Administrator

Administrator

የሰሞኑ የከተማችን አብይ አጀንዳ የገቢዎችና የጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ሃላፊዎችና ትላልቅ ባለሃብቶች በሙስና ተጠርጥረው መያዛቸው ነው፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው የፌደራል ሥነ ምግባር እና ፀረ - ሙስና ኮሚሽን፣ የስነምግባር ትምህርት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ከሆኑት አቶ ብርሃኑ አሰፋ ጋር በወቅታዊ የሙስና ጉዳዮች ዙሪያ ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡ የሙስና ድርጊቶች እየተባባሱ መምጣታቸውን የሚናገሩ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ? የሙስና ተግባር በአለም አቀፍ ደረጃ ነው የሚታየው፡፡ ድንበር ተሻጋሪ ነው፡፡ በአንድ አገር ብቻ ተወስኖ የሚቀርብ ችግር አይደለም። ከሽብርተኝነት ቀጥሎ ሙስና አገርን የሚጐዳ እና እያሳሰበ ያለ ተግባር ነው፡፡ ዛሬ በዓለም ላይ የሚከናወኑ የእርዳታ እና የብድር ጉዳዮች እንዲሁም የንግድ ኢንቨስትመንቶች ሁሉ ከፍተኛ የገንዘብ እንቅስቃሴ የሚካሄድባቸው ናቸው፡፡ ከዚህ አኳያ ሙስና እንዳይስፋፋ አለም በደንብ ተጠናክሮ መስራት አለበት፡፡ ከዛ ውጪ በሙስና የተገኙ ገንዘቦች ህገወጥ በሆነ መንገድ ለተለያዩ ስራዎች የሚውሉበት ጊዜ አለ፡፡ አንዳንዴ ለሽብር ተግባር ሊውል ይችላል፡፡

ስለዚህ ከአለም አኳያ ስናየው የአለምን አጠቃላይ ሁኔታ ሊያናጋ የሚችል መሆኑን ሁሉም ተረድቶታል፡፡ በርካታ ስምምነቶች እየወጡ እየተሠሩበት ይገኛል፡፡ እኛ አገርም ስንመጣ ይሔ የሙስና ተግባር ትኩረት ካላገኘ አደጋ መሆኑ በመንግስት ታምኖበታል፡፡ የመንግስት የመልካም አስተዳደር ግንባታ ስራዎች ስኬታማ ሊሆኑ የሚችሉት ሙስናን መከላከል ስንችል ነው፡፡ ከድህነት ለመውጣት የምናደርገውን ጥረት ያደናቅፋል፡፡ ሙስና ለመብራት፣ ለውሀ፣ ለስልክ፣ ለት/ቤት በአጠቃላይ ለመሠረተ ልማት ግንባታና ለህብረተሠቡ የኑሮ መሻሻል የምናደርጋቸውን እንቅስቃሴዎች በተለያየ መንገድ ይጐዳል፡፡

የዲሞክራሲ ስርአት፣ የህግ የበላይነት፣ የመንግስት ተጠያቂነትና ሁሉም በህግ ፊት እኩል እንዳይሆን የማድረግ ተጽእኖም አለው። አንዳንድ ግለሰቦች በሀቅ ማግኘት ካለባቸው ውጪ ያለ አግባብ እንዲበለጽጉ ያደርጋል፡፡ ይሔ ሁሉ ተደምሮ ከድህነትና ከችግር እንዳንወጣ መሰናክል ይሆንብናል፡፡ መንግስት ይህንን በመመልከት ነው በክልል ደረጃ ዘጠኝ የሚሆኑ ቅርንጫፎችን በመክፈት፤ በፌደራል ደረጃ የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ያቋቋመው፡፡ ኮሚሽኑ ማስተባበር እና መምራት ነው እንጂ ሁሉን ነገር ተክቶ አይሠራም፡፡ ከሚዲያ፣ ከሀይማኖት ተቋማት፣ ከሙያ ማህበራት፣ ከንግዱ ማህበራት፣ እንዲሁም መንግስታዊ ካልሆኑ ተቋማት ጋር ግንኙነት እየፈጠርን መንግስትና ህዝቡ በጋራ የሚሠሩበትን ሁኔታ እያመቻቸን ነው፡፡ የባለሥልጣናትን ሃብት መዝግቦ ይፋ የማድረግ ሂደቱ ዘግይቷል ይባላል? ሀብትና ንብረትን ማሳወቅ ሲሆን ሙስናን ከመከላከል ተግባራት አንዱ ነው፡፡ እንግዲህ ከሁለት አመት ተኩል ጀምሮ ወደ 50ሺህ የሚሆኑ ሀብት ንብረታቸውን ማስመዝገብ የሚገባቸው ሠዎችን መዝግበናል፡፡ መረጃቸውን በሀርድ ኮፒ (በማንዋል) ለማዘጋጀት አስበን እየሠራን ነው፡፡

በዚህ በኩል ብዙ ጥያቄዎች እንዳሉ እናምናለን፤ ነገር ግን ኮሚሽኑም ይሔንን ሀብት ይፋ የማድረጉን ስራ በኢንተርኔት ለማንኛውም ሠው እንዲደርስ ነው ስትራቴጂ የቀየሠው፡፡ ይሔ ሲሆን በቀላሉ ማንም ሠው መረጃውን ማግኘት ይችላል፡፡ መረጃ ለህብረተሠቡ የሚሠጠው ያለ ምክንያት አይደለም። ያልተመዘገቡ ሀብትና ንብረቶች ካሉ፣ ምንጩ ያልታወቀ ሀብትና ንብረት እንዲያሳውቅ ለማድረግ ነው፡፡ ከህብረተሠቡ የሚደበቅ ነገር የለም፡፡ ቢዘገይም ከአለም ባንክ ጋር በመተባበር ይሔንን ስራ ለማካሔድና ግዢ ለማከናወን በእንቅስቃሴ ላይ እንገኛለን፡፡ እስከዛ ግን በማንዋል ደረጃም ቢሆን መረጃ ሲጠየቅ እንሰጣለን፡፡ እስካሁንም የሀያ ሶስት ሠዎችን መረጃ ተጠይቀን የሠጠንበት ሁኔታ አለ፡፡ እኛም ለምርመራ እነዚህን ሠነዶች እየተጠቅምን ነው፡፡

ቀደም ሲል ካሠብነው በላይ ነው የተመዘገበው፡፡ እኛ ያሠብነው 22ሺህ ነበር፤ አሁን ግን 50ሺህ ሠዎች ተመዝግበዋል፡፡ ይሔ አሠራር ለእኛ አዲስ ነው፤ ስለዚህ ከሌሎች አገራት ልምድ በመውሠድ እየሠራን ነው፡፡ በገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ከፍተኛ ሃላፊዎችና ባለሀብቶች ላይ ያደረጋችሁት ምርመራ አንድ አመት ተኩል የፈጀ ነው ተብሏል፡፡ እንዴት ይሔን ያህል ጊዜ ሊወስድ ቻለ? የምርመራው ሒደት እንዴት ተከናወነ፣ ለምን ተከናወነ የሚለውን ብዙም አላውቅም፡፡ ነገር ግን በዚህ ረገድ የሚከናወኑ የሙስና ወንጀሎች በጣም ውስብስብ እንደሆኑ መረዳት ይቻላል። ተጠርጣሪዎቹ ከፍተኛ ባለስልጣናት ያሉበት በመሆኑ ብዙ ጊዜ ይወስዳል፡፡ ከዛ ውጪ ትልቅ የሙስና ድርጊት ነው ብለን ስለምናምን፣ ጉዳዩን በጠንካራ ማስረጃ ላይ ተመስርቶ ለማቅረብ፣ በፍ/ቤትም የተሻለ ውጤት ለመፍጠር ታስቦ የተካሔደ ምርመራ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ ከዛ ውጪ የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር ክቡር አቶ መለስ ዜናዊ የሚከታተሉት የምርመራ ጉዳይ ነበር፡፡

እሳቸው ምርመራው ወደ መጨረሻ ደረጃ ላይ ሲደርስ ከዚህ አለም በሞት መለየታቸው እና ከዛ በኋላም ደግሞ የመተካካቱ ሒደት ስራው በፍጥነት እንዳይካሔድ የራሱ አስተዋፅኦ ነበረው፡፡ በዚህ ምክንያት ሰባት ስምንት ወር ዘግይቷል፡፡ የሰሞኑ ባለስልጣናትና ባለሀብቶች የተጠረጠሩበት የሙስና መጠን ከፍተኛ ነው ይባላል፡፡ ከፍተኛ ሲባል ምን ያህል ነው? እስካሁን የምርመራ ስራዎቻችንን አላጠናቀቅንም፡፡ ቢያንስ ምርመራውን ሊያጠናክሩና ክስ ሊያስከስሱ የሚችሉ መሠረታዊ ጭብጦችን የሚያስይዙ መረጃዎችና ማስረጃዎች እንደተሠበሠቡ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን ተጨማሪ ምርመራ የሚፈልጉ ነገሮች አሉ፡፡ የሠው ምስክር ሊሆን ይችላል፡፡ እነዚህን በማጠናከር ላይ ነው የምንገኘው፡፡ ስለዚህ ጥፋቶች በማን ተፈፀሙ፣ ማን በምን መልኩ የሚለውን በዝርዝር ምላሽ የምናገኘው ወደፊት ነው፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ግን ይሔንን ሁሉ ጊዜ ተወስዶ የተመረመረ መሆኑ በራሱ የጉዳዩን ትልቅነት የሚያሳይ ነው፡፡ ዝርዝር ጉዳዩን ማወቅ የሚቻለው ግን ወደፊት በፍርድ ሒደት ነው፡፡

የተጠርጣሪዎቹ የሀብት መጠን ተመዝግቧል? ሀብት የማስመዝገብ ሀላፊነት የተጣለባቸው ወገኖች፣ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ሠራተኞችን ሃብት እንደመዘገቡ አውቃለሁ፡፡ አካባቢው እና ዘርፉ ለሙስና የተጋለጠ በመሆኑ ሁሉም እንደተመዘገቡ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ሌሎቹ ግን ባለሀብቶች ናቸው፡፡ የግል ንግድ ላይ የተሠማሩት ስለማይመዘገቡ የእነሱ አይታወቅም፡፡ የሀብታቸውን መጠን ማወቅ ይቻላል? በአሁኑ ጊዜ ማሳወቅ ይከብዳል፤ ወደፊት ይፋ ይሆናል፡፡ “ግንዱ አልተነካም ቅርንጫፉም ጥቂቱ ነው የተነካው” የሚሉ ወገኖች አሉ … በመጀመሪያ ደረጃ እኛ የምንይዘው ሠውን አይተን አይደለም፡፡ እኛ የምናየው ምን አይነት የሙስና ወንጀል ወይም ድርጊት ተፈፅሟል የሚለውን ነው፡፡ ኮሚሽኑ ከዚህ በፊትም ቢሆን ከፍተኛ ባለስልጣናት እንዲጠየቁ የሚያደርግበት አሰራር ነበረው፡፡

እነዚህ ሠዎች የሚጠየቁት ከፍተኛ ባለስልጣናት ስለሆኑ ሳይሆን የሙስና ወንጀልን ስለፈፀሙ ነው፡፡ ትንሽም ይሁን ትልቅ ባለስልጣን መነሻችን ይሔ ነው፡፡ ከህግ በላይ የሆነ የለም፡፡ ከዚህ በፊትም ይሔንን ስናደርግ ነበር። ምናልባት በአሁኑ ሠአት በህዝቡ ውስጥ የተለየ ስሜት ፈጥሮ ሊሆን ይችላል፡፡ አሁን በመልካም አስተዳደር ችግሮች ለየት ባለ መልኩ የህዝብ እሮሮ በማየሉ ሊሆን ይችላል። አሁን የተያዙት ቅርንጫፎቹ ናቸው ግንዶቹ አይደሉም ያሉት። እንግዲህ ከሚኒስትር በላይ ግንዱ የቱ እንደሆነ ቢነግሩን ጥሩ ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ እኛ የሙስና ወንጀል እስከተፈፀመ ድረስ ማንንም በህግ እንጠይቃለን፡፡ ፀረ-ሙስና ከዚህ በፊት ትልልቅ ባለሥልጣናትን ለምን እንደማይከስ ተጠይቆ፣ በእኛ አገር እየታየ ያለው ሙስና በጣም ጥቃቅን ነው የሚል መልስ ሠጥቷል፡፡ አሁን ባለው ሁኔታስ ትልልቅ ሙስናዎች እየተፈፀሙ ነው ለማለት ያስችላል? ኮሚሽኑ ትልቅ የሙስና ወንጀል እኛ አገር የለም ብሎ የተናገረበትን ጊዜ አላስታውስም። እኛ አገር ትላልቅ የሙስና ወንጀሎች አሉ፡፡ አጋጥሞን መርምረን ለህግ ያቀረብንበት ጊዜ አለ።

የአሁኑም ተመሳሳይ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ከወርቅ ማጭበርበር ጋር ተያያዞ 153 ሚሊዮን ብር፣ በቴሌ የግዢ ጨረታ 1.8 ቢሊዮን ብር እንዲሁም በመሬት አስተዳደር ላይ ያደረግናቸው እንቅስቃሴዎች አሉ፡፡ ከዛ በኋላም የኤሌክትሪክ ሀይልን ቆጣሪ በማዘዋወር ከ60 ሚሊዮን ብር በላይና ከአገር ሊወጡ የነበሩ ወርቆችን የመሳሰሉ ትላልቅ የሙስና ወንጀሎችን መርምረናል። ሠርተናል፡፡ አንዳንድ ጊዜ እንደዚህ አይነት ሙስናዎች በትላልቅ ባለስልጣን መፈፀማቸው ወይም የገንዘቡ መጠን “ግራንድ ኮራፕሽን” ሊያሠኝ ይችላል፡፡ አንዳንዴ በአገሪቱ ደህንነትና ፀጥታ ላይ የሚያደርሠው ጉዳትም “ግራንድ ኮራፕሽን” ያሰኘዋል፡፡ አሁንም ትላልቅ ባለስልጣናት ላይ የሠራናቸው ምርመራዎች አሉ። ቁምነገሩ ትላልቅ ሙስናዎች አይፈፀሙም ሳይሆን የትኛው ይበዛል የሚለው ነው፡፡ ጥናቶች እንደሚያሳዩት፤ በአብዛኛው በኢትዮጵያ ውስጥ አነስተኛ ሙስና የምንላቸው ጐልተው ይታያሉ።

በቅርቡ ያካሔድነው የኢትዮጵያ የሙስና ቅኝት ጥናት የሚያሳየው፤ አነስተኛ ሙስና እንደሚበዛ ነው፡፡ አነስተኛ ሲባል ግን እያቃለልነው አይደለም። አብዛኛውን የህብረተሠብ ክፍል መቀነት የሚያስፈታና መከራ የሚያሳይ፣ በአገልግሎት አሠጣጥ ላይ እንዲጐሳቆል የሚያደርግ የሙስና አይነት ነው፡፡ ስለዚህ አነስተኛው ተብሎ የሚናቅ አይደለም፡፡ ብዙ ጊዜ የሚከሠቱትና ብዙዎቻችንን የሚያስለቅሱት እንደዚህ አይነት ሙስናዎች ናቸው። ሌላም አገር ብትሔጂ ትልልቅ ሙስናዎች በየዕለቱ አይፈፀሙም፡፡ ለዚህ ይሆናል ህብረተሠቡ ትልልቅ ሙስናዎች ላይ አታተኩሩም የሚለው፡፡ እለት በእለት እየተፈፀሙ ያሉት አነስተኛ የምንላቸው ናቸው፡፡ ለሙስና ተጋላጭ ከሆኑ ተቋማት በቀዳሚነት የምትጠቅሱት ጉምሩክን ነው፡፡ ሁለተኛስ? ገቢዎችና ጉምሩክ ለሙስና የተጋለጠ አካባቢ ነው ስንል፣ አንዳንዶች ሠራተኞቹ በሙስና የተዘፈቁ እና በሙስና የተጨማለቁ አድርገው ይወስዱታል። ይሔ ትክክል አይደለም፡፡

ለሙስና የተጋለጡ የምንላቸው፤ ጥንቃቄ ልናደርግባቸውና አይናችንና ሁለንተናችን ሊያርፍባቸው የሚገባ አሳሳቢዎቹ ቦታዎች ለማለት ነው፡፡ ከእነዚህ አካባቢዎች አንዱ ገቢዎችና ጉምሩክ ነው፡፡ በመቀጠል የኮንስትራክሽን ዘርፍ፣ ትልልቅ የመንግስት ግዢዎች፣… ቴሌኮም፣ የሀይል አቅርቦት፣ የመሬት አስተዳደር፣ ፍቃድ ሠጪ አካላትና የፍትህ አካላት… ለሙስና የተጋለጡ ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ በአገራችን የተሰሩ አንዳንድ ጥናቶችም የሚያሳዩት እነዚህ አካባቢዎች ለሙስና የተጋለጡ መሆናቸውን ነው፡፡ ተጠርጣሪዎቹን በምትይዙበት ወቅት የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ መላኩ ፈንቴ የአዲስ አበባ መስተዳድር ምክር ቤት አባል መሆናቸውን አታውቁም ነበር? በእኛ እምነት ተጠርጣሪው ይሔንን ቢገልፁልን ጥሩ ነበር፡፡ ሆኖም ቅሬታቸውን አቅርበው ፍ/ቤት ለግንቦት 19 ማስረጃቸውን እንዲያቀርቡ አዟል። እኛ ያው ህግን ተከትለን ነውና የምንሠራው ምን እንደሚሆን ወደፊት እናያለን፡፡

በእኛ በኩል መርመሪዎቻችን ይወቁ አይወቁ ገና አላወቅሁም። ግን አባል ከሆኑም ምን ይደረጋል የሚለውን እንወስናለን፡፡ ጥያቄው ከመብት ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ እኛ ግን ምርመራችንን እንቀጥላለን፡፡ አባልነታቸው ከተረጋገጠ ክሱ ይቋረጣል? አይቋረጥም፡፡ ከዚህ በፊትም አጋጥሞናል። ለምሳሌ የቤንሻንጉል አፈ ጉባኤ ያለመከሠስ መብት አላቸው፡፡ ያንን መብታቸውን የማስነሳት አግባብ ስላለ፣ ያንን በማድረግ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት ወስደናል፡፡ በአሁኑ ሁኔታ ግን ገና ምርመራ ላይ ነን። ክስም አልተመሠረተም፡፡ በአገሪቱ የሚፈፀሙትን የሙስና ወንጀሎች በሙሉ የመመርመር አቅም አላችሁ? የአቅም ጉዳይ በብዙ መንገዶች ይከፈላል። የሠው ሀይል ሊሆን ይችላል፡፡ የማቴሪያል ጉዳይ ሊሆንም ይችላል፡፡ ከሙስና ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመመርመር አቅም ያንሰናል የሚል ሀሳብ የለኝም። ነገር ግን የተሟላ ነገር አለን ለማለት አልችልም። የማስፈፀም ችግሮች በሁሉም በኩል የሚታዩ ናቸው፡፡ በእኛም በኩል ይሔ ችግር የለም ብሎ መደምደም አይቻልም፡፡ በአንድ ቦታ ያለን አቅም፣ በሌሎች ተለዋዋጭ ቦታዎች ላይሠራ ይችላል።

አቅም የመገንባቱ ስራ የማያቋርጥ ነው። በአንዱ ነገር አቅም ቢኖረን በሌላው ነገር ደግሞ ክፍተት ሊኖር ይችላል፡፡ አቅም አንዴ የሚገነባ ነው ማለት አይቻልም፤ ነገር ግን አሁን ባለንበት ሁኔታ ጥሩ የሆነ አቅም አለን፡፡ በተጨማሪ ደግሞ ከዚህ በፊት እንዳደረግነው ከሌሎች መንግስታዊ መ/ቤቶች ጋር በመቀናጀት እንሠራለን፡፡ የመረጃ ልውውጥ እናደርጋን፡፡ ለምሳሌ ከፖሊስ፣ ከመረጃና ደህንነት፣ ከዋና ኦዲተሮች ጋር የምንሠራበት ጊዜ አለ፡፡ ኦዲተሮች የእነሱን ሙያ የሚጠይቁ ነገሮች ኦዲት አድርገው እንዲልኩልን እናደርጋለን፡፡ አስፈላጊ ከሆነም የሌሎችን አቅም እንጠቀማለን። ይሔንን በማጠናቀር የበለጠ ሀይል በመያዝ የተለያዩ ስራዎችን እንሠራለን፡፡ ህብረተሠቡም አንዱ ሀይላችን ነው፡፡ ጥቆማ የሚሰጠውና ምስክር የሚሆነው ህብረተሠቡ ነው፡፡ ስለዚህ አቅም የሚባለው ነገር በዚህ በኩል እየተገነባና እየተሠራ የሚሔድ ነው፡፡ የአሁኑ ተጠርጣሪዎችን ጉዳይ ወደ እናንተ ያመጣው ግለሠብ ነው ወይስ ተቋም? ጥቆማውን ማን ሠጠው የሚለውን ነገር ለመናገር ይከብዳል፡፡ ነገር ግን ለእኛ ነው መጀመሪያ የተነገረን፡፡ ስለዚህ ይሔንን ሁኔታ ለማየትና ከሌሎች አካሎች ድጋፍ ለማግኘት ከቀድሞ ጠ/ሚ አስፈላጊው መመሪያ እንዲሠጥ አድርገን፣ በጋራ ስንሠራ ነው የቆየነው፡፡

በጥንቃቄ ለመሠራቱ ማሳያው አብዛኛዎቹ ተጠርጣሪዎቹ በስራ ገበታቸው ላይ እንዳሉ ነው የተያዙት፡፡ እኛ በቂ መረጃ እስኪኖረን ድረስ ምንም አይነት ነገር ማድረግ ስላልፈለግን ስራቸውን እንዲሠሩ ትተናቸው ነበር፡፡ ኮሚሽኑ ሌሎች ከፍተኛ ባለስልጣናትን ለመመርመር ድፍረት አግኝቷል ወይስ አሁንም ጠ/ሚኒስትሩን ማስፈቀድ አለባችሁ? ድሮም የሙስና ወንጀል በማንም በምንም ይፈፀም ድፍረት ያጣንበት ጊዜ የለም፡፡ ሠዎች እንደዚህ አይነት ሀሳብ ሊኖራቸው ይችላል። እኛን የሚያሳስበን ግን ሠዎችን ለመያዝና ወደ ህግ ለማቅረብ በቂ ማስረጃ አለን ወይ የሚለው ነው። ድፍረታችን የሚወሰነው ባለን ማስረጃ ነው። ሠዎችን ደፍረን ለመጠየቅና ፍ/ቤት ለመውሠድ የሚያስችለን ማስረጃ ካለን ምንም የሚያስፈራን ነገር የለም። በዚህ ሁኔታም ከዚህ በፊት ጠይቀናል። አሁንም ከፍተኛ ባለስልጣንን እየጠየቅን ነው። ነገም ማስረጃ ካለን እንጠይቃለን፡፡ ሌላው እኛ ማንንም ሠው ለመያዝ ጠ/ሚኒስትሩን አንጠይቅም። ምናልባት ጠ/ሚኒስትሩን ጠየቀን ያልነው፣ ሌሎች አካላት ድጋፍ እንዲሰጡን ከማድረግ አኳያ እንጂ እኛ ነፃነት አለን፡፡

በኮሚሽኑ አዋጅ ውስጥ በምርመራ ሁኔታ ላይ ያለማንም ጣልቃ ገብነት መስራት እንዳለብን ይደነግጋል፡፡ እስካሁን ጣልቃ ገብቶ ይሔንን አድርግ ያለን አካል የለም፡፡ ከተቋቋማችሁ ጊዜ ጀምሮ ከፍተኛ ምርመራ ጠይቆ የተሠራው የሙስና ወንጀል የአሁኑ ነው ማለት ይቻላል? በእኛ እምነት አሁን እያደረግን ያለነው እንቅስቃሴ ትልቅ ድል ነው፡፡ በፍ/ቤት ተከራክረን በመርታት አጥፊዎች ተገቢውን ቅጣት አግኝተው ያለ አግባብ የተወሠደው የመንግስትና የህዝብ ሀብት እንዲመለስ በማድረግ፣ ሂደቱን በውጤት ስንቋጨው ትልቅ ከሚባሉ የሙስና ወንጀሎች አንዱ እንደሚሆን እርግጠኛ ነኝ፡፡ አንዳንድ ባለሀብት ለስራው የጥሬ እቃ አቅርቦት ያጣና ከውጪ ለማስገባት ሲል ካቅሙ በላይ በሆነ ችግር ጉቦ ተጠይቆ ሊከፍል ይችላል፡፡ ይሄና ያልተገባ ሀብትን ለማፍራት የሚፈፀሙ የሙስና ድርጊቶችን በእኩል ዓይን ነው የምታዩት? ነጋዴው እንዲህ አይነት ችግር ሲደርስበት ሙስና ውስጥ ገብቶ እራሱን፣ ሀብቱንና ቤተሠቡን ችግር ላይ መጣል የለበትም፡፡ እንደ እኛ አይነት አካላት አሉ፡፡ እዛ ሔዶ ችግሩን ማስረዳት እና ችግሩን እንዲፈቱለት ማድረግ እንጂ ወንጀል ውስጥ እየገቡ ተቸግሬ ነው ማለት አያዋጣም፡፡ ይሄ ራስን ለማበልፀግ ካለ ፍላጐት የሚመነጭ እንጂ ምክንያት ሆኖ ሊቀርብ የሚችል አይደለም፡፡

አቶ ሽመልስ ከማል - የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስቴር ሚኒስትር ዲኤታ

   በተለያዩ ማህበራዊ ድረ-ገፆች እንዲሁም በአንዳንድ ፖለቲከኞች ዘንድ ከሙስና ወንጀል ጋር ተያይዞ የታሠሩ ግለሠቦችን በተመለከተ ጉዳዩ የፖለቲካ ነው የሚሉ አስተያየቶች ይሰነዘራሉ፡፡ መንግስት በዚህ ላይ አቋሙ ምንድን ነው? ህብረተሠቡና መንግስት ሙስናን በጋራ ለመከላከል የሚያደርጉትን ጥረት ለማኮሠስ ነው ፖለቲካ ነው የሚባለው፡፡ ይሄን ጥረት ለማክሸፍና ለማምከን የሚደረግ ጥረት ነው፡፡ የተለየ ነገር የለውም፤ በማስረጃ ተደግፎ በጓዳ ሣይሆን በአደባባይ የሚሠራ ነው፡፡

እንዴት ተብሎ ነው ፖለቲካ ነው የሚባለው? የፖለቲካ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እየሠጡ ያለውን አስተያየት እየሠማሁት ነው፡፡ እነሡ ሁለት ስለት ያለው ቢላ ነው ያላቸው፡፡ ደስ ሲላቸዉ ሙስናን አልተከላከለም ብለው መንግስትን ይወቅሣሉ፡፡ መዋጋት ሲጀምር ደግሞ ፖለቲካዊ ነው ብለው ያወግዛሉ፡፡ ምንም የማያስደስታቸው፣ በምንም መንገድ ብለው መንግስትን ለማውገዝ የሚጥሩ ናቸው፡፡ ይህን አይነቱን እርምጃ ፖለቲካዊ ነው ብሎ ማለት ለኪራይ ሠብሣቢነት አሠራር ድጋፍ ማበጀት ነው፡፡ ለኪራይ ሠብሣቢዎች ድጋፍ መስጠት ነው፡፡ ይሄ ከኪራይ ሠብሣቢዎች መንደር የሚነሣ ሃሣብ ነው፡፡ ገና ለገና ይመጣብናል ብሎ የሚያስበው ሁሉ ነው ፖለቲካዊ ነው የሚለው፡፡ አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የተናገሩትን ጋዜጣ ላይ አንብቤአለሁ “ሠው እየተደናበረ ነው” ብለዋል፡፡

ማን ነው የሚደናበረው? የተነካካ ነው የሚደናበረው፤ ይመጣብኛል ብሎ የሚፈራው እሱ ነው፡፡ መንግስት ይህን አይነት እርምጃ ሲወስድ የመጀመሪያ ጊዜው አይደለም፡፡ ከዚህ በፊት ከጠቅላይ ሚኒስትር ታምራት ላይኔ ጀምሮ እንደ ስዬ አይነት የመከላከያ ሚኒስትሮች፣ ሌሎችም ሃላፊዎችን በሙስና ባገኛቸው ጊዜ እርምጃ ወስዶባቸዋል፡፡ የእነሡ ጉዳይ ፀሃይ የሞቀው ነው፤ በፍርድ ቤት ተከራክረውበት በማስረጃ ተረጋግጦ የተቀጡበት ነው፡፡ እርምጃው ዛሬ አልተጀመረም፤ በእርግጥ ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበት ነበር፡፡ አሁን መንግስት በአዲስ መልኩ ተጠናክሮ እቀጥላለሁ ብሎ እየሠራ ነው፡፡ በዚህ ዙሪያ በህብረተሠቡ ዘንድ ወጥነት ያለው ብሄራዊ መግባባት ነው የተፈጠረው ማለት ይቻላል፡፡ ሙስና ላይ ለምን መጣችሁ ብሎ የሚኮንነው ወገን ለይቶ ወጥቷል፡፡

ማን ከሙስና ጐራ እንዳለ አሁን ነው የሚለየው፡፡ ሙሠኞችን ነካችኋቸው ብለው ፖለቲካዊ እርምጃ ነው የሚሉ ሠዎች ማህበራዊ መሠረታቸዉ በሙስና የተበደለው ድሃው ህብረተሠብ ሣይሆን፣ በሙስና በአቋራጭ መክበር የሚፈልገው ኪራይ ሠብሣቢ ነው፡፡ በሌላ አባባል እያሉ ያሉት አትንኳቸው፣ አትምጡባቸው ነው፡፡ መንግስት ለምን ፀረ-ሙስና እና ፀረ ኪራይ ሠብሣቢነት ላይ እርምጃ ወሠደ የሚል አመለካከት ነው፡፡ ህብረተሠቡ በሙሉ ልቡ ፖለቲካዊ ድጋፍ ሠጥቶታል፡፡ ተጠናክሮ ይቀጥል እያለ ነው፡፡ ጥቂት ወገኖች ደግሞ ለምን እርምጃ ይወሠዳል ብለው “ቡራ ከረዩ” እያሉ ነው፡፡ የአንደበት ግልጋሎት ሲሠጡ የነበሩ ግለሠቦች፣አሁን ትክክለኛ ስራው ሲጀመር “አትንኳቸው፣ ፖለቲካዊ ነው” የሚሉ አስተያየቶችን በመስጠት ራሣቸው የሞራል ግብረአበሮች መሆናቸውን እያሳዩ ነው፡፡

“ኢህአዴግም እንደ ድርጅት ሙሠኛ ነው” ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ -የመድረክ አመራሮች አባል

የመንግስት መዋቅር በሙስና የተዘፈቀ ነው የሚል ትችት በተደጋጋሚ ትሰነዝራላችሁ፡፡ ኢህአዴግ ዋናዎቹን ትቶ በትናንሽ ሙሰኞች ላይ ነው የሚያተኩረው፣ይህ ደግሞ ሙስናን እየተከላከለ ነው አያሠኘውም ትላላችሁ፡፡ ከዚህ አንፃር ሠሞኑን በገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከፍተኛ ሃላፊዎችና ባለሃብቶች ላይ የተወሠደው እርምጃ የዚህ ትችትና ምክር ውጤት ነው ማለት ይቻላል? ይህ እንግዲህ አንደኛ በጣም የገዘፈን ነገር እንዲሁ መነካካት ነው፡፡ ምክንያቱም ኢህአዴግና ስርአቱ፣ አባሎቼና ደጋፊዎቼ የሚላቸው አሉ፡፡ እነሡ ሃገሪቱን በሙሉ እንዲበዘብዙ ድጋፍ ይሰጣቸዋል፡፡

ከዚህ አንፃር የሠሞኑ እርምጃ መነካካት ነው፡፡ ዋናውን የሙስና ሠንሠለት ለመበጣጠስ የጀመረው እንቅስቃሴ ነው ለማለት ገና ነው፡፡ እስካሁን ባሳለፈው 21 የስልጣን አመታት አንዳንዴ በፖለቲካውም በዲፕሎማሲውም ሲጨንቀው ከሹመኞቹ ውስጥ ጭዳ የሚያደርጋቸው አሉ፡፡ እነዚያን እየሠዋ ይሄው እርምጃ እየወሠድኩ ነው፤ በማንም ላይ ቢሆን መረጃ እስካለ ድረስ እርምጃ ለመውሠድ ዝግጁ ነኝ የሚል የፖለቲካ ጨዋታ አለው፡፡ በሽግግሩ ወቅት ከአቶ ታምራት ላይኔ አንስቶ፣ አቶ ስዬ፣ ሌሎቹንም ከህወሃት ጋር የተጋጩትን ሲያስር ሲፈታ ነው የኖረው፡፡ በዚያ ሠሞን ኢህአዴጐች ጉባኤ እያካሄዱ ነበር፡፡ ይህ እርምጃ ደግሞ ከጉባኤው ተከትሎ የመጣ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የፖለቲካ ጉዳይ እንዳለበት ምልክትም ሊሆን ይችላል፡፡ የፍትህ ሚኒስትሩ አቶ ብርሃንም እንዲነሡ ተደርጓል፡፡ የገቢዎች ባለሥልጣን እቃዎችን ከቀረጥ ነፃ የማስገባት ነገር ስላለው ከለጋሾች ጋር ያነካካል፡፡

እናም ጫናውን ትንሽ ለማስተንፈስም ጭምር ያደረጉት ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ ሁሉንም በሂደት የምናየው ይሆናል፡፡ እርምጃው በዚህ ላይ ብቻ የሚቆም ከሆነ በመሠረቱ የሚያደላው ፖለቲካዊ ፋይዳው ነው፡፡ ሙስና እንግዲህ አዲስ አበባንም ሆነ ሌሎች ከተሞችን ያጣበበ ነው፡፡ ሁሉም ጋ ሄደው እርምጃ የሚወስዱ ከሆነ እሠየው የሚያሠኝ ነው፡፡ በኛ እምነት ይሄ ሁሉ ከበርቴ ሚሊየነርና ቢሊየነር ዝም ብሎ እየፈላ ያለው፣ የሃገሪቱን ህዝብ ሃብትና ገንዘብ እየበዘበዘ ነው፡፡ ሙሰኝነቱ ነው አብዛኛውን እዚህ ያደረሠው፡፡ ኢህአዴግም እንደ ድርጅት ሙሠኛ ነው፡፡ ኪራይ ሣይከፍል የሚጠቀምባቸው ትላልቅ ህንፃዎች አሉ፡፡ እነሱ የህዝብ ንብረቶች ናቸው፡፡ ኢህአዴግ ከዋናው ፅ/ቤቱ አንስቶ ሌሎች ስራዎችን የሚሠራባቸውን ቢሮዎች እንደማንኛውም ፖለቲካ ፓርቲ ኪራይ እየከፈለ ነው የሚጠቀመው? ይህ እንግዲህ በምርመራ ጋዜጠኞች መጣራት ያለበት ነገር ነው፡፡

እኔ እስከማውቀው ድረስ ግን እንደማይከፍሉ ነው፡፡ በቅርብ ጊዜ የተለወጠ ነገር ከሌለ እያንዳንዱ የኢህአዴግ ካድሬ ገብቶ የሚኖርባቸው ያኔ ከደርግ የወረሣቸዉ ትልልቅ ቤቶች ኪራይ ይከፈልባቸዋል? እኔ እስከማውቀው ድረስ ሣይከፍሉ ነው የሚጠቀሙት፡፡ መረጃው በጋዜጠኞች ሊቀርብ ይገባዋል፡፡ ቦሌ ያሉ የድሮ ትልልቅ መኳንንት የሠሯቸውን ቪላ ቤቶች፣ ከትግሉ መልስ እየተሽቀዳደሙ እንደገቡበት ነው የምናስታውሠው፡፡ ከዚህ በላይ ሙሠኝነት አለ እንዴ? የህዝብ ንብረት እኮ ነው ወይ ለባለቤቶቹ አልተመለሠ? ኢህአዴግ ሙሠኛ ነው ልንል የሚያስችሉን እነዚህ ነጥቦችና ሌሎችም ናቸው፡፡ ሙሠኝነት በኢትዮጵያ ውስጥ መሠረቱ በጣም ሠፊ ነው፡፡ አደገ የሚባለው ኢኮኖሚ፣ ተሠሩ የሚባሉት ሠማይ ጠቀስ ፎቆች መሠረታቸው ሙሠኝነት ነው፡፡

ከበርቴ ነን ከሚሉት የአንዳንዶቹን መነሻ እናውቃለን፡፡ ራሱ ገዥው ፓርቲ የሚያንቀሣቅሳቸው የኢንዱስትሪና የንግድ ድርጅቶች ሣይቀሩ የሙስና ጉዳይ ያለባቸው ናቸው፡፡ አንዳንድ ወገኖች ዘግይቷል ቢሉም በገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣናት ላይ ሰሞኑን የተወሠደው እርምጃ ኢህአዴግ የሙስና ችግሮችን ለማፅዳት መቁረጡን አያመለክትም? በአሁኑ ደረጃ እርምጃ መውሠድ ጀምሯል ማለት አንችልም፡፡ ምክንያቱም አሁንም ትላልቅ አሣዎች አሉ፡፡ በዚህ ዘመን እኮ የኢህአዴግ አባል ወይም ደጋፊ መሆን ማለት ከበርቴ መሆን ነው፡፡ ብዙዎቹ በዚህ መሠረት ተጠቅመዋል፡፡ እንዳሁኑ ዓይነት እርምጃዎች ከቀጠሉ መሠረቱ ሊናጋ ነው ማለት ነው፡፡ ፓርቲው የህዝብ ሃብትን ለራሱ እየተጠቀመ ከመሆኑም በላይ ወዳጆቹን እንዴት እየጠቀመ ነው የሚለውንም ማየት ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ አንፃር ኢህአዴግ ራሱን ማፅዳት ጀመረ ማለት ይቸግራል፡፡ እንዲያ ከሆነ ከውስጥ ትልቅ ቀውስ ተፈጠረ ማለት ነው፡፡

 “ይሄ የዶሮ ትራፊ ነው፤ ትልቁ ገንዘብ የት ነው ያለው?” ኢ/ር ሃይሉ ሻውል -

የመኢአድ ፕሬዚዳንት በሙስና ተጠርጥረው የተያዙት ሠዎች ጉዳይ የፖለቲካ ግንኙነት ያለው ይመስላል፡፡ ይህ ደግሞ አምባገነን መንግስት ባለበት ሁሉ የሚደረግ ነው፡፡ በደርግ ጊዜም የማይፈለግ ሠው እንደዚህ ይደረግ ነበር፡፡ በእርግጥም የተያዙት ሠዎች የተጠረጠሩበት ጉዳይ እውነት ከሆነ እርምጃው ይቀጥላል ብዬ አምናለሁ፡፡ በሙስና የደለቡትን አንስተው ያሣዩን ይሆናል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ነገሩን ሙስና ብቻ ብሎ ለመቀበል ይቸግራል፡፡ በቅርቡ ለፓርላማ በቀረበው ሪፖርት ላይ፣ የፌዴራል ኦዲተሩ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ከፍተኛ የገንዘብ ጉድለት መኖሩን ጠቁሟል፡፡ ዛሬ እነዚህ ሠዎች ቤት አንድ መቶ ሺህ ብር ተገኘ፤ ሲባል ይሄ የዶሮ ትራፊ ነው፤ ትልቁ ገንዘብ የት ነው ያለው? ከዚህ ቀደም የአለም ሚዲያዎች ብዙ ቢሊዮን ዶላር ከሃገር እንደወጣ ነግረውናል፤ እኔ ቁጥሩን አላስታውሠውም፡፡ ይህንንና አሁን የተነገረውን ስናስተያይ ገና ጫፉም አልተነካም፡፡ 

“አሣ ማጥመጃው ትልልቅ አሣዎችን የሚያጠምድ ከሆነ እንተባበራለን” ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማሪያም -

አለማቀፍ የህግ ምሁር በሙስና በተጠረጠሩት ላይ መንግስት በወሠደው እርምጃ ምን አስተያየት አለዎት? የተወሠደው እርምጃ የሚቀጥል ከሆነ በእውነት የሚመሠገን ነው፡፡ የተወሠደው እርምጃ ግን ካለው ሁኔታ ጋር ሲመዛዘን ኢምንት ነው ማለት ይቻላል፡፡ አሁን የታየው ኢምንቱ ነው፡፡ ይህ ተጠናክሮ የሚቀጥል ከሆነ እሠየው የሚያስብል ነው፡፡ ለዚህ ሁሉም ኢትዮጵያዊ መተባበር አለበት፡፡ ለፖለቲካ ጥቅም ወይም በፖለቲካ ግጭት ምክንያት የተፈጠረ ከሆነ ግን ለኢትዮጵያ ህዝብ የሚጠቅመው ነገር የለም፡፡ ዝም ብሎ ጊዜ ማባከን ነው፡፡ መዘንጋት የሌለበት ግን ከእነዚህ የበለጡ ትላልቅ አሣዎች ዛሬም አሉ፡፡ እነዚህ አሣዎች እስካሁን ድረስ አልተነኩም፡፡ አሣ ማጥመጃው እነዚህን ትልልቅ አሣዎች የሚያጠምድ ከሆነ፣ እኛም እሠየው ብለን እንተባበራለን፡፡ አንዳንዶች የጉምሩክ አሠራር በራሱ ለሙስና ምቹ ነው ይላሉ፡፡ እርስዎስ? በእርግጥም ጉምሩክ አሠራሩ በራሱ ለሙስና በር ከፋች ነው፡፡ ራሱ ከሣሽ ነው፣ ዳኛ ነው፡፡ መጀመሪያውኑ ለሙስና አመቺ ሆኖ የተዋቀረ ነው፡፡ ያዋቀሩት ሠዎች ግልፅ ባልሆነ መንገድ የህዝቡን ሃብት ለመንጠቅ ያደረጉትም ሊሆን ይችላል፡፡ እርግጥ ነው አሁን መንግስት ይህን ነገር ማጥፋት ከፈለገ መዋቅራዊ ለውጥ ማድረግ አለበት፡፡ መዋቅሩን በሙሉ መለወጥ አለበት፡፡ አንድ ሁለት ሠው በመክሠስ ብቻ ችግሩ የሚወገድ አይደለም፡፡ ሃገራችን ከዚህ ቀደም ሙስናን በተመለከተ በአለማቀፍ ደረጃ በጣም ጥሩ ሪከርድ ነበራት፡፡ አሁን በትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል አመዘጋገብ ወደ 3ኛ ደረጃ ተጠግታለች፡፡ ይሄ በጣም አሣፋሪ ነው፡፡

“ገቢዎች ከመንግስትም በላይ ስልጣን የተሰጠው አካል ነው” አቶ ሙሼ ሠሙ - የኢዴፓ ሊቀመንበር

ፀረ ሙስና ኮሚሽን ሰሞኑን በሙስና በጠረጠራቸው ትላልቅ ባለስልጣናትና ባለሃብቶች ላይ የወሠደውን እርምጃ እንዴት ይመለከቱታል? ለኛ ይሄ ነገር የተለየ እውቀት የሚጠይቅ አይደለም፡፡ ስቴት ካፒታሊዝም ወይም መንግስታዊ ከበርቴ የምትለው ስርአት አይነተኛ መገለጫው ነው፡፡ ነጋዴውን ህብረተሠብ የሚያሸማቅቅ፣ የመንግስትን ሚና የሚያጐለብት ነው፡፡ የንግዱን ማህበረሠብ የመንግስት ባለስልጣን ጥገኛም እንዲሆን ያደርገዋል፡፡ ጉዳዩን ለማስፈፀም፣ ስራውንም ለመስራት ሣይወድ በግዱ የመንግስት ባለስልጣናት አሽከር ይሆናል፡፡ ነጋዴውና የንግዱ ማህበረሠብ እየተዳከመ መንግስት እንዲተካው ነው ጥረት እየተደረገ ያለው፡፡ መጨረሻ ላይ ይህ ስርአት ወዴት ነው የሚሄደው? ሂደቱ የመንግስት ባለስልጣናትን ከበርቴ የሚያደርግ ነው፡፡

ምክንያቱም ነጋዴው ችግሮቹን የሚፈታበትን መንገድ የሚያመለክት አይደለም፡፡ ባለሃብቱ በጥርጣሬ ነው የሚታየው፡፡ ታማኝ አይደለም፣ ብቁ አይደለም፣ ስርአት የለውም እየተባለ ነው፡፡ ግለሠብ ነጋዴውን በጥርጣሬና በስጋት የማየት አዝማሚያ አለ፡፡ ስግብግብ፣ ሌባ፣ ወንበዴ ወዘተ--- ተደርጐ ነው የሚታየው፡፡ አሁን የተያዙት ባለስልጣኖች ይሄ ሁሉ ጉድ እያለባቸው ነው ነጋዴውን ሲያስፈራሩት፣ ሲዝቱበትና ኪራይ ሠብሣቢ ሲሉት የኖሩት፡፡ ስርአቱ ለእነዚህ ባለስልጣኖች መደራደሪያ በር ከፍቶላቸዋል፡፡ የፈለጉትን ነጋዴ በፈለጉት ጊዜ ጠርተው እያሸማቀቁና ስሙን እያጠፉ ህገወጥ በሆነ መንገድ መጠቀሚያ አድርገውታል፡፡ ይሄ ለኔ ሠዎችን የማሠርና ያለማሠር ጉዳይ ብቻ አይደለም፤ የስርአቱን የአስተሣሠብ ለውጥ የሚፈልግ ነው፡፡

የመንግስት ሹመኞችና ባለስልጣኖች የነጋዴውን ማህበረሠብ እንደ ሌባ፣ አታላይ፣ አጭበርባሪ፣ ኪራይ ሠብሣቢና ጠላት አድርገው የሚያዩበት ሁኔታ እስካልተለወጠ ድረስ ሙስናው ይቀጥላል፣ የመደራደሪያ በር ነው የሚከፍተው፡፡ አሁን የወሠዱት እርምጃ የሚደነቅ ነው፡፡ በሂደት ግን ውሣኔውንም የምናየው ይሆናል፡፡ አሁን የተደረገው “የበረዶ ጫፍ ነው” (Tip of the ice burg) እንደሚሉት ፈረንጆቹ፡፡ ትልቁ ጫፍ ገና ውሃው ውስጥ ነው ያለው፡፡ እንጀራ ጋግራ ከምትሸጥ ሴት ጀምሮ ገንዘብ የሚሠበሰብ መስሪያ ቤት፣ በዚህ ደረጃ መርከስና መበስበስ ውስጥ ከገባ፣ ሥርዓቱ ለአደጋ መጋለጡን ነው የሚያሳየው፡፡ በአጠቃላይ ስርአቱ የተጋረጠበት አደጋ መገለጫው ይሄ ሊሆን ይችላል፡፡ ከዚህም በፊት ሙስና ነበረ፤ ግን በመቶ ሚሊዮኖች አልነበረም፡፡ ነጋዴው አቤት የሚልበት ነፃና ገለልተኛ አካል ነበረው፤ አሁን ግን መስሪያ ቤቱ የራሱ ፖሊስ አለው፡፡

ዳኛ ነው የፈለገውን ነገር ይፈርዳል፡፡ አቃቤ ህግ ነው፡፡ ታዲያ እንዴት ከዚህ መስሪያ ቤት ጋር መስራት ይቻላል? ይሄ እኮ ከመንግስትም በላይ ስልጣን የተሠጠው አካል ነው፡፡ እነዚህ ሠዎች ዳኛ ናቸው፣ ፍርድ ቤት ናቸው፣ አቃቤ ህግ ናቸው፣ ፖሊስ ናቸው፡፡ ስርአቱ እንደፈለጉ እንዲፈልጡ እንዲቆርጡ ስልጣን ስለሠጣቸው፣ የድፍረታቸው ድፍረት ቤታቸው በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ማስቀመጣቸው ተነግሮናል፡፡ ስርአቱን እንዳለ በገንዘብ፣ በጉቦ መቆጣጠር የሚችሉበት ደረጃ ላይ መድረሣቸውን ነው የሚያመለክተው፡፡ አንድ ሌባ የሠረቀውን ነገር ቤቱ የሚያስቀምጠው እኮ በጣም ደፋር ሲሆን ነው፡፡ ይህ እንግዲህ የስርአቱ መገለጫ ነው፡፡ የተወሠደውን እርምጃስ እንደ መልካም ጅማሮ ማየት ይቻላል? ልትወስደው ትችላለህ፡፡ ግን ዋናው ችግር ግለሠቦቹ ላይ አይደለም፤ ሥርዓቱ ላይ ነው፡፡ ማህበረሠቡ ሙስናን የሚፀየፍ ፣ የመንግስት ባለስልጣናት ደግሞ ተገቢውን ክፍያ እያገኙ ስራቸውን እንዲሠሩ ማድረግ ነው ጠቃሚው፡፡ ይሄን ሠውዬ ብታስረው ገና የእሡ ርዝራዦችና መሠሎቹ በየመስሪያ ቤቱ አሉ፡፡

ይሄ ነገር እኮ ሲባል የከረመ ጉዳይ ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩም አንድ እጄን ታስሬ እየሠራሁ ነው እስከማለት ደርሠው ነበር፡፡ ይሄ የሚያሣየው ምን ያህል ስር የሠደደ ችግር እንደሆነ ነው፡፡ ግለሠቦችን ማሠር ሙስናን ለመዋጋት አንድ መገለጫ ነው፤ ዋናው ነገር ግን የአስተሣሠብ ለውጥ ነው፡፡ ፍትሃዊ የሆነ የህግ ስርአት ሊበጅ ይገባል፡፡ ለአንድ መስሪያ ቤት የእግዚአብሔርን ያህል ጉልበት ተሠጥቶት እንዴት ሙስናን መዋጋት ይቻላል፡፡ ህገ ወጥ ነገር ለመስራት ሁሉም ነገር ተመቻችቶለታል፡፡ ይህ እያለ እንዴት ነው ሙስናን መታገል የሚቻለው፡፡ እርግጥ ስርአቱ በሽታውን ተረድቶ እርምጃ ለመውሠድ መነሣሣቱ የሚበረታታ ነው፡፡ ነገር ግን ጉዳዩ እየተጋነነ እየተወራ ነው፡፡ አንዳንድ ነጋዴዎችም እንዲበረግጉ እየተደረገ ነው፡፡

በዚህ ጉዳይ መንግስት ጥንቃቄ ሊያደርግ ይገባል፡፡ ሠዎቹ እንደየጥፋታቸው ፍትህ ፊት ቀርበው ተመጣጣኝ ቅጣት የሚያገኙበትን መንገድ መከተል ነው እንጂ ድራማ መስራት አይጠቅምም፡፡ ማጋነን፣ ነገሩን ከሚገባው በላይ መለጠጥ፣ ማህበረሠቡ በዚህ ጉዳይ የተዛባ መረጃ ኖሮት ያልተገባ ነገር እንዲናገር ማድረግ ተገቢ አይደለም፡፡ እነዚህ ነጋዴዎች ተገደው የገቡ ሊሆኑም ይችላሉ፡፡ ሌሎች ደንግጠውና በርግገው ሃገር ጥለው እንዲሄዱ የሚያደርግ መሆን የለበትም፡፡ እነዚህ ሠዎች አሁንም ገና ተጠርጣሪ ናቸው፡፡ ስርአት ባለው መንገድ ተይዘው የሚቀጡ ከሆነም መቀጣት አለባቸው፡፡ አሁን ግን የሚወራው ያለቀ ጉዳይ ተደርጐ ነው፡፡ ቀድሞ በፕሮፓጋንዳ ግለሠቦቹን ወንጀለኛ አድርጐ ደምድሞ፣ ፍርዱ ትርጉም እንዲያጣ ማድረግ አይገባም፡፡ እነዚህ ሠዎች እኮ በአንድ ጊዜ ስማቸው ወርዷል፣ የፕሮፓጋንዳው ሠለባ ሆነዋል፡፡ ሌሎችም እንዲበረግጉ ሆኗል፡፡ ነገር ግን መንግስት “እነዚህ ግለሠቦች ተይዘዋል፣ ሌላው ነጋዴ ተረጋግቶ ስራውን ይስራ” ማለት ነበረበት፡፡ ጠቅለል ብሎ ሲታይ የዚህ ሁሉ መሠረታዊ ችግር ይሄ መስሪያ ቤት የተሠጠው ከእግዚአብሔር ያልተናነሠ ስልጣን ነው፡፡ መንግስት አሁንም በነጋዴው ላይ ያለውን የተዛባ አመለካከት ይለውጥ፡፡

  • ክሳት የሚታይባቸው አቶ መላኩ፤ “ያለመከሰስ መብቴን ትቼዋለሁ” አሉ፡፡
  • “ፀሐይና ነፋስ በማይገባበት ክፍል ለብቻዬ ታስሬያለሁ” - አቶ መላኩ
  • “በስርዓቱ መሰረት ችግሮችን ለመፍታት እንጥራለን” - ማረሚያ ቤት
  • የተጠርጣሪዎች ቁጥር 31 ደርሷል፤ ሰኞ ፍ/ቤት ይቀርባሉ

የሚኒስትሮች ካቢኔ አባል የሆኑት የጉምሩክና ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ዳሬክተርና ምክትላቸውን ጨምሮ በሙስና ተጠርጥረው የታሰሩ ታዋቂ ባለሃብቶች ፍ/ቤት ሲቀርቡ የሰነበቱ ሲሆን፤ የፀረ ሙስና ኮሚሽን በሁለት ሳምንት ውስጥ ምርመራውን አጠናቅቆ ክስ እንዲመሰርት ፍ/ቤት አዘዘ፡፡ የዋስ መብት ያልተፈቀደላቸው ተጠርጣሪዎች፣ ከጠበቃ ጋር የመገናኘት መብታችን እንዲከበር ፍ/ቤቱ ትዕዛዝ ቢሰጥም ማረሚያ ቤት ፈቃደኛ አልሆነም በማለት አማርረዋል፡፡ በሦስት የምርመራ መዝገብ ከፍሎ ተጠርጣሪዎችን ወደ ፍ/ቤት ያቀረበው የፀረ ሙስና ኮሚሽን፤ በአንደኛው መዝገብ ሰባት ተጠርጣሪዎችን አካትቷል፡፡

ከአሁን ቀደም አራጣ በማበደር፣ ታክስ በማጭበርበርና በኮንትሮባንድ ንግድ ከተከሰሱ ሰዎች ጉቦ ተቀብለው ክስ እንዲቋረጥ አድርገዋል በሚል ጭብጥ ዙሪያ የምርመራ መዝገብ የተከፈተባቸው የሚከተሉት ናቸው፡፡ አቶ መላኩ ፋንታ - የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ እሸቱ ወልደሰማያት - የባለስልጣኑ የአቃቤ ህግ ዳሬክተር አቶ መርክነህ አለማየሁ - የባለስልጣኑ የወንጀል መከላከል ቡድን መሪ አቶ አስመላሽ ወልደማርያም - የቃሊቲ ጉምሩክ ሃላፊ አቶ ከተማ ከበደ - የኬኬ ኩባንያ ባለቤት አቶ ስማቸው ከበደ - የኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ባለቤት ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ - የህክምና ባለሙያ ሰባቱ ተጠርጣሪዎች ፍ/ቤት በቀረቡበት የምርመራ መዝገብ ከፀረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ቡድን ጋር ያደረጉት የቃል ክርክር፣ በዋስ መብትና መቼ ክስ መቅረብ አለበት በሚል ጥያቄ ዙሪያ ነው። አቶ መላኩ ፋንታ በጠበቃቸው በኩል ባቀረቡት መከራከሪያ፣ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል እንደሆኑ ጠቅሰዋል፡፡

የምክር ቤት አባል እጅ ከፍንጅ ካልተያዘ በቀር ያለመከሰስ መብቱ ሳይነሳ መታሰር የለበትም ብለዋል - የአቶ መላኩ ጠበቃ፡፡ መንግስት የሚያውቀው ህመም እንዳለባቸውና የህክምና ክትትል ሲደረግላቸው መቆየቱን አቶ መላኩ ጠቅሰው፤ ህክምናው በማረሚያ ቤት ሳይቋረጥ እንዲቀጥል ጠይቀዋል፡፡ ከቤተሰቦቻቸው፣ ከጠበቃቸው እና ከአማካሪያቸው ጋር ለመገናኘት እንዲፈቀድላቸው ያቀረቡት ጥያቄ፣ የሁሉም ተጠርጣሪዎች ጥያቄ ነው፡፡ ከጠበቃና ከቤተሰብ ጋር የመገናኘት መብታቸውን በሚመለከት ተጠርጣሪዎቹ አቤቱታ ያቀረቡት በመጀመሪያው እለት ነበር፡፡ ፍ/ቤቱም የተጠርጣሪዎችን ጥያቄ በመቀበል፤ የማረሚያ ቤት ኃላፊዎች የተጠርጣሪዎችን መብት እንዲያከብሩ በማሳሰብ ከወዳጅ ቤተሰብ ጋር እንዲገናኙ ማድረግ እንዳለባቸው ትዕዛዝ ሰጥቷል፡ የአካል ጉዳተኛ መሆናቸውን በመጥቀስ ልዩ ድጋፍና እንክብካቤ እንዲደረግላቸው አቶ መርክነህ ያቀረቡት አቤቱታ ላይ ግን ፍርድ ቤቱ የሰጠው ትዕዛዝ የለም፡፡

የአቶ መላኩ ያለመከሰስ መብትን በሚመለከት ደግሞ፣ ተጠርጣሪው የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ለአርብ እንዲያቀርቡ ፍ/ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡ አርብ ዕለት የቀረቡት አቶ መላኩ የምክር ቤቱ አባል መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ካቀረቡ በኋላ ጓደኞቼ እንደሚሆኑት ለመሆን ያለመከሰስ መብቴን ላለመጠቀም ወስኛለሁ ብለዋል - አቶ መላኩ፡፡ የፀረ- ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ቡድን ወደ ፍ/ቤት ባቀረባቸው ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ ለመመስረት ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ያስፈልገኛል በማለት ሲጠይቅ፣ ተጠርጣሪዎች ተቃውሟቸውን አሰምተዋል፡፡ የቤትና የቢሮ ብርበራ አካሂዶ ስለጨረሰና ምርመራ አጠናቅቄአለሁ ብሎ ስለተናገረ ተጨማሪ ቀን ሊፈቀድለት አይገባም ብለዋል - ተጠርጣሪዎች፡፡ መርማሪው ቡድን በበኩሉ፤ ክስ ለመመስረት በቂ ማስረጃ አሰባስቤያለሁ አልኩ እንጂ ምርመራ ጨርሻለሁ አላልኩም በማለት ምላሽ ሰጥቷል።

ፍ/ቤቱ የመርማሪውን ቡድን ጥያቄ በመቀበል፣ ከወንጀሉ አዲስነት፣ ውስብስብነትና ስፋት አንፃር 14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ፈቅጃለሁ ብሏል፡፡ በተመሳሳይ ክስ በሁለተኛው መዝገብ ሰኞ ከሰዓት ፍ/ቤት የቀረቡት የባለስልጣኑ ምክትል ዳሬክተር አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስን ጨምሮ አስራ አንድ ተጠርጣሪዎች ቢሆኑም፣ በፌደራል ፖሊስና ደህንነት ሃይሎች ክትትል በቁጥጥር ስር የዋሉት የባለስልጣኑ የወንጀል ምርመራ ዳሬክተር አቶ ተወልደ ብስራት 12ኛ ተጠርጣሪ ሆነው በማክሰኞ ችሎት ተካተዋል፡፡ በዚህ መዝገብ የተካተቱት ባለስልጣናትና ባለሃብቶች አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስን ጨምሮ አቶ በላቸው በየነ፣ አቶ ነጋ ገ/እግዚያብሄር፣ አቶ ምህረትአብ አሰፋ፣ አቶ ሙሴ ጋሻው፣ አቶ አሞኘ ታገሰ እንዲሁም የአቶ ገ/ዋህድ ባለቤት ኮ/ል ሃይማኖት ተስፋዬ ከነእህታቸው ወ/ሮ ንግስቲ ተስፋዬ ይገኙበታል - ወ/ሮ ንግስቲ ልጅ ሃብታሙ ገ/መድህን ጭምር፡፡ ከአንደኛ እስከ 8ኛ የተጠቀሱት ያልተፈቀደ ሲሚንቶ ወደ ሃገር ውስጥ እንዲገባ አድርገዋል የተባሉት ተጠርጣሪዎች፣ ካሁን ቀደም በኮንትሮባንድ ንግድ የተከሰሱ ሰዎችን ከክስ ነፃ እንዲሆኑ አድርገዋል ተብለዋል፡፡ ቀሪዎቹ ሦስት ታሳሪዎች የአቶ ገ/ዋህድ ባለቤትና ቤተሰብ ናቸው - ሰነድ በማሸሽና በመደበቅ የተጠረጠሩ፡፡

አቶ ገ/ዋህድ ለፍርድ ቤቱ ባቀረቡት የቃል ክርክር ላይ የመንግስት ሚዲያ ዘገባዎች ላይ ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡ የተጠረጠርኩበት ጉዳይ በፍርድ ሂደቱ የሚጣራና እልባት የሚያገኝ ሆኖ ሳለ፣ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በየእለቱ ስሜን የሚያጎድፍ ዘገባ እያቀረበ ነው በማለት ዘገባዎቹ እንዲታገዱላቸው ቢጠይቁም፣ ፍርድ ቤቱ ያስተላለፈው ትዕዛዝ የለም፡፡ ባለቤቴ እና የቤተሰብ አባላት በመታሰራቸው ልጆቼ የት እንዳሉ አላውቅም ያሉት አቶ ገ/ዋህድ፤ ባለቤቴ የፈፀመችው ወንጀል የለም በማለት እንዲለቀቁላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ግን እሳቸው መከራከር የሚችሉት ለራሳቸው ብቻ መሆኑን በመግለፅ ጥያቄያቸውን ሳይቀበል ቀርቷል፡፡ ይሁንና የፀረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ቡድን በኮ/ል ሃይማኖት ክስ ላይ አስተያየት እንዲሰጥበት ፍ/ቤት አዟል፡፡ የመርማሪ ቡድኑ በበኩሉ፤ ኮ/ል ሃይማኖት፣ ወ/ሮ ንግስቲ እና ልጃቸው ለምን እንደታሰሩ ለማስረዳት በሰጠው ምላሽ፣ የአቶ ገ/ዋህድ ሰነዶችን የማሸሽና የመደበቅ ድርጊት ፈጽመዋል ብሏል፡፡ በሙስና የተጠረጠረን ግለሰብ ሰነድ ማሸሽና መደበቅ ራሱ፣ በሙስና ክስ የሚታይ ነው ብሏል - መርማሪው ቡድን፡፡

ሁሉም ተጠርጣሪዎች የዋስትና መብታቸው ተጠብቆላቸው ከእስር እንዲለቀቁና ጉዳያቸውን በውጪ ሆነው እንዲከታተሉ የጠየቁ ቢሆንም፣ ፍርድ ቤት ጥያቄያቸውን ውድቅ በማድረግ ለመርማሪው ቡድን የ14 ቀናት ቀጠሮ ፈቅዷል፡፡ በሶስተኛው መዝገብ የናዝሬት ጉምሩክ ስራ አስኪያጅን ጨምሮ፣ ኮንትሮባንድ የማስገባትና የመተባበር ድርጊት ፈጽመዋል ተብለው የተጠረጠሩ መርማሪዎችና ባለሃብቶች 6 ናቸው፡፡ ስራ አስኪያጁ አቶ መሃመድ ኢሳ፣ ሰይፈ ንጉሴ፣ ዘሪሁን ዘውዴ፣ ማርሸት ተስፋዬ፣ ሙሉቀን ተስፋዬ እና ዳኜ ስንሻው ሰኞ እለት ፍርድ ቤት ከቀረቡ በኋላ፤ ከአማካሪ ጠበቆቻቸው ጋር ተወያይተውና ለቃል ክርክር ተዘጋጅተው እንዲመጡ ተነግሯቸው ነበር፡፡ ይሁንና ከጠበቆቻቸው ጋር እንዲገናኙ ስላልተፈቀደላቸው ማረሚያ ቤቱ በፍ/ቤት ትዕዛዝ መሰረት ተጠርጣሪዎች ከጠበቆቻቸው ጋር እንዲገናኙ መፍቀድ እንዳለበት ተገልፆለት እንደገና ለሐሙስ ግንቦት 9 ቀን የቃል ክርክሩ እንዲካሄድ ተቀጥሯል፡፡

ሁለተኛ መዝገብ የተከሰሱት በእነ አቶ ገ/ዋህድ ጉዳይም ማረሚያ ቤቱ ጠበቆች እንዲገቡ ባለመፍቀዱ፤ ተጠርጣሪዎች ከጠበቆቻቸው ጋር ሳይማከሩ ነበር ፍ/ቤት የቀረቡት፡፡ እዚያው ፍርድ ቤቱ ውስጥ ነው፣ ለ10 ደቂቃ ያህል ተመካክረው የቃል ክርክራቸውን እንዲቀጥሉ የተደረገው፡፡ ጠበቆች ከተጠርጣሪዎች ጋር እንዲገናኙ ፍርድ ቤት ያስተላለፈው ትዕዛዝ ለምን በማረሚያ ቤት ተፈፃሚ እንዳልተደረገ ኮማንደር አበበ ብርሃኔ ወደችሎት ቀርበው እንዲያሰረዱ ታዘዋል፡፡ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባልነት ማረጋገጫ ይዘው በመቅረብ ያለ መከሠስ መብታቸውን እንዲያስረዱ ለትናንት ተቀጥረው የነበሩት አቶ መላኩ ፈንታ፤ ትናንት ከሰዓት በኋላ ለተሰየመው ችሎት ማስረጃውን አቅርበዋል፡፡ የመክሳትና የመገርጣት ምልክት የሚታይባቸው አቶ መላኩ፤ ያለመከሠስ መብታቸውን መጠቀም እንደማይፈልጉ በመግለፅ ጉዳያቸው ከሌሎቹ ተጠርጣሪዎች ጋር እንዲታይ ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል፡፡

“ያለመከሰስ መብቴን ትቼዋለሁ፤ እንደ ጓደኞቼ እሆናለሁ” ብለዋል፡፡ የፀረ ሙስና መርማሪ ቡድን በበኩሉ፤ አቶ መላኩ በ2000 ዓ.ም ምርጫ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል እንዲሆኑ ቢመረጡም ዘንድሮ በሚያዝያ ወር በተካሄደው ምርጫ ስላልተመረጡ ያለመከሰስ መብት የላቸውም ብሎ ተከራክሯል፡፡ ፍ/ቤቱ የመርማሪውን ቡድን መከራከሪያ ባይቀበለውም፤ አቶ መላኩ በራሳቸው ፈቃድ ያለመከሰስ መብታቸውን በመተዋቸው ሂደቱ እንዲቀጥል ወስኗል፡፡ የአቶ መላኩ ጠበቃ ትናንት እንደገና ለፍርድ ቤቱ ባቀረቡት አቤቱታ፤ ደንበኛቸው በማረሚያ ቤት ጨለማ ቤት እንዲቀመጡ ከመደረጉም በላይ ምግብና መድሃኒት በአግባቡ እየቀረበላቸው አይደለም ብለዋል፡፡ ጠበቃው አክለውም፤ አቶ መላኩ ያጋጠማቸው የህመም አይነት ከኢትዮጵያ የህክምና ባለሙያዎች አቅም በላይ እንደሆነ በመንግስት የሚታወቅ በመሆኑ የተሻለ ህክምና የሚያገኙበት መንገድ እንዲመቻችላቸው ጠይቀዋል፡፡

ህክምናውን በቶሎ ካላገኙ ለህይወታቸው አስጊ መሆኑን በመግለጽ ጭምር፡፡ ሌላው በጠበቃው የቀረበው ቅሬታ ደንበኛቸው ከቤተሰቦቻቸው፣ ከልጆቻቸው እና ከባለቤታቸው እንዲሁም ከጠበቃቸው ጋር እንዳይገናኙ ተደርገዋል የሚል ነው፡፡ ተጠርጣሪዎች ከጠበቆች ጋር እንዲገናኙ በፍ/ቤት የተላለፈው ማሳሰቢያ ለምን ተፈፃሚ እንዳልሆነ ማረሚያ ቤቱ እንዲያስረዳ በመታዘዙ ኮማንደር ብርሃኑ አበበ ትናንት ፍ/ቤት ፊት ቀርበዋል፡፡ “ጠበቃው ደንበኛቸው በጨለማ ክፍል ተቀምጠዋል ያሉትን እቃወማለሁ በማረሚያ ቤቱ ጭለማ የሚባል ክፍል የለም” ያሉት ኮንደር ብርሃኑ፣ ጤናን በተመለከተ ማረሚያ ቤቱ ውስጥ ተጠርጣሪዎችን የሚያክም ክሊኒክ አለ፡፡ ከዚያ ካለፈም ስርአቱ በሚፈቅደው መሠረት ሌላ ቦታ ሊታከሙ ይችላሉ፡፡ እንደተባለው ሣይሆን መድሃኒት ተገዝቶላቸዉ ተጠቅመዋል” ብለዋል፡፡ “ከቤተሠብ ጥየቃ እንዲሁም ከጠበቆችና ደንበኞች ግንኙነት ጋር በተያያዘ ችግር ተፈጥሮብኛል ብሎ የጠየቀ የለም፣ እኛም አሠራሩ በሚፈቅደው መሠረት፤ ህገ መንግስቱ በሠጣቸው መብት ተጠቅመው እንዲገናኙ እንፈልጋለን” ብለዋል ኮማንደር ብርሃኑ፡፡ ተፈጠሩ የተባሉትን ችግሮች ለመቅረፍ እንደሚጥሩ ኮማንደር ብርሃኑ ለፍርድ ቤቱ ቃል ገብተዋል፡፡

አቶ መላኩ ፈንታ በበኩላቸው፤ ስርአቱ ትክክል ሆኖ ሣለ፣ የአፈፃፀም ችግር በማረሚያ ቤቱ እንዳጋጠማቸው ገልፀው፤ “የህክምና ጉዳይ ጠይቄያለሁ፡፡ መድሃኒቱ ውጪ ይገዛ ቢባልም በተባለው ቀን አይደለም የደረሠልኝ፡፡ የታሠርኩት ጭለማ ቤት ሳይሆን አንድ ክፍል ውስጥ ለብቻዬ ነው፡፡ ፀሃይና አየር አላገኝም፤ ለሽንት ብቻ እንድወጣ ይፈቀድልኛ” ብለዋል፡፡ ማረሚያ ቤቱ የቀረቡበትን ቅሬታዎች እንዲያስተካክል ትዕዛዝ ከተሰጠ በኋላ፤ ለግንቦት 19 ቀን ቀጠሮ እንደተያዘ ፍ/ቤቱ ገልጿል፡፡ በተመሣሣይ ከጠበቆቻቸዉ ጋር ተመካክረው እንዲቀርቡና የቃል ክርክራቸውን ትናንት እንዲያከናውኑ ተቀጥረው የነበሩት በእነ አቶ መሃመድ ኢሣ መዝገብ የተከሠሡት 6 ግለሠቦች፤ በማረሚያ ቤቱ ባለመቅረባቸው አቃቤ ህግ ሠኞ ግንቦት 12 ቀን 4ኛ መዝገብ ከሚከፈትባቸው ከእነ ዳዊት ኢትዮጵያ ጋር እንዲቀርቡ ፍ/ቤቱ ትዕዛዝ ሠጥቷል፡፡ ኮሚሽኑ በተጠርጣሪነት 7 ተጨማሪ ግለሠቦችን በቁጥጥር ስር ያዋለ ሲሆን፣ እነሡም አቶ ዳዊት ኢትዮጵያ፣ ፍፁም ገ/መድህን፣ ማሞ ኪሮስ፣ አለልኝ ተስፋዬ፣ አሸብር ተሠማ፣ ማሞ አብዲ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ኮሚሽኑ በተጠርጣሪነት የያዛቸው ግለሠቦች ቁጥርም ከ25 ወደ 32 በማደጉ 4ኛ የምርመራ መዝገብ ይከፈታል ተብሏል፡፡

በሶሪያ መላ የታጣለትን የእርስበርስ ጦርነት በመሸሽ ወደ ዮርዳኖስ የተሰደዱ እናቶች፣ ህይወት ፈተና ሆኖባቸው ሴት ልጆቻቸውን “ለጊዜያዊ ትዳር” እየሸጡ ነው፡፡ ስደተኛ ወላጆች በሴት ልጆቻቸው ላይ መጨከን እንደጀመሩ የዘገበው ሲኤስ፣ ኑሮን ለመግፋት የሚያስችላቸው ብቸኛ አማራጭ ሆኖ ያገኙት ሴት ልጆቻቸውን በሺዎች በሚቆጠሩ ዶላሮች ለጋብቻ መሸጥ ነው፡፡ ከዮርዳኖስም ሆነ በሌሎች የመካከለኛው ምስራቅ አገራት ጋብቻ ፈላጊ ወንዶች ለሴቷ ቤተሰቦች ገንዘብ የሚሰጡበት ባህል አለ፡፡ ይሄም ሆኖ ግን የሰሞኑ የዮርዳኖስ ስደተኛ ካምፖች “የጋብቻ ገበያ”፣ እርግጥም ወንዶች ሴቶችን ለዘላቂ ትዳር የሚገዙበት አይደለም፡፡ አብዛኛዎቹ “ትዳሮች” ከሳምንታት የዘለቀ ዕድሜ እንደማይኖራቸው የገለፀው ዘገባው፤ ይልቁንም “የወሲብ ገበያ” ሊባል የሚችል መሆኑን አስረድቷል፡፡

ይህንን የሴት ልጆች ሽያጭ ከሚያቀላጥፉትና ራሳቸውን “የጋብቻ ደላላ” ብለው ከሚጠሩት መካከል ሶሪያዊቷ ስደተኛ ኡም ማጄጅ አንዷ ናት፡፡ ኡም ማጄድ ከሰሞኑ እየጦፈ በመጣው የስደተኛ ልጃገረዶች ሽያጭ ገበያ ፋታ አጥታለች፡፡ የሞባይል ስልኳ በገዢዎች ጥሪ ተጨናንቋል፡፡ ኡም ማጄድ ከወላጆች ጋር በመነጋገር ለሽያጭ ከምታቀርባቸው ሴቶች ጠቀም ያለ ኮሚሽን ታገኛለች፡፡ ክብረ ንጽህናዋ ያልተገረሰሰ ልጃገረድ በሰሞኑ ገበያ እስከ 5ሺህ ዶላር ታወጣለች፡፡ አያ የተባለችዋ የ17 አመቷ ሶሪያዊት ስደተኛ አያ፤ ከቤተሰቦቿ ጋር በስደት ወደ ዮርዳኖስ ከመጣች አንድ አመት ያህል ሆኗታል፡፡

ይሄም ሆኖ ግን የስደት ኑሮ ለእሷም ሆነ ለቤተሰቧ አሳር ሲሆንባቸው፣ ብቸኛውን አማራጭ ለመውሰድ ተገደዱ፡፡ አያ ለ70 አመት ሳኡዲ አረቢያዊ “ትዳር ፈላጊ” ሽማግሌ በ3ሺህ 500 ዶላር ተሸጠች፡፡ ትዳር ፈላጊው ሽማግሌ ግን ከሙሽሪት አያ ጋር የመሰረተውን ትዳር ለማፍረስ የፈጀበት የአንድ ወር ጊዜ ብቻ ነበር፡፡ “ከእሱ ጋር ያሳለፍኩት አንድ አመት ልክ እንደ አስፈሪ ቅዠት ነበር፡፡ ግማሹን ወር በመራር ለቅሶ ነው ያሳለፍኩት፡፡ ከቤተሰቦቼ ጋር እንድገናኝና እንዳወራ አይፈቅድልኝም ነበር፡፡ ምርጫ አልነበረኝምና በሰቀቀን ነበር የምኖረው” ብላለች - አያ ስለ ሽያጩ ትዳሯ ስትናገር፡፡

እንዲህ ለጋ ልጃገረዶችን ለገበያ አቅርባ የምታሻሽጠው ኡም ማጄድ እየሰራችው ስላለችው ነገር ሃፍረትም ሆነ ፀፀት አይሰማትም፡፡ “መኖር የምችልበት ብቸኛው መንገድ ይህ “ስራ” ነው፡፡ ሶሪያውያን ስደተኞች በዮርዳኖስ ሌላ ስራ መስራትና ገቢ ማግኘት አንችልም፡፡ ስለዚህ ምን ማድረግ እንችላለን?...እንስረቅ?...እንግደል?” ትላለች ማጄድ፡፡ የሚገርመው ግን “አንቺስ የ13 አመት ልጃገረድ ልጅሽን ለመሸጥ ትፈቅጃለሽ?” ለሚለው የጋዜጠኞች ጥያቄ የሰጠችው መልስ ነው፡፡ “በፍፁም አላደርገውም!... ልጆቼን ከምሸጥ አይኖቼን አውጥቼ ብሸጣቸው እመርጣለሁ!” ነው ያለችው ማጄድ፡፡

Saturday, 18 May 2013 10:04

የ5 ሚሊዮን ብር መኪና

የዛሬ አርባ አመት ገደማ፣ ይህን ማዕረግ ለማግኘት የመኪናዋ አቅም 300 የፈረስ ጉልበት መሆን ነበረበት። ፍጥነቷም ቢያንስ ከ160 ኪሎሜትር በላይ። ዛሬ ይሄ ተቀይሯል። ሱፐርካር ለመባል ከ600 በላይ የፈረስ ጉልበት፣ እንዲሁም በሰዓት ከ350 ኪሎሜትር በላይ የመብረር አቅም ያስፈልጋል። ይህን መመዘኛ አሟልተው በአመቱ ከተመረቱት ልዩ መኪኖች መካከል፣ በማክማረን ኦቶሞቲቭ የተሰራው ስፓይደር የተሰኘው መኪና የ“ራብ ሪፖርት” ምርጫ ሆኗል።

ከመቼው የመኪናው ሞተር ተነስቶ፣ ከመቼው መብረር እንደሚጀምር ሲታይ ያስደንቃል። በሶስት ሴኮንድ ውስጥ፣ ፍጥነቱ ከ“95” በላይ ይሆናል። በሌላ አነጋገር፣ ቆሞ የነበረው መኪና… ገና 1፣ 2፣ 3 ብለን ቆጥረን ሳንጨርስ፣ ከ400 ሜትር በላይ ርቀት ተጉዟል። ከዚያማ ማርሽ እየቀየሩ ፍጥነት መጨመር ብቻ ነው - በሰባት ማርሽ። በአንድ ሊትር 10 ኪሎሜትር ይጓዛል። ታዲያ ዋጋው ቀላል አይደለም። 266ሺ ዶላር ነው (5 ሚሊዮን ብር ገደማ መሆኑ ነው)።

በመፅሄቱ ሪፖርት ላይ እንደዘረዘረው፣ የማክማረን ስሪት የሆነው “ስፓይደር”፣ እንደፌራሪና ላምቡርገኒ ከመሳሰሉ በጉልበትና በፍጥነት ከሚታወቁ የቅንጦት መኪኖች በምንም አያንስም። ለነገሩ ማክማረን የሚያመርታቸው የስፖርት ውድድር መኪኖችም፣ በአለም የሚታወቁ ናቸው። የተለያዩ ውድድሮችን በማሸነፍ፣ ከፌራሪ ቀጥሎ የሚጠቀሰው ማክማረን ነው ይላል ሪፖርቱ። በእርግጥ የስፖርት መኪኖቹ ዋጋ ከፍ ይላል። በ2013 መጨረሻ አካባቢ ከ“ስፓይደር” ጎን ለገበያ የሚቀርበው “ፒ1” የተሰኘ አዲስ የማክማረን የስፖርት መኪና፣ ዋጋው 1.1 ሚሊዮን ዶላር ነው - ሃያ ሚሊዮን ብር! ጉልበቱና ፍጥነቱ ግን እንደ ዋጋው ነው። በ960 የፈረስ ጉልበት፣ በሰዓት 400 ኪሎሜትሩን ፉት ብሎ መጨረስ ይችላል።

ወርዷ ክንፎቿንም ጨምሮ፣ ከአንድ ጣት ውፍረት ብዙም አይበልጥም። “ንብ የምታክል ሮቦት” ለማለትም ይመስላል፤ ስሟን RoboBee ብለው የሰየሟት። በእርግጥ ባለፉት አስር አመታት በተካሄዱ ጥናቶችና ምርምሮች ጥቃቅን በራሪ ማሽኖች (ሮቦቶች) ተፈጥረዋል። ሁለት ሶስት ግራም የሚመዝኑ ብቻ ሳይሆኑ፤ ከአንድ ግራም በታች ክብደት ያላቸው እንደ ነፍሳት ማንዣበብ ወይም መብረር የሚችሉ ሮቦቶች ተሰርተዋል። በሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ አራት የጥናት አመታትን የጠየቀው RoboBee (ሮቦንብ) ግን፣ ከእስካሁኖቹ ጥቃቅን በራሪዎች ሁሉ እጅጉን ያነሰ ነው። 12 በራሪዎች ቢመዘኑ፣ በድምር አንድ ግራም አይሞሉም።

የተመራማሪዎቹ ጥረት ተሳክቶ ሰሞኑን፣ እንደ ንብ ክንፉን የሚያርገበግብ በራሪ ሮቦት በይፋ አስመርቀዋል። ደግሞም፣ እንደ ንብ መንጋ፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ “ንብ የመሰሉ ሮቦቶችን” ማምረት ቀላል እንደሆነ ተመራማሪዎቹ ገልፀዋል። “ድንቅ ፈጠራ” ተብሎ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ተቋማት የተደነቀው “ሮቦንብ”፣ በብዙዎች ዘንድ ስጋት ማሳደሩ አልቀረም። ትናንሽና ጥቃቅን በራሪ አካላት አሁን አሁን ቁጥራቸው እየተበራከተ መጥቷል። መንግስታት ለወታደራዊ ስለላና ለፖሊስ ቅኝት በራሪ “ሮቦቶችን” መጠቀም ጀምረዋል። ዜጎችን ለመሰለልና የአፈና ቁጥጥር የማካሄድ ጥማት ያለባቸው መንግስታት፤ በየከተማው በሚሊዮን የሚቆጠሩ ትናንሽና ጥቃቅን በራሪ ሮቦቶችን ቀን ከሌት እንዳያዘምቱ ምን ያግዳቸዋል? አሳሳቢው ነገር ይሄ ነው።

“ እኔ ወደጋንዲ ሆስፒታል የመጣሁት ሁለት ሴት ልጆች የመደፈር ጥቃት ስለደረሰባቸው ነው፡፡ ልጆቹ የጎረቤት እና የራሴ ሲሆኑ የጎረቤ ልጅ የዘጠኝ አመት ስትሆን የእራሴ ግን የሰባት አመት ናት፡፡ ልጆቹ ለእኛ እንደነገሩን ከሆነ የመደፈር ጥቃት የተፈጸመባቸው አንድ ጊቢ አብሮን በሚኖር ሰው ነው፡፡ በእርግጥ ገና በህግ እስኪረጋገጥ እንዲህ ነው ማለት ባይቻልም የልጆቹ አንደበት የመሰከረው ይህንኑ ነው፡፡ አሁን በሕክምናው ታይተዋል፡፡ ቀጥሎ ደግሞ በፖሊስ መዝገብ ላይ ሁኔታው ሰፍሮ ወደ ፍትሕ እንሄዳለን፡፡ ጉዳዩ እጅግ በጣም ፈታኝ ነው፡፡ እኛም ተከራዮች ነን...እሱም ተከራይቶ የሚኖር ነው፡፡ ወደፊት እንዴት እንደምናደርግ አላውቅም” አሳካሚ እናት... የሴቶችና ሕጻናት የተቀናጀ የፍትህና የእንክብካቤ ማአከል በጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል ከተቋቋመ ሚያዝያ 2005 ዓ/ም ልክ አንድ አመት ሆኖታል፡፡

ማእከሉ በዩኒሴፍ የገንዘብ እርዳታ እና በፍትህ ሚኒስር የበላይነት የተቋቋመው የዛሬ አመት ሚያዝያ 22/2004 ዓ/ም ነበር እንደ ዶ/ር ደረጀ አለማየሁ የጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር መረጃ ፡፡ይህ ማእከል ከመቋቋሙ በፊት በአገር አቀፍ ደረጃ የሚመለከታቸው መስሪያ ቤቶች ተወካዮች ያሉበት አንድ ኮሚ ተቋቁሞ ልምድ ለመቅሰም ወደ ደቡብ አፍሪካ እንዲሄድ ተደርጎ የነበረ ሲሆን በዚያ መሰረት ማእከሉ ተቋቁሞ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነው፡፡ የሴቶችና ሕጻናት የፍትህና የእንክብካቤ ማእከል አገልግሎት የሚሰጠው ከፈቃዳቸው ውጭ በሆነ መንገድ የግዳጅ ወሲብ ለተፈጸመባቸው ሴቶች ሲሆን በዚህ አንድ አመት ውስጥ ወደ 1100/አንድ ሺህ አንድ መቶ የሚሆኑ ባለጉዳዮች ተስተናግደዋል፡፡ በእድሜም ከአንድ አመት ከአራት ወር ሕጻን እስከ 80/ሰማንያ አመት የእድሜ ባለጸጋ የሚሆኑ ሴቶች የአስገዳጅ ወሲብ ተፈጽሞባቸዋል፡፡

የዚህን ማእከል የስራ እንቅስቃሴ ለመመልከት በጋንዲ ሆስፒታል በተገኘንበት ወቅት የሁለት አመት ከስድስት ወር ሴት ሕጻን በዚሁ ጉዳይ በሐኪም እየታየች ነበር፡፡ አስተባባሪ ነርስ የሆነችው ሲስተር ሙሉነሽ ወልደመስቀል በማእከሉ ከአስተባባሪነት በተጨማሪ ከስነአእምሮ ጋር በተገናኘ ችግር ያለባቸውን እንዲሁም ከመደፈር ጋር ተያይዞ ጭንቀት የደረሰባቸውን ማረጋጋት እንዲሁም ሕክምና መስጠት የመሳሰለውን ሁሉ ትሰራለች፡፡ ሲስተር ሙሉነሽ እንደገለጸችው ሴቶች በቤታቸው፣ በስራ ቦታ እንዲሁም በተለያየ አጋጣሚ ሊደፈሩ ስለሚችሉ አገልግሎቱ የሚሰጠው የእድሜ ገደብ ሳይኖረው ለሁሉም ሴቶች ነው፡፡ የመደፈር ጥቃት በሴቶች ብቻ ሳይሆን በወንዶች ላይም እንደሚከሰት የታወቅ ሲሆን ማእከሉም እንደ ተከፈተ ብዙ ወንዶች የሐኪም መረጃ ለማግኘት ወደማእከሉ ቢመጡም ሊሟሉ የሚገባቸው ብዙ የህክምና አሰራሮች ስላሉ በአሁኑ ወቅት ግን የወንዶቹ ተቋርጦአል። ስለዚህ ወንዶቹ የሚሄዱት ወደሌሎች ሆስፒታሎች ሲሆን ጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል የሴቶች እንደመሆኑ መጠን ሴቶቹ ሙሉ ለሙሉ ሕክምናው ይሰጣቸዋል ብለዋል፡፡

በማእከሉ የሚሰጠውን አገልግሎት ተዘዋውረን እንደተመለከትነው ከሆነ ሕጻናቱ የሚጫወቱባቸው ቁሳቁሶች እንዲሁም ቤተሰብ የሌላቸው ለተወሰኑ ቀናት የሚያርፉበት መኝታ ክፍል እና በተሟላ የምግብ አቅርቦት እንደሚስተናገዱ ለመመልከት ተችሎአል፡፡ ሲ/ር ሙሉነሽ ወልደመስቀል እንደተናገሩት ከሆነ ሕጻናቱን እና የተጎዱትን በማስተናገዱ ረገድ በክፍሉ ውስጥ ያሉት ነርሶች በሙሉ ፈቃደኝነት አገልግሎቱን እንደሚሰጡ ለመረዳት ተችሎአል፡፡ ዶ/ር ስንታየሁ ታከለ የማእከሉ አስተባባሪ ናቸው፡፡ ዶር ስንታየሁ እንደገለጹት ተጠቂዎቹ ሕጻናት ከሆኑ በቤተሰባቸው አማካኝነት አዋቂዎቹ ደግሞ እራሳቸው ወደማእከሉ ይቀርባሉ። ማንኛዋም ሴት ተደፍሬአለሁ ስትል ቃሉዋ ታማኝነት አለው። ስለዚህ ተጠቂዋ ካርድ በማውጣት የህክምናውን አገልግሎት ለላቦራቶሪ ፣ለመድሀኒት፣ ተኝቶ ለመታከም ...ወዘተ ሁሉንም ሙሉ በሙሉ በነጻ ታገኛለች፡፡ በተለይም ሴትዋ ጥቃቱ በተፈጸመ በቅርብ ቀን ድረስ ባለው ጊዜ ...ማለትም ፡- ጥቃቱ ከተፈጸመባት እስከ ሶስት ቀን ድረስ ባለው ጊዜ ወደማእከሉ ከመጣች ከኤችአይቪ ቫይረስ ለመከላከል የሚያስችለውን መድሀኒት እንድታገኝ ይደረጋል፡፡ ጥቃቱ በተፈጸመ እስከ አምስት ቀን ድረስ ወደ ሕክምናው ማአከል ከመጣች ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል የሚያስችል መድሀኒት ይሰጣታል፡፡ ጥቃቱ ከተፈጸመባት እስከ ሁለት ሳምንት ድረስ ባለው ጊዜ ከመጣች የአባላዘር በሽታ እንዳይይዛት የሚከላከል መድሀኒት ይሰጣታል፡፡

ዶ/ር ስንታየሁ እንደችግር የገለጹት ተጠቂዎቹ ሁሉም በቅርብ ቀን ውስጥ ወደህክምና ማእከሉ አለመምጣታቸውን ነው፡፡ ማእከሉ ከተከፈተ ጀምሮ እንደታየው ልምድ ከሆነ ሴቶች የሚመጡት ጥቃቱ በተፈጸመ ከሶስት እስከ ስድስት ወር እና ከዚያም ካለፈ በሁዋላ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ወደማእከሉ የሚደርሱት ያልተፈለገ እርግዝና ከተከሰተባቸው በሁዋላ ሲሆን በአገሪቱ የውርጃ ሕግ መሰረት ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚደረግ ቢሆንም በከፊል ይህንን እርዳታ ሊያገኙ የማይችሉ ይሆናሉ። ለምሳሌም እርግዝናው ከ28/ሀያ ስምንት ሳምንት በላይ ከሆነው ተንከባክበናት እንድትወልደው ከማድረግ ውጭ ሌላ እርዳታ ማድረግ አይቻልም፡፡ከዚያም ውጭ ሌሎች በሽታዎችን ለመከላከል ሲባል ሊያገኙ የሚገባቸውን እርዳታ እንዳያገኙ ይሆናሉ እንደዶክተር ስንታየሁ ማብራሪያ፡፡ ዶ/ር ስንታየሁ አክለውም ይህ ማእከል ከሚሰራቸው ስራዎች መካከል የህክምና ማስረጃ መስጠት ይገኝበታል፡፡ ይህ የህክምና ማስረጃ እንደቀድሞው በእንግሊዝኛ ሳይሆን በአማርኛ የሚጻፍ ነው፡፡ እንደቀድሞው በእንግሊዝኛ ተዘጋጅቶ ወደትርጉም ቤት የሚያስኬድ እና የሚያስቸግር ሳይሆን በወቅቱ በሴትዋ አካል ላይ የተገኘውን መረጃ መሰረት በማድረግ ወደፖሊስ የሚላበት ነው ፡፡

በእርግጥ ይህ ወንጀል ነው አይደለም የሚለውን የሚወስነው የፍትህ አካሉ እንጂ ሕክምናው አይደለም፡፡ በዚህ አጋጣሚ የምናገረው አሉ ዶ/ር ስንታየሁ ...ማንኛዋም ጥቃቱ የደረሰባት ሴት ችግሩ በደረሰ ውስን ቀናት ውስጥ ወደማእከሉ መቅረብ ብትችል መረጃውን በተሟላ ሁኔታ ማቅረብ ይቻላል፡፡ ነገር ግን ብዙዎቹ የቆሰለው አካላቸው ድኖ ገላቸውን ፣ልብሳቸውን ታጥበው እና ከቀናትም ባለፈ ወራት ፈጅተው ስለሚመጡ ምንም መረጃ የማይገኝበት አጋጣሚ ብዙ ነው ብለዋል ዶ/ር ስንታየሁ ታከለ የማእከሉ አስተባባሪ፡፡ በማእከሉ ያገኘናት የፖሊስ ባልደረባ ም/ሳይጅን ጽጌ ደግፌ ትባላለች፡፡ ም/ሳጅን ጽጌ ቢሮ ውስጥ አንድ ጥሩ አሻንጉሊት ፊት ለፊት ተቀምጦአል፡፡ እሱዋም እንደገለጸችው ይህ አሻንጉ ሊት ሴቶቹ በተለይም ህጻናቱ የደረሰባቸውን ችግር ለማስረዳት እፍረት ቢሰማቸውና ድብቅ ቢሆኑ እንዲናገሩ ለማጫወቻነት የተቀመጠ ነው፡፡

እንደ ምክትል ሳይጅን ጽጌ መግለጫ ቀደም ሲል በፖሊስ ጣቢያ ይህ ስራ በሚሰራበት ጊዜ መረጃው በፍጥነት ስለማይደርስና ባለጉዳ ዮቹም ከቦታ ቦታ በመዘዋወር እንግልት ስለሚደርስባቸው ጉዳዩ ፍትህ ሳያገኝ መዝገብ የሚዘጋበት እና ተከሳሾች ነጻ የሚወጡበት አጋጣሚ ይስተዋል ነበር፡፡ አሁን ግን ከአንድ አመት ወዲህ ይህ የፖሊስ ስራ ከህክምናው ጋር ተጣምሮ በአንድ ማእከል ውስጥ ሐኪም፣ አቃቤ ሕግ እና ፖሊስ በመሆን መስራት በመቻሉ ውጤቱን በፍጥነት በመቀባበል ተጎጂዎቹም ሳይንገላቱ መረጃው ለፍትህ አካላቱ እንዲደርስ አስችሎአል፡፡ ም/ሳይጅን ጽጌ የተጠቂዎችን የእለት ሁኔታ ስትገልጽ ከአስሩም ክፍለ ከተማ አንዳንድ ጊዜ ምንም ተጎጂ ላይመጣ ሲችል አንዳንዴ ደግሞ በቀን እስከ አስር እና ከዚያም በላይ ሴቶች ተጎጅዎች ወደ ማከሉ ሊመጡ ይችላሉ፡፡ በእድሜ ደረጃም በአብዛኛው ሕጻናት በተለይም እስከ አስራ አምስት አመት ድረስ ያሉት ተጎጂዎች ናቸው፡፡ በጋንዲ ሆስፒታል በተቀቋቋመው ማእከል ውስጥ አገልግሎት የሚያገኙ ተጎጂዎች ሕክምናውን ካገኙና የደረሰውን ችግር ካስረዱ በሁዋላ ወደመጡበት ክፍለ ከተማ በመሄድ የፖሊስ ሪፖርቱን እንዲያገኙ ይደረጋል፡፡ ጉዳት ያደረሱት ሰዎች ተገቢውን የፍትህ እርምጃ እንዲያገኙና ተጎጂዎቹም በዚህ ፍትሕ እንዲረኩ ለማድረግ ዋናው የህክምናው ማስረጃ ሲሆን ለዚህም ተጎጂዎች በጊዜ ወደህክምና ማእከሉ በመቅረብ ተገቢውን ክትትል ቢያደርጉ ለአሰራር ይበልጥ አመቺ መሆኑን እንመሰክራለን፡፡

የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ከፍትሕ አካሉና ከህክምና ማእከሉ ጋር በመጣመር ይህንን ስራ ከጀመረ ወዲህ በሴቶችና በቤተሰብ ላይ የነበረው መንገላታት በእጅጉ መቀነሱን መመስከር ይቻላል ብላለች ም/ሳጅን ጽጌ ደግፌ፡፡ የሜዲካል ዳይሬክተሩ ዶ/ር ደረጀ አለማየሁ እንደሚሉት ፖሊስ፣ አቃቤ ህግና የህክምናው ዘርፍ በጋራ የሚሰሩበት ይህ የሴቶችና ሕጻናት የተቀናጀ የፍትህና የእንክብካቤ ማእከል በሀገራችን የመጀመሪያው ሞዴል ማእከል ነው፡፡ የጋንዲ ሆስፒታል የተመረጠበትም ምክንያት የሴቶች ሆስፒታል ስለሆነ እና አገልግሎቱን ከዚያ በፊትም ስለሚሰጥ ነው፡፡ በፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስርና በጤና ቢሮ አማካኝነት ጥያቄው ሲቀርብ የህብረተሰቡ ትልቅ ችግር እና ሴት ሕጻ ናቱ የሚጎዱበት እንደመሆኑ ጋንዲ ሆስፒታልም የራሱን ግልጋሎት ሊሰጥ ይገባል በሚል ከስም ምነት ተደርሶ እነሆ ስራው ከተጀመረ አንድ አመትን አስቆጥሮአል፡፡

በአሁኑ ወቅት በአገራ ችን ከፍላጎታቸው ውጭ የወሲብ ጥቃት ለደረሰባቸው ሴቶች የህክምና ማስረጃን ለፍትህ አካል የማ ቅረብ ስራን የሚሰራው ይህ በጋንዲ ሆስፒታል የሚገኘው የሴቶችና ሕጻናት የተቀናጀ የፍት ህና የእንክብካቤ ማእከል ብቻ ነው፡፡ ወንዶቹን በሚመለከት ግን የህክምናውን ማስረጃ በትክክል ከሚመለከተው ሐኪም የማግኘትን አሰራር በመከተል ወደ ጥቁር አንበሳ እና ዘውዲቱ ሆስፒታል እንዲሄዱ ይደረጋል ብለዋል ዶ/ር ደረጀ አለማየሁ የጋንዲ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር፡፡

በአዲስ ተስፋ የተዘጋጀ “የፊልም ድርሰት አፃፃፍ ብልሃት” የተሰኘ አዲስ መጽሐፍ ሰሞን ለንባብ በቅቷል፡፡ ረዳት ፕሮፌሰር ሙሉጌታ ጀዋሬ በመጽሐፉ ጀርባ ላይ በሰጡት አስተያየት፤ “የአገራችን የፊልም ኢንዱስትሪ በእውቀት የሚጽፉ ሙያተኞች እጅጉን ያስፈልጉታል፡፡

አሁን አሁን በፊልም ጥበብ ላይ የተዘጋጁ መፃሕፍት ታትመው ለንባብ እየበቁ ነው… የፈጠራ ጽሑፍ ተሰጥኦ እያላቸው አቅጣጫው (ቴክኒኩ) ለጠፋቸው ሁሉ እነሆ አቅጣጫው እላለሁ” ብለዋል፡፡ መጽሐፉ ከያዛቸው አብይ ርዕሰ ጉዳዮች መካከል “የድራማ ምንነትና ታሪክ”፣ “ፊልም ምንድነው?” “ፊልም እንዴት ይፃፋል” እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡ በ171 ገፆች የተቀነበበው መጽሐፉ በ55 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

ጥበብ ኢትዮጵያ የጥበባት ማዕከል አምስተኛውን “ኢትዮጵያ ታንብብ” የንባብ ፌስቲቫል ከትላንት በስቲያ የጀመረ ሲሆን ፌስቲቫሉ ለአምስት ቀናት በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚቀጥል ታውቋል፡፡ በተለያዩ የንባብ ፕሮግራሞች በሚካሄደው በዚህ ፌስቲቫል፤ በአንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች ታላላቅ ደራሲያን የንባብ ልምዳቸውን የሚያካፍሉበት መድረክ የተዘጋጀ ሲሆን ስለአገራችን የንባብ ባህል ጥናታዊ ጽሑፍ እንደሚቀርብም ተገልጿል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ መጽሐፍ አሳታሚዎች፣ አታሚዎች፣ አከፋፋዮች፣ ቤተመፃሕፍትና ማተሚያ ቤቶች የሚሳተፉበት ለአምስት ቀን የሚቆይ የመጽሐፍ አውደርዕይ እና ባዛር እንደተዘጋጀም ለማወቅ ተችሏል፡፡