Administrator

Administrator

በስድስት ወር ጊዜ ውስጥ 28 ጋዜጠኞች ለቀዋል

የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅትን ለስምንት ዓመታት በዋና ዳይሬክተርነት ያገለገሉት አቶ ዘርዓይ አስገዶም ተነስተው፣ የኢህአዴግ የሚዲያ ተቋማትን ሲመሩ የነበሩት አቶ ብርሃነ ኪዳነማርያም እንደተተኩ ታወቀ፡፡ በኢህአዴግ ስር የተመዘገቡ የፓርቲው የሚዲያ ተቋማትን ብቻ ሳይሆን ኢህአዴግ ቀመስ የሆነውን ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከልን በኃላፊነት በመምራት የሚታወቁት አቶ ብርሃነ፣ የመቀሌ ከንቲባ ሆነው መሥራታቸው ይታወሣል፡፡ በተጨማሪም ግዙፍ ኩባንያዎችን ባካተተው የኤፈርት ፋውንዴሽን የአመራር ቦታ ነበራቸው፡፡የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ዘርዓይ አስገዶም፤ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ኤጀንሲ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሆነው መሾማቸው ታውቋል፡፡

በሌላ በኩል፤ የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጽ/ቤት ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን በሰብሳቢነት የሚመሩት የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ቦርድ ከትናንት በስቲያ ለፓርላማ ባቀረበው የግማሽ ዓመት ሪፖርት፣ ከተቃዋሚ ፓርቲ ተወካይ አቶ ግርማ ሰይፋ ትችት ተሰንዝሮበታል። የኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቪዥን የኢህአዴግን የአብዮታዊ ዲሞክራሲ አስተሳሰብን ያራምዳል ያሉት አቶ ግርማ፤ ይህም ህገ መንግስቱን ይጥሳል ብለዋል፡፡ ድርጅቱ ልማትንና ዴሞክራሲን ለማዳበር እንደሚሰራ የተናገሩት አቶ ሬድዋን በበኩላቸው፤ የተለያዩ ድክመቶችና ችግሮች መኖራቸውን ጠቅሰው፣ ለልማትና ለዴሞክራሲ ግንባታ መስራት ግን ህገ መንግስትን የሚጥስ አይደለም ብለዋል፡፡ ባለፈው አመት በባህርዳር በተካሄደ የኢህአዴግ ጉባኤ፣ በመንግስት ሚዲያዎች ላይ የመንግስትን ብቻ እንጂ የህዝብን ሃሣቦችና ጥያቄዎችን አያስተናግዱም በማለት ፓርቲው ላይ ከፍተኛ አመራሮች ትችት መሰንዘራቸው ይታወሣል፡፡ የድርጅቱ ቦርድ ለፓርላማ ባቀረበው ሪፖርት፤ 118 ቅርንጫፎችና ከ470 በላይ ጋዜጠኞች እንዳሉት ቢገለጽም የአቅም እጥረት እንዳለበት ጠቅሷል፡፡ በግማሽ ዓመት ውስጥ ድርጅቱን ከለቀቁ 140 ገደማ ሠራተኞች መካከል 28ቱ ጋዜጠኞች ናቸው፡፡ በዝቅተኛ ደሞዝ እና ምቹ ያልሆነ የሥራ ሁኔታ ሳቢያ ሠራተኞች ድርጅቱን እንደሚለቅቁ ቦርዱ ገልጾ፤ የድርጅቱ መንታ መዋቅርም ችግር ፈጥሯል ብሏል፡፡

“በቤተክርስትያናችን ሽፍጥና ጉቦ ተንሰራፍቷል”
ሰንበት ት/ቤቶቹ የአማሳኝ አስተዳዳሪዎችን ዶሴ ለፓትርያርኩ ለማቅረብ ተዘጋጅተዋል

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ በተንሰራፋው ሙስናና ሸፍጥ ላይ በተጠናከረ ኃይል በመዝመት የተጀመረውን የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ከዳር እንዲያደርሱ አዘዙ፡፡ አቡነ ማትያስ ትእዛዙን የሰጡት ሙስናና ብልሹ አስተዳደርን በሥር ነቀል የእርማት ርምጃዎች ለማስተካከል ያስተላለፉትን መግለጫ ለመደገፍና የፓትርያርኩ ልዩ ሀ/ስብከት የኾነው የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ያዘጋጀው የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ጥናት ተግባራዊ እንዲኾን ለመጠየቅ ከትላንት በስቲያ ኀሙስ፣ ጥር 8 ቀን 2006 ዓ.ም. በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ለተሰበሰቡት በሺሕ ለሚቆጠሩ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በሰጡት መመሪያ፣ ቃለ ምዕዳንና የበዓለ ጥምቀት ቡራኬ ነው፡፡

ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት 160 ገዳማትና አድባራት የተሰበሰቡት 1800 ያህል የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በሀ/ስብከቱ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሥራ አመራር አማካይነት ባወጡት መግለጫ፤ ፓትርያርኩ ሙስናና ብልሹ አስተዳደርን በማውገዝ ለማስተካከል አበክረው ሥራ በመጀመራቸው ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ ብዙኃን የሰንበት ት/ቤት አባላት አይነኬ ኾኖ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሲያስተቻት የቆየውን ሙስናና ብልሹ አስተዳደር ስከ እስር ደርሰው ሲታገሉት እንደቆዩም ተናግረዋል፡፡ የሙስናና ብልሹ አስተዳደር ተጠቂ እየኾኑ በማደጋቸው አስከፊነቱን በሚገባ እንደሚያውቁ በመግለጫቸው ያተቱት የሰንበት ት/ቤት ወጣቶቹ፤ ፓትርያርኩ በየጊዜው ያስተላለፏቸውን መመሪያዎች በመከታተልና የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ለአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ ስለ ሚያደርገው እንቅስቃሴ በመወያየት ችግሩ ከመሠረቱ እንደሚወገድና በዘመናቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር ትንሣኤ እንደቀረበ መገንዘባቸውን ገልጸዋል፡፡ ሙስናንና ብልሹ አስተዳደርን ለማረም የሚካሔደው እንቅስቃሴ በእነርሱም በወላጆቻቸውም ጽኑ እምነትና አቋም እንደተያዘበት የጠቀሱት ወጣቶቹ፤ ጥረቱን ከግቡ ለማድረስ ከፓትርያርኩ ጎን ቆመው በታዘዙበት መሥመር ለመሰለፍ ዝግጁ መኾናቸውን አስታውቀዋል፡፡

‹‹የፀረ ሙስና እንቅስቃሴውን እንደግፋለን ብላችኁኛል፤ እኔም እንደምትደግፉኝ አምናለኹ፤›› በማለት ተስፋቸውን የገለጹት ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በበኩላቸው÷ ‹‹ዘመኑ የእምነት ጉድለትና የኑፋቄ ነው፤ ሐቅ፣ መልካም አስተዳደር፣ እውነተኝነትና ሓላፊነት ጠፍቷል፤ በቤተ ክርስቲያናችን ሸፍጥና ጉቦ ተንሰራፍቷል፤›› ሲሉ አምርረው ተናግረዋል፡፡ ስለሙስናና ብክነት ከሚሰጧቸው ተደጋጋሚ መግለጫዎች ጋር ተያይዞ ‹‹ኹላችንም ሌቦች ተብለናል›› የሚል ቅሬታ ያቀረቡላቸው ወገኖች መኖራቸውን ያልሸሸጉት አቡነ ማትያስ፤ ‹‹የሚያመው ያመው ይኾናል፤ ሁላችኁም አማሳኞች ናችሁ የሚል አልወጣኝም፤ የሚያማስኑ እንዳሉ ግን ሐቅ ነው፤›› ሲሉ የችግሩ አስከፊነት ሊካድ እንደማይገባው አረጋግጠዋል፡፡ ሙስና ማለት ጥፋት ነው ሲሉ የቃሉን ትክክለኛ ንባብና ገላጭነት ያብራሩት ፓትርያርኩ፣ ‹‹በቤተ ክርስቲያን ያለው የሙስና ሙስና›› መኾኑን በመግለጽ፣ በፀረ ሙስና ቅስቀሳው የሰንበት ት/ቤት ወጣቶቹ በይበልጥ እንዲዘምቱበት አሳስበዋቸዋል፡፡ ‹‹ተይዞ ባለው የፀረ ሙስና ቅስቀሳ እናንት የሰንበት ት/ቤት አባላት በይበልጥ ብትዘምቱበት፤ በተጠናከረ ኃይል ይህን ብትረዱኝና ከዳር ብናደርሰው አመሰግናችኋለሁ፡፡›› በተያያዘ ዜና÷ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን የአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ እንቅስቃሴ የሚበዙት የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የጽ/ቤት ሠራተኞች፣ ማኅበረ ካህናት፣ ማኅበረ ምእመናንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች እንደሚደግፉት እየተገለጸ ቢሰነብትም ‹‹ምእመናን በእኛ ሕግ ምን ያገባቸዋል፤›› የሚሉ አንዳንድ አስተዳዳሪዎች ቅሬታቸውን ለፓትርያርኩ ማቅረባቸውን የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

እንደምንጮቹ መረጃ፣ ቅሬታ አቅራቢ አስተዳዳሪዎቹ የመዋቅር ለውጡን የሚቃወሙ ሲኾኑ ከእነርሱም መካከል ለአደረጃጀትና አሠራር ለውጡ በተከታታይ የተካሔዱት የድጋፍ መግለጫ ስብሰባዎች ምእመናኑን በእነርሱ ላይ ኾነ ተብሎ ለማነሣሣት የታለሙ ናቸው ብለው ያምናሉ፡፡ ሰንበት ት/ቤቶቹ ከፓትርያርኩ ጋር ባካሔዱት ውይይት፣ ሙስናና ብልሹ አስተዳደርን በግልጽ በመቃወማቸውና በማጋለጣቸው ያሳሰሯቸውና ያስደበደቧቸው አስተዳዳሪዎች እንዳሉ ተገልጧል፡፡ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶቹ የቤተ ክርስቲያንን ሀብትና ንብረት ለግል ጥቅም በማዋልና ለባዕድ አሳልፎ በመስጠት አላግባብ በልጽገዋል የሚሏቸውን አማሳኝ አስተዳዳሪዎች ዶሴ ለፓትርያርኩ ለማቅረብ፣ እንደ ሕጉ አግባብም ለፀረ ሙስና ኮሚሽን ለማመልከትም ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን ከአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሥራ አመራር አባላት ተጠቁሟል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ የጥቅምት ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ÷ ቤተ ክርስቲያኒቱ ‹‹የሃይማኖት ዕንከን ሳይኖርባት፣ ሞያ ሳያንሳትና ተቆርቋሪ ምእመናን እያሏት›› በመልካም አስተዳደርና በፋይናንስ አያያዝ ምክንያት የምትወቀስበትና ልጆቿን የምታጣበት ታሪክ መገታት እንዳለበት የገለጸ ሲሆን የቤተ ክርስቲያኒቱን የአገልግሎት አፈጻጸም እሴቶችና መርሖዎች የሚገልጸው መሪ ዕቅድ ከገመገመ በኋላ ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦትን ከሥሩ ለመቅረፍ በሚያስችል አኳኋን ተዘጋጅቶ እንዲቀርብለት መመሪያ መስጠቱ ይታወሳል፡፡

ተማሪዎች ያለዕድሜያቸው ጫት፣ ሲጋራና ልቅ ወሲብ ይጀምራሉ
ሴት የቢሮ ሠራተኛ ሴቶች በወሲብ ንግድ ኑሮአቸውን ይደጉማሉ

በአዲስ አበባ ከአንደኛ ደረጃ እስከ ከፍተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የሚማሩ ተማሪዎች፤ ለከፍተኛ የስነ ምግባር ጉድለቶች እንደተጋለጡ ጥናቶች አመለከቱ፡፡ ሰሞኑን የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ከባለድርሻ አካላት ጋር “ስነምግባር ለእድገት ሁሉ መሠረት ነው” በሚል ርዕስ ባዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ በቀረቡት ጥናቶች በተለይ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች፤ በየትምህርት ቤቶቹ አካባቢ ባሉ ህገወጥ የአልኮል፣ የአደንዛዥ እጽ መጠቀሚያ እና የወሲብ ፊልሞች ማሣያ ቤቶች መበራከት የተነሣ ለችግሩ ተጋላጭነታቸው በከፍተኛ ደረጃ መጨመሩ ተጠቁሟል፡፡ አብዛኞቹ ተማሪዎች ወሲብ መፈፀም የሚጀምሩት በዚሁ የትምህርት ደረጃ ላይ እያሉ ነው ተብሏል፡፡ ከጥናት አቅራቢዎቹ አንዷ የሆኑት ወ/ሮ ጽዮን አክሊሉ በጥናታቸው እንዳመለከቱት፤ ተማሪዎች ሲጋራ፣ የአልኮል መጠጥ፣ ጫት እና ልቅ ወሲብ የሚጀምሩት በአብዛኛው ሁለተኛ ደረጃ ከገቡ በኋላ ሲሆን 41.5 በመቶ የሚሆኑት የሁለተኛ ደረጃ ተማሪ እያሉ ሲጋራ ማጨስ እንደሚጀምሩ ጠቅሰው፤ 67.1 በመቶ ያህሉ ደግሞ በዚህ የትምህርት ደረጃ ወሲብ መፈፀም ይጀምራሉ ብለዋል፡፡

18.1 በመቶ የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎችም ያለ እድሜያቸው በሲጋራ ሱስ የሚጠመዱ ሲሆን 20.6 በመቶዎቹም በዚህ የእድሜ እርከን ውስጥ ወሲብ መፈፀም እንደሚጀምሩ ተጠቁሟል፡፡ የአልኮል መጠጥ እና የጫት ተጠቃሚነትን መጠን በተመለከተ ከሌሎች የትምህርት ደረጃዎች ይልቅ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች በከፍተኛ ደረጃ የድርጊቱ ጀማሪዎችና አዘውታሪዎች እንደሆኑ ጥናቱ ይገልፃል፡፡ በጥናቱ ከተካተቱ ተማሪዎች መካከል 51.4 በመቶዎቹ የአልኮል ተጠቃሚነትን የሁለተኛ ደረጃ ተማሪ እያሉ የጀመሩ ሲሆን፤ 27.2 በመቶዎቹ ደግሞ የአንደኛ ደረጃ ተማሪ እያሉ ጀምረዋል፡፡ 44.6 በመቶ የሚሆኑት ጫት የጀመሩት የሁለተኛ ደረጃ ተማሪ እያሉ ሲሆን፤ 15.1 በመቶዎቹ ደግሞ የ1ኛ ደረጃ ተማሪ እያሉ መጀመራቸው ታውቋል፡፡ በተለይ የአንደኛ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች በከፍተኛ መጠን ያለእድሜያቸው ለአጓጉል ድርጊቶች መጋለጣቸው፣ በስነምግባር የታነፁ ዜጐችን በማፍራት ረገድ አገሪቱ ፈታኝ ሁኔታ ላይ እንደምትገኝ አመላካች ነው ብለዋል - ጥናት አቅራቢዋ፡፡ እጽና አልኮል መጠቀም፣ ልቅ ወሲብ ከመፈፀም ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት እንዳለው ያመላከቱት አጥኚዋ፤ በተለይ ለችግሩ ይበልጥ ተጋላጭ የሆኑት የከተማ ልጆች ሲሆኑ ወላጆቻቸው የተማሩ የሚባሉና ከፍ ያለ የገንዘብ አቅም ያላቸው እንደሆኑ ጠቅሰዋል። ከገጠር አካባቢ የሚመጡ ተማሪዎች በአንፃሩ የገንዘብ አቅማቸው አነስተኛ በመሆኑ፣ አልኮልና እፆችን እንዲሁም የወሲብ ተግባራትን እንደልባቸው ለመፈፀም እንደሚቸገሩ ተጠቁሟል፡፡

በእነዚህ የትምህርት ደረጃዎች ያሉና የአቻ ግፊት ሳይበግራቸው ከእነዚህ ሁሉ ሱሶች ነፃ ሆነው የተገኙት ለስነ ምግባራቸው መታነጽ ምክንያቱ፣ በወላጅ ምክር ያደጉና የሃይማኖት ጥንካሬ ያላቸው መሆኑን ያመለከቱት ጥናት አቅራቢዋ፤ የሃይማኖት ተቋማት በዚህ ረገድ ጠንካራ ስራ ለመስራት ቢሞክሩ የበለጠ ውጤት ማምጣት እንደሚቻል ጠቁመዋል፡፡ በእኚሁ ጥናት አቅራቢ የቀረበው ሌላው ርዕሰ ጉዳይ በጐልማሶች ላይ ያተኮረ ሲሆን በሀገራችን ከ150ሺህ በላይ ሴተኛ አዳሪዎች እንዳሉ ቢገመትም በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ደረጃ ሴት የቢሮ ሠራተኞች እና ተማሪዎች በወሲብ ንግድ ተሰማርተው በአቋራጭ ተጨማሪ ገቢ እያገኙ ኑሮአቸውን እየደጐሙ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ለዚህ ልማድ መስፋፋት ደግሞ ባለሃብቶችና በእድሜ የገፉ ሰዎች አማጋጭ እየሆኑ መምት፣ የመዲናዋ የቱሪስቶችና ዓለማቀፍ ክንውኖች ማዕከልነቷ ማደጉና የጥበብ ውጤቶች ስለ ወሲብ የተዛባ አመለካከት ይዘው ብቅ ማለታቸው በምክንያትነት ተቀምጧል፡፡ ማሣጅ ቤቶችና ራቁት የዳንስ ቤቶች ወሲብ ንግድ መስፋፋቱ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውም በጥናቱ ተጠቅሷል፡፡

ለእነዚህ ሁሉ የስነምግባር ጉድለቶችና ማህበረሰባዊ እሴቶች ውድቀት የህግ ክፍተት መኖሩ ትልቅ ሚና እንዳለው ባይካድም፣ በመንግስት ሚዲያዎች ሳይቀር የሚተላለፉ የማስታወቂያ መልዕክቶች፣ የቃላት አመራረጥና የፕሮግራም አቅራቢዎቹ አለባበስ፣ የመረጃዎች ፍሬ ሃሳብ እና ስነ ምግባር የጐደላቸው ጽሑፎች በስፋት መስተናገድ አስተዋጽኦ አበርክተዋል ተብሏል፡፡ ሌላው ጥናት አቅራቢ አባ በአማን ግሩም የተባሉ የሃይማኖት አባት በበኩላቸው፤ ከቤተሰብ እስከ አገር አቀፍ ደረጃ የመከባበር እሴት መጥፋት፣ ማታለልና ሙስና መስፋፋት ለትውልዱ በስነምግባር አለመታነጽ እንደምክንያት ካቀረቧቸው መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ ይሄን ለመቀየር ከሃይማኖት መሪዎችም ሆነ ከመንግስት የስራ ሃላፊዎች የአርአያነት ተግባር እንደሚያስፈልግ የጠቆሙት አባ በአማን፤ እነዚህ አካላት የትውልዱን ስነምግባር በማነጽ ረገድ ያላቸው ሚና እንዲጐላ ቢደረግ መልካም ነው ብለዋል፡፡ ምቀኝነት፣ ውሸት፣ ሃሜት፣ ስርቆት፣ ሙስና፣ የህፃናት ጉልበት ብዝበዛ፣ አስገድዶ መድፈር፣ የአደንዛዥ እፅ ዝውውርና ተጠቃሚነት እንዲሁም ሽብርና ጦርነት በዓለም ላይ መበራከታቸው ለስነምግባር እሴቶች መጓደል ምክንያት መሆኑን የዘረዘሩት ሌላው ጥናት አቅራቢ ሐጂ አብዱልሃማድ አቡበከር፤ መንግስት እና የሃይማኖት ተቋማት እንዲሁም ማህበረሰቡ በጋራ ኢትዮጵያውያን ወጣት ተማሪዎች ከእነዚህ የስነምግባር ጉድለቶች የሚርቁበትን አቅጣጫ ማሳየት እንደሚገባቸው አስረግጠው ተናግረዋል፡፡ የከተማው የትምህርት ቢሮ ሃላፊ አቶ ዲሳሞ ኦቶሬ በበኩላቸው፤ ተማሪዎችን ከአልኮል፣ አደገኛ እጽ፣ ጫት እና ከወሲብ ሱስ ተጋላጭነት የራቁ ለማድረግ ቢሮአቸው የተለያዩ የድርጊት መርሃ ግብሮችን ቀርፆ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አመልክተዋል፡፡ ከተለያዩ የባለድርሻ አካላት ጋር በመሆንም፣ ለእነዚህ መጤ ልማዶች መስፋፋት ምክንያት የሆኑ የንግድ ቤቶች ከትምህርት ቤቶች አካባቢ የሚርቁበትን የወሰን መጠን የሚያስቀምጥና ህጋዊ ክልከላ የሚያደርግ ህግ እየተረቀቀ እንደሆነ በቢሮው ሃላፊዎች ተገልጿል፡፡

ፈጣሪ በየትውልዱ የራሱን ድምጽ ያወጣል
ፍቅር ያሸንፋል-- የኔ ሳይሆን የትውልድ ድምጽ ነው
እዳ አለ የምንል ከሆነም፤ እዳ የሚከፈለውና የሚሸፈነው በፍቅር ብቻ ነው

“ከታሪክ ከወረስነው ቂም ይልቅ የምናወርሰው ፍቅር ይበልጣል”

የፍቅር ጉዞ ከሚለው ሃሳብ እንጀምር፡፡

መነሻው ምንድነው? “አቦጊዳ ብዬ፣ ፊደል “ሀ”ን ቆጥሬ፤

የፍቅርን ትርጉም ለልቤ አስተምሬ፣

ይዤሽ በአኮፋዳ እንደቆሎ ተማሪ፣

አቦጊዳ ልበል የፍቅር ጀማሪ…”

እንዲህ ነው የኔ የዘፈን ህይወት የሚጀምረው። አሁን የፍቅር ጉዞ ላይ ደርሷል፡፡ ሁላችንም፣ በተለያዩ የታሪክ አጋጣሚዎች ውስጥ እናልፋለን። ብዙ ቅሬታና ብዙ ደስታ፣ ብዙ ትክክል የሆኑ ነገሮችና ብዙ ትክክል ያልሆኑ ነገሮች አሉበት - ያለፍንበት ታሪክ፡፡ ትልቁ ነጥብ፣ ካለፍንበት ታሪክ ተነስተን ለሚቀጥለው ጊዜ ምን እናድርግ የሚለው ነው፡፡ ያዘንበትን ነገር በይቅርታ ሰርዘን፣ የወደድነውን ነገር ደግሞ አሳድገን ለመጓዝ፣ ትልቁ መድሃኒት ፍቅር ነው፡፡ ይቅር ተባብሎ የቀድሞ ስህተቶችን ለማስተካከልና በህብረት ተጠራርቶ የቀድሞ ትክክለኛ ነገሮችን ለማሳደግ፣ ፍቅር ያስፈልጋል፡፡ አቡጊዳ ብለን ነው ፍቅርን የምንጀምረው፡፡ “ዳህላክ” ላይም፣ ለልጆቻችን ቂምን አናውርስ ብለናል፡፡ “ካስተማርሽው ፍቅርን በጊዜ፣ አይሻለሁ ወይ ባሱ ጊዜ…” ኢትዮጵያና ኤርትራ ተራርቀው የተፈጠረው ግጭት የሩቅ ጊዜ ታሪክ አይደለም። የብዙዎችን ህይወት በቀጠፈው ግጭት፣ ብዙ የተበተነ ቤተሰብ፣ የደማ ስሜት አለ፡፡ ይሄ ቁስል ዘላለም እንደመረቀዘ መቀጠል አለበት? መዳን መፈወስ የለብንም? ይቅር መባባልን ነው በ“ያስተሰርያል” የዘፈንነው፡፡ ለምንወልዳቸው ልጆች፤ ለምንፈጥራቸው አዲስ ትውልዶች የምናወርሰው ቂምን ከሆነ፣ ያለፈው መቁሰል ሳይበቃ ለወደፊትም ሌላ አደጋ እንዲፈጠር እየተባበርን ነው ማለት ነው፡፡ የሚሻለው መፍትሔ፣ እኛ የወረስነው አለመግባባት ካለ፣ በቂም ሰበብ የተቋሰልነው ነገር ካለ፣ የአዲሱን ትውልድ ህይወት እንዳያውክ፣ እኛ ጋ መቆም አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡

የዘመናችን ፈተናዎች ሳያንሱ፣ የቅርብ ጊዜ የቂም ታሪክንም እየተሸከመን፣ ከዚያም አልፎ የሩቅ ጊዜ የቅሬታ ታሪኩንም እየቆሰቆስን ቂምን የምናወርስ ከሆነ፣ ለማናችንም ሕይወት የማይጠቅም፣ የልጆቻችንንም ተስፋ የሚያጨልም አደጋ እየፈጠርን እናልፋለን፡፡ ቂምን መሻር፣ ቁስልን መፈወስ፤ ከዚያም አልፎ ለሁላችንም የሚበጅና የተስፋ ብርሃንን የሚያደምቅ ነገር መስራት የምንችለው በፍቅር ነው፡፡ ከ “አቡጊዳ” እስከ “ያስተሰርያል”፣ “ዳህላክ”፣ ቀላል ይሆናል”…እና ሌሎች ዘፈኖች ይህንን መልዕክት ያስተላልፋሉ፡፡ ግን ልዩ አዋቂ ስለሆንኩ ወይም ልዩ ሃይል ስላለኝ አይደለም፡፡ በፈጣሪ ሃይል ነው። ፈጣሪ በየትውልዱ የራሱን ድምጽ ያወጣል። የትውልዱን ድምጽ በኔ አድርጐ ማውጣቱን አምናለሁ፡፡ አሁን፣ ቅን እና ጥሩ ትውልድ አለ፡፡ የዚህ ቅን ትውልድ ድምጽ የፍቅር ድምጽ ነው። ግራ የሚያጋቡ፣ የሚያስጨንቁና የተተበተቡ ችግሮች ሁሉ በፍቅር ይፈታሉ፡፡ ከቂም፣ ከቁስል በፍቅር እንዳን፣ ፍቅር ያሸንፋል የሚለው መልዕክት የኔ ሳይሆን የትውልድ ድምጽ ነው፡፡ ይህ ቅን ትውልድ ተቀራርቦ፣ ተሰባስቦ አንድ ላይ የፍቅር ድምፁን የሚያስተጋባበት እንዲሆን ታስቦ የተዘጋጀ ነው የፍቅር ጉዞ፡፡

በፖለቲካም ሆነ በሌላ ምክንያት፣ በተለያየ ችግርና አለመግባባት በአገራችን ለተከሰተው ቂምና ቁርሾም፣ እዚህ አገር ቤትም ሆነ በየአገሩ ተበታትነው የሚገኙ ወገኖቻችን፣ ቢያንስ ለልጆቻቸው ሲሉ ይቅር መባባልን እንዲቀበሉ ለመጋበዝ፤ የአዲሱ ትውልድ ስሜትም ይሄ እንደሆነ የሚገልፁ ዝግጅቶችን ለማቅረብ ነበር ያቀድነው፡፡ ዝግጅቱን በተለያዩ የኢትዮጵያ ከተሞች በስፋት ለማዳረስ ነው፤ በሄኒከን ከሚተዳደረው በደሌ ቢራ ጋር ተነጋግረን ውል የተፈራረምነው፡፡ በተፈራረምንበት እለት እንደተገለፀውም፤ የቋንቋና የብሔር ስብጥር ውስጥ ህብረትና አንድነታችንን የሚያጠናክር፣ ቂም እንዳንወርስና መልካም መንፈስን ለመጋራት አንድ ላይ የሚጮህ የፍቅር አላማ ያለው ዝግጅት ነው፡፡ ግን፣ የኢትዮጵያ ታሪክም ሆነ የኢትዮጵያውያን ሕይወት አንተ እንደምትለው፣ በፍቅርና ሰላም ብቻ የተሞላ ሳይሆን፣ በቂምና በግጭትም የተበረዘ ነው፡፡

አይደለም? ምን ጥርጥር አለው! ያሉና የነበሩ ነገሮች ናቸው፡፡ የህይወት እና የደስታ ውድነት ትርጉም የሚኖረው ከሞትና ከሀዘን ጋር ነው፡፡ የፍቅር ውበት የሚጐላው፣ ከጥላቻ ጋር ሲነፃፀር ነው። ነገር ግን ያሳዘኑን ነገሮች ላይ ብቻ ስናተኩር፣ አዲሱንና የወደፊቱን ትውልድ ያውካል፡፡ እዳ አለ የምንል ከሆነም፤ እዳ የሚከፈለውና የሚሸፈነው በፍቅር ብቻ ነው፡፡ ፍቅር መድሃኒት ነው፡፡ የነገር ሁሉ መጀመሪያና መጨረሻ ነው፡፡ ሁላችንም ህፃናትን ማቀፍና መሳም የምንወደው ለምንድነው? ገና ሲወለዱ፣ ገና ከመነሻው ሲፈጠሩ ፍፁም ፍቅር ስለሆኑ ነው፡፡ ያ የፍቅር ሃይል ነው የሚስበን፡፡ ህፃኑም እናቱ ጉያ ውስጥ የሚገባው በፍቅር ሃይል ነው፡፡ እንኳን ሰውን የመሰለ ክቡር ፍጥረት ይቅርና አውሬ የምንላቸው እንስሳት ውስጥም የምናየው የተፈጥሮ ሃይል ነው፤ ፍቅር፡፡ ነገር ግን በኑሮ ውስጥ በብዙ ውጣ ውረድ፣ ብዙ ቅሬታዎችና እንከኖች ስለሚያጋጥሙን ፍቅራችንን ሊበርዙብን ወይም ውስጣችንን መርዘው የውስጥ ህመም ሊሆኑብን ይችላሉ፡፡ ባዘንበትና በተቀየምንበት ነገር ላይ ቆመን ተውጠን ስንቀር በሽታ ይሆኑብናል፡፡ ለቅያሜ እልባት እየሰጠንና እየሰረዝን ካልሄድን፣ ይባስ ብለን ለልጅ ልጅ እያወረስን ከቀጠልን፣ በማህበረሰብ ደረጃ እንደዝገት ውስጣችንን እየበላ ይጨርሰናል ወይም እንደተዳፈነ እሳት በሆነ አቅጣጫ ተግለብልቦ ያቃጥለናል፡፡

እና ምን ይሻለናል ብለን ስናስብ፣ በቀድሞ ዘመን ወይም ባለፍንበት ጊዜ የተፈፀሙ መልካም ነገሮችን ወይም ስህተቶችን እንዳልነበሩ ማድረግ አንችልም። ወደኋላ ተመልሰን በህይወት የሌሉ ሰዎችን መሸለም ወይም እዳ ማስከፈል አንችልም፡፡ እነሱ በዘመናቸው አልፈዋል፡፡ ነገሩ ያለው የዛሬ ነዋሪዎች ላይ ነው፡፡ በቀድሞ ሰዎች ታሪክ የምንደሰትበትና የምናዝንበት፣ ትክክል የሆኑና የተሳሳቱ ስራዎች፣ የወደድነውና የተቀየምንበት ነገር ይኖራል፡፡ ቀጥለው የመጡ ትውልዶች የትኛውን ስሜት መያዝ፣ የትኛውን ስሜት ማውረስ አለባቸው? እኛስ የትኛውን ወርሰን የትኛውን ማሳደግ አለብን? ቅሬታና ቂምን ይዘው ያወርሱናል ወይስ ፍቅርንና መዋደድን? ቅያሜና ቂም ብንወርስ ምን ይበጀናል? ወደ ኋላ ተመልሰን እዳ ማስከፈል አንችል? ህይወት የሚቀጥለው፣ ካለው ነገር ላይ በመነሳት ነው፡፡ ስህተቶችን ትተን፣ ትክክል የሆኑትን ይዘን፣ ያን እያሳደግን ነው መቀጠል ያለብን፡፡ ታላላቆቻችን በተለያዩ አለመግባባቶች ውስጥ ያልፋሉ፡፡ አለመግባባትና ቅሬታ ባይፈጠር መልካም ነበር፡፡ ነገር ግን ቢያንስ ቢያንስ፣ የታላላቆችን አለመግባባት ወደ አዲሱ ትውልድ እንዳይሻገርና መጪውን ጉዞ እንዳያውክብን፣ ታላላቆቻችን ስለ አዲሱ ትውልድና ስለመጪው ትውልድ መጨነቅ ያስፈልጋቸዋል ብዬ አስባለሁ። ፍቅር ያሸንፋል የሚለው የታናናሾች የአዲሱ ትውልድ ድምጽም ጐልቶ መሰማት እንዳለበት አምናለሁ፡፡ የፍቅር ጉዞ የዚህ የአዲሱ ትውልድ መንፈስ ነው፡፡ የፍቅር ጉዞ ዝግጅት ከበደሌ ቢራ ጋር ተፈራርመህ በሳምንቱ ነው ውዝግብ የተፈጠረው። እንዴት ነበር የሰማኸው? ከጊዜ በኋላ ነው የሰማሁት፡፡

አንደኛ በድሬዳዋ አንድ ተብሎ የሚጀመረው ጉዞ፣ ትልቅ የፍቅር መልዕክት የያዘ ስለሆነ፣ ያልተበታተነ ትኩረት ይፈለጋል፡፡ ከዚህ ውጭ ባለው ጊዜ ደግሞ፣ በሚቀጥለው መስከረም ወይም ብዙ ሳይቆይ አዲስ አልበም ለማድረስ የጀመርኩት ስራ አለ፡፡ ሁለቱም ቀናተኛ ስራዎች ናቸው፡፡ አእምሮህ ሌላ ነገር እንዲያስተናግድ አይፈቅዱልህም፡፡ በዚህ ምክንያት፣ ባልደረቦቼ በኢንተርኔት በተፈጠረው ውዝግብ ዙሪያ ሊያናግሩኝ ሲሞክሩ ስራ ላይ ሆኜ ብዙም ፈቃደኛ አልነበርኩም፡፡ ሲደጋገም ግን ሰማሁ፡፡ ማኔጀሬ (ዘካሪያስ) ተጨንቆ ነው የነገረኝ። ከሥራ አስኪያጅ አንፃር ሆነህ ስታየው መጨነቁ አይገርምም፡፡ ግን ተረጋግተን ነው የተነጋገርነው፡፡ አልተረበሻችሁም? ነገሩን አቅልለን አላየነውም፡፡ የፍቅር ጉዞ ትልቅ ዝግጅት ነው፡፡ ነገር ግን፣ በብዙ ወጣ ገባ መንገድ ከማለፍ እና ብዙ ውጣ ውረድ ከማየት የተነሳ፣ ችግሮችን ማስተናገድ ትለማመዳለህ፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ የፍቅር መልእክት፣ በቴዎድሮስ ካሳሁን የተፈጠረ ሃሳብ አይደለም፡፡ የነበረ ያለና የሚኖር የእግዚአብሔር ሃሳብ ነው፡፡ ያንተ ድርሻ ያ ሃሳብ ሲሰጥህ መቀበል ነው እንጂ፤ አንተ ከምትጨነቀው በላይ ከምንም አስበልጦ፣ ፈጣሪ ስለ አላማውና ስለሃሳቡ፣ ስለ እኛ እና ስለትውልዱ ስለሚጨነቅ፣ ብዙ አልተሸበርንም፡፡ ሁሉንም ነገር ለበጐ ያደርገዋል ብዬ አምናለሁ፡፡

“ጥቁር ሰው” በሚለው ዘፈንህ በአድዋ ጦርነት ዙሪያ ምኒልክንና ሌሎች የታሪክ ሰዎችን በማንሳት ዘፍነሃል፡፡ የምኒልክ ታሪክ ላይ ያለህን አስተሳሰብ በቅርቡ ቃለ ምልልስ አድርገህ በመጽሔት ታትሟል፡፡ ከዚህ ቃለ ምልልስ ጋር ተያይዞ ነው የምኒልክ ጦርነት ቅዱስ ነው የሚል አወዛጋቢው አባባል የተሰራጨው፡፡ በመጽሔት ታትሞ በወጣው ቃለምልልስ ላይ፣ እንደዚያ አይነት አባባል የለም፡፡ “አካሄዱን ያየ አመጣጡን ያውቃል” በሚል ርዕስ በእንቁ መጽሔት ታትሞ የወጣውን ቃለምልልስ ማየት ይቻላል፡፡ በምኒልክ መቶኛ የሙት ዓመት መነሻነት የተደረገ ቃለምልልስ ነው፡፡ በዚህ ቃለምልልስ ውስጥ ማንንም የሚያስቀይም አባባል የለበትም፡፡ ነገር ግን በኢንተርኔት ሲሰራጭ የኔ ያልሆነ አባባል ታክሎበት የተከፉ ሰዎች እንዳሉ ስሰማ፣ የተሳሳተውን መረጃ ለማስተካከል ምላሽ ሰጥተናል፡፡ እኔ ብቻ ሳልሆን፣ የመጽሔቱ አዘጋጅም አወዛጋቢው አባባል እኔ የተናገርኩት እንዳልሆነ፣ በመጽሔቱ ህትመት ውስጥም እንዳልነበረ አስረድቷል፡፡ ነገር ግን ውዝግቡ በዚህ አልተቋጨም፡፡ ለምን የፍቅር ጉዞን የሚያስተጓጉል ነገር ተፈጠረ አልልም፡፡ እዚህ ምድር ከተገለጡትም ሆነ ካልተገለጡት ሃይሎች ሁሉ የሚልቀው ፍቅር ነው፡፡ ክብደቱም የዚያኑ ያህል ነው፡፡

ስለዚህ የፍቅር ጉዞ ብለህ ስትነሳ፣ ያለ እክል እና ያለ ችግር ትደርሳለህ ማለት አይደለም፡፡ እንኳን ትልቁና ከባዱ ጉዞ ላይ ይቅርና፣ እንደ ቀላል የምናያቸው ጉዞዎች ላይም፣ ወደ ናዝሬት ወይም ወደ አዋሳ ለመሄድ ስትነሳ እንኳ፣ በመኪኖች መጨናነቅ ጉዞህ ሊጓተት ይችላል። ጐማ ቢተነፍስ ወይም ሞተር ቢግል፣ ጐማ ለመቀየርና የራዲያተር ውሃ ለመለወጥ መቆምህ አይቀርም፡፡ ከሁሉም የከበደው የፍቅር ጉዞ ላይማ፣ ለምን ፈተና ይፈጠራል ማለት አይቻልም። ከምንም በላይ ይቅር መባባልን የሚያበዛ የእርቅ መንፈስን ይዘህ ስትጓዝ፣ እንዲያውም ከተቻለ ታላላቆችህም እንዲግባቡልህና መግባባትን እንዲያወርሱ ስትጮህ፣ በዚህ ምክንያት ካንተ ጋር የማይግባባ ነገር ሲፈጠር፣ ነገሩን ንቀህ የምታልፈው አይሆንም፡፡ ምንም እንኳ፣ በተሳሳተ መረጃ ምክንያት የተፈጠረ ቅሬታ ቢሆንም፣ አንተም በተራህ የቅሬታ ባለቤት መሆን የለብህም፡፡ ፍቅር ሁሉንም ያቅፋል፡፡ በተሳሳተ መረጃ የተነሳ ያልወደደህንም ሰው ማቀፍ አለበት። የቃለምልልሱ ሁለተኛ ክፍል በሚቀጥለው ሳምንት ይጠብቁን፡፡

ዙምራ እና እኔ (የመጨረሻው ክፍል)

ከትንሿ የኤግዚቢሽን አዳራሽ ተቀምጨ ዙምራን ስጠብቅ ብዙ ጥያቄዎች በህሊናዬ ተመላልሰዋል፡፡ ዕውን በህጻንነቴ የአዋቂ አብራሄ - ህሊና /Enlightenment/ ነበረኝ ያለው ልጅ ከወሎ ጐጃም ጐንደር ሄዶ ማስተማር የፈለገው? ፈጣሪ አስመልክቶት ነውን ወይስ የአእምሮው ፍጥረት ነው አስተሳሰቡን የሰረፀበት? የሚለው ጥያቄ በአዕምሮዬ ግዘፍ - ነስቷል፡፡ ከአምስት አስተሳሰቦች /አስተምሮት/ በላይ እንዲሰፋ ይፈልጋል ወይስ አይፈልግም? መማር ለምን አልፈለገም? 6 ሚስቶች መፍታት ለምን አስፈለገው? የአካባቢው ህዝብ በጥላቻ ዓይን እንደሚያያቸው ካወቁ ለምን ግንኙነታቸውን ለማሻሻል አልፈለጉም? ከ8 በላይ ኮምፒዩተሮች አንድ ኤን ጂ ኦ የተሰጣቸው ካሉ፣ ከዓለም ጋር ያላቸው ግንኙነት ሊሰፋ መሆኑ ነው፡፡

ይህን እንዴት ያዩታል? … ወዘተ እያልኩ ከራሴ ጋር እጠያየቃለሁ… በመጨረሻ ዙምራ መጣ፡፡ ከገመትኩት በታች አጭር ነው፡፡ ቆፍጠን ያለ ነው፡፡ በልቤ በተለያየ አጋጣሚ ያወቅኋቸውን አዋቂዎችና ፈላስፋዎች፤ የሀይማኖት ፈጣሪዎች፣ በፈረንጂኛ Great Avatars የሚባሉትን ለምሳሌ:- እየሱስ ክርስቶስን፣ ቡድሃን፣ ዘሮስተርን እና ክሪሽናን ወዘተ ሌላው ቀርቶ፤ የአርሲ ፈረቀሳ መሪ የሆኑትን እሥር ቤት አግኝቻቸው የነበሩትን ቀኛዝማች ታየ መሸሻን ሳይቀር፤ ሃሣቤ ውስጥ አስገብቼ አውጠነጥናለሁ፡፡ አሁን የማየው የዙምራ ቁመት ከሁሉም ያጥራል፡፡ “እስቲ ስለልጅነትህ ንገረኝ?” አልኩት ሰላምታ ከተለዋወጥን በኋላ፡፡ በ64 ነው የጀመርኩት፡፡ በ4 ዓመት ዕድሜዬ ስለ ሰው ልጅ ማህበራዊ ኑሮ እንዳነሳሁ ከእኔ ቀድመው ያወቁት ይነግሩኛል፡፡ እናቴ ናት ዋናዋ፡፡ በልጅነቴ ያን ሁሉ ነገር ሳደርግ ለእኔ አትገልጥልኝም፡፡ “ሃሣቡ ከሰው ተለይቶ፣ ታሞ ነው” ትላለች፡፡ በየመድሀኒት ቤቱ ስትወስደኝ ነው የማውቀው፡፡ ግን አልዳንኩላትም፡፡

ከዚህ በ64 ዓ.ም እነሱን ሳገኝ ነው የረጋሁት፡፡ በ6 ወሩ ቆሞ ይሄድ ነበር ነው የምትለው፡፡ እኔ ቆሜ መሄዴን አውቃለሁ? አላውቅም፡፡ “ወደዚያ ሄደህ ያው የታወቁ ትላልቅ ሰዎች ማግኘትህን መቼም ታስታውሰዋለህ ብዬ ነው?” ሙሉውን ነው እማውቀው ሙሉውን! ተህጻንነቴ ጀምሮ ሃሣቡን ይዤው የምሄድ ስለሆነ አሁን የሚመራኝ ያው ሃሣብ ነው!፡፡ ተሃይማኖት አባቶች ቦታ እሄዳለሁ፡፡ ቤተክርስቲያንም መስኪድም … ሰው በተሰበሰበበት አደባባይ እሄዳለሁ … ሄጄ ግን ሁለት ሶስት አራት ጥያቄዎችን ነው የማነሳው፡፡ መቼም ተማያቸው እየተነሳሁ ነው ሰዎች ከሚሠሩዋቸው፣ ከሚናገሯቸው ….. ስላልተማርኩም ነው፤ ያስተማረኝ ባካባቢ የሚሠራው ህዝብ ነው፡፡ መጀመሪያ 4 ሀሣቦችን ነበር አንስቼ የነበረው፡፡ ኋላ ላይ ወደ 5 ሄደዋል። ይሄ በዙረት ነው፤ በ13 ዓመቴ፡፡ ውጪ በወጣሁ ጊዜ ግን አንድ ቦታ ላይ አንተ አንቺ ሲሉ አያለሁ። ሌላ ቦታ ላይ እርስዎ ሲሉ እሰማለሁ፡፡ አንቱታና አንተታ፤ አንድ ቦታ አንዱን ሽማግሌ ሰውዬ አንተ ሲሉ እሰማለሁ፤ እድሜ የማይመለከተውን ሰው ደግሞ አንቱ ሲሉ እሰማለሁ፡፡ አንቱታ ሥራው ምንድን ነው የሚል ጥያቄ አመጣሁ፡፡ ለክብር ነው ይሉኛል፤ ለክብርማ አይደለም፡፡ የላይና የታች ሰው መምረጥ የለበትም፡፡

ለክብር ቢሆን የመጀመሪያውን እድል እናትና አባት ይወስዱት ነበር፡፡ ከዚያም ቀጥሎ ዘመድ ይጋራው ነበር፡፡ ይሄ ከመነሻው ላይ ራሳችን በሰው ልጅ ላይ ልዩነት የፈጠርንበት ነው፡፡ ተሰባት ትውልድ በኋላ ባዕድ፣ ተሰባት ትውልድ በፊት ዘመድ፤ ብለን የፈጠርን ጊዜ፤ ለክብር ከሆነ ዘመድ ለምን ክብር አጣ? ነው ጥያቄዬ፡፡ “የራቀውን ባዕድ ሄደን አንተ ብንል ቀድሞ የጣልከኝን አሁን የት ታውቀኛለህ? የሚል ቁጣ ነው የሚያስነሳው፡፡ ዘመድ ዘንድ መጥተህ ደግሞ፤ አንቱ ብትል ያዝናል፡፡ እኔ ወንድምህ አደለሁ ወይ እንዴት አንተ ትለኛለህ ይልሃል፡፡” “እነዚያ ታላላቅ የተባሉት ሰዎች ካንተ ጋር ስለሃሳብህ ሲወያዩ የጨመሩት የለም፣ የቀነሱት የለም? የተለዩበት የለም?” “እነሱ ባይሰጡኝም እኔ እመልስላቸዋለሁ፡፡ የትኛው ነው ልኩ እላቸዋለሁ፡፡ ይህ ልክ ነው፤ “ግን ሰው አልሄደበትም የሚል ምላሽ ነው የሚሰጡኝ፡፡ አብሮ መሄድ አይቻልም፡፡ አንተ ግን ትክክክል ነህ” ነው እሚሉኝ፡፡ ስለዚህ ሁኔታውን ያዙት ብያቸው እሄዳለሁ … በ13 ዓመቴ ነው የሄድኩት … ዕብድ ነው ታሟል ተብሎ ነበር እሚባል በእናቴ በኩል፡፡ ከ4-13 ዓመት ተቤተሰቤ፣ ተዚያም ከህ/ሰቡ ጋር ነበርኩ፡፡” “በ13 ዓመቱ ኬት አመጣው ?ብለው ነዋ የማይሰሙት” አልኩ ለማስረገጥ፡፡ “ዕብድን ማን ያደምጣል? እሃይማኖት አባቶች ጋ ሄጃለሁ፡፡

ግን ብዙ ነገር አለ፤ መግለፅ የማልችለው እዚህ ውስጥ .. /በእስልምና በኩል ትንሽ ቅር የሚለኝ አለ/ በኦርቶዶክስ በኩል ግን በ13 ዓመቴ ነው እሚሉት እስከ 15 ዓመት ድረስ፡፡ ሁሉን ነገር ጨርሼ ተስፋ ቆርጨ፣ ጠይቄ አብቅቻለሁ፤ እሆነውን ሆኛለሁ። በኦርቶዶክስ በኩል ያገኘኋቸው ሊቅ አዋቂዎች ማን ይሄኮ የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ነው የሚሉት እንዴት አመጣሽው? ከምን አገኘሽው አዕምሮው ባልፈቀደው ልጅ እንዴት መጣ? እና ሲያዩኝ ምግብ የለም፤ ምን የለም ዝም ብዬ ነው እምሄደው፡፡ ከሣምንት ከአሥራምስት ቀን ምግብ ባገኝ ነው ዝም ብዬ ነው እምሄደው፡፡ አሁንም እኔ የፈጣሪ ስዕል ነው ብዬ ነው እምሄደው … የእኔ ስዕል አይደለም። ያን ኩሉ ተቋቁሜ መሄድ አልችልም ነበር የእሱ ስዕል ባይሆን! ባንድ በኩል አሳዝናቸዋለሁ፡፡ ባንድ በኩል ደግሞ “እንዴት እቺ ልጅ በፈጣሪ ሥራ እንዴት ገብታ ትቸገራለች” ይላሉ፡፡ በእዝነት ነው እሚያዩት፡፡ በክብር ነው እሚያዩት! በጣም ይገርማቸዋል! በሙስሊሙ በኩል ግን ከነቢዩ መሃመድ ጋር ነው እሚያይዙትም፤ ብዙም አይደለም ፍላጐታቸው አንዳንዶች ኦርቶዶክሶች እንዲያውም “በሕዝብ ያላወረድነውን የመጽሃፍ ቃል ነውኮ እምትናገረው” ይላሉ /አንቺ ነው የሚሉኝ/ … እሷ ይዛ ያለችው፡፡ “የእናትህ ማ/ሰብ ግን በሽተኛ ነው ነው የሚልህ?” “ስሙንም ያወጡልኝ እነሱ ናቸው፡፡...እና…” “ደህና ቤ/ሰብ ነበር ግን ቤተሰብህ? ሀብት ነበረው?” “እናቴ ካባቴ ጋር ሳለv ሀብት ነበራት፡፡ በጊዜው ጥሩ ሰዎች ነበሩ፡፡አባቴ በህጻንነቴ በ4 ዓመቴ ነው የሞተ፡፡

እስከ 13 ዓመቴ ድረስ እናቴ ጋ ነው የቆየሁ፡፡ ለእናቴ እኔ አራተኛ ልጅ ነኝ፡፡ ከበታችም ከበላዬም አሉ… ብቻዋን ነበረች እሷ ሀብት ቢኖርም!” “ወንድም እህት አለህ?” “እህት የለኝም ወንድሞች አሉ፡፡ እናቴ ሴት ልጅ አልወለደችም፡፡” “እነሱስ ስላንተ ምን ይላሉ?” “ታሁን በፊት ታሟል ይሉ የነበሩ፣ “ለካ አንተ አልታመምክም፤ የታመምነው እኛ ነን” የታመምን እኛ ነው! ሚሉ፡፡” “ወደ አውራምባ ታዲያ እንዴት መጣህ? ከዚህ እስቴ አደል የተመለስክ?” “እስቴ ላይ ተመለስኩ፡፡ እስቴ ሆኜ ወደ ትዳር ዓለም ገባሁ፡፡ በትዳር ዓለም እያለሁ እርሻ አርሼ፤ በጋ በጋ ላይ-ብቻዬን መኖር ስለማልችል፤ ሰው ፍለጋ እዞራለሁ፡፡ ለብዙ ዓመታት ከዞርኩ በኋላ እዚህ አካባቢ ሃሣቤን የሚያደምጥ ሰው ሳገኝ፣ በተደጋጋሚ መጥቼ ካስረዳሁ በኋላ እዚሁ መጥቼ ብቀመጥስ አልኩኝ፡፡” የተሻለ ህይወትም አገኛለሁ አልኩ” “ሚስትህንስ እንዴት አገባሀት ታዲያ!? አስተሳሰብህን ተቀብላህ ነው፤ ወይስ እንዲሁ መፈቃቀድ ነው?” “መጀመሪያ ገበሬ ስሆን አጋቡኝ፡፡ ባመቱ ምርቱ የደረሰ ጊዜ እኔ ያገኘሁትን ምርት በአካባቢ ላሉ ችግርተኞች ማካፈል፡፡ የእኔ ደስታዬ እሱ ነው፡፡ እሱን በማደርግ ጊዜ ሚስቴ መስጠቴን የማትፈልግ ሆነች፡፡ “አዬ ዕብድ ነው እያሉኝ ገብቼ! ዕብደቱ የእኔ ነው እያወኩ የገባሁት፤ ራሴ ነኝ እያለች እምቢ አለች፡፡ እሷን ተውሁና እኔ ወደዚህ ማህበረሰብ መምጣት ፈልግሁ፡፡ አሁን እዚሁ አድጋ የተወለደች ልጅ አገኘሁ፡፡

እያሉ ጥለውኝ ሄዱ፤ እነዚያ በዕብደቴ ጥለውኝ ሄዱ፡፡ እነሱ ሀብት ማካበት የሚፈልጉ ይመስለኛል። ምርት እስከሚመጣማ ደህና ነኝ፡፡ ምርቱን የምሰጥበት ጊዜ ነው እምንጣላ! እኔ ደግሞ ማካበት እምፈልገው ሰውን ነው፡፡ ለዕለት የምትለብሰውን ካገኘህ ሌላው ትርፍ ነው፡፡ እሚፈለገው ለጥቂቱ ነው፡፡” “ምን ይሉ ይሆን እነዚህ የፈታሃቸው ሴቶች?” “ዛሬ ላይ ነው?” “አዎ፡፡” “እንግዲህ አላገኘኋቸውም” “እኔ ባገኛቸው ጥሩ ነበር እጠይቃቸው ነበር?” “እኔም አላገኘኋቸው” “ለየት ያለ ባህሪ ነው እንግዲህ አኗኗራችሁ ነገሩ ማ/ሰቡ ባህሉ ለየት ያለ እንዲሆን አድርጐታል ይመስለኛል፡፡” “አዎ፡፡ እኔኮ በሰዎቹ አልፈርድም፡፡ እነሱ’ኮ አደሉም የገቡብኝ፡፡ እኔ ነኝ የተውኳቸው። እየተውኳቸው እሄዳለሁ፡፡ ተመልሼ መጥቼ ይሄ መሆን ነበረበት እላለሁ የምትለው፤ መሆን ያለበትማ አንተ እምትለው ነው፡፡ ግን እንዴት ይቻላል ነው” እሚሉኝ:: “ታዲያ ለምን ለማስፋፋት አልሞከርክም? ይሄ ነገር ከአውራምባ ለምን አልወጣም?” “ዕብድ ነው ተብያለሁ፡፡ ከ93 ወዲህኮ ነው መስፋፋት የጀመርነው፡፡ ተሰደን እኮ ነበር፡፡ የማህበሩ አባል በቁጥር የማይገኝ ነው፡፡ የማ/ሰቡ አባል የማህበሩ አባል ነው፡፡

እየበዛ ነው፡፡ የሃሣቡ ተካፋይ ነው ማ/ሰቡ፡፡” “ከአራቱ ሃሣቦች አምስተኛ ስድስተኛ ሰባተኛ እያልክ ለምን አልቀጠልክም ነው? አልመጣልህም?” “ሃሣቦቼ እንደሱ ሆኖ የተፈቀደልኝ ነው፤ እነሱኮ ብዙ ናቸው?” “ ሲመነዘሩ?” “አንደኛው የሴቶች እኩልነት ነው፡፡ ሴት በሴትነቷ እናት ናት፤ ወንድ በወንድነቱ አባት ነው፡፡ እኩል ናቸው፡፡ እሱ በቤቱ ገዢ ሆኖ አዛዥ ቢፈልግ እሚረግማት፣ ቢፈልግ እሚሰድባት፣ ቢፈልግ እሚደበድባት፣ ሲፈልግ ውጪልኝ ከቤቴ ብሎ አስወጥቷት እሚቀመጥ ለምን? ነው ጥያቄው፡፡ እናት በሌለችበት አባት የለም፡፡ አባት በሌለበት እናት የለችም፡፡ እኩል ናቸው ግን እሷን እንደሞግዚት ያደረግነው ለምንድነው?! በጉልበት ነው? አይደለም፡፡ አፈጣጠሩ እኩል ነው፡፡ ሌላው ህጻናቶችን በሚመለከት ነው ሥራ ሲሰጣቸው አያለሁ ያ ሥራ ሲጠፋባቸው ለምን አጠፋህ ለምን አበላሸህ? አርጩሜ ይከተላል፡፡ ለምን ይሆናል? ነው፡፡” “ከመግረፍ ይልቅ ታዲያ በምን መለወጥ ይቻላል? በነሱ አቅም ምን ይደረጋል?” “በአቅማቸው የሚሆን ነገር መስጠት፡፡ ከዚያም ምክር መስጠት ነው፡፡ እኛ ያልቻልነውን እነሱ አይችሉም፡፡ ተማርን ያልነው ዱላ ስናነሳ ምን ይዘው ያድጋሉ? እሱን ይዘው ነው ሚያድጉት፡፡ እና ለምን? ምን ዘርተን ምን ልናመርት እንፈልጋለን? ምርታችንን ከፍ እያደረግን ነው ከእኛ ይበልጥ እነሱ ይሸከማሉ ለምን ነው?” 3ኛው/ ባካባቢው የወደቁ አረጋውያን አሉ በእርጅና ጠንካራው ደካሞቹን እንዲያስተዳድራቸው፣ በልተው ጠጥተው አርፈው እንዲኖሩ ነው፡፡ እንደኛው ሰው ናቸው እኛ ትተናቸው ከሄድን ማን አላቸው፡፡

ለሰው ደራሹ ሰው ነው፡፡ እኛም አንድ ቀን እንወድቃለን፡፡ የሚረዳን የሚያስጠጋን እንፈልጋለን? እኛ እንደምንፈልገው ሁሉ እነሱም ያስፈልጋቸዋል፡፡ 4ኛው/ ሰውን ሰው ሲዋሸው፣ ሲሰርቀው፣ ሲዘርፈው፣ ሲደበድበው ይታያል፡፡ ለምን? ለራሳችን ሊደረግብን የማይገባ ነገር ለምን በሰው ልጆች ላይ እናደርጋለን ነው፡፡ ከሌሎች እንስሳት የተለየ ከሌለን ለሰውነታችን ምን መኖር አተረፍን? እሄን ባልኩ ሰው እንደሚያስበው አታስብም ይሉኛል የማይወጣ ጥጃ ከማሠሪያው ይታወቃል። ዕውነት አይደለም ወይ? “ዕውነትማ ዕውነታ ነው፤ ግን መሸከም አይቻልም” ይላሉ፡፡ 5ኛ/ ሌላው ቅድም ያልኩህ ነው የአንቱታና ያንተታ ጉዳይ፡፡ ትልቁ ሀብት ሰው መሆን አለበት ሌላው ሁለተኛ ነው፡፡ ሌላው ጠብ እስከናካቴው ተምድረ-ገጽ መወገድ አለበት፡፡ ሰላምን መስርተን ገነትን ፈጥረን መሄድ አለብን፡፡ ጠብ እንዴት ይኖራል? ትላለህ ነው ጥያቄው፡፡ ጠብን የምንሠራው እኛ ነን ከዚያ ይልቅ ፍቅርን ብንሠራ!” “ግን ተገንብቷል? ማህበረሰቦች የተገነባ ሥርዓት አላቸው በዚያ ውስጥ ጠብም ተገንብቷል፡፡ አሁን ጠብ አይኑር ብትለው ማንም እሺ አይል ፡፡ውስጡ ተገንብቷልና ልጆች ግን እንደ አዲስ ማስተማር ከያዝክ ቀላል ነው እሚሆነው፡፡ ምክንያቱም ልጆች ናቸው ጠብ እንደማይኖርና እንዳይኖር አድርገው ያድጋሉ፡፡

ጥሩ አርገህ ከተንከባከብካቸው ያን ይዘው ያድጋሉ፡፡ ህ/ሰቡ አንዴ የያዘውን ይዞ ታንጿል፡፡ ስለዚህ ለመለወጥ ሳይከብድ አይቀርም። አሁን ለምሳሌ አንተ ሄደህ ከፈላስፎች ጋር አትነጋገርም፡፡ የነሱ ሃሣብ ላንተ ያንተም ለነሱ ሆኖ ምናልባት ልትለውጣቸውም ከቻልክ ለምን አትለውጣቸውም? እዚህ አውራአምባ ውስጥ ብቻ በመኖር ተከልሎ መቆየቱ፣ ብዙ እድሜ እዚሁ እንዲቀር አያረገውም ወይ? አላስፋፋኸውም ማለቴ ነው፡፡ ወደ ህ/ሰቡ ማስተማር ለማደግ…” እያልኩ አቋረጠኝና ትንሽ ቆጣ ብሎ “የተማርነውን ይዘን ከዚህ ብንገባስ የአገኘነውን ይዘን ብንገባስ? እኔ ብቻ ሳልሆን ከኔ ብቻ ሳትጠብቁ የአገኘነውን ይዘን ብንሄድ ቤታችን ብንገባስ?” “እኔኮ እዚህ ድረስ መጥቼ ነው ያገኘሁህ? አንተ ወደህብረተሰባችን አልመጣህም!” “የእኔ እግር ተጠብቆ ነው ታዲያ?! ዓለም እምትድነው የእኔ እግር ተጠብቆ አይደለም፡፡ በአንድ አካባቢ በአንድ ሰው አንድ ሃሣብ ሲመነጭ የግለሰቡ ድካም ብቻ መሆን የለበትም፡፡ ያገሪቱ ንብረት ነው መሆን ያለበት! ያገሪቱ ንብረት ይሁን ታልን ደሞ ምሁሮች ናችሁ መረከብ ያለባችሁ፡፡ “ምሁሮች እንዲረከቡ መማር አለባቸዋ ፍልስፍናህን?” አዎ ምሁሮች ናቸው መረከብ ያለባቸው ምሁሮች ቁጣው እየጋለ ነው፡፡ “አዎ ምሁሮች ናቸው፣ ወደዱም ጠሉም መረከብ ያለባቸው፡፡ እነማናቸው? የሃይማኖት አባቶችም ይሁኑ፣ የቀለም ምሁሮች መረከብ አለባቸው! ተረክበው ወደ ሀገሪቱ እንዲሰርጥ ማድረግ የምሁሮች ፋንታ ነው! እንደመነጨህ አገሪቱን እየሄድክ አልብስ እሚሉት ፈሊጥ ነው ችግሩ! ከተገኘ አባይን አሁን በአገሪቱ እንውሰደው ብንል ማንም መውሰድ አይችልም፡፡ በራሱ መሄድ አይችልም፡፡ ቅብብሎሽ ካረግነው ግን ይቻላል፡፡ ምሁሮቹ ደሞ ጥሪውን አግኝተው ወደ ህዝብ የማያሰርጡ ከሆነ ያገኙትን ዕውቀት ያገራቸው ሀብት ለራሳቸው ብቻ ለምን ይሆናል ነው፡፡

ሀብት ጥሪት ሳይያዝ ምሁርነታቸው ምንድነው ነው? ተጠያቂ ናቸው! አይደለም በሉኝ አስረዱኝ ምሁርነታቸው ምንድነው? ስተት ነው በሉኝ ተምኑ ላይ? እኔም መማር አለብኝ፡፡ ነው ካልነ ለማን እንተወው ?መቼ ላደርሰው ነው ለህ/ሰቡ ማለት አለባቸው… አሁን ደርሷል በቴሌቪዥን፣ በራዲዮ፣ በመጽሔት፣ በጋዜጣ፣ በኢንተርኔት… ዓለምንም ሞልቷል፡፡ ንብረታችን ነው እንውሰደው። አለበለዚያ አንተ እየሄድክ እየተንቆረቆርክ አድርስ ከሆነ እምትሉ እኔ ቀጠልኩ፤ ስንፈት ወይም ቂመት ወይም ቅጥፈት ወይም ሽንፈት ነው ብዬ ነው እማስበው ሽንፈት ነው!!” በጣም ተቆጣ አሁን፡፡ “አሁን ሰዎች ተቀበሉት በኢንተርኔት እንበል። የራሳቸውን ጨመሩበት እንበል አንተ እሥሩ ከሌለህ፤ ኦርጅናሌው ሰው ከሌለህ፣ ነገ እየተዛባ ቢሄድ ማንም ሊከላከለው አይችልም፡፡ ስለዚህ፤ ወይ አንተ የማሳወቂያ መንገድ መፍጠር አለብህ ማለት ነው፡፡ እኔ ሳስበው ግን አንተ መጣጣር አለብህ። ሁልጊዜ እምለው፤ ለምን አይሰፋም? ለምን አዲስ ሃሣብ አልመጣለትም? ለምን አልጨመረም ዙምራ? እላለሁ፡፡ ከሰማሁ ቆይቻለሁ፤ እንደው ዕድሉን ባገኝና ባገኘው ይሄን እለዋለሁ ስል ነበር።” “እንዳንተው ለመፈለግ ያልፈለገ ሁኖ ነው። እንዳንተው፡፡ ከሰማህ ጀምረህ አልመጣህል፡፡” “ያለሁበት አይፈቅድልኝም ነበር፡፡ ፈቃደኛ ሳልሆን ቀርቼ ሳይሆን ሁኔታው አልፈቀደልኝም ነው የምለው፡፡” ዙምራ እየተቆጣኝ እየገነፈለብኝ ነው አሁን፡፡ “ማነው ተጠያቂ እሺ?” “ካልመጣሁ አዎ ተጠያቂ ራሴ ነኝ፡፡ አንተ አትሆንም… ግን ፈቃደኛ ስላልሆንኩ አይደለም… አሁን ለምሣሌ አንተ አውሮፖ ሂድ ብልህ አቅም ላይኖርህ ይችላል.. ግን አውሮጳ አንድ ፈላስፋ ይኖራል ያንተ አይነት አስተሳሰብ ያለው፡፡

ይህን ሰውዬ ባገኝ ጥሩ ነበር የማለት ሃሣብ ካለህ ብቻ ነው በጐ ፈቃደኛ የምትባለው፡፡ ግን… እሱም ለራሱ ነው እኔም የራሴ ነኝ ከሆነ መደጋገፋችን ቀርቷል፡፡ አንዱን ዓላማ ስተነዋል ማለት ነው፡፡ እኔ እምለው አንተ የምታውቀውን ካላካፈልክ ይጐዳል ሰው ላገርህ ነውና ጥቅሙ፡፡ ስለዚህ ወዳንተ መምጣት የሚችለው ይምጣ፡፡ አንተም ደግሞ የምትችለውን መንገድ ፍጠር! ያንተ አስተሳሰብ ቢሰፋ ማ/ሰቡ ይጠቀማል እንጂ አይጐዳም፡፡ ጥሩ አስተሳሰብ አለበትና፡፡ ዋናው ግን ማድረግ መሞከር አለብህ ነው ምልህ!” “በእኔነቴ ስዞር ስዞር ብዙ ቆይቻለሁ፡፡ ወይም እሚሰማኝ ባገኝ ብዬ ወይ የሚጠይቀኝ ብዬ … “ልክ ነው” “አሁን አይደለም፡፡ ኢትÄጵያ አፍሪካ ብናንኳኳ አውቃለሁ የሚል ብቻ ነው ያለው! ‘አውቆ የተደበቀ ቢጠሩት ወይ አይልም’ ነው፡፡ “ልክ ነው” “ተሰማ በኋላ ግን ይህ ነገር ንብረት ነው ብለን ለንብረት መቆርቆር ያለብን ሁላችንም ነን፡፡ ተቆርቁሮ ያልበረረ ሰው ነገር ብትግተው አይዋጠውም፡፡ ዛሬ ብዙ ቀጣፊ አሳማኞች ያሉበት ጊዜ ነው! በየደጃፉ እየቆረቆርክ ይሄ ምንድን ነው ብትለው፤ ሊሰማህ አይሻም፡፡ ምነው ብትል አውቆ…. “አውቆ የተኛ ነው!” “ሊክ! ‘አውቆ የተኛ ቢቀሰቅሱት አይነቃ’ ነው፡፡ የሆኑ ፈረንጆች ገቡ፡፡ ሰላም አልኳቸው፡፡ “አሁን አውራምባ ታውቋል፡፡ እነዚህ ሁሉ እሚመጡት ኢንተርኔት አስተዋወቀን እያሉ ነው…” “እኔም ስሄድ ላስተዋውቅ እሞክራለሁ” “እየጣፍክ በየሼልፉ ብታስቀምጥም ገልጠህ ዕቃውን ካሳየህ ዋጋ የለውም… መውሰድ አለብህ። ወስደህለት ካልወሰደ አይወሰድም … ይሄ ዕንቁ ነው ሀብታችን ነው ካልነው ግን ወደፈለቀበት ወደ ምንጩ ይመጣል፡፡ ወደቦታው ስንመጣ ነው እውነት የሚሆነው፡፡ ኑሮ እኖራለሁ ብዬ ባሰብኩ ኑሮዬን በሰው ልጆች ላይ ባደረኩ ነበር፡፡ የለም። አይሆንም፡፡ እና የእኔ ሃሣብ ይሄ ነው፡፡ ሌላው በኢንተርኔት እየታወቀ ነው፡፡ ገለጻዬን መስጠት ነው፡፡

አንድ አውቶቢስ ሰው እዚህ ቢመጣ አሁን፤ ብዙ ገንዘብ ይቀበላቸዋል፡፡ ያን ከማድረግ ይልቅ፤ እኔን ወደዚያ ወስደውኝ ሃሣቤን ብሰጥ መልካም ይሆን ነበር!” “ትክክል ነው አሁን ተግባባን!” “እሱ ነው መሆን ያለበት፡፡ ምንጩ እስከሚታወቅ ድረስ የለፋሁትን ልፋት ብታስብ፣ ይሄ ደጅ እንዴት ይታለፋል ሲሉ፣ አልፌ ሄጃለሁ፡፡ የእኔ ስዕል ሳይሆን የፈጣሪ ስዕል ነው፡፡ እዚያ ድረስ ሄጃለሁ፡፡ አሁን ላይ ግን ተጣቧል፡፡ ከጠበበ በኋላ ዝም ብለን እምናይ ከሆነ ተኝተናል፡፡ ምሁሮች ራሳችንን እያታለልን ነው የምንኖረው፡፡ ባናታልል ጥሩ ነበር፡፡ እኔ አንድ ነገር የማስበው አለኝ፡፡ እኔ ገበሬ ነኝ፡፡ ያንድ ገበሬ ሃሣብ ነው፡፡ በታሪክ ስናይ እየሱስ ክርስቶስንም እንውሰድ ነብዩ መሃመድንም እንውሰድ፤ ብዙ መማርና ትምህርት መውሰድ የነበረባቸው ሰዎች ጥላቻቸውን ተከናንበው ተኝተው ነበር፡፡ በዚያን ጊዜ በነበራቸው ሰዓት ጠይቀው ተረድተው ቢኖር ኖሮ ይሄ ሁሉ መከፋፈል ባልነበረ! ከራሳቸው ከባለቤቶቹ አንደበት ሰምተው ቢሆን ኖሮ ይሄ ሁሉ መከፋፈል ባልነበረ እነሱን አርቀን አርቀን ከገፋናቸው በኋላ፤ ጊዜያቸውን ሳይጠቀሙበት ካለፉ በኋላ መጽሐፍ ተጽፎ በስማ በለው አይሆንም፡፡ ….ነገር ሁሉ እሚበላሸው እንደዚህ እየሆነ ነው፡፡ …. እንዲያው ከሰማሁት ታሪኩን ልንገርህ ብዬ ነው፡፡ እኔ በየኢትÄጵያ ይሄን ምንጭ ይዘን ቁጭ እንበል፣ እንኑር ከሆነ ራስን መተቸት ነው…” “ግን የመማር ዕድል አልነበረህም? ለምን አልተማርክም?” “እስካሁን የተማርኩትስ “ፊደል ቆጠራውን ማለቴ ነው… “እውነት ካልከኝማ አለመማሬ ይቆጨኛል አንዳንዴ! አንደዜ ደግሞ አይቆጨኝም፡፡ “አንደዜ እሚቆጨኝ ምንድነው? መጣፍ ማሠራጨት ጥሩ ነበር…” “ልክ ነው” “ለራሴ መጣፍ አልችልም፡፡

ማንበብ አልችልም። ስላልተማርኩ ማለት ነው፡፡ እንግሊዝኛ ሲናገሩ እኔ ደንቆር ነኝ፡፡ አውቅላቸው ነበር እሚፈልጉትን፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ አይቆጨኝም። ለምን? አገራችን ምሁር አላጣችም፡፡ የት ነው የደረስነው ብዬ ሳስብ የትም አልደረስንም! አድቀናታል፡፡ ትልቅ ዳቦ ያማራቸው ሰዎች ሠርተው ያሳደጓት አገር ናት ኢትÄጵያ፡፡ እኔም ብማር ኖሮ አገሬን አደቃት ነበር እላለሁ፡፡” “ሌላ ጥያቄ አለህ?” “ጨርሻለሁ?” እኔ እምለው ነገር ነው እምለው ነው፡፡ ካልክ ምሁር ነህ ውሰደው፡፡ አይደለም ካልክ እምኑጋ እኔም ልማር!” “አመሰግናለሁ!” በልቤ አውራምባ ደግሜ መምጣት አለብኝ - አልኩ፡፡ የቀረኝ ነገር አለ፡፡ “ሰዎች ከሚሠሩት እያየሁ ነው የተማርኩት፤ በ4 ዓመቴ ነው አስተሳሰቡን የጀመርኩት፤ በላቸው አለ ዙምራ ለአስተርጓሚው፤ ለፈረንጆች እንዲነገርለት፡፡ ዕውነትም እንግሊዝኛ አለማወቁ፣ መቆጨቱ ልክ ነው እያልኩ በሆዴ፤ ወጣሁ፡፡ * * * እነሆ ለብዙ ሣምንታት፣ ከእየሩሣሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት (ኢህማልድ - JECCDO) ጋር ከአመሠራረታቸው ጀምሮ ልማታዊ ትሥሥር ያላቸውን ማህበረሰብ ተኮና ድርጅቶች (CBOs) (ማህበራትና እድሮች) ስጐበኝ ቆይቻለሁ፡፡ በዚህ ጉዞ ከደብረ ዘይት ጀምሬ፣ በናዝሬት አድርጌ፣ በአዋሳ አቋርጬ፣ ደብረ ብርሃንን አካልዬ በመካያው ባህርዳር ከትሜ፣ የአውራምባን ማህበረሰብ አይቼ አበቃሁ፡፡ የሀገር ልማትና ጥንካሬ በማህበረሰቦች ድርጅታዊና ማህበራዊ አቅም ላይ መመሥረቱን፣ ህዝብን መሠረት አድርጐ የሚጓዝ ልማታዊ እንቅስቃሴ ምንጊዜም ዘላቂነት አንዳለው፣ አስተውያለሁ፡፡

የከተማ ግብርና የህፃናት ትምህርት፣ የአረጋውያን እንክብካቤ፣ የጽዳትና የጤና አጠባበቅ ስልቶች፣ የሴቶች ልባዊ ተሳትፎ የአምራቾች የኅብረት ሥራ ቅስቃሴ በማህበረሰብ ቁጥጥር የሚመራ የገቢ ምንጭ ሀብቶች ጥራት በማህበረሰቡ በራሱ ይዞታዬ፣ ጉዳዬ ተብሎ ሲያዝ ምን ያህል ዘላቂና ለሀገር ልማት ልዩ ፍኖት ሊሆን እንደሚችል ተገንዝቤአለሁ፡፡ ይህን መሰል እንቅስቃ እንደአስፈላጊነቱና እንደአግባቡ ከመንግሥት ጋር እንዴት ተደጋግፎ ለመሥራት እንደሚቻልም ልብ ብያለሁ፡፡ እንደእየሩሳሌመ ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅትና ሌሎች መሰል ድርጅቶች ህብረተሰብን በማስተባበር፣ በማገዝና ራሱን እንዲችለና እንዲበቃ ከማቴሪያል ጀምሮ እስከ ከፋይናንስና ሥልጠና ድጋፍ በመስጠት፤ ማህበረሰቡ በሁለት እግሩ ሲቆምና ራሱን በራሱ ለማዝለቅ ሲችል፤ ጉዳያቸውን ጨርሰው በመውጣት (Phase – out በማድረግ) ዕድገትን ለማጠናከር እየተንቀሳቀሱ መሆኑን ያየሁበትን ጉዞ አብቅቻለሁ፡፡ ምናልባት በቦታና በጊዜ ጥበት ምክንያት የተውኳቸውን አያሌ አስገራማ ዝርዝር ሰዋዊ አሻራዎች፤ ሌላ ጊዜ በሌላ መልክ እጽፍላችሁ ይሆናል፡፡

“ሙዚየሙ ያለበት ግቢ በዲሞክራሲ ሂደት ላይ ጉልህ ሚና ተጫውቷል”

ሰዓሊ ግርማ ቡልቲ እና ሰዓሊ ቅድስት ብርሃኔ፤ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ለሚገኘው የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ሙዚየም አራት ስዕሎችን በስጦታ አበርክተዋል፡፡ በዕለቱ የሙዚየሙ ኃላፊዎችና ሠራተኞች እንደገለፁት፤ ተቋሙ ባለፉት 50 ዓመታት ለባህላዊ ስዕሎች ሰፊ ትኩረት ሰጥቶ ብዙ ሥራዎችን ያሰባሰበ ሲሆን አሁን ደግሞ ዘመናዊ ስዕሎችን ለማሰባሰብ ታቅዷል፡፡ ስለ ሙዚየሙ አመሠራረትና የሥራ ሂደት የሙዚየሙ ኃላፊ ከሆኑት ከዶ/ር ሀሰን ሰኢድ ጋር ቆይታ አድርጌያለሁ፡፡ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም አመሠራረት ታሪክ ምን ይመስላል? ሙዚየሙ እንዲቋቋም የመጀመሪያውን መሠረታዊ ሥራ የሰሩት የፖላንድ ተወላጅ የሆኑት ፕሮፌሰር ስታንስላቭ ሆይናይስኪ ናቸው፡፡ አይሁዳዊነት ስላላቸው በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወደ ካናዳ ሄደው በመማር ላይ ሳሉ ተጋብዘው ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጡት፡፡

ፕሮፌሰሩ ዩኒቨርስቲ ውስጥ ላይብረሪ እንዲያደራጁ ተጋብዘው በመጡበት ወቅት፤ በ4 ኪሎ ዩኒቨርስቲ ግቢ ያዩዋቸው ተማሪዎች፣ ከተለያዩ ክፍለ ሀገራትና ብሔረሰቦች የተውጣጡ መሆኑ አስገርሟቸው ስለነበር፣ ተማሪዎቹ ባህላቸውን የሚወክል ቁሳቁስ እንዲያመጡ እየጠየቁ ቅርስ ማሰባሰብ ጀመሩ፡፡ በ1955 ዓ.ም የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም ሙዚየም በ6 ኪሎ ዩኒቨርስቲ ግቢ ሲቋቋም ፕሮፌሰር ስታንስላቭ ሆይናይስኪ ያሰባሰቧቸው ቅርሶች ወደዚህ መጡ፡፡ ፕሮፌሰሩ የኢትዮጵያ ኢትኖሎጂ ሶሳይቲ መስራችም ናቸው፡፡ የሶሳይቲውን ጆርናልም ያዘጋጁ ነበር፡፡ ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ዳይሬክተር ሲሆኑ ፕሮፌሰር ስታንስላቭ ሆይናይስኪ ፀሐፊ ሆነውም አገልግለዋል፡፡ ተቋሙ በሁለቱ ሰዎች እየተመራ እስከ 1974 ዓ.ም ድረስ ዘልቋል፡፡ የተመሠረተበት ዓላማ ምን ነበር? ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን ማጥናት ርዕሰ ጉዳዩ በማድረግ ነው የተነሳው፡፡ ዛሬም የኢትዮጵያ ጥናት ምንድን ነው? ብለው የሚጠይቁ ሰዎች አሉ። የተቋሙ መሥራቾች ሲጀምሩ እንዳመኑበትና ዛሬም ብዙዎቻችን እንደምንስማማበት ኢትዮጵያ ከ80 በላይ የተለያየ ባሕልና አመለካከት ያላቸው ብሔረሰቦች ተፈቃቅደውና ተከባብረው በአንድነት የሚኖሩበት አገር ናት፡፡ የዚህን ሕዝብ ባህል፣ ቋንቋ፣ እምነት … ማጥናት ትልቅ ተግባር ነው፡፡ ኢትዮጵያ ገናና ስልጣኔ ታይቶ የከሰመባት ምድር ናት፤ ይህ በራሱ ለጥናት ይጋብዛል፡፡

ልክ ሲሪዮሎጂ፣ ኤጀፕቶሎጂ እንደሚባለው የኢትዮጵያም ጥናት ያስፈልጋል በሚል ዓላማ ነው የተቋቋመው፡፡ ሙዚየሙ ምን ስብስቦችን ይዞ ነው ሥራ የጀመረው? የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ከተመሠረተ በኋላ እንቅስቃሴው ሁሉ እንደ ብሔራዊ ሙዚየም ነበር፡፡ ፕሮፌሰር ስታንስላቭ ሆይናይስኪ የማይሰበስቡት ነገር አልነበረም፡፡ ኢትዮጵያን ይገልፃሉ የሚባሉ ነገሮችን ሁሉ ከመሰብሰብ ወደ ኋላ አላሉም ነበር፡፡ ቆርኪ፣ የመኪና ታርጋ ሁሉ ይሰበስቡ ነበር፡፡ ቅርስ ማሰባሰቡ በጀመረው መልኩ ነው የቀጠለው? የመጀመሪያው ቅርስ ማሰባሰብ ሥራ በፍላጎትና በፍቅር ላይ የተመሠረተ ነበር፡፡ አሁን አኩዚሽን ፖሊሲ መከተል አስፈልጎናል፡፡ ሙዚየሙ 13 ሺህ የሚደርሱ ታሪካዊ ስብስቦች አሉት፡፡ የተበላሸ ቅርስ መጠገኛ ላቦራቶሪ ግን የለውም፡፡ በፖሊሲ መመራታችን የቅድመ አደጋ ጥንቃቄ ላይ በሚገባ እንድንሰራ ይረዳናል፡፡ ሁሉም ሙዚየሞች የሚመሩበት ፖሊሲ ያስፈልጋቸዋል፡፡ በዚህ ምክንያትና ዓላማ የሙዚዮሎጂ ኮርስ በዩኒቨርስቲው ግቢ ከ2006 እ.ኤ.አ ጀምሮ ማስተማር ስለጀመርን ትምህርቱን ያገኙ ባለሙያዎች በተለያዩ ሙዚየሞች በመሥራት ላይ ይገኛሉ፡፡

የሙዚየም ጥናት ኮርሱ ምን ላይ ያተኩራል? የሙዚየምን ሳይንስ ነው የምናስተምረው፡፡ አንድ ሙዚየም ጥራት ያለው ስብስብ እንዲኖረው ከተፈለገ የሚመራበት ፖሊሲ ያስፈልገዋል፡፡ ብሔራዊ የፖስታ ወይም የቡና ሙዚየም አንድ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ነው ትኩረት ያደረጉት፡፡ ሙዚየሞች በማንኛውም አካል ሲቋቋሙ በምን ጉዳይ፣ ለምን ዓላማ … እንደሚቋቋሙ ግልጽ አድርገው እንዲነሱ የሙዚዮሎጂ ትምህርት ግንዛቤ ይሰጣል፡፡ ሁሉንም አማረን ብሎ ማከማቸት ቅርስ መሰብሰብ ሳይሆን ማበላሸት ነው የሚሆነው፡፡ ለምሳሌ የአንድ ሙዚየም ባለሙያ ጥንታዊ ቅርስ ስላገኘ ብቻ ወደ ሙዚየሙ ማስገባት የለበትም። ለቅርሱ ተገቢ የሆነ ማስቀመጫ አለኝ ወይ? ቅርሱ ቢበላሽ የሚጠገንበት ላቦራቶሪና ባለሙያ ይገኛል? ብሎ ቀድሞ ሳያስብበት ቅርሱን ሙዚየም ቢያስገባ ቅርሱ ተጠብቋል ማለት አይደለም፡፡ የሙዚዮሎጂ ጥናት በቅርስነት ተመዝግበው የተቀመጡትን ቅርሶች በልዩ ጥንቃቄ እንዲያዙ ያግዛል፣ በተቃራኒው ቅርስ ከማግበስበስ እንድንቆጠብም ይረዳናል፡፡

አሰራራችን ሳይንሳዊ ከሆነ የዲስፕሌይ መርህንም እንድንከተል ያስገድደናል፡፡ መርሁ መረጃ የሌለውን ቅርስ ለእይታ አታቅርብ ይላል። ለእይታ ባቀረብከው ነገር ልታስተምር ነውና ቅርሱ የማን እንደነበር፣ ከየት እንደተገኘ፣ ለምን አገልግሎት ይውል እንደነበር፣ መሠረታዊ ምላሾችን ሳታስቀምጥ አታወጣውም፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ቅርሱ ለእይታ ቢቀርብ ለአደጋ የመጋለጥ እድሉ ሰፊ ከሆነና የሥነ ጥበብ ዋጋና ደረጃውም ከተጎዳ ለእይታ እንዲቀርብ አይበረታታም፡፡ የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም ሙዚየም ቅርሶች ሁሉም መረጃ አላቸው? እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ሙዚየሙ የማይሰበስበው ነገር አልነበረም፡፡ ከንጉሳዊያን ቤተሰብ፣ ከቤተክርስቲያናት፣ ትግራይና ጎጃምን ከመሳሰሉ የተለያዩ አካባቢዎች ባህልና ቅርስን የሚያመለክቱ በርካታ ነገሮች ተሰብስበዋል፡፡ ቅርሶቹ ዝርዝር መረጃ ያላቸውም የሌላቸውም ይገኙበታል፡፡ የእኛ ሙዚየም ቤተ መንግሥት ሆኖ ያገለገለ ቤት በመሆኑ የተነሳ ከቤተመንግሥት የመጡ ስብስቦች አሉን፣ ግን ሙሉ መረጃ የሌላቸው ቅርሶችም አሉን፡፡

ይህ አሳዛኝ ነገር ነው፡፡ ሰሀንን ሰሀን ከማለት ውጭ መቼ ተሰራ? ማን ነበር የሚገለገልበት? ከየት አገር ተሰርቶ መጣ? በግዢ ነው በስጦታ የተገኘው? … ለሚለው ጥያቄ መረጃ የሌላቸው አልባሳት፣ ቦርሳዎች፣ ጫማዎች … አሉ፡፡ የመረጃ እጥረቱን ለመሙላት ጥረት በማድረግ ላይ እንገኛለን፡፡ ከላይ እንዳልኩት የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም ሙዚየም የተቋቋመው የኢትዮጵያ ባህልና ቅርስ ፍቅር ባሳደረባቸው ሰዎች ስለነበር፤ ያንን መነሻ በማድረግ ያለ ገደብና ምርጫ ብዙ ነገር ሰብስቧል። የአፄ ኃይለሥላሴና የቤተሰባቸው መገልገያዎች፣ የከፋው ንጉሥ ባህላዊ ዘውድ፣ አርበኞች ተገልግለውበታል የሚባሉ የጦር መሣሪያዎች … የመሳሰሉ በርካታና የተለያዩ ስብስቦች ይገኛሉ። ቅርሶቹ በዚያን ዘመን በዚህ መልኩ ባይሰባሰቡ የመሰረቅና የመጥፋት አደጋ ሊያገኛቸው ይችል ነበር፡፡ ይህ በጥሩ ጎኑ ቢነሳም የቤተመንግሥቱ፣ የሕብረተሰቡ፣ የጦር ሚኒስትሩ፣ የየክፍለ ሀገሩ … ቅርሶች ራሳቸውን በቻሉ ተቋማት አለመሰብሰባቸው የመረጃ እጥረት አስከትሏል፡፡ እንዲህም ሆኖ 13ሺውንም ቅርሶች የመዘገብንበት አክሴሽን ካርድ አለ፡፡ አንድ ሰው ጤና ጣቢያ ሲሄድ እንደሚሰጠው ካርድ እያንዳንዱ ቅርስም የራሱ የሆነ መለያ ቁጥር ያለው ካርድ አለ፡፡ የቅርሱ ሥም፣ የተሰራበት ቦታ፣ ይሰጥ የነበረው አገልግሎት፣ የተገኘበት አካባቢ፣ ውፍረቱ፣ ቅጥነቱ፣ ክብደቱ፣ የደህንነት ደረጃውና ፎቶውን ጭምር ይዟል፡፡ በካርድ ብቻ ሳይሆን በካታሎግ የተመዘገቡ ቅርሶችም አሉ፡፡ የሙዚየሙ ዋነኛ ተግባርም የቅርሶቹን መረጃ ማሟላት፣ መጠበቅ፣ ማናፈስ፣ ቀጣይ ዕድሜያቸው የሚረዝምበትን አሰራር መከተል፣ ለጥፋትና ስርቆት እንዳይጋለጡ ጥንቃቄ ማድረግ፣ ለጥናትና ምርምር ምቹ እንዲሆኑ ማመቻቸትና ሥነ ጥበባዊ ዋጋቸውን መጠበቅ ነው፡፡

የሙዚየሙ አደረጃጀት ምን ይመስላል? ሙዚየሙ ያለበት ግቢ በኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ሂደት ላይ ጉልህ ሚና ተጫውቷል፡፡ ግቢው ከቤተ መንግሥት ወደ ዩኒቨርስቲ የተለወጠበትንና ዩኒቨርስቲ ከሆነ በኋላ በአገር ላይ ተጽዕኖ ያሳደሩ ሂደቶችን በማሳየት ነው የሙዚየሙ አደረጃጀት የተዋቀረው፡፡ በመቀጠል ከልጅነት እስከ ሞት የሚል ክፍል አለ፡፡ በዚህ ውስጥ የልጆች ጨዋታ፣ ትምህርት፣ ባህል፣ ሃይማኖት፣ ሞትና ሐውልቶችን ማሳያዎች አሉ፡፡ የንጉሱና የእቴጌይቱ እልፍኝ ሌላው ክፍል ነው፡፡ ለጥናትና ምርምር የሚረዱ በርካታ ስብስቦች ያሉበት ይህ ክፍል፣ ከአፄ ምኒልክ ጊዜ ጀምሮ በአገራችን የታተሙ ቴምብሮች ይገኙበታል፡፡ የባህላዊ ሙዚቃ መሣሪያ ክፍል ሌላኛው አደረጃጀት ነው፡፡ የክር፣ የትንፋሽ፣ የምት … ባህላዊ ሙዚቃ መሣሪያዎች ይገኙበታል፡፡ የሙዚየሙ ሌላኛው አካል አርት ጋለሪው ሲሆን በአብዛኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክን መሠረት ያደረጉ ስዕሎች አሉበት፡፡ የመስቀል ስብስቦች ሌላኛው የሙዚየሙ አካል ነው፡፡

በንጉሡና በእቴጌይቱ መኝታ ክፍል ስላሉት አልባሳት ምን መረጃ አላችሁ? የንጉሥ ኃይለሥላሴና የእቴጌ መነን አልባሳት መሆናቸውን እርግጠኛ የሆንባቸው ስብስቦች አሉን፡፡ ማን ይገለገልባቸው እንደነበረ ባይታወቅም ፊታውራሪ፣ ቀኛዝማች፣ ሊቀመኳስ … መሰል ማዕረግ አመልካች አልባሳትም አሉ፡፡ በአልባሳቱ ላይ የሚታዩት የሙካሽ ሥራ፣ የብረታ ብረት ጌጦችና ፈርጦች ምንነት የተጠኑም ያልተጠኑም ይገኙበታል። በሙካሽ የሚገለጽ የማዕረግ ዓይነት፣ ሙካሽ የት ይሰራ እንደነበር፣ ማቴሪያሉ ከየት እንደሚመጣ፣ የሙካሽ ሥራ ዕውቀት ኢትዮጵያ ውስጥ እንዴት እንደጀመረ … የመመረቂያ ጽሑፍ ተሰርቶበታል። እኛም ጥናቱን ኮፒ አድርገን የሙዚየማችን አካል አድርገነዋል፡፡ በአልባሳቱ ላይ የሚገኙት የብረታ ብረት ጌጣ ጌጦች “ጋሻ ጉብ ጉብ” የሚባለው ቅርጽ ያላቸውና ከአንድ ወርክ ሾፕ የወጡ መሆኑን አስረግጦ መናገር የሚቻል የጥበብ ሥራ ናቸው፡፡ የት ይሰሩ እንደነበር፣ ከምን ማዕድናት እንደተሰሩ ገና መጠናት ያለበት ነው፡፡ ከአልባሳቱ ቁልፎች ጋር በተያያዘ የተሰራ ምንም ጥናት የለም፡፡ አንጥረኝነትን የምናደንቅበት አቅም ስላልነበረን ዛሬ ላለብን የመረጃ እጥረት አንዱ ምክንያት ሆኗል እንጂ፤ ኢትዮጵያዊያኑ አንጥረኞች “ቡዳ” እየተባሉም ቢሆን ብዙ ነገር መሥራታቸውን የሚያሳዩ በርካታ ቅርሶች አሉ፡፡ ሙዚየሙ የታዋቂ ሰዎችን አልባሳትና የግል መገልገያ ቁሳቁስ እየተቀበለ ማስቀመጡን ቀጥሎበታል፡፡

ይህ አሰራር ሙዚየሞች በተወሰነ ነገር ላይ ትኩረት አድርገው መስራት አለባቸው ከሚለው ጋር አይጋጭም ? አሁን እየሰበሰብን ያለውን ብቻ ሳይሆን 13ሺውንም ስብስቦች በፊት ከሚገኙበት በተሻለ ሁኔታ በየርዕሰ ጉዳዩ ከፋፍለን በመመደብ ለእይታ የማቅረብ እቅድ አለን፡፡ የዩኒቨርስቲው አዲሱ የአስተዳደር ሕንፃ ግንባታው አልቆ ሥራ ሲጀምር፣ በመኮንን አዳራሽ ያሉ በርካታ ክፍሎች ስለሚለቀቁ፣ እነዚህን የሙዚየሙ አካል የማድረግ እቅድ አለ፡፡ በእቅዳችን መሠረት ቀጣዩ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ሙዚየም የሕፃናት ክፍል ከነመዝናኛው፣ የአርበኞች ክፍል፣ የደራሲያን ክፍል፣ የባህላዊ ሸክላ ሥራና የአንጥረኞች ክፍል፣ የዘመናዊ ሰዓሊያን ክፍል ይኖሩታል፡፡ ይህንን እቅድና ዓላማ ምክንያት በማድረግም የተለያዩ የአርበኛ፣ የሚሊተሪና ታዋቂ ሰዎች ታሪካዊ ስብስቦችን ከቤተሰቦቻቸው ተቀብለን አስቀምጠናል፡፡

እነዚህ ስብስቦች ሙሉ መረጃ ያላቸው ናቸው። በዚህ መልኩ የታዋቂ ሰዎችን አልባሳት፣ መገልገያ ቁሳቁስ፣ መፃሕፍት ከሰጡን መሐል የፀጋዬ ገ/መድህን፣ የመንግሥቱ ለማ፣ የከበደ ሚካኤል፣ የሀዲስ አለማየሁ፣ የማሞ ውድነህ፣ የጳውሎስ ኞኞ ቤተሰቦች ይገኙበታል፡፡ በመጨረሻ የሚያነሱት ነገር ካለ … ሙዚየሞችን በተመለከተ በአገራችን መስተካከል ያለባቸው ብዙ አሰራሮች አሉ፡፡ አገራችን የሙዚየሞች ዓለም አቀፍ ስምምነትን በ1978 ዓ.ም ፈርማለች፡፡ ስምምነቱ ቅርሶች ወደተገኙበት ምንጭ እንዲመለሱ ያሳስባል፡፡ በውጭ አገራት ያሉ ቅርሶቻችን እንዲመለሱልን የምንጠይቀው በዚህ ምክንያት ነው። ስምምነቱ በአገር ውስጥም ከመገኛቸው ርቀው የሚገኙት ወደ ነበሩበት ይመለሱ ስለሚል በዚህ ዙሪያ ብዙ ሥራ መስራት ያለብን ይመስለኛል፡፡

Saturday, 18 January 2014 12:10

ክፍል አራት

ከባለፈው እትም የቀጠለ
የግል ንግድ ተቋማት ማህበራዊ ሃላፊነትና የህጻናት ጥቅም

ቀደም ባሉት ክፍሎች እንዳየነው የግል ንግድ ተቋማት በማንኛውም የንግድ እንቅስቃሴያቸውና አቅርቦታቸው ውስጥ የህጻናትን ደህንነት የማረጋገጥ ብሎም ምርትና አገልግሎታቸው የህጻናትን ጥቅምና ፍላጎት ያማከለ ስለመሆኑ የማረጋገጥ ሃላፊነት እንዳለባቸው ያስረዳሉ ፡፡ ስድስተኛው መርህ ሽያጭና ማስታወቂያዎች የህጻናትን ደህንነት ማክበርና መደገፍ እንዳለባቸው ያስረዳል፡፡ እንደሚታወቀው ሽያጭና ማስታወቂያ ለማንኛውም ንግድ የደም ስር መሆናቸው ይታወቃል፤ ሆኖም እነዚህ ሁለት እንቅስቃሴዎች ሲካሄዱ በልጆች ላይ ለያደርሱ የሚችሉት ተጽእኖ ብዙም ቦታ ላይሰጠውና ላይተኮርበት ይችላል፡፡ ስለዚህም በማንኛውም መንገድ ምርታቸውን በሚሸጡበት አልያም በሚያስተዋውቁበት ወቅት በህጻናት ላይ ምን ሊያስከትል ይችላል የሚለውን ቅደሚያ ከግምት ማስገባት ያለባቸው ጉዳይ ስለመሆኑ ያስረዳል፡፡

መርሁ የሽያጭ ሂደትም አድልዎ ሊኖርበት እንደማይገባና@ ለተጠቃሚዎች ውሳኔ ይረዳ ዘንድም የምርቶችን ደረጃ በይፋ የማሳወቅ ሃላፊነት እንዳለባቸውም ያስረዳል፡፡ምንም ያህል የጠበቀ ቢሆን፤ የምርት ማስተዋወቅ ሂደትና ማስታወቂያ የአለም አቀፍ የጤና ድርጅትን እንዲሁም ከአገር አቀፍ ደረጃዎች ጋር የሚስማሙ መሆን አንዳለባቸው ያስረዳል፡፡ እንደ መርሁ አገላለጽ የንግድ ድርጅቶቹ በሽያጭ ወይም በማስታወቂያቸው በጎ አመለካከቶችን(አስተሳሰቦችን) ፣ጥቃትን መቃወም እና ጤነኛ የአኗኗር ዘዴን በማንጸባረቅ በተለይም የህጻናት ጥቅሞችን የሚደግፉ መሆን እንዳለባቸው ያስረዳል፡፡

ሰባተኛው መርህ ህጻናት ከአከባቢያቸው፣ ከመሬት ይዞታና አጠቃቀም ጋር ያለቸውን መብቶች ስለማክበርና ስለመደገፍ ይመለከታል፡፡ ህጻናት ከአከባቢያቸው ጋር በተያያዘ ያሏቸው ፍላጎቶች ከግምት ውስጥ ሊገቡ ይገባቸዋል፡፡ አከባቢን አስመልክቶ የሚወጡ ማናቸውም እቅዶችና ሰትራቴጂዎች የህጻናትን፣የቤተሰቦቻቸውን አንዲሁም የማህበረሰቡን ፍላጎት ያማከሉ መሆን እንዳለባቸው ያስረዳል፡፡ በተጨማሪም እነዚሁ እቅዶች በአከባቢና በጤና ላይ ለሚደርሱ ጉዳቶች፣በስራ አጋጣሚ ለሚከሰቱ ጉዳቶች የሚሆኑ የካሳ አከፋፈል ስርአትን የማካተት ሃላፊነት ለነዚህ ተቋማት ይሰጣል፡፡ እንደ መርሁ አገላለጽ በመሬት ይዞታና አጠቃቀም ዙሪያም እነዚህ የንግድ ተቋማት@ ከመኖሪያ ቦታ የመፈናቀል አጋጣሚን በመቀነስና ህብረተሰቡን አሳታፊ በሆነ መልኩ የህጻናትን ጥቅም መከበርን ከግምት ማስገባት ይኖርባቸዋል፡፡ በተጨማሪም ከአከባቢ ጥበቃ ጋር በተያያዘ የህጻናት የመማር፣የደህንነት፣የጤና፣በቂ ምግብ የማግኘት፣ በጥሩ ሁኔታ የመኖር እንዲሁም የተሳትፎ ፍላጎቶቻቸው ሊከበሩ እነደሚገባም ያስረዳል፡፡ ስለዚህም የንግድ ተቋማት ከአከባቢ እንዲሁም ከመሬት ይዞታ ጋር በተያያዘ የሚያከናውኗቸው ተግባራት@ ለአከባቢ ደህንነት ብሎም ለቀጣዩ ትወልድ አሉታዊ ተጽእኖዎችን ሊያስከትሉ እንደሚችሉ በመገመት ከወዲሁ ለዘላቂ ልማት አስተዋጽኦ ማድረግ እንዳለባቸው ያስረዳል፡፡

Saturday, 18 January 2014 12:08

አዲስ አባ

ቀለበት አስሮ እንደያዘው
እንደደለለው ጋብቻ
ግብሩን ከቶ ሳላገኘው
ተጃጅዬ በስም ብቻ
በምኞት ህልም
በአጉል ተስፋ
እስትንፋሴ እየራቀ
አኗኗሬ እየከፋ
ውስጤ ላዬ እያደፈ
ብዙ አበቅቴ ተታለፈ፤
ቱር…ሳልል ብርር ….ሳልል
እዚህ እዚያ ሳላዳርስ
ጭብጥ ጥሬ እንኳ ይዤ
ባልጠግበውም ላመል ሳልቀምስ
ባይሞቀኝም እንዳይበርደኝ
ጐጆ ይዤ ጭስ ሳላጨስ
“እልፍ ካሉ - እ - ልፍ” እንዲሉ
ዞር ማለቱን ሰንፌ
እንዳኖሩት ግዑዝ ድንጋይ
ቀረሁብሽ ተወዝፌ፤
ውሃ እንደተጠማ ኩታ
ልዋጭ እንደሌለው ጨርቅ
ገምቼ ገልምቼ ስቼ
ከእድፌ ጋር ስጨቃጨቅ
ስትገፊኝ እምቢኝ እያልኩ .
ዛሬም አለሁ አንቺን ሳለቅ፤
አዲስ አባ
ውሃሽ በመዘውር አልፎ
ዙሪያ ገባሽን ቢሞላ
ለኔ በባሊ ነፍጐ
ለረጠበው እያደላ
“ዝናብ ቢዘንብ በባህሩ…”
ብሎ እንዳለው መምህሩ
ገበሬ እንኳ ዓመት ለፍቶ
ለጐተራሽ ቢዘረግፍ
እጀ ረጅሙ ደርሶ
አግበስብሶ ነው… እሚልፍ
እናም አዋጅ ልንገር ጐረቤት ሁሉ ይስማ
ርስቴን ለቀቅሁ ወጣሁ ወደ ሌላ ከተማ፡፡
አውላቸው ለማ   

ጃኖ ባንድ ለዓመቱ የመጀመሪያ የሆነውን የሙዚቃ ኮንሰርት ዛሬ ምሽት በትሮፒካል ጋርደን ያቀርባሉ፡፡ ኮንሰርቱን ከአምስት ሺ በላይ ሙዚቃ አፍቃሪዎች ይታደሙታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የመግቢያ ዋጋ 200 ብር እና ለቪአይፒ 400 ብር እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ጃኖ ባንድ በመቀጠል በቀጣይነት ተመሳሳይ የሙዚቃ ድግሶች በጐንደር፣ ባህርዳር፣ ድሬዳዋ እንደሚቀርቡ ታውቋል፡፡

የሥነፅሁፍ ምሁሩን ዶ/ር ፍቅሬ ቶሎሳን የሚዘክር የኪነጥበብ ዝግጅት ዛሬ ከ3 ሰዓት እስከ 6 ሰዓት በብሄራዊ ቲያትር ቤት ይቀርባል፡፡ ከ40 ዓመት በላይ በኢትዮጵያ ስነፅሁፍ ዘርፍ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያበረከቱት ዶ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ፤ በአሜሪካ ሎስአንጀለስ ዩኒቨርስቲ ውስጥ መምህር ናቸው፡፡ ምሁሩን ለመዘከር በተሰናዳው የኪነጥበብ ዝግጅት፤ የስነፅሁፍ ባለሙያዎች ግጥሞችን፤ ተውኔቶችንና መነባንቦችን እንደሚያቀርቡ የፕሮግራሙ አዘጋጅ አብርሃ ግዛው ኢንተርቴይንመንትና ፕሬስ ሥራዎች ገልጿል፡፡