Administrator

Administrator

“ማን ኦፍ ስቲል” በተባለው ፊልም ላይ የሱፐር ማንን ገፀባህርይ በብቃት በመተወን ሄነሪ ካቪል እንደተዋጣለት “ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር” ገለፀ፡፡ እንግሊዛዊው ተዋናይ ሄነሪ ካቪል ሱፐርማንን ለመምሰል ሲል 40 ፓውንድ ኪሎ ቀንሷል ያለው ዘገባው፤ ይህን ለማሳካትም ለ11 ወራት በሳምንት 12 ሰዓታትን የአካል ብቃት እንቅስቃሴን ማድረጉን አትቷል፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት ለእይታ የበቃው ፊልሙ፤ በመላው ዓለም ያስገባው ገቢ 400 ሚሊዮን ዶላር ደርሷል፡፡

የሱፐር ማን ፊልሞች ተወዳጅነት በአሜሪካ ብቻ ተወስኖ ቢቆይም “ማን ኦፍ ስቲል” ከአሜሪካ ባሻገር በመላው ዓለም ተወዳጅነት በማግኘት የመጀመርያው እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ዋርነር ብሮስ ለፊልሙ በጀት 225 ሚሊዮን ዶላር ያወጣ ሲሆን፤ የሱፐር ማን ገፀባህርይ በካርቱን ኮሚክ መፅሃፍ፤ በቲቪ ተከታታይ ፊልሞች እና እስካሁን በተሰሩ ፊልሞቹ ላለፉት 70 አመታት ዝናና ስኬትን ተቀዳጅቶ መቆየቱ ይታወቃል፡፡ “ማን ኦፍ ስቲል” መታየት ከጀመረ በኋላ ከሱፐር ማን ጋር የተያያዙ የንግድ እንቅስቃሴዎች መሟሟቃቸውን የዘገበው “ብሉምበርግ ኒውስ” በበኩሉ፤ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የሱፐር ማን ቲሸርቶች እና አሻንጉሊቶች እንደተቸበቸቡ ገልጿል፡፡

ቁምነገር የጋዜጠኞች ማሰልጠኛ ማዕከል በተለያዩ የጋዜጠኝነት ዘርፎች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ትናንት ማታ አስመረቀ፡፡ ለአራተኛ ዙር የተመረቁት 31 ተማሪዎች በመሰረታዊ ጋዜጠኝነት፣ ዜናና ፊቸር አፃፃፍ እና በቃለምልልስ ቴክኒክ ስልጠና ተሰጥቷቸዋል፡፡ ምረቃው የተካሄደው ራስ ሆቴል ጀርባ በሚገኘው የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 7 አዳራሽ ነው፡፡

በአንጋፋው ድምፃዊ መሐሙድ አህመድ በ“የሺ ሀረጊቱ” የተሰኘ ዘፈን መነሻነት የተፃፈው ልቦለድ መፅሐፍ ታትሞ ለንባብ ቀረበ፡፡ በዚህ ሳምንት እየተሰራጨ ያለውን መፅሐፍ የደረሰው ደጀኔ ተሰማ ነው፡፡ 235 ገፆች ያለውን መፅሐፍ ያተመው እታፍዘር ማተሚያ ቤት ሲሆን አከፋፋዩ ሊትማን ጀነራል ትሬዲንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ነው፡፡ መፅሐፉ በ40 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ በሌላም በኩል በጋዜጠኛ አቤል አለማየሁ እና ኤልያስ ገብሩ የተዘጋጀው “ኢትዮጵያን ማን ይታደጋት” መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡

ጋዜጠኞቹ 255 ገፆች ባለው መፅሐፋቸው ከ12 ምሁራን፣ ጋዜጠኞች፣ የሐይማኖት ልሂቃን እና ፖለቲከኞች ጋር የተደረጉ ሙግቶችና ውይይቶች አካተዋል፡፡ በመፅሐፉ ያለፈው መንግሥት ከፍተኛ ባለስልጣን የነበሩትና ዘንድሮ ህይወታቸው ያለፈው ኮሎኔል ደበላ ዲንሳ የመጨረሻ ቃል፣ የሃይማኖት መቻቻል፣ ሕገመንግስት፣ የብርቱካን ሚደቅሳ ፖለቲካ የሚሉና ሌሎች ርእሰ ጉዳዮች ተካተዋል፡፡ መፅሐፉ በሀገር ውስጥ በ49.60 ብር በውጭ ሀገራት በ20 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡

በሰሜን አሜሪካ ከሚገኘዉ ታዋቂዉ የፊልም ኩባንያ ከ”አባይ ሙቪስ” እና በርካታ ሀገርኛ ሲኒማ በመስራት ላይ የሚገኘዉ እና በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሥራ ላይ የተሰማራዉ ኦክቴት ኮምፒዉተር ቴክኖሎጂ በመተባበር በሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሚያዘጋጀዉን እና የሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የተመሰረተበትን የ30ኛ ዓመት አከባበር ሥነ-ስርዓት ከሰኔ 23 2005 ዓ.ም እስከ ሰኔ 30 2005ዓ.ም በሰሜን አሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ ሜሪላንድ ዉስጥ በርካታ ቁጥር ያላቸዉ ኢትዮጵያዉያን እና ትዉልደ ኢትዮጵያን በሚገኙበትን ይከበራል፡፡በዚህም ዝግጅት ላይ ታዋቂ የሀገርችን አርቲስቶች የሙዚቃ እና የተለያዩ ባህላዊ እሴቶችን የሚያንጸባርቁ ዝግጅቶችን ያቀርባሉ፡፡ በዝግጅቱም ላይ በርካታ ታዋቂ ስፖርተኞች፣ ጋዜጠኞች የፊልም ባለሙያዎች በዝግጅቱ ላይ ይታደማሉ፡፡ ዝግጅቱ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ይተላለፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ብሉ ኦሽንና ናይት ክለብ በመሪ ሲኤምሲ አካባቢ ተከፈተ፡፡ ክለብ ቪ አይ ፒ ሰርቪስ ያለው መስተንግዶ ጋር የሚሰጥ ከ 70 በላይ ለሰራተኞች እድል እንደፈጠረ በተመጣጣኝ አገልግሎት የተለያዩ ባህላዊና የውጪ አገር ምግቦች ያቀርባል በተለይ አርብና ቅዳሜ በዲጄ ሳሚ ይቀርባል፡፡ ብሉ ኦሽን ናይት ክለብ በዘመናዊ የመብራት እና የድምጽ ቴክኖሎጂ የተዋቀረ በውስጥና የውጭ መስተንግዶ በመስጠት ከሌሎች ናይት ክለቦች በተለይ መልኩ አገልግሎት እንደሚሰጥ ሰኔ 15ቀን 2005 ዓ.ም በተመረቀበት ጊዜ ተገልጿል፡፡

በፋሲል አስማማው ተፅፎ በደረጀ ደመቀ የተዘጋጀው “ጀንኖ” የተሰኘ አዲስ ፊልም ዛሬ በሐዋሳ ከተማ እና በሌሎች ክልል ከተሞች ይመረቃል። በጵንኤል ፕሮሞሽንና ማስታወቂያ ድርጅት ፕሮዱዩሰርነትና በታምሩ ብርሃኑ ፕሮዳክሽን የተሠራው ፊልሙ፣ የሮማንቲክ ኮሜዲ ዘውግ ሲኖረው አልጋነሽ ታሪኩ፤እንቁስላሴ ወርቅ አገኘሁ፣ዘነቡ ገሠሠ፣ ደረጀ ደመቀና ተመስገን ታንቱን ጨምሮ ከ60 በላይ ተዋናዮች ተካፍለውበታል፡፡ ፊልሙ በሐዋሳው የሲዳማ ባህል አዳራሽ በሚመረቅበት በዛሬው ዕለት በዲላ፣ በሻሸመኔ እና በነገሌ ቦረና እንደሚመረቅ የፊልሙ ደራሲ ፋሲል አስማማው ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ በቅርቡም በአዲስ አበባ በሚገኙ ሲኒማ ቤቶች ይመረቃል፡፡

Saturday, 29 June 2013 10:38

የፍቅር ሽልማት

ፍቅር ሽልማት የለውም
አንተ ግን ሽልማት አለህ!
እንደ ትንቢት - ተናጋሪ፣ የነገን ዕውቀት አበጀህ!
የእናት ያባት ዕውቀት ማለት፤
የልጅ ሽልማት ውብ ኩራት!!
የራስህ ትምርት ትጋት
የራስህ ትምርት ንጋት
የዛሬህን ጐዶሎ፣በነገ ጥበብህ መሙላት
ይሄ ብቻ ነው ዓለምህ፣ የራስህ ፍቅር ጉልላት!!
(ነ.መ፤ ኢዮብና አሥቴር ለፍቅር የትምህርት ድል)
ሰኔ 21 2005 ዓ.ም

ከዛሬ አሥር ዓመት በፊት በሣሉ ብዕረኛ ተፈሪ መኮንን “ግጥም ሞቷል” ሲል በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ መርዶ በማርዳት ቁጣዬ የበረታ እንደነበር አስታውሳለሁ። ከፀሐፊው ጋር የስልክ ሙግት መግጠሜም አልቀረም፡፡ ውሎ ሲያድር ግን የጥበቡን ሰማይ ሳይ ከዋክብት እየነጠፉ፣ ውበት እየጨለመ ሲመጣ ልቤ ደረቴን በስጋት መደብደብ ጀምራ ነበር፡፡ ያ ሥጋትም ስለግጥም ይበልጥ ማሰብ፣ ከዚያም አለፍ ሲል እያነበቡ ሃሳብ ወደማቅረብ የገፋኝ ይመስለኛል እንደተፈራው፡፡ የግጥሙ ሰፈር ልክ የሌላቸው ገለባዎች መፈንጫም መሆኑ አልቀረም፡፡ ነፍስ የሌላቸው ገለባዎች እንደፈርጥ የሚንቦገቦጉትን የብዕር ውበቶች እንዳያንቁ ብዙዎቻችን ሠግተናል። አዝነን አንገታችንንም ደፍተናል፡፡ ግና አሁን አሁን ሰማዩን ሳየው ተስፋ ያረገዘ፣ ውበት ያነገተ ይመስላል፤ ብዙ ገላባዎች ቢኖሩም ፍሬ ያላቸው ወጣት ገጣሚያን መጋረጃውን ገልጠው ብቅ ብቅ እያሉ ነው፡፡

ወጣትነት ሙሉነት የሚጠበቅበት ዕድሜ አይደለም፡፡ ወደ ሙሉነት የመድረሻ ጉዞ ፍንጭ እንጂ፡፡ የቀደሙትና ብርቱ የሚባሉት ገጣሚያንም መንገድ ከዚህ የተለየ አልነበረም፡፡ አሁን የዘመናችን ወጣት ገጣሚያን መንገድ ጥሩ ተስፋ እየሰጠ ነው፡፡ በጣት የሚቆጠሩ ቢሆኑም ለጥበቡ ውበት፣ መሥመር እያበጁ፣ ሕይወት እያፈሩ መምጣታቸው አይቀሬ ነውና ልብ የሚሞላ ጉጉት ፈጥሯል፡፡ እውነት ለመናገር የቀደመው ዘመን አፍርቷል ከምንላቸው ገጣሚያን የማያንሱ ገጣሚያን ቁጥርም እየፈጠርን ይመስለኛል፡፡ አሁን የሚያስፈልገን የንባብ ባህል ይበልጥ እንዲጨምር በማድረግ እምቡጦቹ አብበውና አፍርተው፣ ጐደሎዎቻችንን እንዲሞሉ ማስቻል ነው፡፡ በቅርብ ጊዜ የታተሙ የግጥም መጻሕፍትን ሳይ የተሰማኝ ስሜት ያ ነው፡፡ ተስፋ ያንለጠለጠለ በሣቅ የታጀበ፡፡ ዛሬ ያየነው ተስፋ ነገ በውበት የደመቁ ዓመታት እንደሚወልዱልን አያጠራጥርም፡፡

ቀደም ሲል በዮሐንስ ሞላ መጽሐፍ ላይ የደመቀ ተስፋ እንዳየሁ ሁሉ የወሎው ገጣሚ መንግስቱ ዘገየም ደስ በሚል ልብና ኃይል ተገልጦ አይቼዋለሁ፡፡ ጋዜጠኛ በረከት በላይነህም “የመንፈስ ከፍታ” በሚለው ጥራዙ የፋርስ ግጥሞችን መርጦ በመተርጐምና የራሱን ግጥሞች በማቅረብ የጥበብ ሆዳችንን ረሃብ ለማስታገስ የሚችል አበርክቶት አኑረዋል፡፡ ደስ ይላል፡፡ የበረከት ግጥሞችን በጥልቀት የመገምገምና የመተንተኑን ሥራ ላቆየውና ለጊዜው ቀልቤን የኮረኮሩትን ግጥሞች ልዳስስ መርጫለሁ፡፡ “የፈሪዎቹ ጥግ” ስሜቴን ከዳሳሱት፣ ሃሳቤን ከነጠቁት ግጥሞቹ አንዱ ነው፡፡ እንዲህ ይነበባል:- በማያውቀው ስንዝር ዕድሜው እንዳይለካ፤ ባልቀመሰው እርሾ ነገው እንዳይቦካ፤ ይፈራል የሰው ልጅ፤ ይሰጋል የሰው ልጅ አይጨብጥ አይነካ፡፡ አይገርምም! መሸጥ አያሰጋው፣ መግዛት እየፈራ፣ “አለመወሰኑን” ትርፍ ብሎ ጠራ፡፡ እኔ የምለው! ቀኝ ግራ ኋላ፣ ፊት - እስካልተከለለ፤ በጥግ - የለሽ ነገር መሃል መስፈር አለ? ይህ ምስኪን ወገኔ! ላበጀው ጥያቄ እስካልተፈተሸ፤ ቅዠት አቅፎ ያድራል - ሕልሙን እየሸሸ፡፡ ገጣሚው በረከት ተናግሮታል ብዬ የማደምቀው ሃሳብ፣ ሰው ነገር የሚያይበት ተጨባጭ ራዕይ፣ የሚጓዝበትን መንገድ የሚያስተውልበት አይን አጥቶ፣ በሰከረ ዓይን የሚዋዥቅ ሆኗል የሚለውን ይመስላል፡፡ ሁሉ አማረሽ በመሆኑ ወደፊት ፈቅ የሚልበትን ምርጫ እንደ ጨርቅ አውልቆ ጥሏል።

መላ ቅጡ በጠፋ ስካር ውስጥ ተዘፍቆ ትክክለኛ አድራሻውን የሚያሳየውን ሕልሙን ወደ ኋላ ዘንግቷል ነው የሚለው፡፡ ሕልም የሌለውና ሕልሙን የሸሸ ሰው መድረሻው የት እንደሚሆን ሊሰብከን አልሞከረም፡፡ የወደደ ሰው ወደ መጽሐፍ ቅዱሱ ዮሴፍ፣ ወዲህ ቀረብ ሲል ደግሞ ወደ ማርቲን ሉተር ኪንግ ተጠግቶ “ሕልም አለኝ” የምትለውን ሃሳብ መፈልፈል አለበት፡፡ ለዚያም መሰለኝ “ይህ ምስኪን” ብሎ ለሕልም አልባው ሰው ከንፈር የመጠጠለት! “ሸማኔ ሲፎርሽ” ለኔ ከተመቹኝ ግጥሞች አንዱ ነው፡፡ “ታታሪው” ሸማኔ! ከመመሳሰል ውስጥ ውበትን ቀምሮ፤ “ጥበብ” ያለብስናል ካንድ ቀለም ነክሮ፡፡ ለባሾች አይደለን? እንተያያለን፤ እንተያያለን፤ ኤዲያ!! ጥለቱ ጋ ስንደርስ እንለያያለን፡፡ መቼም አይታክተን! እንወርዳለን ቆላ፤ እንወጣለን ደጋ፤ ጥለት አመሳሳይ ሸማኔ ፍለጋ እዚህ ግጥም ውስጥ ዋነኛው ተዋናይ ሸማኔ ነው፡፡ በእማሬያዊ ፍቺው ምናልባት ሸማኔው ብዙ ሲሆን፤ በብዙ ሊተነተን ይቻላል፡፡

በርግጥም ስለግጥም የፃፉ ምሁራን እንደሚሉት ግጥም ራቁቱን የተሰጣ ባይሆን ይመረጣል፡፡ ለአንባቢው አዲስ ቃና፣ ፍልፍል ውበት ቢያበቅል ደስ ይላል፡፡ እንደግጥሙ ሆኖልን ጥለት ውበት በመሆኑ ሸማኔ ፍለጋ ላይ ታች ካልን ይገርማል፡፡ ደስ የማይለው ግን ለማመሳሰል መሆኑ ነው፡፡ ከመመሳሰል መለያየት ሳይሻል አይቀርም፡፡ እንኳን ጥበብ ሰው ራሱ ቢመሳሰል ሕይወት ትሠለቻለች፤ ተስፋ ትርቃለች። ቀለምም አያምርም፡፡ ዜማም ይጠነዛል፡፡ በረከት ያለው የትኛው መመሳሰል እንደሆነ ስላላወቅን የየራሳችንን መጠርጠር እንጂ የየልባችንን መደምደሚያ ቀዳዳ የለንም፡፡ ቢሆንም እንዲህ ወዲያ ወዲህ መባዘንም ጥሩ ነው፡፡ መመርመር ክፋት የለውም፡፡ የበረከት “የመንፈስ ከፍታ” የፋርሶቹን ግጥሞችም ይዟል፡፡ ለዛሬ ላስቃኛችሁ የወደድኩት ግን የራሱን የበረከትን ስለሆነ አልነካውም እንጂ እጅግ ያደነቅሁለት ምርጥ ግጥሞችን አስሶ መተርጐሙ ነው፡፡ አሁን ግን ወደ በረከት “ልዩነት” ተመልሼ በመሄድ ጥቂት እላለሁ፡፡

ብዙዎች አንደበቱ ባይጥም፤ ለጆሮ ባይመች ትምህርት አሰጣጡ “ኤዲያ” የጋን ውስጥ መብራት በማለት አድመው ካዳራሹ ወጡ፡፡ ጥቂቶች የመምህሩ ዕውቀት፤ “የጋን ውስጥ መብራት” መሆኑን ያመኑ፤ አምነው የተግባቡ አዳራሹን ትተው “ወደ ጋኑ” ገቡ፡፡ እዚህ ግጥም ውስጥ አንድ መምህር ጐልቶ ይታያል፤ ማስረዳት የማይችል፤ ለሌሎች ዕውቀቱን ማካፈል ያልታደለ፡፡ ቅላፄው ለጆሮ የማይጥም። በዚህ ምክንያት የክፍሉ ተማሪዎች ለሁለት ተከፍለዋል፡፡ አንዱ ወገን እዚህ ሰውዬ ዘንድ ተቀምጦ ጊዜ ከማቃጠል አዳራሹን ለቅቆ መሄድ ይሻላል በሚል መምህሩን ንቆ ትቶት ወጥቷል፡፡ ሌላኛው ወገን ደግሞ መምህሩ ቀሽም በመሆኑ ተስማምቷል፤ ሃሳቡን ለሌሎች ማካፈል የማይችል የጋን ውስጥ መብራት በሚለው ተግባብቷል፤ ስለዚህም በተመሳሳይ አዳራሹን ትተው ወጥተዋል። ግን የውስጡን እሣትና ብርሃን ፍለጋ ጋኑን መፈልፈል ይዘዋል፡፡ የጋኑን መብራት ያነቀው ምንድነው የሚል ፍለጋ ይመስላል፡፡

ተስፋ የቆረጠና ተስፋውን ያልጣለ ወገን ለየቅል ቆመዋል፡፡ መምህሩ የተደበቀ ሕይወት፣ መንገድ ያጣ ውበት ቋጥሯል። ግን መንገድ የለውም፤ ጋን ውስጥ ገብቶ ከጋን ውስጥ እሣቱን ማውጣት ይቻል ይሆን…ቢሆንም የበረከት ከፊል ገፀ ባህርያት ወደ ጋኑ ገብተዋል። አዳራሹ ውስጥ መምህሩ ሻማ መሆን ካልቻለ መምህሩ ውስጥ ያለውን ሻማ ፍለጋ መዳከር ሊጀምሩ ይሆን? ማን ያውቃል? “ኑሮና ጣዕም” ሌላው የበረከት በረከት ነው፡፡ ሙያዬን ታውቃለህ፤ ማጀቴን ታያለህ፤ “እንጀራሽ እንክርዳድ፣ ገበታሽ ጣዕም - አልባ” ለምን ትለኛለህ በል ዝም ብለህ ብላ ቸርቻሪ መንግስታት፣ ሰነፍ ገበሬዎች፤ በዝባዥ ነጋዴዎች፣ በበዙባት ዓለም፤ ጠንካራ ጥርስ እንጂ ቀማሽ ምላስ የለም ሕይወትን አትመራመር፣ አታጣጥም…ዓለም በስግብግቦች ተሞልታለች፡፡

ቀልብ ያለው የለም፤ የሰው ጆሮ ሣንቲም ሲያቃጭል ከመደንበር ያለፈ ማጣጣም አቅቶታል ስለዚህ አቃቂር ለማውጣት አትሞክር! ይልቅ እዚህ ውበት ስትፈለፍል፤ ቃና ስታጣጥም ከሩጫው እንዳትቀር ዓለም ውበቷን ጥላለች፡፡ ሰውየው ብቻህን አትበድ…!ሁሉም ነገር ተናካሽ ጥርስ እንጂ አጣጣሚ ምላስ አጥፍቷል፡፡ ሰውየው አትጃጃል ባይ ትመስላለች፡፡ ጠቅለል ሲል በረከት፤ በቃላቱ ሃይል አያስደነግጥም፤ በዜማ ሽባነት ግራ አያገባም፡፡ ቀለል አድርጐ ስንኝ መቋጠር ይችላል፡፡ ግጥም ቀዳሚ ተግባሩ ደስታ መፈንጠቅ ነው - የሚለውን የበርካታ ምሁራን ሃሳብ ይዞ የሚቀጥል ይመስላል። ወደፊት ደግሞ የተሻለ ችቦ ከመንገዱ ሲንቦገቦግ ይታየኛል፡፡ ተስፋው ሩቅ፣ ዕድሜው ለጋ ነው….የወጣትነቱ እፍታ ጥሩ ነው፡፡ የፋርስ ግጥሞቹ ምርጫና ስልት ደግሞ ልዩ ነው፡፡

የጀግና ሰው መልኩ ሁለት ብቻ ነው፤ አንድ ፊት መስዋዕት በአንድ ፊት ድሉ ነው፤ የሁሉም ማሰሪያ ማተቡ ብቻ ነው፡፡ (“የአሲምባ ፍቅር” ገፅ 140) ካህሳይ አብርሃ ወይም በበረሀ ስሙ አማኑኤል ተብሎ ይጠራል፡፡ መስከረም 27ቀን 1968 ዓም የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ሰራዊትን ለመቀላቀል ወደ ትግል ወጣ፡፡ ሰኔ 27ቀን 1968 ዓም ወልዲያ ለተልዕኮ የወጣ የሠራዊቱ ቡድን ወደ አሲምባ በተመለሠበት ዕለት በተፈጠረ የጦርነት አጋጣሚ ከይመር ንጉሴ ጋር ተገናኘ፡፡

በ1970 በኤርትራ አድርጎ ሱዳን በመግባት ከሠራዊቱ ተለየ፡፡ ኑሮውም በአሜሪካ ሆነ፡፡ የደርግ አገዛዝ ሲገረሰስ ይመር ንጉሴን ለማግኘት እንዲሁም የመጀመሪያ የሴት ፍቅረኛው የተሠዋችበትን ቦታ ለማየት ወደ ኢትዮጵያ መጣ። በሰራዊቱ ውስጥ ስላሳለፈው የትግል ህይወት የሚተርክ “የአሲምባ ፍቅር” የተሰኘ መፅሀፍ ባለፈው ቅዳሜ የቀድሞ የኢህአፓ አባላትና ሌሎች እንግዶች በተገኙበት አስመርቋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ በአሜሪካ ከሚኖረውና በፋርማሲ ባለሙያነት ከተሰማራው ካህሳይ አብርሃ ጋር ስለ መፅሀፉ እና የትግል ህይወቱ አነጋግራዋለች፡፡

                                                    ***

በየትኛው ስም ልጠቀም---- አማኑኤል በሚለው ወይስ በበረሀ ስምህ ካህሳይ? በፈለግሽው መጠቀም ትችያለሽ፡፡ ወደ አሲምባ የገባህበትን የመጀመሪያዎቹን ቀናት እንዴት ታስታውሳቸዋለህ? ስሜቱን ልገልፀው አልችልም፡፡ ለመብት ከሚታገል ድርጅት ጋር መቀላቀል ደስታ ፈጥሮብኝ ነበር፡፡ ኑሮው ውጣ ውረድ ያለበት መሆኑ አልከበደህም? ረሀቡ፣ ጥማቱ እና ውጣ ውረዱ ያለ መሆኑን ገምቼ ስለገባሁበት እንቅፋት አልሆነብኝም፡፡ የታጠቁትን መሳሪያ ሳይ ደግሞ በጣም ደስ አለኝ። እዛ ያሉትን ጓዶች ሳያቸው የበለጠ ተደሰትኩ፡፡ በጣም አዋቂ ሰዎች ነበሩ፡፡ ከሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢ የመጡ፡፡ የኢህአፓ አባል የሆንከው ቆይተህ ነው፡፡ ለረጅም ጊዜ የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ሠራዊት (ኢህአሠ) አባል ነበርክ፡፡ ስለፓርቲው ምን ያህል እውቀት ነበረህ? ፓርቲው የበላይ አካል እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ የፓርቲ አባል ባልሆንም የሚደረጉትን ነገሮች በሙሉ አውቅ ነበር፡፡

ለምሳሌ የፓርቲው አባሎች ስብሰባ ሲያደርጉ ለፀጥታ ጉዳይና ለደህንነት በሚል መሪዎች ይነግሩናል፡፡ ስለዚህ ኮሚሳሩ “እገሌ እገሌን ይዘን እንሄዳለን” ካለኝ የፓርቲ ስብሰባ እንዳለ እናውቃለን ማለት ነው፡፡ የሆነ መመሪያ በሚወጣበት ጊዜ በመጀመሪያ የፓርቲ አባሎች ይወያዩበታል፤ ከዛ ወደ ሠራዊቱ ይመጣል፡፡ የፓርቲ አባል ስሆን በህይወት እቆያለሁ የሚል ሀሳብ አልነበረኝም፡፡ በማንኛውም ወቅት ግዳጄን ስወጣ ህይወቴ ሊያልፍ እንደሚችል ነበር የማምነው፡፡ እስቲ ይመር ንጉሴ ከተባለው የገበሬ ሚሊሻ ጋር የተገናኛችሁበትን አስገራሚ ገጠመኝና ከዛ በኋላ የሆነውን ነገር ንገረኝ … ወሎ ግዳጅ ወጥተን ጉራወርቄ በምትባል ቦታ እየሄድን የሁካታ ድምፅ ሰማን፡፡ የገበሬ ታጣቂ ሚሊሽያዎች ከኋላችን እየተከተሉን ነበር፡፡ አጠገባችን ሲደርሱ ተኩስ ከፈቱ፡፡ አንዳንድ ጓዶች ጥይት ጨርሰዋል፡፡ አንዱ በመጥረቢያ ተመትቶ ወድቋል፤ ሌላው በጩቤ ተወግቷል፡፡

ሁኔታዎች ከቁጥጥራችን ውጪ ሆነዋል፡፡ በዚህ መሀል ያነጣጠርኩበትን ገበሬ ያለምንም ጥቅም እንደምገድለው እርግጠኛ ነበርኩ። በዚያ ሁኔታ ውስጥ ነፍስ ማጥፋት ዋጋ እንደሌለው ተሰማኝ፡፡ በመተኮስና ባለመተኮስ መሀል ሳመነታ ገበሬው ሰፈረብኝ፣ ተያያዝን ወደቅን፡፡ “ጥይት አልጨረስክም፤ ለምን ተኩሰህ አልገደልከኝም” ሲለኝ “እንኳን አልገደልኩህ” አልኩት፡፡ ምን መለሰልህ? በጣም ገርሞት “ምን ማለትህ ነው” አለኝ፡፡ “አንተ ምናልባት የምታስተዳድራቸው ብዙ ሰዎች ሊኖሩ ይችላሉ፣ እኔ የለኝም፡፡ ብትገድለኝ አንድ ብቻዬን ነኝ” ስለው በተኛሁበት በያዘው ገመድ እጆቼን ማሰሩን ተወው፡፡ የሞቱትን ጓዶቻችንን ከቀበርን በኋላ፣ ጠመንጃውን አውርዶ ወደ ሰማይ እየተኮሰ ወደእኔ መጣ፡፡ “ይህን ሰው አላስይዝም፤ መሄድ ወደሚፈልግበት እሸኘዋለሁ” ብሎ ወደቤቱ ወሰደኝ፡፡ ከዛስ? የመጀመሪያው ሌሊት እንቅልፍ የሚባል በአይኔ አልዞረም፡፡

ምክንያቱም ጠዋት ምን ሊፈጠር እንደሚችል እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ ይገድለኛል? ያስረኛል? አሳልፎ ይሰጠኛል የማውቀው ነገር የለም። ስለዚህ ጠዋት ማምለጥ የምችልበትን ሁኔታ እያሰላሰልኩ ነበር፡፡ ነገር ግን ወዲያው እሱ እኔን ይዞ ሲመጣ ፈጥኖ ደራሽ መጥቶ “ይመር ንጉሴ” እየተባለ ሲጠራ ሰምቻለሁ፡፡ እሱ ግን “ምንም አትሆንም አሳልፌ አልሰጥህም፤ ወደዚህ የሚመጡና የምንታኮስ ከሆነ ወደ ደኑ ማምለጥ ትችላለህ፡፡ እኔ በህይወት ካለሁ መጥቼ እፈልግሀለሁ” ሲለኝ እሱን ከማመን ውጪ ምንም ምርጫ እንደሌለኝ አወቅሁኝ፡፡ በዚህ ወቅት ምን ተሰማህ? እኔና ይመር በህይወት ተቀያይረናል፡፡ እሱን እኔ አልገደልኩትም፤ እሱም በተራው የእኔን ህይወት አትርፏል፡፡ ከዛ ወደ ሚስቱ ዘመዶች አገር ወስዶኝ ተመልሼ አሲምባ ገባሁ፡፡ አሲምባን ስናስብ የሚመጣብን የጦርነት ታሪክ ነው፡፡ መፅሀፍህ “የአሲምባ ፍቅር” ይላል፡፡

እስቲ ስለ አሲምባ እና ፍቅር ግንኙነት ንገረኝ? አሲምባ የኢህአሰ የመጀመሪያው ቤዝ ነው። አሲምባ ላይ ብዙ ነገሮች ተካሂደዋል፡፡ ሰዎች ተገድለውበታል፡፡ ግን እኔ የማየው ከዛ በላይ ነው። ምክንያቱም የጓዶች ፍቅርና መተሳሰብ … ከብዙ የተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች የተውጣጡ ግን የአንድ ቤተሰብ ያህል የሚተሳሰቡና የሚዋደዱ ነበሩ። ሠራዊቱ ከህዝቡ ጋር ህዝቡም ከሠራዊቱ ጋር ያለውን ፍቅር ያሳያል፡፡ ህዝቡ ባይፈቅድ ኖሮ እዛ መኖር አንችልም ነበር፡፡ ሌላው የአገሩ ፍቅር ነው። ጋራው፣ ሸንተረሩ፣ ወንዙ ይናፍቃል፡፡ ትግራይ፣ ወሎ፣ በጌምድር ሁሉም የሚናፈቅ ፍቅር አላቸው፡፡ የመጀመሪያ የሴት ፍቅረኛዬ እና ጓዴ የድላይ ፍቅር አለ፡፡ አንተ የፍቅር ጓደኝነት በጀመርክበት ጊዜ ፓርቲው ያንን ይፈቅድ ነበር? አይፈቅድም እንደዚህ ዓይነት ግንኙነት ተፈጽሞ ቢገኝ እርምጃው ምንድነው? በህገ ደንቡ መሠረት መባረር ነው፡፡ ግን ፍቅረኞች ነበርን እንጂ ወሲብ አልፈፀምንም፡፡ ስለ ኃይማኖት አቋምህ ስትጠየቅ የተሰማህ ስሜት ምን ነበር? ኃይማኖት ከሌለኝ ኮምኒስት አይደለህም የምባል ወይም የሚመልሱኝ መስሎኝ ስጋት ገብቶኝ ነበር ግን እውነቱን ነግሬያቸዋለሁ፡፡ እስቲ ስለ በረሀ ምግቦች ንገረኝ? ምን ነበር የምትበሉት? ቁርስ የሚባል ነገር የለም፡፡ ለምሳ ለእራትም የሚባል ራሸን የለም፡፡ ያገኘነውን ነው የምንበላው።

ዳቦም ይሁን ቂጣ ወይም እንጀራ ህዝብ የሰጠሽን ትበያለሽ፤ ህዝብ ካልሰጠሽ ደግሞ የተገኘውን ነው የምትበይው፡፡ በለስም ቢሆን … ካልተገኘ ደግሞ ውሀ ጠጥተሽ ታድሪያለሽ፡፡ ውሀም የማይገኝበት ጊዜ አለ። ያንንም መቻል ነው፡፡ አንድ ጊዜ ወደ አርባያ በለሳ ስንሄድ ውሀ በጣም ጠማን፡፡ አንድ ወንዝ አገኘን፤ ውሀው በጣም ቆሻሻ ነበር፤ ግን ትንሽ መጐንጨት ነበረብን፡፡ በነጠላ ትሎቹን እያጠለልን ትንሽ ተንሽ ቀምሰን ሄደናል፡፡ ሽንት የሚጠጡም ነበሩ፡፡ በመፅሃፍህ ውስጥ ፀጋዬ ገብረመድህን (ደብተራው) “ቅማል መቅመል ይወዳል” ብለሀል፡፡ እስቲ ስለሱ ንገረኝ…. በየጊዜው ገላ መታጠብ እና ልብስ ማጠብ አይቻልም፡፡ አኗኗራችን የትግል ነው፤ ከቦታ ቦታ ነው የምንሄደው፡፡ ጊዜ ስናገኝ እንቀማመል ነበር። በተለይ ደብተራው መቅመል ይወዳል፡፡ ልጆች ስለነበርን በቅማል ስንሰቃይ በጣም ይጨንቀው ነበር፡፡ ቅማላችንን አራግፎ ሲሰደን በጣም ነበር የሚደሰተው። እኛ ደግሞ እሱን እንቀምለው ነበር። አንድ ጊዜ በኤርትራ በኩል የመጣ መድሃኒት ነበር፤ ዱቄት ነው፡፡ በውሀ በጥብጠን ልብሳችንን እንነክረዋለን፤ ከዛ እናሰጣዋለን፤ ቅማሎች ይራገፋሉ። አንዳንዴ ለፀጉራችንም እንጠቀምበት ነበር፡፡

ግን በጣም አደገኛ ነው፤ አንዳንዶች ራሳቸውን ይስቱ ነበር፡፡ ምክንያቱም መጠኑን አናውቀውም ነበር፡፡ ሰራዊቱ የሴቶች አያያዝ ላይ እንዴት ነበር? በእኩልነት ላይ የተመሰረተ ነበር፡፡ የሴቶች ጭቆና ድርብርብ መሆኑን ያምን ነበር፡፡ የመደብ እና የፆታ ችግር እንዳለ ያምናል፡፡ ከመጀመሪያ ፍቅረኛህ ከድላይ ጋር እቃ እንድታመጣ አብራችሁ ሄዳችሁ ነበር፡፡ እስቲ ስለሱ ደግሞ … ጓዶች ሱሪህን አውልቀህ ስጣት አሉኝ፡፡ ያኔ የሚቀልዱ ነበር የመሰለኝ፡፡ “ቶሎ በል ጊዜ ስለሌለ ቶሎ አውልቀህ ስጣት” ስባል ነው ያመንኩት፡፡ ትንሽ ዞር ብዬ ነጠላዬን አገለደምኩና ሱሪዬን አውልቄ ሰጠኋት፡፡ ያኔ ሱሪዋ ቆሽሾ ይሆናል ብዬ ነበር ያሰብኩት፡፡ ወደ ማታ ደግሞ “ይዘሀት ወደ ነበለት ትገባለህ፤ የምትፈልገውን እቃ ይዛ ትመለሳለች” ሲሉኝ ለድርጅቱ ስራ አብሪያት እንደምሄድ ነበር የጠረጠርኩት፡፡ እሷን ስጠይቃት ግን ሞዴስ ላመጣ ነው አለችኝ፡፡ ምን እንደሆነ ስጠይቃት ብትነግረኝም አልገባኝም፡፡

በመንገድ ላይ ስኮረኩራት ስኮረኩራት ነው ምን እንደሆነ የነገረችኝ፡፡ ፍቅረኛህ ድላይ በተደጋጋሚ ውሳኔህን እንድታሳውቃት ታስጠነቅቅህ ነበር፡፡ ሰራዊቱን ትተህ ወደ ሱዳን ለመውጣት ስታስብ ለመንገር ባትችል እንኳን ለምን መልዕክት አልላክባትም? ሱዳን ሆኜ ተስፋይ ኢዲዩ ደብዳቤ ላድርስልህ ቢለኝም የምልከው በነሱ ከሆነ ያነቡታል፤ ስለዚህ የግል ሚስጥር የሚባል ነገር የለም፤ ለዚህ ነው ደብዳቤውን ያልላኩት፡፡ አሲምባ የሠራዊቱ ፍርድ ቤት ነበር፡፡ አንተም ተከሰህ ለፍርድ ቀርበህ እንደነበር በመፅሃፉ ገልፀሃል። የፍርድ ቤቱ ውሳኔ ፍትሀዊ ነው የሚል አዝማሚያ በፅሁፍህ ላይ ይንፀባረቃል፡፡ እውነት ፍትሀዊ ነበር ትላለህ? ለኔ በጣም ፍትሃዊ ነው፡፡ እኔ ከስሼም ተከስሼም ስለማላውቅ አማካሪ ያስፈልገዋል ተባልኩ፡፡ በዚህ ምክንያት ነው ሰላማዊት ጠበቃዬ የሆነችው፡፡ መከሰሴን ተገቢ ነው ባልልም ውሳኔው ግን ጥሩ ነበር። ፀሎተ ህዝቅያስ በፍርድ ቤት ውሳኔ ነው የተገደለው? መፅሐፍህ ላይ “ፀሎተን ደጀኔ ገደለው፣ ደጀኔን ዳዊት ገደለው፣ ደብተራው ወደ ላይ እየተኮሰ መጣ” ብለህ ነው የገለፅከው፡፡ ምንድን ነበር የሆነው? ያየሁትን ብቻ ነው የምናገረው፡፡ ፀሎተ ገና ሳይሞት ነው የደረስኩት፤ ደጀኔ ሞቶ ነበር፡፡ ይሄ የፍርድ ቤት ውሳኔ አይደለም፡፡

በዛን ጊዜ ማንኛውም የአመራር አባል ለደህንነቱ ሲባል የሚሄድበትን ይነግረናል፡፡ ጠዋት ደብተራው መጣና “ደጀኔና ፀሎተ ወደ ወንዝ ለመታጠብ ሄደዋል፤ ጥበቃ እንዲደረግላቸው” ሲለኝ የተባለው ተደረገ፡፡ በተለይ ፀሎተ የአመራር አባል ስለሆነ ጥበቃው ጠንከር ይላል፡፡ ከዛ ደብተራው ትንሽ ቆይቶ ተመለሰና “እኔና ዳዊት ይህ ቦታ ስለጠበበን ፊትለፊት ካለው ጋራ ቤት እናያለን፤ ስለዚህ ጥበቃ ይደረግ” አለ፤ ያንን አደረግን። ወድያው የሁለት አውቶማቲክ መሳሪያ ተኩስ ሰማን፡፡ መጀመሪያ እኔ ወደ ወንዙ ስደርስ ደብተራው ወጥቶ ሽጉጥ ወደሰማይ ይተኩሳል፡፡ እርዳታ ፈልጐ ይመስለኛል፡፡ እኔ ከደብተራው በስተቀር ሁሉም የተገደሉ ነበር የመሰለኝ ፡፡ ደብተራውን ምን ተፈጠረ ብዬ ስጠይቀው “ደጀኔ ፀሎተን ገደለው፤ እኛ ደግሞ ደጀኔን ገደልነው” አለኝ፡፡ ደጀኔ ሞቷል፤ ፀሎተ አልሞተም ነበር፡፡ ዳዊት ጭንቅላቱን ይዞ ሲያለቅስ ነበር፡፡ ፀሎተን ወደ ጥላ ወሰድነው፤ ከዛም ብዙ ሳይቆይ ሞተ፡፡ የዕበዮ፤ የኢህአሰ ሰራዊት ውቅሮ ላይ ባደረገው ውጊያ ነው የተገደለው፡፡ ከሱ ጋር ያለውን ተያያዥ ታሪክ ንገረኝ… የዕበዮ የውቅሮ ልጅ ነው፡፡

ስለዚህ ውቅሮ በሚደረገው ውጊያ እንዳይገባ ተወስኖ አይሆንም ብሎ ተከራክሮ ነበር ወደ ውጊያው የገባው፡፡ በውጊያው ከተሰዋ በኋላ በህይወት የተረፍነው እሱን ስንቀብር ሌሎቹ ጓዶች “አንገቱ ይቆረጥና ይቀበር፤ ምክንያቱም ደርግ የእሱ አስከሬን መሆኑን ከለየ መንገድ ላይ ያወጣዋል” ሲሉኝ “አይኔ እያየ አንገቱን አይቆረጥም” ብዬ ሳይቆረጥ ተቀበረ፡፡ እኔ ሠራዊቱን ትቼ ሱዳን ከገባሁ በኋላ ደርግ በማግስቱ አስከሬኑን ስለለየው ውቅሮ ከተማ መንገድ ላይ አስከሬኑን በመዘርጋቱ፣ እናቱም ያንን አይታ የአዕምሮ ህመምተኛ እንደሆነች ሰማሁ፡፡ ዛሬ ላይ ሳስበው ተቆርጦ ቢሆን ኖሮ እናቱ ትድን ነበር እላለሁ፡፡ ያን ጊዜ ግን የምወደውን ሰው አንገት ቆርጦ ለመውሰድ ህሊናዬ አልፈቀደልኝም፡፡ በበጌ ምድር፣ በባሕር ዳር በየከተማው የነበረውን የኢህአፓ እንቅስቃሴ በቅርበት ታውቁ ነበር? በረሃ በወጡት የፓርቲው ተወካዮች በኩል የምንሰማው መረጃ እንጂ ሌላ እውቀት የለም፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጋር ስትገናኙ እንዴት ነበር? የተገናኘው በ1968 ዓ.ም ነው፡፡ ከራዛ ጦርነት በኋላ የተገኘውን መሳሪያ ለመውሰድ ኤርትራ ውስጥ መነኩሲቶ የምትባል ቦታ ሄድን፡፡ አቶ መለስን አይተነው፤ ስለሱ ሰምተንም አናውቅም ነበር፡፡ እሱ የሆነ መልዕክት ይዞ የመጣ ይመስለኛል፡፡ ለሊቱን በመደዳ ተኝተን አሳለፍን፡፡ በቆይታችን ስለነበረን ልዩነቶች ተነጋግረናል፡፡ የሀሳብ ልዩነት ላይ መስማማት ስላልቻልን “ብሬይን ወሽድ ስለሆናችሁ እናንተን ማሳመን አይቻልም” አለን፡፡

ቃሉን ለመጀመሪያ ጊዜ ስለሰማሁት ፃፍኩትና ወደ ቦታችን ስንመለስ፣ መለስ ያለንን ነገርኳቸውና ምን ማለት እንደሆነ አስረዱኝ፡፡ ከህወሓት እና ከኢህአፓ ህዝቡ የቱን እንደሚመርጥ ሪፈረንደም አድርጋችሁ ነበር፡፡ እስቲ ምንድነው የሆነው? በወቅቱ የአንድ መንደር ህዝብ አስተዳዳሪው የቱ እንደሚሆን ይመርጥ ነበር፡፡ ከሁለቱ ድርጅቶች በየቱ መተዳደር ትፈልጋላችሁ ይባልና ውሳኔው ተግባራዊ ይደረጋል፡፡ ወያኔ ካለ እኛ እንለቃለን፤ ኢህአፓ ካሉ እነሱ ይለቃሉ፡፡ ህዝቡ ተወካዩን እንዲመርጥ እናደርጋለን፡፡ ታድያ ሁኔታዎች ለምን ተበላሹ? በሁለቱ ድርጅቶች መካከል የተፈጠረው ነገር በኔ ደረጃ የሚገለፅ አይደለም፤ እኔ ተራ ታጋይ ነበርኩ፡፡ ከበለሳው ቡድን በኋላ ኢህዴን/ብአዴን ከሆኑት ማንን ታውቃለህ? ያኔ አብረውን ከነበሩ ሰዎች እንደሰማሁት አርባፀጓር ላይ አቶ በረከት ስምኦን አጠገቤ እንደነበሩ ነግረውኛል፡፡ ግን አንተዋወቅም፡፡ አቶ በረከትም ከቤጌምድር ጋንታ መጥቶ ነበር፡፡ ከደብተራው ጋር ከነበራችሁ ፍቅር የተነሳ ስትለያዩ ማስታወሻ ስጠኝ ብለኸው ለማስታወሻነት መሳሪያችሁን ተለዋውጣችኋል፡፡ የደብተራው ማስታወሻ መሳሪያ የት ገባች? ከደብተራው ጋር ለየት ያለ ፍቅር ነበረን፡፡ በኔ ላይ ጥሩ እምነት ነበረው፡፡

ስለ አማኑኤል ጥሩ እንጂ መጥፎ ነገር አትንገሩኝ ይል እንደነበር አሁን በህይወት ያሉ አመራሮች ይነግሩኛል፡፡ ስንለያይ ብረት ተለዋወጥን፡፡ ወደ ሱዳን ስሄድ በኤርትራ በኩል ስለሆነ ለኤርትራ ድርጅት አስረከብኳት፡፡ ሳስረክባት እውነቴን ነው እሱንም ያስረከብኩት ነው የመሰለኝ፡፡ ኢህአፓ እና ኢህአሠ የተቆራኙ ወይም የሚናበቡ አይመስሉም፡፡ ወታደራዊ ግዳጆቹ የተበጣጠሱ ናቸው፡፡ ስለዚህ ጉዳይ ምን ትላለህ? እኔ በማውቀው ደረጃ ያንቺን ጥያቄ መመለስ ይከብደኛል፡፡ እኛ ዛሬ እዚህ ትሄዳላችሁ ስንባል እንሄዳለን፤ ውጊያ ታካሂዳላችሁ ሲባል እንፈፅማለን። ፓርቲው ሠራዊቱን ያዛል፤ ሠራዊቱ ይፈፅማል፤ በየክፍሉ የፓርቲ ወኪሎች አሉ፡፡ በሠራዊቱ ውስጥ የነበረው የተማሩና ያልተማሩ አባላትን ልዩነት ንገረኝ? እኛ የታዘዝነውን እንፈፅማለን፡፡

አንዳንድ የተማሩት እኛን “የአመራር ቡችሎች” እና “ክሊኮች” ይሉናል፡፡ እኛ ስለፓርቲው ጠልቀን አናውቅም፤ እነሱ ስለፓርቲው ድክመትና መፈረካከስ ያውቃሉ፤ በዚህ መሀል መናበብ የለም፡፡ ያኔ እነሱ ተስፋ መቁረጥ ውስጥ ናቸው፤ እኛ ደግሞ ለምን የታዘዙትን አይፈፅሙም እንላለን፡፡ እኛ ስላልተማርን ንቀውን ሳይሆን ውስጣችን የተለያየ ነገር ስለነበር ነው፤ በአቅምም እንድናድግ ጥረት ይደረግ ነበር፡፡ ለምሳሌ ጓድ ሽፈራው “The military Tactic of the Vietnamese Revolution” የሚል መፅሐፍ አስነብቦናል፡፡ ኢህአፓ/ኢህአሠ ለምን ፈረሰ? ብዙ ብቃት ያላቸው ለመስዋእትነት ዝግጁ የሆነ ሠራዊት ነበረው፡፡ ድርጅቱ ለምን ፈረሰ በኔ አቅም አይመለስም፡፡ ልዩነቶች እንደነበሩ እንሰማ ነበር፡፡ እኛ በይፋ የተነገረን በ1970 ቢሆንም ችግሩ ከ1968 ጀምሮ የነበረ ነው፡፡ ብርሃነመስቀል ከድርጅቱ ወጥቷል ይባል ነበር፡፡ ያንን የፓርቲ አባሎች ያውቃሉ፡፡

እኛ ግን በሀሜት ደረጃ እንጂ በይፋ አልተነገረንም፡፡ ድርጅቱ እየተከፋፈለ አንጃ ተብለው ታስረው የተገደሉ አሉ። በጣም የምንወዳቸውና የምናከብራቸው መዝሙር፣ በሽር፣ ታሪኩ የተባሉ እና ሌሎችም ተገደሉ፡፡ ብዙ ጓዶች በዚህ ላይ ቅሬታ ነበራቸው፡፡ ከኤርትራና ከወያኔ ጋር የነበረን ግንኙነት መሻከር ተደማምረው ይመስለኛል ለመፍረስ የበቃው፡፡ “የአሲምባ ፍቅር” … ይቅርታ ጠይቀን አስቆምናቸውና “እዚህ አካባቢ የሚኖር ሰው ብጠይቃችሁ ታውቃላችሁ?” አልናቸው፡፡ አንደኛው ሰውዬ “መሃመድ እባላለሁ፤ እዚሁ አካባቢ ነው ሀገሬ ፣እዚህ ወጣ ብሎ ይሄንን ጋራ ተሻግራችሁ ነው፡፡ ማንን ፈልጋችሁ ነው? ስሙን ታውቃላችሁ?” አሉን፡፡ “ይመር ንጉሴ የሚባል ሰው” አልኳቸው “ይመር ንጉሴ? ወይ ወንድሜን!” ብለው ጭንቅላታቸውን ይዘው ማልቀስ ጀመሩ፡፡ ልቤ ስንጥቅ አለ፡፡

የሆነውን መጠየቅ አስፈላጊ አልነበረም፤ አውቄዋለሁ፡፡ እውነቱን መቀበል ግን አልፈለግኩም፡፡ ለመናገር መዘጋጀቴን ሳላውቀው ከአፌ ምነው? የሚል ቃል ሲወጣ በጆሮዎቼ ተሰማኝ። “ይመር ንጉሴ እኮ ሞቷል!” አሉ፡፡ “እንዴት ሆኖ?” “በቃ እንዴት እንደሆነ አላወቅንም፤” የወያኔ ታጋዳዮችና በርካታ መሪዎች አውቅ ነበር፤ ብዙዎቹን በአካል ሌሎቹን ደግሞ በዝናና በወሬ ደረጃ ስማቸውን ሰምቻለሁ፣መለስን ግን ያየሁትም ሆነ ስሙን የሰማሁት ለመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡ መለስ የለበሰው የዘማቾች ካኪ ዩኒፎርም ሲሆን አንድ ቦርሳ ሙሉ መፅሃፍ ይዟል፡፡ ሰውነቱ ጠንካራ፣ ከመካከለኛ ሰው ትንሽ አጠር ያለ ቁመት ያለው፣ ክብ ፊትና ንቁ ዓይኖች ያለው ሰው ነው፡፡ መለስ ጨዋታና ቀልድ የሚያውቅ፣ ሃለኛ ተከራካሪ፣ በውይይት ጊዜ ፊቱን ቅጭም የሚያደርግና የሚመሰጥ እንደሆነ በዛን ቀን ቆይታችን አስተውያለሁ፡፡…የምንከራከረው እኔና አስመሮም ከአንድ ወገን፣ መለስ ደግሞ ብቻውን ስለነበር ውይታችን አድካሚ ሳይሆንበት አልቀረም። እርሱ ግን እንዲህ በቀላሉ ደክሞት የሚተው ሰው አልነበረምና እኛን ለማሳመን ብዙ ደከመ።

በመጨረሻም ከሀሳቡ መደጋገም በቀር አዲስ ነገር እያለቀብን ሲመጣ፣ “ብሬይን ወሸድ(brain washed) ስለሆናችሁ፣ እናንተን ማሳመን አይቻልም” አለ፡፡ ጸጋዬ ደብተራውን በጣም ስለምወደው “አሁን ጎንደር ከሄድኩ ላንገናኝ እንችላለንና አንተን ማስታወሻ የሚሆነኝ አንድ ነገር ስጠኝ” አልኩት፡፡ እሱም ሳቅ አለና ትንሽ ካሰበ በኋላ “እንካ ጠመንጃዬን ልቀይርህና ማስታወሻ ይሆንልሃል” ብሎ ሰጠኝ፡፡ የእርሱን ወስጄ የእኔን ሰጠሁትና ተቃቅፈን ተሳሳምን፡፡ ሁለቱም የክላሽን ኮቭ ጠመንጃዎች ነበሩ፤ምንም ልዩነት የላቸውም፡፡ ቢያንስ አንዳንዴ ጠመንጃዬን ሳይ ግን እሱን ያስታውሰኛል ብዬ በጣም ደስ አለኝ፡፡

… በጣም ግራ ገባኝ “ከሴት አስተማሪዎች የምትቀበይው ወይም ደግሞ የምታመጪው ምን እቃ ነው?” ብዬ እንደገና ስጠይቃት ሳቀች፡፡ “አንተ አታውቀውም፣ የሴት እቃ ነው፣ አማኑኤል” አለችና እንደገና አከታትላ “አማኑኤል እኔ እኮ አሞኛል፡፡ ቀኑን በሙሉ ያንተን ልብስ ለብሼ እንደዋልኩ ታውቅ የለ፡፡ የእኔ ሱሪ ተበላሽቶ ስለነበር ለማጠብ ነበር የአንተን ለብሼ ወደ ወንዝ የወረድኩት” ብትለኝም ችግሯን በትክክል አልተረዳሁትም፡፡ “ታዲያ ምንድን ነው የምናመጣው?” “እቃው ሞዴስ ይባላል” አለችኝ፡፡ “ሞዴስ ምንድነው?” “ሞዴስ ሴቶች ብቻ የሚጠቀሙበት የሴት እቃ ነው፡፡ ወንዶች ብዙም አታውቁትም” አለችና ለአፍታ ያህል ስታስብ ቆየች፡፡ “ወንዶች እኮ እንደዚህ ዓይነት ነገር ስለማታውቁ ታድላችኋል” በድምጿ ውስጥ ሐዘን ተሰማኝ፤ ችግሩ ወይም ሕመሟ ቀላል እንደሆነ ተረዳሁ፡፡ ግን ምን እንዳመማት በትክክል አልተረዳሁም፡፡ “ሞዴስ” የሚለውን ቃል ስሰማ ለመጀመሪያ ጊዜ ነበር፡፡ አሁን ግን የሴት እቃ ከመሆኑ ሌላ ያሽልሻል ማለት ነው?” አልኳት፡፡ (በካህሳይ አብርሃ ብስራት ተፅፎ ባለፈው ቅዳሜ ከተመረቀው “የአሲምባ ፍቅር” መፅሃፍ የተቀነጨበ)

(1. የእንግሊዝኛ ቋንቋ 2. ኮምፒዩተር 3. ኢንተርኔት … ናቸው ስጦታዎቹ። መፃህፍት እንደልብ ለማንበብና ስኬትን ለመቀዳጀት) እውቀት የዶ/ር ቤን ካርሰን ታሪክ ምስክር ነው። በህፃንነቱ “ደደብ ነኝ” ይል ነበር - ትምህርት ጨርሶ የማይገባው። ከድህነት ጋር በምትታገል እናቱ ግፊት መፅሃፍ ማንበብ ጀመረ። በአንጎል ቀዶ ህክምና በቀዳሚነት የሚጠቀስ ሃኪም ለመሆን በቃ። በ2016 ለአሜሪካ ፕሬዚዳንትነት ይወዳደራል ተብሎ ይጠበቃል። “ተአምር” መስራት የሚቻልበት ዘመን ላይ ደርሰናል። ከሃያ አመታት በፊት በፍፁም የማይሞከሩ ነገሮች፣ ዛሬ በቀላሉ በመዳፋችን ውስጥ ልናስገባቸው እንችላለን። እስቲ አስቡት። በዚህ ሳምንት ብቻ፣ ከሁለት ሺ በላይ በእንግሊዝኛ የተፃፉ አዳዲስ የልብወለድ ድርሰቶች በኢንተርኔት አግኝቼ ኮምፒዩተሬ ውስጥ አስቀምጫለሁ - በ2012 እና በ2013 የታተሙ ተወዳጅ (bestseller) መፃህፍት ናቸው። በመቶ እና በሺ የሚቆጠሩ አዳዲስ መፃህፍት ማግኘት ይቅርና፣ ሦስት አራት አዳዲስ መፃህፍት ማግኘት ምን ያህል ብርቅ እንደነበር አታስታውሱም? ለነገሩ፣ ለብዙ ሰዎች ዛሬም ድረስ ብርቅ ነው።

የልብወለድ ድርሰቶችን ለጊዜው እንርሳቸው። ከአንደኛ ክፍል ጀምሮ እስከ ሃይስኩል፣ የሂሳብም ሆነ የተፈጥሮ ሳይንስ መማሪያ መፃህፍት፣ ከዩኒቨርስቲ የ‘ፍሬሽማን’ ትምህርት እስከ ማስተርስ ዲግሪ ድረስ፣ ከኤሌክትሪክ ምህንድስና እስከ ሕክምና፣ ከቢዝነስ ማኔጅመንት እስከ አለማቀፍ ዲፕሎማሲ… በመላው አለም እጅግ የሚፈለግ ውድ መፅሃፍ በየአይነቱ “በገፍ” ቢቀርብልን ብላችሁ አስቡ። ባለፉት ምዕተ አመታት የተፃፉ ዘመን የማይሽራቸው የሳይንስ መፃህፍትን ከፈለጋችሁ… ሞልቷል። አዳዲስ የዘመናችን ምርጥ የሳይንስ፣ የቴክኖሎጂና የመማሪያ መፃህፍትም እንደልብ ነው። እድሜ ለኢንተርኔት! በሺ ከሚቆጠሩት የትምህርት መፃህፍት መካከል፣ ለሙከራ ያህል ሁለት መቶ የሚሆኑትን ሰሞኑን ኮምፒዩተሬ ላይ ጭኛቸዋለሁ። አንዳንዶቹን ገለጥ ገለጥ አድርጌ አይቻቸዋለሁ። ባለፈው አመት ወይም ባለፉት ስድስት ወራት የታተሙ አዳዲስ የትምህርት መፃህፍትን እንዲህ እንደልብ ማግኘት “ተአምር” አይደለም? በቢዝነስ ጉዳዮች ዙሪያ እንደ ፎርብስ እና ዘ ኢኮኖሚስት የመሳሰሉ መፅሄቶች ሞልተዋል። የቴክኖሎጂና የሳይንስ ዘገባዎችን ወይም የጥናት ውጤቶችን ለመከታተልም፣ እንደ ፖፑላር ሜካኒክስ፣ ኔቸር፣ ዋየርድ፣ ናሽናል ጂኦግራፊ የመሳሰሉ መፅሄቶች አሉ። አዳዲስ የሰሞኑ እትሞቻቸውን በኢንተርኔት ወደ ኮምፒዩተሬ ገልብጬ አየት አየት እያደረግኳቸው ነው።

ስልጡን የፖለቲካ ባህል በቀጥታ ለማየት የሚፈልግ ካለም ምንም አይቸገርም። የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ወይም ቃል አቀባያቸው ለጋዜጠኞች የሚሰጡትን መግለጫ በቀጥታ መከታተል ይችላል። በአሜሪካ፣ የኮንግረስና የሴኔት ምክር ቤት ውስጥ የሚካሄዱ ክርክሮችን፣ በዚያው ሴኮንድ በቀጥታ ሲሰራጩ መመልከትስ? ከአራቱ የሲ-ስፓን ቻናሎች መካከል እያማረጡ መመልከት ነው። የምክር ቤት አባላት፣ የአክብሮት ስነምግባርን ሳይጥሱ፣ የመንግስት ሚኒስትሮችንና ከፍተኛ ባለስልጣናትን ወጥረው ሲያፋጥጡ ይታያሉ። የሳይንስና የቴክኖሎጂ ሰዎች እድሜ ይስጣቸውና፣ እንደየዝንባሌያችን እያማረጥን ያሻንን ያህል ማንበብና መከታተል የምንችልበት ዘመን ላይ ደርሰናል። ሙሉ ትኩረታችንን የሚጠይቅ ትምህርታዊ መፅሃፍ ማንበብ፣… ምን ያህል እንደሚመስጥና እንደሚያስደስት ታውቁት ይሆናል። ግን በየመሃሉ አረፍ ብሎ መንፈስን ማደስ ያስፈልግ የለ? ለምሳሌ፣ ቀለል ያለ፣ ልብ አንጠልጣይ የልብወለድ ድርሰት ማንበብ፣ ጥሩ የመዝናኛ ዘዴ ነው። ምን ጠፍቶ! አምናና ዘንድሮ በአሜሪካ የታተሙ አዳዲስ የልብወለድ መፃህፍት ሰሞኑን “በገፍ” አግኝቻለሁ።

ግን፣ በ20ኛው ክፍለዘመን፣ በልብ አንጠልጣይ የልብወለድ ድርሰት ገንነው ከሚጠቀሱ ደራሲዎች መካከል አንዱ የሆነው ሚኪ ስፕሌን ትዝ አለኝ። የስፕሌን ድርሰት ባገኝ… ብዬ በኢንተርኔት ፈለግሁ። 13 ድርሰቶቹን አገኘሁና፣ በ5 ደቂቃ ውስጥ ሁሉንም ወደ ኮምፒዩተሬ ገለበጥኳቸው። አንዱን መርጬ አነበብኩታ። በእርግጥም ዘና አደረገኝ። በዚያው አጋጣሚ ግን፣ በቪዲዮ፣ በድምፅ እና በፅሁፍ የተዘጋጁ የእንግሊዝኛ ቋንቋ መማሪያዎችን አይቻለሁ - ብዛታቸውና አይነታቸው እንዲህ ቀላል አይደለም። ከነባሮቹና ከአዳዲሶቹ የቋንቋ መማሪያዎች መካከል እየመረጥኩ ወደ ኮምፒዩተሬ መገልበጥ ነው የሚቀረኝ። በመላው አለም በጣም የሚፈለጉ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ማስተማሪያ መፃህፍትን ብቻ ሳይሆን፣ በድምፅና በቪዲዮ የተዘጋጁ አጋዥ መማሪያዎችን እንደ ልብ ማግኘት! “ምናለ፣ ይሄ ሁሉ እድል፣ ከአስር አመት ከሃያ አመት በፊትም በኖረ” ብዬ መቆጨቴ አልቀረም። ግን፣ አሁን መገኘቱም “ተአምር” ነው። ይልቅ፣ ይህን እድል ለመጠቀም መትጋት ነው የሚሻለው። ቀለል ባለ ልብወለድ መፅሃፍ ዘና ካልኩ በኋላ ወዲያውኑ ለሥራዬ በቀጥታ የሚጠቅመኝን መፅሃፍ ላነብ አልኩና… እንደአጋጣሚ ሃሳቤን ቀየርኩ። አልነገርኳችሁም እንጂ፤… በዚህ ሳምንት፣ ከልብወለድ ድርሰቶች በተጨማሪ፣ አንድ ሺ የሚሆኑ አዳዲስ “የሕይወት ታሪክ” መፃህፍትንም በኢንተርኔት ወደ ኮምፒዩተሬ ገልብጫለሁ።

ታዋቂው ሥራ ፈጣሪና ቢሊዮነር ሪቻርድ ብሮንሰን በ2011 ያሳተመው የግል የህይወት ታሪክ፣ የአሜሪካዊቷ ፖለቲከኛ ሳራ ፓይሊን፣ የበርማዊቷ የፖለቲካ መሪ አንሷን ሱኪ የህይወት ታሪኮች … በኢራቅ ጦርነት ብዙ አሸባሪዎችን በመግደል ሪከርድ የሰበረው ክሪስ ካይል ያሳተመው መፅሃፍ ሳይቀር… ብቻ ምን አለፋችሁ? በያዝነው የሰኔ ወር “ቤስትሴለር” ሰንጠረዥ ውስጥ ቁንጮውን ቦታ የተቆጣጠሩ መፃህፍት ሁሉ ቁጭ ብለው ለመነበብ ይጠብቃሉ። አንድ በአንድ አየኋቸው… የቀድሞው የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቶኒ ብሌር ያዘጋጁት መፅሐፍ፣ የጆርጅ ቡሽ መፅሃፍ… እነዚህ ቆየት ያሉ ናቸው። ሌላ ጊዜ አነባቸዋለሁ። አዳዲሶቹንም አየሁ - ታዋቂው የአንጎል ቀዶ ህክምና ባለሙያ ዶ/ር ቤን ካርሰን ያሳተሙት መፅሃፍ ላይ ደረስኩ። በቅርቡ ከፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ጋር በትልቅ አመታዊ ጉባኤ ላይ ንግግር እንዲያቀርቡ ተጋብዘው የነበሩት ጥቁሩ አሜሪካዊ ቤን ካርሰን፣ ኦባማን በመተቸት ባቀረቡት የግማሽ ሰዓት ንግግር “አጃኢብ” ሲባልላቸው እንደሰነበቱ አውቃለሁ። ከኦባማ ጋር የሚያለያያቸውን ሃሳብ ዶ/ር ካርሰን ሲገልፁ፣ ድሆችን እንደግፋቸው በሚል ሰበብ የአገሪቱ ዜጎች የመንግስት ጥገኛ እንዲሆኑ እየተደረገ ነው በማለት ተናግረዋል።

አሜሪካ የተመሰረተችው ግን፣ ዜጎች ምንም ድሃ ቢሆኑ እንደየጥረታቸው ራሳቸውን ችለው የሚበለፅጉባት የነፃነት አገር እንድትሆን ነው ይላሉ - ዶ/ር ካርሰን። ይህን ሃሳባቸው ለማስረዳትም ነው አዲስ መፅሐፍ ያሳተሙት። ሃብታሞችንና ድሆችን የሚለያቸው ምንድነው? ዶ/ር ካርሰን ስለ ድህነትም ሆነ ስለ ሃብታምነት ቢናገሩ ያምርባቸዋል። ያለፉበት ሕይወት ነው። ከችጋር ወደ ብልፅግና እንዴት እንደተሸጋገሩ መነሻና መድረሻውን ያውቁታል። መፅሃፋቸውን አግኝቼ ላነበው ከተዘጋጀሁ በኋላ ነው፣ ካሁን በፊት ያሳተሟቸውን የመፃህፍት ዝርዝር ያየሁት። የመጀመሪያው መፅሃፍ “ጊፍትድ ሃንድስ” በሚል ርዕስ የታተመ ነው። ርዕሱን አስታወስኩት። መፅሃፉን ባላነበውም፣ ፊልሙን አይቼዋለሁ። ለካ፣ ኩባ ጉዲን የተወነበት ያ ምርጥ ፊልም፣ በዶ/ር ቤን ካርሰን የህይወት ታሪክ ላይ የተመሰረተ ነው። ከልጅነት እስከ እውቀት፣ የሕይወት ታሪካቸውን ባሰፈሩበት መፅሃፍ ውስጥም፣ ወደ ኋላ መለስ ብለው በድህነትና በ“ደደብነት” ያሳለፉትን የልጅነት ጊዜ ይተርካሉ። ስኬታማ ሰው ለምልክት ያህል በማይታይበት የድሆች ሰፈር ውስጥ ነው፣ ሕፃኑ ቤን ካርሰን ያለ አባት ያደገው። “እንደ እገሌ ስኬታማ እሆናለሁ” የሚያስብልና በአርአያነት የሚጠቀስ ሰው አልነበረውም - በቤተሰቡም ሆነ በሰፈሩ ውስጥ። ያልተማረችና ማንበብ የማትችል የካርሰን እናት፣ ሁለት ልጆቿን ለማሳደግ ያላየችው መከራ የለም። የሃብታሞችን ሰፈር ስታካልል ነው የምትውለው።

የሃብታሞችን ቤት በማፅዳት በምታገኛት አነስተኛ ገቢ ካርሰንና ወንድሙ ፆም እንዳያድሩ ብቻ ሳይሆን፣ ከትምህርት እንዳይርቁም ከንጋት እስከ ምሽት ትሰራለች። የእለት ተእለት ልፋቷ ትዕግስትን የሚፈታተን ቢሆንም፣ እጅግ የሚከነክናትና የሚያንገበግባት ግን፣ የድካሟን ያህል ውጤት አለማየቷ ነው። ልጆቿ፣ በየእለቱ ወደ ትምህርት ቤት መሄዳቸው ባይቀርም፣ ጠብ የሚል እውቀት አልቀሰሙም። ካርሰን እንደ ወንድሙ ክፍል ውስጥ “ሲማር” ይውላል፤ አስተማሪ አንዳች ጥያቄ ሲሰነዝር፣ ሌሎቹ ተማሪዎች መልስ ለመስጠት ይሻማሉ - እውቀታቸውን ለማሳየት። ግን፣ ካርሰን ሲጠየቅ ማየትም ያጓጓቸዋል - መመለስ ሲያቅተው ወይም ከጥያቄው ጋር የማይገናኝ ነገር ሲዘባርቅ መሳቅ ለምደዋል። ፈተና ሲመጣ፣ ካርሰን ከሌሎቹ ተማሪዎች ጋር አብሮ ይፈተናል። ተማሪዎች የፈተና ውጤታቸውን በኩራት ይናገራሉ፤ 25 ከ25 የሚደፍን ይኖራል፣ አነሰ ቢባል 20 የሚያመጣም ይኖራል። ካርሰን ድምፁን ዝቅ አድርጎ የራሱን ውጤት ይናገራል። አስተማሪዋ በደንብ አልሰማቸውም… “Nine?” በጣም ጥሩ ነው፤ 9 ከ 25? በጣም ተሻሽለሃልሳ! አለችው... ደስ ብሏታል። ካርሰን አስተማሪዋን ሊያርማት ይሞክራል - “Nine” ሳይሆን፣ “None” በማለት። ከፈተናው ጥያቄዎች ውስጥ አንዱንም በትክክል አልመለሰም፤ ዜሮ ነው ያመጣው። እንደተለመደው ተማሪዎቹ ይስቁበታል። ሲስቁበት አይከፋውም።

ራሱም ቢሆን፣ “ትምህርት አይገባኝም፣ ደደብ ነኝ” ብሎ በግልፅ ይናገራል። እናቱ ግን በዝምታ አታልፈውም። “ደደብ አይደለህም፤ አንጎል አለህ አይደለም?” ትለዋለች። “አዎ” ይላል እያመነታ። “ስለዚህ፤ አንጎልህን ተጠቀምበት። አለም ሁሉ በእጅህ ናት” ትለዋለች። ባትማርም፣ በጣም አስተዋይና ብልህ እናት ናት። የካርሰን እናት፣ ልጆቿ ስኬታማ መሆን እንደሚችሉ ከምር ታምናለች። እንዴት ስኬታማ እንደሚሆኑ ነው ያላወቀችው። ማሰብ ማሰላሰሏን ግን አላቋረጠችም። የሰፈሯን የድህነት አኗኗር በደንብ ታውቀዋለች። የሃብታሞች ሰፈር ሄዳ ቤት ስታፀዳም አኗኗራቸውን ትመለከታለች። ድሆቹንና ሃብታሞቹን የሚያለያቸው ምንድነው? አስተዋይ መሆኗ ጠቀማት። አንድ ቀን፣ በሃብታም ቤተሰብ መኖሪያ ቤት ውስጥ ሰፊውን ክፍል እያፀዳችና ቴሌቪዥን የተቀመጠበትን አካባቢ እየጠራረገች ሳለ… ተገለጠላት። ተደራርበው የተቀመጡት መፃህፍት ቴሌቪዥኑን በከፊል ከልለውታል። አንዳንዶቹ መፃህፍት ገለጥ ገለጥ ተደርገው ተቀምጠዋል። ቀና ስትል… ያን የሚያክል ሰፊ ክፍል፣ ከወለል እስከ ጣራ ድረስ… መደርደሪያው ሁሉ በመፃህፍት ተጠቅጥቋል። በቃ! ገባት። ያን እለት በየቦታው ለሥራ ስትደክም ውላ ማታ ወደ ቤት ስትመለስ፣ ካርሰንና ወንድሙ አሮጌ ቴሌቪዥን ላይ አፍጥጠው አገኘቻቸው። ቴሌቪዥኑን አጠፋችው። “ከዛሬ ጀምሮ፣ ቴሌቪዥን የምታዩት በሳምንት ሁለት ቀን ብቻ ነው” አለቻቸው።

ለምሳሌ፤ የተማሪዎች የጥያቄና መልስ ውድድር ማየት ይችላሉ። “ሁለት ቀን ብቻ? ሌላውንስ ጊዜ ምን እንሰራበታለን?” ብለው ጠየቁ። “ይህንን ጥያቄ ነበር ከናንተ የምጠብቀው። ምን እንደምታደርጉ እነግራችኋለሁ። ቤተመፃህፍት ትሄዳላችሁ። በሳምንት ሁለት መፅሃፍ ታነባላችሁ” ስትላቸው፣ የምሯን አልመሰላቸውም። መፅሃፍ ማንበብ የሚባል ነገር በእውናቸውም በህልማቸውም መጥቶላቸው አያውቅም። እንግዲህ ምን ይደረጋል? ከቤተመፃህፍት በውሰት መፅሃፍ ማምጣት የግድ ቢሆንም፣ የውሸት “አንብቤዋለሁ” ብሎ መመለስ እንደሚቻል ማሰባቸው አልቀረም። ሃሳባቸውን ያወቀች ይመስል፣ ሌላ ትዕዛዝ ጨመረችላቸው። “ያነበባችሁትን ቁምነገር፣ በየራሳችሁ አገላለፅ አሳጥራችሁ ትፅፉና ለኔ ትሰጡኛላችሁ” አለቻቸው። መፅሃፍ ማንበብ፣ ለካርሰንና ለወንድሙ ቀላል አልሆነላቸውም። ትግል ነው። ግን ደግሞ፣ መፃህፍቱ ውስጥ በሚያገኟቸው አስደናቂ ታሪኮችና እውቀቶች… ተገርመዋል። እስካሁን የማያውቁትና ጨርሶ ያልጠበቁት አይነት ልዩ ደስታ አግኝተውበታል። ብዙም ሳይቆይ፣ መፅሃፍ ማንበብ፣ “ግዴታ” መሆኑ ቀረ።

በንባብ ፍቅር፣ መፅሃፍ እንደያዙ ሌሊቱ ይጋመሳል። መፅሃፍ አንብቡ እያለች ስትወተውታቸው የነበረችው እናት፣ ቶሎ አንብበው በጊዜ እንዲተኙ መምከር ጀመረች። ካርሰን፣ “ደደብ” እንዳልሆነ ገባው። የሳይንስም ሆነ የሂሳብ፣ የቋንቋም ሆነ የታሪክ ትምህርቶችን ሁሉ በቀላሉ መረዳት እንደሚችል ሲያይ፣ ለማመን ከብዶት ነበር። ግን፣ የፈተና ውጤቱም በአጭር ጊዜ ውስጥ ተሻሽሏል። በሁለተኛው አመት ደግሞ፣ ከክፍሉ አንደኛ ወጣ። ከዚያም ከትምህርት ቤቱ አንደኛ በመሆን ተሸለመ። የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ሲያጠናቅቅ በመላ አሜሪካ ከፍተኛ ውጤት የሚያስመዘግቡ ተማሪዎችን አወዳድሮ ወደሚቀበለው ሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ገባ - በከፍተኛ ውጤት ነፃ የትምህርት እድል ተሰጥቶት። በቃ፤ የሚያቆመው አልተገኘም። ጆን ሆፕኪንስ ዩኒቨርስቲ ገብቶ፣ የአንጎል ቀዶ ህክምናን በማጥናት ተመረቀ። በሳይንሳዊ ጥናቶች ዙሪያ፣ ጆን ሆፕኪንስ ዩኒቨርስቲን የሚስተካከል የትምህርት ተቋም በአለማችን የለም። 33 የዩኒቨርስቲው ተመራቂዎችና አስተማሪዎች የኖቤል ተሸላሚ ሆነዋል። በዚህ ዩኒቨርስቲ ተምሮ መመረቅ ራሱ፣ ለካርሰን ትልቅ ስኬት ነው።

ግን አልበቃውም። በየአመቱ ከሶስት መቶ በላይ ከባድ የቀዶ ህክምና አገልግሎት በመስጠት የብዙ ሰዎችን ህይወት አድኗል። ይህም ብቻ አይደለም። በህፃናት የአንጎል ህክምና ላይ፣ መፍትሄ ላልነበራቸው በሽታዎች አዳዲስ የህክምና ዘዴዎችን በመፍጠር በመላው አለም በቀዳሚነት የሚጠቀስ ታላቅ ሰው ለመሆን በቅቷል - ዶ/ር ቤን ካርሰን። ሰዎች በራሳቸው ጥረት፣ ከ“ደደብነት” ወደ እውቀት ማማ መምጠቅ፣ በእውቀታቸውም ከድህነት ወደ ብልፅግና መሸጋገር እንደሚችሉ ይጠረጠራል? በቤን ካርሰን የጀግንነት ታሪክ ውስጥኮ ቁልጭ ብሎ ይታያል። አርአያነቱ፣ ለሁላችንም ነው። እውቀትን እየጨበጡ ወደ ስኬት መጓዝ ይቻላል። እስካሁን በጥበበኛ ሰዎች ጥረት የተገኙ አስደናቂ እውቀቶችን በስፋት መቅሰም የምንችለው ከመፃህፍት ነው። አዳዲስ እውቀቶችን ለመጨበጥ የሚያስችሉ ሳይንሳዊ ዘዴዎችንም ከመፃህፍት ውስጥ እናገኛለን። ያኔ፣ እንደ እውቀታችን መጠን እየሰራን ስኬትን እናጣጥማለን - በቃ… የጥረት ጉዳይ ነው፤ የንባብን ፍቅር የማዳበር ጉዳይ ነው። በእርግጥ፣ ሁሉም ሰው እንደ ልብ ጥሩ ጥሩ መፃህፍት ያገኛል ማለት አይደለም። የምንፈልገው አይነት መፅሃፍ ማግኘት… ለብዙዎች ብርቅ ነበር - እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ።

ኢትዮጵያ ውስጥ ቤተመፃህፍት ያላቸው ከተሞች ስንት ቢሆኑ ነው? እነሱም ቢሆኑ፣ የያዙት የመፃህፍት አይነትና ብዛት ቢቆጠር ኢምንት ነው። ዛሬ ግን፣ ያ ሁሉ “የመፅሃፍ ችጋር” ተረት እየሆነ ነው። የ“ኮፒ ራይት” ጥያቄ አነጋጋሪ ቢሆንም፣ በየትኛውም የእውቀት መስክ፣ በየትኛውም የእውቀት ደረጃ… ማማረጥ እስኪቸግረን ድረስ እልፍ መፃህፍት ማግኘት እንችላለን - በኢንተርኔት። ዛሬ፣ በመፃህፍት እጥረት ማሳበብ አይቻልም። የእውቀትና የስኬት በር፣ እዚሁ አጠገባችን መጥቷል። አንኳኩቶ መክፈትና መግባት ነው የኛ ድርሻ። በሩ ኮምፒዩተር ነው። ኢንተርኔትን በመጠቀም እናንኳኳ። መክፈቻው፣ የ“እንግሊዝኛ” ቋንቋ ነው። አብዛኞቹ መፃህፍት በእንግሊዝኛ የተዘጋጁ ናቸውና።