሩ ነው።
የአሜሪካ መንግስት አሻንጉሊት የነበረው የባቲስታ ፉልጂኒቺዮ ጦር እጅግ አድርጎ እየበረታ፣ በአንጻሩ የታጋቾቹ ጦር እየተመናመነ ምን ማድረግ እንዳለባቸው  በጨነቃቸው ሰዓት ካስትሮ አንድ ሃሳብ አመጣ ይባላል።
“እንግዲህ ጓዶች ትግሉ እየመረረ፣ የጠላት ኃይል እያየለ እየመጣ ነው። ዕውነተኛ ታጋይነታችን፣ ቆራጥነታችን፣ ለነጻነታችን ከልብ የመቆማችን እውነተኛነት የሚለይበት ሰዓት ደርሷል። ስለዚህ ቃል እንግባ?”
“ምን የሚባል ቃል?” አለ ቼ።
“ምናልባት የጠላት ኃይል ከባድ ጥቃት አድርሶ ድንገት በእጁ ካስገባን፣ የሚያደርስብን ቅጣት፣ እኛ በሱ ላይ ያደረስንበትን ጥቃት ያህል ነው። ያው በእኛ ላይ ያለውን የጥላቻውን መጠን ያህል መሆኑ መቼም ጥርጥር የለውም። ባቲስታ ዓይኑን ካጠፋኸው ዓይንህን ያጠፋሃል። በጥይት ከቆላኀው በጥይት ይቆላሃል። እንዲያውም በዕጥፍ-ድርብ አብዝቶ፣ አንዱን በሺ መንዝሮ ነው ዋጋህን የሚሰጥህ። ስለዚህ ሁላችንም ለዓላማችን ስንል እኩል ጥቃት ማድረሳችን ከሆነ ብቻ ነው። አለበለዚያ ግን ከኛ መካከል ትንሽ ቅጣት የተቀጣ ሰው ዓላማችንን ክዷል ማለት ነው። ስለዚህ ዓላማችንን ላንክድ እንማማል።” ቼጉቬራም፣ ጠንካራው ታጋይም፣ በሃሳቡ ተስማሙ። ተማማሉ።ካስትሮ እንደፈራው ሦስቱም ተዋጊዎች ጠላት እጅ ወደቁ።
ከዚያም ለፍርድ ቀረቡ። ተፈረደባቸው። እንደየጥፋታቸው በቁማቸው እንዲቀበሩ ተወሰነ።አቀነባበራቸው የሚከተለውን ዓይነት ሆነ።
ቼ ጉቬራ ጨርሶ አይታይም። ካስትሮ ጉልበቱ ድረስ ብቻ ነው የተቀበረው። ጠንካራው ተዋጊ ወታደር ግን እደረቱ ድረስ መሬት ተቀብሯል። ይሄ ወታደር የካስትሮን እጉልበቱ ድረስ ብቻ መቀበር ባየ ጊዜ እንዲህ ሲል ወቀሰው።
”ካስትሮ ተማምለን ነበር። ከዳኸኝ። እኔን ደረቴ ድረስ ቀበሩኝ። አንተን ጉልበትህ ድረስ። የእኔን ያህል ጥቃት አላደረስክባቸውም ማለት ነው። ከሀዲ ነህ!”
ካስትሮም እንዲህ ሲል መለሰ!
“የለም የለም! አትሳት ጓድ። ጉልበት ድረስ ብቻ ወደ መሬት የገባሁበትን ምክንያት አላወቅህም። የቆምኩት!ኮ ቼ ጉቬራ ጭንቅላት ላይ ነው።
***
የራሳቸው ጭንቅላት የሌላቸው መሪዎች፣አለቆች፣ ኃላፊዎች በሌሎች ጭንቅላት መኖራቸው የተለመደ ነገር ነው። ሆኖም ውሎ ሲያድር የሌሎቹ ጭንቅላት፣ የሌሎቹ ስም፣ የሌሎቹ ታሪክ ለመኖሪያነት የሚያገለግበት ጊዜ ያልፍና ሁልህም በየራስህ ጭንቅላት ኑር የተባለ እለት የሚይዙት የሚጨብጡት የሚጠፋባቸው አያሌ ይሆናሉ። “አፍረው የተውት፣ ፈርተው የተውት ይመስለዋል” እንዲሉ፣  ለጊዜው የሚመጻደቅ ይኖራል። ቀኑ የደረሰ ጊዜ ግን ሁሉም ወደ ተገቢ ቦታው፣ ወደ ተገቢ ዕሴቱ የሚሄድበት፣ ተፈረካከሰ ያለውም ወደሚበታተንበት አቅጣጫ መጓዙ አይቀሬ ይሆናል።
አምባገነንነት ከልሂቅ እስከ ደቂቅ መከሰቻው ብዙ ነው። የየሰፈሩ ጌታ አለ እንደማለት ነው።
 የመሪ ጌታ አለ፣ የገንዘብ አለ። አምባገነንነትን አስመልክቶ ብሪታኒያዊው ባለሃብትና ታዋቂው ሰው ሪቻርድ ብራንሰን፤ “እኔ በጥሩ አምባገነንነት አምናለሁ። ዋናው ነገር አምባገነኑ እኔ ራሴ መሆን አለብኝ።” ብሏል። አምባገነኑ እኔ መሆን አለብኝ ብለው በይፋ የሚናገሩ አምባገነኖች ብዙ አይደሉም። በየውስጠ-ልቡናቸው የመጨቆን፣ የመግፋት፣ የማፈን፣ የማን-አለብኝ ባህሪ ያላቸው ሙልሙል አምባገነኖች ብቅ ብቅ በሚሉበት ጊዜ አገር ተኮነነች ማለት ነው። ሀሳዊ-ዴሞክራት የማታለያ ስብከትን (Demagogue) ያበዛል። ስሜታዊነትን ከምክንያታዊነት ያስቀድማል። በትንሽ ነገር ኩፍ ይላል-ገፁ ይለዋወጣል።
 ለማገዱ፣ ለማገቱ፣ ለማሰሩ፣ ለመግደሉ ወዘተ ሁሉ ምክንያት ይሰጣል። በየትኛውም ደረጃ ይሄን ባህሪ ይዞ የሚገኝ እሱ አምባገነን ነው። ከእንዲህ ያለው ይሰውረን ዘንድ ነው “ዕውነተኛ ዲሞክራሲ ሆይ፤ ከእኛ አትራቂ” እያልን የምንጸልየው። “የመናገር የመጻፍና ሃሳብን የመግለጽ ነጻነት ሆይ፣ ከእኛ አትራቂ” እያልን ሱባዔ የምንገባው ለዚህ ነው። ጉባዔ ሲያቅት ሱባኤ እንዲሉ።ሁሉን በእርጋታ፣ ሁሉን በትዕግስት መከወን፣ የብልህነትና የብስልነት ምልክት ነው ይላሉ። “ተመልሰህ ለምታፍሰው፣ ቸኩለህ አታፍስሰው” ነው ነገሩ። ቸኩሎ ድምዳሜ ላይ መድረስ፣ ቸኩሎ መውቀስ ቸኩሎ ማወደስ፣ ቸኩሎ መራገም ከንቱ ሆኖ ሳለ፣ ኃይለኛ አለቆችና መሪዎች የዕለት መፈክራቸው ያደርጉታል። ይህ አገርን አያሳድግም። ህዝብን ነፃ አያደርግም። ጥንቃቄ ያሻዋል።ለህዝብ ተቆርቋሪ፣ ለሀገር አሳቢ የሚመስሉ በርካታ ግለሰቦች፣ ቡድኖችም ሆኑ መንግሥታት፣ እንደሚኖሩ አለመርሳት ተገቢ ነው። በርካታ ሃሳዊ-መሢሃን እንዳሉ ልብ ማለት ያስፈልጋል።
 የበግ ለምድ የለበሰ ቀበሮ ብቻ ሳይሆን፣ የቀበሮ ቆዳ የሚለብስ በግም እንደማይጠፋ ማወቅ ደግ ነው። ከነጋ ለማጨብጨብ ከመሸ ለመሳደብ የማይተኙ በርካታ የአለቃ ሚዜና አጃቢዎች “ሽቶው ውሃ ነው”  እስኪባሉ አንደኛ ማዕረግ ቦታ ሊቀመጡ ይችላሉ። የዛሬ ዕድሜ ግን በውሃ መስላ ሻማ ናት።
በሀገርና ህዝብ ጉዳይ የቲዮሪ አንጓች፣
የፖሊሲ መካሪ፣ የህግ አማካሪ፣ የቅርብ ተጠሪ፣ የሩቅ ተጧሪ የሆኑ ሰዎች፣ ቡድኖች፣  ፓርቲዎች፣ ሀገሮች ፍሬያቸው ብስል መስሎ ጥሬ፣ ምክራቸው አዛኝ መስሎ ገዳይ ከሆነ፣ “የሚስቴን ወገብ ይዞ የሚጨፍር ሚዜዬ አይደለም” የሚል ህዝብ እንዳለ ሊገነዘብ ይገባል።

ግራር፣ የጠቢባን መናኸሪያ ከተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) – አሽበርግ ፕሮግራም ጋር በመተባበር፣ “ሠዓሊትን ፍለጋ የተሰኘ ሴት ሠዓሊያንን  ማብቃት ላይ ያተኮረ ፕሮጀክት በይፋ አስጀምሯል።
ይህ ፕሮጀክት ሁሉን አቀፍ የሴት የሥነ ጥበብ ሙያተኞችን ብራንዳቸውንና የዲጂታል ሰብዕና ከማጎልበት ባሻገር ሚዛናዊ የባህል ምርቶችና አገልግሎቶች ስርጭት እንዲሁም የአርቲስቶችና የባህል ሙያተኞች ተንቀሳቀሶ የመስራት ዕድሎችን ለማጎልበት አንዲቻል፣ ሴት ሠዓሊያን በብራንዲንግ፣ ዲጂታል አካታችነትና የንቅናቄ መፍጠሪያ መድረኮች ያካተተ ነው።
“ሠዓሊትን ፍለጋ” የዘመኑ የዲጂታል አሰራር የፈጠረውን ዓለም አቀፍና የባሕልና ጥበብ እንዱስትሪ ትስስር ያለውን ዕድል በአግባቡ የተገነዘበ ፕሮጀክት ነው። በመሆኑም በዚህ ፕሮጀክት የሴት ሠዓሊያንን የብቃት ደረጃ ማጎልበትን፣ መሰረታዊ መብቶቻቸውን ለመጠበቅና በዲጂታል ሥነ ምህዳር ያለውን የተሳትፎ  ክፍተት ማጥበብ፤ የአርቲስቶች የፈጠራ ሃሳቦቻቸውን በነፃነት የሚገልፁበትን፣ በነፃነት ተንቀሳቅሶ የመስራትና ተመጣጣኝ  የገበያ እድሎችን ተደራሽ ማድረግን፣ የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መብቶች ጥበቃን እንዲሁም ፍትሃዊ ክፍያ ለጥበብ የፈጠራ ስራዎች እንዲኖር  አስተዋጽኦ ያበረክታል  ተብሏል። ይህ ፕሮጀክት የዲጂታል ክህሎት ስልጠናን በመስጠት የ20 ሴት ሠዓሊያንን በዲጂታል ስርዓት ውስጥ ያለውን የሥርዓተ ጾታ  ኢ-ፍትሃዊነት በማጥበብ፣ ስኬታማ የሙያ እድገት እንዲኖራቸው  እንደሚያስችል ተገልጿል ።
በፕሮጀክቱ  ለ20ዎቹ ሴት ሠዓሊያን ጋር በቅርበት በሚሰሩና ድጋፍ በሚያደርጉ ባለሙያዎች  በብራንዲንግ፣ በማህበራዊ ሚዲያ አመራር፣ ድረ ገጽ አጠቃቀም የይዘት ዝግጅትና የገበያ ልማት ስልቶች ላይ ያተኮሩ ስልጠናዎች  እንዲያገኙ ይደረጋል። ይህም ሠዓሊያኑ ስራዎቻቸውን ለታዳሚ ለማቅረብ ለሰፊው የጥበብ አፍቃሪው ማህበረሰብ ተደራሽ ለመሆንና በዓለም አቀፍ የዲጂታል ሥነ ምህዳር ውስጥ ያሉ አዳዲስ የገበያ ዕድሎችን ለመጠቀም ያስችላቸዋል።
ፕሮጀክቱ በፈጣን እድገት ላይ የዲጂታል ሽግግርና የሰብዕና ግንባታ ያለውን ሚና በመገንዘብ የሴት የጥበብ ሙያተኞችን ተሰሚነትን ከማጎልበት ባሻገር፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ የባህል ምርቶች ማስፋፋትና የባህል ትውውቅን ለማጎልበት ይሰራል።
በተጨማሪም ሠዓሊትን ፍለጋ ለ100 በጥበብ ና ቴክኖሎጂ ዘርፎች ላይ የተሰማሩ ወጣቶች የሥራ ዕድሎች የሚፈጥር ነው። ፕሮጀክቱ እያደጉ  የመጡ የቴክኖሎጂና ፈጠራ አቅሞችን በመገንዘብ፣ ቀጣዩን ትውልድ ለፈጠራ ማነሳሳትን ታሳቢ አድርጎ ይሰራል ተብሏል። ይህ ፕሮጀክት የባህልና የጥበብ ዘርፉ ላይ አስተዋጽኦ የሚያበረክቱ የፈጠራና ጥበባትን ስራዎች በማበረታታት፣ ብዝሃ ባህልን የሚያጎለብቱ ስራዎች ለመደገፍ ያለውን ቁርጠኝነት  በተግባር የሚያሳይበት እንደሆነም ተነግሯል ፡፡
የግራር፣ የጠቢባን መናኸሪያ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሴሚናስ ሀደራ እንደገለፁት፤ “ ሠዓሊትን ፍለጋ ፕሮጀክት ሴት ሠዓሊያን ያላቸው ፈጠራና ተሰጥኦ ተገቢውን እውቅና አንዲያገኙ የሚያስችል ፕሮጀክት  ሲሆን   ግራር፣ የጠቢባን መናኸሪያ  ከዩኔስኮ - አሽበርግ ፕሮግራም ጋር በመተባበር  ሴት የሥነ ጥበብ ሙያተኞችን አቅም ለማጎልበትና ለማብቃት እንሰራለን ብለዋል ።
በዚህ ፕሮጀክት የዲጂታል ክህሎት ስልጠናን በመስጠት፣ የዲጂታል ሰብዕና መገንቢያ አሰራሮችን በማልማትና በመተግበር የሴት ሠዓሊያ በዲጂታል ስርዓት ውስጥ ያለውን የሥርዓተ ጾታ ኢፍትሃዊነት በማጥበብ እንዲሁም አካታች እና ፍትሃዊ የጥበብ እና ፈጠራ ሥነ ምህዳር እንዲጎለተ በመስራት ሴት ሠዓሊያኑ በዘመናዊው የዲጂታል ዓለም ውስጥ ጉልህ ድርሻ አንዲኖራቸው ድጋፍ ይደረግላቸዋል ተብሏል፡፡

Saturday, 09 March 2024 20:06

11ቢሊየን

ሰሞኑን ለመጀመሪያ ጊዜ 20 ግዙፍ ቦይንግ 777X-9 አውሮፕላኖች ለመግዛት ከቦይንግ ጋር ተፈራርሟል።
የአውሮፕላኖቹ ዋጋ እስከ 11ቢ. ዶላር ይገመታል
አውሮፕላኑ 50 የቢዝነስና 390 የኢኮኖሚ መቀመጫዎች አሉት
አየር መንገዱ አውሮፕላኖቹን በማዘዝ ከአፍሪካ ቀዳሚው ነው
እ.ኤ.አ ከ2027 እስከ 2030 አውሮፕላኖችን ይረከባል

መልዕክተኛው የፕሪቶሪያው ስምምነት አፈጻፀምን ይገመግማሉ ተብሏል

የአሜሪካ መንግሥት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ማይክ ሐመር፣ በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች የተከሰቱ  ግጭቶች በድርድር እንዲፈቱ ለማድረግ በሚቻልባቸው ጉዳዮችና   በመንግሥትና  በህወሓት መካከል የተደረሰው ስምምነት አፈጻጸም  ግምገማ ዙሪያ በአዲስ አበባ እየመከሩ ነው ። የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ይፋ ባደረገው መግለጫ ላይ እንደተጠቆመው፤ ልዩ መልዕክተኛው  በአሁኑ ጊዜ በተባባሰው የአማራ ክልል ግጭትና ዓመታትን ባስቆጠረው የኦሮሚያ ክልል አለመረጋጋት ዙሪያ ሰላም ለማምጣት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ከኢትዮጵያ መንግሥት ባለሥልጣናት ጋር  ይመክራሉ ተብሏል፡፡
በትግራይ ሲካሄድ የነበረውን ጦርነት ለማስቆም በተደረገው ጥረት ውስጥ ጉልህ ሚና እንደነበራቸው የሚነገርላቸው አምባሳደር ማይክ ሐመር፤ ደም አፋሳሹን የሰሜን ኢትዮጵያን የእስር በርስ ጦርነት ያስቆመውን የፕሪቶሪያውን ስምምነት አፈጻጸም በተመለከተ በአፍሪካ ኅብረት አስተናጋጅነት፣ ከየካቲት 28 አስከ መጋቢት 4 ቀን 2016 ዓ.ም. በሚካሄደው ግምገማ ላይ ተሣታፊ እንደሆኑም ተገልጿል። ከተፈረመ አንድ ዓመት ያለፈውን የፕሪቶሪያው ስምምነት የአፈጻጸም ሂደት በተመለከተ የስምምነቱ አሸማጋዮችና ታዛቢዎች የሚሳተፉበት ግምገማ እንደሚካሄድ ሲነገር ቆይቷል፡፡ ልዩ መልዕክተኛው  አምባሣደር ሐመር፣ ከኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ጋር  በመገናኘት  በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ውስጥ ያለውን ግጭት ለማብቃት የሚደረጉ ጥረቶችን ለማፋጠን በሚያስችሉ ሁኔታዎችንና ግጭቱን በድርድር ለመፍታት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ እንደሚመክሩ የአሜሪካው  የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት፣ የአምባሳደር ሐመርን ጉዞ በተመለከተ ባወጣው መግለጫ ላይ አመልክቷል።
ካለፈው አመት ሐምሌ ወር ጀምሮ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር በሚገኘውና  ከፍተኛ አለመረጋጋት ውስጥ በገባው የአማራ ክልል ውስጥ በፌደራል መንግሥቱ ኃይሎችና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል የሚካሄደው ግጭት መባባሱን ተከትሎ ግጭቱን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት  አሜሪካ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ  እንደምትገኝም መግለጫው ጠቁሟል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በመንግሥትና ራሱን የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት እያለ በሚጠራው ታጣቂ ኃይል  መካከል  ያሉ ግጭቶችን ለማስቆምና ሰላም ለማውረድ የተደረጉ ሙከራዎች ውጤት ሳያመጡ መቅረታቸው አይዘነጋም፡፡ የፊታችን ረቡዕ ይጠናቀቃል ተብሎ በሚጠበቀው ውይይት፤ ግጭት ውስጥ ያሉ ሃይሎች ወደ ሠላማዊ  መንገዶች የሚመጡበትንና ችግሮቻቸውን በውይይት ለመፍታት የሚችሉበትን ሁኔታ ለማመቻቸት ዕድል ይፈጠራል ተብሎ ይጠበቃል።

በቅርቡ ይጸድቃል ተብሎ የሚጠበቀው ረቂቁ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ፣ ለሕዝብ ቀርቦ ዜጎች ውይይት እንዲያደርጉበትና  እንዲተች  የሚጠይቅ ምክረሃሳብ ለፍትህ ሚኒስቴር ቀረበ ። ”ስብስብ ለሰብዓዊ  መብቶች በኢትዮጵያ“  የተሰኘ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት፣ ከሌሎች በሰብዓዊ መብቶች ላይ ከሚሠሩ አገር በቀል የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ጋር በመተባበር፣ ለረቂቅ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲው  ግብዓት የሚኾኑ ሀሳቦችን የያዘ የምክር ሀሳብ ሰነድ ለፍትህ ሚኒስቴር በጽሁፍ አቅርቧል።
ይኸው ለፍትህ ሚኒስቴር የቀረበው የምክር ሃሳብ ሰነዱ፣ በቅርቡ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ ይጸድቃል ተብሎ የሚጠበቀው  ረቂቅ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ፣ ለሕዝብ ቀርቦ እንዲተችና ሕዝቡ በጉዳዩ ላይ ሃሣብ እንዲሰጥበት የሚጠይቅ ሲሆን፤  ከሽግግር ፍትህ ፖሊሲው ትግበራ  አስቀድሞ    መንግሥት  በተለያዩ የአገሪቱ  አካባቢዎች በመካሄድ ላይ የሚገኙ  ግጭቶችን  ማስቆም እንዳለበት  እንዲሁም  በፖሊሲው ሂደት አግባብነት ያላቸው ተቋማት ሚና  መካተት እንዳለበት ይጠቁማል፡፡
 በተጨማሪም ሰነዱ የፖሊሲው የተፈጻሚነት ውሰን፣ በሰሜኑ ጦርነት ከባድ ወንጀሎችን የፈጸሙ የኤርትራ ወታደሮችን በልዩ ፍርድ ቤት ማየትን ጭምር እንዲያካትት የሚጠይቁና ሌሎች ምክረ ሃሳቦችንም ይዟል፡፡ ድርጅቱ፤ ከሌሎች በሰብዓዊ መብቶች ላይ ከሚሰሩ ተቋማት ጋር በመተባበር ለፍትህ ሚኒስቴር ባቀረበው ምክረ ሃሣብ፣ ረቂቁ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ፣ በምክር ቤቱ ከመፅደቁ በፊት ለህዝብ ውይይት ሊቀርብ እንደሚገባው  ጠቁሟል፡፡



አገኘሁ_አዳነ_ድልነሣሁ-


በቤልጅዬም የኢትዮጵያ ኤምባሲ፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ_የሥነጥበብና_ዲዛይን_ት_ቤት ጋር በመተባበር በቤልጅዬም ከየካቲት 18 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ የሥዕል ትርዒት አቅርበዋል። ይህ ኤግዚቢሽን መልኩና ፈርጁ ብዙ የሆነውን የዲፕሎማሲ ዓለም በሥነጥበብና ባህል ለማዋዛት፣ ነባሩ የሥነ ጥበብ ብሂል በዘመነኛው የሥነ ሥዕል እንቅስቃሴ ላይ ያሳደረውን ክንደ ብርቱ ተፅዕኖ ለማመላከትና ት/ቤቱ ከቀረው ዓለም አቻ ተቋማት ጋር ትስስር መፍጠር እንዲችል ታስቦ የተሰናዳ ነበር።  በትርዒቱ መክፈቻ የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ግንኙነት  ቢሮ ዋና ፀሐፊ ስቴፋኖ ሳኒኖ (Stefano Sannino)፣ የቤልጂየም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካይ፣ አምባሳደር  ባርት ዴ ግሩፍ፣ የአካፓድ ምክትል ዋና ፀሐፊ ዶ/ር ኖርበርት ሪቻርድ ኢብራሂም፣ በብራስልስ የሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ አባላት የተገኙ ሲሆን፣ የሥነ ጥበብ ልሂቃንና የሥነ ጥበብ አፍቃርያን ታድመውበታል።
በቤልጅዬም የኢትዮጵያ ኤምባሲ ባለሙሉ ስልጣን እንደራሴ አምባሳደር ሒሩት ዘመነ፣ አምባሳደር ሞላልኝ አስፋው እና የሥራ ጓዶቻቸው ዝግጅቱ የተሳካ ይሆን ዘንድ የሚያስመካ ጥረት አድርገዋል። ጥረቱ ፍሬ አፍርቶም በቤልጅዬም የሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰቡ፣ የታሪክ፣ የሂስ እና የሥነጥበብ ንድፈ ሐሳብ ልሂቃን በኤምባሲው እንዲሰበሰቡ ሆነዋል።
የአንትወርፕን (Antwerpen) Royal Academy of the Arts መምህራንም በኤምባሲው ተገኝተው ፍሬ ያለው ውይይት ማድረግ ችለናል። ምሑራኑ ትርዒቱን ተመልከተው መደነቃቸውን የገለጹልን ሲሆን፣  በምንተባበርባቸው ተቋማዊ የጋራ ጉዳዮች ላይ መክረናል።  
የቀረበው የሥዕል ትርዒት ተወዳጅነቱ ከፍ በማለቱ ምክንያት ለተጨማሪ አንድ ሳምንት የተራዘመ ሲሆን፣ ለአካባቢው ማኅበረሰብ መነቃቃት መፍጠሩን በዝግጅቱ አካል የሆንነው ሙያተኞች መታዘባችንን እንመሰክራለን።
ሀገራችን ኢትዮጵያ ከሌላው ዓለም ጋር የምትነጋገርበትን የቋንቋ አማራጭ ለማስፋት ሥነጥበብን ወደ ዲፕሎማሲው ዓለም የጋበዙትን አምባሳደር ሒሩት ዘመነን፣ አምባሳደር ሞላልኝ አስፋውንና የሥራ ጓዶቻቸውን  ማመስገን ይገባል።

አገኘሁ_አዳነ_ድልነሣሁ-


በቤልጅዬም የኢትዮጵያ ኤምባሲ፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ_የሥነጥበብና_ዲዛይን_ት_ቤት ጋር በመተባበር በቤልጅዬም ከየካቲት 18 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ የሥዕል ትርዒት አቅርበዋል። ይህ ኤግዚቢሽን መልኩና ፈርጁ ብዙ የሆነውን የዲፕሎማሲ ዓለም በሥነጥበብና ባህል ለማዋዛት፣ ነባሩ የሥነ ጥበብ ብሂል በዘመነኛው የሥነ ሥዕል እንቅስቃሴ ላይ ያሳደረውን ክንደ ብርቱ ተፅዕኖ ለማመላከትና ት/ቤቱ ከቀረው ዓለም አቻ ተቋማት ጋር ትስስር መፍጠር እንዲችል ታስቦ የተሰናዳ ነበር።  በትርዒቱ መክፈቻ የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ግንኙነት  ቢሮ ዋና ፀሐፊ ስቴፋኖ ሳኒኖ (Stefano Sannino)፣ የቤልጂየም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካይ፣ አምባሳደር  ባርት ዴ ግሩፍ፣ የአካፓድ ምክትል ዋና ፀሐፊ ዶ/ር ኖርበርት ሪቻርድ ኢብራሂም፣ በብራስልስ የሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ አባላት የተገኙ ሲሆን፣ የሥነ ጥበብ ልሂቃንና የሥነ ጥበብ አፍቃርያን ታድመውበታል።
በቤልጅዬም የኢትዮጵያ ኤምባሲ ባለሙሉ ስልጣን እንደራሴ አምባሳደር ሒሩት ዘመነ፣ አምባሳደር ሞላልኝ አስፋው እና የሥራ ጓዶቻቸው ዝግጅቱ የተሳካ ይሆን ዘንድ የሚያስመካ ጥረት አድርገዋል። ጥረቱ ፍሬ አፍርቶም በቤልጅዬም የሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰቡ፣ የታሪክ፣ የሂስ እና የሥነጥበብ ንድፈ ሐሳብ ልሂቃን በኤምባሲው እንዲሰበሰቡ ሆነዋል።
የአንትወርፕን (Antwerpen) Royal Academy of the Arts መምህራንም በኤምባሲው ተገኝተው ፍሬ ያለው ውይይት ማድረግ ችለናል። ምሑራኑ ትርዒቱን ተመልከተው መደነቃቸውን የገለጹልን ሲሆን፣  በምንተባበርባቸው ተቋማዊ የጋራ ጉዳዮች ላይ መክረናል።  
የቀረበው የሥዕል ትርዒት ተወዳጅነቱ ከፍ በማለቱ ምክንያት ለተጨማሪ አንድ ሳምንት የተራዘመ ሲሆን፣ ለአካባቢው ማኅበረሰብ መነቃቃት መፍጠሩን በዝግጅቱ አካል የሆንነው ሙያተኞች መታዘባችንን እንመሰክራለን።
ሀገራችን ኢትዮጵያ ከሌላው ዓለም ጋር የምትነጋገርበትን የቋንቋ አማራጭ ለማስፋት ሥነጥበብን ወደ ዲፕሎማሲው ዓለም የጋበዙትን አምባሳደር ሒሩት ዘመነን፣ አምባሳደር ሞላልኝ አስፋውንና የሥራ ጓዶቻቸውን  ማመስገን ይገባል።

ዳሸን ባንክ ሸሪክ የተሰኘ ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት የጀመረበትን 6ኛ ዓመት ባከበረበት ዕለት ከደንበኞች በበጎ አደራጎት ፈንድ በአደራ የሰበሰበውን 12.5 ሚሊዮን ብር ለ18 አገር በቀል የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ለገሰ፡፡  

ዳሸን ባንክ በሚሰጠዉ ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት ብቻ አሁን ላይ ከ1 ሚሊየን በላይ ደንበኞችን ማፍራት የቻለ ሲሆን፤ይህንንም በተለያዩ ስነ-ስርዓቶች አክብሯል፡፡

የዳሸን ባንክ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አስፋው ዓለሙ በስነ-ስርዓቱ ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፤ ለባንኩ አመኔታቸውን ለሰጡ ደንበኞች ከፍ ያለ ምስጋናቸውን አቅርበው፣ ወደፊትም ለላቀ ስኬት የሸሪዓህ መርህን በመከተል አዳዲስ የባንክ አገልግሎቶቸን እንደሚያቀርብ ገልፀዋል፡፡

አቶ አስፋው አክለውም፤ በአደራ የተሰጣቸውን ገንዘብ የተረከቡ 18 አገር በቀል በጎ አድራጎት ድርጅቶች የማህበረሰቡን ችግር ለመቅረፍ በሚያስችሉ ስራዎች ላይ እንዲያውሉት አደራ ብለዋል፡፡ በቀጣይም ባንኩ እነኚህንም ሆነ መሰል ሌሎች ተቋማትን የማህበረሰቡን ችግሮች በዘላቂነት በሚፈቱ ስራዎች ላይ በጋራ ለመስራት የሚሻ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

ዳሸን ባንክ፤ የካቲት 26 ቀን 2010 ዓ.ም በአንድ መስኮት መስጠት የጀመረው አገልግሎት አድጎ ዛሬ ላይ ከ70 በላይ ሙሉ በሙሉ ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት በሚሰጡ ቅርንጫፎች እንዲሁም ከ800 በላይ በሆኑ ቅርንጫፎች ደግሞ በመስኮት ለደንበኞቹ የተሟላ ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ ከደንበኞቹም ከ9.5 ቢሊየን ብር በላይ ማሰባሰብ የቻለ ሲሆን፤ ከዚህም ውስጥ ከ6 ቢሊየን ብር በላይ በተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ ለተሰማሩ ደንበኞቹ ፋይናንስ አድርጓል፡፡

ባንኩ ከወለድ-ነፃ የባንክ አገልግሎት የሚጠይቀውን ሙያዊና ሸሪዓዊ ስነ-ምግባር ተግባራዊ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በዚህም ረገድ እ.ኤ.አ ህዳር 28 ቀን 2023 በባህሬን ማናማ በተካሄደው 9ኛው የኢስላሚክ ሪቴል ባንክ ሽልማት ላይ ጠንካራው ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት በኢትዮጵያ የሚሰጥ ባንክ (The strongest Islamik Retail Banking Window in Ethiopia 2025) በሚል ተቀማጭነቱ ሎንዶን በሚገኘውና  በፋይናንስ ዘርፍ ጥናትና ምርምር በሚሰራዉ  ኬምብሪጅ አይ ኤፍ ኤ(Cambridge IFA) የተሰኘ ተቋም ሽልማት አግኝቷል፡፡ ባንኩን ለዚህ ሽልማት ካበቁት መሰፈርቶች አንዱ  ጠንካራ የሸሪዓህ አስተዳደር ማዕቀፍ በመተግበሩ ነው፡፡

ባንኩ በአለም አቀፍ ደረጃ የእስላማዊ ፋይናንስ ተቋማትን የሂሳብ፣ ኦዲትና ሸሪዓህ መስፈርቶችን የሚያወጣው ተቋም (AAOIFI) ቋሚ አባል የሆነ፣ በኢትዮጳያ ብቸኛው የፋይናንስ ተቋም መሆኑ ይታወቃል፡፡

በሙዚቃው ኢንዱስትሪ ውስጥ ከሚገኙ አለም አቀፍ ተቋማት ጋር  በጋራ እየሰራ የሚገኘው ሰዋሰው መልቲሚዲያ፣ በትውልደ ኢትዮጵያውያን በተመሰረተውና በተለያዩ የአሜሪካን ግዛቶች በስፋት በዲጂታል ማስታወቂያው ዘርፍ ላይ እየሰራ ከሚገኘው አድ ቴክ ሶሉሽን ጋር  በጋራ ለመስራት በዛሬው ዕለት ከስምምነት ላይ ደረሱ፡፡

የዛሬው ስምምነት ኢትዮጵያውያን አርቲስቶችን ወደ ዓለም አቀፉ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ እንዲሁም በሙዚቃው ዘርፍ የተሰማሩ ግዙፍ አለም አቀፍ ተቋማትን ደግሞ ወደ ሀገራችን የኪነ-ጥበብ ዘርፍ ለማስገባት አልሞ ለሚሰራው  ሰዋሰው መልቲሚዲያ ወሳኝ ምዕራፍ ነው ተብሏል፡፡

በተለያዩ የአሜሪካን ግዛቶች በኢትዮጵያውያን በሚዘጋጁ ትልልቅ ፕሮግራሞች፣ በአብዛኞቹ የሀገሪቱ ግዛቶች በሚገኙ ሞሎች፣ አደባባዮች፣ ሆቴሎችና በርካታ ሰዎች በሚሰበሰቡባቸው ጎዳናዎች ላይ የዲጂታል ማስታወቂያ ስራን የሚሰራው አድ ቴክ ሶሉሽን፣ በሰዋሰው በኩል የሚወጡ አልበሞችን፣ የተለያዩ አርቲስቶችን ስራዎች እንዲሁም ከሰዋሰው ጋር በጋራ የሚሰሩ ተቋማትን አገልግሎቶች የሚያስተዋውቅ ይሆናል፡፡

የሰዋሰው ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ሀብቱ ነጋሽ፤ በመላው አለም የሰዋሰው አርቲስቶችንና ስራዎችን ለማስተዋወቅና ለማስፋፋት ከምናደርጋቸው ስራዎች መካከል ይህ አንደኛው መሆኑን ጠቅሰው፣ በስምምነቱም ደስተኛ መሆናቸውን ገልፃዋል፡፡

በኢትዮጵያ የአድ ቴክ ሶሉሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አማኑኤል ኪዳኔ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያን የሙዚቃ ኢንዱስትሪ በተለየ መልክ ለማሻሻልና ለመለወጥ ከሚሰራው ሰዋሰው ጋር በጋራ ለመስራት በመስማማታችን ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶናል ብለዋል፡፡

ሁለቱ ድርጅቶች በቀጣይ በአውሮፓ የተለያዩ ሀገራት በጋራ የመስራት ውጥን እንዳላቸውም ተጠቁሟል፡፡

Page 8 of 700