Administrator

Administrator

 የውጭ ምንዛሬ በመንግሥት ተመን ሳይሆን በገበያ ዋጋ?
•     እንዲህ ዐይነት የምንዛሬ አሠራር ባለፉት 50 ዓመታት ውስጥ ያልታየ “ሥር-ነቀል ለውጥ” ነው።
•     ጥቅሙና ጉዳቱ ላይ ሰዎች ብዙ መነጋገርና መከራከር፣ ከዚያም ባሻገር መጨቃጨቅ ይችላሉ።
አስጨፋሪዎችም አስለቃሾችም ሞልተዋል


ለክፉም ለደጉም፣ አዲሱ የምንዛሬ ሥርዓት በግማሽ ምዕተ ዓመት ውስጥ ያልታየ “ታሪካዊ ለውጥ” መሆኑ ግን አያከራክርም። ብዙዎች በዚህ አባባል የሚስማሙ ይመስላል። “ለውጡን ቢቃወሙም ቢደግፉም”። ይህም ብቻ አይደለም።
እውነት ለመነጋገር ከፈለጉ፣ ቢያንስ ቢያንስ ለተወሰነ ጊዜ የዋጋ ንረትንና የኑሮ ውድነትን እንደሚያባብስም መመስከር ይችላሉ - ለውጡን ቢደግፉም ቢቃወሙም፣ እውነታውን ላለማየት እስካልሸሹ ድረስ።
ሌሎች የመስማሚያ ነጥቦችም አሉ።
ነባሩ የምንዛሬ ተመን እንደስካሁኑ ወደፊት ሊቀጥል የማችልበት ደረጃ ላይ እንደደረሰ ለመረዳት ከባድ አይደለም። በሆነ መንገድ ካልተስተካከለ በቀር፣ የመንግሥት የምንዛሬ ተመንና የጥቁር ገበያ ዋጋ በዕጥፍ ተለያይቶ እስከመቼ ይዘልቃል? በዚህ መንገድስ የኤክስፖርት ምርት እንዴት ሊያድግ ይችላል?
ከዐሥር ዓመት በፊት፣ አነስተኛ የወርቅ አምራቾች በዓመት ስምንት ኩንታል ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ የሸጡበት ጊዜ እንደነበር ይታወሳል።
የምንዛሬ ተመኑ አላዋጣ ሲላቸውስ? ለብሔራዊ ባንክ ከመሸጥ ይልቅ፣ በሰው በሰው፣ በነጋዴ በደላላ በየአካባቢያቸው በደህና ዋጋ ለመሸጥ ይሞክራሉ። ዞሮ ዞሮ በድንበር በኩል በኮንትሮባንድ በዶላር ወደ ውጭ አገር ይሄዳል። መንግሥት በቁጥጥር ብዛት ይህን ኮንትሮባንድ ማስተካከል አይችልም። ለነገሩ፣ አምራቾችም በቁፋሮ ያገኗትን ወርቅ በድብቅ ለመሸጥ እየተጨናነቁና በመንግሥት ቁጥጥር እየተሳቀቁ ምርታቸውን ማሳደግ አይችሉም። አገሪቱም ዶላር አታገኝም።
በዶላር ዕጥረት ሳቢያ ገደል አፋፍ ላይ የደረሰችው ለምን ሆነና! IMF ከሳምንት በፊት ባወጣው ሰነድ እንደገለጸው ከሆነ፣ የአገሪቱ የውጭ ምንዛሬ ክምችት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተራቆተ፣ ለአንድ ሳምንት የማዘልቅ ሆኗል። ይሰውረን አትሉም? የምንዛሬ ተመን፣ ከዚህ አደጋ አላዳነንም። ለአደጋ ዳረገን እንጂ። IMF እንደዚያ ይላል።
በእርግጥ የዶላር ዕጥረቱና አደጋው በፍጥነት እየተባባሰ የአገሪቱ ኢኮኖሚ ከክፉ ቀውስ የተጋለው፣ በጦርነት ሳቢያ ነው። ጦርነት መደበኛ ኑሮ ሊሆንብን ምን ቀረው? ከጦርነት ጋር አብረው የሚመጡ የሥነ ምግባር ብልሹነትና የሥርዓት አልበኝነት በሽታዎችን በየአካባቢያችሁ እየታዘባችሁ ነው? ሌላውን እርሱት። የኢኮኖሚ ጉዳዮችን በመዘገብ የሚታወቀው ዘ ኢኮኖሚስት መጽሔት ሰሞኑን ስለ ኢትዮጵያ ምን ብሎ እንደዘገበ አይታችኋል?
የምንዛሬ አሠራር ለውጥ፣ የአይኤምኤፍና የዓለም ባንክ ብድር… ምናምን አልዘገበም። ለእግረ መንገድ ያህል ጠቀስ ጠቀስ አድርጎ ጽፏል። የዘገባው ዋና ትኩረት ግን ሌላ ነው። የሰዎች እገታ በኢትዮጵያ እየተስፋፋ እንደመጣ በሰፊው ይተነትናል።
የምንዛሬ የማሻሻያ ለውጥ፣ ኢንቨስትመንትንና ኤክስፖርትን ለማሳደግ ሊጠቅም ይችላል። ሰላም ከሌለ፣ ጦርነት ካልቆመ፣ ሥርዓት አልበኝነት ከተስፋፋ፣ ሽፍትነትና እገታ “ሃይ ባይ” ካጣ… ለኢንቨስትመንት የሚጓጓ አይኖርም። ከኢንቨስትመንት የሚሸሽ እንጂ። ዘኢኮኖሚስት እንደዚያ ብሏል። እኛስ የጦርነትን ክፋት ጠፍቶን ነው?
ጦርነት የማዘውተው አባዜያችንን ካላራገፍን፣ ከዶላር ዕጦት አንገላገልም። ጦርነትን ዕርም ብለን ካልተውን፣ የትኛውም ዐይነት የምንዛሬ አሠራር የትም አያደርሰንም። ጦርነትን መግታትና ማስቀረትም ግን በቂ አይደለም።
በእስከዛሬው የምንዛሬ አሠራር የዶላር ዕጥረትን ማቃለል አይቻልም። በሌላ አነጋገር፣ የውጭ ኢንቨስትመንትንና ኤክስፖርትን የሚያዳክም እንጂ የሚያሳድግ አይደለም - ነባሩ የምንዛሬ አሠራር።
እንደታሰበው ቢሆን፣ ዘንድሮ ከኤክስፖርት ምርት 10 ቢሊዮን ዶላር ገደማ መገኘት ነበረበት። ግን ብዙም ፎቀቅ አላለም።


*

ሥር-ነቀል የምንዛሬ ለውጥ - ብዙ ጣጣ አለው!
በሌላ በኩልም ግን፣ ነባሩ የምንዛሬ አሠራር በአንዴ ከሥር ተነቃቅሎ ሲለወጥ ብዙ ነገሮችን ያናጋሉ። ለኢኮኖሚ አደጋዎችም ያጋልጣል። “ነባር የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች” በሙሉ እንደገና ካልተከለሱና ካልተለወጡ፣ ከአዲሱ የምንዛሬ አሠራር ጋር አብረው ሊሄዱ አይችሉም። የፋብሪካዎች ሥራ በመለዋወጫ ዕቃ ዕጦት እንዳይደናቀፍ “ተጨማሪ የውጭ ምንዛሬ እንዲያገኙ በመንግሥት ተወስኗል” የሚል ዜና ካሁን በኋላ አይሠራም።
“የውጭ ምንዛሬ ለፍጆታ ሸቀጦች አናባክንም። የውጭ ምንዛሬ፣ ነዳጅና ማዳበሪያ ለመሳሰሉ መሠረታዊ ምርቶች፣ እንዲሁም ለኢንዱስትሪ ዕድገት የሚያስፈልጉ የፋብሪካ ማሽኖች መዋል አለበት”… እንዲህ ዐይነት አባባል ካሁን በኋላ ብዙ አያስኬድም። ለጊዜው ለሁለት ለሦስት ዓመት ያህል፣ ለነዳጅና ለማዳበሪያ የዶላር ኮታና ድጎማ መመደብ ይቻላል። ግን ለጊዜው ብቻ ነው ተብሏል። ወደ ፊት አይኖርም።
“ስንዴና ስኳር ከእንግዲህ ከውጭ አንገዛም። ብስኩትና ማስቲካ ከውጭ አናስገባም! የሸቀጥ ማራገፊያ አንሆንም”… የሚሉ አባባሎችም ከእንግዲህ ብዙ አያራምዱም። ይህም ብቻ አይደለም።
እንደምታውቁት፣ የኤሌክትሪክ ግድብ፣ የመንገድ ግንባታ፣ የኢንዱስትሪ ፓርክ፣ የማዳበሪያና የስኳር ፋብሪካ… የመንግሥት የፕሮጀክቶች ዐይነትና ቁጥር ብዙ ነው። ካሁን በኋላ ግን፣ እንደ ልብ መሆን አይቻልም። የምንዛሬ ገበያ ለመንግሥት አስቸጋሪ ነው። መንግሥት ከውጭ እየተበደረ የፕሮጀክቶችን የመጀመር ብዙ ዐቅም አይኖረውም። ዕዳ ከተከማቸበት በኋላ ብድሩን እንዴት መመለስ ይችላል?
የምንዛሬ ተመንና የምንዛሬ ገበያ - የሒሳብ ልዩነት።
የውጭ ብድር ከነወለዱ በየዓመቱ 2 ቢሊዮን ዶላር ሲከፍል እንደነበር ታስታውሳላችሁ። ያው መንግሥት ዶላር አይወልድም። ራሱ መንግሥት በሚመራው ተመን፣ በ60 ብር የምንዛሬ ሒሳብ ከባንኮች ዶላር ይወስዳል።
2 ቢሊዮን ዶላር ለመውሰድ 120 ቢሊዮን ብር ይከፍል ነበር ማለት ነው።
አሁንስ?
የምንዛሬ ዋጋው 100 ብር እያለፈ አይደል? በመቶ ብር ብናሰላው እንኳ፣ መንግሥት ከባንኮች 2 ቢሊዮን ዶላር ለማግኘት 200 ቢሊዮን ብር መክፈል ይኖርበታል።
ልዩነቱ ቀላል አይደለም። የመንግሥት በጀት ላይ ተጨማሪ የ80 ቢሊዮን ብር ወጪ ያስከትልበታል - የምንዛሬ አሠራር ስለተለወጠ ብቻ።
በሌላ አነጋገር፣ ዶላር ለመንግሥትም እጅግ ውድ ይሆንበታል። መንግሥት ቅድሚያ በሚሰጣቸው የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ “አዳዲስ ግንባታዎችን እጀምራለሁ፤ የማስፋፊያ ፕሮጀክቶችን እሠራለሁ” እያለ የውጭ ብድር የማምጣት ዐቅሙ ይዳከማል።
እንዲህ ሲባል ግን፣ ሙሉ ለሙሉ ከፕሮጀክቶችና ከውጭ ብድር ጋር ይቆራረጣል ማለት አይደለም።
የዓለም ባንክና የአፍሪካ ልማት ባንክ ከመሳሰሉ ተቋማት ጥቂት የፕሮጀክት ብድሮችን ማግኘቱ አይቀርም። ነገር ግን፣ አሁን አሁን የፕሮጀክቶቹ ባህርይም እየተቀየረ አይደል?
ድሮ ድሮ አብዛኛው ብድርና እርዳታ… የመንገድ ግንባታና የኤሌክትሪክ ግድብ ለመሳሰሉ ፕሮጀክቶች ነበር የሚውለው። ዛሬ ዛሬ ግን፣ ለምግብ ዋስትና… ማለትም ችግረኛ የገጠርና የከተማ ነዋሪዎችን ለመርዳት ነው ብድር የሚመጣው። አስቸጋሪ ነው። በብድር በልቶ ማደር! ወዴት እንደሚያደርሰን እንጃ።
የሆነ ሆኖ፣ የዶላር ጨዋታው “ከነባር የምንዛሬ ተመን” ወደ “አዲስ የምንዛሬ ገበያ” ሲለወጥ፣ “ነባር የኢኮኖሚ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎችም” ጊዜ ያልፍባቸዋል።
“ጥራት ያለው የቡና ምርት በአገር ውስጥ ገበያ ለመሸጥ የሞከሩ ነጋዴዎች በፖሊስ ክትትል ተያዙ፣ ንብረታቸው ተወረሰ” የሚሉ ዜናዎችን ታስታውሱ ይሆናል።
የራሳቸውን ምርት ወደ ገበያ አውጥተው ለመሸጥ ስለሞከሩ እንደ ሌባ ይቆጠራሉ። ውንጀላውማ ከዚህም ይብሳል። በአገር ኢኮኖሚ ላይ አሻጥር የሠሩ፣ የአገር ክህደት የፈጸሙ ያህል ነው የክስ መዓት የሚወራባቸው። ለምን እንደሆነ ይገባችኋል መቼም።
ያው፣ መንግሥት ዶላር ይፈልጋል። ማን የማይፈልግ አለ? ዶላር ተገኝቶ ነው! ሁሉም ይፈልጋል። መንግሥትም ዶላር ይፈልጋል። የመንግሥት ፍላጎት ግን ትንሽ ለየት ይላል። ጉልበት ይጨምርበታል። በምንዛሬ አሠራር ላይ አዲስ ሕግ ማወጅ፣ ደንብና መመሪያ አውጥቶ በጉልበት ማስፈጸም ይችላል። ራሱ ባወጣው የምንዛሬ ተመን የሰዎችን ዶላር ይወስዳል። ማን ከልካይ አለበት?
ጥራት ያለው የቡና ምርት እዚሁ መርካቶ ውስጥ ከተሸጠ መንግሥት ምንም ጥቅም አያገኝም። ቡናው ወደ ውጭ ከተላከ ግን ዶላር ይመጣል። ወደ ባንክ ይገባል። መንግሥት በገበያ ዋጋ ሳይሆን በራሱ የምንዛሬ ተመን ዶላሩን ይወስዳል - ለምሳሴ በ60 ብር ሒሳብ። ይህን እንዳያስቀሩበት ነው በኤክስፖርት ላይ ጥብቅ ቁጥጥር የሚያካሂደው።
አሁን ግን፣ መንግሥት የሰዎችን ዶላር መውሰድ ከፈለገ… ያው በገበያ ዋጋ መግዛት ይኖርበታል ተብሏል። በመቶ ምናምን ብር ሒሳብ መሆኑ ነው። ቡና ነጋዴዎች ምን ቸገራቸው? በገበያ ዋጋ የዶላራቸውን ምንዛሬ የሚያገኙ ከሆነ፣ የራሳቸውን ንብረት በድብቅ በአገር ውስጥ ለመሸጥ የሚሞክሩበት ምክንያት ብዙም አይኖርም። ከሸጡም… ያው በገዛ ንብረታቸው ማን ይከለክላቸዋል? ወርቅ አምራቾችም እንዲሁ!
መንግሥትስ፣ እንደ ድሮው የኤክስፖርት ዶላሮችን በአነስተኛ የምንዛሬ ተመን መውሰድ ካልቻለ፣ ለቁጥጥር መስገበገብ ምን ያደርግለታል?
ምናለፋችሁ! የምንዛሬ አሠራር ላይ የተደረገው ለውጥ ሁሉንም ነገር ይነካካል። እንዲህ ሲባል ግን፣ “በምንዛሬ ተመን” ምትክ የመጣው “የምንዛሬ ገበያ” ምን ዐይነት መልክ እንደሚኖረው ሙሉ ለሙሉ ይታወቃል ማለት አይደለም።
የምንዛሬ ገበያው ምን ያህል ለገበያ እንደሚለቀቅ ከወዲሁ እርግጡን መናገር ያስቸግራል።
“ማስተካከያ ሕጎችን”፣ “ማሻሻያ ደንቦችን”፣ “ማሟያ መመሪያዎችን”… በየጊዜው በቁጥ ቁጥ እያዘጋጁ ማምጣት የተለመደ ነው። በሳምንታት ውስጥ፣ ወይም በጥቂት ወራት፣ አለያም ከመንፈቅና ከዓመት በኋላ፣ የምንዛሬ ገበያው መልክና አሠራር ቀስ በቀስ እየተቀየረ ሊሄድ ይችላል። ፊቱ ወደ ግራ ይሁን ወደ ቀኝ፣ ወዴት አቅጣጫ እንደሚዞር መገመት ቢያስቸግርም፣… ሲውል ሲያድር፣ ብዙም ሳይቆይ፣ አንድ ሁለት እያሉ፣ የማሻሻያ አንቀጾችና ልዩ መመሪያዎች እንደሚመጡ ግን አትጠራጠሩ።
እንደ ሁኔታው ነው። በአንድ በኩል መንግሥት አሁኑኑ ከIMFና ከዓለም ባንክ ጋር መጣላት አይፈልግም። የለየት ጥል ይቅርና ኩርፊያም ጉዳት ይኖረዋል። በዶላር ዕጥረት ሳቢያ ከገደል አፋፍ ላይ የደረሰች አገር ምን ዐቅም ይኖራታል? ግንባራቸውን ከቋጠሩባት ምን ይውጣታል?
ለብድር የዘረጉትን እጅ እንደገና መልሰው ካጠፉ፣ ነገሩ ሁሉ “ፉርሽ” ይሆናል። ብድር ቢያቋርጡባት አይደለም ቢያዘገዩባትም እንኳ ትቸገራለች።
የተመደበውን ብድር እየወሰደች ካጋመሰች በኋላ፣… ለጊዜው ከዶላር ዕጥረት ትንሽ ፋታ ካገኘች፣… ከዓመት ከሁለት ዓመት በኋላ መንግሥት ምን ለማድረግ እንደሚወስን ማን ያውቃል? አሁን በጀመረው መንገድ “የምንዛሬ ገበያን” አጥብቆ መያዝና መቀጠል ይችላል። ከባድ ነው። ግን ይቻላል።
በሌላ በኩል ግን…. አዳዲስ ፕሮጀክቶችን መገንባት ሲያምረው፣ ዶላር ሲቸግረው፣ በጀት ሲያጥረው፣ በአነስተኛ የምንዛሬ ተመን ከባንኮች ዶላር መውሰድ ሊያሠኘው ይችላል።
ለይቶለት ወደ ምንዛሬ ተመን ባይመለስ እንኳ፣ “የገበያ ማሻሻያ ደንቦችን” ወይም “ጊዜያዊ አስቸኳይ መመሪያዎችን” ማወጅ አያቅተውም። ምክንያትና ሰበብ አይጠፋም። “አገራዊ ፕሮጀክቶች”፣ “ወሳኝ የኢኮኖሚ ዘርፎች”፣ “ድሀ ተኮር ምርቶች”፣ “ሕዝባዊ ጥያቄዎች”… በልዩ አሠራርና በልዩ ተመን የዶላር ኮታ የሚያገኙበት መመሪያ ቁጥር 1 ቁጥር 2 እያለ ማውጣት ይችላል።
መቼም IMFና የዓለም ባንክ… “የምንዛሬ ገበያ ተነካ፣ ተጣሰ” ብለው ወዲያውኑ እንደማይጣሉት ቢያስብ ቢገምት ብዙም አይገርምም። ትችትና ቅሬታ ይሰነዝሩ ይሆናል። ለማኩረፍ ግን ጊዜ ሊፈጅባቸው ይችላል።
መንግሥት በዚህ ግምት ተማምኖ፣ የምንዛሬ ገበያውን ቀስ በቀስ ወደ ቀድሞው የምንዛሬ ተመን እያንሸራተተ ለማስጠጋት ቢሞክር ማን ይመልሰዋል? እንዲያውም “ሚዛኑን የጠበቀ የምንዛሬ ሥርዓት” የሚል የሙገሳ አስተያየት ሊቀርብለት ይችላል።
ችግሩ ምንድነው? የተቀየጠ የተቃወሰ የምንዛሬ ሥርዓት ሆኖ ሊያርፈው ይችላል።
ከሆነ አይቀር፣ “የገበያ ምንዛሬ” ብለው ከጀመሩት አይቀር፣ ያንኑን እያጣሩና ቅጥ አያስያዙ ለመጓዝ መጣር ይሻላል። በእርግጥ ዋናው ትኩረት ለሥራ የተመቸ አገርና ሥርዓት የመፍጠር ጉዳይ ነው። ኢንቨስትመንት እየተስፋፋ ኤክስፖርት የሚያድግበት ጸዳ ሥርዓት ነው ዋናው ቁም ነገር። እንደ አያያዛችን ሆነ ግን፣ ሁለመናችንን በጦርነት የተጠመደ ነው የሚመስለው። ጸዳ ያለ ሥርዓት ይቅርና አገርን ማረጋጋትና ሰላምን በወጉ መፍጠር አቅቶናል።

አንድ ተረት አለ። የኢንዶኔዢያ ሳይሆን አይቀርም።
አንዲት የመንደሩ ሰው ንብረት የሆነች በግ አልፋፋ ብላ ህዝቡ ሲጨነቅ፤ ሹሙ አዩና፤ ወደ አደባባዩ መጥተው፤ በውይይት መልክ፤ በኃይለ-ቃል ጠየቁ።
"ምንድን ነው ለዚች በግ ያስጨነቃችሁ"
የህዝቡ ተወካይም፤
"ማሳደግ አቃተን። ግጦሹ ተወደደ። የአራዳው ዘበኛ ያገኘችውን  እንድትግጥ እድል አልሰጥ እያለ አለንጋ ያቀምሳታል። እንዳናርዳት አልሰባች፣ እንዲሁ እንዳንተዋት ጣጣዋ ተረፈን! እንዲያው ምን ይመክሩናል ሹም ሆይ?"
ሹሙም፤
"ለምን እኔ ግቢ መጥታ አትፋፋላችሁም?" ሲሉ፤ ጫን ብለው ጥያቄውን በጥያቄ መለሱ። መቼም ሹም ናቸውና የሹም ጥያቄ በአሉታ አይመለሰም። ከፊሉ ህዝብ ጭጭ አለ። ከፊሉ እሺም እምቢም ማለቱ በማይገባ ቋንቋ ራሱን ነቀነቀ። ጥቂቱ "ይሁን፤ እንደርሶ ግቢ የሚመች የት ይገኛል። ግቢዎስ ግቢያችን አይደለም ወይ?!" አላቸው።
በጊቱ ሹሙ ግቢ ገባች።
ጊዜ እየገፋ መጣ። በጊቱ ግን አልወፈረችም። ጭራሽ እየከሳች መጣች። ህዝቡ ወደ ሹሙ ግቢ አሻግሮ እያየ "ኧረ እቺን በግ አክስተው ሊገድሏት ነው፤ ጎበዝ?" እያለ በየመንደር መናኸሪያው ያጉተመትማል። ደፈር ያለም ሹሙን ወይም ባለሟሎቻቸውን ይጠይቃል። በተለያየ ጊዜ የተለያየ መልስ ያገኛል።
አንዴ፤ "የቤተ መንግሥት አጥር እየታከከች እየዋለች ስላስቸገረች ግጦሽ ተከልክላ ነው" ይባላል።
አንዴ ደግሞ፤ "የንጉሥ ማሳ ገብታ በአፈ-ላማ ተያዘች" ይባላል፤
"አሞሌ ሲሰጧት የቀላቢዋንም እጅ ልሼ ካልበላሁ እያለች አስቀየመችውና ተቀጣች" ይባላል። ደሞ ሌላ ቀን፤ እንዳጋጣሚ ደግሞ ባለሟል ይመጣና እውነቴን ያወጣል፤ "አፏን ሸብበው ሳር-ማሳ እየከተትዋት እንዴት ትወፍር። በዚያ ላይ ከወፈረች የጠገበች ትመስላለች፤ የህዝብ ሀብት ስለሆነች እንደከሳች ብትቆይ ምን አለበት?  ትባላለች" ይላል።
ሌላ ውስጥ አዋቂ ይቀጥላል። "በተጨማሪም ደግሞ ከሌሎች በጎች ጋር ሲያዩዋት ታረግዝብናለች፣ "ወንድ" የወለደች እንደሁ ኋላ ምን ሊባል ነው፤ ሲሉ ነበረ" ብሎ ያጋልጣል። ጨመር አድርጎም፤ "ጎረቤትና የሩቅ አገር ሰው ሲመጣ ዐይን ትገባለች ብለው ገመድ ሆዷ ላይ ያስሩባታል" ብሎ ሚስጥር ያወጣል።
እንዲህ እንዲህ ስትባል፤ ቀን ገፋ። በሹሙ በኩል ያልፍልሻል፤ አይዞሽ ትጠግቢያለሽ፣ ስትባል፤ ህዝቡ በበኩሉ፣ ዘንድሮስ እንጃላት ሲላት፣ ገናን አለፈች። ፋሲካ ደረሰ።
ህዝቡ ከእንግዲህ መበያዋ ደረሰ ሲላት፣ ገናን አለፈች። ፋሲካ ደረሰ።
ህዝቡ እንግዲህ መበያዋ ደረሰ በቃ አለና አንገቱን ደፋ።
ይሄኔ አንድ ሽማግሌ የመጣው ይምጣ በሚል ድፍረት፤ ወደ ሹሙ ባለሟሎች ሄደው፤
"ኧረ እቺን በግ ሹሙ አክስተው ሲገድሏት ነው። መቼ ሊበሏት ነው?" ሲሉ ጠየቁ።
የባለሟሎቹ ተወካይም፤
"ገና ንጉሥ ፊት ቀርባ፤ አክሷት ባሉበት አፋቸው፣ ብሏት ያሉ እንደሆነ ነዋ!" አላቸው።

እንደ ከሲታዋ በግ ማደግ ያቃተው ዲሞክራሲያችን ያልታደለ ነው። እንደልብ ግጦሽ ሳር ማጣት የምስኪንነት ጥግ ነው። ደህና ግቢ ይግባ ሲባል በአፈ-ላማ ተይዞ፣ በቅጣት ታጥሮ፣ ግጦሽ ተከልክሎ፤ አፉ ተሸብሽቦ፣ ከተራበ አደጋ ነው ተብሎ፣ በJamming ታፍኖ፣ ከውጪ ሰውም ተከልክሎ… ከቶውንም ሊዘልቅ አይችልም። የፕሬስ ነፃነት "የተከለከለ የበሰለ ፍሬ" በሆነበት ቦታ የዲሞክራሲ ህልውና ቀርቶ ሽውታውም አይታሰብም።
በሀገራችን እንደ ምስኪኗ በግ የሆኑ ብዙ ጥያቄዎች አሉ። ከዛሬ ነገ ይመለሳሉ ሲባል ጭራሽ "እነዚህ ጥያቄዎች የእኛ አልነበሩም እንዴ?" እስከሚባል ድረስ ከኦርጅናሌ ባለቤታቸው እጅ ይወጣሉ። የሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ጥያቄዎች፣ በተለይም ደግሞ የፕሬስ ነጸነት ጥያቄ፣ ከከሲታዋ በግ በበለጠ እሰው ግቢ ገብቶ ቀልጦ የቀረ ይመስላል። ሰሚ ጆሮ፣ አዛኝ አንጀት ያገኘ አይመስልም። ይልቁንም "ጎራዴን እጀታውን የያዘ ያሸንፋል" የተባለው አነጋገር ዛሬ ከምንም ጊዜ የበለጠ ሚዛን ያነሳው በሱው ሰበብ ነው። "ስለቱን የያዙ ቢንጠለጠሉበት እጃቸውን ማጣት ይሆናል ዕጣ-ፈንታቸው። "ከእጃችን በቀር የምናጣው ነገር የለም" ካላሉ በቀር። ( We have nothing to lose except our chains እንዲሉ)
የተሄደበት መንገድ ሁሉ ወደዚያው ወደተነሳበት የሚመልሰን ከሆነ "ነገር ቢኖራችሁ ነው እንጂ፣ የማለዳው መንገድ ጠፍቶባችሁ ነው ወይ?" ያሰኛል።
አንድ ዘመን የአዲስ አበባ ሰው የኮክቴል ድግስ ሲጠራ ጠብ የሚልለት ነገር ሳይኖር በባዶ ሆዱ ዘፈን ብቻ እየሰማ፣ ሠርግ አጅቦ መመለሱ ልማድ ሲሆንበት "የድጋፍ ሠልፍ" የሚል ስም አውጥቶለት ነበር አሉ።
ለአሳታፊ ዲሞክራሲ ቁልፉ ግትርነት የሌለበትና "ስሜት ያልተጫጫነው" ውይይት ለማካሄድ መቻል ነበር ቢያድለን፤ ሆኖም ነገራችን ሁሉ "ቤቴን ሠርቼ ጣራ ስመታ ሆነ እንጂ ምክራችሁስ የሚወድቅም ነገር አልነበረው" ያለው ጮሌ ቤተ-ሰሪ ዓይነት ሆነ።
"ለዲሞክራሲያዊ ውይይቱ" ሁሉ የጦር ስትራቴጂ አውጥተን፣ አንዘልቀውም ብሎ ማሰብ የአባት ነው። ረዥምና ዘላቂ በሚመስለን ዕድሜያችን ውስጥ ምን እንደሚያጋጥመን ሳናውቅ የተከለከለ መንገድ፣ የተዘጋ በር፣ የታጠረ አዕምሮ፣ የተሸበሸበ አፍ፣ በጓጉንቸር ሽቦ የተለጠፈ ብዕር ይዞ ለሰላም፣ ለዲሞክራሲ፣ ለነፃነትና ለፍትህ የቆመ ፕሬስ ማለም፣ የማለም "ነፃነት" እንጂ የፕሬስ ነፃነት አይሆንም። ማለምም ተበርትቶ- መተኛት ከተቻለ ነው። ከቶውንም በስርጥ  መንገድም መጣ በቀለበት መንገድ፣ በአውራ  ጎዳናም መጣ በመጋቢ መንገድ፣ እንደብራ መብረቅም መጣ እንደ ነጎድጓዳማ ዶፍ፤ "ዝናብና አዋቂ ሲመጡ ያስተውላሉ" ነውና ዓይኑን ለከፈተ ዜጋ የቀጭን ትዕዛዛት አመጣጥ ይታየዋል። "ገና ንጉሥ ፊት ቀርባ አክሷት ባሉበት አፋቸው፣ ብሏት ያሉ እንደሁ ነዋ" እንደተባለችው በግ የመሆን ሥጋት ለተጋረጠበት የሀሳብ ነፃነት፤
"አቤት በሰማይ ያለ ምፅአት
አቤት በምድር ያለ መዓት" ቢለው፤ "የት አየኸው?"፣ "አመጣጡን መች አጣሁ" የሚለው ተረት ወቅታዊ ሆኗል። ከሁሉም ይሰውረን።



በገበያ ላይ ተመስርተው የውጭ ምንዛሪ በጥሬ ገንዘብ መሸጥና መግዛት የሚፈልጉ የግል የውጭ ምንዛሪ ቢሮዎች እንዲቋቋሙ በተፈቀደው መሰረት፣. ከሰሞኑ ብሔራዊ ባንክ የሥራ  ፈቃድ መስጠት ጀምሯል፡፡
ፈቃዱን ለማውጣት ዝቅተኛ 15 ሚሊዮን ብር ካፒታልና በዝግ በየትኛውም ባንክ የተቀመጠ 30 ሚሊዮን ብር ያስፈልጋል ተብሏል።
ባንኩ፤ “የግል የውጭ ምንዛሪ ቢሮዎች መቋቋም የውጭ ምንዛሪ ገበያን መሠረት ለማስፋትና ለማጠናከር እንዲሁም የውጭ ምንዛሪ በጥሬ ገንዘብ ለመሸጥም ሆነ ለመግዛት የሚሹ ደንበኞችን ፍላጎት ለማርካት እንደሚረዳ እሙን ነው" ብሏል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ አቶ ማሞ ምህረቱ፣ “የግል የውጭ ምንዛሪ ቢሮዎች እንዲከፈቱ የሥራ ፈቃድ መስጠታችን የኢትዮጵያን የፋይናንስ ዘርፍ ለውጭ ኢንቨስትመንት ለመክፈትና ዘርፉን በቀጣይ ዓመታት ከዓለም ምርጥ ተሞክሮዎችና አሠራሮች ጋር የተመጣጣነና ተወዳዳሪ ለማድረግ የጀመርነውን አዲስ ምዕራፍ እንዲሁም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የጀመረውን ስትራቴጂካዊ የሆነ ለውጥ ከግብ ለማድረስ በቁርጠኝነት መነሣሣቱን የሚያመለከት ነው” ብለውታል።
በአፍሪካና በሌሎች ዓለማት  የግል የውጭ ምንዛሬ ቢሮዎች  አገልግሎት እንደሚሰጡ የሚታወቅ ሲሆን፣ እነዚሁ ቢሮዎች የራሳቸው ጥቅሞች እንዳሏቸው ባለሞያዎች ይናገራሉ። እንደምጣኔ ሃብት ባለሞያዎች ገለጻ፣ የግል ምንዛሬ ቢሮዎች ብዙውን ጊዜ ከባንኮች የተሻለ የምንዛሬ ዋጋ መስጠታቸው፣ ምቹ ቦታዎችን በመምረጥ ያለ ቢሮክራሲያዊ መዘግየት  ምንዛሬ መለዋወጥን ማስቻላቸው ተመራጭ ያደርጋቸዋል፡፡
የምንዛሬ ዋጋዎች በፍጥነት ሊለዋወጡ ስለሚችሉ፣ እነዚህ ቢሮዎች ትርፋማነትን ለማስጠበቅ አደጋዎችን በብቃት መቆጣጠር እንዳለባቸው የሚናገሩት  ባለሞያዎች፣ ከውድድር ባለፈ በደንበኞቻቸው ዘንድ ተዓማኒነትን የማትረፍ የቤት ስራ አለባቸው ይላሉ፡፡ ከፍተኛ የአገልግሎት ክፍያዎችን የመጠየቅ፣ የቁጥጥር ማጣት፣ ተለዋዋጭ የምንዛሬ ተመኖችን ማውጣታቸውና ለማጭበርበር ወንጀል ክፍት መሆናቸው ከእነዚሁ ቢሮዎች ጉዳቶች ጥቂቶቹ መሆናቸው በምጣኔ ሃብት ባለሞያዎች ይነገራል። ደንበኞች ላደረጉት የምንዛሬ ልውውጥ በቂ ደረሰኝ ስለማያገኙ ለመጨበርበር ሊዳረጉ እንደሚችሉም ነው የተነገረው።
ናይጄሪያ፣ ኬንያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ግብጽና ጋናን  ጨምሮ በተለያዩ የአፍሪካ አገራት የግል የምንዛሬ ቢሮዎች አገልግሎት እንደሚሰጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

“ይህን ህገ ወጥ እንቅስቃሴ እንታገለዋለን”


የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ “ይካሄዳል” ከተባለው የህወሓት ድርጅታዊ ጉባዔ ራሳቸውን እንዳገለሉ አስታውቀዋል። አቶ ጌታቸው ይህን ያስታወቁት ለህወሓት ሊቀ መንበር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል (ዶ/ር) እና የፓርቲው ማዕከላዊ ቁጥጥር ኮሚሽን ሊቀ መንበር አቶ ተክለብርሃን አርአያ ትናንት በጻፉት ደብዳቤ ነው።
አቶ ጌታቸው “ከወራት በፊት ጉባዔውን ለማካሄድ ያቋቋምነው ኮሚቴ ከድርጅታችን መርህ እና አሰራር ወጥቶ በጥቂት ሰዎች ስለተጠለፈ፣ የማዕከላዊ ቁጥጥር ኮሚሽን ራሱን ከኮሚቴው አግልሏል” በማለት የኮሚሽኑን ዕርምጃ አውስተው፣ በዞን እና በወረዳ ደረጃ በርካታ አመራሮችና አባላት ከጉባዔው ራሳቸውን ማግለላቸውን ጠቅሰዋል። በዚህም የህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ ድርጅታዊ ጉባዔ መቼ እና እንዴት እንደሚካሄድ አንድ ዓይነት አተያይ አለመኖሩን ያነሱት አቶ ጌታቸው፣ “ቅጥ የጎደለው” ያሉት እንቅስቃሴ ሕዝብን እና ድርጅታቸውን ወደ አደጋ የሚከት መሆኑን አመልክተዋል።
ፕሬዝዳንቱ በደብዳቤያቸው “የድርጅታችንን አሰራር እና አወቃቀር በመጣስ፣ አንድ አካል የራሱን ጠባብ ጥቅም ለማስጠበቅ በማሰብ ድርጅታችንን ወደማይወጣበት አደጋ ለመክተት እየጣረ ነው።” በማለት ስሞታቸውን አቅርበዋል። ይሁንና ስለዚሁ አካል ግልጽ መረጃ ከመስጠት ተቆጥበዋል።
ማዕከላዊ ኮሚቴው በአዲሱ የምርጫ ቦርድ ዓዋጅ መሰረት፣ የተጭበረበረ እና ያልተፈረ ሰነድ ለቦርዱ ማቅረቡ “ተራ ስሕተት አይደለም” የሚሉት አቶ ጌታቸው፤ “የትግራይን ሕዝብ ትግል እና ድርጅቱን ለማፍረስ ሆነ ተብሎ የሚሰራ ቡድናዊ ዕንቅስቃሴ ነው” ብለዋል።
“ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቀረበው የዕውቅና ጥያቄና በህወሓት ስም የሚደረገው የጉባዔ ዝግጅት በአንድ ቡድን የሚደረጉ ሕገ ወጥ እንቅስቃሴዎች በመሆናቸው ራሴን ከጉባዔው አግልልያለሁ” ሲሉ በጻፉት ደብዳቤ አትተዋል፤ አቶ ጌታቸው። አክለውም “እየተደረገ ነው” ያሉትን ዕንቅስቃሴ ለመታገል ዝግጁ መሆናቸውን አስታውቀዋል።
ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ድርጅታዊ ጉባዔውን ባለፈው ሐምሌ ወር መጨረሻ እንደሚያደርግ በሊቀ መንበሩ በደብረጽዮን ገብረሚካኤል (ዶ/ር) በኩል ቢገለጽም፣ እስካሁን ጉባዔው አልተካሄደም። ነገር ግን በዞን እና በወረዳ ደረጃ የካድሬዎች እና የከፍተኛ አመራሮች የድርጅታዊ ጉባዔ ዝግጅት ውይይቶች እየተደረጉ ነው። ለአቶ ጌታቸው ረዳ ደብዳቤ፣ ከህወሓት በይፋ የተሰጠ ምላሽ የለም።

የአክሱም ከተማ አስተዳደር ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ ገብረመድህን ተስፋይ፣ የግድያ ሙከራ እንደተፈጸመባቸው ተገልጿል። የግድያ ሙከራው የተፈጸመባቸው ባለፈው ዕሁድ ሐምሌ 28 ቀን 2016 ዓ.ም. ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ላይ እንደነበርም ተጠቁሟል።
የከተማዋ የሕዝብ ግንኙነት ጽሕፈት ቤት በይፋዊ የማሕበራዊ ትስስር ገጹ እንዳስነበበው፣ አቶ ገብረመድህን ቀን ላይ ከባልደረቦቻቸው ጋር ስራቸውን ሲያከናውኑ ከቆዩ በኋላ፣ ወደ መኖሪያ ቤታቸው በመመለስ ላይ ሳሉ ነበር የግድያ ሙከራው የተፈጸመባቸው። ሃላፊውን ከጀርባ ሆነው ሲከታተሉ የቆዩ ግለሰቦች፣  ወደ መኖሪያ ቤታቸው መግባታቸውን ተከትሎ ሁለት ጊዜ ጥይት በመተኮስ የግድያ ሙከራውን እንደፈጸሙባቸው ተናግሯል።
የግድያ ሙከራውን ፖሊስ እያጣራ መሆኑ ሲነገር፣ ድርጊቱን ፈጻሚዎች በቅርቡ በቁጥጥር ስር እንደሚውሉም የአክሱም ከተማ አስተዳደር አመልክቷል። ይሁንና በጉዳዩ ዙሪያ ማብራሪያ ለማግኘት  በተደጋጋሚ ጥረት ብናደርግም፣ ሊሳካ አልቻለም።
በሌላ በኩል፣ በደቡብ ትግራይ የህወሓት ፕሮፓጋንዳና ቅስቀሳ ሃላፊ አቶ ዳንኤል ሃጎስ ሐሙስ ነሐሴ 2 ቀን 2016 ዓ.ም. በጸጥታ ሃይሎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች አስታውቀዋል። እንደ ምንጮቹ ገለጻ ከሆነ፣ አቶ ዳንኤል ለእስር የተዳረጉት አሮጌና የወዳደቁ የጦር መሳሪያዎችን በመሸጥ ተጠርጥረው ነው ተብሏል።
አቶ ዳንኤል በቁጥጥር ስር የዋሉት በትግራይ ክልል፣ ማዕከላዊ ዞን፣ ማይጨው ከተማ ላይ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል።
በተመሳሳይ ቀን፣ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ዕቅድና ፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ ምሕረት በየነ (ዶ/ር)ን ጨምሮ አምስት ሌሎች የመንግስት ባለስልጣናት በቁጥጥር ስር መዋላቸው ተጠቁሟል። እነዚህ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር የዋሉት ከ52 ሚሊዮን ብር በላይ የተገዛ ጥራት የሌለው ንብረት እንዲሰራጭ አድርገዋል በሚል ጉዳይ ተጠርጥረው መሆኑን ምንጮች ተናግረዋል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኮሙኒኬሽን ቢሮ ለስድስተኛ ዙር “የምትተክል አገር፣ የሚያጸና ትውልድ” በሚል መሪ ቃል እየተካሄደ የሚገኘው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አንድ አካል የሆነ የችግኝ ተከላ ስነ ስርዓት ዛሬ በእንጦጦ ፓርክ አከናውኗል። በስነ ስርዓቱም የቢሮው ሃላፊ ወይዘሮ እናትዓለም መለሰ፣ በአዲስ አበባ ምክር ቤት የሴቶችና ሕጻናት የማህበራዊ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ ዘይነባ ሽኩር እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው ታዋቂ ግለሰቦች፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ ከማዕከል እስከ ወረዳ የሚገኙ የኮሙኒኬሽን አመራሮችና ሰራተኞች መሳተፋቸው ተገልጿል።
ስነ ስርዓቱን በንግግር ያስጀመሩት ወይዘሮ እናትዓለም መለሰ፣ ታላላቅ ሃሳቦችን ስለሚያነሱ ግለሰቦች እና የእነርሱን ፈለግ ሲለሚከተሉ ወገኖች በማውሳት፣ የአረንጓዴ አሻራን ሃሳብ ማሰራጨት እንደሚገባ በአጽንዖት ገልጸዋል። ለስነ ስርዓቱ ተሳታፊዎች "አምና አብራችሁን ነበራችሁ። ምን ያህል ሃሳብ እንዳሰራጨን ሳይሆን እንደተከልን ታስታውሳላችሁ" ሲሉ ተናግረዋል።
ሃላፊዋ አክለውም፣ አገር በቀል ችግኞችን የመትከልን አስፈላጊነት ዘርዝረው፣ "ችግኞቹ የራሳቸው ታሪክ አላቸው። እናንተ ስትተክሏቸው ደግሞ በሚሊዮን የሚቆጠር ቶን ታሪክ ይኖራቸዋል።" ብለዋል።
በዚሁ ስነ ስርዓት ላይ አገር በቀል ችግኞች በብዛት የተተከሉ ሲሆን፣ ለአዲስ አድማስ አስተያየታቸውን የሰጡ የስነ ስርዓቱ ተሳታፊዎች ችግኝ በመትከላቸው ዕርካታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል። ታዋቂው ተዋናይ እና የማስታወቂያ ባለሞያ ጥላሁን ጉግሳ እጅግ በጣም የጠለቀ ደስታ እንደተሰማው በመጠቆም፣ “ባለፈው ዓመት ‘ለነገ ዛሬ እንትከል’ ብለን ነበር። ያ ነገ ዛሬ ሆኖ ችግኝ ለመትከል በቅተናል። ይህንን ስራ አጥብቀን መያዝ ይኖርብናል።” በማለት ለአዲስ አድማስ ተናግሯል።
አያይዞም፣ እርሱ ለ12 ዓመታት ያህል በትወና እና በአዘጋጅነት የሚሳተፍበት “ቤቶች” የተሰኘው ሲትኮም ድራማ ላይ ስለአረንጓዴ ልማት መልዕክቶች ሲተላለፉ መቆየታቸውን አስታውሶ፣ የድራማው ተሳታፊ ባለሞያዎች ለ12 ዓመታት የችግኝ ተከላ እና እንክብካቤ ስራ ሲሰሩ መቆየታቸውን አስረድቷል።
ጋዜጠኛ ሽመልስ ለማ በበኩሉ፣ በዚህ ስነ ስርዓት ላይ በመሳተፉ ከልብ የመነጨ ደስታ እንደተሰማው ገልጿል። በተጨማሪም፣ ይህ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን አረንጓዴ ልማት እያሳደገ እንደሚገኝ አመልክቷል። ሁሉም ወገን በዚህ መርሃ ግብር እንዲሳተፍ ጋዜጠኛ ሽመልስ ጥሪውን አቅርቧል።
 
 
 
 
 
 
 
 

 

 

ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሕጋዊ ሰውነት ተሰጥቶታል። ፓርቲው ሕጋዊ ሰውነት የተሰጠው በተሻሻለው የፖለቲካ ፓርቲዎች ዓዋጅ መሰረት እንደሆነም ተነግሯል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዛሬ ባወጣው መግለጫ፤ ህወሓት ሚያዚያ 13 እና 28 2015 ዓ.ም. ሕጋዊ ሰውነቱ ወደነበረበት እንዲመለስ ጥያቄ አቅርቦ እንደነበር በማስታወስ፣ በዓዋጅ ቁጥር 1162/2011 መሰረት የቀድሞውን የፓርቲ ሕልውና መመለስ እንደማይቻል የሚገልጽ ውሳኔውን ግንቦት 4 ቀን 2015 ዓ.ም. ለፓርቲው ማሳወቁን አውስቷል፡፡

የተሻሻለው ዓዋጅ ቁጥር 1332/2016 በዓመጽ ተግባር ተሰማርቶ ለተሰረዘ ፓርቲ "የቀድሞ ሕልውናውን መልሶ የሚሰጥ የሕግ ድንጋጌ ያልያዘ" በመሆኑ በድጋሚ የቀረበለትን ጥያቄ አለመቀበሉንም ጠቅሷል።

በተሻሻለው ዓዋጅ አንቀጽ 2፣ ንዑስ አንቀጽ 1 መሰረት፣ ፍትሕ ሚኒስቴር ሰኔ 17 ቀን 2016 ዓ.ም. ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በጻፈው ደብዳቤ፣ ህወሓት ሃይልን መሰረት ያደረገ የአምጽ ተግባሩን በማቆም ሕገ መንግስታዊ ዲሞክራሲያዊ ስርዓትን አክብሮ ለመንቀሳቀስ መስማማቱን በመጥቀስ፣ በልዩ ሁኔታ እንደ ፖለቲካ ፓርቲ እንዲመዘገብ ለቦርዱ ማረጋገጫ መስጠቱን አንስቷል። ህወሓት በበኩሉ፤ የፖለቲካ ፓርቲ ፕሮግራም፣ መተዳደሪያ ደንብ፣ የፓርቲ ሃላፊዎች ስምና ፊርማ የያዘ ሰነድ ለቦርዱ አቅርቧል።

በሰነዶቹ መሰረት ቦርዱ፣ ህወሓት እንደፖለቲካ ፓርቲ እንዲመዘገብ ውሳኔ ያሳለፈ ሲሆን፣ ለፓርቲው የሚሰጠው የሕጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ "በልዩ ሁኔታ" የሚል ቃል ያለበት እንደሚሆንም ነው ያመለከተው። ህወሓት በልዩ ሁኔታ የመመዝገብ ውሳኔን የያዘው ደብዳቤ በደረሰው በስድስት ወራት ውስጥ ታዛቢዎች በተገኙበት ጠቅላላ ጉባዔ እንዲያደርግ፣ የመተዳደሪያ ደንቡን እንዲያጸድቅና አመራሮቹን እንዲያስመርጥ ወስኗል።

አፍታሜይራ ግሩፕ 25/75 የቤት ብድር መጀመሩን አስታወቀ። ድርጅቱ ዛሬ በስካይላይት ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ በግንባታ ላይ ያሉ ሳይቶችን ለሽያጭ ማቅረቡን ገልጿል።

የአፍታሜይራ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አሚራ አብዱልዋሃብ ተቋሙ ላለፉት ስምንት ዓመታት በኤክስፖርት፣ ኢምፖርት እና ሪልእስቴት ዘርፎች ተሰማርቶ መቆየቱን በማስታወስ፣ አሁን በአዲስ አማራጭ ለቤት ገዢዎች ብድር ማቅረቡን ተናግረዋል። የቤቶቹ ግንባታ እየተከናወነ የሚገኘው በለቡ መብራት፣ በጎፋ እና በቦሌ ቡልቡላ በሚገኙ ሳይቶች ላይ እንደሆነ ዋና ስራ አስፈጻሚው አብራርተዋል።

የተቋሙ ምክትል ስራ አስፈጻሚ አቶ ፍሬው ወንድሙ በበኩላቸው፣ በተለያዩ የግንባታ አሰራሮችን ተጠቅሞ ከብራይት የብድር እና ቁጠባ ተቋም ጋር በመቀናጀት የ25/75 የቁጠባ አማራጭ ማቅረቡን ገልጸዋል። አያይዘውም፣ 5 ደረጃ አንድ ኮንትራክተሮች በግንባታው ሂደት ሲሳተፉ፣ እያንዳንዱ ኮንትራክተር ሁለት ሕንጻዎችን የመገንባት ሃላፊነት እንዳለበትም ጠቁመዋል።

እንዲሁም ቤት ገዢዎች አጠቃላይ የግንባታ ሂደቱን የሚከታተሉበት አግባብ መኖሩን ያስታወቁ ሲሆን፣ የፕሪፋብ፤ የመደበኛ እና የፕላስቲክ ፎርምዎርክ የግንባት ስልቶች ተግባራዊ እንደሚሆኑ ነው የጠቀሱት።

"በምንዛሬ አሰራር ላይ ለውጥ እንደሚኖር እናውቅ ነበር። ጊዜውን ጠብቀን ነው የመጣነው።" ያሉት አቶ ፍሬው፣ ተቋማቸው ላለፉት አምስት ዓመታት የሪልእስቴት ሕግ በነጻ እንዳማከረ አስረድተዋል።

በተጨማሪም፣ "Ethio Addis Estate" የተባለ ድረ ገጽ ወደ ስራ እንደገባ እና 1 ሺህ 500 ሪልእስቴቶች በድረ ገጹ ላይ እንደተካተቱ አብራርተዋል። በአፍታሜይራ ግሩፕ ስር 15 ፕሮጀክቶች በዕቅድ እንደተያዙ በመግለጽ፣ "ሁለቱን ግን እናስቀድማለን" ብለዋል። እንዲሁም "ወደ ካፒታል ገበያ የመግባት ዕቅድ አለን" ሲሉ ተናግረዋል፣ አቶ ፍሬው።

25 በመቶ ከቤት ገዢዎች፣ በብራይት ብድርና ቁጠባ ተቋም በከፈቱት የራሳቸው አካውንት ተቀማጭ የሚደረግ ገንዘብ ሲሆን፣ በስድስት ወር ጊዜ ውስጥ መቆጠብ ይኖርባቸዋል። ይኸውም ቁጠባ የወለድ ምጣኔው ከ14 ነጥብ 5 በመቶ እስከ 15 ነጥብ 5 በመቶ ይደርሳል። ደንበኞች የሶስትዮሽ ውል አካልና ውሉን የሚዋዋሉት ከብራይት ብድርና ቁጠባ ተቋም ጋር እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል።

75 በመቶ የሚሆነው ብድር ደግሞ በተለያዩ የመያዣ አማራጮች ብራይት ብድርና ቁጠባ ተቋም እንደሚያቀርብም በዚሁ ጋዜጣዊ መግለጫ ተነግሯል።

የቢትወደድ ዘውዴ ገብረ ሕይወት ግለ-ታሪክ ሲመረቅ በልጃቸው ጥያቄ መሰረት ተጋብዘው የነበሩ አንድ አንጋፋ የሀገራችን ምሁር ይሄን በማለት የሰውዬው የህይወት ታሪክ መጽሐፍ ለሌሎችም አብነት መሆን እንደሚገባው ለማስረዳት ሞክሩ፤… [አበሾች ዘንድ ስለ ግለታሪክ ህይወታችን የመጻፍ ልምድ ባለመኖሩ ታሪክ በእጅጉ ይጎዳል፡፡ ፈረንጅ ለአንድ ትንሽ ነገር ትልቅ መጽሐፍ ይጽፋል፤ ሀበሻ ተራራ የሚያህል ታሪክ ይዞ መቃብር ይወርዳል፡፡]
የኛ ታላላቆች ያለፉበትን ታሪክ ለመጻፍ የመቸገር ጣጣ እዚህች አጭር አረፍተ ነገር ውስጥ ተጠቃሎ በምልአት ተገልጧል ማለት ይቻላል፡፡ አዎን! ታሪክ ውቅያኖስ ነው፡፡ ባህር አይለይም፣ ገባር ኩሬዎችን አይመርጥም፡፡ ባደጉ ሀገሮች ደግ የሰራ ሰው ብቻ ሳይሆን ክፉ የሰራ ግለሰብም ቢሆን ታሪኩ ይጻፋል፡፡ አዶልፍ ሄክማን ይቆየንና፤ ሂትለር ሁለተኛ የአለም ጦርነትን ከመቀስቀሱም ባለፈ ብዙ ሚሊዮኖችን በግፍ ገድሏል፡፡ ይሁንና በሱ ላይ አያሌ የታሪክ መጻሕፍት ከትላንት እስከ ዛሬ ተከትቧል፡፡ በሀገራችንም በተመሳሳይ ባይሆንም እንኳን በግፍ ግብራቸው የንጹሀንን እንባ ያፈሰሱ፤ አያሌ ባለቱባ ታሪክ ባንዳዎችን በዝርዝር መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከዚህ አንፃር የነሱ ታሪክ ታስሶ መፃፍ አልነበረበትምን? ሌላው ቀርቶ የደርጉን ሳዲስት፣ (ሳዲሰቶች ሌሎች ላይ በሚፈጽሙአቸው የጭካኔ ድርጊቶች ደስታን የሚያገኙ ሰዎች ናቸው፡፡) ‹‹አብዮታዊ ውሳኔ›› በሚል ስም የስንት ምስኪንና ንጹሃን የሆኑ ኢትዮጵያውያንን ህይወት የቀጠፈው ግርማ ከበደ፣ ታሪኩን በቁንጽል ካልሆነ በስተቀር በዝርዝር ሰንዶ ማን አቆየልን! መቼ አነበብነው - የት ተማርንበት - ማንንስ አስተማርንበት - ትውልድ ለመቀጣጫ እንዲያውቀውስ ለምን አላደረግነውም? በወቅቱ ሰዎች ከፍርድ ቤት ውጭ በደርግ ውሳኔ፤ በቀበሌ ፍርድ ሸንጎ ውሳኔ፣ በአብዮትና በዘመቻ ኮሚቴ ፍርድ እንደ ቀልድ ይገደሉ ነበር፡፡ ከፍርድ ቤት ውጭ የሚወሰኑት፣ የሚወሰዱት የእስራትና የግድያ እርምጃዎች ደግሞ አብዮታዊ ውሳኔ ይባሉ ነበር፡፡ እንግዲህ ግርማ ከበደ ሰዎችን የገቡበት ገብቶ አድኖ የሚገድል ሊቀመንበርና የደርግ ካድሬ ነበር፡፡ የጭካኔውን ደረጃ ቃላት የሚገልጹት አይደሉም፡፡ ሰውዬው እንኳን በግንባር ታይቶ ስሙም ሲጠራ ያስፈራል፣ ያስበረግጋል፡፡ የቅርብ ጓደኞቹንና በትምህርት ቤት ወይንም በስራ ቦታ የሚያውቃቸውን ነገር ግን በራሱ ምክንያት የማይወዳቸውን ሰዎች አጋጣሚውን ተጠቅሞ እንደገደላቸው፣ አብዮታዊ እርምጃ እንደወሰደባቸው ይነገራል፡፡ በሚያውቃቸው ላይ ሰይፉ በዚህ ልክ መበርታቱ የቅናት ይሁን የምቀኝነት የሚያውቀው እሱ ብቻ ነው፡፡ በቀይ ሽብርም ይሁን በነፃ እርምጃ እስራቱን፣ ሰቆቃውን፣ ግድያውን ሁሉ የሚፈጽሙት በአዋጅ ህጋዊ ካባ በማልበስ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ በግርማ አማካኝነት የደርግ ሰይፍ ካረፈባቸው ሰዎች መካከል ዳሮ ነጋሽ የተባለች የስምንት ልጆች እናትና የዘጠኝ ወር ነፍሰ ጡር አንዷ ነበረች፡፡ ካለችበት ቦታ በድንገት ወስዶ ነብሰ ጡር እንደሆነች እያወቀ ነው የገደላት፡፡ ይህን የሰማ የአራት ኪሎ ህዝብ ሁሉ በንዴት ያብዳል፡፡ እናቶች በሰልፍ እየጮሁ ወደ ቤተ መንግስት ይሄዳሉ፡፡ ድርጊቱ እጅግ ዘግናኝና አሳዛኝም ጭምር ስለነበረ የደርግ አመራሮች ይደነግጣሉ፡፡ ወዲያው ግርማ ከበደና ግብረ አበሮቹ እንዲያዙ ይደረጋል፡፡ በተያዘበት ጊዜ በቀጣይ የሚገድላቸውን ሰዎች ስም ዝርዘር የያዘ ሰነድ በእጁ ተገኝቶ ነበር፡፡ ከስሞቹ መካከል አንዱ አስራት ወልዴ የተባሉ የፕሬዚዳንት መንግስቱ ኃይለማሪያም አጎት ይገኙበት ሁሉ ነበር፡፡ ፕሬዚዳንቱ የዳሮ ነጋሽ ግድያ ይሁን፣ የአጎታቸው በስም ዝርዝር ውስጥ መገኘት አሊያም ደግሞ የእናቶች ጩኸት ተሰምቷቸው አይታወቅም… ግርማ በሞት እንዲቀጣ ፈረዱበት፡፡ ግርማ የመጀመሪያ ዲግሪ ነበረው፡፡ በባህሪው ትምህርት የገራው ሰው ግን አልነበረም፡፡ ትምህርት አንዳንድ ሰዎችን ከመጥፎ ባህሪያቸው እንደማይመልሳቸው ማሳያ ሞዴል ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡ የተማሩና የተመራመሩ፣ ሀገርና ህዝብን ከፊት ሆነው የሚመሩ ሆነው ነገር ግን አስተሳሰባቸው ከራሳቸው ፍላጎት የማያልፍ፣ ድርጊታቸው የእንስሳና የአራዊት፣ የሚያደርጉት ሁሉ ለታይታ፣ ለክብርና ለዝና ብቻ የሆነ፣ ለጥቅማቸው ምንም ከማድረግ የማይቆጠቡ፣ ‹እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል› ባዮች ትላንት እንደ ነበሩ ሁሉ ዛሬም እንዳሉና ነገም እንደሚኖሩ ግልጽ ነው፡፡
በነገራችን ላይ የሰው ልጅ የተማረም ይሁን ያልተማረ፣ ሰው በመሆኑ ብቻ ክፉን ከደግ የመለየት ፀጋ ከፈጣሪ ተሰጥቶታል፡፡ መማር ደግሞ ይህንን ፀጋ የበለጠ እንዲያድግና እንዲበለጽግ ያደርገዋል ተብሎ ይታመናል፡፡ ለሁሉም ግን አይደለም፤ ትምህርት አንዳንድ ሰዎች ዘንድ በተለይም ጨካኝነት፣ ክፋት፣ ተንኮልና ሴራ፣ ምቀኝነት፣ ንፉግነትና ራስ ወዳድነት የተጠናወታቸው ላይ ሲደርስ አይደለም ማበልጸግ እስከናካቴው ያመክንዋል፡፡ የነዚህ ሰዎች የሀሳባቸውና የድርጊታቸው መነሻ ምንጭ አእምሮአቸው ሳይሆን በደመ ነፍሳቸው የሚመራ የግል ጉዳያቸው ምኞታቸውና ተራ የለት-ተለት ፍላጎታቸው ብቻ እንደሆነ በልሂቃን ይጠቀሳል፡፡ በዚህ ልክ ትምህርትን የታከኩት አለምክንያት አይደለም፡፡ በቆቆ ቀበሌ እስከ ስልሳዎቹ አጋማሽ ድረስ በዩኒቨርስቲ ደረጃ የተማረ የአንድ ታላቅ ግለሰብ ህይወቱን፣ የተማሪነትና የትምህርት ጉዞውን፣ የፖለቲካ ተሳትፎውን፣ የእስር ዘመኑን ጨምሮ ለመመልከት ስለወደድኩ ነው፡፡…የመጀመሪያው የሀገራችን የትምህርት ስርአት እንዴት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሽቆለቆለ እንደሄደ እና አሁን ያለበትንም ተጨባጭ ደረጃ፣ ሁሉም የሚያውቀው ጉዳይ ነው፡፡ በይበልጥ ደግሞ የቅርብ ጊዜው የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተና ውጤት የዚህን ማሽቆልቆል ጥግ በይፋ አሳይቶናል ሊባል ይችላል፡፡ ያ ትውልድ በዚህ ረገድ እድለኛ ነበር፡፡ ብዛትን የሚያጅበው የጥራት መጓደል ሰለባ አልነበረምና! መምህራኖቹ በሙያቸው ብቃት የነበራቸው ከመሆናቸው ባሻገር ተማሪዎቻቸውን (ከቤተሰብ ጥብቅ ክትትል ባልተናነሰ መልኩ) በቅርበት የሚከታተሉም ነበሩ፡፡ በንጉሱና በደርጉ ዘመን ከስልሳዎቹ መጀመሪያ እስከ ሰባዎቹ መጨረሻ ስርዓቶቹ ትውልዱን ከአንደኛ ክፍል ጀምሮ ከአማርኛ በስተቀር ሁሉንም ትምህርት በእንግሊዘኛ በማስተማራቸው፣ በአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን በአለም አቀፍ ደረጃም ተወዳዳሪ ሆኖ ለመውጣት በቅተዋል፣ ችለዋልም፡፡ በተለይም ቀዳማዊ ኃይለስላሴ በርካታ ተማሪ ቤቶችን የምዕራቡ አለም ትምህርት ይቀሰምባቸው ዘንድ አመቻቹ፡፡ የድህረ አብዮቱ ቀንደኛ ተሳታፊና ዋነኛ ተዋናይ የነበሩት የእነ ዶ/ር መላኩ ተገኝ ትውልድ (ከሰንጋ ተራ እስከ አምስተርዳምን ልብ ይሏል) እራሱን በንባብ ያስታጠቀ በመሆኑ በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው ባለመማራቸው አልተጎዳንም፣ አላጎደለንምም እሚሉ አባላቶቹ ጥቂት አይደሉም፡፡ ዛሬ-ዛሬ ትግላቸውን መለስ ብለው በመቃኘት ትዝታቸውን ያኖሩልን እንደነ ተድላ ድረሴ ያሉ፣ ያ የትምህርት ስርዓትና አስተሳሰብ ያፈራቸው ናቸው፡፡ ከዚህ በተቃራኒ ደግሞ በኮተቤ ዩኒቨርሲቲ የቋንቋና ስነጽሑፍ መምህር የሆነው ባዩልኝ አያሌው፤ በዚሁ ጋዜጣ ላይ በዘመናዊ ትምህርት ዙሪያ ባዘጋጀው ጥናታዊ መጣጥፉ እንዳስነበበን፤ ”ሀገራችን የምዕራቡን አለም ስርዓተ ትምህርት ከእነ ቋንቋው የተቀበለችው ተማሪ ቤት አቁማ በመሆኑ በዚያው ቅጽበት ለዘመናት ማህበረሰብን በህግና በስርዓት፣ ከእውቀት ማዕድ ገሸሽ አደረገችው፡፡ ይሁንና የዘመናዊ ትምህርትን ያህል የሞራልና የስነምግባር እሴቶቻችንን በመጠበቅ ድርሻ ያለው ሌላ ያለ አይመስልም›› ሲል የደረሰበትን ድምዳሜ አስቀምጧል፡፡ (ቁጥር 1265.ሚያዚያ 5/2016)
ያ ትውልዶች በምዕራባውያን በአሜሪካና በሌሎችም ሀገሮች የከፍተኛ ትምህርታቸውን ይከታተሉ እንጂ፣ ከጥልቅ ንባብ ባሻገር የተወያዩ፣ የተከራከሩ፣ የሞገቱና የተሞገቱ ምሁራን ነበሩ፡፡ በርግጥ ሀገር በቀሉን የህብረተሰብ ተጨባጭ የእውቀት ክፍተት ለማካካስና ለመሙላት ሲሉ ደግሞ በወቅቱ በእናት ቋንቋቸው በአማርኛ የተጻፉና የተሰነዱ ድርሰቶችን ከዳር እስከ ዳር በማገላበጥ ይተጋሉ፡፡ የታሪክ ተማራማሪ የሆኑት ባህሩ ዘውዴ በ‹ኅብር ህይወቴ› ግለታሪካቸው፣ የእስር ዘመናቸውን ባወሱበት ምዕራፍ ስለዚህ ጉዳይ ሲጽፉ፤ ”በባእድ ቋንቋ ከተማርን በኋላ ለማጠናከር ዋና መንገድ ብዙ መጽሐፍ ማንበብ ነው!”…ይላሉ፡፡ ፕሮፌሰሩ አክለው…‹‹በዚህ ረገድ በተለይ ልብ ወለድ መጽሐፍት ይመረጣሉ፡፡ ምክንያቱም የነሱ ስነቃል የሰፋ፣ አገላለፃቸውም የዳበረ ስለሆነ ነው፡፡ ለዚህ በጣም የምንጠቀምባቸው ልብ አንጠልጣይ ልብወለዶችን ነበር፡፡ ከተፈታን በኋላ ትውስታ ስንለዋወጥ እኔ አንድ ቋንቋ ለማወቅ የሚያስፈልጉህ ሶስት ነገሮች ናቸው፤ እነሱም አንድ ጥሩ መዝገበ ቃላት፤ እና ብዙ የልብ ወለድ መጻሕፍት ስል እሸቱ ‹‹አንድ እስር ቤት ጨምርበት›› አለ፡፡ ( ገጽ.158 ) መምህር ተድላ ድረሴ ከነዚህ የቀለም ቀንድ ከሆኑ ከነባር የ-ያ ትውልድ ጉምቱ ምሁራን አባላት መካከል ግለህይወት ታሪካቸውን በቀላል ቋንቋ ሰንደውና አሰናድተው ያገኘናቸው፤ ከመጀመሪያዎቹም ረድፍ በጉልህ የሚጠቀሱ ግለሰብ ናቸው፡፡ የተማሪነትና የመምህርነት ረጅም ጉዞዋቸው የተዋቀረበት መጽሐፋቸው ለዚህ የዘመናዊ የቀለም ትምህርት ግስጋሴ ሁነኛ አስረጂ ነው፡፡ ባለታሪካችን ተድላ ከደብረ ብርሃን እና ጣርማበር አካባቢ፣ ከመንዝ ከምትጎራበተውና ጥቂት ኪሎ ሜትሮችንም እርቃ በምትገኘው ‹ቆቆ› በተባለች አነስተኛ መንደር ውስጥ ተወልደውና ተምረው ያደጉ ናቸው፡፡ ደብረሲና፣ ሰላድንጋይ…ሌሎችም አያሌ የተድላ ከልጅነት እስከ እውቀት የተከናወኑ የታሪክ ኩነቶች መነሻ ቦታዎች ናቸው፡፡ ቺቸሮ የተባለ ሮማዊ ተናጋሪና ደራሲ ‹ትምህርት›ን ከግሪክኛ ወደ ላቲን ሲተረጉም “(cultural animi) ትምህርት ህሊናን የማለዘብ፣ የማለስለስ የመንፈስ እርሻ ነው!” ብሎ ሰይሞታል፡፡ ተድላ መምህር ከመሆናቸው ቀድሞ በርሳቸው የልጅነት እድሜ ትምህርት ለማግኘት በልጆች ላይ ይደርስ የነበረውን የኑሮ ውጣ ውረድና እንግልት በስፋት ይዳስሳሉ፡፡ ከመንዝ ወደ ደብረብርሃን ልብስና ስንቅን ተሸክሞ ሁለት ቀን ያህልም ተጉዞ መማር፣ ከቁርና ከሀሩር፣ ከረሃብና ከህመም…ከሌሎችም ስቃዮች ጋር እየታገሉ ፊደልን መለየት ጠንቅቆ የሚያውቀው የቀመሰው ተድላ ብቻ ነው፡፡ አንዳንዴ በሌሊት፣ በጨለማም ጭምር ጉዞ መጀመር ግድ ሆኖ በመሸበት ማደርም አለ፡፡ አዳሩ ደግሞ በየሰው ቤት ‹የመሸበት መንገደኛ አሳድሩኝ!› በማለት ተለምኖም ጭምር ነው፡፡ ቤት ለእንግዳ ብለው የሚያስተናግዱት ሰዎች ኑሮ እንደነገሩ ከሆነ የሚላስ የሚቀመስ ይጠፋና ጦም ማደርም ይኖራል፡፡ ለመተኛ የሚጎዘጎዝ ሳር ይቀርናም መሬት ላይ መተኛት ይከተላል፡፡ ቀኑን ሙሉ በመጓዝ ሰውነት ዝሎ፣ ረሃብ ሆድን እየሞረሞረ ማደር ይመጣል፡፡ ቆላና ወይና ደጋው ላይ ትኋኑና ቁንጫው አይጣል ነው፡፡ በዚያ ላይ የሚታደረው ብርዳማ አውራጃ ስለሆነ ውርጩ ይነጫል፡፡ ያልታሰበ ነገርም ሊያጋጥም ሁሉ ይችላል፡፡…
“ተማር አትማርም ወይ፤ እረኛ መሆን ይሻልሀል ወይ?፤ አሳ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል፤ የሰው ፈላጊ የራሱን ያጣል” … በርግጥ በዘመኑ የትምህርት ጠቃሚነትን፣መልካም ስነምግባርን የሚነግሩና ህብረተሰቡ ውስጥም የሚያሰርጹ እንዲህ ያሉ መዝሙሮች በተለያየ ዜማ የሚዘመሩበት፣ ተማሪው ከፍ ያለ ዋጋ ከፍሎ እንዲማር የሚያነቃቁበት፣ ሰልፍና መዝሙሮችም ለዚሁ ቅስቀሳ ሲባል በስፋት የሚደረጉበትም ነበር፡፡ ይሁንና ግን ችግሩ ት/ቤት በቅርብ አለመኖሩ፣ ህዝቡም ስለትምህርት አስፈላጊነት በቂውን ያህል ግንዛቤ ማጣቱ ብቻም አልነበረም፡፡ ማህበረሰቡ ልጁ ከብት ቢጠብቅለት፣ ሴት ከሆነች ደግሞ ብትዳርለት ነበር እሚወድደው፡፡ የድሃ ልጅ እንዳይማር የሚገድብና ትውልዱን ባጭር የሚቀጩ ደንቦች እንዳይኖሩ ጥቂት ቀለም የቀመሱ መምህራን ድምጻቸውን የሚያሰሙበት፣ መፈክራቸውን እያዘመሩ ሰልፍ የሚያስወጡበት፣ የሚያስነግሩበትም ነበር - እንዲህ… ‹‹ደሃ ደሃ ደሃ ምን ታየበት እንዳይማር የሆነበት››፡፡ ተድላም እናቱ ተምሮ ትልቅ ቦታ እንዲደርስላት ኑሮዋን ሰውታለች፣ የሞቀ ቤትዋን አፍርሳለች፡፡ ‹‹ትምህርት እና ቤተሰብ›› ሲል በሰየመው ንዑስ ርዕስ ስር እንዳሰፈረው፤ እናቱ የመኖርዋ ሰበብና እርካታ እሱ በትምህርት የሚደርስበት ትልቅ ደረጃ ብቻ ነበር፡፡ እንግዲህ ሰውዬው ተድላ በዚህ በተከፈለለት ከፍ ያለ ዋጋ፣ በግሉም ባደረገው ትንቅንቅ ውስጥ አልፎ ነው ቀለም ቀመስ ለመሆን የበቃው፡፡ ለዚህም ይመስላል ከማስተማር ጎን ለጎን ከሰራቸው ስራዎች ሁሉ መምህርነቱን በፍቅር የሚወድደው፤…‹‹እኔ በመንፈሴ ምንጊዜም መምህር ነኝ፡፡ መምህር የነበርነው ሁሉ ስንገናኝ የምናወራው ስለ መምህርነት ህይወት ነው፡፡ ሌላ መስሪያ ቤትም እየሰራሁ በነበርኩበት ጊዜ ሁሉ የሚሰማኝ መምህርነቴ ነው፡፡ ትዝ ይለኛል በአንድ ስልጠና ላይ በዋናነት ለምን መምህር ለመሆን እንደፈለግን ሲጠይቁን ለዚህ የሰጠሁት መልስ፣ መምህርነት የተቀደሰ ሙያ ስለሆነ ነው አስተማሪ ለመሆን የፈለግሁት በማለት (“teaching is a very profession”)
ሲባልና እኛም ስንል ነው ከልጅነታችን ጀምሮ የምናውቀው፡፡ አስተማሪዎቻችን እንዲህ እያሉን ነው መምህርነታችንን የወደድነው፡፡ (ገጽ.153)
ተድላም በተራው ያልተማረ ወገኑን መልሶ በእውቀት ነፃ ሊያወጣው ታጥቆ የተነሳው፣ ማልዶ የዘመተው እምብዛም ሳያረፋፍድ…ትምህርቱን ዳር ለማድረስ ብዙ ሳይገፋበት ነበር፡፡ ቀደም ብሎም የመንዝ ህዝብ በትምህርት ወደ ኋላ መቅረት ሲያሳዝነውና፣ ሲያስቆጨውም ኖሯል፡፡ ወደ መንደሩ በመዝመት በህዝቡ ልብ ውስጥ የእውቀትን ብርሀን በመለኮስ ሊያቀጣጥል ሲጥር በመጽሐፉ ምንባቦች ተዘግቦ ያጋጥመናል፡፡ በወቅቱ የነበረው የትምህርት ፖሊሲ ተምረው የደረሱ ወጣቶችን መንግስት አስተማሪ ለመሆን መብቃታቸውን ተምሳሌት በማድረግ የአካባቢው ታዳጊዎችም ይሄን በማየት እንዲነቃቁ ለማስቻል ወደመጡበት ቀዬ በመመደብ በሞያቸው እንዲያገለግሉ ያደርጋቸውም ነበር፡፡ በዘመኑ አስተማሪ መሆን ቀርቶ ያስተማሪ ቤተሰብ፣ ያስተማሪ ዘመድ፣ ጎረቤትም መሆን ያስቀና ሁሉ ነበር፡፡ አስተማሪ በማንኛውም ስፍራ ጠርቶ ያናገረው ተማሪ እንደ እድለኛ ይቆጠራል፡፡ አስተማሪ ይከበራል፣ ከማንም በላይ በትልቅነት ይታያል፡፡ ከወላጅ በላይ ሁሉ ሳይታይ ይቀራል?! ሌላው ቢቀር የኛ ሙሽራ ባለድሪ ወሰዳት አስተማሪ›! ተብሎ ይዘፈን የነበረውን ያልሰማና ያላነበበስ ማነው?፡ ሰውዬው በቀለም ትምህርት እውቀታቸው የገፉ ጠቢብ ይሁኑ እንጂ መጽሐፋቸውን ስንመለከት ግን አካዳሚ ነክ ጉዳዮችን በሚዛንና በተገቢው ቦታቸው ላይ እንጂ አላግባብ በአወቅሁ ባይነት እያነሱ አያቸኩንም፡፡ በቲዎሪና በተራ ንድፈ ሀሳብ ላይ ብቻ ሳይወሰኑ የሰው ልጆችን ሁሉ በሚያቅፍ አስተምህሮት፣ በተግባራዊ ሳይንስ የተደገፈ የልምድ ችሎታ በመታገዝ ተሞክሮአቸውን እያዋዙ ያካፍሉናል፡፡ መልካሙንና ክፉውን ከሚያሳውቀው እውቀቶቻቸው፣ ከእውቀት ዛፍ ላይ እንግዳና ልዩ-ልዩ ፍሬዎችን እየቀጠፉ ያቀብሉናል፡፡
ከኢህአፓ ግንባር ቀደም አመራር አባላት መካከል አንዱ የሆኑትና የፖለቲካ እስረኛም የነበሩት ተድላ፣ ከካበተ የህይወት ልምዳቸው የሀገሪቱን ነባራዊም ሆነ ተጨባጩን አስተዳደራዊ ሁኔታና ክስተት በሚገባ በማጤናቸው ጠንቅቀውም እንደሚያውቁ ከሚያነሱዋቸውና ከሚሰነዝሯቸው አጥጋቢ አስተያየቶችና ግላዊ ምልከታዎቻቸው በቅጡ መረዳታቸውን እንገነዘባለን፡፡ የስነልቦና ውቅራቸው እንደዘመነኞቻቸው ትላንትናቸው ላይ ብቻ ያልተገታ፣ ለአሁናዊ ሀገራዊ ጉዳዮች በሩን ገርበብ አድርጎ ለመፍረድ የመቆም ጭምር ነው፡፡ መንዜው ተድላ የነገር ብልት በብቃት የሚያወጣ ሀሳቡን አፍታቶም፣ ሲያሰኘው አብራርቶም በአጭሩ መግለጥ የሚሆንለትና በቃላትም ቢሆን በቦታው ያልነበርነውን፣ ሁነቱና ድርጊቱ በተከናወነበት ጊዜ የሌለነውን አንባቢያን የማሳመንና የማግባባት አቅምና ልዩ ክህሎታቸውን በዚህ ህይወት ታሪክ ንባቤ ለማስተዋል ችያለሁ፡፡ መጽሐፉ በጥናት ላይ የተመረኮዙና በበቂ ማስረጃዎች የተደገፉ ተአማኒነት ያላቸው አያሌ የግለሰብ እውነተኛ ገጠመኞችን በውስጡ አካቷል፡፡ ቁም ነገር የሰሩ ነገር ግን ያልተነገረላቸውና ያልተዘመረላቸው ናቸው ብለው የሚያምኑባቸውን የዘመን ተጋሪ ጓዶቻቸውን እሚችሉትን እና እሚያውቁትን ያህል ሊመሰክሩላቸውም ጥረዋል፡፡ በጥቂት ዋና-ዋና አንኳር ርእሶች፣ በአያሌ ንዑስ ርዕሶች ተደልድሎ የተሰናኘ ተነባቢ ስራ ነው፡፡ ባልተለመደ ሁኔታ ግለታሪክ እንደ ፖስት ካርድ እስቶሪ በአጫጭር፣ ቅልብጭና ቁልጭ ባለ አተራክና ውብ አቀራረብ ታትሞ ሳነብ ለኔ በግል ይሄ የመጀመሪያዬ ነው፡፡
ያ ትውልድ በመባል የሚፈረጀው ወገን የሚታወቅበትና የሚለይበት አብዮታዊ የፖለቲካ ተሳትፎ እንደሆነ እሙን ነው፡፡ ተድላም ‹‹ፍፁም ነው እምነቴ የትግሉ ነው ህይወቴ፣ ብዝበዛና ጭቆና እስኪጠፋ ረሀብ ችግር አይፈታንም፣ የህዝቡ ታማኝ አገልጋይ የሰርቶ አደሩ ወታደር ነኝ››…መሰል የኢህአፓ የቃል ኪዳን የመዝሙር ስንኞች እየዘመሩ ማልደው ከተነሱ ጓዶቹ መሀል አንዱ ነበር፡፡ በእርግጥ ተድላና መሰሎቹ የህዝቡ ባለእዳ ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ ለመሞት ቆርጠው ትግሉን የተቀላቀሉት ጦሙን እያደረ ያስተማራቸውን ህዝብ ከድህነት ለማውጣት፣ ገበሬው የሚያርሰው መሬት ባለቤት እንዲሆን፣ ህብረተሰቡ ያለቆቹና የገዢዎቹ አሽከር ከመሆን ነፃ እንዲወጣ ለማስቻል በማሰብ ነበር፡፡ እንዲያ ባይሆንማ ለራሳቸው የጎደላቸው ነገር የለም፡፡ በቂውን ያህል ተምረዋል፣ ነገም ደግሞ የፈለጉትን ስራ ሰርተው መኖር ይችሉ ነበር፡፡ ለዚህም ሲሉ ነው በፖሊቲካ ጀልባ ተሳፍረው፣ በፖለቲካ ባህር ላይ እየቀዘፉ... በዚህ የደርግን አገዛዝ ለመነቅነቅ፣ በዚያ ደግሞ ከመኢሶኖች ጋር በመተናነቅ፣ ብሎም አድሀሪያንን በመዋጋት ብዙ ፍዳ ያዩት፣ ብዙ ዋጋም የከፈሉት፡፡ በኢህአፓ አመራር ውስጥ በተፈጠረ መከፋፈል ሳቢያ እስከ ታች ድረስ ወዳሉት መዋቅሮች በመውረዱ ለእስር ከርቸሌ መውረዱ ይቅርና ለሞት የመዳረጉ አደጋ ሲበዛ የሰፋ ነበር፡፡ በእያንዳንዳቸው አባላት ላይ እያንዣበበና እየተጋረጠም መምጣቱ ገሀድ ነበር፡፡ ተድላም የዚህ ሰለባ ከመሆን አላመለጠም፡፡ እጁን በውዴታ በመስጠት ለመታሰር እንደማይፈቅድ ቀድሞ ለራሱ ቃል ገብቷል፡፡ ለነገሩ እሱ ብቻ አይደለም፤ ያ የኢህአፓ ተራማጅ አስተሳሰብ የነበረው ትንታግ ትውልድ ጓዶቹ ከፊሉ ታስረው፣ ገሚሱም ደግሞ ሞተው ቀሪው ምንም ሳይሆን ሲኖር ሰላም እሚነሳቸውና እሚጸጽታቸው፣ የመንፈስ እረፍት እንደማይሰጣቸው እነሱም ደግሞ ከሁለቱ በአንዱ እስኪቀላቀሏቸው እንቅልፍ የሌላቸው የማይረጋጉ ትውልዶች እንደነበሩ ካገላበጥናቸው የትውልዱ ታሪካዊ መዝገቦችና ማስታወሻዎች አስረግጠው የሚነግሩን ሀቅ ነው፡፡ ተድላም በመጨረሻ ተይዞ ከማእከላዊ ምርመራ ወደ ከርቸሌ ሲጋዝ በዚያ ያሳለፈውንና የተሰማውን ሲተርክ የሚያረጋግጥልን ከላይ ያለውን እውነት ነው፡፡ ከእስር ቤት ውጭ ባለው አለም ውስጥ እንደሚታዩት ልዩ-ልዩ ነገሮች ሁሉ በከርቸሌም በየ‘እለቱ የሚታይ ክስተት አለ፡፡ ደግና ክፉ፣ የሚያስቅና የሚያስለቅስ፣ የሚያስደስትም ሆነ የሚያሳዝን፣ የሚያስደንቅና የሚያሳፍር…ሌሎችም፡፡ ተድላ በዚያ የተከናወኑና ፍንትው ብለው የታዩትን አይረሴ የሚላቸውን ገጠመኞች፣ ታሪካዊ ክስተቶች ለዛ ባለው መልኩ ተርኳል፡፡ በተለይ ይሄ የመጽሐፉ ክፍል ሲበዛ መሳጭ ነው፡፡ ራሱን የቻለ መጽሐፍ መሆን የሚችል አቅምም አለው፡፡
ስህተቶቻቸው
በተለምዶ ያ ትውልድን እርስ በእርሱ የተገዳደለ፣ በትንንሽ ነገሮች ላይ እንኳን የማይግባባ፣ ችግሮችን በውይይት የማይፈታ፣ በሀይል የሚያምን ወዘተ… በማለት በዚህ ትውልድ አባላት ይብጠለጠላል፣ የሰላ ትችትም ይሰነዘርበታል፡፡ ከተድላ ሊነቀስ የሚችል አንድ ድክመት ወይንም ስህተት ቢኖር በዚህና በአንዳንድ የሀገሪቱ ነባር የታሪክ ውዝግቦችና የትውልዱ አሉታዊ ምልከታዎች ላይ በእማኝነት ለምስክርነት ብለው የሚታደሙባቸው አላስፈላጊና አታካች የሆኑ ችሎቶች ናቸው፡፡ በፖለቲካ እንቅስቃሴውም ሆነ ስለ ያ ትውልድ ከእውነት የራቀና ፈሩን የለቀቀ ነው በሚሉት አስተያየቶች ላይ ሚዛኑን ያልጠበቀና ስሜት ያጠላበት ጠንከርና ጠጠር ባሉ ቃላት፣ ጠልቀውም ከርዕሰ ጉዳዮቻቸው እርቀውም ይሄን ትውልድ ይወቅሳሉ፣ ጨከን ብለውም ይገስጻሉ፡፡ ሌላው ቢቀር ለዚህ ሁሉ ንትርክ እሳቸው የጻፉልን መጽሐፍ በቂና አጥጋቢ ምላሽ መሆኑን በተደጋጋሚ ይጠቅሳሉ፡፡ በሁሉም ትውልዶች ውስጥ የተዛባ ትርክት እንዳለና እሱን የማጥራት ስራ ደግሞ የታሪክ ተመራማሪዎች መሆኑን እንዴት ልብ ሳይሉ ቀሩም ያስብላል፡፡
ማጠቃለያ
እጓለ ገ/ዮሀንስ ”የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ” በተሰኘ ተወዳጅ መጽሐፋቸው ውስጥ የኢትዮጵያ ህዝብ ከታሪካዊ እድሉ ለመድረስ ከዛሬው የሚበልጠውን የነገውን ትልቅነት በእጁ ለማድረግ በተምኔት እየተመራ ወደ ፊት ይጓዛል፤ ከዚህ አላማው ከሚያደርሱት መሳሪያዎች አንደኛው ትምህርት ነው፤ ሁለተኛው ትምህርት ነው፤ ሶስተኛውም ትምህርት ነው”...ይላሉ፡፡ መምህር ተድላ ድረሴም ከእድል ፈንታቸው ለመድረስ ያበቃቸው ብቸኛው መሳሪያ ከአንድ እስከ ሶስት ሳንቆጥር ትምህርት መሆኑን ግለታሪካቸው በዝርዝር ያስረዳል፡፡ የዚያን ዘመን መምህራን በሄዱበት ቦታ ሁሉ አካባቢውን እንደተወለዱበት’ ህዝቡን ደግሞ እንደ ቤተሰብ በመቁጠር ተመሳስለው እየኖሩ እውቀታቸውንና ችሎታቸውን አቅም በፊደላቸው መጠን ሁሉ አንዳች ሳይቆጥቡ እንዳገለገሉ ድርሳኑ በአፅንኦት ይተርካል፡፡ ያ ትውልድ ላገሩና ለወገኑ ሲል በቀለም ትምህርት ረገድ በከተማና በገጠር ያደረገውን አበርክቶና ተጋድሎም እንዲሁ በጥልቀት ይቃኛል፡፡
በዚህች ባላደገችና ባልተመነደገች’ የዪንቨርስቲዎቿን ቁጥር ማብዛት ላይ እንጂ ትምህርትን ተደራሽ አድርጋ ገና ለሁሉም ዜጎችዋ በቅጡ ባላዳረሰች፣ ዛሬም በቁጥር እሚበዙት ዜጎችዋ ገና ከመሀይምነትና ፊደል ካለመለየት ድንቁርና ባልተላቀቁባት ሀገር፣ የተከተልነው የዘመናዊ ትምህርት ተሞክሮን ጨምሮ ከመነሻው እስከ መዳረሻው’ ከጥንስሱ እስከ ድግሱ እንዴት ያለ’ እንደነበረ ለመረዳት የተድላ መጽሐፍ በምርኩዝነት ያግዛል፡፡ የኔታ ተድላ ትውልድን በእውቀታቸው ሲመግቡ ኖረው በዚህ የእድሜ አመሻሻቸው ወቅት ደግሞ በመጽሐፋቸው እኛኑ ተደራሲያኑን የዘመን ልምዳቸውን ከሀ እስከ ፐ እያስቆጠሩ አካፍለውናልና ላቅ ያለ ክብርና ምስጋና ይገባቸዋል፡፡

ባለፈው ሳምንት የብራሰልስ/የቤልጂየምን ብርድ ለመቋቋም ሬስቶራንት ፍለጋ ዞረን፣ አንዲት መካከለኛ ሬስቶራንት አግኝተን እየተረጋጋን ሳለን ነበር ጽሁፌን ያቆምኩት። ከዚያው እንቀጥላለን።
በነገራችን ላይ ከዛ በፊት ስላጋጠሙኝ ሁለት ነገሮች ልንገራችሁ።
1ኛው/ አንድ ወጣት ሚኒባስ ላይ አግኝቶኝ ተዋወቀንና፣ “የኛ ሰው በአሜሪካ አልቆ ነወይ፤ የኛ ሰው በብራሰልስ የጀመርከው?” ብሎ ጠየቀኝ።
እኔም “አይደለም ባለኝ የውጪ ማስታወሻ ላይ ተጨማሪ ስላገኘሁ ነው። ከዚህ ቀደም የሄድኩበትን ማስታወሻዬ ላይ ስላሰፈርኩት የት ይሄድብናል? ዕድሜውን ይስጠን እንጂ እናነበዋለን” አልኩት። “እንዲህ ከሆነማ ሁልጊዜ በየአገሩ በወሰዱህ አሪፍ ይሆንልን ነበር” አለ።
“ኢትዮጵያዊ የሌለበት ቦታ ከወሰዱኝ ነው ጉዱ!”
“ኢትዮጵያዊ የሌለበት ቦታ ፈጽሞ የለም! ጨረቃ ላይም አለ” አለኝ ኮስተር ብሎ፤ ነገር -ዓለሙ ገርሞኛል።
“እዛስ በምንም መንገድ ለመሄድ የምችል አይመስለኝም” ስለው፤
በጣም ፍርጥም ብሎና በተመስጦ፤ “ግዴለህም ነቢይ፤ አንድ ቀን ዲቪ ይደርስሃል!” አለኝና የመጨረሻ አሳቀኝ። ወጣቱ ከታክሲው ወርዶ ሲሄድ በማያዩ አይኖች እያየሁት ለብዙ ችግሮቻችን መፍትሄው ዲቪ መሆኑ ገረመኝ። የሐሳባችን ውሱንነት ሀሳብ ውስጥ ከተተኝ። ገጣሚ ፀጋዬ ገ/መድህን መንፈሴ ውስጥ ገባ- በከርሞ ሰው በኩል።
“… ምኞቴ እንደ ጉም መንጥቃ
ተስፋዬ እንደ ጉድፍ ወድቃ
የወንድሜን ልጆች እንኳ ለርስታቸው ሳላበቃ
የኔ ነገር በቃ በቃ!!”
2ኛው/ አጋጣሚ
እንደዚሁ ታክሲ ውስጥ ነው። ልጆች ሲጨዋወቱ፤
አንደኛው “አይዞህ እኔ አሜሪካ ስሄድ፣ እኔ ነኝ ያለ ስኒከር፣ እልክልሃለሁ!!” ደሞ ትንሽ ተጫውተው፣
“እኔ አሜሪካ ስሄድ የቀወጠ ጃኬት እልክልሃለሁ!!” ይለዋል። እንዲሁ እያለ “እኔ አሜሪካ ስሄድ”ን ቀጠለ። “እኔ አሜሪካ ስሄድ…” ብሎ እንደገና ሊጀምር ሲል ጓደኝዬው አቋረጠውና፤
“ቆይ ኧረ፤ እኔ አሜሪካ ስሄድ፣ ይህን እልክልሃለሁ፣ ይሄን እሰድልሃለሁ የምትለው፣ እኔ ዋሊያ ነኝ፤ ቀይ ቀበሮ ነኝ… ወይስ መለስ ነኝ፤ ወደ አሜሪካ የማልሄደው?”
“አይ!! አንተ እንኳን ወደ አሜሪካ የምትሄደው ወይ “ከቦሌ ዲሲ” የሚሠራ ሚኒባስ ጀምሮ ወያላው “ዲሲ! ዲሲ!” እያለ ሲጠራ ካጋጠመህ፤ አለበለዚያ ኢትዮጵያ ራሷ ዲቪ ሲደርሳት ነው!” አለውና ተሳሳቁ።
ሦስት ነገር ገረመኝ። አንደኛው ሚኒባስ ላይ ሆነው የሚኒባስን እድገት አስበው ከቦሌ ዲሲ ስለሚለው ሚኒባስ ማሰባቸው ነው። ሁለተኛው መለስን እንደ ብርቅዬ እንስሳ ሲጠቅሰው፤ እንኳን ስለ ጠቅላይ ሚኒስትር ስለ መሥሪያ ቤት ዘበኛም የሚያወራ አለመምሰሉ ነው። ሦስተኛው ለኢትዮጵያ ለሀገሪቱም ዲቪ መመኘታቸው ነው።
***
የሬስቶራንቱ ዋጋ አስፈሪ አይደለም። ሁለት ትላልቅ ሳንድዊች መጣልን። እርቦን ስለነበር እየተስገበገብን ሳንበላ አልቀረንም። ሁለታችንም የምንበላው አትክልቱንም፣ ስጋውንም ከውስጥ እየቦጠቦጥን ነው። ገርበብ ብለን ቀና ስንል አብሮኝ የሚመገበው ተጓዥ ወዳጄ፡-
“እኔ የምልህ?” አለ
“እ!”
“ይሄ ምግብ በሁለት ሳህን ለምን መጣ?”
“እንዴት በሁለት ሣህን?”
“ይሄው አንደኛው ሳህን” አለና ምግቡ የቀረበበትን ሳህን አሳየኝ።
ቀጥሎ ደግሞ!
“ይሄው ሌላው ሳህን” ብሎ ሁለተኛውን ሳህን አሳየኝ። ሁለተኛው ሳህን ብሎ ያሳየኝ አንድ ጥርብ እንጨት ሁለት ላይ ተሰንጥቆ ማህሉ ስጋና አትክልት የተደረገበት የሚመስለውን ትላልቅ ዳቦ ነው ለካ። ዕውነትም ሁለታችንም ዳቦውን እንደ ዳቦ ሳይሆን እንደ ምግብ ማስቀመጫ ነው ያየነው- ሳናውቀው።
በጣም ተሳሳቅን።
ለማንኛውም ከርሃብ እፎይ ብለን ቢራችንን መጠጣት ቀጠልን። “እስቲ እንግዲህ ደግሞ ሌላ ቢራ ቤት ዘወር ዘወር ብለን እንመልከት” አለኝ ጓደኛዬ። ከፈለና ወጣን። እዚያው የብርድ ግግር ውስጥ ጥልቅ አልን። ጀመረን ብርዱ። ግን እንደ መጀመሪያው አይደለም። “ኑሮ ካሉት ፍሪጅም ይሞቃል” ወደሚለው አንድረስ እንጂ ብርዱን የመልመድን፤ መንገድ መንገዱን ጀምረነዋል።
የዚያን ዕለት በቤልጂየም አንድ ያስገረመን ነገር ፀጥታው ነው። ሰው ወዲያ ወዲህ አይልም። ቀኑ ቅዳሜ ነው። መቼም ሰው በቅዳሜ ምድር እቤቱ ክትት አይልም የሚለው የኢትዮጵያ አዋዋል ግምታችን እዚህም ተከትሎን መጥቶ ነው መሰለኝ። ብቻ ጭር ጭው ብሏል። ያ ስንመጣ ነው።
አሁን ግን ቢራ ፍለጋ ወዲያ ወዲህ ማለት ስንጀምር ሰው ማየት ጀመርን።
“ምናልባት የምሳ ሰዓት ቢሆን ነው ጭር ያለው” አልኩት ለጓደኛዬ።
ጓደኛዬም- “ነው ብለህ ነው? ሁሉም፣ እንዲህ ክትት እስከሚል ድረስ deserted (ሰው የት ይሄዳል) ይሆናል ብለህ ነው ታዲያ?”
እናም- “ይመስለኛል። ሌላ ምን ምክንያት ትሰጠዋለህ ታዲያ? በብራሰልሱ የስብሰባ ፕሮግራማችን ላይ እንኳ በደምብ ብታስተውለው ቅዳሜና እሁድን በጥንቃቄ ነው የዘለሏቸው። ስለዚህ የእረፍት ቀንነቱን ኮስተር ብለው ቢያምኑበት ነው”
“እስቲ እናያለን” አለ ጓደኛዬ።
አንድ ሬስቶራንት ገባን። ቤቱ ከቅድሙ ተለቅ ያለና ግርማ-ሞገሱም ገዘፍ ያለ ነው።
“ቢራ” አልኩኝ።
“ምን ዓይነት ቢራ?” አለ አስተናጋጁ።
“እንግዲህ ገና በስም አናውቀውም- ቅድም የጠጣነው “ሜዝ” ይሁን “ሜስ” በደንብ አላወቅነውም እንጂ እሱን ብናዝ ጥሩ ነው” አልኩኝ።
“Do you have some light beer?” አለ ጓደኛዬ። (ቀለል ያለ ቢራ አላችሁ እንዴ? እንደ ማለት ነው)
“We have many types of birr! Something like 400 what do you want?...”
(ብዙ ነው ያለን! 400 ገደማ የተለያዩ ዓይነት ቢራዎች አሉን፤ የትኛውን ፈለጋችሁ?)
“የሰማያቱ ያለህ!” አልኩኝ በሆዴ። 400 ዓይነት ቢራ?!
ጥቂት ቆየት አለና ጠየቀን። “Shall I bring you maes?” (ሜስ የሚባለውን ላምጣላችሁ? ማለቱ ነው)
እንግድነታችን ገብቶታል።
“አዎን” አልኩኝ ወዲያውኑ!
“ይቺ ከላፍቶ ክፍለ ከተማ የማትበልጥ ከተማ እንዲህ ትጫወትብን?” አለ ጓደኛዬ። ተሳሳቅን።
“ምን ታደርገዋለህ? ሁሉም ነገር እንዳገሩ እንድትሆን ይወስንሃል”
“This is maes!” (ይኸው “ሜስ”!) አለ አስተናጋጁ። ድምፁ ውስጥ ያለው ልበ-ሙሉነት ሲታይ፤ ራሱ የጠመቀው ነው የሚመስለው።
“ራሱ ነው!” አልኩኝ አንዴ ተጎንጭቼ። እየተጎነጨን ጨዋታ ያዝን።
ተጨዋውተን፣ ጠጣጥተን ስናበቃ ወደ ሆቴላችን ሄደን አራተኛውን ጓደኛችንን፤ከፍራንክፈርት ዘግይቶ የሚመጣውን ማለት ነው፤ ልናገኘው አስበን መንገድ ጀመርን።
እኔ ሁሌ የምከራከርበት “ሁሉ አገር አዙሪት አለው” የሚል ሙግት አለኝ። አንዳንድ ወዳጆቼ አይቀበሉኝም። እኔ የናዝሬት ልጅ ነኝ። የናዝሬት ልጆች፣ ናዝሬት አዙሪት አለ ብለን እናምናለን። አዙሪት ማለት እንዲህ ነው።
ወደ አንድ ምንም ከዚህ ቀደም አይታችሁት ወደማታውቁበት ቦታ ሄዳችኋል እንበል። ባንዱ ቅያስ ሄዳችሁ ስታበቁ ተመልሼ ያንኑ ቅያስ አገኛለሁ ብላችሁ ስትመጡ፣ ምኑም ምኑም ያንን ቅያስ የሚመስል አንድ መንገድ ታገኛላችሁ። በእርግጠኝነት “ጎሽ አገኘሁት!” ብላችሁ ትገቡበታላችሁ። ትንሽ እንደሄዳችሁ ፍፁም ያንኑ ቅያስና መንገድ የሚመስል ታገኛላችሁ። ሊዞርባችሁ ይጀምራል። ትመለሳላችሁ። በቃ የአዙሪቱ ቀለበት ውስጥ ገባችሁ ማለት ነው። ያደረጋችሁት ምልክት የጠፋችሁ ይመስላችኋል። ሰው ልጠይቅ ብላችሁ አላፊ- አግዳሚ መማተር ትጀምራላችሁ። አንዱን አግኝታችሁ፡-
“እባክህ አንድ ነገር እርዳኝ?” ትሉታላችሁ። ደግ ሰው ከሆነ “ምን ልርዳህ? ምን ፈለግህ?” ይላል።
“እንዲህ እንዲህ የሚባል ቦታ ነበር የምፈልገው። ከዚህ ምን ያህል ይርቅ ይሆን?”
“ It is right behind you…or it is right in front of you there, across the road” ይላችኋል።
(ይኸው ከጀርባህ’ኮ ነው ያለው…ወይ ያው ፊት ለፊትህ መንገዱን ተሻግሮ’ኮ ነው)
ብሎ ወጣቱ ይጠቁማችኋል። ይሄ ዐይናችሁ ስር እያለ የሚጋርድባችሁ፤ ሲያዞር ሲያንቀዋልላችሁ የሚውለው ነገር ነው እንግዲህ “አዙሪት” የሚባለው። ቅድም እንዳልኩት በናዝሬት ልጅነት የማውቀው አዙሪት የቅያሶቹ መመሳሰል፣ የቤቶቹ ቅርፅና ዕድሜ አንድ መሆን፣ ከጠራራዋ የናዝሬት ጸሐይ ጋር ተደምሮ ናላ ይነካል፤ ብዥ-ድንብር ያደርጋል። ብዙ ሰው ይዞርበታል። ያ ነው እንግዲህ አዙሪት የሚሆነው። በተጨማሪም እንደ አገሬው እምነት “ቆሌዋ ሳትወድድህ ስትቀር ነው” የሚባለውም አለው። ያ በመጠኑ ወደ ዕምነታዊው አቅጣጫ ያመራናልና ለሌላ ጊዜ ልተወው።
ከሬስቶራንቱ ተመልሰን ወደ ሆቴላችን በሰላም እንዳንገባ የቤልጅንግ አዙሪት በዬት በኩል! ዞረን እዛው! ሄደን ሄደን እዛው! ብዙ ከተንገላታን በኋላ
“ያው ሆቴላችን!” አለ ወዳጄ።
በራሳችን ሳቅን። ልክ ወደ ሆቴላችን ልንገባ ስንል ከኋላችን አንድ ድምጽ ጓደኛዬን ጠራው።
ጓደኛዬ ዘወር አለ። የሚያውቀውን ሰው አግኝቶ ነው ብዬ እኔ በቀስታ ወደፊት ሳመራ ጓደኛዬ ጠራኝና፤ “ና እንጂ አትተዋወቁም እንዴ?” ብሎ መተዋወቅ ወደ አለብኝ ሰው በአይኖቼ አመላከተኝ።
ሰውዬውን በአካል አግኝቼው ባላውቅም ብዙ ቦታ አይቼዋለሁ። በቴሌቪዥንማ ሁሌ አለ።
ተጨባበጥን። ከሀገራችን የተቃዋሚ ድርጅት መሪዎች አንዱ ነው! ከጓደኛው ጋር ነው።
ጓደኛዬ በመገረም፤ “እንዴ እዚህ ነው እንዴ ያላችሁት?” አለና ጠየቀው።
“አዎ እዚሁ ሰንብተናል፤ ለስብሰባ መጥተን ነው” አለ መሪው
“ትቆያላችሁ?”
“የለም ዛሬ ማታ ወደ እንግሊዝ እሄዳለሁ። እዚያ አንድ ቀን አድርና ለአንድ ሳምንት አሜሪካ እሄዳለሁ”
“ምን ለመስራት ነው የምትሄዱት?”
“ያው lobby ለማድረግ ነዋ!” (ለመቀስቀስ ማለቱ ነው።)
ከተለያየን በኋላ ጓደኛዬ፤ “የዓለም ጠባብነት አይገርምህም። ከእነዚህ ሰዎች ጋር እዚህ እንገናኛለን ብለህ ታስባለህ አሁን?!” እውነትም እኛ ኢትዮጵያ ጥለናቸው የመጣን መስሎን ነበር፤ ለካ እነሱ ናቸው ጥለውን የመጡት።
“The world is a village nowadays man!`”
(ዛሬ ጊዜ ዓለም እንደ መንደር ጠባለች ወዳጄ!) የነገ ፕሮግራማችን ብራሰልስን በአስጎብኚ እየዞሩ ማየት ነው። የነገ ሰው ይበለን።
***
(አዲስ አድማስ፤ ሚያዝያ 1 ቀን 1997 ዓ.ም)

Page 4 of 719