Administrator

Administrator

Saturday, 21 June 2014 14:51

የብራ መብረቅ በናይጀሪያ

ቦኮ ሃራም ባጠመደው ቦንብ 21 ወጣቶች ሲሞቱ፤ 27ቱ ቆስለዋል

ናይጀሪያውያን የእኛን ቡድን በደርሶ መልስ ጨዋታ አሸንፎ ለ20ኛው የአለም ዋንጨ ባለፈው የአፍሪካ ሻምፒዮን ብሔራዊ ቡድናቸው በእጅጉ ደስተኞች በመሆናቸው የብራዚሉ የአለም ዋንጫ እስኪጀመር በጣም ቸኩለው ነበር፡፡
አብዛኞቹ ናይጀሪያውንም ቡድናቐው ተካፋይ የሆነበት የብራዚሉ የአለም ዋንጫ,ኧ እስከ ፍፃሜው ድረስ (ያለው የአንድ ወር ጊዜ በየአደባባዩ ተሰብስበው የሚዝናኑበት አሪፍ የፌሽታ ጊዜ እንደሚሆንላቸው ሙሉ እምነት ነበራቸው፡፡
የሰሜን ምስራቅ ግዛቶች ውስጥ በሚኖሩት ናይጀሪያውያን ዘንድ ግን ይህን መሰሉ ስሜት ብዙም አልቆየም፡፡ ፅንፈኛ እስላማዊ አሸባሪ ቡድን የሆነው ቦኮ ሃራም በዋናነት ይንቀሳቀስበታል በሚባለው በዚህ አካባቢ የዓለም ዋንጫን መመልከት የታገደው ከጨዋታው ቀደም ብሎ ነው፡፡ ቦኮ ሀራም በዮቤና በአዳማዊ ግዛቶች “አዳሜ ሁሉ የአለም ዋንጫ ውድድርን በአደባባይ ተሰብስቤ እየጨፈርኩ በቴሌቪዥን እከታተላለሁ ስትል ውርድ ከራሴ!” በማለት በበራሪ ወረቀት የሰጠው ማስጠንቀቂያ ብዙዎችን ከፍ ያለ ስጋት ውስጥ መጣሉ አልቀረም፡፡
በእግር ኳስ ፍቅር ልባቸው ክፉኛ የነደደ በርካታ ናይጀሪያውያን ግን ስጋታቸውን እንደያዙም ቢሆን ሰብሰብ ብለው እየጨፈሩ ውድድሩን ከመመልከት ወደኋላ አላሉም፡፡ የዮቤ ግዛት የዳማቱሩ ከተማ ነዋሪ የሆኑ እግር ኳስ አፍቃሪ ናይጀሪያውያን ባለፈው ማክሰኞ ያደረጉትም ይህንኑ ነበር፡፡
ለቦኮ ሀራም ግን የእነዚህ ናይጀሪያውያን ድርጊት ማስጠንቀቂያን ቸል የማለት ተራ ስህተት ሳይሆን በሞት የሚያስቀጣ ከፍተኛ ወንጀል ነበር፡፡ እናም የቅጣት ቦምብ ተጠመደላቸው፡፡ ባለፈው ሳምንት ብራዚልና ሜክሲኮ እየተጫወቱ ሳለ ማንም ባላሰበውና ባልጠበቀው ሁኔታ የተጠመደው ቦምብ ድንገት ፈነዳ፡፡ አገር ሰላም ብለው ጨዋታውን በመከተተል ላይ ከነበሩት ወጣቶች መካከል ሃያ አንዱ ወዲያውኑ ሲሞቱ፤ ሃያ ሰባቱ የሚሆኑት ደግሞ ቀላልና ከባድ ጉዳት ደረሰባቸው፡፡ ብዙዎችን ድንጋጤ ውስጥ የከተተ የብራ መብረቅ!

Saturday, 21 June 2014 14:42

ጎል ለምን በዛ?

20ኛው ዓለም ዋንጫ በጎል ብዛት የተንበሻበሸ ሆኗል፡፡ ትናንት ከምድብ 4 የሁለተኛ ዙር ጨዋታዎች በፊት በተደረጉት 23 ግጥሚያዎች ላይ 66 ጎሎች ከመረብ አርፈዋል፡፡ በአማካይ በአንድ ጨዋታ 2.87 ጎሎች ማለት ነው፡፡ ዓለም ዋንጫ በ32 ቡድኖች በሚደረጉ 64 ጨዋታዎች መካሄድ ከጀመረ ወዲህ በየውድድሩ አንድ ጨዋታ አማካይ የጎል ብዛት 2.5 ነው፡፡  በ2002 እኤአ ላይ 2.5፤ በ2006 እኤአ 2.3 እንዲሁም በ2010 እኤአ 2.3 ጎሎች በአንድ የዓለም ዋንጫ ጨዋታ በአማካይ ሲመዘገብ ነበር፡፡  ለጎሎች መብዛት የተለያዩ ምክንያቶችም እየቀረቡ ናቸው፡፡ ብራዙካ የተባለችው ኳስ አመቺነት፤ የቡድኖች አጨዋወት በአመዛኙ በማጥቃት ላይ የተመሰረተ መሆኑ፤ በርካታ ምርጥ የአጥቂ መስመር ተሰላፊዎች በየብሄራዊ ቡድኖቻቸው አስገራሚ ብቃት ማሳየታቸውና የብራዚል ስታድዬሞች ማራኪ ድባብ ይጠቀሳሉ፡፡ ብራዚላዊ ዚኮ  በዓለም ዋንጫው ጎሎች የበዙት የየብሄራዊ ቡድን አሰልጣኞች ግብ እንዳይቆጠርባቸው ከመከላከል ይልቅ አስቀድመው በማግባት ለማሸነፍ በተከተሉት ታክቲክ መሆኑን አስተያየት ሰጥቷል፡፡ ብዙዎቹ አሰልጣኞች የቡድናቸውን አጨዋወት በማጥቃት ላይ እንዲመሰረት ማድረጋቸውን ታዝቢያለሁ ብሏል ዚኮ፡፡ የጎሎች መብዛት የዓለም ዋንጫውን የፉክክር ድባብ አድምቆታል፡፡ በበየጨዋታው አጓጊ ድራማዎችና ልብ ሰቃይ ትእይንቶች እየተፈጠሩ ናቸው፡፡
በኮከብ ግብ አግቢነቱ ፉክክር ሶስት ተጨዋቾች በሶስት ጎሎች ተያይዘዋል፡፡ የጀርመኑ ቶማስ ሙለር እና ሆላንዳውያኑ ሮበን ቫን ፕርሲ እና አርያን ሩበን ናቸው፡፡ እያንዳንዳቸው ሁለት ጎሎች ያስመዘገቡት 7 ተጨዋቾች ደግሞ   የብራዚሎ ኔይማር፣ የአውስትራሊያው ቲም ካሂል፣ የኮሎምቢያው ጀምስ ሮድሪጌዝ፤ የክሮሽያው ማርዮ ማንዱዚክ፣ የፈረንሳዩ ካሬም ቤንዜማ፤ የአይቬሪኮስቱ ጀርቪንሆ እና የኡራጋዩ ሊውስ ሱዋሬዝ ናቸው፡፡



የፊፋ  ሽልማትና ቦነሶች
ለሽልማትና ለክለቦች ክፍያ በፊፋ የተዘጋጀው 576 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡ በ19ኛው ዓለም ዋንጫ ከነበረው በ37% ጨምሯል፡፡  ተጨዋቾቻቸውን ለሚያሳትፉ ክለቦች  ፊፋ 70 ሚሊዮን ዶላር እንደየደረጃው የሚከፍል ሲሆን ይኸም ከ4 ዓመት በፊት ከነበረው በ75 % ጭማሪ ታይቶበታል፡፡ ፊፋ በዓለም ዋንጫው ለሚሳተፉ ብሔራዊ ቡድኖች ለዝግጅት የሚሆን አስቀድሞ  1.5 ሚሊዮን ዶላር  ከመስጠቱም በላይ በውድድሩ ተሳታፊነት ብቻ ለ32ቱ አገራት ለእያንዳንዳቸው 8 ሚሊዮን ዶላር ይከፍላቸዋል፡፡ በገንዘብ ሽልማቱ ዝርዝር አከፋፈል መሰረት ዋንጫውን የሚያሸንፍ 35 ሚሊዮን ዶላር ሲከፈለው  ፤ ለሁለተኛ 25ሚ ዶላር፤ ለሦስተኛ ደረጃ 22 ሚሊዮን ዶላር ለ4ኛ ደረጃቨ 20 ሚሊዮን ዶላር  ይበረከታል፡፡ በሩብ ፍፃሜ የሚሰናበቱ 4 ቡድኖች እያንዳንዳቸው 14 ሚ. ዶላር ፤በጥሎ ማለፍ የሚሰናበቱ 8 ቡድኖች ለእያንዳንዳቸው 9 ሚ ዶላር እንዲሁም ከምድብ ለሚሰናበቱ 16 ቡድኖች 8ሚ.ዶላር ይከፋፈላል፡፡
የማበረታቻ ቦነስ እና ሌሎች ክፍያዎችን ለመስጠት ላለፉት 6 ወራት በየአገሩ ቃል ሲገባ ነበር፡፡  የስፔን ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች  የሻምፒዮናነት ክብራቸውን ካስጠበቁ በነፍስ ወከፍ 979ሺ ዶላር እንደሚታሰብላቸው ቃል መገባቱ  ከፍተኛው ቦነስ ነበረ፡፡ በትልልቅ ውድድሮች ላይ ከፍተኛ ግምት እየተሰጠው ብዙ  ለማይቀናው የእንግሊዝ ብሔራዊ ቡድንም  ለዋንጫ ድል የቀረበው ቦነስ ለእያንዳንዳቸው 587ሺ ዶላር ነው፡፡
 በአዘጋጇ ብራዚል  448ሺ ዶላር ቦነስ እንደምትሰጥ ሲገለፅ ለፈረንሳይ ቡድንም በተመሳሳይ መጠን  ቀርቧል፡፡ በጀርመን  408ሺ ዶላር ፤  በአሜሪካ 405ሺ ዶላር  እንዲሁም በሆላንድ ደግሞ 371ሺ ዶላር ቦነስ ለእያንዳንዱ ተጨዋች በነፍስ ወከፍ  ለመስጠት ተዘጋጅቷል፡፡
በማበረታቻ የቦነስ ክፍያዎች ዙሪያ በተለይ ብሔራዊ ቡድኖች እና ፌደሬሽኖቻቸው ከፍተኛ ውዝግብ መግባታቸው የተለመደው በአፍሪካ ነው፡፡ የካሜሮን ብሔራዊ ቡድን ተጨዋቾች በፌደሬሽን በኩል ስለሚሰጣቸው ክፍያ ውዝግብ ገብተው የምንፈልገው ካልተሟላ ልምምድ እናቆማለን ብለው መነጋገርያ ሆነዋል፡፡ በመጨረሻም የካሜሮን እግር ኳስ ፌደሬሽን ለእያንዳንዱ ተጨዋች በዓለም ዋንጫው አጠቃላይ ተሳትፎ 91.5ሺ ዶላር በመመደብ ውዝግቡን ሲያበርድ የተጨዋቾቹ ፍላጎት እስከ 160ሺ ዶላር ነበር፡፡  የጋና ብሔራዊ ቡድን ተጨዋቾች በበኩላቸው በየጨዋታው በሚያስመዘግቡት ድል የሚሰጣቸው የቦነስ ክፍያ 30% አስቀድሞ እንዲከፈላቸው ጠይቀዋል፡፡

ሲመረጡ “ልከኛ” የነበሩ የፓርላማ አባላት “ዙጦ” ሆነዋል

      የደቡብ አፍሪካ መንግስት ለበርካታ ዓመታት ኤችአይቪ/ኤድስን ለመቆጣጠር ከፍተኛ ትግል ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ የጤና ባለሙያዎች እንደሚሉት፤ አሁን ትኩረቱን ከልክ በላይ ውፍረት ላይ ማድረግ አለበት፡፡ መቀመጫውን ለንደን ባደረገው “Lancet” የተሰኘ የህክምና ጆርናል ላይ የታተመ ዓለም አቀፍ ጥናት እንዳመለከተው፤ ከደቡብ አፍሪካ አዋቂ ሴቶች ውስጥ 70 በመቶ ያህሉና 40 በመቶው ወንዶች ከልክ በላይ ወፍራሞች ናቸው፡፡ ልጆቹም ቢሆኑ ከውፍረት አላመለጡም ይለናል ጥናቱ፡፡ ሩብ ያህሉ ልጃገረዶችና 20 በመቶ የሚሆኑ ወንድ ልጆች ሲበዛ ወፍራም ናቸው፡፡ በዚህም የተነሳ ከስኳር በሽታ እስከ ልብ ህመም ድረስ ላሉ ደዌዎች የመጠቃት ዕድላቸው ከፍተኛ ነው - ዘ ኢኮኖሚስት እንደዘገበው፡፡
በደቡብ አፍሪካ ብቻ ሳይሆን በቀሩት የአፍሪካና ሌሎች ድሃ አገራትም በቀጣዮቹ ሁለት አስርት ዓመታት ከልክ በላይ የሆነ ውፍረት በከፍተኛ መጠን እንደሚጨምር የጠቆመው ጥናቱ፤ ከመጠን ያለፈ ውፍረት ከከተሞች መስፋፋትና ከኢኮኖሚ ዕድገት ጋር ተያይዞ የሚከሰት እንደሆነ አመልክቷል። ህፃናት በምግብ እጥረት በከፍተኛ ደረጃ በሚቀጭባቸው አካባቢዎች የአዋቂዎች ከልክ በላይ ውፍረት ይበልጥ እየጨመረ መምጣቱ አያዎ (Paradox) ነው ብለዋል-ተመራማሪዎች፡፡
ከልክ በላይ ውፍረት ለተለያዩ በሽታዎች የሚያጋልጥ ቢሆንም አብዛኞቹ ደቡብ አፍሪካውያን ግን በውፍረታቸው ደስተኞች ናቸው፡፡ የኑሮ ዘይቤያቸውንና የአመጋገብ ልማዳቸውንም የመቀየር ፍላጎት የላቸውም፡፡ ቃለ-መጠይቅ ከተደረገላቸው 25ሺ500 ደቡብ አፍሪካውያን መካከል 88 በመቶ የሚሆኑት አሪፍ ነው ብለው የሚያምኑት የሰውነት አቋም ወፍራምነትን እንደሆነ ጥናቱ ይጠቁማል፡፡
የጤና ሚኒስትሩ አሮን ሞትሶአሌዲ ግን በዚህ አይስማሙም፡፡ የህክምና ዶክተር የሆኑት ሚኒስትሩ፤ ጠዋት የእግር ጉዞ በማድረግና ጤናማ የአመጋገብ ልማድን በመተግበር  መሸንቀጥ እንደሚገባ አርአያ በመሆን እያሳዩ ይገኛሉ፡፡ የሥራ ባልደረቦቻቸው የእሳቸውን ምሳሌነት እንዲከተሉ ያደረጉት ጥረት ግን አልተሳካም፡፡
በያዝነው ወር መጀመርያ ላይ የደቡብ አፍሪካ የፓርላማ አባላት ካፊቴሪያቸው  ከልክ በላይ ለሆነ ውፍረት የሚዳርጉ ምግቦችን ያቀርባል ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡ አባላት ሲመረጡ “ጥሩና ልከኛ” ነበሩ ያለችው የአፍሪካ ብሄራዊ ኮንግረስ የፓርላማ አባል ሼይላ ሲትሆል፤ “አሁን ግን ሁሉም ዙጦ ሆነዋል” ብላለች - ዘ ኢኮኖሚስት እንደዘገበው።
በነገራችሁ ላይ ኢትዮጵያን በተመለከተ የወጣ ጥናት እንደሚጠቁመው፤ ለጊዜውም ቢሆን ከልክ በላይ ውፍረት እኛን አያሰጋንም፡፡ ሌላ የሚያሰጋን ነገር ግን አልጠፋም፡፡ ውፍረቱ ኢትዮጵያ ውስጥ የሌለው አመጋገባችን ላይ የተለየ ጥንቃቄ አድርገን አይደለም፡፡ በከተማ መስፋፋትና በኢኮኖሚ ዕድገት ገና በመሆናችን ነው፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የእንግሊዙ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ባወጣው ሪፖርት፤ ኢትዮጵያ በድህነት ከዓለም በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ይፋ አድርጓል - ከኒጀር ቀጥሎ ማለት ነው፡፡ ጐበዝ ድህነትን ለማጥፋት ብዙ ትጋትና ረዥም ጉዞ ይጠብቀናል፡፡ ግን የማይቻል ነገር የለም!!       


የምግብ ጭማሪ ምንድነው?
የምግብ ጭማሪ ማለት እንደ ምግብ አካል የሚቆጠር ሲሆን ምግብን ለማጣፈጥ፣ ለማቅለም፣ ሳይበላሽ ለማቆየት ወይም ለማሳመር የሚረዳ በምግብ ላይ የሚጨመር ማንኛውም ንጥረ ነገር ነው፡፡
የምግብ ጭማሪዎች በምግብ ውስጥ ለምን ይጨመራሉ?
የምግብ ጭማሪዎች የተለያዩ ጥቅሞች ያሉት ሲሆን ከዚህ በታች የተዘረዘሩት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
የምግብን ደህንነትን ለመጠበቅ - የተለያዩ የምግብ ጭማሪዎች ምግብን ለብክለት የሚያጋልጡ እንደ ሻጋታ፣ የተለያዩ ፈንገሶችና ባክቴሪያዎች እንዳይራቡና እንዳያድጉ ምቹ ያልሆነ ሁኔታን በመፍጠር ምግቡ ለረጅም ጊዜ ሳይበላሽ አገልግሎት ላይ እንዲውል ለማድረግ ጥቅም ላይ ይውላሉ፡፡
ተፈጥሯዊ የምግብ ንጥረ ነገርን ማሻሻል - የተለያዩ የምግብ ንጥረ ነገሮች እንደ ቫይታሚን፣ መዓድናት፣ ፋይበሮችና ሌሎች ለሰውነታችን አስፈላጊ የሆኑ ንጥረ ምግቦችን በተለያዩ የምግብ ጭማሪዎች መልክ በማዘጋጀት፣ በተፈጥሮ ምግቡ ውስጥ ያልነበረውን ወይም በተፈጥሮ ምግቡ ውስጥ የሚገኝ ቢሆንም በተለያዩ የምግብ ዝግጅቶች ወቅት የሚወገዱትን የምግብ ንጥረ ነገሮችን በመተካት፣ የምግቡን የንጥረ ነገር ይዘት በማሻሻል፣ በነዚህ ንጥረ ምግቦች እጥረት ሊከሰቱ የሚችሉ የህብረተሰብ የጤና ችግሮችን ለመከላከል ይረዳል፡፡
የምግብ ቃናን፤ ጣዕምን፣ ልስላሴንና እይታን ያሻሽላሉ - የተለያዩ ምግብ ጭማሪዎች በምግብ ውስጥ የሚጨመሩት የምግቡን ጣዕም ለመጨመር፣ ቃናውን ለማሻሻል፣ ቀለሙን ከተፈጥሯዊ ቀለሙ በማሻሻል ሳቢ ወደ ሆነ ቀለም ለመለወጥ እንዲሁም ልስላሴን በመጨመር የምግቡን ተፈጥሯዊ ይዘት በማሻሻል የምግቡን ተፈላጊ ለማድረግ ነው፡፡
የምግብ ጭማሪ ጥራትና ደህንነት ቁጥጥር
የምግብ ጭማሪን ምግብ ውስጥ በመጨመር የምግብን ተፈጥሯዊ ባህሪ በመለወጥ፣ የምግቡን ተወዳጅነት ለማሳደግ የሚደረገው ተግባር ከአባቶቻችን ጋር የቆየ ባህል ነው፡፡ ለምሳሌ ጨውን ፈጭቶ እንደ ሥጋና ዓሣ በመሳሰሉት በከፍተኛ ሁኔታ የሚበላሹ የምግብ አይነቶች ውስጥ በመጨመር፣ የምግቦቹን የመጠቀሚያ ጊዜ ለማስረዘም ይጠቀሙበት ነበር፡፡ የተለያዩ ቅመማ ቅመሞችን በመጠቀምም የምግቦቹን ጣዕምና ቃና የተሻለ ያደርጉ  ነበር፡፡
በአሁኑ ጊዜም ህብረተሰቡ ጣዕሙና ቃናው የተሻለ፣ በተለያዩ የምግብ ንጥረ ነገሮች የበለፀገ፣ ደህንቱ ተጠብቆ ለረዥም ጊዜ ሊጠቀምበት የሚችልና እይታው ማራኪ የሆነ ምግብ ለማግኘት ፍላጐቱ ከፍተኛ በመሆኑ፣ የተለያዩ የምግብ አምራች ድርጅቶች የተለያዩ የምግብ ጭማሪዎችን መጠቀም፣ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መጥቷል፡፡
የምግብ ጭማሪ ጥራትና ደህንነት አስመልክቶ፣ ከፍተኛ ሳይንሳዊ ምርምሮች እየተደረጉም ይገኛሉ፣ በሀገራችንም የነዚህን የምግብ ጭማሪዎች ጥራታቸውንና ደህንነታቸውን ጠብቀው ለህብረተሰቡ እንዲደርሱ የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድኃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደር እና ቁጥጥር ባለስልጣን፣ የተለያዩ የጥራትና ደህንነት ማረጋገጫ ሥራዎችን እያከናወነ ነው፡፡ ከነዚህም መካከል በሀገር ውስጥ እንዲሁም ውጭ አገር ተመርተው ወደ ሀገራችን በመግባት ለህብረተሰቡ እየቀረቡ የሚገኙትን የምግብ ጭማሪዎች ጥራትና ደህንነት ለማረጋገጥ የተለያዩ የቁጥጥር ስራዎችን ያከናውናል፡፡
ህብረተሰቡም የቁጥጥሩ ባለቤት በመሆን፣ የራሱን ጤና ራሱ ይጠብቅ ዘንድ፣ የምግብ ጭማሪዎች ጥራታቸውንና ደህንነታቸውን የጠበቁ እንዲሆኑ ለማረጋገጥ የሚከተሉትን ነጥቦች ማጤን ይጠበቅበታል፡፡
የምግቡን ጭማሪ ይዘትና ባህሪ በተቻለ መጠን ማወቅ፣
ሊያስከትል የሚችለውን የአጭርና የረዥም ጊዜ የጤና ችግር መገንዘብ፣
የምግብ ጭማሪው ማሸጊያ ላይ የተለጠፈውን ገላጭ ጽሑፍ በትኩረት መመልከትና ቢያንስ የሚከተሉትን መረጃዎች ያካተተ መሆኑን ማረጋገጥ:-
የምግብ ጭማሪው የንግድ ስም፣
የምግብ ጭማሪው አምራች ድርጅት፣ ስምና ሙሉ አድራሻ፣
የምግብ ጭማሪው በሌላ ምግብ ላይ በሚጨመርበት ጊዜ በምን ያህል መጠን መሆን እንዳለበትና ምን አይነት የባህሪ ለውጥ በምግቡ ላይ እንደሚያመጣ የሚገልፅ ጽሑፍ መኖሩን ማየት፣
በማሸጊያው ላይ በግልፅ “የምግብ ጭማሪ” የሚል ጽሑፍ መፈለግ፣
ምግቡ የተመረተበትና የመጠቀሚያ ጊዜው የሚያበቃበት ቀን፣
የምርት መለያ ቁጥር፣
የምግብ ጭማሪው አግባባዊ የአጠቃቀም፣ የአያያዝና የጥንቃቄ ሁኔታ የሚጠቁም ጽሑፍ መታተሙን ምግቡን ከመግዛቱና ከመጠቀሙ በፊት በጥሞና ተመልክቶ ማረጋገጥ ይኖርበታል፡፡
ምንጭ፡ (“የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና ጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን” የተገኘ)   

             በአርባ ምንጭ የአዞ እርባታ ጣቢያ ለጉብኝት ታድመናል፡፡ የጣቢያው አስጎብኚ ወ/ት ህይወት አሰፋ ትባላለች፡፡ ስለ አዞ አፈጣጠር ስታብራራ መስማት ያልፈለገን ሰው ሳይቀር በማራኪ አቀራረቧ እንዲያደምጣት ታስገድዳለች፡፡ አቀራረቧ እስከዛሬ በርካቶቻችን ስለ አዞ የምናውቀውን እውነታ አጥርቶ ትክክለኛ መረጃ እንድንይዝ የሚያደርግ ነው፡፡ ህይወት የተረከችውን የአዞ አፈጣጠር እንዲህ አቅርቤዋለሁ፡፡
“የአዞ ተፈጥሮ በህይወት አንደበት”
ሃይቅ ዳርቻ ላይ አዞ እናት ከውሃው ከ20 እስከ 30 ሜትር ትርቅና፣ 60 ሣ. ሜትር ያህል አሸዋውን ቆፍራ እንቁላሎቹን ትቀብራለች፡፡ እንቁላሎቹ አዞ ለመፈልፈል 90 ቀናት ይበቃቸዋል፡፡ ጫጩት አዞ ገና እንደተፈለፈለ አሸዋ ውስጥ ሆኖ ድምፅ ማሰማት ይችላል፡፡ አንድ አዞ ከ 3 ዓመት እስከ 6 ዓመት ባለው ጊዜ ውስጥ ለእርድ ይደርሳል፡፡ አዞ አናቱ ካልተመታ አይሞትም፡፡
የሚታረደውም እንደሌሎች የእርድ እንስሳት ከአንገቱ ስር ሳይሆን በጀርባው በኩል ነው፡፡ ምክንያቱም የስረኛው ቆዳ እጅግ ተፈላጊ ስለሆነ እንዳይጎዳ ነው፡፡
ቆዳቸው እስከ 400 ዶላር ይሸጣል፤ ስጋቸው ግን በማርቢያ ጣቢያው መልሶ ለራሳቸው ምግብነት እየዋለ ቢሆንም እየተገነባ ያለው ዘመናዊ ቄራ ሲጠናቀቅ፣ ሃገሪቱ የአዞ ስጋ ወደ ውጭ ትልካለች፡፡ አንድ ኪሎ የአዞ ስጋ በአሁኑ ወቅት እስከ 160 ዶላር ይሸጣል።
የአዞን ፆታ ለመለየት በሚገባ ስለ አዞ የሚያውቁ ሰዎች ያስፈልጋሉ፡፡ ማንም ሰው በእይታ ብቻ ይሄ ወንድ ነው፣ ይህቺ ሴት ነች ብሎ መለየት አይችልም። ባይን የሚታይ የፆታ መለያ አዞ ጨርሶ የለውም፡፡ የአዞዎች የፆታ ሁኔታ በባለሙያዎች የሚለየው የተፈለፈሉበትን አሸዋ ሙቀት በመለካት ነው፡፡ ሙቀቱ ከፍተኛ ከሆነ ወንዶች ይሆናሉ፤ ቀዝቀዝ ካለ ሴቶች ይሆናሉ፡፡
እናት አዞ፤ በአሸዋ ውስጥ የቀበረችውን እንቁላል በየጊዜው እየተመላለሰች ደህንነቱን ትከታተላለች። ከተፈለፈሉ በኋላ ድምፃቸውን ከአሸዋ ውስጥ ስትሰማ በአፏ እየያዘች ታወጣና ውሃ ዳር ሳር ውስጥ ታስቀምጣቸዋለች፡፡ ይህን የምታደርግበት ምክንያት ጫጩት አዞዎች ትናንሽ ነፍሳትን እንዲመገቡ ነው፡፡ በሌላ በኩል በውሃ ውስጥ የሚገኙ ትላልቅ አዞዎች እንዳይበሉባትም ለመከላከል ነው፡፡ እናት አዞ ልጆቿን ከአደጋ ለመጠበቅ ዛፍ ላይ ወጥታ 360 ዲግሪ እየተመለከተች በትጋት ቅኝት ታደርጋለች፡፡
ጫጩት አዞዎች ከጥርስ ጋር ስለሚፈጠሩ ገና ከአሸዋ ውስጥ ሲወጡ መናከስ ይጀምራሉ። የጥርሳቸው ብዛት ከ62 እስከ 66 ይደርሳል፡፡ አዞ በነዚህ ጥርሶቹ እየቆረጠ ዋጥ ማድረግ እንጂ ማኘክ፣ ማላመጥ የሚባል ጣጣ አያውቅም። ከስጋ ውጪም አዞ ሌላ ምግብ አያውቅም። አዞ ተንቀሳቃሽ ምላስ የለውም፤ ለዚህ ነው የማያላምጠው፡፡
አስጎብኚያችን ህይወት እዚህ ጋ ጥያቄ ልጠይቃችሁ አለች፡፡ የአዞ እንባ የሚባለው ምንድን ነው? አዞ ምግብ ሲበላ ያለቅሳል የሚባለውስ? ብላ ጠየቀችን፡፡ በርካቶች የመሰላቸውን ሞከሩ፤ አንዳቸውም ግን መልሱን አላወቁትም፡፡ እኔው መልስ ልስጥ አለችን፡፡
አዞ ቆዳው ጥቅጥቅ ነው፡፡ የላብ ማስወጫ የለውም። በብዛት ቆርጦ ሲውጥ ጉሮሮው ይጨናነቃል፡፡ ጎሮሮው ሲጨናነቅ ላብ ያልበዋል፡፡ ላቡ በአይኑ በኩል ይወጣል፡፡ ስለዚህ የአዞ እንባ ላብ ነው፡፡ አዞ ያስለቅሳል እንጂ አያለቅስም” አለችን፡፡
ስለ አዞ አንዳንድ እውነታዎች
አንዲት አዞ በአንድ ጊዜ ከ30-70 የሚደርስ እንቁላል ትጥላለች፣ በአመት አንድ ጊዜ ብቻ የምትጥል ሲሆን 85 በመቶው ይፈለፈላል። በአለም ላይ 25 ዓይነት የአዞ ዝርያዎች ሲኖሩ አራቱ በአፍሪካ ይገኛሉ፡፡ሰ በኢትዮጵያ የሚገኘው አደገኛው የናይል አዞ የሚባለው ብቻ ነው፡፡
አንድ ትልቅ አዞ ከ7-8 ሜትር ሲረዝም፣ ከ500-700 ኪ.ግ ይመዝናል፡፡ ከ120-150 አመትም ይኖራል፡፡ የአዞ ቆዳ በአለማቀፍ ደረጃ እጅግ ተፈላጊ ሲሆን ከ27-37 ሣ. ሜትር ስፋት ያለውና ሽንቁር የሌለው ንፁህ ቆዳ 1ኛ ደረጃ ተብሎ እስከ 400 ዶላር ይሸጣል፡፡





ቀለም የዘለቃቸው ዋሾዎች ከፖለቲከኞችም ይብሳሉ ተባለ!

           ባለፈው ሳምንት የአብዛኞቹ ሚዲያዎቻችን ሰበር ዜና የሆኑት ግለሰብ ለዚህ “ልዩ ጽሑፍ” መሰናዳት ሰበብ እንደሆኑኝ ለመግለጽ እወዳለሁ፡፡(እውነቱን መናገር ይሻላል ብዬ እኮ ነው!) ምስጋናውን ለማን ማቅረብ እንዳለብኝ ግን እርግጠኛ ስላልሆንኩ ለጊዜው “የምስጋና ማዕቀብ” ማድረጉን መርጬአለሁ፡፡ እናም በቀጥታ ወደ ርዕሰ ጉዳያችን እንግባ፡፡ ዛሬ አምዱ ለዋሾዎች ተለቋል (ድሮስ የማን ነበር አትሉኝም?)
ባለፈው ቅዳሜና እሁድ ምን ሰማሁ መሰላችሁ? እኚህ የትምህርት መረጃቸውን አስመልክቶ ዋሽተዋል የተባሉት ግለሰብ እንግዲህ አነቃቂ ንግግሮችን በማድረግ ይታወቃሉ አሉ ?! እናላችሁ ---- በሳቸው የማነቃቂያ ንግግር ተነሳስተው ለውጥ ያመጡ አንዳንድ ግለሰቦች በጣም ተናደዱ ተባለ፡፡ ለምን መሰላችሁ? የውሸት አነቃቅቶናል ብለው እኮ ነው። እኔ የምለው ---- “ፌክ ማነቃቂያ” አለ እንዴ? (“የወደቀ ዛፍ ምሳር ይበዛበታል” አሉ!) እንግዲህ በውሸት ማነቃቂያ ተነቃቅተን ነበር ያሉትን ሰዎች ወደቀድሞው “እንቅልፋቸው” መመለስ ከባድ ይመስለኛል፡፡ (የቀድሞ እንቅልፋቸውን ከፈለጉ ማለቴ ነው!)
እኔማ ምስኪኑ ከባባድ ውሸቶችን የሚዳፈሩት ፖለቲከኞች ብቻ ይመስሉኝ ነበር፡፡ ለካስ የቀለም ቀንድ የሚባሉትም ሳይቀሩ ድብን አድርገው ይዋሻሉና! (ተምሮ ውሸት አይደብርም?) ሰሞኑን ታዲያ በዋሾነት ዙሪያ የተደረጉ ጥናቶችን ሳነብላችሁ ነበር (“የቸገረው እርጉዝ ያገባል” አሉ!) እናላችሁ…ባለ ከባድ ሚዛን ዋሾዎች ሲገጥሟችሁ ነገርየውን የሞራል ጉዳይ ብቻ አድርጋችሁ አትመልከቱት፡፡ ጉዳዩ ህክምና የሚሻ በሽታ ወይም አደገኛ ሱስ  ነው ይላሉ - አጥኚዎቹ፡፡
መቼም ዋሾነትን በተመለከተ የሰለጠኑት አገራት ተመክሮ ምን እንደሚመስል መቃኘት ተገቢ ይመስለኛል፡፡ ለውድድርና ለንፅፅር ብቻ ሳይሆን ግንዛቤን ለማስፋትም ያግዛል፡፡ እናላችሁ---- ከኢንተርኔት ያገኘኋቸው በርካታ አስገራሚ መረጃዎች እንኳን ለእኔ ለናንተም የሚተርፍ ነው። (ለካ የሰለጠኑትም  ይዋሻሉ!) አሁን በቀጥታ የሰለጠኑ አገራትን የዋሾነት ተመክሮ ወደመቃኘቱ እንግባ፡፡ (የፅሁፉ ዓላማ መረጃ ማቀበል  እንደሆነ ይታወቅልኝ!) ከታላቋ እንግሊዝ እንጀምር። (እንግሊዝ የታሪኩ መቼት እንጂ ባለቤት አይደለችም!)
  እንግሊዛዊው የዝነኞች ሼፍ ሮበርት አይርቪንግ እ.ኤ.አ በ2008 ዓ.ም ከገዛ ራሱ የምግብ ዝግጅት የቴሌቪዥን ሾው የተባረረው በሌላ ሳይሆን በዋሾነቱ ነበር፡፡ ይሄ ዓለምአቀፍ ሼፍ ምን ቢዋሽ ጥሩ ነው? “የልኡል ቻርልስና የልዕልት ዲያናን የሰርግ ኬክ የሰራሁት እኔ ነኝ” ብሎ ማውራት ማስወራት ጀመረ፡፡ (ያለዕዳው ዘማች አሉ!) የማታ ማታ ታዲያ የልኡሉንና የልእልቷን ኬክ የሰራው ሌላ ሼፍ መሆኑ በመረጋገጡ አይርቪንግ ቅሌት ተከናነበ፡፡ ኬኩ በተሰራበት ት/ቤት ተገኝቶ ከመመልከት ባሻገር ለኬኩ ማስጊያጫ የሚሆኑ ፍራፍሬዎችን ያቀረበ ቢሆንም ፈፅሞ ኬኩን በመስራት አልተሳተፈም ነበር፡፡ ተዋረድ ሲለው ግን እኔ ነኝ የሰራሁት እያለ “ሲሰጥ” ከረመ (ሳይቸግር ጤፍ ብድር አሉ!)
አሁን ደግሞ ወደ አማሪካ መጥተናል፡፡ ማሪል ጆንስ በማሳቹሴትስ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ኮሌጅ ውስጥ ለ28 ዓመታት በዲንነት ያገለገለች ስትሆን መጀመርያ ስትቀጠር የባችለር ድግሪና ማስተርስ አለኝ ብላ ማመልከቻዋ ላይ ጽፋ ነበር፡፡ በመጨረሻ ግን ጆንስ  የኮሌጅ ድግሪ የሚባል ነገር ፈጽሞ እንደሌላት ይፋ ሆነ፡፡ (“አበስ ገበርኩ” ማለት ይሄኔ ነው!) ዋሾነቷ ያተረፈላት ነገር ታዲያ በውርደት ከስራ መባረርን ብቻ ነው፡፡ (ሰው 28 ዓመት ሙሉ ይዋሻል?)
ጆንስ በ2007 ዓ.ም ሥራዋን ስትለቅ በዩኒቨርስቲው ድረገጽ ላይ ባሰፈረችው ጽሑፍ፤ የትምህርት ማስረጃዎቿን በተመለከተ ለተቋሙ የተሳሳተ መረጃ ማቅረቧን ጠቁማ፣  ያኔ ለሥራ ስታመለክትም ሆነ ከዚያ በኋላ በነበሩት ጊዜያት የትምህርት ማስረጃዎቿን የማስተካከል ወኔ እንዳልነበራት ተናግራለች (የምን ወኔ ነው የምታወራው?!) አሁን ማሪል ጆንስ፤ በበርክሌይ ኮሌጅ ኦፍ ሚዩዚክ የተማሪዎች ቅበላ አማካሪ ሆና እየሰራች ትገኛለች፡፡ (ውሸት አያስከስስም እንዴ?)
የIBM ሶፍትዌርን የሚሰራው “ሎተስ ዴቨሎፕመንት” ፕሬዚዳንት ጄፍሬይ ፓፖስ ስለትምህርቱና የውትድርና ታሪኩ የተናገረው ሁሉ ቅጥፈት መሆኑ የታወቀው ዘግይቶ ነው፡፡ ፓፖስ ፓይለት ነበርኩ ቢልም የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪ ሆኖ የተገኘ ሲሆን የባህር ሃይል መቶ አለቃነቱንም በሻምበልነት ሽሮ ነው ሥራ የተቀጠረው፡፡ ይሄ ብቻ ቢሆን ጥሩ ነበር፡፡ ፒኤችዲውን ከፔፕርዲን ዩኒቨርሲቲ መቀበሉንም ለቀጣሪዎቹ ዋሽቶ ነበር፡፡ እውነቱ ሲወጣ ግን ፒኤችዲውን ያገኘው ዕውቅና ከሌለው የተልዕኮ ት/ቤት እንደሆነ ተጋለጠ።  ጄፍሬይ ፓፖስ ይሄን ሁሉ ቢዋሽም ከስራው አልተባበረም ነበር፡፡ ሆኖም ብዙም አልቆየ፡፡ የፆታ መድልዎ ፈጽሟል በሚል በቀረበበት ቅሬታ ሥራውን ለቀቀ። አሁን የMaptu Corp. and weblayers inc. ዋና ሥራ አስፈፃሚ በመሆን እየሰራ ይገኛል፡፡
በአንድ ወቅት የ”ሳሎሞን ስሚዝ ባርኔይ” ተቀጣሪ የነበረው ጃክ ግሩብማን፤ የዎልስትሪት ከፍተኛ ተከፋይ አናሊስት ነበር፡፡ በዓመት 20 ሚ. ዶላር የሚከፈለው (በወር ከ1.5 ሚ.ብር በላይ ማለት ነው) ጉድና ጅራት ከወደ ኋላ ነው እንዲሉ ግን፣መጨረሻ ላይ የተማረበትን ዩኒቨርሲቲ በተመለከተ መዋሸቱ ታወቀበት፡፡  እሱ እንዳለው፤ ከማሳቹሴትስ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ኮሌጅ አልነበረም የተመረቀው፡፡ ከቦስተን ዩኒቨርሲቲ እንጂ፡፡ (እንደ እኛ አገር ዋናው መመረቁ ነው ተብሎ አልታለፈም!)
ግሩብማን ውሸቱ መጋለጡን ተከትሎ ለቢዝነስ ዊክ በሰጠው ቃለምልልስ፤ የዋሸው የሥራ ደህንነት ስጋት ተሰምቶት ሳይሆን እንደማይቀር ተናግሯል። (የሥነ ልቦና ባለሙያዎች ግን የግብረገብነት ችግር ነው ባይ ናቸው!)
አሁን ግሩብማን፤ ለቴሌኮምና ለቴክኖሎጂ ኩባንያዎች የምክር አገልግሎት የሚሰጥ Magee Group የተባለ ኩባንያ አቋቁሞ እየሰራ ይገኛል፡፡ (አሁንስ እንመነው?)  የቀድሞ የያሁ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ስኮት ቶምፕሰን፤ መጀመሪያ የተቀጠረው በአነስተኛ የስራ መደብ ስለነበር፣ የትምህርት ማስረጃዎቹን በተመለከተ ነገሬ ብሎ የመረመረው አልነበረም። እሱም ታዲያ ተመቸኝ ብሎ በደንብ ዋሸ፡፡ ከስቶንሂል ኮሌጅ በአካውንቲንግና በኮምፒዩተር ሳይንስ ሁለት ዲግሪዎች ተቀብያለሁ በማለት፡፡
የቀድሞው “paypal” ፕሬዚዳንት ቶምፕሰን፤ በጃንዋሪ 2012 ዓ.ም የያሁ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሆኖ ሲሾም ነው ከዓመታት በፊት በገዛ እጁ የቀበረው ፈንጂ የፈነዳው፡፡ የያሁ ባለድርሻ የሆነው ዳንኤል ኤስ. ሎብ መረጃ ከየት እንዳገኘ ባይታወቅም የቶምፕሰንን የትምህርት ታሪክ ይፈትሽ ገባ። በመጨረሻም አዲሱ ሥራ አስፈፃሚ ቶምፕሰን በአካውንቲንግ እንጂ በኮምፒዩተር ሳይንስ ድግሪ እንደሌለው አረጋገጠ። የቶምፕሰንን ዋሾነት በመንቀፍ አስተያየቱን የሰጠው ዳንኤል ኤስ ሎብ፤ “አሁን ከመቼውም ጊዜ የበለጠ የያሁ ኢንቨስተሮች እምነት የሚጥሉበት ዋና ስራ አስፈፃሚ የሚያስፈልጋቸው ሰዓት ነው” ሲል የተናገረ ቢሆንም ለጊዜውም ቢሆን ዋና ሥራ አስፈፃሚው ይሄ ነው የሚባል እርምጃ አልተወሰደበትም፡፡  
የያሁ ሥራ አስፈፃሚ በዋሾነቱ የተነሳ ከስራው ባይባረርም፣ ከኃላፊነቱ ባይነሳም፣ የደሞዙ መጠን ባይቀነስም… ከሃፍረትና ከመሸማቀቅ እንደማይድን ቀጣሪዎቹ ነግረውት ነበር፡፡ (የዋሾነት ደሞዙ ሃፍረትና መሸማቀቅ ነው እንደማለት!) በነገራችሁ ላይ የእነዚህ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች የትምህርት ማስረጃ ማጭበርበር ጉዳይ አንድ ሰሞን የአሜሪካ ጋዜጦች ዋነኛ ርዕሰ ጉዳይ ሆኖ ነበር፡፡ (አንዱ ድግሪ የእውነት፣ ሌላኛው ድግሪ የውሸት እየሆነ አስቸገራቸዋ!)
ኬኔዝ ሎንቻር፤ “ቨሪታስ” የተባለውን ትልቁን የሶፍትዌር ኩባንያ የተቀላቀለው በ1997 ዓ.ም ነበር። ከአራት ዓመት በኋላ የውጭ ባለድርሻ አካላትን ውጤታማ በሆነ መንገድ በመምራት “CFo Magazine’s Excellence Award” አሸነፈ። በቀጣዩ ዓመት ግን ትከሻው ላይ የተደረበለትን የስኬት ፀጋ ተገፈፈ። ለምን ቢሉ? ከስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ አግኝቻለሁ ያለው MBA የውሸት መሆኑ በመረጋገጡ ነው። ከአሪዞና ስቴት ዩኒቨርሲቲ ተቀብያለሁ ያለውም የአካውንቲንግ ድግሪ ቅጥፈት ነው ተባለ፡፡ እሱ ድግሪውን ያገኘው ከአይዳሆ ዩኒቨርስቲ ነበር። ይሄንን ተከትሎም የኩባንያው የስቶክ ዋጋ በ20 በመቶ አሽቆለቆለ፡፡ ከዚያም ሎንቻር በኩባንያው የተዘጋጀለትን መግለጫ ሰጥቶ  ሥራውን እንዲለቅ ተጠየቀ፡፡
“በዚህ የተሳሳተ የትምህርት ማስረጃዬ አዝናለሁ። አሁን ባለው ሁኔታ ሥራዬን መልቀቄ ለእኔም ሆነ ለኩባንያው ጥቅም ይበጃል ብዬ አምናለሁ” ሲል ሚ/ር ኬኔዝ ሎንቻር የስንብት መግለጫውን ሰጥቷል።
በ1994 ዓ.ም “ሬዲዮ ሻክ”ን የተቀላቀለው ዴቪድ ኤድመንድሰን፤ የኩባንያውን የዕድገት መሰላል በከፍተኛ ፍጥነት ተወጣጥቶ፣ በ2005 ዓ.ም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ለመሆን በቅቷል፡፡ አዲሱን ሹመት ባገኘ በዓመቱ ግን “ፎርዝ ዎርዝ ስታር ቴሌግራም” የተሰኘው ጋዜጣ አንድ ውሸት አጋለጠ፡፡ ኤድመንድሰን ሥራውን ሲቀጠር እንደገለፀው፤ (እንደዋሸው ቢባል ይሻላል!) ከ “ኸርትላንድ ባፕቲስት ባይብል ኮሌጅ” በሥነ መለኮትና በሥነልቦና ድግሪውን አለማግኘቱን አረጋግጫለሁ አለ - ጋዜጣው፡፡  የሬዲዮ ሻክ የዳይሬክተሮች ቦርድ ዋና ሥራ አስፈፃሚው ከስራው እንዲባረር ባይፈልጉም ኤድመንድሰን ግን ሥራውን ለመልቀቅ ቅንጣት አላቅማማም፡፡ (ሃፍረቱ እንዴ ያሰራው?) “የትምህርቴን ጉዳይ በተመለከተ የተዛባ መረጃ  አቅርቤአለሁ፤ ለዚህ መዛባት ተጠያቂው እኔ ብቻ ነኝ። አሁን የሥነመለኮት ዲፕሎማ ማቅረብ እንደማልችል አውቃለሁ” ብሏል - ከመልቀቁ በፊት በሰጠው መግለጫ፡፡
የዓይን ጤና መጠበቅያ ምርቶችን የሚያቀርበው “Bausch and Lomb” የተሰኘው ኩባንያ የቀድሞ  ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሮናልድ ዛሬላም የዋሾነት ሰለባ ከመሆን አልዳኑም፡፡ እሳቸው ደግሞ ከኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ ኤምቢኤዬን ተቀብያለሁ በማለት ነው የዋሹት፡፡ በእርግጥ ትምህርቱን ጀምረውት ነበር፤ ሆኖም ዳር ሳያደርሱት ማቋረጣቸውን ዩኒቨርስቲው ጠቁሟል፡፡ እናም ለዚህ ዋሾነታቸው የ1 ሚሊዮን ዶላር ቦነሳቸውን አጥተዋል፡፡ ሥራቸውን ግን አላጡም፡፡ “ለኩባንያው በጣም አስፈላጊ ናቸው” ተብለው በሃላፊነታቸው ሊቀጥሉ ችለዋል፡፡ የማታ የማታ ግን (በ2008 ዓ.ም) ኩባንያው እጅግ በርካታ የታዘዙ ምርቶቹ ተመላሽ ሲሆኑና በፍ/ቤት ክስ ሲጨናነቅ ዛሬላም ጥለውት ውልቅ አሉ፡፡
የኖርዌይ ተወላጇ ሊቭ ሎበርግ፤ በፍ/ቤት ተከስሳ ጥፋተኝነቷ ከመረጋገጡ በፊት፣ ለበርካታ ዓመታት በጤና እንክብካቤ ዘርፍና በሌሎች የመንግስት ተቋማት በከፍተኛ የአስተዳደር ቦታዎች ላይ ተመድባ ስታገለግል ቆይታለች፡፡ (በአገሯ ኖርዌይ ማለት ነው!) በኖርዌይ የፕሮግረስ ፓርቲ ውስጥም በፖለቲከኛነት ተሳትፋለች፡፡ (ውሸት ለፖለቲከኛ ብርቁ አይደለም!)
በ2010 ዓ.ም ነው አንድ ጋዜጠኛ እውነቱን ያፍረጠረጠባት፡፡ ከለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ፣ ከኩዊን ሜሪ ኮሌጅና ከኖርጅስ ሃንድልሾይስኮሌ አግኝቻለሁ ያለቻቸው ድግሪዎች በሙሉ የውሸት እንደሆኑ ጋዜጠኛው አጋልጧል፡፡ ሌላው ቀርቶ በመንግስት የብቃት ማረጋገጫ የተሰጣት (Certified) ነርስ እንደሆነች ስትናገር የከረመችው ሁሉ ቅጥፈት መሆኑ ተነገረ፡፡ ሎበርግ፤ እንኳንስ ኮሌጅ ልትገባ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን እንኳን አላጠናቀቀችም ነው የተባለው፡፡ የነርስ ትምህርቷም የአንድ ዓመት የተግባር ትምህርት ብቻ እንደሆነ  ታውቋል፡፡ የዚህችን እንስት ጉዳይ ከሌሎቹ ለየት የሚያደርገው በፍ/ቤት መከሰሷ ነው፡፡ በ2012 ዓ.ም ፍ/ቤቱ ጥፋተኛነቷን አረጋግጦ፣ የ14 ወር እስርና የገንዘብ ቅጣት በይኖባታል፡፡ (በኖርዌይ ውሸት ያስከስሳል ማለት ነው?!) እንግዲህ የተለያዩ የውሸት ገፆችና መልኮችን ለመቃኘት ሞክረናል፡፡ የአገራችን የሥነልቦና ባለሙያዎች ዋሾነትን በተመለከተ የሚሰጡት ትንተና ምን እንደሆነ ባላውቅም የውጭዎቹ ግን አደገኛ በሽታ ስለሆነ የህክምና ባለሙያ እርዳታ ያስፈልገዋል ይላሉ። ዋሾዎቹ ወደ ወህኒ ቤት ከመወሰዳቸው በፊትም ሆስፒታል መግባት እንዳለባቸው ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ እናንተ ምን ትላላችሁ? እንዲህ ከሆነ እኮ ሆስፒታሎቻችን በሙሉ በፖለቲከኞች ሊጨናነቅ ነው፡፡ እነ ዓለም ባንክ የፋይናንስና የባለሙያ እገዛ ካላደረጉልን ነገሩን በራሳችን አቅም ብቻ  እንደማንወጣው እርግጠኛ ነኝ። (ወይስ ፀበል እንሞክር ይሆን?)

Saturday, 21 June 2014 14:23

የፖለቲካ ጥግ

ምንም ዝግጅት አያስፈልገውም ተብሎ የሚታሰብ ብቸኛው ሙያ፣ ፖለቲካ ሳይሆን አይቀርም፡፡
ሮበርት ሉዊስ ስቲቨንሰን
ፖለቲካ፤ ሰዎች በትክክል በሚመለከቷቸው ጉዳዮች ላይ እንዳይሳተፉ የመከልከል ጥበብ ነው፡፡
ፓውል ቫለሪ
አልፎ አልፎ ሁሉንም ሰው ልታሞኝ ትችላለህ፡፡
አንዳንዱን ሰው ሁልጊዜም ልታሞኘው ትችላለህ።
ሁሉንም ሰው ግን ሁልጊዜ ልታሞኘው አትችልም፡፡
አብርሃም ሊንከን
አገርን በትክክል መምራት የሚያውቁበት ሰዎች በታክሲ ሹፌርነትና በፀጉር አስተካካይነት ሥራ መጠመዳቸው በእጅጉ ያሳዝናል፡፡
ጆርጅ በርንስ
ፖለቲከኞች የትም ዓለም ላይ አንድ ናቸው፡፡ ወንዝ በሌለበትም ጭምር ድልድይ እንሰራለን ብለው ቃል ይገባሉ፡፡
ኒኪታ ክሩስቼቭ
ፖለቲካ ከፊዚክስ የበለጠ አስቸጋሪ ነው፡፡
አልበርት አንስታይን

አዲሱ የበጀት ዝርዝር ስለ ሠራተኞች ደሞዝ የሚለው ነገር አለ
ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ይኖራል። የግድ ነው። ለምን? ሶስት ምክንያቶች አሉ።
ለመጪው ዓመት የተመደበው የደሞዝ በጀት(ከነመጠባበቂያው)፣ ከዘንድሮው በ66% ይበልጣል
በጀቱና መጠባበቂያው ከ11.5 ቢ ብር ወደ 19.1 ቢ ብር እንዲጨምር ተደርጓል (የ7.6 ቢ ብር ጭማሪ)
ጊዜው የምርጫ ጊዜ ነው። የመንግሥት ሠራተኞችን በከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ማንበሻበሽ ያዋጣል
ግን ማን ያውቃል! የደሞዝ ጭማሪ ላይኖር ይችላል። ለምን? ሶስት ምክንያቶች አሉ
ባልተለመደ ሁኔታ አብዛኛው የበጀት ጭማሪ “መጠባበቂያ” ተብሎ ነው የተያዘው  (6.5 ቢ. ብር)
ጊዜው የምርጫ ነው። ምርጫ ሲቃረብ ደሞዝ እንደማይጨመር አቶ መለስ ዜናዊ ተናግረው ነበር።
የመንግስት ሠራተኞች ወፍራም ጭማሪ ቢያገኙ የዋጋ ንረትና የኑሮ ውድነት ሊፈጠር ይችላል

የመንግስት ሠራተኞችን ደሞዝ በተመለከተ ለ2007 ዓ.ም የተዘጋጀው በጀት፣ ከወትሮው በተለየና ባልተለመደ ሁኔታ፤ የተምታታ ወይም የሚያምታታ ሆኗል። “ደሞዝ ይጨመራል ወይስ አይጨመርም?” ለሚለው ጥያቄ፣ ከበጀት ምደባው ቁርጥ ያለ ምላሽ ማግኘት የለብንም እንዴ? በጀት ማለትኮ እቅድ ነው። በተወሰነ ጊዜ ውስጥ፣ “ይህን ይህን ያህል ገንዘብ ከዚህና ከዚህ አገኛለሁ”፤ “ያንን ያንን ያህል ገንዘብ ለዚያና ለዚያ እከፍላለሁ” ብሎ እቅጩን መናገር አለበት፡፡ የዘንድሮው በጀት ግን፣ በተለይ የሠራተኞችን ደሞዝ በተመለከተ፣ ቁርጡን ለመናገር የፈለገ አይመስልም።
በእርግጥ በ2007 ዓ.ም ለደሞዝ ክፍያ ይውላል ተብሎ የተመደበው አጠቃላይ በጀት፣ በጣም ብዙ ነው። ከዘንድሮው ጋር ሲነፃፀር በ7.6 ቢሊዮን ብር ይበልጣል። ዘንድሮ ለደሞዝ ክፍያ ከነመጠባበቂያው ተይዞ በነበረው 11.5 ቢሊዮን ብር በጀት ላይ፣ ድንገት በአንድ ጊዜ 7.6 ቢሊዮን ብር እንዲጨመርለት የተወሰነው በምን ምክንያት ይሆን? የሠራተኞች ደሞዝ “በወፍራሙ” ካልተጨመረ በቀር ይሄን ሁሉ ገንዘብ መመደብ አስፈላጊ አይደለም። ሌላ ምክንያት ሊኖረው አይችልም። እንዴት በሉ፡፡
የደሞዝ በጀት ላይ ከፍተኛ ጭማሪ የታየበት አመት ቢኖር በ2003 ዓ.ም ነው። ያኔ ታዲያ፤ የደሞዝ በጀት በ40 በመቶ እንዲያድግ የተደረገው፤ በሌላ ምክንያት ሳይሆን ለመንግስት ሠራተኞች የደሞዝ ጭማሪ ስለተሰጠ ነው። የመጪው አመት የደሞዝ በጀት ጭማሪ ግን ከዚህም ይልቃል - ከዘንድሮው በጀት ጋር ሲነፃፀር በ66% ይበልጣል። ይህም ለመንግስት ሠራተኞች ቀላል የማይባል ደሞዝ ለመጨመር መታሰቡን ያረጋግጣል። በዚያ ላይ አስቡት።
የ2007 ምርጫ እየተቃረበ ነው። ገዢው ፓርቲ፣ የደሞዝ ጭማሪውን ለምርጫ ዘመቻ ሊጠቀምበት ከፈለገ፤ ትክክለኛው ጊዜ አሁን ነው።
ደግሞስ ብዙዎቹ የመንግስት ሠራተኞች የገዢው ፓርቲ አባላት አይደሉ? “ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ” በሚለው ፈሊጥ ዳጎስ ያለ የደሞዝ ጭማሪ ቢያሸክማቸው ማንም አይከለክለውም። በእርግጥም ሳያሳንስ የሚቆርሰው ከየራሱ ምጣድና መሶብ እስከሆነ ድረስ፣ “ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ” የሚለው አባባል ቅንጣት ስህተት አይወጣለትም። ችግሩ ምን መሰላችሁ? ለመንግስት ሠራተኞች ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ለመስጠት፣ ገንዘብ ያስፈልጋል። ገንዘቡ ደግሞ ከሰማይ አይዘንብም። ከሌሎች ዜጎች ኪስ መውሰድ የግድ ሊሆን ነው። ከሌሎች ዜጎች ማዕድ ላይ ቆርሶ መውሰድ... ይሄ ነው ችግሩ።
ሌላኛው አማራጭ የብር ኖት በገፍ ማተም ነው። ምን ዋጋ አለው? ይሄኛው አማራጭም፤ የዋጋ ንረትን በማስከተል የዜጐችን ኪስ ያኮሰምናል፡፡
የሆነ ሆኖ፤ ለደሞዝ የሚመደበው በጀት ታይቶ በማይታወቅ ከፍተኛ መጠን እንዲጨምር ተደርጓል። ከምርጫው ጋር ግንኙነት ይኑረውም አይኑረው፤ የገንዘቡ ምንጭ ምንም ይሁን ምን፤ በጀቱ ሙሉ ለሙሉ ሥራ ላይ ሊውል የሚችለው፣ ለመንግስት ሠራተኞች ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ከተደረገ ብቻ ነው። አለበለዚያ የወረቀት በጀት ሆኖ ይቀራል። ስለዚህ የመንግስት ሠራተኞች ያለ ጥርጥር ደሞዝ ይጨመርላቸዋል ብለን በእርግጠኛነት መናገር እንችላለን፡፡
ግን፤ በጀቱ የወረቀት በጀት ሆኖ ቢቀርስ?
እውነት ነው፤ መንግስት ለሠራተኞቹ ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ለመስጠት ቢወስንም፤ ሙሉ ለሙሉ የቆረጠለት አይመስልም። ለምን በሉ። የበጀት ድልድሉ፣ ከሌላው ጊዜ ይለያል። እንደወትሮው ቢሆን፣ አብዛኛው የደሞዝ በጀት፣ ለእያንዳንዱ መሥሪያ ቤት ምን ያህል እንደሚደርሰው በዝርዝር ተሸንሽኖ ይቀርባል። የተወሰነ ገንዘብ ደግሞ መጠባበቂያ ተብሎ ይቀመጣል። ለእያንዳንዱ መሥሪያ ቤት ከተመደበው የደሞዝ በጀት ባሻገር አንዳች ያልተጠበቀና ያልታሰበ ወጪ ቢያጋጥም ችግር አይፈጠርም። የደሞዝ መጠባበቂያ የሚያስፈልገው ለዚህ ለዚህ ነው። ካቻምናና ከዚያ በፊት በየአመቱ 150 ሚ. ብር  የደሞዝ መጠባበቂያ ይመደብ ነበር። አምና ደግሞ 200 ሚ. ብር። ለዘንድሮ የተቀመጠው የደሞዝ መጠባበቂያ 350 ሚ. ብር ነው።
ለመጪው አመት የተመደበው የደሞዝ መጠባበቂያ ግን፣ ከእስከዛሬው በእጅጉ በእጅጉ ይለያል። 6.5 ቢሊዮን ብር ነው የደሞዝ መጠባበቂያ ተብሎ የተመደበው። ለምን? የገንዘብ ሚኒስትሩም ሆኑ የበጀት ሰነዱ፣ በዚህ ጉዳይ ላይ ትንፍሽ ያሉት ነገር የለም። ለነገሩ፤ ጥያቄ ለመሰንዘር ትንፍሽ ያለ ፓርቲ፣ ፖለቲከኛ ወይም ምሁርም የለም። “ለ12.6 ቢሊዮን ብር መደበኛ ደሞዝ 6.5 ቢሊዮን ብር መጠባበቂያ! ኧረ እንዲህ አይነት መጠባበቂያ በታሪክ ታይቶ አይታወቅም! ምንድነው ነገሩ?” የሚል ጥያቄ እስካሁን አልቀረበም።
እንዲህ ጉዳዩ እንደተድበሰበሰ በጀቱ ቢፀድቅ፤ ምን ሊፈጠር እንደሚችል አስቡት። ምንም አይፈጠርም፡፡ መንግስት ለሠራተኞቹ ደሞዝ የመጨመርና ያለመጨመር አማራጮች ይኖሩታል። ከፈለገ ደሞዝ ይጨምራል። የበጀት እጥረት አይገጥመውም። የደሞዝ መጠባበቂያ ተብሎ የተመደበ ብዙ ገንዘብ አለለት። ካልፈለገ ደግሞ ደሞዝ አለመጨመር ይችላል። መጠባበቂያውን ትቶ፤ ለየመሥሪያ ቤቱ ተከፋፍሎ የተመደበውን የደሞዝ በጀት ብቻ ይጠቀማል። በሌላ አነጋገር፣ “መንግስት ደሞዝ ለመጨመርና ላለመጨመር እያመነታ ይሆን ነገሩን በእንጥልጥል ለማቆየት ፈልጐ ይሆን?” ብለን እንድናስብ ይገፋፋናል - ያልተለመደው የበጀት አመዳደብ፡፡
ነገር ግን በደፈናው “የደሞዝ መጠባበቂያ” ተብሎ 6.5 ቢ.ብር የተመደበው በሌላ ምክንያት ሊሆን ይችላል። የበጀት ዝግጅት ሲጀመር፣ ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ መነሳቱ አይቀርም። ከተወሰነ ክርክር በኋላ፣ ሃሳቡ ውድቅ ይሆንና፣ ዝርዝር በጀት ይዘጋጃል። የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ያዘጋጀው ሰነድ እንደሚገልፀው፤ የየመሥሪያ ቤቱ ዝርዝር የበጀት ድልድል የተዘጋጀው የደሞዝ ጭማሪ አይኖርም በሚል መመሪያ ነው፡፡ የበጀት ዝግጅቱ ከተጋመሰ በኋላ ወይም ሊጠናቀቅ ከተቃረበ በኋላ፤ መንግስት ሃሳቡን ቢቀይርስ? ማለትም፤ ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ እንደገና ይነሳል። ለምን?
የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ ስለሚዋዥቅ፤ ከዚሁ ጋር አብሮ የመንግስት ሃሳብም ቢዋዥቅ አይገርምም። ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ ከወራት በፊት ውድቅ ቢደረግ፣ ከጊዜ በኋላ ፖለቲካው ሲንገራገጭ እንደገና ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ ይነሳል፤ ባለቀ ሰዓትም ተቀባይነት ያገኛል። ነገር ግን፣ በዝርዝር የተዘጋጀውን በጀት እንደገና ለመከለስ ቀላሉ ዘዴ ምንድነው? ለደሞዝ ጭማሪ የሚያስፈልገውን በጀት፣ በደፈናው “መጠባበቂያ” ተብሎ እንዲገባ ማድረግ ነው ቀላሉ ዘዴ።
ግን ከምር የሠራተኞች ደሞዝ ይጨመራል? አንዱ ችግር፤ 2007 ዓ.ም የምርጫ አመት መሆኑ ነው፡፡ ታስታውሱ እንደሆነ በ2002 ዓ.ም ለሠራተኞች ደሞዝ እንዲጨመርላቸው ጥያቄ ቀርቦ ነበር፡፡
የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ጥያቄውን አልተቀበሉትም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥያቄውን ውድቅ ያደረጉት “ለመንግስት ሠራተኞች ደሞዝ ሊጨመርላቸው አይገባም” በሚል አይደለም፡፡ ምርጫ በሚቃረብበት ወቅት ለመንግስት ሠራተኞች ደሞዝ መጨመር የአገሪቱን ፖለቲካ እንደሚያበላሽ የተናገሩት አቶ መለስ፤ ኢህአዴግ በምርጫ አመት የደሞዝ ጭማሪ እንደማያደርግ ተናግረው ነበር - በ2002 ዓ.ም፡፡ በ2007ስ?

     በሥልጣኔ በተራመዱት አገራት፣ ትልቁ የፖለቲካ መከራከሪያ ምን መሰላችሁ? “የመንግስት በጀት” ነው። ታስታውሱ እንደሆነ፤ ከአመት በፊት በርካታ የአሜሪካ የመንግስት መሥሪያ ቤቶች በበጀት ክርክር ሳቢያ ለሳምንታት ያህል ተዘግተው ቆይተዋል፡፡
የተፎካካሪ ፓርቲዎች የበጀት ክርክር መቼም ቢሆን አያባራም፡፡ የእንግሊዝ ፓርላማ አብዛኛውን ጊዜ የሚሟሟቀው በበጀት ሙግት ነው፡፡ የጣሊያን፣ የፈረንሳይ፣ የግሪክ፣ የስፔን መንግስታት ሲንገዳገዱና ከስልጣን ሲወርዱ የምናየው፤ የአውሮፓ መንግስታት በኢኮኖሚ ቀውስ ሲወዛገቡና ጐዳናዎች በተቃውሞ ሰልፍ ሲጥለቀለቁ የምንመለከተው በሌላ ምክንያት አይደለም፤ በበጀት ጉዳይ እንጂ፡፡ በእርግጥም የፓርቲዎችና የፖለቲከኞች የአስተሳሰብ ልዩነት፣ በተጨባጭና በግላጭ አፍጥጦና አግጥጦ የሚወጣው፣ የበጀት መጠንና አመዳደብ ላይ ነው።
ወደ ነፃ ገበያ ሥርዓት የሚያዘነብሉ ፓርቲዎች፣ ለምሳሌ በአሜሪካ ሪፐብሊካን ፓርቲ፤ የእንግሊዝ ኮንሰርቫቲቭ ፓርቲ በተቻለ መጠን የመንግስት በጀት በየጊዜው እያበጠ እንዳይሄድ ይከራከራሉ። በአብዛኛው፣ ለፍርድ ቤቶች፣ ለህግ አስከባሪና ለመከላከያ ሃይል የሚመደበው በጀት ግን እንዲቀንስ አይፈልጉም፡፡ በተቃራኒው ለነፃ ገበያ ሥርዓት ያን ያህልም ፍቅር የሌላቸውና  ገናና መንግስት እንዲኖር የሚፈልጉ ፓርቲዎች ደግሞ፤ መንግስት ሁሉም ነገር ውስጥ እንዲገባ እየገፋፉ፣ ለዚህኛውም ለዚያኛውም በጀት እንዲጨመር ይወተውታሉ። በአጭሩ፤ የፓርቲዎች የፖለቲካ አቋም በተግባር የሚገለጠው የበጀት አመዳደብ ላይ ስለሆነ አጥብቀው ይከራከራሉ።
እንደ “አለመታደል” ሆኖ፣ በኛ አገር በበጀት ጉዳይ የሚከራከርና የሚሟገት ፓርቲም ሆነ ፖለቲከኛ ብዙ አይታይም። መንግስት ለ2007 ዓ.ም ያዘጋጀው የበጀት ዝርዝር ለፓርላማ ከቀረበ ሁለት ሳምንት አለፈው። ገንዘቡም ቀላል አይደለም። ከ178 ቢሊዮን ብር በላይ ነው። ከዜጎች ጠቅላላ አመታዊ ገቢ (ምርት) ውስጥ ሩብ ያህሉ ማለት ነው። ግን፣ ስለ በጀቱ መጠንና አመዳደብ እስካሁን ለምልክት ያህል እንኳ ውይይትና ክርክር አልሰማንም።
አንደኛ፤ የበጀቱ መጠን፤ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ፣ የዜጎችን ኪስና ኑሮን ይነካል። መንግስት፤ በየአመቱ የብዙ ቢሊዮን ብር በጀት የሚመድበው ታክስ በመሰብሰብና የብር ኖት በማሳተም ነው፡፡ ታክስ የሚሰበሰበው ከዜጎች ኪስ ነው። በ2000 ዓ.ም እና በ2003 ዓ.ም እንደተደረገው መንግስት የብር ኖት በገፍ አትማለሁ የሚል ከሆነም፤ በዋጋ ንረትና በኑሮ ውድነት የዜጐች ህይወት ይጐሳቆላል፡፡ ሁለተኛ፤ የበጀቱ መጠን ብቻ ሳይሆን የበጀቱ አመዳደብም የዜጐችን ኑሮ ይነካል። ለምሳሌ… ላለፉት 7 አመታት... “በዚህ ዓመት ግንባታቸው ይጠናቀቃል” እየተባለ፣ በየአመቱ ከቢሊዮን ብር በላይ ሲመደብላቸው የነበሩ የተንዳሆ፣ የከሰም፣ ከዚያም የርብ ግድቦች... በመጪው አመትም ከቢሊዮን ብር በላይ ይመደብላቸዋል። ገንዘቡ የት እየገባ ይሆን ግንባታዎቹ ለአመታት የተጓተቱት?
ሃብት በማባከን ዋና ተጠቃሽ ሆነው ለተገኙት ዩኒቨርስቲዎች የሚመደበው በጀትስ? በትምህርት ሚኒስቴር ስር ለሚተዳደሩት ዩኒቨርስቲዎችና ተቋማት፣ ዘንድሮ 25 ቢሊዮን ብር እንደሚመደብላቸው ስንሰማ፣ ይሄ ሁሉ ብር የት ይገባ ይሆን ብለን በደንብ ማሰብ አያስፈልገንም? ይህንን እንደ ዋነኛ ሥራ የሚቆጥሩ ፖለቲከኞች የሚፈጠሩት መቼ ይሆን? ምሁራንስ?

“የሚስቅልህ ሰው ስለበዛ፣ ትክክል ነኝ ብለህ አታስብ”
(የእንግሊዞች አባባል)

ከዕለታት አንድ ቀን አንደ ቀንድ - አውጣ (Snail) ወደ አንድ ቡና ቤት ከመሸ በኋላ ይሄዳል፡፡ ከዚያም በሩን ያንኳኳል፡፡
ባለቡና ቤቱ፤ በሩን ዘጋግቶ እየጨራረሰ ነው፡፡
“ማነው?” ይላል የቡና ቤት ባለቤት፡፡
“እኔ ነኝ!” ይላል ቀንድ አውጣ፡፡
“ትንሽ መጠጣት ፈልጌ ነበር”
“መሸኮ! ከዚህ ወዲያ አላስተናግድም!”
“እረ በእግዚሃር አስተናግደኝ! ምንም ሄጄ እምዝናናበት ቦታ የለኝም፡፡ የት እንደምሄድም አላውቅም! እባክህ ተባበረኝ!”
“አያ ቀንዳውጣ! እየዘጋሁ ነው ስልህ ምንድን ነው ችግርህ? ትመለሳለህ ተመለስ አለበለዚያ ዋጋህን ታገኛለህ! ተግባባን?”
“ባለቡና ቤት፤ እኔ አንድ ነገር ሳልቀምስ ወደ መኝታዬ መሄድ አልችልም! ይገባሃል?”
“ቆይ እንግዲህ እንዲገባህ ምን ማድረግ እንደምችል አሳይሃለሁ!” እያለ የዘጋውን በር ይከፍትና ይወጣል፡፡
ቀንድ - አውጣው በሁኔታው ተደስቶና የበለጠውን ዕውነት አስረዳዋለሁ ብሎ ፍንድቅድቅ ብሏል፡፡
ሰውዬው ግን ንግግሩን ሁሉ አቋርጦ በንዴት ተወጥሮ ወደውጪ መጣና፤
“አንተ ማነኝ ብለህ ነው ይሄ ሁሉ ጉራ? ይሄ ሁሉ ያዙኝ ልቀቁኝ ማለት?” ሲል ጠየቀው፡፡
ቀንዳውጣውም፤
“ጌታዬ፤ ውሃ ጠምቶኝ ነው ያስቸገርኩህ፡፡ እባክህ…” ብሎ ሳይጨርስ፣ ባለሆቴሉ ባለ በሌለ ኀይሉ በቲራ ጠረገው፡፡ ቀንድ አውጣው ሩቅ ከመሽቀንጠሩ የተነሳ፤ የት ሄዶ እንደወደቀ እንኳን ያየው የለም!!
ከአንድ ዓመት በኋላ ቀንድ አውጣው ወደዚያው ሆቴል መጣ፡፡ ዛሬም ሰዓቱ በጣም ረፍዷል፡፡ ያ ባለ ሆቴል በሩ ሲንኳኳ፤
“ማነው?” አለ፡፡
“እኔ ነኝ!”
“ማ?”
“እኔ ቀንድ አውጣ!”
“አንተ ዛሬም ልትለክፈኝ መጣህ?”
“አይ፤ ዛሬስ አንድ ጥያቄ ብቻ ኖሮኝ ነው የመጣሁት”
ባለሆቴሉ ወጣና፤
“ምንድን ነው የፈለከው?”
ቀንዳውጣውም፤
“አንዲት ጥያቄ ብቻ ናት ያለችኝ፡፡”
“እሺ ተናገር?”
“ባለፈው ዓመት አሽቀንጥረህ ከጣልከኝ ቦታ እዚህ ለመድረስ ተጉዤ ተጉዤ፤ ይሄው ዛሬ ደረስኩኝ፡፡ ለመሆኑ ለምን ነበር እንደዛ በቲራ የመታኸኝ?!”
*    *    *
በየትኛውም ሰዓት ያረፈደ ሰው፤ ቅጣቱ እንደተጠበቀ መሆኑን አንርሳ፡፡ ማንም በመሸ ሰዓት ረግጦ ሊያሽቀነጥረን እንደሚችልም እንገንዘብ፡፡
ማዝገማችን፣ መንቀርፈፋችንና መዘግየታችን በራሱ መልክና ጊዜ ወደኛው ፊቱን አዙሮ እንደቀንድ አውጣው ሊያስመታን መቻሉ አይቀሬ ነው፡፡ ለምን ሆነ? ብለን በዓመቱ መጠየቅ ቢያንስ መሳቂያ ከመሆን አያሳልፈንም፡፡ ሌሎች ውቴላቸውን ዘግተው ሳይቆልፉ በፊት ነቅቶ መምጣት ብልህነት ነው፡፡
የሀገራችን ስሞች አስገራሚ ናቸው፡፡ በወትሮ ማዕረጉ የሹም/የንብረት ባለቤት የምንለው፤ ስሙ የኃደራ ስም ይባላል፡፡ ባላገር፣ ወታደር፣ ባላባት፣ ስደተኛ፤ ባለቤት እንዲሉ፡፡ የሀገር ባለኃደራነት መሆኑ ነው፡፡
የማኅደር ስም የሚባል አለ ደግሞ፡፡ አደራችንን አንዘንጋ የሚል የማደሪያ ስም ነው፤ ቃሉ፡፡ በየጊዜው ቃል ስንገባም “ዕውን እፈጽመዋለሁ? እንበል፡፡ የመሬት፣ የቦታ ርስት ወዘተ ንብረት ባለቤትነት ዶሴ እንደማለት ነው፡፡ የሚገርመው የማህደርም፤ የባለኃደራም ሌብነት ነበር፡፡ የዱሮ ዘመን ባለቤትነት ከዛሬ ሊለይ ይችላል፡፡ እንደ እውነቱ ግን ሁሉም ከላይ እየታዘዘ ከመፈፀሙ አኳያ፤ የቋንቋ ነገር ካልሆነ በቀር  ሁሉም ስሙ “ሙስና” ነው፡፡
የተቀብዖ ስም እንዲል መጽሐፍ ሹመት ብቻውን ፍሬ አያፈራም! የተቀባንበት፣ የተሾምንበት፣ ኃላፊነት የተቀበልንበት ስም ያው የተቀብዖ ስም ነው፡፡ ታዲያ “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋልን”፣ “ከሰው መርጦ ለሹመት፣ ከእንጨት መርጦ ለሹመት”ን እንደበቀቀን እያቀነቀንን፤ እስከመቼ እንጓዛለን? ምንም ዓይነት ኮርስ ልውሰድ፣ ዋናው ቁም ነገር፣ “ሹመቱ ለአገር እንዳገለግል፣ ኃላፊነቴን እንድወጣ ነው” እንላለን? ወይስ በሹምነቱ ዘመን ያልበላ፣ እየበላ ያለና ወደፊትም የማይበላ ማን ሹም አለ? ከበይው የሚይቋደስ፣ ባለ አላባ፣ ባለ ኮሚሽንስ ማን አለ?
ሐዲድ ተሠራ ስንል ሲመነቀል፣ አገር ያደነቀው ምሁር አፈራን ስንል፤ “አያሌው ሞኙ ሰው አማኙ” ሲለን፣ ውጪ አገር ወኪል አድርገን ስንልክ “አፍንጫችሁን ላሱ” ሲለን፤ ምን ዓይነት ተዓማኒነት ልናስተናገድ ነው?
“እያንዳንዱ አሣ አጥንት እንዳለሁ ሁሉ፤ እያንዳንዱ ሰው ስህተት አለው” ይላሉ አዋቂዎች፡፡ ሆኖም ይህን ብሂል መሠረት አድርገን ስንሳሳት፣ አውቀን ስንሳሳትና ለሁሉም ዋናው ሰበብ ማግኘት ነው ስንባል መክረማችን፤ አሳሳቢ ነው፡፡
“አንድ ‹ባሪያ› በምድር ላይ እየተጓዘ እስካለ ድረስ ያንተ ነፃ መሆን (ተዓምር) ፍፁም አልሆነም!” ይላሉ የፍልስፍና ሊቃውንት፡፡
ዕውነት ነው፡፡ የአስተሳሰብ ባርነት፣ የአመለካከት ባርነት፣ የጠባብነት ባርነት፣ የመላላት ባርነት፣ እኔን ከተከተልክ - ነፃ ነህ የመባል ባርነት፤ ዲሞክራሲን እንደፈለጉ በሚተረጉሙና በሚተገብሩ የፖለቲካ ባላባቶች መጠርነፍ ባርነት…ወዘተ ውስጥ መኮድኮድ እርግማን ነው፡፡ ስለሆነም እንዴት? ለምን? ብሎ መጠየቅ ታላቅ እርምጃ ነው!
“የመጨረሻው ከባድ የብረት በርም የሚከፈተው በትንሽ ቁልፍ ነው” (ቻርለስ ዲከንስ)
ቻርለስ ዲከንስ ትንሽ ነን ብለን ተስፋ አንቁረጥ፡፡ ችሎታና ዕውቀቱን ከያዝን የመጨረሻውን ከተምበሪ ልንከፍተው እንችላለን ሲል ነው፡፡ አንዱ የእኛ ፖለቲከኞች ችግር እራስን አሳንሶ ማየት የሚሆነው ለዚህ ነው!!
የሚከተለው አገርኛ ግጥም በልኩ ያስገነዝበናል፡፡
“ዓመት ነው?”
ዕድሜ ነው?
ስሜት ነው?
ተስፋ ነው መጪው ቀን?
ወይስ ኩራት እራት፣ ከውስጡ የቀረ፣ ትርጉም ይኖር ይሆን?”
ተስፈኝነት፣ አዎንታዊነት፣ ትዕግሥትና ጽናት ከሌሉ ለአገራችን ትግል አስተዋጽኦ አይዋጣልንም፡፡
ማርቲን ሉተር ኪንግ፤
“ዓለም ነገ ልታልቅ ነው ቢሉኝም፣ ዛሬ ዛፍ መትከሌን አልተውም” ያለን ለዚህ ነው፡፡
በአንፃሩ ትላንትም፣ አሁንም፣ ያለውን ሁኔታ እደግፋለሁ፤ አንደኛ የልማት አርበኛ ነኝ፤ አንደኛ “ኮብል ስቶኒስት ነኝ!”፤ አንደኛ አገራዊ ምሁርና የሚዲያ ተቆርቋሪ፤ የፖለቲከኛ ተንታኝ ነኝ የሚል ቢበዛ፤ ቆም ብሎ “ዕውን ነውን?” ማለት ያባት ነው! “የሚስቅልህ ሰው ስለበዛ፣ ትክክል ነኝ ብለህ አታስብ!” የሚለው የእንግሊዞች አባባል፤ ፍሬ - ጉዳይ አለው የሚባለው ለዚህ ነው፡፡