Administrator

Administrator

         የኢትዮጵያ አየር መንገድና የቱር ኦፕሬተርስ አሶስዬሽን የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ቱሪስቶችን ቁጥር ለመጨመር፣ በትራንስፖርትና በአገልግሎት ክፍያ ዋጋ ላይ ቅናሽ ማድረጋቸውን አስታወቁ፡፡ የሆቴሎች ዋጋም ይቀንሳል ተብሏል፡፡ በቅርቡ የተቋቋመው የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድና አገልግሎት ሰጪ የሆነው የአስጐብኚ ድርጅቶች ማኅበር (ቱር ኦፕሬተርስ አሶስዬሽን) ከትናንት በስቲያ በጋራ በሰጡት መግለጫ፤ ኢትዮጵያ በርካታ የቱሪስት መዳረሻ ባለቤት ብትሆንም፣ የቱሪስቶች ፍሰት ከቁጥር የማይገባ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

በውጭ አገራት ያሉ የተፎካካሪ አገራት የቱሪስት ወኪሎች “ኢትዮጵያን ለመጐብኘት የትራንስፖርትና የሰርቪስ ዋጋ ውድ ነው፣ የአገልግሎት አሰጣጡ (የሆቴሎች ንፅህና፣ መስተንግዶ) ጥራት ዝቅተኛ ነው፤….” በማለት የሚያሰራጩትን የአገሪቱን ገጽታ አፍራሽ ፕሮፓጋንዳ ለማክሸፍ፣ አዲስ ስትራቴጂ ቀርፀው መንቀሳቀስ መጀመራቸውን ድርጅቶቹ ተናግረዋል፡፡ በዚሁ መሠረት የኢትዮጵያ አየር መንገድ የቱሪስቶችን ቁጥር ለማብዛት በትራንስፖርት ክፍያ ላይ 40 በመቶ ቅናሽ ማድረጉን የአየር መንገዱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገ/ማርያም የገለጹ ሲሆን፣ የቱር ኦፕሬተሮች አሶስዬሽን ፕሬዚዳንት አቶ ፍፁም ገዛኸኝ በበኩላቸው፤ አስጐብኚ ድርጅቶች ከሚያስከፍሉት የአገልግሎት ዋጋ ላይ 20 በመቶ እንደሚቀንሱ አስታውቀዋል፡፡

የሆቴሎች ማኅበር ፕሬዚዳንት አገር ውስጥ ባለመኖራቸው ምን ያህል እንደሚቀንሱ አልታወቀም፡፡ አዲሱ ስትራቴጂ የኢትዮጵያ ተፈጥሯዊና ታሪካዊ የቱሪስት መስህቦች አውቆ መለየትና ለቱሪስቶች ማስተዋወቅ ነው ያሉት የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሰለሞን ታደሰ፣ ለቱሪስት መዳረሻዎቹ አስፈላጊ መሠረተ ልማት (የአየርና የየብስ ትራንስፖርት፣ የንፁህ ውሃና የመብራት) አገልግሎት ማሟላት በቱሪስት መዳረሻዎቹ አካባቢ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው ንፅህናው የተሟላ የመኝታ፣ የምግብ፣ አስተማማኝ ጥበቃና የደህንነት አገልግሎት በመስጠት፣ የኢትዮጵያ እምቅ ተፈጥሮዊና ታሪካዊ መስህቦች ለዓለም ማስተዋወቅ፣ የቱሪስቶችን ቁጥር ማብዛትና ከቱሪዝም ዘርፍ የሚገኘውን ገቢ ማሳደግ የስትራቴጂው ግብ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡ ቀደም ሲል በረሃብ፣ ድርቅና ጦርነት የምትታወቀው ኢትዮጵያ፤ ባለፉት 20 ዓመታት ባሳየችው የልማት እንቅስቃሴ በዓለም አቀፍ ደረጃ ገጽታዋ እየተለወጠ ነው ያሉት አቶ ተወልደ፤ ሚዲያውና በዘርፉ የተሰማራን ሁሉ ይህን አጋጣሚ በመጠቀም፣ ዓለም አቀፍ ደረጃን ያሟላ አገልግሎት በመስጠት፣ ቱሪስቶችን ለመሳብ እንረባረብ ብለዋል፡፡

የምሥራቅ አፍሪካ አገሮችን (ኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ታንዛንያ) የሚጐበኙ ቱሪስቶች ቁጥር በርካታ እንደሆነ የገለፁት አቶ ተወልደ፤ ለምሳሌ በዓመት ኬንያን የሚጐበኙ ቱሪስቶች ቁጥር ከ1.5 ሚሊዮን በላይ ሲሆን ኢትዮጵያን የሚጎበኙት ቱሪስቶች ከግማሽ ሚሊዮን በታች እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ ኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም ታዋቂና የአፍሪካ መዳረሻውም ብዙ ስለሆነ፣ ቱሪስቶች ወደ ምስራቅ አፍሪካ አገራት የሚጓዙት በእኛ አውሮፕላን ነው፡፡ በአዲሱ ስትራቴጂ ዋጋችን ተመጣጣኝና ተወዳዳሪ ስለሚያደርገን፣ የምንሰጠውም አገልግሎት ዓለም አቀፍ ደረጃውን የሚያሟላ ስለሚሆን ብዙ ቱሪስቶች ወደ አገራችን ይመጣሉ ብለዋል፡፡ የቱሪስት መስህቦቻችንን ማልማትና ማስተዋወቅ/ በቅርቡ የተቋቋሙት የኢትዮጵያ ቱሪዝም ቦርድና ኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ዋነኛ ተግባር ናቸው ያሉት አቶ ፍፁም፤ 80 በመቶ መስህቦቻችንን ለማልማት፣ 20 በመቶ ዳግም ለማስተዋወቅ ሥራ የተሰጠ በመሆኑ፣ የቱሪስት መዳረሻዎችን መሰረተ ልማት ማሟላት፣ ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት መስጠት፣ ማህበረሰቡን ማስተማር ሰፊ ድርሻ የተሰጠው በመሆኑ፤ የቱሪስቶች ቅሬታ ስለሚወገድ ብዙ ጎብኚ ይኖረናል ብለዋል፡፡

         የሼፎችና ባሬስታዎች ውድድር ይካሄዳል ሁለተኛው “ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ 2006”፤ ከግንቦት 8 እስከ 10 በሚሊኒየም አዳራሽ እንደሚካሄድ ኦዚ ሆስፒታሊቲ እና ቢዝነስ ግሩፕ አስታወቀ፡፡ በፕሮግራሙ ላይ የተለያዩ ዝግጅቶች የሚቀርቡ ሲሆን ከአነስተኛ እስከ ከፍተኛ ማሽኖችና ሶፍትዌር አቅራቢዎች፣ የሆቴል አማካሪ ድርጅቶች፣ ሆቴሎች፣ ሪዞርቶች ፣ የሆቴል እቃ አቅራቢዎችና የአስጐብኚ ድርጅቶች የሚሳተፉበት የንግድ ትርኢት እንደሚቀርብ ተጠቁሟል፡፡ የሀገሪቱን የሆቴልና ሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪ ወደተሻለ ደረጃ ለማድረስ እና ተወዳዳሪ ለማድረግ የሚያስችል ሲምፖዚየምም የዝግጅቱ አካል ሲሆን በሲምፖዚየሙ ላይ ከ400 በላይ በዘርፉ የተሰማሩ ባለሙያዎች ምክክር ያደርጉበታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የሼፎችና ባሬስታዎች ውድድርም የሚካሄድ ሲሆን ውድድሩ ከጣሊያን እና ቱርክ በመጡ ዳኞች እንደሚዳኝ ተገልጿል፡፡ “ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ 2006” በኢፌዲሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ድጋፍ እንደሚደረግለት የተገለፀ ሲሆን ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል እንዲጐበኘውና በዘርፉ ያለው ግንዛቤ እንዲሰፋ መግቢያ በነፃ እንዲሆን መወሰኑ ተገልጿል፡፡ ዝግጅቱን ከ35ሺህ በላይ ሰዎች ይጐበኙታል ተብሎ እንደሚጠበቅ አዘጋጁ ኦዚ ሆስፒታሊቲ እና ቢዝነስ ግሩፕ ጠቁሟል፡ የመጀመሪያው “ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ 2006” ከመስከረም 30 እስከ ጥቅምት 2 ቀን 2006 ዓ.ም በተባበሩት መንግስታት የስብሰባ አዳራሽ መካሄዱ የሚታወስ ሲሆን ከ7500 በላይ ሰዎች የንግድ ትርኢቱን እንደጐበኙት ታውቋል፡፡

             ከሩብ ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ ለመኪና ማቆሚያ የሚሆን ፎቅ እንደሚያስገነባ የገለፀው ኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል፤ በቡራዩ እና በቢሾፍቱ ሁለት ዘመናዊ ሪዞርቶችን ሊያስገነባ ነው፡፡ ባለፈው ህዳር ወር ስራ የጀመረው ኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል፤ አለማቀፍ ደረጃዎችን በማሟላት በሃገራችን አሉ ከሚባሉ ሆቴሎች አንዱ መሆኑን የገለፁት ስራ አስኪያጁ ፕ/ር ኤዲ ባሬንቶ፤ በግንባታ ጥበቡ በውስጣዊ ይዘቱ፣ በቴክኖሎጂዎች አጠቃቀሙና በሰው ኃይል አደረጃጀቱ እጅግ ዘመናዊ በመሆኑ የአፍሪካ መዲና የሆነችው አዲስ አበባ ድምቀት እንደሆነ ማንም ሊመሰክር ይችላል ብለዋል፡፡ በ1690 ካሬ ሜትር ለመኪኖች ማቆሚያ (ፓርኪንግ) አገልግሎት የሚሰጥ አለማቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ፎቅ በ 258 ሚሊዮን ብር እንደሚያስገነባ ስራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡

የኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ባለቤት አቶ ገምሹ በየነ፤ ዘመናዊ የመዝናኛ ስፍራዎችንና ሰፋፊ የስብሰባ አዳራሾችን ያካተተ ሪዞርት በቡራዩ እያስገነቡ ሲሆን፤ ሪዞርቱ አዲስ አበባን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ከፍታ ቦታ ላይ መሆኑን ፕ/ር ባሬንቶ ገልፀዋል፡፡ በቢሾፍቱ ባቦጋያ ሃይቅ አካባቢ እየተገነባ ያለው ሌላው ሪዞርት እጅግ ዘመናዊ መሆኑን ፕ/ር ባሬንቱ ሲያስረዱ፤ በአገሪቱ የመጀመሪያው ተጠቃሽ እንደሚሆን ጠቁመው፤ 2500 ሰው መያዝ የሚችል የስብሰባ አዳራሽ የያዘ ነው ብለዋል፡፡

በሆቴል ዘርፍ በቢሊዮን ብር የሚቆጠር ሃብት ኢንቨስት ያደረጉት አቶ ገምሹ በየነ፤ በመሰረተ ልማት በተለይም በመንገድ ግንባታ ላይ የተሰማራ “ገምሹ በየነ ኮንስትራክሽን (GEBECON)” የተሰኘ ኩባንያ ባለቤት መሆናቸውን ፕ/ሩ ጠቅሰው፤ በሃገሪቱ የመሰረተ ልማት እድገትና የስራ እድል ፈጠራ ላይ የራሳቸውን አሻራ ለማሳረፍ እንደቻሉ ተናግረዋል፡፡ ከ6ሺ በላይ ሰራተኞች ያሉት የኮንስትራክሽን ኩባንያው፤ በእውቅ የምህንድስና ባለሙያዎች የተደራጀ መሆኑን የገለፁት ፕ/ሩ፣ ከገነባቸው መንገዶች መካከል በትግራይ ከማሃበሬ እስከ ዲማ እና ከዲማ እስከ ፈየል ውሃ፣ በጐንደር ከአዘዞ እስከ ጎርጎራ እና የመሃል ሜዳ መንገድ ይገኙበታል፡፡ በተጨማሪም ከድሬድዋ እስከ ደወሌ እንዲሁም በሶማሌና በሃረሪ ክልል የመንገድ ግንባታዎችን ያከናወነው ኩባንያው፣ በርካታ መንገዶችን ሰርቶ እንዳስረከበ ተገልጿል፡፡

ፕ/ር ባሬንቶ ስለ አቶ ገምሹ በየነ ሲናገሩ፤ ከኢንቨስትመንት ጋር በተለይ በበጐ አድራጐትና በአገር ወዳድነታቸው የሚታወቁ ናቸው ይላሉ፡፡ በዘርና በጎሳ የማያምኑ፣ ሁሉም ኢትዮጵያዊያን ባላቸው እውቀትና ብቃት ሰርተው ኑሯቸውን እያሻሻሉ፣ ሃገራቸውንም እንዲጠቅሙ የሚጣጣሩ በመሆናቸው፣ በፈተና እና በስራ ምዘና እንጂ በዝምድና እንኳ እንደማይቀጥሩ በማየት እናደንቃቸዋለን ብለዋል፤ ፕ/ር ባሬንቶ፡፡


ዳሽን ባንክ እና የአሜሪካው ኤክስፕረስ ኔትወርክ የኤቲኤም የካርድ አገልግሎት ስምምነት የተፈራረሙ ሲሆን በቅርቡ የአሜሪካ ኤክስፕረስ ካርድ አገልግሎት በሁሉም የዳሽን ባንክ ኤቲኤም ማሽኖች እንደሚጀምር ተገለፀ፡፡ የባንኩ የፕሮሞሽን ዋና ክፍል ኃላፊ አቶ እስጢፋኖስ በፈቃዱ፤ የኤቲኤም ማሽን የካርድ አገልግሎቶችን እየተገበረ መሆኑን አስታውሰው፤ በሃገሪቱ ብቸኛ ባንክ የሚያደርገው፤ የአሜሪካን ኤክስፕረስ ካርድ አገልግሎት፣ የሙከራ ሂደቱ እንደተጠናቀቀ በይፋ ይጀምራል ብለዋል፡ በርካታ የውጭ ሃገር ቱሪስቶች የአሜሪካን ኤክስፕረስ ካርድ ተጠቃሚ ናቸው ያሉት ኃላፊው እስከዛሬ በዚህ ካርድ በኢትዮጵያ ውስጥ ገንዘብ ማውጣት እንደማይቻል ጠቁመው፤ ዳሽን ባንክ አገልግሎቱን መጀመሩ ብቸኛው እንደሚያደርገው ተናግረዋል፡፡ የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ ብርሃኑ ወ/ስላሴ በስምምነት ፊርማው ላይ ባደረጉት ንግግር፤ ባንካቸው በኢትዮጵያ ያለውን የልማት እንቅስቃሴ እየደገፉ መሆኑን ጠቅሰው፤ እስካሁን ካሉት የኤቲኤም ካርዶች በተጨማሪ፣ የአሜሪካን ኤክስፕረስ ካርድ አገልግሎት መጀመሩ፣ ባንኩንም ሃገሪቱንም ተጠቃሚ ያደርጋቸዋል ብለዋል፡፡ ዳሽን ባንክ በኢትዮጵያ ተጠቃሽ ከሆኑ የፋይናንስ ተቋማት አንዱ ነው ያሉት የአሜሪካ ኤክስፕረስ ዋና ስራ አስፈፃሚ ፒተር ላይስ በበኩላቸው፤ ባንኩ ለደንበኞች አገልግሎት እርካታ የሚተጋ መሆኑን፣ የአሜሪካን ኤክስፕረስ ካርድ ተጠቃሚነቱ ይመሰክራል ብለዋል፡፡

ይኸው ተገልጦ ከማያልቀው ታሪካችን ለዛሬ ይህን ገፅ ፈቅዳችሁ ብታነቡኝ በመጨረሻ አእምሮአችሁ ውስጥ በርካታ ጥያቄዎች ሊነሱ እንደሚችሉ እገምታለሁ፡፡ አንባቢው ፀሃፊ (የስነ ፅሁፍ ሰው) ከሆነ ደግሞ ቀጥሎ ከማወጋችሁ ብጥስጣሽ የህይወት ገፅታዎች ጫፋቸውን ይዞ በመከተል ሌሎች ደርዞችን ሊያወጣ ይችላል፡፡
በየትኛው ግለሰብ ታሪክ ልጀምር፡- ስሜትን በሚጎዱ፣ በሚያሳዝኑ፣ እጅግ በሚደንቁና በሚያስደስቱ፣ የሚገርም የስነ ልቦና ብርታት በሚታይባቸው፣ ወደ ስጋት ስሜት በሚጨምሩ? ቆይታዬ እስከ አስር የሚደርሱ ታዳጊ ወጣቶች ጋር ነበር እድሜአቸው ከ14 እስከ 18 ነው፡፡ የተለያዩ ጥያቄዎችን እያነሳሁ፡፡ የግል ጉዳይ ከመሆኑ አንፃር አንድ በአንድ ለማውጋት ችለናል፡፡
እድሜህ ስንት ነው?
   “14”
ስንተኛ ክፍል ነህ?
  “9ኛ”
የትምህርት ደረጃህ እዴት ነው ጎበዝ ነህ ወይስ?
  “ በጣም ጎበዝ ተማሪ ነኝ 8ኛ ክፍል በት/ቤቴ ከፍተኛ
   ውጤት ካመጡ ውስጥ አንዱ ነኝ 92 ነው ያመጣሁት
   ከ7 ወደ 8ኛ አንደኛ ነው የወጣሁት”
ቤት ምን ይደረግልሃል እደዚህ ከፍተኛ ውጤት   ስታመጣ?
   “ ብስክሌት ሁሉ ተሸልሜ አውቃለሁ”

ሌላዋ የ 18 ዓመት ታዳጊ ወጣት የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ስትሆን የጤና ትምህርት ትማራለች፡፡ መቼና እንዴት ከቫይረሱ ጋር እንደምትኖር አወጋችኝ፡፡ የሰባት አመት ልጅ ከሆነች በኋላ የጊዜ ቁጥጥር እየተደረገ መድሃኒት እንድትወስድ ይደረጋል፡፡ ይህን መድሃኒት ግን ሌሎች ታላላቆቿ አይወስዱም፡፡ እንክብካቤ ይበዛባል፡፡ በተወሰኑ ጊዜያት በሁለትና በሶስት ወራት ጊዜ ሃኪም ቤት በመሄድ የጤና ምርመራ እንድትወስድ ይደርጋል፡፡ ይች ህፃን እያደገች ስትሄድ የንባብ አቅሟም ከነበረበት ሲጎለብት ከመድሃኒቷና ምርመራዋ ጋር የተያያዙ ወረቀቶችን ታነባለች፡፡ ልጆች እንኳንስ እንዲህ የተለያዩ ጉዳዮችን እየተመለከቱ እንዲሁም በርካታ ጥያቄዎችን ማንሳታቸው የማይቀር ነው፡፡ ይች ልጅም ጥያቄዎችን ማጉረፍ ጀመረች… ቀጠለች፡፡ እድሜዎ 13 ሲደርስ ግን የሆነው ሁሉ በሃኪሟ አማካኝነት ተገለጠላት
“ ግን ያኔ አብዛኛውን ጉዳይ ቀድሜ ስለጠረጠርኩና ስላወኩ ብዙ አልተደናገጥኩም፡፡ ቤተሰቦቼም በጣም አገዙኝ፡፡”
ሌላዋ የሞያና ቴክኒክ ተማሪ የሆነችው የ17 ዓመት ታዳጊ ወጣትም በተመሳሳይ መንገድ ነው ከቫይረሱ ጋር መኖሯን ያወቀችው፡፡ የምትወስዳቸው መድሃኒቶችና ሌሎች የምርመራ ወረቀቶቿን (CD4 መጠንን የሚገልፁ) አስቀድማ ታነብ ነበር፡፡ ሆኖም እናቷን  ላለማስጨነቅ ጥያቄውን ማንሳት አልፈለገችም፡፡ በኋላ ሃኪሟ ከቫይረሱ ጋር እንደምትኖር (አግባብ ነው ባለችው እድሜ) ስትገልፅላት አውቃለሁ አትጨነቂ በሚል ነው የተቀበለችው፡፡ ጊዜውን ጠብቆ መድሃኒት መውሰድ ለብዙዎቹ ታዳጊ ወጣቶች መደበኛና በጣም ተለመደ ድርጊት ነው፡፡ “ለእኔ ኖርማል ነው፡፡ ቁርስ ምሳ ትበላለህ ውኃ ትጠጣለህ እነዚህ ጉዳዮች ለመኖር አስፈላጊ ናቸው፤ ሳትበላ ወይም ሳትጠጣ መኖር አይቻልም መድሃኒቱም ለእኛ እንደዛው ነው” ይላል ሌላው የ16 ዓመት ታዳጊ፡፡
ከእነዚህ ታዳጊ ወጣቶች ጋር በነበረኝ ቆይታ ሌላው በጣም አስፈላጊ የነበረው ጉዳይ የፆታ ግንኙነትን የተመለከተው ­ጥያቄ ነው፡፡ ወጣቶች ናቸው፣ በርካታ ጓደኞች ይኖራሉ፤ ትምህርት፣ ጨዋታ፣ መዝናናት፣ ይኖራል፡፡ በዚህ እድሜና የህይወት ገፅ ላይ ደግሞ መወደድም መውደድም (ማፍቀርም መፈቀርም) ይኖራል፡፡ የፆታ ጓደኝነትና የፍቅር ግንኙነት ጥያቄም ሊቀርብ ወይም ሊያቀርቡ ይችላሉ፡፡ ይህን በተመለከተ ያለው አስተሳሰብ የተለያየ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ይህን ጉዳይ ፈፅሞ አስበውበት የማያውቁ ናቸው፤ አንዳንዶቹ ጓደኛ አላቸው፡፡ ሆኖም ጓደኛ የያዙት በተመሳሳይ መንገድ (ከእናት ወደ ልጅ ቫይረሱ ከተላለፈባቸውና) ከቫይረሱ ጋር ከሚኖሩ የእድሜ አቻዎቻቸው ጋር ነው፡፡ ያም ሆነ ይህ ፍቅሩ መዋደዱ ወይም ጥያቄው ከቫይረሱ ጋር ከማይኖር ሰው ከመጣስ ወይም ከተፈጠረስ ለሚለው ጥያቄ አንዳንዶች ፈፅሞ አላደርገውም ተገቢም አይደለም ብለው ያስባሉ፡፡ ከዚህ ሁኔታም መራቅ እንደሚፈልጉ ይገልፃሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ እንደሁኔታው ሊወሰን ይችላል፡፡ ለምሳሌ “ጥያቄውን የሚያነሳው ከቫይረሱ ጋር የማይኖር ሰው ከሆነ ራሴን እገልፅላታለሁ፡፡ ሆኖም ፍቅሩ ካየለና መለያየቱ ከባድ ከሆነ አብሬ ልሆን እችላለሁ” ሌላዋ ወጣት ደግሞ “ይከብዳል ምናልባት ዛሬ በአፍላ እድሜና ፍቅር ምንም አይደለም ሊባል ይችላል ነገ ከነገ በኋላ ግን ግጭት ሊፈጠር ይችላል፣ ስሜትን የሚጎዱ ነገሮች ሊከሰቱ ይችላሉ” የሚሉ አስተሳሰቦች ይሰማሉ፡፡
ልጆቹ በአብዛኛው እንደገለፁልን በመኖርያ አካባቢያቸውና በትምህርት ቤቶቻቸው ያላቸው የህይወት ጉዳይ ሁለት የተለያየ ገፅ የያዘ ነው፡፡ በሰፈራቸው አብረዋቸው ለመብላት የሚፈሩ አብሮ መጫወት የሚሰጉ፣ ተገቢ ያልሆኑ ድርጊቶችን የሚፈፀሙ ሰዎች እንዳሉ ይነገራሉ፡፡ በአንፃሩ በት/ቤቶቻቸው ደግሞ የልጆቹ ማንነት ምንም ስለማይታወቅ ሁሉም ነገር ምንም ባልተለየ መንገድ ይጓዛል(ማግለል፣ መፍራት፣ መፈራት፣ አይታይም)፡፡ ይሁንና ትላለች የዩኒቨርሲቲ የጤና ተማሪ የሆነችው የ18ዓመት ታዳጊ ወጣት አብዛኞቹ የጤና ተማሪዎች አይመስሉም ስለ ኤች አይ ቪ ያላቸው አስተሳሰብና እውቀት ያስደነግጠኛል ፍፁም ከእነሱ የማይጠበቅ ጉዳይ ያጋጥማል በቁንጫ ቫይረሱ ይተላለፋል የሚል ግምት ያለው ሰው ያጋጥማል፡፡
አብዛኞቹ ከቫይረሱ ጋር በሚኖሩ ታዳጊ ወጣቶች ዘንድ የተገነዘብኩትና ተመሳሳይ ሆኖ ያገኘሁት አንድ ጉዳይ አለ፣ ከቫይረሱ ጋር መኖራቸውን እያወቁ(እየተጠራጠሩ) ደጋግመው ጥያቄዎችን ለወላጆች (ለአሳደጊዎቻቸው፡- በአያት፣ በአክስት፣ በእናት ብቻ፣ ወዘተ የሚያድጉ አሉ) ማንሳት አይፈልጉም መድሃኒት በየቀኑ ለምን እንደመሚወስዱና ሃኪም ቤት በተደጋጋሚ ለምን እንደሚሄዱ አይጠይቁም፣ አባታቸው ወይም እናታቸው (ወይም ሁለቱም) በህይዎት ይኑሩ አይኑሩ አይጠይቁም፡፡ ለምን ለሚለው ጥያቄ የአብዛኞቹ  አስተሳሰብ ሲጠቀለል ወላጆቻቸው እንዲጨነቁ ስለማይፈልጉ ነው፡፡ በፈለጉት ጊዜ ይንገሩንየሚል ሃሳብ ነው ያላቸው፡፡ በእርግጥ ይህ አስተሳሰብ የአብዛኞቹ እንጂ የሁሉም አይደለም፡፡ ለምሳሌ የ17 አመት ታዳጊ ወጣት የሆነችው ባለታሪክ እድሜዋ 14 እስኪደርስ ከቫይረሱ ጋር እንደምትኖር አታውቅም፡፡ ሁለት ወንድሞች አሏት ፣ እናቷ ከቫይረሱ ጋር ይኖራሉ፣ አባትዋ በህይወት የሉም፡፡ ይች ታዳጊ ወጣት ጉዳዩን እናቷ እስከዚህ እድሜ በመደበቃቸው እጅግ እንዳዘነች (እያለቀሰች) ትናገራለች፡፡ እናቴ ይህን ብቻ ሳይሆን ሌሎች ብዙ ጉዳዮች እንደምትደብቀኝ ተሰማኝ በወቅቱ መድሃኒቱን በአግባብና ለምን እነደምወስድ ሳልጨነቅ መውሰድ እችል ነበር፡፡ ሆኖም ለብዙ ጊዜ ደበቀችኝ፡፡ ይህች ታዳጊ ወጣት ከሁለት ወንድሞቿ ውስጥ አንዱ ቫይረሱ የለበትም፡፡ የሌላኛው ሁኔታ ግን አይታወቅም፡፡ የራሱ ሁኔታ አለመታወቁ ብቻ ሳይሆን ስለ ቤተሰቦቹ(ስለ እናትና እህቱ) ከቫይረሱ ጋር መኖር አያውቅም፡፡ ይህም በጣም እንዳሳሰባት ትገልፃለች፡፡
እንግዲህ ወደ ኋላ መለስ ብለን ያለፈውን ጊዜ ስንመለከት ከ20 ዓመታት በፊት ከነበረው ጊዜ ጀምሮ የቫይረሱ ስርጭት እየጨመረ በርካቶች የእድሜ ማራዘሚያ መድሃኒት ባለማግኘታቸው እንዲያልፉ ግድ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ወላጆች ብቻ ሳይሆኑ ከእነርሱ የሚወለዱ ልጆች ከተወለዱበት ቀን ጀምሮ በወራት እድሜ ውስጥ በርካቶች ከእቅፍ አምልጠዋል፡፡ ጊዜ ተለውጦ መድሃኒቱ ወደ ሀገራችን ከገባበት ( በተለይ በነፃ ከቀረበበት) ጊዜ ጀምሮ በርካታ ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ወገኖች ህይወታቸውን በአግባቡና በጤና ለመመራት ያስቻለ ሲሆን ራስን የመተካት ምኞትም እውን ሆኗል፡፡ መድሃኒቱ በተለይ ቫይረሱ ከእናት ወደ ልጅ የመተላለፍ እድል እንዳይኖር ረድቷል፡፡ ይሁንና ዛሬ የዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆኑት ታዳጊዎች ምንም እንኳን መድሃኒቱ ደርሶላቸው ከቫይረሱ ነፃ መሆን ባይችሉም እድሜያቸውን ለማራዘም ግን መደበኛውን መድሃኒታቸውን ተግተው ይወስዳሉ፡፡ አብዛኞቹ ትልቅ ተስፋ አላቸው የሳይንስ እድገት በእነሱ እድሜ መፍትሄ እንደሚወልድ፡፡ የሁላችንም ተስፋ ነው፡፡ በርቱልን
 የዚህ ርእሰ ጉዳይ ወግ አልተጠናቀቀም፣ ከፈቀዳችሁ ሳምንት አንብቡኝ፡፡   

በ5 አመት 30 ሺ ስደተኛ ቻይናዊያንን በነዋሪነት የተቀበለች ከተማ ተሸላሚ ሆናለች - 1.6 ሚ. ስደተኞች በከተማዋ ይኖራሉ
          ከተሞች ውስጥ በቋሚነት የሚኖሩ ቻይናዊያን ቢቆጠሩ ወደ 700 ሚሊዮን ገደማ ናቸው። የቻይና መንግስትና ገዢ ፓርቲ እንዲሁም ገለልተኛና ዓለማቀፍ ተቋማት በዚህ ያምናሉ። ነገር ግን፤ እዚያው በዚያው ሌላ ነገር ትሰማላችሁ። የከተማ ነዋሪዎች ቁጥር ወደ 440 ሚሊዮን ገደማ እንደሆነ በይፋ ይነገራል፤ ሪፖርት ይቀርባል። “በአንድ አፍ ሁለት ምላስ” አትሉም? የተሳሳተ ነገር የፃፍኩ እንዳይመስላችሁ። ነገሩ እውነት ነው። “በከተማ የሚኖሩ” እና “የከተማ ነዋሪዎች” ቁጥር እንዴት ይለያያል? የእንቆቅልሹ ፍቺ ይሄውላችሁ። 260 ሚሊዮኖቹ ስደተኞች ናቸው። ከሌላ አገር የመጡ አይደሉም። እዚያው አገራቸው ውስጥ ከገጠር ወደ ከተማ የገቡና በስደተኛነት የተመዘገቡ ቻይናዊያን ናቸው። ከተማ ውስጥ 20 አመት ቢያሳልፉ፣ ቤተሰብ ቢመሰርቱና እዚያው ከተማ ልጅ ቢወልዱ ለውጥ የለውም። “የከተማ ነዋሪ” የሚል እውቅና አያገኙም። ከነልጃቸው “ስደተኛ” በሚል መጠሪያ ነው የሚታወቁት። “ሁለተኛ ደረጃ ዜጎች” የሚል ስያሜም የተለመደ ነው - እዚያው በቻይና የሚዲያ ዘገባዎች ውስጥ ሳይቀር።
“የከተማ ነዋሪ” መሆንና “ስደተኛ” ተብሎ መኖር፣ ልዩነቱ የስያሜ ጉዳይ ብቻ አይደለም። በአንድ ከተማ ውስጥ እየኖሩ፣ በአንድ ፋብሪካ ውስጥ በተመሳሳይ ሙያና ብቃት የሚሰሩ ሁለት ቻይናዊያን እኩል ደሞዝ እንዳያገኙ የሚያደርግ ስርዓት ነው። ጡረታ ሲወጡ የሚያገኙት ክፍያም በ10 እጥፍ ይለያያል። በአጠቃላይ፤ በርካታ አመታትን ያስቆጠረው አድልዎ ከአፓርታይድ ጋር ይመሳሰላል - ባለፈው ሳምንት የወጣው ዘ ኢኮኖሚስት መፅሔት እንደገለፀው።
ነገርዬው፤ የ21ኛው ክፍለዘመን ታሪክ ስለማይመስል ግር ያሰኛል። ምናልባት፤ቻይናን እንደ ሁለት አገር ብንቆጥራት ሳይሻል አይቀርም። ታሪኩ የሚጀምረው፤ የዛሬ 55 ዓመት ነው። በብዙዎቹ ኮሙኒስት ፓርቲዎች ላይ እንደተለመደው፣ የቻይናው ኮሙኒስት ፓርቲ መሪ ማኦ ዜዱንግ ለከተሜነት ጥሩ ስሜት አልነበራቸውም። “ሰዎች በገፍ ከገጠር ወደ ከተማ እየፈለሱ ቀውስ ይፈጥራሉ” የሚለው ሰበብ ተጨመረበትና ቻይናዊያን የመኖሪያ አካባቢያቸውን እንዳይለውጡ የሚከለክል የቁጥጥር ስርዓት ተፈጠረ። በደርግ ዘመን ተጀምሮ ከነበረው ቁጥጥር ጋር ይመሳሰላል። ከቀበሌ “የይለፍ ወረቀት” እና “የመልቀቂያ ፈቃድ” ያላገኘ ሰው ከመኖሪያ አካባቢው መልቀቅ አይችልም ነበር። ያው፤ ኮሙኒስቶች፣ የሁሉንም ሰው ኑሮና ንብረት የመቆጣጠር ረሃብ አለባቸው - የስልጣን ጥም ልትሉት ትችላላችሁ። የቻይናው ቁጥጥር ፈፅሞ የማያፈናፍን መሆኑ ነው ልዩ የሚያደርገው።
የሆነ ሆኖ፤ማኦ ባወጡት ሕግ መሰረት የአገሬው ሰዎች በሁለት ጎራ ተከፍለው ተመዘገቡ - የከተማ እና የገጠር ነዋሪ (hukou) በሚል። “የከተማ ዜጋ እና የገጠር ዜጋ” ልንለውም እንችላለን። ለምን ብትሉ? በጣም አስቸጋሪ ነው። ከገጠር ነዋሪነት ወደ ከተማ ነዋሪነት መሸጋገር፤ ከአንድ የአፍሪካ አገር ተሟሙቶ የአሜሪካ ቪዛና የመኖሪያ ፈቃድ እንደማግኘትና ከዚያም ዜግነት እንደመለወጥ ነው። የገጠር ነዋሪ (ዜጋ) የነበረ፣ እድሜ ልኩን የገጠር ዜጋ እንደሆነ ይቀጥላል - ከነልጆቹ፣ ከነልጅ ልጆቹ።
አዋጁና ቁጥጥሩ ቀስ በቀስ እየላላ የመጣው፣ ከማኦ ህልፈት በኋላ በዴንግ ዚያዎፒንግ መሪነት ኮሙኒስት ፓርቲው የኢኮኖሚ ስርዓት ማሻሻያዎችን ተግባራዊ ማድረግ ሲጀምር ነው። በማኦ ዘመን፣ የአገሪቱ ኢኮኖሚ በሙሉ በመንግስት ቁጥጥር ስር መግባቱ፣ ድህነት መባባሱና ረሃብ መከሰቱ አይገርምም። ሌሎች ኮሙኒስት አገራትም የሚጋሩት ታሪክ ነውና። አስገራሚው ነገር፤ የቻይና ኮሙኒስቶች ከድህነት ለመውጣት፣ መጠነኛ የካፒታሊዝም ወይም የነፃ ገበያ ስርዓት ተግባራዊ ለማድረግ መወሰናቸው ነው - የዛሬ 35 ዓመት ገደማ። “የጋራ መሬትና የጋራ ምርት” በሚል በግዴታ በማህበር ተደራጅተው በጋራ ሲደኸዩ የነበሩ ገበሬዎች፤ ማሳ ተከፋፍለው በግል እንዲያመርቱ ተፈቀደ። በከተማም፣ ንብረት ማፍራት፣ የንግድ ወይም የማምረቻ ቢዝነስ መክፈት ይቻላል ተባለ። ሃብት ማፍራትን እንደ ትልቅ ክህደትና ወንጀል ይቆጥር የነበረ ኮሙኒስት ፓርቲ፤ “ሃብታም መሆን ጀግንነት (ቅዱስነት) ነው - To be rich is Glorious” እያለ በባነርና በፖስተር፣ በሬድዮና በቲቪ ያስተምር ጀመር።
በተከፈተችው የነፃ ገበያ ጭላንጭል አማካኝነት፣ የሚታይ የሚጨበጥ ፍሬ ለማግኘት ጊዜ አልፈጀባቸውም። የአገሪቱ ኢኮኖሚ መሻሻል ጀመረ። የነፃ ገበያ ማሻሻያውም ቀስ በቀስ እየሰፋ፣ በአምስት አመታት ውስጥ ኢኮኖሚያቸው ወደ ፈጣን እድገት ተሸጋገረ። ከዚሁ ጋር አብሮ ነው፤ ታይቶ በማይታወቅ ፍጥነት የስራ እድል መስፋፋት የጀመረው - በከተሞች በተለይም በማምረቻ የኢንዱስትሪ ቢዝነሶች። ነገር ግን፤ ሰዎች ከገጠር ወደ ከተማ እንዳይፈልሱ የሚያግድ ሕግ ይዘው፣ በኢኮኖሚ እድገት መቀጠል አይችሉም። የግድ መለወጥ አለበት። ደግሞም ለውጠውታል።
በእርግጥ ህጉ አልተሻረም። ነገር ግን፤ ሕጉን የሚያላላ ዘዴ ተፈጠረ። ወደ ከተማ ሄደው ለመስራት የሚፈልጉ የገጠር ነዋሪዎች፣ በጊዜያዊነት የይለፍና የመኖሪያ ፈቃድ የሚያገኙበት ሰፊ እድል እንዲያገኙ ነው የተወሰነው። “የአገር ውስጥ የዲቪ ሎተሪ” በሉት። በስደት ጊዜያዊ ቪዛና ጊዜያዊ ግሪን ካርድ እንደማግኘት ነው። ጊዜያዊ ተብሎ የተጀመረው ስደት እየሰፋ ቀጠለ እንጂ አልቆመም - ከተማ የገቡት ስደተኞች ወደ አገር ቤት አልተመለሱም። ግን ደግሞ፣ ጊዜያዊ የመኖሪያ ፈቃዳቸው ወደ ሙሉ ዜግነት አልተለወጠም። 10 እና 20 ዓመት ቢያልፋቸውም፤ ቤተሰብ መስርተው ልጆችን ቢያፈሩም፤ የአገሪቱ ህግ “የከተማ ነዋሪ” በሚል ስያሜ አያውቃቸውም።
ሕይወታቸው ሲታይ፣ በከተማ ከ20 አመት በላይ የኖሩ ናቸው። በህጉ ሲታይ ደግሞ፣ ከነልጆቻቸው ስደተኛ “የገጠር ነዋሪ (ዜጋ)” ናቸው። ከጥቂቶች በስተቀር፣ የብዙዎቹ ስደተኞች እጣ ፋንታ ከዚህ የተለየ ባለመሆኑ፣ ዛሬ ቁጥራቸው 260 ሚሊዮን ደርሷል። በሌላ አነጋገር፣ በከተማ ከሚኖሩት ሰዎች መካከል፣ 37 በመቶ ያህሉ ስደተኛ ወይም ሁለተኛ ደረጃ ዜጎች ናቸው። ልጆቻቸው በመንግስት ትምህርት ቤት ወይም ዩኒቨርስቲ ውስጥ ማስመዝገብ አይፈቀድላቸውም። በመንግስት ሆስፒታል ውስጥ አገልግሎት ማግኘት አይችሉም። መኖሪያ ቤት ሽያጭና ኪራይ ላይ በመንግስት የሚመደቡ ድጎማዎችንም አያገኙም። በዚያ ላይ ከፍተኛ የጡረታ ክፍያ አድልዎ ይጠብቃቸዋል።ይህንን አድልዎ ለማስወገድ እየጣረ እንደሆነ፣ የቻይና መንግስት መግለፁ አልቀረም። ለበርካታ አመታት በከተማ የኖሩ “ስደተኞች”፣ ሙሉ“የከተማ ነዋሪነት”ን የሚቀዳጁበት ሂደት እንደተጀመረም ይገልፃል። ነገር ግን፤ ሂደቱ ገና ፈቅ አላለም። በአርአያነት የተሸለመችውን ከተማ መጥቀስ ይቻላል። ዞንግሹን ትባላለች። በከተማዋ ከሚኖሩ ሰዎች መካከል ግማሾቹ “ስደተኞች” ናቸው - 1.6 ሚሊዮን ያህል። ባለፉት አምስት አመታት ከእነዚህ ውስጥ “የከተማ ነዋሪነት”ን የተቀዳጁት 30ሺ ያህሉ ብቻ ናቸው። በከተማዋ ውስጥ ካሉት 200ሺ የስደተኛ ልጆች መካከልም በመንግስት ትምህርት ቤት እንዲመዘገቡ የተፈቀደላቸው ለ25ሺ ያህሉ ነው። የማኦ ቅርስ የኮሙኒዝም ውርስ የሆነው አድልዎ ገና አልተነካም ቢባል ይሻላል።

ሳውዲ ዓረቢያ በዚህ ወር 50 ስሞችን ጥቁር መዝገብ ውስጥ አስገባች
አንዳንድ መንግስታት፣ ይህንንም ከልክለው ያንንም አግደው ሲያበቁ የሚሰሩት ነገር እየጠፋባቸው የሚጨነቁ ይመስላሉ - የሚከለከል ነገር ቢጠፋ የስም አይነት ይከለክላሉ፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የአንዳንድ ወላጆች ነገረ ሥራ ከአብዮት አይተናነስም፡፡ በስዊድን አገር የልጃቸውን ስም ሲያስመዘግቡ፣ “Brfxxccxx” ብለው ነው የጀመሩት፡፡ የልጃቸው ስም ገና ተጽፎ አላለቀም፡፡ ከ40 በላይ ፊደሎችን የያዘ ስም ነው፡፡ የመጨረሻዎቹ ስምንት ፊደላት “Sqlbb11116” ይላል፡፡ በስንት መከራ ነው ለልጃቸው ሌላ ስም እንዲያወጡ የተደረጉት፡፡
በየአገሩ በልጆቹ ስም ላይ ለመጫወት ወይም ለመቀናጣት የሚሞክር ወላጅ እንደማይጠፋ በመጠቆም፣ ግሎባል ፖስት ዘገባውን ሲያቀርብ በኒውዝላንድ ሁለት ወላጆች ሊነበብ የማይችሉ ስሞችን እንዳስመዘገቡ ገልጿል፡፡
እንደ ገመድ የረዘሙ ስሞችን አልመረጡም፡፡ እጥር ምጥን ያሉ ስሞችን ነው ያስመዘገቡት፡፡ አንደኛው ወላጅ ለልጃቸው ስም ሲመርጡለት በአንድ ነጥብ ጨረሱት፡፡ አንዲት የነጥብ ምልክት ብቻ ነች የምትታየው - ሲመዘገብ በድምጽ ምን ተብሎ እንደሚጠራ እንጃ፡፡ ሌላኛው ወላጅም እንዲሁ የልጃቸውን ስም ሲያስመዘግቡ ትንጥዬ ጨረር መሰል ምልክት አስፍረዋል (*) በዚህም በዚያም ተብሎ የኋላ ኋላ ለልጆቻቸው ሌላ ስም ለመምረጥ ተስማምተዋል
እንዲህ አይነት ችግሮችን ለማስወገድ፤ በጃፓን፣ የልጆች ስም በቀላሉ በጽሑፍ የሚገለጽና የሚነበብ መሆን አለበት የሚል ህግ አለ፡፡ ተገቢ አይደሉም የሚባሉ ስሞችም ይከለክላሉ፡፡ ለምሳሌ “አኩማ” ብሎ ስም አይፈቀድም - ሰይጣን እንደማለት ነው፡፡
በጀርመን፣ የወንዶችን ስም ለሴት ወይም ደግሞ የሴቶችን ስም ለወንድ መጠቀም አይቻልም፡፡ ከዚህ በላይ፤ የወንድ ይሁን የሴት ተለይተው የማይታወቁ ስሞች ተቀባይነት አይኖራቸውም፡፡
አንዳንድ አገሮችማ የሚፈቀዱና የማይፈቀዱ የስም አይነቶችን እየዘረዘሩ አዋጅ አውጥተዋል፡፡ በክርስትና የሃይማኖት አክራሪነት በነበረበት ዘመን በፖርቱጋል የሚፈቀዱ ስሞች በሃይማኖታዊ መፃሕፍት ውስጥ የተጠቀሱ ስሞች ብቻ ነበሩ፡፡ በእስልምና የሃይማኖት አክራሪነትን የሚያራምዱ ሰዎች በመበርከታቸው ይመስላል፣ ማሌዢያ ከስምንት አመት በፊት አዲስ ህግ አውጥታለች፡፡ ልጆችን በእንስሳት፣ በነፍሳት፣ በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በቅጠላቅጠልና በቀለም አይነቶች መሰየም ይከለክላል ህጉ፡፡ ብርቱኳን፣ ሃረገወይን፣ አንበሴ፣ ነብሮ፣ ግራር ወይም ፅድ ብሎ መሰየም አይቻልም፡፡ በዚህ ወር በሳዑዲ አረቢያ በጥቁር መዝገብ ውስጥ እንዲካተቱ ከተደረጉት 50 ስሞች መካከል ገሚሶቹ የተወገዙት ከውጭ አገር የተወሰዱ ናቸው በሚል ምክንያት ነው - ሊንዳ እና አሊክ የመሳሰሉ ስሞች፡፡ የንጉሳዊውን ቤተሰብ ክብር ይዳፈራሉ ተብለው ከታገዱት ስሞች መካከል ደግሞ “ማሊካ” የሚል ይገኝበታል - እቴጌ ወይም ንግስት ማለት ነው፡፡ በሃይማኖት ሰበብ የተከለከሉም አሉ፡፡ ጅብሪል (ገብርኤል) ብለው ለልጅዎ ስም ማውጣት አይችሉም፡፡  

በታዋቂዋ የክራር ተጫዋችና ድምጻዊት በአስናቀች ወርቁ የህይወት ታሪክ ዙሪያ የሚያጠነጥነውና ‘አስኒ’ የሚል ርዕስ ያለው ዘጋቢ ፊልም፣ ከትናንት በስቲያ በኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ የአፍሪካ-አሜሪካ ጉዳዮች የሲኒማ ጥናቶችና የአፍሪካ ጥናቶች ፕሮግራም ኢንስቲቲዩት ለመጀመሪያ ጊዜ ለእይታ በቃ፡፡
ነዋሪነቷ በአሜሪካ በሆነው ራሄል ሳሙኤል ዳይሬክተርነት የተዘጋጀውና ሰርቶ ለማጠናቀቅ ከአራት አመታት በላይ የፈጀው ይህ ዘጋቢ ፊልም፣ የድምጻዊቷን የህይወትና የሙያ ጉዞ በጥልቀት የሚዳስስ እንደሆነ ታዲያስ መጽሄት ከኒውዮርክ ዘግቧል፡፡
‘አስኒ’ ዘጋቢ ፊልም፣ ከሶስት አመታት በፊት በ76 ዓመት ዕድሜዋ ከዚህ አለም በሞት የተለየችው ድምጻዊት አስናቀች ወርቁ፣ በኢትዮጵያ ሙዚቃ ውስጥ የራሷን ደማቅ አሻራ ጥላ ያለፈች፣ በዘመኗ ለነበሩ ወጣት አርቲስቶች ፈር የቀደደችና፣ በትወናው መስክም ድንቅ ክህሎቷን ያሳየች ዘመን ተሻጋሪ አርቲስት መሆኗን የሚያሳይ እንደሆነ ተነግሯል፡፡
የፊልሙ ዳይሬክተር ራሄል ሳሙኤል ከዚህ በፊትም በሳንፍራንሲስኮ ውስጥ በተከናወኑ ታላላቅ የማስታወቂያ ፕሮጀክቶች ላይ በተለያዩ ኤጀንሲዎች አማካይነት ስትሰራ የቆየች ሲሆን፣ ፊልሙን ኤዲት ያደረገውና በጋራ ፕሮዲዩስ ያደረገውም፣ በኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ ሞሬስ ካንባር የፊልምና የቴሌቪዥን ኢንስቲቲዩት ተባባሪ ፕሮፌሰር የሆነው ኢትዮጵያዊው የማነ ደምሴ ነው፡፡

  የአድዋ ድልን 118ኛ ዓመት ክብረ በዓል ምክንያት በማድረግ “ዝክረ አድዋ” የኪነ-ጥበብ ፌስቲቫል የፊታችን ሰኞ ከ11፡30 ጀምሮ በብሄራዊ ቴአትር እንደሚካሄድ “ኬር ኢቨንትስ እና ኮሙዩኒኬሽን” አስታወቀ፡፡ ፌስቲቫሉ ለሶስተኛ ጊዜ የሚካሄድ ሲሆን የዘንድሮው የአድዋ ድል 118ኛ ዓመትና የሚያዚያ 27 የአርበኞች ድል 74ኛ ዓመት በጥምረት እንደሚከበር ድርጅቱ ገልጿል፡፡ “ዓለምን ያስደነቀውን የያኔዎቹ ጀግኖች አባቶቻችንንና እናቶቻችንን አኩሪ ድል በቴአትር፣ በሽለላ፣ በውዝዋዜ፣ በፊልም፣ በፎቶና በውይይት እንድንዘክረው ወስነናል” ብሏል አዘጋጁ፡፡
በፌስቲቫሉ ላይ መገኘት የሚፈልጉ ሁሉ እንዲታደሙለትም ጥሪውን አስተላልፏል ኬር ኤቨንትስ እና ኮሙዩኒኬሽን፡፡     

“ሚኒልክና አድዋ” በተሰኘው የሬይሞንድ ጆናስ መጽሐፍ ላይ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ገለፀ፡፡
ውይይቱ ነገ ከቀኑ ስምንት ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተ መፅሐፍትና ቤተ - መዛግብት ኤጀንሲ የስብሰባ አዳራሽ እንደሚካሄድም ታውቋል፡፡ ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ የሚያቀርቡት  የታሪክ ምሁር የሆኑት አቶ ብርሃኑ ደቦጭ ሲሆኑ፤ በውይይቱ ላይ የንባብ ቤተሰቦች  እንዲሳተፉ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጋብዟል፡፡