Administrator

Administrator

የቀድሞ ድምፃዊ ሙሉቀን መለሰ ባደረበት ህመም በህክምና ሲረዳ ቆይቶ በተወለደ በ70 ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡
ከሦስት አስርት ዓመታት በላይ በሀገረ አሜሪካ ኑሮውን ያደረገው ሙሉቀን መለሰ፤ የሙዚቃውን ዓለም በመተው በመንፈሳዊ የሙዝሙር ስራዎች ውስጥ ያሳልፍ እንደነበር ይታወሳል።
 
ሙሉቀን መለሰ በጎጃም ክፍለ ሀገር አነደድ ወረዳ ውስጥ ዳማ ኪዳነ ምሕረት በምትባል መንደር በ1946 ዓ.ም እንደተወለደ ግለታሪኩ ያወሳል። አሥር ዓመት ሲሆነው እናቱ ስለሞቱ፤ አዲስ አበባ ይኖሩ ከነበሩ አጐቱ ጋር እንዲማር ብለው ያመጡት ሙሉቀን መለሰ፤ ኮልፌ ሰፈር ጳውሎስ ትምህርት ቤት ሊገባ ችሏል።
 
ለሙዚቃ ልዩ ፍቅር የነበረው ድምፃዊው፤ እርሱ በነበረበት አካባቢ በተከፈተው የሙዚቃ ትምህርት ቤት ገብቶ በአቶ ተፈራ አቡነ ወልድ አማካይነት ለስድስት ወራት የዘለቀ የትምህርት እገዛ አግኝቷል።
ገና የ13 ዕድሜ ታዳጊ ሳለ ሙዚቃን የጀመረው ድምፃዊው፤ በ1958 ዓ.ም በፈጣን ኦርኬስትራ ውስጥ ተቀላቅሎ በመግባት ለሁለት ዓመታት ያህል መስራት ችሏል። ከእዚያ በማስከተል በ1960 ዓ.ም ወደ ፖሊስ ኦርኬስትራ ክፍል በመግባት ይበልጥ በሙዚቃ ስራው ዝናን ማትረፍ ችሎ ነበር።
በ1972 ዓ.ም ላይ ደግሞ ከዳህላክ ባንድ ጋር ተቀላቅሎ ሰርቷል፡፡ እስከ 1980ዎቹ ድረስ በነበሩት ዓመታት እጅግ ተወዳጅ የሙዚቃ ስራዎችንም መስራት ችሏል።
ድምጻዊው፤ የአንጋፋዋ ሁለገብ ከያኒት የአለምፀሐይ ወዳጆ እና የተስፋዬ ለሜሳን ግጥምና ዜማዎች አቀንቅኗል።
ሙዚቃ በቃኝ ብሎ ራሱን ከሙዚቃው ዓለም እስካገለለበት ጊዜ ድረስ በርካታ የሙዚቃ ስራዎችን ለትውልድ አበርክቷል።
ከ1980ዎቹ በኋላ ፊቱን ወደ መንፈሳዊ ስራዎች በማዞር የመዝሙር ስራዎችን ሲሰራ ቆይቷል።
እስከ ህልፈተ ሕይወቱ ድረስ በሀገረ አሜሪካ ኑሮውን አድርጎ በእዚያው ቆይቷል።
የዝግጅት ክፍላችን በአንጋፋው ድምጻዊ ሙሉቀን መለሰ ህልፈት የተሰማውን ሀዘን እየገለጸ፤ ለቤተሰቦቹና ለአድናቂዎቹ መጽናናትን ይመኛል።
 

“አንዱን ሥራ ከሌላው አላበላልጥም“

      አለማየሁ ገላጋይ የቃላት አመራረጡና አተራረኩ፣ ቦታዎችን የሚመርጥበትና አገላለፁ በእጅጉ ይገርመኛል፡፡ በየትኛውም የዕድሜ ክልል ያሉ ሰዎች የሚያነቧቸው መጻሕፍት  እያበረከተልን ነው፡፡ የብርሀን  ፈለጎች ወደ ፊልም ቢቀየሩ ምርጥ ድርሰት ነው፡፡ ውልብታ፤ የፖስት ካርድ አፃፃፍ ሙከራ ድንቅ ነው፡፡ በበኩሌ አንዱን መፅሐፍ ከሌላው ማበላለጥ አልችል፡፡ ምክኒያቱም ሁሉም የራሳቸው የሆነ ጣዕምና ለዛ አላቸው፡፡
(አስቴር - መምህርና አድናቂ)
***
አለማየሁ ገላጋይ - የአማርኛ ሥነጽሁፍ ጌጥ
አለማየሁ ገላጋይ ገና በማለዳው ጠለቅ ባለ ንባብ፣ በመጠቀ ምናብ፣ አድማስ-ዘለል ጭብጥና ጥልቅ ሥነ ልቡናዊ ፍተሻን በመፍተል ጀምሮ፣በየጊዜው መሰላሉን በወጉ እየረገጠ፣ ከፍ ያለ ማማ ላይ የተቀመጠ የአማርኛ ሥነ ጽሑፍ ጌጥ ነው። መሥዋዕትነቱ እንደ ጆርጅ በርናንድ ሾ ፣ ተቆርቋሪነቱ እንደ ፑሽኪን፣የሰው ወገናዊነቱ እንደ ቶልስቶይ፣ፍልስፍናው እንደ ኤሚሊ ዲክንሰን ሆነው በጽሑፎቹ ውስጥ ብቅ ይላሉ።
አለማየሁ ወደ ፈጠራ ሥነ ጽሑፍ እልፍኝ ሲገባ፣ዘው ብሎ ሳይሆን ትንፋሹን ቆጥቦ፣የካበተ የንባብ ሀብቱን በካዝናው አጭቆ፣ በቶጀረ አቅም ስለሆነ ደመናውን ካሳየ በኋላ የጥበብ ዝናቡ ሳያባራ አስራ ሰባተኛ ጎሉን ሊያስቆጥር ነው። ቤቱን በአሸዋ ላይ አልጀመረምና የመጣው ንፋስ ሁሉ ሳይነቀንቀው፣የንፋሱን ፉጨት ሙዚቃው አድርጎ እየታጀበ፣ የሥነ ጽሑፍ ማጀታችንን እየሞላ፣ረሀባችንን እያስታገሰ፣ከአድማስ አንደምትናፈቅ የክረምት ጀንበር ብርቅ ሆኗል። ይህንንም ሲያደርግ፣ የአዲሱን ትውልድ ቀለም ሳይንቅ ፣ለቀደመው ሳይሰግድ፤የፈረንጁን ሳይገፋ፣ሀገራዊ እርሾውን ሳይደፋ አዋህዶና አዋድዶ፣በሮማዊ ሥልጣኔ ብልሃት፣የጥበብ ሥራውን ቀጥሏል። በቋንቋ ውበት፣በገለጻ ብቃት እያሳመረ፣በጣፋጭ ኪናዊ  ትረካ እነሆ የተጠማውን ምድረበዳ እያራሰ ዛሬን ደርሷል።
(ደራሲ ደረጀ በላይነሀ)
***


“የአገር ጉዳይ የሚገደው ደራሲ“
ለከት የተበጀለት ምናባዊነት የድርሰት ማባያ ነው፤ ምናብ ከዕውን የሰማይ ያክል መራቅ አይጠበቅበትም፤ ታዲያ ዓለማየሁ ገላጋይ ለምናባዊነት ገደብ ያበጅና፣ ማሕበረ-ባሕላዊ ዕሴቶቻችንን፣ ግርንቢጦሻዊ የአኗኗር ይትባሃላችንን፣ ላይሞላ ጎጆ ጉዟችን በመናጆ፣ የሚጣምን ግብታዊነታችንን…ሌላም ሌላም በድርሰቶቹ አስጎብኝቶናል፤ ከሚጽፍለትና ከሚጽፍበት ማሕበረሰብ የተናጠበ ድርሰት ጀባ ባለማለቱ ሁሌም ምስጉን ነው፤ የማይለፋደዱና የማይነታረኩ ስልታዊ ማንቂያና ማብቂያ ናቸው ድርሰቶቹ!... …ዓለማየሁ ገላጋይ አገር ይገደዋል፤ የአለማሰብ ጣመን ይመዘምዘዋል፤ ወለፈንዴነታችን እንደሻህላ ይቧጥጠዋል፤ በግብታዊነት የምንኖረው ሁሉ እንደ ለበቅ ይፈጀዋል፤ እንደ ዕጣን ፎናኔ ላንታይ ላናይ መንከላወስ መባተላችን ይመዘምዘዋል፤ ቁምነገር ላንጽፍ እንደ ጉንዳን ኮቴ መጥተን ማለፋችን የዕንቅልፍ ለምኔው ምክንያት ነው፤ ትውልድ እንዲገደው ዕሙን ነው፤ ገጸ-ባሕሪይ እና መቼት መቅረፅ ከረቀቀባቸው ጉዳዮች መካከል ዋንኞቹ ናቸው፤ የንባብ ልምዱ ግሩም ነው፤ ያንን ማካፈል ያውቅበታል፤ ሀሳቡን የሚሸከም ቋንቋ መቀመም ልማዱ ሆኖ በአሥራ ስድስቱም ድርሰቶቹ አስተውለናል፤ በአዲሱ ሥራ አዳዲስ የአተራረክ ቴክኒኮችን ይዞ እንደሚመጣ በልበ-ሙሉነት እጠባበቃለሁ!
(ዮናስ ታምሩ - ሃያሲ)




__________________




                     ”አሌክስ የሥነጽሁፍ አዝመራው ሰፊ ነው”


       አንድን ደራሲ ልናደንቀው የሚገባን በአንባቢነቱ መሆን የለበትም ብዬ አምናለሁ:: ወታደሩን ያለ ተኩስ፣ ገበሬውንም ያለ እርሻ ማሰብ ከባድ እንደሆነው ሁሉ፣ ለደራሲ ትጥቁና ስንቁ መጻሕፍት ናቸው:: ይልቁንስ ደራሲ ሊደነቅ የሚገባው ሳይታክት መናበብ ሲችል ነው::
ወዳጃችን አለማየሁ ገላጋይ ለዚህ ታድሏል:: ብዙውን ጊዜ ከራሱ፣ ከጊዜው መንፈስና ከዘመኑ የሥነፅሁፍ እንቅስቃሴ ጋር ለመናበብ ቤቱ ብቻ ሳይሆን ልቡም ክፍት ነው፡፡ ለዚህም ነው በሃሳብ የተለየህ ብትሆን እንኳን ሊያነብህና ሊያስነብብህ ዝግጁ ሆኖ የሚያስተናግድህ!
አሌክስ የሥነጽሁፍ አዝመራው ሰፊ ነው! ደግሞም በሰጠ ቁጥር የሚበዛለት አይነት ሰው:: ሲሰጥ የፊተኛውን ያልመሰለ እንዲሆንለት ይመኛል:: በተለይ ከቴክኒክ አንጻር! እንኳንስ ሌላውን ራሱንም ባይኮርጅ ጽኑ ምኞቱ ነው:: ጭብጦቹ የማህበረሰቡን ፎከሎር የሚገልፁ፣ ለተገፋው ለተከፋውና  ለተናቀው ‘ምስኪን’ ጥብቅና የሚቆሙ ናቸው:: የሚሞግቱ የሚያሟግቱ፣ ምን ሆነን ነው ከነበርንበት ዝቅ ያልነው? የሚሉ!
ዛሬ ዛሬ ‘እገሌ መጽሀፍ አወጣ!’ ሲባል፣ ‘ስለምን?’ ብለን ሳንጠይቅ፣ ተማምነን የምንገዛቸው ጥቂት ደራሲያን  መሃል አንዱ አለማየሁ ገላጋይ ሆኗል፤ መልሶ መላልሶ በመጣልን የምንለው ደራሲ ነው፤ እናም እንጓጓለን፤ በአዲሱ መፅሐፉ ምን ብሎ ያጫውተን፣ ይጎነትለን ይሆን እያልን!
(ደራሲ እንዳለጌታ ከበደ)




_________________




                 ሌላው “የሥነጽሁፍ ወዛደር”


       ዓለማየሁ ገላጋይ፣ በወሪሳ አውድማ ላይ በምጸታዊ መንሽ ማኅበራዊ አዝዕርትን ንፋስ ላይ አበጥሯል። በታለ ማሰሮ ጦማራዊ ልቦለድን ንጧል። በኢህአዴግን እከስሳለሁ ሙቀጫ የጋዜጠኝነትን ዘነዘና ይዞ ምኩራብ ወጥቷል። በቅበላ ብራና የድህረ ዘመናዊ ልቦለድን ከትቧል። በመልክአ ስብሃት ሰፌድ ላይ ሰበዝም፣ አለላም፣ አክርማም ሆነ ስንደዶ ለመሆን የሚመች፥ የደቦ ከያኔ መሆኑን ተመልክተናል። በየፍልስፍና አጽናፍ ተርጓሚነቱን፣ በስብሃት ገ/እግዚአብሔር ሕይወትና ክሕሎት - ኀያሲነቱን አስመስክሯል። በየተጠላው እንዳልተጠላው አይነኬ ዕሳቤዎችን በመጠይቅ ወንፊት አንገዋሏል። በአጥቢያ የንስር ዓይናማነቱን፣ በመለያየት ሞት ነው ሊቀ-መጣጥፍነቱን፣ በፍቅር ስም ላይ ደግሞ experimental novelist-ነቱን ተመልክተናል። በኩርቢት መም ላይ የስሜት ጂምናስቲክ አሠርቶናል። በ17ኛው መጽሐፉ ደሞ 24 እንዳልሞላው ሊያስታውቀን ተከስቷል። እኔ በበኩሌ በጋሽ ወንድዬ ዓሊ ብሂል፤ “የሥነ-ጽሑፍ ወዛደር” ብዬዋለሁ።
(ደራሲ ቢንያም ቡራ)




__________________




                  “ቃላት አጠቃቀሙ ልክ እንደ ቼኾቭ ነው”


       ከጓደኞቻችን መሀል እንደሱ በንባብ የበልፀግ ሰው አላየሁም፤ የአስተሳሰብ አድማሱ ጥልቅ ነው ፤ ቃላት አጠቃቀሙ ልክ እንደ ቼኸቭ ነው፤ ገፀ ባሕርያቶቹን ደሞ የሚያብሰለስላቸው ልክ እንደ ደስታየቭስኪ ነው ፣ ያውቅበታል።
የጨፈገገ ፊት ያለው ደራሲ  አለማየው ገላጋይ፤ ተወልዶ ያደገው  የከተማ እንብርት በሆነችው አራት ኪሎ በፈካና በነቃ ማህበረሰብ ውስጥ ነው ።  በዚያ ሳቅና ፈገግታ፣ ጨዋታና ፌሽታ፣ ዝሙትና  ስካር ፣ማግኘትና ማጣት፤ ከዩኒቨርሲቲ ተማሪ እስከ ዩንቨርስቲ ምሁራን፣ ከቄስ ቆጶሳት እስከ መነኮሳት ፣እስከ ጳጳሳት፣ ሲበሉ ሲጠጡ ሲሾሙ ሲሻሩ፣ ሲነግሱ፣ ሲረክሱ፤ የከተማ መናኝ ሆኖ ዘመኑንና  ዓይኑን በንባብና በትዝብት ያሳለፈ፤ የዓይን ምስክርነቱን በፃፋቸው መጻሕፍቱ  ፍትሃነቱን ያስመሰከረ፤ ከደመና መሳይ ጭጋግማ መልኩ ፈገግታን የሚፈነጥቅ ፣ሲያሻውም በምፀት የሚያስጨንቅ ሀቀኛ ብዕረኛ ነውና፡፡       ብዙ ህይወትና ገጠመኙን በመኖር ሳይሆን በትዝብትና በማብሰልሰል የሚፈጅ፤ አጭር ጊዜውን በማብሰልሰል የቋጠረውን የሀሳብ ሽል ደበቅ ብሎ እራሱን የሚያዋልድና ፈገግታ ፣ሀዘንና ፣ቁጭቱን ፣ህልምና ተስፋውን ፣ግን በመልካም ሥነ ፅሁፍ ላደገበትና ለኖረበት ማህበረሰብ የበኩሉን ዕሳቤ ጠብ የሚያደርግ. ኢትዮጵያ ዊ ዶስቶቭስኪ ነውና
     ዓለማየሁ ገላጋይ በአተራረኩ እየተረከ ሳይኾን እያጫወተ ያወያያል፣ ገጸ ባሕርያቱ አጠገብህ ያሉ እየመሰለኽ ከንባብ ተናጥበህ ዙሪያህ  ትፈልጋቸዋለህ። የሚጽፋቸው ልቦለዶች ውስጥ ጥልቅ ንባቡንና ብያኔዎቹን ታገኛቸዋለህ። ለመጻፍ ብሎ የጻፈ ይመስልሃል እንጂ እርሱ ግን ከንባቡ ሞልቶ ሲፈስ ነው የጻፈው። አንዳንዶች አለማየሁ ያነበበውን አስታውሶ ይጽፋል ቢሉትም፣ ነገሩ ግን ሙዚቃዊ ወይም ግጥማዊ ድንገቴነት የከሰተው ይመስለኛል።
(አለማየሁ አሊ)


ባልተለመደ መልኩ በምስጢር ተይዞ የቆየው የአንጋፋው ደራሲና ሃያሲ አለማየሁ ገላጋይ 17ኛ መፅሐፍ ዛሬ  ከቀኑ በ10 ሰዓት ይመረቃል።
የመፅሀፉ ርዕስም ሆነ ርዕሰ ጉዳይ በዛሬው ዕለት በዋልያ መፃህፍት ሲመረቅ ይፋ እንደሚሆን ነው የታወቀው።
በ17ኛው አዲስ መፅሐፉ ዙሪያ አዲስ አድማስ ጥያቄ ያቀረበለት ደራሲው፤ ሁሉም ነገር ርዕሱን ጨምሮ ለህዝብ ይፋ የሚደረገው በዛሬው ዕለት መሆኑን ተናግሯል።
አዲስ አድማስ በደራሲ አለማየሁ ገላጋይ የፈጠራ ስራዎች  ዙሪያ ከተለያዩ የሥነ-ጽሁፍ ሰዎች ያሰባሰባቸውን አስተያየቶች በገጽ 12 ይመልከቱ።

 (በጓድዬ ብሽዬ ኤረማ) የቤተ-ጉራጌ ምሳሌያዊ አነጋገር


         አንድ በጣም ባለፀጋ የሆኑ የተከበሩ ባላባት በአንድ መንደር ይኖራሉ፡፡ ጌታዬ ጌታዬ የማይላቸው የለም፡፡ እኝህ የተከበሩ ባላባት አንድ ብርቄ የሚባል ነባር አሽከር ነበራቸው፡፡ ብርቄ አሽከርነት ያምርበታል፡፡ ሲልኩት ወዴት፣ ሲጠሩት አቤት ለማለት ይችልበታል፡፡ ዘወትር ግብር ገብቶ፣ ድግሱ ተበልቶ ጌትዬውን ብርቄ እጅ ሲያስታጥብ፤
“ሰማህ ወይ ብርቄ” ይሉታል፡፡
“አቤት ጌታዬ” ይላል ብርቄ፡፡
“አሁን እኔ ብሞት ምን ታደርግ ይመስልሀል?”
“ጌታዬ፤ እርሶ ከዚህቺ አለም ተለይተው እኔ ከዚህ ቤት አልቀመጥም”
“ታዲያ ምን ትሆናለህ?”
“እመንናለሁ፡፡ አለም በቃኝ እላለሁ፡፡ ጀርባዬን ለአለም ፊቴን ለገዳም እሰጣለሁ”
“ተው፤ አታረገውም ብርቄ?”
“በጭራሽ፡፡ እርሶ ሞተው እኔ እዚህች ቤት አንዲት ቀን እህል ውሃ አልቀምስም!”
“መልካም፡፡ ለዚህ ታማኝነትህ አንድ ኩታ ተሸልመሃል!” ብርቄ እጅ ነስቶ ኩታወን አገኘ፡፡
ሌላም ቀን፤ “ብርቄ እኔ ብሞት ምን ታደርጋለህ?” ይሉታል፡፡
“ምን ያጠያይቃል ጌታዬ? መመነን ነዋ! ከእርሶ ወዲያ አለም ለምኔ” ይላል፡፡
”ብርሌ ጠጅ ስጡት ይባላል!”
ሌላ ቀን፡፡ “ብርቄ እኔ ብሞት ምን ታደርጋለህ”
“እለቱን፤ እኔን ጨርቄን ሳልል፣ ወደ ገዳም ነዋ ጌታዬ!”
“እውነት ታደርገዋለህ፤ ብርቄ?”
“አይጠራጠሩ ጌታዬ! ምን ቀረኝ ብዬ እዚህ ቤት እቀመጣለሁ?”
“እኔ ምልህ ብርቄ?”
“አቤት ጌታዬ?”
“እንደው ለነገሩ፤ ከኔ ቀድመህ መሞት ታስቦህ ያውቃል? አንዳንዴ ለምን እኔ ቀድሜዎት ልሙት እንኳ አትለኝም?”
ብርቄም ትንሽ አሰብ አድርጎ፤
“አይ ጌታዬ ሳላስበው ቀርቼ መስሎት? አስቤዋለሁ፡፡ ግን ከተናገርኩ የጌታዬን የተሻማሁ እንዳይመስልብኝ ብዬ ነው፡፡”
ሌላ ቀን፡፡ ብርቄን ጠርተው ደግመው በጨዋታ መሃል፤
“ከእኔ ቀድመህ የምትሞት አይመስልህም?”
“ኸረ በጭራሽ ጌታዬ?”
“ለምን?”
“እኔ ከሞትኩ ማን እንደኔ ያለቅስሎታል! ኸረ በጭራሽ እግዜር እንደዚህ ያለ ነገር አያድርስብን!! እርሶ ከሞቱ ግን እዚህች ቤት አንዲት ጀንበር አላድርም- ወደ ገዳም ነው!”
“ይህን ያህል ትወደኛለሃ?”
“እንዴት ይጠራጠራሉ?”
ከባድ ጉርሻ ያጎርሱትና “ጠጅ ስጡት!” ብለው ያዙለታል፡፡
ጌትየው እንዳሉት እሳቸው ቀድመውት ሞቱ፡፡  ከሚስታቸው አንድ ትንሽ ወንድ ልጅ ብቻ ነው ያላቸው፡፡ ሚስታቸው 6 ወር ሃዘኑንም መንፈቃቸው ከወጡ በኋላ ሌላ ባል አገቡ፡፡ ብርቄም ያዲሱ ጌታ አሽከር ሆኑ፡፡ “እርሶ ከሞቱ እመንናለሁ!” ማለቱን ቀጠለ፡፡
አንድ ቀን አዲሱ ጌታው ግብር አግብቶ፣ ሰው በድንኳን ግጥም ብሎ እየተበላ፣ እየተጠጣ ብርቄ እንደልማዱ ተፍ ተፍ እያለ እያስተናገደ ሳለ፤ አንድ አዝማሪ ተነስቶ መሰንቆውን እየገዘገዘ ጨዋታ ጀመረ፡፡
ድምፁን አዝልጎ “ትላንትና ማታ ጌታዬን አግኝቼ” አለና ጀመረ፡፡ ህዝቡ በከፊል፤ አዝማሪውም የሞቱትን ጌታ በማንሳቱ “ምን ሊል ይሆን?” በሚል አይነት ፀጥ አለ፡፡ አዝማሪው፤ ደገመና
“ትላንትና ማታ ጌታዬን አግኝቼ” አለ፡፡
አሁን ሰው ሙሉ በሙሉ ጸጥ እርጭ  አለ፡፡ ምን ሊል ነው በሚል መንፈስ፡፡ አዝማሪውም
“ትላንትና ማታ ጌታዬን አግኝቼ
… ሚስቴስ ደና ናት ወይ? (ወደ ሚስትየው እያየ)
… ልጄስ አደገ ወይ? (ወደ ልጅየው እያየ)
… ብርቄስ መ…መ…ነ ወይ!?” (ወደ ብርቄ ቀና ብሎ) ብለው ቢጠይቁኝ፣
ሚስቶት ደና ናቸው፤ ልጆትም አድጓል፡፡
(ቆም አድርጎ ወደ ብርቄ እያየና እያንዳንዱን ቃል እየረገጠ)
…ብ…ር…ቄ….ም አ…ል…መ…ነ…ነ…ም!! ብዬ ብነግራቸው፤
አይጉድ! አይጉድ! አይጉድ! ያሉበት፤ እረገፈ ጣታቸው!!”
ሲል ገጠም፡፡ ሰው ሁሉ ወደ ብርቄ ተመለከተ፡፡ ብርቄን የሰው አይን ከአገር አስወጣው፡፡
*   *   *
ለእምነታቸው የሚኖሩ፣ ማተማቸውን የማይበጥሱ፣ የተናገሩትን የማያፈርሱ፣ በምላሳቸው የማይኖሩ ብቻ ናቸው በህዝብ የሚታመኑት፡፡ ጌታቸውንና አለቃቸውን ለማስደሰት ወይም ለመሸንገል ሲሉ ብቻ “አቤት!” “ወዴት!” የሚሉ የየሥርአቱ አሸርጋጅ ይሆናሉ እንጂ፣ በየተደገሰበት ሁሉ ከበሮ መቺ ይሆናሉ እንጂ ለህሊናቸውና ለእምነታቸው አያድሩም፡፡ “ህዝቡን ልናገለግል” ፣ “አገርን ልናድን” “ምድር ሰማዩ ልናለማ”፣ “የህዝቡን የአኗኗር ዘይቤ ልንለውጥ”፣ “ከተማ ልናሰፋ፣ የገጠሩን ህዝብ ልናሰለጥን፣” ወዘተ የሚል አይነት ቃል መግባትና “ይህ ካልሆነ ወንበሬን እለቃለሁ”፣ “ይህ ካልሆነ የጓዶች አጥንት እሾህ ሆኖ ይውጋኝ!”፣ “ይህ ካልሆነ ማናቸውንም ፍዳ ልቀበል!” ማለት የተለመደ ሆኗል፡፡ እንደ ብርቄ “እርሶ ከሞቱ በቃ፤ እመንናለሁ” ማለት፡፡ ከዚያም ምንም ለውጥ ሳይመጣ ሲቀር ለአዲሱ ጌታ ማደር፡፡ አይንን በጨው ታጥቦ “ዛሬም እንደ ትላንት በአላማ ፅናት ራእይን እውን ለማድረግ “እስከ መጨረሻ ድረስ የደም ጠብታ፣ እስከ መጨረሻ አንድ ሰው፤ እታገላለሁ” ሲሉ ቃለመሃላ ማዥጎድጎድ፡፡ ጌታዬ ከሞቱ እዚህች አገር አንዲትም ቀን አልውልም አላድርም ማለት!... ቃል መግባት … እቅድ ማቀድ… ፖሊሲ መንደፍ… በየወንዙ መማል… መማማል መመሪያ ማውጣት… አዋጅ ማወጅ… በየፌርማታው አበጀህ መባባል… መግለጫ ማውጣት… መፅሐፍ መግለጥ… ፕሮጀክት መቅረፅ… መርቆ መክፈት… መጨባበጥ “ከመቸውም በበለጠ በአዲስ መንፈስ ተነስተናል” ማለት… ትላንትን በላጲስ ማጥፋት… ነገን በእርሳስ መሳል… ተግባርና “አፈፃፀም” ግን የለም፡፡ ቃል ይፈርሳል፡፡ ቃል ይበላል፡፡ የሚወገዝ ይወገዛል፡፡ መካድ፡፡ መካካድ ይቀጥላል፡፡ የሚረገም ይረገማል፡፡ በድሮ ጊዜ ብሎ ጥሩምባ ነፊው “ካድሬያችን ኑና አራግሙን ብሏል!” እንደተባለው ነው፡፡ በትብብር፣ በደቦ፣ በብዙሃን ድምፅ መራገም እንጂ ከልብ የሚሆን ምንም ነገር የለም እንደማለት ነው፡፡ “ሲቸግር የእንጀራ እናቱን እምዬ ይልዋል” ነውና የትላንቶቹን ለመርገም የትላንት ወዲያውን መጥቀስና ማወደስ ይቀጥላል፡፡
አዲስ መፈክር ይቀመራል፡፡ በህብረት ያንን መፈክር ማስገር ይቀጥላል፡፡ በልብ መክዳት በአካል አለሁ ማለት ይዘወተራል፡፡ እስከ ሌላ መከዳዳት፣ እስከ ሌላ ቃል ማፍረስ “ልጅ እገሌ” ፣ “ጉድ እገሌ”፣ “ክቡር እምክቡራን” መባባል፡፡ ሆኖም “በጭለማ ማፍጠጥ ደንቆሮን መቆጣት ነው” እንደሚባለው ልብ ውስጥ እውነተኛ ፍቅር፣ እውነተኛ አገር መውደድ፣ እውነተኛ ለህዝብ የመቆም ስሜት፣ ሳይኖር አላማና እቅድን በስራ ላይ ማዋል ከቶም ዘበት ነገር ነው፡፡ መሪና መሪ፣ አለቃና አለቃ፣ ፓርቲና ፓርቲ፣ ባለስልጣንና ባለስልጣን፣ ዜጋና ዜጋ በመካከላቸው ልባዊ መተማነን ከሌለው ስራ አይሰራም፤ እቅድ አይፈፀምም፡፡ ፕሮግራም አይተገበርም፡፡ ቃል ህይወት አይሆንም፡፡ ይስሙላ፣ ለበጣ፣ የአደባባይ ማስመሰል፣ የሸንጎ ዲስኮ፣ የስብሰባ ንግግር ብቻ ሆኖ ይቀራል፡፡
የሀገራችን አንዱ አንኳር ችግር ከእቅድ ነዳፊው እስከ ፈፃሚው ድረስ ልባዊ መተማመን አለመኖር ነው፡፡ “ይህን ያለው ይህን ሊል ፈልጎ ነው” በሚል የግራ ትርጉም የታጠረው አስተሳሰብ ይበዛል፤ ቡድንና ቡድን አይተማመንም፡፡ መስመሩን ሳይሆን በመስመሮች መሃል ማንበብ (Between the lines እንዲሉ) ነው ፈሊጡ፡፡ በውስጡ የተቀበረው ፍላጎት (Hidden motive) ካለ ምንዛሬ ይበዛል፤ ቅጥያና ዘርፍ እያበዙ “ትርጉም የኔ”፣ “ስርዝ ያንተ”፣ “ቅንፍ የነሱ” ማለት ቋንቋ ይሆናል፡፡ አፋዊ የሆነ ያሸበረቀ ቃል ሲበዛ ተግባር ባዶውን ይቀራል፡፡ ዞሮ ዞሮ ወሳኙ ግን ልባችን ውስጥ ምን አለ የሚለው ነው፡፡ ልባችን ትግል እያሰበ አፋችን ድል ቢያወራ ዋጋ የለውም፡፡ ልባችን አትጠጉኝ እያለ አፋችን ስለ አፍሪካ ህብረት እና ጉባኤ ቢያወራ ነገር ሁሉ የይስሙላ ይሆናል፡፡ ልባችን ሹመት እያሰበ አፋችን የኢኮኖሚ ልማት ቢያወራ ነገ የሚጋለጥ ከንቱ ዲስኩር ይሆናል፡፡ ሁሉም የሚያስተጋባውና የሚተገብረው ጥንት የተሰራበትን ንጥረ-ነገር ነው፤ የውስጡን፡፡ የጠዋቱን፡፡
እውነተኛ ፍሬ ከእውነተኛ ተግባር፣ ከእውነተኛ እምነት ነው የሚገኘው፡፡ ያ ሳይኖር ፍሬ መጠበቅ ከንቱ ነው፡፡ ነጭ ባህር ዛፍ ላይ ቀይ ባህር ዛፍ አይበቅልም ማለትም ይኸው ነው፡፡


 የቴሌግራም ቻናልችንን  በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

 

የሶማሊያ ፌደራል መንግሥት፣ በፑንትላንድ ዋና ከተማ ጋሮዌ የሚገኘው የኢትዮጵያ ቆንስላ እንዲዘጋ ያስተላለፈውን ትዕዛዝ እንደማትቀበል ፑንትላንድ አስታወቀች።
የሶማሊያ  መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት በውስጥ ጉዳዬ ጣልቃ እየገባ ነው በሚል በሞቃዲሾ የኢትዮጵያ አምባሳደር አገሪቱን ለቀው እንዲወጡና በከፊል ራስ ገዟ ፑንትላንድና ነጻነቷን ባወጀችው ሶማሊላንድ ያሉት የኢትዮጵያ ቆንስላ ጽህፈት ቤቶች እንዲዘጉ ማዘዙን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡  
ከጎረቤት አገር ኢትዮጵያ፣ ነጻ አገር ነኝ ከምትለው ሶማሊላንድና በከፊል ራስ ገዝ ከሆነችው ፑንትላንድ ጋር ፖለቲካዊ እሰጣ ገባው ውስጥ የገባው የሶማሊያ ፌደራል መንግሥት፣ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ሦስቱን መንግሥታት የተመለከተ ጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ እርምጃ መውሰዱን አስታውቋል። የፑንትላንድ አስተዳዳር ትላንት ዓርብ መጋቢት 27 ቀን 2016 ዓ.ም. ባወጠው መግለጫ ቆንስላው እንዲዘጋ የተላለፈው ትዕዛዝ፣ የሶማሊያን ሕገ-መንግሥት የሚጥስ ነው በማለት ተግባራዊ እንደማይደረግ አስታውቋል።
የፕሬዚዳንት  ሐሰን ሼክ ሙሐመድ አስተዳደር የኢትዮጵያው አምባሳደር ሙክታር ከድር ዋሬ፣ በ72 ሰዓታት ከአገር እንዲወጡ ትዕዛዝ ከማስተላለፉ በተጨማሪ፣ አዲስ አበባ በሐርጌሳና ጋሮዌ ያላት ቆንስላዎች በአንድ ሳምንት ውስጥ እንዲዘጉ ትዕዛዝ ሰጥቷል።
ይሁን እንጂ የሶማሊላንድና ፑንትላንድ በሚኒስትር ደረጃ ያሉ መሪዎች የፌደራል መንግሥቱ ውሳኔን እንደማይቀበሉ ተናግረው ነበር። ከዚህ በተጨማሪም የሶማሊያ መንግሥት በአዲስ አበባ የሚገኙትን አምባሳደሩን “ለአጠቃላይ ምክክር” ከኢትዮጵያ ለቀው እንዲወጡ ማዘዙን የሶማሊያ የውጭ ጉዳይና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሚኒስቴር ይፋ አድርጓል።
የሶማሊያ መንግሥት በመግለጫው፤ ኢትዮጵያ “በሶማሊያ ሉዓላዊነትና የውስጥ ጉዳይ” ጣልቃ ገብታለች ሲል ከሷል። ኢትዮጵያ ታኅሣሥ 2016 ዓ.ም. ነጻ አገርነቷን ካወጀችው ሶማሊላንድ ጋር የባሕር ጠረፍ ማግኘት የሚያስችላትን የመግባቢያ ስምምነት መፈረሟ ሞቃዲሾን ያስቆጣ ሲሆን፣ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኑነትም አጠልሽቶት ቆይቷል።
ባለፈው ሳምንት ማብቂያ ላይ ደግሞ የሶማሊያ መንግሥት ያደረገውን የሕገ-መንግሥት ማሻሻያ በመቃወም ከፊል ራስ ገዝ የሆነችው ፑንትላንድ ለፌደራል መንግሥቱ እውቅና መስጠት አቁሚያለሁ ብላለች።
ይህ የፑንትላንድ ውሳኔ በሶማሊያ ፖለቲካ ውጥረት ፈጥሮ ባለበት ወቅት የፑንትላንድ የገንዘብ ሚኒስትር ባለፈወው  ረቡዕ መጋቢት 25 ቀን 2016 ዓ.ም. ለጉብኝት አዲስ አበባ ገብተው ከኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ጋር መወያየታቸው ሶማሊያን አስቆጥቷል፡፡
የሶማሊያ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት አሁን የኢትዮጵያን ዲፕሎማት ለማባረርና የቆንስላ ጽህፈት ቤቶቿ እንዲዘጉ ከውሳኔ ላይ የደረሰው የገንዘብ ሚኒስትሩን ጉብኝት ተከትሎ ሊሆን እንደሚችል ተገምቷል።
የፑንትላንድ አስተዳደር መንግሥት ትላንት ዓርብ  ባወጣው መግለጫ፤ የሶማሊያን ውሳኔ እንደሚቃወም ገልጾ፤ ፑንትላንድ የውጭ ፍላጎቷን ለማስጠበቅ ከማዕከላዊው የሶማሊያ መንግሥት እውቅና ውጪ በቀጥታ በራሷ አማካይነት ግንኙነቶችን እንደምታደርግም ጨምራ ገልጻለች።

ባሮክ ኤቨንት ኦርጋናይዘር አ.ማ፣ ከሚያዚያ 10 እስከ ሚያዚያ 28 ቀን 2016 ዓ.ም የሚቆይ  የፋሲካ  ባዛርና ኤክስፖ በሚሊኒየም አዳራሽ እንደሚያካሂድ አስታወቀ፡፡

ለ20 ቀናት ገደማ ክፍት የሚሆነው ባዛርና ኤክስፖ፤ ሸማቹ በተመጣጣኝና ቅናሽ ዋጋ ከራሱ ከአምራቹና አስመጪው የሚገበያይበት ነው የተባለ ሲሆን፤ አምራቹም ከሸማቹ ከፍተኛ ገበያ የሚያገኝበት እንደሚሆን ተነግሯል፡፡

ከ2ሺ በላይ አስመጪና ሻጮች እንደሚሳተፉበት በተነገረለት በዚህ ባዛርና ኤክስፖ፤ በቀን እስከ 10ሺ የሚደርሱ ሸማቾች ይጎበኙታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በዚህ ባዛርና ኤክስፖ ከዓውዳመት ሸቀጦች በተጨማሪ፣ በየቀኑ ታዋቂ ሙዚቀኞች፣ ተወዳጅ ሥራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡ ታውቋል፡፡

የፋሲካ ባዛርና ኤክስፖ የፊታችን ሚያዚያ 12 ቀን 2016 ዓ.ም ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ባለሃብቶች፣ የሚዲያ ባለሙያዎችና ታዋቂ ግለሰቦች በተገኙበት በይፋ ይከፈታል ተብሏል፡፡

የደራሲ እያዩ ደባስ ሦስተኛ መጽሐፍ “ፓርታ” ለንባብ የበቃ ሲሆን፤ ደራሲው በመግቢያው ላይ እንዳሰፈረው፤ “ፓርታ ላልተጻፈው የሐሳብ ዕዳ ክፍያ ይሆን ዘንድ ነው። እነርሱን የመሆን የሐሳብ ዕዳ ውስጥ ለገባ አንድ አሳቢ፣ ሰውን ነጻ የማውጣት የቀናነት ትግል ነው።

መጽሐፉ የትችት፣ የመወቃቀስ፣ የሐሜትና የጥላቻ ግብ የለውም። ከሐሳብነት የተረፈ የመቆሚያ ሥፍራም የለው፤ ብሏል ደራሲው።

የዚህ መጽሐፍ ዋና ገጸ-ባሕርይ “ሐሳብ” መሆኑ የተጠቆመ ሲሆን፤ደራሲው የእድሜ ዘመን ንባብ ያላቸውን ታዋቂ ግለሰቦችን ገጸ ባህሪ አድርጎ በማምጣት፣ለሃሳብ የበረታ ድርሰት ከትቧል፡፡
 
“ፓርታ” በ273 ገጾችና 68 ምዕራፎች የተቀነበበ መጽሐፍ ሲሆን አሳታሚና አከፋፋዩ ጃዕፈር መጻሕፍት መደብር ነው ተብሏል፡፡ መጽሐፉ  በ400 ብር ለአንባቢያን ቀርቧል።

•  የመጀመሪያውን ዙር የመኪና ርክክብ አድርገዋል

አሚጎስ የገንዘብ ቁጠባና ብድር ህብረት ስራ ማህበርና ኢትዮፒካር፣. የኤሌክትሪክ መኪኖችን በብድር ለማቅረብ የሚያስችል ስምምነት ዛሬ ጠዋት መጋቢት 27 ቀን 2016 ዓ.ም  የፈፀሙ ሲሆን፤ የብድር መስፈርቱን ላሟሉ ሰባት የ“ምሰሶ የታክሲ ማህበር” አባላት የመኪና ርክክብ አድርገዋል።

ስምምነቱን የፈፀሙት የአሚጎስ ም/ሥራ አስኪያጅ አቶ ዘላለም ይልማና የኢትዮፒካር ባለቤት አቶ ሳሙኤል አዲስዓለም  ናቸው።

በስምምነቱ መሰረት፣ የ"ሆን ዞ" አውቶ ፋክተሪ የኢትዮጵያና ምስራቅ አፍሪካ ብቸኛ ወኪል የሆነው ኢትዮፒካር፣ የአሚጎስ አባላት የሚፈልጓቸውን የኤሌክትሪክ መኪኖች ምቹና ቀልጣፋ በሆነ መልኩ በብድር እንደሚያቀርብ ታውቋል፡፡

 ኢትዮጵያ እንደ ሃገር የውጭ ምንዛሬ እጥረትን ብሎም የአየር ንብረትን ለመጠበቅ ይረዳ ዘንድ የኤሌክትሪክ መኪናን እንደ አማራጭ የመጠቀም ፖሊሲን እየተገበረች ሲሆን፤ በሃገራችን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ፍላጎትም እያደገ መምጣቱ ተነግሯል፡፡

የአለማችን ተጠቃሽ የኤሌክትሪክ መኪኖች አምራች የሆነው የ"ሆን ዞን" አውቶ ፋክተሪ የኢትዮጵያና ምስራቅ አፍሪካ ብቸኛ ወኪል ኢትዮፒካር ብራንድ፣ የኤሌክትሪክ መኪኖችን ወደ ኢትዮጵያ በማስገባት ለተጠቃሚዎች እያቀረበ ይገኛል፡፡

የዜጎችን ኑሮ ባማከለ መልኩ በባንክ ብድር አማራጭ የሚቀርቡት እነዚህ የኤሌክትሪክ መኪኖች፣ የፋብሪካ ዋስትና እንዳላቸው የተገለጸ ሲሆን፤ድርጅቱ መኪኖቹን መቶ በመቶ በብድር ብቻ ለተጠቃሚዎች ለማቅረብም እየሰራ እንደሚገኝም ለማወቅ ተችሏል፡፡

• ለመጀመሪያ ጊዜ በኦንላይን የተመዘገበ ሰርተፊኬት ተሰጥቷል
የአዲስ አበባ ሌጀንድ ኢንተርናሽናል ፕሮ ቴኳንዶ አሶሴሽን፤ የ2016 ዓ.ም የመጀመሪያዎቹን የ3ኛ ደረጃ የዳኝነት ሥልጠናና ዓለማቀፍ የፕሮ ቴኳንዶ የመጀመሪያ ራስን መከላከል ስልጠና ተሳታፊዎች ትላንት መጋቢት 26 ቀን 2016 ዓ.ም በወወክማ አዳራሽ አስመረቀ፡፡
ሥልጠናው ከአዲስ አበባና ከክልሎች ለተውጣጡ 28 ተሳታፊዎች ለ15 ቀናት ሲሰጥ የቆየ ሲሆን፤ ተመራቂዎቹ ለመጀመሪያ ጊዜ በኦንላይን የተመዘገበ ሰርተፊኬት ማግኘታቸው ታውቋል፡፡
 
ከሰልጣኞቹ መካከል 19 ያህሉ ሥልጠናውን በተሟላ መልኩ አልፈዋል የተባለ ሲሆን ሁለቱ አለማለፋቸው ነው የተነገረው፡፡
በምረቃ ሥነስርዓቱ ላይ እንደተነገረው፤ ሳኦል ኹነቶች ለአራት ሰልጣኞች የስፖርት ማዘውተሪያ አዳራሽ ያመቻቸ ሲሆን፤ በቅርቡ ፒያሳ አካባቢ በኮሪደር ልማት ሳቢያ የስፖርት ማዘውተሪያ ለፈረሰበት አንድ ወጣት በቀጣይ ቦታ ለማመቻችት ቃል ተገብቶለታል።
የአዲስ አበባ ሌጀንድ ኢንተርናሽናል ፕሮ ቴኳንዶ አሶሴሽን ፕሬዚዳንት ማስተር ሃይለየሱስ ፍስሃ በመርሐግብሩ ላይ እንደገለጹት፤ የተሰጠው 3ኛ ደረጃ የዳኝነት ሥልጠና፣ ሌጀንድ ኢንተርናሽናል በኢትዮጵያ የሠጠው የመጀመሪያ ኮርስ ነው፡፡
የሌጀንድ ኢንተርናሽናል ፕሮ ቴኳንዶ አሶሴሽን የአፍሪካ ፕሬዚዳንት የኢትዮጵያ የበላይ ጠባቂ ግራንድ ማስተር (ፒ ኤች ዲ በማርሻል አርት ሳይንስ) ሄኖክ ግርማ፣ለተመራቂዎቹ ሰልጣኞች ሽልማት ሰጥተዋል፡፡
 
ይህ በዚህ እንዳለ፣ የአዲስ አበባ ወርልድ ቴኳንዶ ፌዴሬሽን ከሳኦል ኩነቶች ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የአዲስ አበባ ወርልድ ቴኳንዶ 2016/2024 ኦፕን ቶርናመንት፣ ከግንቦት 3 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ የሚካሄድ ሲሆን፤ ውድድሩን አስመልክቶ ነገ ቅዳሜ በአራት ኪሎ ስፖ/ትም/ሥልጠና ማዕከል በሚገኘው ትልቁ ጅምናዚየም ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ ታውቋል፡፡

ይህ ‹‹ሆኖ መገኘት፤ እኔም ኃይሌ ነኝ›› የተሰኘ መጽሐፍ በኢትዮጵያ የድርጅቶች አገልግሎት ልህቀትን ለማሳደግ በማሰብ የተደረገ የእውቀት ሽግግር ጥረት ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ ወደ ልህቀት የሚደረግን ጉዞ የሚያግዝ ብቻ አይደለም፤ ይልቁንም መንገድንም የሚያመላክት እንጅ፡፡

‹‹ሆኖ መገኘት›› ማዕከል የሚያደርገው የአገልግሎት ልህቀት ከፍ እያለ በተግባር እየታየበት ያለውን ኃይሌ ሪሶርቶችና ሆቴሎች ሲሆን የሥረ ነገር ማጠንጠኛውም ራሱ ሆኖ መገኘትን ያሳዬን ኃይሌ ገብረ ሥላሴ ነው፡፡ መጽሐፉ የሥራ ባህል ምን ያህል ወሳኝ መሆኑን አጽኦት የሚሰጥ ከመሆኑም በላይ የስራ ባህል ምንነትን እና ተግባራትን ከመቅረጽ አንጻር ያለውን ሚና ያትታል፡፡

ሆን ተብሎ ቢሆንም እና ባይሆንም ባህል እያንዳንዱ ከባቢ ላይ ተጽዕኖውን ያሳርፋል፤ የግለሰቦች ይሁን የድርጅቶችንም ግብር እና ምግባር ይቀርጻል፡፡ ይህን ሀቅ ስንቅ አድርጎ በመያዝ ኃይሌ ሪሶርቶችና ሆቴሎች  ከቃል በላይ የሆነ በተግባርም የተገለጸ አዲስ ባህልን ለመፍጠር ችሏል፡፡

በዚህ መጽሐፍ የምንነግራችሁ ንድፈ ሐሳብ አይደለም፤ ይልቁንም እየተኖረ ያለ እና በተግባር የተገለጸን እውቀት እንጅ፡፡ ይህም እውቀት የጋራ የሆነ እንጅ ለጥቂቱ ተገልጦ ብዙኃኑ ያላገኙት ትንቢት አይደለም፡፡ ለውጡም ከተግባርዎ፣ ከምግባርዎ፣ ከሥነ ልቦናዎም ዘንዳ የሚታጨድ እሸት ነው፡፡ ስሊዚህም እንዲህ እንላለን ‹‹ማንም ቢሆን ልክ እንደ ኃይሌ ማሰብን መልመድን እና መሥራትን ይችላል›› ስለዚህም ‹‹እኔም ኃይሌ ነኝ›› ፍልስፍና የስኬት ቁልፍ ለእርስዎ እነሆ!

Page 3 of 701