Administrator

Administrator

ታይላንድ የገዢ ፓርቲ ባለስልጣናትና ተቃዋሚዎች ሐሙስ እለት ታስረዋል

ገዢውን ፓርቲ የሚደግፉና የሚቃወሙ ቡድኖች በሚያካሂዱት አመፅ ስትታመስ የከረመችው ታይላንድ፤ በዚህ ሳምንት ለወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ተዳርጋለች። “የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ” ተግባራዊ ለማድረግ መወሰኑን ማክሰኞ እለት የገለፀው የአገሪቱ የጦር ሃይል፣ ውሳኔው የመንግስት ግልበጣ አይደለም በማለት ደጋግሞ ተናግሯል። “የጦር ሃይል፣ የመንግስት ግልበጣ ሳያካሂድ በአገሪቱ ላይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የመጫን ስልጣን አለው” ሲልም ከመቶ አመት በላይ ያስቆጠረና የተረሳ ጥንታዊ የሕግ አንቀፅ በመጥቀስ ለማስረዳትና ለማስተባበል ሞክሯል። ማስተባበያው ግን ከሁለት ቀን በላይ አልዘለለም። ሐሙስ እለት፤ ወደለየለት መፈንቅለ መንግስት ተሸጋግሯል።
ስልጣን የተቆጣጠረው የጦር ሃይል፤ የተቃውሞ ሰልፎችን በማገድ ወታደሮችን ለቁጥጥር ካሰማራ በኋላ የዋና ከተማዋ ጎዳናዎች ፀጥ ረጭ ብለዋል። ከተቀናቃኝ ፓርቲዎች ጋር ጎራ ለይተው ቀውሱን ያባብሳሉ የተባሉ 14 የቴሌቪዥን ቻናሎችና 3000 የሬዲዮ ቻናሎችም ለጊዜው ታግዳችኋል ተብለዋል።
ከዚሁ ጎን ለጎን፤ ተቀናቃኝ ፓርቲዎች እንዲሁም ከፓርቲዎቹ ጋር ጎራ ለይተው የተሰለፉ ተቀናቃኝ ቡድኖች ለውይይት እንዲሰበሰቡ ወታደራዊው ሃይል ማክሰኞ እለት በቴሌቪዥን ማሳሰቢያ አሰራጭቷል። ለአመታት ሲወዛገቡ የቆዩትና በተለይም ባለፉት ስድስት ወራት በየአደባባዩ ሲጋጩ የከረሙት ተቀናቃኝ ፓርቲዎችና ቡድኖች፤ አንድም ጊዜ ተቀራርበው ለመነጋገር ፈቃደኛ አልነበሩም።
ወታደራዊው ሃይል ማሳሰቢያ ባሰራጨ ማግስት ግን፣ ለውይይት ፈቃደኛ ሆነው ተሰብስበዋል። ሁለት ሰዓት ተኩል በፈጀው ውይይት አንዳች የመፍትሄ ሃሳብ ላይ ባይደርሱም ጥሩ ጅምር ነው ብሏል የወታደራዊው ሃይል ቃል አቀባይ። ፓርቲዎቹ እንደገና ሃሙስ እለት ለመገናኘት ተቀጣጥረው ነበር - በስልጣን ክፍፍልና በምርጫ ዝግጅት ላይ ለመወያየት።
የሃሙሱ ስብሰባ የተካሄደው በጦር ሃይሎች ክለብ ውስጥ ነው። ምርጫ እስኪካሄድ ድረስ በጊዜያዊነት ስልጣን የያዘው ገዢ ፓርቲና ተቃዋሚ ፓርቲ፤ እንዲሁም ጎራ ለይተው ከሁለቱ ፓርቲዎች ጋር የተሰለፉ ተቀናቃኝ ቡድኖች ለስብሰባው መጥተዋል። ሚኒስትሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች፣ የፖለቲካ ቡድኖ ተወካዮች፤ ማክሰኞ እለት እንዳደረጉት ሃሙስ እለትም ወደ ሁለት ሰዓት ገደማ ተነጋግረዋል። ግን፤ ሊስማሙ አልቻሉም። ገዢው ፓርቲ ስልጣን ለመልቀቅ ፈቃደኛ አይደለም። ተቃዋሚው ፓርቲ ስልጣን ካልተሰጠኝ ሞቼ እገኛለሁ ይላል።  ይሄኔ ነው፤ የጦር ሃይሎች ዋና አዛዥ ጄነራል ፕራዩዝ ቻንኦቻ፤ ትእግስታቸው እንዳለቀ የገለፁት። ተሰብሳቢዎቹም ሆኑ ውይይቱን ለመዘገብ የመጡ ጋዜጠኞች ምን እየተፈጠረ እንደሆነ አላወቁም። “የናንተ ንግግር ማለቂያ የለውም” ሲሉ የተናገሩት ጄ/ል ፕራዩዝ፤ “ከአሁን ጀምሮ፣ ስልጣን በኔ እጅ ውስጥ ገብቷል” በማለት ነገሩን በአጭሩ ቋጩት። ለውይይት የተሰባሰቡት ሚኒስትሮች፣ ተቃዋሚዎች፣ የፖለቲካ ቡድን መሪዎች በዚሁ የሚሰነባበቱ መስሏቸው ነበር። ነገር ግን እዚያው እንደተሰበሰቡ ወደ ምድር ጦር ካምፕ ተወስደው እንዲታሰሩ ነው ጄነራሉ ትዕዛዝ የሰጡት። ፖለቲከኞች ሲወያዩ ለማየት የሄዱ ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞች ሲታሰሩ አይተው ተመለሱ። በስብሰባው ላይ ያልተገኙ ሚኒስትሮችና የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች፣ በአንድ ቀን ውስጥ እጃቸውን እንዲሰጡ በሚዲያ ማስጠንቀቂያ ተሰራጭቷል።
የጦር ሃይል ዋና አዛዥ ጄ/ል ፕራዩዝና ምክትላቸው፤ እንዲሁም ኤታማዦር ሹም፣ የባህር ሃይል፣ የአየር ሃይልና የፖሊስ ዋና አዛዦችን ያካተተ የአምስት ጄነራሎች ኮሚቴ፤ የመንግስትን ስልጣን እንደተቆጣጠረ ጄ/ል ፕራዩዝ ገልፀዋል። ትምህርት ቤቶች ተዘግተዋል። ሁሉም የሚዲያ ተቋማት፤ የግል የቴሌቪዢንና የሬድዮ ጣቢያዎችም ጭምር፤ ከወታደራዊው ጁንታ ከሚመጣላቸው ነገር ውጭ ምንም እንዳያሰራጩ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል። የፖለቲካ ፓርቲ እንቅስቃሴ፣ ሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ተከልክሏል። የማታ ሰዓት እላፊ ታውጇል።
በአጠቃላይ፤ ከመፈንቅለ መንግስት ጋር ተያይዘው የሚመጡ እርምጃዎች በሙሉ በፍጥነት ተከናውነዋል። ፍጥነታቸው አይገርምም። ታይላንድ በመፈንቅለ መንግስት በኩል፤ ከፍተኛ ልምድ የተከማቸባት አገር ናት። በመቶ አመታት ውስጥ 19 የመፈንቅለ መንግስት ታሪኮችን በማስተናገድር በአለም ቀዳሚ አገር ናት ተብሎላታል።

Saturday, 24 May 2014 15:13

የሳምንቱ ምርጥ 10

Billboard TOP 10 Albums

Turn Blue  -The Black Keys
Xscape   -Michael Jackson
NOW 50   -Various Artists
Frozen   -Soundtrack
Rewind   -Rascal Flatts
Blue Smoke   -Dolly Parton
Unrepentant Geraldines   -Tori Amos
Shine On  - Sarah McLachlan
Storyline   -Hunter Hayes
Sovereign   -Michael W. Smith




Top 10 Best Sellers  Books on Amazon
1.The Fault in Our Stars by John Green
Oh, The Places You’ll Go! by Dr. Seuss
The Conscious Parent by Dr. Shefali Tsabary
Capital in the Twenty-First Century by Thomas Piketty
One Nation by Ben Carson M.D.
Frozen Little Golden Book by Victoria Saxon
.City of Heavenly Fire by Cassandra Clare
Ultimate Sticker Book: Frozen by DK Publishing
The Goldfinch: A Novel by Donna Tartt
 Skin Game (Dresden Files) by Jim Butcher


Box Office Top 10

Godzilla
Neighbors
The Amazing Spider-Man 2
Million Dollar Arm
The Other Woman
Heaven is for Real
Rio 2
Captain America: The Winter Soldier
Legends of Oz: Dorothy’s Return
Mom’s Night Out

Saturday, 24 May 2014 15:13

የግጥም ጥግ

የዕድገት 10ቱ ቃላት!
አንዱ የዕድገት ትርጉሙ ጠፍቶበታል
አንዳንዱ ቁልቁል ማደግም ዕድገት ነው ይላል!
አንዳንዱ እንኳን ማደግ ከነመወለዱም ጠፍቶበታል!
አንዳንዱ እንዴት እንደሚታደግ ማወቅ ተስኖታል!
አንዳንዱ ፎቅ ይሰራ ይሰራና የሚከራይ ሲያጣ፤ “ይህ ህዝብ ዕድገት አይገባውም” ይላል፡፡
አንዳንዱ ፎቅ ሰርቶ ሰርቶ ሰርቶ ጫፍ ይወጣና “መሬት ማለት ምን ማለት ነው?” ብሎ ይጠይቃል፡፡
አንዳንዱ “ዕድገት አለ ግን ወረቀት ላይ ነው ያለው፡፡ ስለዚህ ዋናው የወረቀት ዋጋ ማደግ ነው” ይላል፡፡
“አንዳንዱ ዕድገት ማለት ሌሎች ሲያድጉ ማየት ነው፡፡ ስለዚህ የድንኳን ሰባሪ እድገት ነው”! ይላል
አንዳንዱ እድገት ማለት ከዚህ ወዲያም ለምን እንዳላደግን ማሰብ ነው፡፡ በቃ ካሰብክ የግድህን ታድጋለህ” ይላል፡፡
አንዳንዱ ግን ጥብስቅ አድርጎ… አድጎ… አድጎ ከአቅሙ በላይ ተመንድጎ ማደጉን ማቆሙ ጨንቆት “ብቻዬን አድጌ እስከመቼ! የሚያግዘኝ ይቅር የሚቃወመኝ እንዴት ይጥፋ?
የኔን ፎቅ ማየት ካልቻለ
ጎጆው ሲፈረስ ይማር የለ?”
በቃ ዛሬ ገና ይግባው
ቦታ ቀይሮ ሲሰፍር ለውጥም ዕድገትም የሱው ነው፡፡
ግንቦት 2006 ዓ.ም (ለአፍቃሬ ዕድገቶች)

ወ/ሮ ይድነቃቸው የሁለት ልጆች እናት ናት፡፡ ልጆቿ በመጽሐፍ ቅዱስ ዕውቀት ተኮትኩተው እንዲያድጉ ስለፈለገች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ዕውቀትን በቀላል አቀራረብና ቋንቋ የያዙ የልጆች መፃሕፍት ፍለጋ ብዙ ቦታዎች ጠይቃ ማጣቷን ትናገራለች፡፡ የዚህች እናት ገጠመኝ በአገራችን ያለውን የመፃሕፍት ስርጭት ችግር ያመለክት እንደሆነ እንጂ ለሕፃናት የተዘጋጁ መፃሕፍት የሉም ወደሚል ድምዳሜ አያደርሰንም፡፡
የመፃህፍቱን ሥርጭት እንዲሁም ብዛትና ዓይነቱን ለማወቅ የሚቻልበት መንገድ የለም እንጂ ለሕፃናት የታለሙ በርካታ መፃሕፍት ተጽፈዋል፡፡ የደራሲ ማይክል ዳንኤል አምባቸው ሙት ዓመት በጣይቱ ሆቴል ሲከበር እንደተገለፀው፤ ሟቹ አብዛኛው በእንግሊዝኛ ቋንቋ ቢሆንም  40 የልጆች መፃሕፍትን አዘጋጅተው አሳትመዋል፡፡
በሌላ አጋጣሚ ደግሞ 49 የልጆች መፃሕፍት አሳትመዋል የተባሉ አንድ ደራሲ የማግኘት እድል ገጥሞኝ ነበር፡፡ የፃፏቸውን 49 የልጆች መፃሕፍት፣ በየክልሉ ባሉ ትምህርት ቤቶች ማከፋፈላቸውን ነግረውኛል፡፡
ለልጆች ታስበው የታተሙት መፃሕፍት ቁጥር ቀላል አይደለም፤ ይዘትና አቀራረባቸው ግን ብዙ ሊያነጋግር እንደሚችል እሙን ነው፡፡ በቅርቡ “የሉሲ ክዋክብትና ሌሎችም” በሚል ርዕስ በደራሲ ገብረክርስቶስ ኃይለሥላሴ የተዘጋጀው የልጆች መፅሃፍ፤ ልጆች መልካም ሥነ ምግባር እንዲማሩበት ታስቦ የተሰናዳ ሲሆን ለልጆች የሚዘጋጁ መፃሕፍት እንዴት መቅረብ እንዳለባቸው ጥሩ ማሳያ ይመስለኛል፡፡
በ145 ገፆች ተቀንብቦ የቀረበው መጽሐፉ፤ በአራት ምዕራፎች 36 ተረቶችን ይዟል፡፡ “ከአሁን ቀደም ከጓደኛዬ ጋር ‹ናብሊስ› በሚል ርዕስ ከ5ኛ እስከ 8ኛ ክፍል ላሉ ተማሪዎች ሊሆን የሚችል የልጆች መጽሐፍ አዘጋጅቻለሁ” ሲሉ በመግቢያው ላይ ያሰፈሩት ደራሲው “ይህ ጥረት በተመሳሳይ ሁኔታ መቀጠል እንዳለበት አጥብቄ ስላመንሁበት፣ ከ1ኛ እስከ 5ኛ ክፍል ለሚማሩ ተማሪዎች የሚሆን ተነባቢና ጣፋጭ ታሪኮችን በውርስ ትርጉም መልክ አዘጋጅቼ አቅርቤያለሁ” ብለዋል፡፡ ታሪኮቹ በ24 ስዕሎች ታጅበው ነው የቀረቡት፡፡
ደራሲ ገብረክርስቶስ፤ ለሕፃናት የሚዘጋጁ መፃሕፍትን በዕድሜና በክፍል ደረጃቸው እየለዩ ማቅረብ እንደሚገባ አስምረውበታል፡፡ ርዕሰ ጉዳዩ ምንም ይሁን ለአዋቂዎች እንዴት መቅረብ እንደሚችል፣ ለልጆችስ በምን መልኩ እንደሚዘጋጅ በደራሲው መፅሐፍ በተመሳሳይ ጭብጥ ከቀረብ ታሪክ ጋር ለማመልከት እሞክራለሁ፡፡
በ“ሉሲ ክዋክብትና ሌሎችም” መጽሐፍ ውስጥ ስለ ስስትና አልጠግብ ባይነት የቀረበው ታሪክ “ቀላዋጩ ሸረሪት” የሚል ርዕስ አለው፡፡ በድሮ ዘመን ሸረሪት ወገቡ ወፍራም ነበር፡፡ በአንዱ ዕለት ጫካ ውስጥ ያሉ ሁለት እንስሳት፣ በሁለት የተለያዩ መንደሮች ድግስ መሰናዳቱን ነገሩት፡፡ በሁለቱም ድግስ መብላት የፈለገው ሸረሪት፣ የትኛው ድግስ ቀድሞ እንደሚጀመር ስላላወቀ፣ ዘዴ ማፈላለግ ያዘ፡፡
“ወደ ቤቱ እየከነፈ ሄደና ረጃጅም ገመዶችን ያዘ፡፡ ሁለቱን ወንድና ሴት ልጆቹንም ጠራቸው፡፡ ልጆቹንና ገመዶቹን ይዞ ላይ ሰፈርንና ታች ሰፈርን በአማካይ ወደሚያዋስነው ወንዝ ሄዱ፡፡ አቶ ሸረሪት፤ በአንዱ የገመድ ጫፍ ወገቡን አሰረና ሌላኛውን ጫፍ ለሴት ልጁ ሰጣት፡፡ እርሷም የገመዱን ጫፍ እየጎተተች ወደ ታች ሰፈር ሄዳ፣ ግብዣው ሲጀመር ገመዱን በመሳብ ምልክት እንድትሰጠው ታዘዘች፡፡ በሁለተኛውም ገመድ በተመሳሳይ ወገቡን አስሮ፣ ጫፉን ለወንድ ልጁ ሰጠው፡፡ ወንድ ልጁም ወደ ላይኛው ሰፈር ሄዶ እንዲያመለክተው ታዘዘ፡፡ ሁለቱም ልጆቹ የታዘዙትን ለመፈፀም ወደየተመደቡበት ቦታ ገመድ እየጎተቱ ሄዱ፡፡ አቶ ሸረሪት ወገቡን በሁለት ገመዶች እንደታሰረ በመሀል ሆኖ ይጠባበቅ ጀመር…
“አጋጣሚ ሆኖ የሸረሪት ሀሳብ እንዳቀደው አልሆነም፡፡ የላይ ሰፈርና የታች ሰፈር የግብዣው ሰዓት ተመሳሳይ ሆነ፡፡ ሁለቱ የሸረሪት ልጆች፣ ግብዣዎቹ እንደተጀመሩ አባታቸው እንዳዘዛቸው ለመፈጸም ገመዶቻቸውን መሳብ ጀመሩ፡፡ ምስኪኑ አባት፤ ሸረሪት በሁለት አቅጣጫ በሚሳቡ ገመዶች ተወጥሮ በመሀል ተንጠለጠለ፡፡”
“ሸረሪት ወገቡ ቀጥኖ የሚታየው በዚህ ምክንያት ነው የሚለው ይህ ታሪክ በመቋጫ ላይ ልጆች አልጠግብ ባይና ስስታም እንዳይሆኑ የሚያስተምር ሀሳብ አቅርቧል፡፡
“በዓለም የታወቁ አጫጭር ልቦለዶች” በሚል ርዕስ በአምሳሉ አክሊሉ ተተርጉሞ፣ በ1981 ዓ.ም ለአንባብያን የቀረበው መጽሐፍም ስስትና አልጠግብ ባይነት ምን ጉዳት እንደሚያስከትል የሚያስተምር ታሪክ ይዟል፡፡ ከሩስያዊው ደራሲ ሊዎ ቶልስቶይ ሥራዎች ተወስዶ “ላንድ ሰው ምን ያህል መሬት ይበቃዋል?” በሚል ርዕስ በቀረበው ልቦለድ ውስጥ፣ አንድ ደሀና ምንም ያልነበረው ገበሬ፣ ሀብት ማካበትን ዓላማው አድርጎ መንቀሳቀስ ሲጀምር፣ የስግብግብና አልጠግብ ባይነት ስሜቱ አጉል አወዳደቅ ላይ እንደጣለው ያስቃኛል፡፡
የልቦለዱ ገፀ ባሕሪ ሚስት፣ ልጆች፣ ከሲታም ቢሆኑ የቤት እንስሳት፣ አነስተኛም ቢሆን የራሱ መሬትና ኑሮ ነበረው፡፡ ይህንን ኑሮውን ሌሎች ሲተቹበት ነበር ሀብት ለማፍራት መንቀሳቀስ የጀመረው፡፡ በምኞት፣ በጥረትና በድካም ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሰ በርካታ መሬትና ሀብት አፈራ፡፡ ከእርካታ ጋር መገናኘት ግን ሳይቻለው ስለቀረ፣ የተጨማሪ መሬት ባለቤት ለመሆን ጉጉትና ፍላጎቱ እያየለ መጣ፡፡
በዚህ ወቅት ደግሞ ሊታመን በማይችል ዋጋ፣ የሰፊ መሬት ባለቤት ሊያደርገው የሚችል ዕድል አገኘ፡፡ አንድ ሺህ ሩብል ብቻ የሚከፍልበትን መሬት መርጦ፣ ለክቶና በቃኝ ብሎ የመወሰን መብት ነበረው፡፡ በዚህ መብት ውስጥ የተሰጠው ግዴታ ግን ነበር፡፡ የሚፈልገውን መሬት መርጦ ለመጨረስ፣ ፀሐይ ስትወጣ ጉዞ የጀመረበት መነሻ ላይ ጀምበር ስትጠልቅ መድረስ አለበት፡፡ የሚያየውን ለም መሬት ሁሉ ባለቤት ለመሆን ከመነሻው እየራቀ ስለሄደ፣ በመልስ ጉዞው ለብዙ ድካምና እንግልት ተዳረገ፡፡ ጀምበር ከመጥለቋ በፊት መነሻ ቦታ ላይ ቢደርስም ነፍስና ስጋው በምድር መኖር የሚያስችል አቅም አልነበራቸውም፡፡ አንድ ሜትር ጉድጓድ ተቆፍሮ እዚያው እንዲቀበር ሆነ፡፡
“ቀላዋጩ ሸረሪት” እና “ላንድ ሰው ምን ያህል መሬት ይበቃዋል?” የሚል ርዕስ ያላቸው ታሪኮች መሰረታዊ ጭብጥ አንድ ነው፡፡ ስስታምና አልጠግብ ባይነት በስተመጨረሻ ጉዳት ማስከተላቸው እንደማይቀር ትምህርት ይሰጣሉ፡፡
የሁለቱ ታሪኮች አቀራረብ ግን ተደራሻቸውን ታሳቢ ያደረጉ ናቸው፡፡ የደራሲ ገብረክርስቶስ ኃይለሥላሴ “የሉሲ ክዋክብትና ሌሎችም” መጽሐፍ፤ ለልጆች የሚዘጋጁ መፃሕፍት እንዴት መቅረብ እንዳለባቸው ማሳያ ሆኖ ሊቀርብ ይችላል ያልኩት በዚህ ምክንያት ነው፡፡

በያቢ ፊልም ፕሮዳክሽን የተሰራው “ከቃል በላይ” የተሰኘ አስቂኝ የፍቅር ፊልም፣ የፊታችን ሰኞ በአቤል ሲኒማ ይመረቃል፡፡ በፊልሙ ላይ ወጣትና አንጋፋ ተዋንያን እንደተወኑበት የፊልሙ ፕሮዱዩሰሮች ገልፀዋል፡፡

በኢዮብ ጌታሁን የተፃፈውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተው “ያልተኖረ ልጅነት” መጽሐፍ በአሜሪካዊቷ ሻርሊን ቻምበርስ ቦልድዊን ወደ እንግሊዝኛ ተተረጎመ፡፡
“ኦርፋንስ ሶንግ” የሚል ርዕስ የተሰጠው ይኸው የእንግሊዝኛ ትርጉም፣ ከአማርኛው ጋር እንዳይጣረስ የመፅሐፉ ደራሲ በአርታኢነት ተሳትፎበታል፡፡ መፅሐፉ 270 ገፆች ያሉት ሲሆን በዋናነት ከኢትዮጵያ ውጪ እንዲሸጥ ታስቦ የተዘጋጀ ነው፡፡ የመፅሀፉም ዋጋ 14.95 ዶላር ነው፡፡ መጽሐፉ በኢትዮጵያ ውስጥ በቡክ ወርልድ የመፃህፍት መደብሮች ለሽያጭ ይቀርባል ተብሏል፡፡

በደራሲ መዓዛ ወርቁ “Desperate to Fight” በሚል በእንግሊዘኛ ቋንቋ ተፅፎ በሱንዳንስ ተቋም የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ውድድር ላይ የተመረጠው ተውኔት፤ “ከሰላምታ ጋር” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ ተተርጉሞ በኢትዮጵያ መታየት ሊጀምር ነው፡፡ ቲያትሩ ከዚህ ቀደም በእንግሊዝኛ ቋንቋ በኬንያ፣ በኒውዮርክ፣ በስቶክሆልም ስዊድን ለተመልካች ቀርቦ ተወዳጅነትን እንዳተረፈ ተገልጿል፡፡ በተጨማሪም በጀርመንኛ ቋንቋ ተተርጎሞ በጀርመን እና በአውሮፓ ለሚገኙ ተመልካቾች ለማቅረብ theatralize company ከደራሲዋ ጋር ኮንትራት ተፈራርሟል፡፡ ቲያትሩ የኬኒያ፣ የዩጋንዳ፣ የአሜሪካ እና የስዊድን ዜግነት ባላቸው ተዋንያን የተሰራ ሲሆን ለሀገራችን በሚቀርበው ተውኔት ላይ በቲያትር ሙያ የዳበረ ዕውቀት እና ልምድ ያላቸው አርቲስት ኤልሳቤጥ መላኩ እና ፈለቀ የማርውሃ አበበ እንደሚተውኑበት ታውቋል፡፡
በኪባ መልቲ ሚዲያ ፕሮዳክሽን ፕሮዱዩስ የተደረገው ይኸው ቲያትር፤ ከፊታችን ሰኞ ጀምሮ በጃዝ አምባ ላውንጅ በየሳምንቱ ለተመልካች ይቀርባል ተብሏል፡፡ ወደፊትም በሌሎች መድረኮች እንደሚቀርብ ለማወቅ ተችሏል፡፡   

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ለመጀመሪያ ጊዜ የእያንዳንዱን ክልል የጋብቻ ስነ - ስርዓትና ትውፊታዊ ክንውን ሰንዶ ሊያስቀምጥ እንደሆነ አስታወቀ፡፡ በዚህም መሰረት ሰኔ 2 ቀን 2006 ዓ.ም እያንዳንዱ ክልል፣ ክልሉን ይወክላሉ ያላቸውን የጋብቻ ሥርዓቶች ይዞ በመቅረብ ለሌላው ህብረተሰብ ያስተዋውቃል ተብሏል፡፡ የጋብቻ ስነ ስርዓቱና ትውፊታዊ ክንውኑ በመገናኛ ብዙሃን የሚሰራጭ ሲሆን ከዚያም በብሔራዊ ቴአትር ተሰንዶ ይቀመጣል ተብሏል፡፡ በዚህ ዝግጅት ላይ ሁሉም ክልሎች ተወክለው ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር በላከው መግለጫ አስታውቋል።

“የኢትዮጵያ ህያው ሙዚየም” የተሰኘ የሙዚየም ማውጫ ታትሞ ወጣ፡፡ በሀገሬ ሚዲያ ኮሙዩኒኬሽን የተዘጋጀው ይሄው የሙዚየም ማውጫ፤ በሁለት ከተማ አስተዳደሮችና በሌሎችም ክልሎች የሚገኙ ሙዚየሞችን ይዟል፡፡ 80 ገፆች ያሉት ማውጫው፤ በክፍል አንድ ከያዛቸው ሙዚየሞች ውስጥ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም፣ የኢትዮጵያ ፖስታ ሙዚየም የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ሙዚየም፤ በኦሮሚያ የሻሼ ሀውልትና ባህል ሙዚየም፣ በደቡብ ክልል የስልጤ ዞን ሙዚየም፣ የሆሌሎጂ ሙዚየም፣ የኮንሶ ሙዚየምና በተለያዩ ክልሎች ያሉ በርካታ ሙዚየሞችን አካትቷል፡፡ ሀገሬ ሚዲያና ኮሙዩኒኬሽን ከዚህ ቀደም የቱሪዝም ማውጫዎችን ያሳተመ ሲሆን በቱሪዝም ላይ ትኩረት አድርጐ የሚሰራ ድርጅት ነው፡፡

አድናቂዎች ለዕጩዎቹ ድምጽ መስጠት ይችላሉ

ኢትዮጵያውያኑ ድምጻውያን አስቴር አወቀና ጃኪ ጎሲ፣ “አፍሪካን ሚዩዚክ ማጋዚን አዋርድስ” (አፍሪማ) ለተባለው ታላቅ አህጉራዊ የሙዚቃ ሽልማት በተለያዩ ዘርፎች በእጩነት ቀረቡ፡፡
አፍሪማ ሰሞኑን ይፋ ባደረገው የ2014 ሽልማት እጩዎች ዝርዝር ላይ እንደተጠቀሰው፣ ድምጻዊት አስቴር አወቀ በ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ሴት ድምጻዊት”፣ ጃኪ ጎሲ ደግሞ በ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ወንድ ድምጻዊ” ዘርፍ በእጩነት የቀረቡ ሲሆን፣ የሌሎች የአፍሪካ አገራት ድምጻውያን፣ የሙዚቃ ቡድኖች፣ ማኔጀሮች፣ ዳይሬክተሮች፣ ፕሮዱዩሰሮች፣ ዲጄዎች፣ የዳንስ ቡድኖችና የሙዚቃ ቪዲዮዎችም በተለያዩ 26 ዘርፎች ለሽልማት ታጭተዋል፡፡
አስቴር አወቀ በታጨችበት የ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ሴት ድምጻዊት” ዘርፍ፣ ሌሎች ሁለት የኡጋንዳ፣ ሁለት የኬኒያና አንድ የታንዛኒያ ታዋቂ ድምጻውያን በእጩነት የቀረቡ ሲሆን፤ ጃኪ ጎሲ በቀረበበት የ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ወንድ ድምጻዊ” ዘርፍ ደግሞ፣ ሌሎች ሁለት የታንዛኒያ፣ ሁለት የኡጋንዳና አንድ የኬኒያ ድምጻውያን በእጩነት ቀርበዋል፡፡
አድናቂዎች http://afrimma.com/afrimma-nominees-2014/ በሚለው የድረ-ገጽ አድራሻ በመጠቀም ለሚፈልጓቸው እጩ ድምጻውያን፣ የሙዚቃ ቡድኖችና ሌሎች እጩዎች ድምጻቸውን በመስጠት፣ አሸናፊ እንዲሆኑ የራሳቸውን ድጋፍ ማድረግ እንደሚችሉ የሽልማቱ አዘጋጆች ተናግረዋል።
በመጪው ሃምሌ ወር አጋማሽ በአሜሪካ ቴክሳስ ግዛት፣ ሪቻርድሰን ውስጥ በሚከናወነው የሽልማት ስነስርዓት ላይ፣ በአለማቀፍ ደረጃ እውቅናን ያተረፉ የተመረጡ አፍሪካውያን ድምጻውያን፣ ማኔጀሮች፣ ፕሮዲዩሰሮች፣ ዲጄዎች፣ ባህላዊ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች በክብር ይሸለማሉ ተብሏል፡፡ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ከተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች የተጋበዙና ከ17 የአፍሪካ አገራት በክብር እንግድነት ተጋብዘው የሚመጡ ታላላቅ ጀግኖች ይታደማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የአፍሪካን ሙዚቃ የማስተዋወቅ አላማ ያለውና በየአመቱ በሚከናወን ደማቅ ስነስርኣት ለአሸናፊዎች የሚበረከተው ይህ ሽልማት፤ በዘርፉ ከሚሰጡ ታላላቅ አህጉራዊ ሽልማቶች አንዱ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂ የሆኑ ድምጻውያንና የሙዚቃ ቡድኖች ስራዎቻቸውን የሚያቀርቡበትና በቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት ለእይታ የሚበቃውን የዘንድሮውን የአፍሪማ የሙዚቃ ሽልማት ስነስርዓት ስፖንሰር ያደረጉት የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ፓዎር ሃውስ ኢንተርናሽናል ኤርላይንና አክሴስ የተባለው የአሜሪካ ሶፍትዌር አምራች ኩባንያ መሆናቸውንም የሽልማት ድርጅቱ መስራች አንደርሰን ኦቢያጉ በድረ-ገጻቸው ላይ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል፡፡