Administrator

Administrator

    “ቴአትረ ቦለቲካ” የሚል መፅሃፍ ሊያወጡ ነው
በመጪው ግንቦት በሚካሄደው አገራዊ ምርጫ ካለፈው ምርጫ የተለየ ውጤት ቨመጣል ብለው እንደማይጠብቁ የተናገሩት የቀድሞው የኢዴፓ ፕሬዚዳንት አቶ ልደቱ አያሌው፤ በምርጫውም እንደማይወዳደሩ አስታወቁ፡፡ በ “ቴአትረ ቦፖለቲካ ፣ አሉባልታና የአገራችን ፖለቲካ ገመና” በሚል ርዕስ የፃፉት አዲስ መፅሀፍ በቅርቡ በገበያ ላይ እንደሚውልም ተናግረዋል፡፡
“የኢህአዴግን አካሄድና የተቃዋሚው ጎራ ያለበትን ሁኔታ ሳየው በግንቦቱ ምርጫ ካለፈው የተለየ ነገር ይመጣል ብዬ አላስብም” ያሉት አቶ ልደቱ፤ ኢህአዴግ ምርጫውን ሙሉ በሙሉ በራሱ ቁጥጥር ስር አድርጎ እንደቀጠለ ነው፣ ተቃዋሚው ጎራም ካለፉት ስህተቶቹና ድክመቶቹ ተምሮ ራሱን ለማሻሻል ያደረገው ብዙ ነገር የለም ሲሉ ምክንያታቸውን ገልፀዋል፡፡ “ድፍረት አይሁንብኝ እንጂ ተቃዋሚው ጎራ በፓርላማ ያለችውን አንድ መቀመጫ አስጠብቆ ይቀጥላል ወይ የሚለው በራሱ ለኔ ጥያቄ ነው” ሲሉም ጥርጣሬያቸውን አስቀምጠዋል፡፡

በተቃዋሚ ፓርቲ ዙሪያ የተደረጉ የትብብር ሙከራዎች ትግሉን የጎዱ እንጂ የጠቀሙ አይደሉም ሲሉ የሚሞግቱት አቶ ልደቱ፤ ፓርቲዎች በእንተባበር ጥያቄዎች ባይዳከሙ ኖሮ በአሁኑ ወቅት ሁለት ወይም ሶስት ጠንካራ ፓርቲዎች ይኖሩን ነበር ብለዋል፡፡

“ቴአትረ ቦለቲካ፡ አሉባልታና የአገራችን ፖለቲካ ገመና” የተሰኘ ሶስተኛ መፅሃፋቸው በቅርቡ እንደሚወጣ የጠቆሙት አቶ ልደቱ፤ መፅሃፉ በኢትዮጵያ ፖለቲካ አሉባልታዎች ዙሪያ እንደሚያጠነጥን ተናግረዋል፡፡ አሉባልታ የተቃውሞ ጎራውን ትግል ክፉኛ እንደጎዳውም ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ገልጸዋል፡፡

ልጅ ወልዶ የመሳም ፍላጎት አንድ ሰው በህይወት ዘመኑ ሊያገኛቸው ከሚጓጓላቸው ነገሮች መካከል አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ ታዲያ ይህ ልጅ የማግኘት ጉጉት በተለያዩ ተፈጥሯዊም ሆነ ሰው ሰራሽ ምክንያቶች ሊስተጓጎል አልፎም መሀንነትን ሊያስከትል ይችላል፡፡   
የአለም የጤና ድርጅት በፈረንጆቹ 2010ዓ/ም ባወጣው ጥናት መሰረት በአለማችን ላይ ቁጥራቸው 48.5 ሚሊዮን የሚገመት ጥንዶች የዚህ የማሀንነት ችግር ተጠቂዎች ናቸው፡፡ ጥናቱ የተደረገው በፈረንጆቹ አቆጣጠር ከ1990-2010/ አመተ ምህረት በ190/ የተለያዩ ሀገሮች ነው፡፡ በጥናቱም በ1990/ ዓ/ም 42.2/ ሚሊዮን የነበረው የመሀንነት ችግር ያለባቸው ጥንዶች ቁጥር በ2010/ ዓ/ም 48.5/ ሚሊዮን መድረሱን ጠቁሟል፡፡
በዛሬው ፅሁፋችን በተፈጥሮ ከሚከሰተው መሀንነት ውጪ ከአኗኗር እንዲሁም ከመድሀኒት አጠቃቀም ጋር በተያያዘ መሀንነትን ሊያስከትሉ የሚችሉ ነገሮች በሚመለከት የባለሙያ ማብራሪያ አካተን ያጠናቀርነውን ፅሁፍ እንዲህ ልናስነብባችሁ ወደናል፡፡
ለዛሬ ያነጋገርናቸው ባለሙያ ዶክተር አበበ ሀይለማሪያም ይባላሉ፡፡ ዶክተር አበበ በዘውዲቱ ሆስፒታል የማህፀንና ፅንስ ሀኪም ናቸው ለመሆኑ በህክምናው ሳይንስ መሀንነት እንዴት ይገለፃል? በቅድሚያ ያነሳንላቸው ጥያቄ ነበር፡፡
“...ሁለት ጥንዶች ምንም አይነት የእርግዝና መከላከያ ሳይወስዱ በተገቢው መጠን የግብረስጋ ግንኙነት እያደረጉ ቢያንስ ለአንድ አመት መውለድ ካልቻሉ መሀንነት ይኖራል ተብሎ ይታሰባል፡፡ ነገር ግን መከላከያ ሳይወስዱ መውለድ አለመቻላቸው የመሀንነት ምልክት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል እንጂ መሀንነት ነው ብሎ እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ መሀንነት መሆኑን ለማረጋገጥ የተለያዩ ምርመራዎች ሊያስፈልጉ ይችላሉ፡፡”
የወር አበባ ኡደት መዛባት፣ ቀደም ሲል ተከስቶ የነበረ የአባላዘር በሽታ በማህጸን ቱቦ ወይንም በህክምናው fallopian tube ተብሎ የሚጠራው አካባቢ ትቶት የሚያልፈው ቋሚ የሆነ ጠባሳ  መሀንነትን ሊያስከትሉ የሚችሉ ዋነኛ ምክንያቶች ናቸው ይላሉ ዶክተር አበበ፡-
“በሴቶች በኩል መሀንነትን ሊያስከትሉ ከሚችሉ ምክንያቶች መካከል ዋነኛው የእድሜ ጉዳይ ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ እንቁላል የሚያመነጩት እጢዎች እድሜ እየገፋ በሄደ ቁጥር ቀደም ሲል ያመነጩ የነበረውን ያህል እንቁላል ላያመነጩ ይችላሉ፡፡
ስለዚህ እድሜ ትልቁና ዋነኛው ምክንያት ነው ማለት እንችላለን፡፡ የወር አበባ ኡደት ሲዛባም የሴቷ እንቁላል ላይመነጭ ይችላል ወይም ደግሞ እንዳስፈላጊነቱ ጊዜውን ጠብቆ ላይመጣ ይችላል፡፡ ከዛ ውጪ ከተለያዩ ኢንፌክሽኖች እንዲሁም የአባላዘር በሽታዎች የተነሳ የማህፀን ቱቦ መዘጋት ሊኖር ይችላል ይህም የሴቷን እንቁላልና የወንዱ የዘር ፍሬ በተገቢው መንገድ እንዳይገናኙ ሊያደርግ ስለሚችል ለመሀንነት አንዱ ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ አንዳንድ ጊዜ በተፈጥሮ ለመራባት የሚያስፈልጉ አካላት ላይኖሩ ይችላሉ እሱም ሌላኛው ምክንያት ነው፡፡ ሌሎች እንደ ቲቢ ያሉ በሽታዎችም ማህፅን አካባቢ ከሚፈጥሩት ችግር የተነሳ ፅንስ እንዳይፈጠር ሊያደርግ ይችላል፡፡”
በዝርዝ ከተጠቀሱት ምክንያቶች በተጨማሪም የተለያዩ መድሀኒቶች ከመውሰድ ለምሳሌ ከአእምሮ ህመም ጋር በተያያዘ ለረዥም ጊዜ መውሰዱ መድሀኒቶች በሴቷ በኩል መሀንነትን ሊያመጡ እንደሚችሉ ዶክተር አበበ ይገልፃሉ፡፡
“...ለመሀንነት የሚያጋልጡ የተለያዩ መድሀኒቶች አሉ፡፡ ለምሳሌ አንዳንድ የደም ግፊት መድሀኒቶች ለመሀንነት የሚያጋልጡበት ሁኔታ አለ፡፡ ይህ ማለት ሁሉም የደም ግፊት መድሀኒቶች ለመሀንነት ያጋልጣሉ ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን አንዳንዶቹ መድሀኒቶች በውስጣቸው የያዙት ንጥረነገር ለመሀንነት የሚኖረውን ተጋላጭነት የሚጨምሩበት ሁኔታ አለ፡፡ አንዳንድ ለአእምሮ ህመም ለረዥም ጊዜ የሚወሰዱ መድሀኒቶችም በተመሳሳይ ለዚህ ችግር ሊዳርጉ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን በአብዛኛው እንደዚህ አይነት መድኒቶች በሀኪም ትእዛዝ የሚወሰዱ ስለሆኑ ይህን አይነቱን ችግር እንደሚያስከትል ከታወቀ ባለሙያው ሌሎች መድሀኒቶችን ሊያዝ ይችላል፡፡
በተለምዶ በአብዛኛው ህብረተሰብ ዘንድ የእርግዝና መከላከያ እንክብሎች ወይም መርፌ ለዚህ ይዳርጋል የሚል አስተሳሰብ አለ፡፡ ነገርግን በህክምናው ሳይንስ የዚህ አይነት አመኔታ የለም፡፡ ማለትም ይህን በሚመለከት በተደረጉት የተለያዩ ጥናቶች የዚህ አይነት መድሀኒቶች መሀንነትን እንደማያመጡ ተረጋግጧል፡፡”
ቀደም ሲል የተጠቀሱት ምክንያቶች በሴቶች በኩል መሀንነትን ሊያስከትሉ ከሚችሉ ምክንያቶች መካከል ዋነኞቹ ይሁኑ እንጂ ለመሀንነት ሴቷም ሆነች ወንዱ ተመጣጣኝ የሆነ አስተዋፅኦ ሊኖራቸው ይችላል ብለዋል ዶክተር አበበ፡፡
“...በአብዛኛው ከወንዱም ከሴቷም በኩል ተመጣጣኝ የሆነ ምክንያት ሊኖር ይችላል፡፡ ለምሳሌ ወንዱ ከ30-50% ወይም በአማካኝ 40% የወንዱ ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ በተመሳሳይ የተቀረው 40% በሴቷ በኩል የሚከሰት ችግር ነው፡፡ ከሁለቱም ምክንያት ሊሆን የሚችልበት 10% ይሄ ነው ተብሎ የማይገለፅ ደግሞ 10% ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ በአጠቃላይ መሀንነት ምክንያቱ በአንድ ወገን ነው ብሎ መደምደም አይቻለም፡፡”
ቀደም ሲል ባለሙያውም እንደ ገለፁት ምንም እንኳን ወንዱ እንዲሁም ሴቷ ለመሀንነት ያላቸው አስተዋፅኦ በመቶኛ ደረጃ ይለያይ እንጂ መሀንነት በሴቶች ብቻ ሳይወሰን በሁለቱም ፆታዎች ላይ ሊከሰት የሚችል ችግር ነው፡፡ ነገር ግን በአብዛኛው የህብረተሰብ ክፍል ዘንድ መሀንነት በሴቶች ላይ ብቻ የሚከሰት ችግር አድርጎ የማሰብ የቆየ ልማድ አለ፡፡ ይህም የህክምናው ሳይንስ ከሚለው ፈፅሞ የራቀ ነው እንደ ማብራሪያው፡፡
“...በተለይ እንደኛ ባሉ ታዳጊ ሀገሮች መሀንነት የሴቷ ችግር ብቻ ተደርጎ ይታሰባል፡፡ ይህ የሆነበት የተለያዩ ባህላዊ እንዲሁም ሀይማኖታዊ አመለካከቶች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ሌላውና ለዚህ አይነቱ አመለካከት መንስኤ የሚሆነው ደግሞ ችግር ሲኖር ሁለቱም ጥንዶች በጋራ ሆነው ህክምናቸውን ለመከታተል የሚኖራቸው ተነሳሽነት ነው፡፡ በአብዛኛው ይህ የመሀንነት ችግር ሲከሰት ሴቶች ፈጥነው ወደ ህክምና ተቋም ይመጣሉ፡፡ አብዛኞቹ ወንዶች ይህን ለማድረግ ፈቃደኛ አይሆኑም ስለዚህም ሴቷ እንደ ምክንያትነት ትጠቀሳለች፡፡ ነገር ግን መሀንነት በተመጣጣኝ ሁኔታ በወንዱም ሆነ በሴቷ ላይ ሊከሰት የሚችል ችግር ነው፡፡”
መሀንነት በተፈጥሮ እና በአንዳንድ የጤና ችግሮች የሚከሰት ቢሆንም ከአኗኗር እንዲሁም ከመድሀኒት አጠቃቀም ጋር በተያያዘ መሀንነትን ሊያስከትሉ የሚችሉ ነገሮች አሉ፡፡
“...ቀደም ሲል የጠቀስኳቸው ተፈጥሯዊና እንደ አባላዘር ያሉ በሽታዎች ለመሀንነት ሚዳርጉ ዋነኛ ምክንያቶች ይሁኑ እንጂ ከዛ ውጪ ሌሎች ከአመጋገባችን ወይም እለትተለት የምናደርገው እንቅስቃሴ ለመሀንነት የሚኖረንን ተጋላጭነት ከፍ ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ ለምሳሌ አመጋገብን ብንመለከት አንዳንድ ሴቶች የሰውነታቸው ክብደት በጣም ዝቅተኛ ይሆንና ሰውነታቸው የሚፈለገውን ንጥረ ነገሮች በተገቢው መንገድ ላያገኝ ይችላል፡፡ ይህ ደግሞ የወር አበባ መዛባትን አንዳንዴም ጭርሱንም እንዲቀር ሊያደርገው ይችላል፡፡ ስለዚህ ይህ ሁኔታ ልጅ ለመውለድ የሚኖረውን ሁኔታ ሊያዘገይ ወይም መሀንነትን ሊያስከትል ይችላል፡፡”
የሴቷ የሰውነት ክብደት ጤናማ የሚባለው ምን ያህል እንደሆነና የክብደት መቀነስ የሚለው ቀደም ሲል ከተጠቀሰው የወር አበባ መዛባትን ከማስከተሉ ባለፈ መሀንነትን ሊያስከትል የሚችልባቸውን መንገዶች ዶ/ር አበበ እንደሚከተለው ገልጸዋል፡፡   
“..አንዲት ሴት በአማካኝ ሊኖራት የሚገባው የሰውነት ክብደት ሀምሳ ኪሎ እንዲሆን ይጠበቃል፡፡ ነገር ግን ክብደቷ ከዛ በታች ከሆነ ይህ የክብደት ማነስ ለወር አበባ መዘግየት ብቻም ሳይሆን ከአእምሮ የሚመነጩ የተለያዩ ኬሚካሎች በተገቢው መጠን እንዳይመነጩ ሊያደር ይችላል፡፡ ይህም የሴቷ እንቁላል ከዘር ማፍሪያ እጢ ፅንሱ እስከ ሚፈጠርበት የማህፀን ክፍል የሚኖረው መንገድ ላይ ተፅእኖ ሊፈጥር ስለሚችል በዚህ ሁኔታ መውለድ ሊዘገይ ወይም መሀንነት ሊከሰት ይችላል፡፡”   
መሀንነትን በሚመለከት በህብረተሰቡ ዘንድ የተለያዩ አመለካከቶች አሉ፡፡ ከእነዚህ ለዘመናት የመሀንነት መንስኤ ናቸው ተብለው በአብዛኛው የህብረተሰብ ክፍል ዘንድ እንደ ምክንያት ከሚጠቀሱት ነገሮች መካከል መሀንነትን በዘር የሚመጣ ችግር አድርጎ ማሰብ አንዱ ነው፡፡ ለዚህም ነው አንዳንድ ሰዎች ከቤተሰብ አባላት መካከል አንዳቸው ይህ የመሀንነት ችግር ሲገጥማቸው “ኧረ እኛ በዘራችን መሀንነት የለም...” ሲሉ የሚደመጡት፡
“..ሁሉም የመሀንነት ችግር በዘር የሚመጣ ነው ብሎ መደምደም ባይቻልም በተወሰነ ደረጃ ከዘር ጋር የሚያያዝበት ሁኔታ አለ፡፡ ቀደም ሲል ጠቅሼዋለሁ ለመሀንነት ሚያጋልጡ የተለያዩ ምክንያቶች አሉ፡፡ ነገር ግን አልፎ አልፎ የተለያዩ genetic disorder ወይንም በዘር የሚወረስ የተፈጥሮ መዛባት የምንላቸው ችግሮች ሊያጋጥሙ ይችላሉ፡፡
ይህ ማለት አንዳንድ ጊዜ  በተፈጥሮ ለመራባት የሚያስፈልጉት ህዋሶች (Gene) በሰውነታችን ውስጥ ላይገኙ ይችላሉ ወይም ደግሞ ባላስፈላጊ ሁኔታ ተባዝተው ሊገኙ ይችላሉ፡፡
ስለዚህ የዚህ አይነት ምክንያቶች ለመሀንነት የሚዳርጉበት ሁኔታ አለ፡፡ ነገር ግን ከቤተሰብ አባላት ውስጥ የመሀንነት ችግር ተከስቶ ስለማያውቅ ወይም ይህ አይነቱ ችግር ያለበት ሰው የለም ማለት ፈፅሞ መሀንነት ሊያስከትል አይችልም ማለት አይደለም...” እንደ ዶ/ር አበበ ኃ/ማርያም የጽንስና ማህጸን ህክምና እስፔሻሊስት፡፡

የአንዲት ሴተኛ አዳሪ ኢትዮጵያዊትን የዕለት ማስታወሻ የሚተርከውና በአርታኢ ፍፁም ብርሃኔ የተዘጋጀው “ሮዛ ቁጥር ሁለት” መፅሃፍ ገበያ ላይ ዋለ፡፡
ነዋሪነቱ በደቡብ አፍሪካ ጆሃንስበርግ ከተማ የሆነው የመፅሃፉ አርታኢ የባለታሪኳን ዳያሪዎች አሰባስቦ ለህትመት ለማብቃት አንድ ዓመት እንደወሰደበት ግልጿል፡፡ በዚህ መፅሃፍ የመጀመሪያው ክፍል ከአንድ ዓመት በፊት የታተመ ሲሆን ከ45ሺ በላይ ሰዎች እንዳነበቡትና መፅሃፉን ወደ እንግሊዝኛ ቋንቋ ለመተርጎም በዝግጅት ላይ እንደሚገኙም ተገልጿል፡፡  

በአቢሲኒያ ኢንተርቴይንመንት እየተዘጋጀ በኤፍኤም 96.3 ላይ ሲሰራጭ የቆየው የቀጥታ የስልክ መስመር የድምፅ ውድድር ዛሬ ይጠናቀቃል፡፡
ለመጨረሻ ውድድር የቀረቡ አምስት ተወዳዳሪዎች በቀጥታ ከስቱዲዮ የሚያካሂዱትን የድምፅ ውድድር ለመዳኘት ታዋቂ የሙዚቃ አቀናባሪዎችና ድምፃውያን በስፍራው ይገኛሉ፡፡ በውድድሩ ከአንድ እስከ ሶስት የሚወጡት ተወዳዳሪዎች የግጥም፣ የዜማና የሙዚቃ ቅንብር ሙሉ ወጪያቸው ተችሎ ነጠላ ዜማ እንዲሰሩ እንደሚደረግ የፕሮግራሙ ዋና አዘጋጅ አቶ አባተ ማንደፍሮ ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡
አቢሲኒያ ኢንተርቴይንመንት እስከ አሁን ድረስ በአምስት ዙሮች ባደረገው የቀጥታ ስልክ መስመር የድምጽ ውድድር በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ከ350 በላይ ጀማሪ ድምጻውያን እንደተካፈሉ አቶ አባተ ተናግሯል፡፡ ፕሮግራሙ የተጀመረበት 4ኛ ዓመት በዚሁ ዕለት እንደሚከበርም ገልጿል፡፡

በድምፃዊ ዳንኤል ዘውዱ የተሰራው “የዝና” የተሰኘና ነባር ዘፈኖች የተካተቱበት የሙዚቃ አልበም በገበያ ላይ ዋለ፡፡
በ1990ዎቹ መጀመሪያ ላይ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየውን የተስፋዬ ወርቅነህን ተወዳጅ ዜማዎች ሪሚክስ በማድረግና በድጋሚ በመስራት በገበያ ላይ ያዋለው ድምፃዊ ዳንኤል ዘውዱ ለዘፈኖቹ ግጥምና ዜማ ደራሲዎች ተገቢውን ክፍያ መፈፀሙንና የቅጂ መብቱን ጠብቆ መስራቱን ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡
የዘፈኖቹ ግጥሞች የተወሰነ ማሻሻያዎች እንደተደረጉባቸውና በታዋቂ የሙዚቃ አቀናባሪዎች መሰራታቸውንም ድምፃዊው ተናግሯል፡፡  

ላለፉት ሃምሳ አመታት ተስለው የተጠራቀሙ የሰዓሊ ወርቁ ጐሹ የስዕል ስራዎች ለዕይታየ ማቀርቡበት “ላይት” የተሰኘ የስዕል አውደ ርዕይ የፊታችን አርብ ከቀኑ 11 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ሙዚየም አርት ጋለሪ ይከፈታል፡፡
በዚህ አውደ ርዕይ እጅግ በርካታ የስዕል ስራዎች የሚቀርቡ ሲሆን የተለያዩ ጉዳዮችን እንደሚዳስሱም ተገልጿል፡፡
አውደ ርዕዩ እስከ ፌቡራሪ 23 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ ለጐብኚዎች ክፍት ሆኖ እንደሚቆይም አዘጋጁ ጐሹ አርት ጋለሪ ከላከው መግለጫ ለማወቅ ተችሏል፡፡


ቫይረሱ በትንፋሽ መተላለፍ ሊጀምር እንደሚችል ተሰግቷል

በምዕራብ አፍሪካ አገራት ተከስቶ ከ22 ሺህ በላይ ሰዎችን ያጠቃውና ወደ 9 ሺህ የሚደርሱትንም ለህልፈት የዳረገው የኢቦላ ቫይረስ፣ ባህሪውን እየለወጠ እንደሚገኝና ለውጡ ቫይረሱን ከሰው ወደ ሰው በቀላሉ መዛመት እንደሚያስችለው ለማወቅ  ጥናት እየተካሄደ  መሆኑን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የፈረንሳዩን ፓስተር ኢንስቲቲዩት ተመራማሪዎች ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ቫይረሱ የቀድሞ ባህሪውን እየለወጠ እንደሚገኝ የተረጋገጠ ሲሆን ተመራማሪዎቹ የቫይረሱ የባህሪ ለውጥ የከፋ አደጋ የሚያስከትል መሆኑን ለማወቅ  በጊኒ፣ በቫይረሱ በተጠቁ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የደም ናሙና ላይ ምርምር እያደረጉ ይገኛሉ፡፡
የተመራማሪ ቡድኑ አባል የሆኑት ዶክተር አናቫይ ሳኩንታቢ እንዳሉት፤ የኢቦላ ቫይረስ በሚገርም ሁኔታ የተፈጥሮ ባህሪውን እየቀየረ እንደሚገኝ በጥናታቸው አረጋግጠዋል፡፡ ቫይረሶች በጊዜ ሂደት የተፈጥሮ ባህሪያቸውን መቀየራቸው የተለመደ ክስተት ነው ያሉት ዶክተሩ፣ ኢቦላም እንደ ኤች አይቪ ኤድስና ኢንፍሉዌንዛ ቫይረሶች ሁሉ በከፍተኛ ሁኔታ የባህሪ ለውጥ የማካሄድ ተፈጥሯዊ ባህሪ እንዳለው ተናግረዋል፡፡ ይህም ቫይረሱ ከሁኔታዎች ጋር የመላመድ አቅሙን ከፍ እንደሚያደርገውና የበለጠ ሊስፋፋ ይችላል የሚል ስጋት እንደፈጠረ አክለው ገልጸዋል፡፡
ቫይረሱ በርካታ ሰዎችን እያጠቃና የባህሪ ለውጡን እየቀጠለ ከሄደ፣ በትንፋሽ የመተላለፍ ዕድል ሊኖረው ይችላል የሚል ስጋት መኖሩን የተናገሩት ተመራማሪዎቹ፣ ይህም ሆኖ ግን ለጊዜው ቫይረሱ በትንፋሽ እየተላለፈ እንደሚገኝ የሚያረጋግጥ ምንም አይነት ተጨባጭ ማስረጃ አለመኖሩን ገልጸዋል፡፡
በተያያዘ ዜና የአለም ባንክ ፕሬዚደንት ጂም ያንግ ኪም፤ አለማችን በቀጣይ ሊከሰቱ ለሚችሉ ኢቦላን የመሳሰሉ ገዳይ በሽታዎች ይህ ነው የሚባል ዝግጅት አለማድረጓንና ይህም ከፍተኛ ጥፋት ሊያስከትል እንደሚችል አስታወቁ፡፡
መንግስታት፣ የእርዳታ ድርጅቶች፣ አለማቀፍ ተቋማትና ኩባንያዎች ወደፊት ሊከሰቱ የሚችሉ የገዳይ በሽታዎች ወረርሽኞችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር እጅ ለእጅ ተያይዘው መስራት ይገባቸዋል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ በምዕራብ አፍሪካ አገራት ከፍተኛ ጥፋት ካደረሰው የኢቦላ ወረርሽኝ በመማር አለም ከወዲሁ ዝግጅት ማድረግ ይጠበቅባታል ብለዋል፡፡

የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው አውሮፕላኖችንና መንገደኞችን በማስተናገድ በአለማችን ከሚገኙ አውሮፕላን ማረፊያዎች የመጀመሪያውን ደረጃ መያዙን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡
በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2014 ዓ.ም 70 ነጥብ 47 ሚሊዮን መንገደኞችን ያስተናገደው የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ፣ ከዚህ በፊት በርካታ መንገደኞችን በማስተናገድ ቀዳሚነቱን ይዞ የቆየውን የለንደኑን ሄትሮው አውሮፕላን ማረፊያ በመብለጥ በአንደኝነት መቀመጡን ዘገባው አስታውቋል፡፡
የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ስራ አስኪያጅ ሼህ አህመድ ቢን ሰኢድ አል መክቱም እንደገለጹት፣ በርካታ አለማቀፍ በረራዎችን በማስተናገድ የሚታወቀው አውሮፕላን ማረፊያው የሚያስተናግዳቸውን መንገደኞቹን ቁጥር ባለፉት አምስት አመታት በኣማካይ በሁለት ዲጂት እያሳደገ መጥቷል፡፡
አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው ዱባይን የአለማቀፍ የአየር በረራ ማዕከል የማድረግ ግቡን ወደ ማሳካት እየተቃረበ ነው ያሉት ስራ አስኪያጁ፣ በተያዘው የፈረንጆች አመትም የመንገደኞቹን ብዛት በከፍተኛ ሁኔታ ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
የአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ፖል ግሪቭስ በበኩላቸው፣ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው አዲስ የበረራ ማስተናገጃ በመክፈት፣ አመታዊ የመንገደኞች ማሰተናገድ አቅሙን በያዝነው የፈረንጆች አመት 90 ሚሊዮን ለማድረስ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡
ከዚህ ቀደም በርካታ መንገደኞችን በማስተናገድ በቀዳሚነት ይጠቀስ የነበረው የለንደኑን ሄትሮው አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ በ2014 ያስተናገዳቸው መንገደኞች ቁጥር 68.1 ሚሊዮን እንደነበር ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡

የአፍሪካ ህብረት የአህጉሪቱን ርዕሰ መዲናዎች በመንገድ፣ በባቡርና በአየር በረራ ማስተሳሰር ያስችላል የተባለ ትልቅ ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ ከቻይና መንግስት ጋር የትራንስፖርት የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረመ፡፡
ከቻይና ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዚያንግ ሚንግ ጋር የመግባቢያ ስምምነቱን የተፈራረሙት የህብረቱ ሊቀመንበር ንኮሳዛ ድላሚኒ ዙማ፣ ባለፈው ማክሰኞ በአዲስ አበባ የተፈረመውን ስምምነት ህብረቱ እስካሁን ከአጋሮች ጋር ከተፈራረማቸው ስምምነቶች ሁሉ ጉልህ ስፍራ የሚሰጠው ነው ብለውታል፡፡
ዚያንግ ሚንግ በበኩላቸው፤ የመግባቢያ ስምምነቱ የምዕተ አመቱ ትልቅ ሰነድ ነው፣ በአየር በረራ መስክ የተፈረመው ስምምነትም በአፍሪካ ህብረት እና በቻይና መካከል ያለውን ትብብር ወደ አዲስ መስክ ያሰፋ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከአንደኛው የአፍሪካ ክፍል ወደ ሌላኛው ለመጓዝ የተሻለ አማራጭ ተደርጎ የሚወሰደው የአውሮፓን የበረራ መስመር የተከተለ አካሄድ ነው ያሉት ሚንግ፣ አህጉሪቱ ሰፊ እንደመሆኗ በአውሮፓ የበረራ መስመሮች ላይ ጥገኛ ያልሆነና አገራቱን በቀላሉ የሚያስተሳስር የራሷ የትራንስፖርት አውታር ሊኖራት ይገባል ሲሉ መናገራቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

አሜሪካ በኩባ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ እንዳትገባ ያስጠነቀቁት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ራኡል ካስትሮ፤ መሰል ጣልቃ ገብነቶች በሁለቱ አገራት መካከል እንደገና የተጀመረውን ግንኙነት ትርጉም አልባ ያደርጉታል ሲሉ  መናገራቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡ ከ40 አመታት በኋላ ኩባን በመጎብኘት የመጀመሪያው የአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ረዳት ጸሃፊ ሮቤርታ ጃኮብሰን ባለፈው ሳምንት አገሪቱን መጎብኘታቸውን ተከትሎ ፕሬዚዳንት ራኡል ካስትሮ የአሜሪካ አካሄድ በኩባ ላይ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጫና ለመፍጠር ማሰቧን ያመላክታል  ብለዋል፡፡
አሜሪካ ይህንን አካሄዷን የማታስተካክል ከሆነ በሁለቱ አገራት መካከል እንደገና የተጀመረው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ትርጉም ያጣል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ አሜሪካ በውስጥ ጉዳያችን ጣልቃ ለመግባት የምታደርገውን ማንኛውም አይነት ሙከራ አገራቸው በዝምታ እንደማታልፈው አስጠንቅቀዋል፡፡
አሜሪካ በኩባ ውስጣዊ የፖለቲካ ተቃውሞን ለማቀጣጠል እያሴረች ነው ያሉት ራኡል ካስትሮ፣ ይሄም ሆኖ ግን ከዚህ የጣልቃ ገብነት ተግባሯ መታቀብ በምትችልበት ሁኔታ ዙሪያ ከአሜሪካ ጋር ለመምከር ፈቃደኛ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ አገራቸው በኩባ ላይ የጣለችውንና ለአስርት አመታት የዘለቀውን የኢኮኖሚ ማዕቀብ እንድታነሳ ጫና እንዲያሳድሩ ጥሪ ያቀረቡት ራኡል ካስትሮ፣ ኩባንያዎቿ በኩባ የቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ ላይ እንዲሰማሩ የፈቀደችው አሜሪካ፣ በሌሎች የኢኮኖሚ መስኮች ላይም እንደምትሰራ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል፡፡