Administrator

Administrator

በአለን ሌከን ተፅፎ አባተ መንግሥቱ የተረጐመው “ስኬታማ የጊዜ አጠቃቀም” እየተሸጠ ነው፡፡ በውጤታማ የጊዜ አጠቃቀም ዙርያ የተፃፈው መፅሐፍ ኤችኬ ፐብሊሺንግ የታተመ ሲሆን ዋጋው 25 ብር ከ35 ነው፡፡የመጽሐፉን የአርትኦት ስራ ደራሲና ሃያሲ መስፍን ሃብተማርያም ነው የሰራው፡፡ ይህ በዚህ እንዳለ የሮቢን ሻርማ “The Monk Who Sold His Ferrari” በብርሃኑ በላቸው “ራስን ማወቅ” በሚል ርዕስ ተተርጉሞ ለገበያ የበቃ ሲሆን በ35 ብርም እየተሸጠ ነው፡፡ በፋርኢስት ትሬዲንግ የታተመው መፅሐፉ፤ 176 ገፆች አሉት፡፡ መፅሐፉን መገናኛ አካባቢ የሚገኘው ዩኒቲ መፃህፍት መደብር እንሚያከፋፍል ታውቋል፡፡

በወይንሸት መርከቡ የተደረሱ አምስት አጫጭር ልቦለዶች የተካተቱበት “እኔና ቄስ ገንዘቤ” የአጫጭር ልቦለዶች መድበል ለንባብ በቃ፡፡ በመፅሐፉ “እኔና ቄስ ገንዘቤ” ባለ አራት ክፍል አጭር ልቦለድ እንዲሁም “ማትሪክ”፣ “አቢይ እና አባይ”፣ “ኮሌጅ” እና “ይድረስ ለፈጣሪ” የተሰኙ ሌሎች አጫጭር ልቦለዶች ተካተውበታል፡፡ 118 ገፅ ያለው መፅሐፉ ባናዊ ማተሚያ ቤት የታተመ ሲሆን ዋጋው ለሀገር ውስጥ 25 ብር፣ ለውጭ ሀገራት 10 ዶላር ነው፡፡ በሰሎሞን ታደሰ የተደረሱ ወጐችና እውነተኛ ታሪኮች የተካተቱበት “የሸገር ወጐች እና እውነተኛ ታሪኮች” መፅሐፍ እንዲሁ ለንባብ በቅቷል፡፡ በመፅሐፉ “የሸገር ወጐች”፣ “መጣንላችሁ ማሳጆች”፣ “የጨለሙ ታሪኮች በዱባይ” እና ሌሎች ታሪኮች ተካተዋል፡፡ ደራሲው ካሁን በፊት “ቦሌ ፒኮክ ጋ ጠብቂኝ” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ አብቅቷል፡፡ “የሸገር ወጐች” በ39.50 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

በሙዚቃው ንጉስ ማይክል ጃክሰን አሟሟት ላይ በተመሰረተ ክስ የተጀመረው የፍርድ ሂደት 10ኛ ሳምንቱን ሲይዝ ሁኔታዎች እየተወሳሰቡ መምጣታቸውን ዘገባዎች አመለከቱ፡፡ ታዋቂው የኮንሰርት አዘጋጅ ኤኢጂ ላይቭ ለአሟሟቱ ተጠያቂ መሆን አለበት በሚል የማይክል ካትሪን ጃክሰን እና ቤተሰባቸው ክስ እንደመሰረቱ ሲታወቅ፤ በክሱ የ40 ቢሊዮን ዶላር ካሳ የከፈለን በሚል እየተሟገቱ ናቸው፡፡ ማይክል ጃክሰን ከአምስት ዓመት በፊት ከመጠኑ ያለፈ መድሃኒት በመውሰድ ለድንገተኛ ሞት መብቃቱ የሚታወስ ሲሆን የተጠየቀው ካሳ አርቲስቱ በ50 ዓመቱ እድሜው ህይወቱ ባያልፍ ኖሮ በኮንሰርት ስራዎች እና በአልበም ሽያጭ ሊያገኝ የሚችለው ገቢን በማስላት የተተመነ ነው፡፡ የግሉ ሃኪም የነበሩት ዶክተር ኮናርድ ሙራይ ለሞቱ መንስኤ የሆነ መድሃኒት ያለጥንቃቄ ሰጥተዋል በሚል ክስ ተጠያቂ መደረጋቸው ይታወቃል፡፡ አሁን በተጀመረው የፍርድ ክርክር ደግሞ የኮንሰርት አዘጋጁ ኤኢጂ ላይቭ ታላቁን ሙዚቀኛ አላግባብ ትኩረት በመንፈግ ከሞት አደጋው ሳይታደጉ ቀርተዋል በሚል ተከስሰዋል፡፡ የኤኢጂ ጠበቃዎች ማይክል ጃክሰን ለሞት የተዳረገው ራሱ በቀጠረው እና በወር እስከ 150ሺ ዶላር በሚከፍለው የግሉ ሃኪም ስህተት እንጂ ከሚያቀርበው ዓለም አቀፍ ኮንሰርት በተያያዘ አለመሆኑን በመግለፅ የክስ መከላከያቸውን አቅርበዋል፡፡

ኤኢጂ ላይቭ የማይክል የግል ሀኪም የነበሩትን ዶክተር ኮናርድ ሙራይ አልቀጠርኩም ብሎ ከመካዱም በላይ ለሞቱ ምን ሃላፊነት የለብኝም ይላል፡፡የማይክል ቤተሰብ በጉዳዩ ላይ 97 ምስክሮችን እንዲሁም ኤኢጂ ላይቭ ደግሞ 113 ምስክሮችን ለክስ መከላከያው በማቅረብ ለወራት በጉዳዩ ላይ በመሟገት ይቀጥላሉ፡፡ በሌላ ዜና ማይክል ጃክሰን በሞቱ ማግስት በ500 ሚሊዮን ዶላር እዳ ተይዞ እንደነበር ያስታወሰው ሴሌብሪቲኔይዎርዝ ከዚህ እዳው ሙሉለሙሉ ነፃ መውጣቱን አስታውቋል፡፡ የማይክል ጃክሰን ሃብት ንብረትን ለመሰብሰብ ቤተሰቡ ለጠበቆች እስከ 13.6 ሚሊዮን ዶላር መክፈላቸውን ያወሳው ሴለብሪቲ ኔትዎርዝ የሃብት መጠኑ 600 ሚሊዮን ዶላር እንደሚደርስ አመልክቷል፡፡ ማይክል ጃክሰን በኑዛዜው ከሃብት ንብረቱ 40 በመቶውን ለልጆቹ፤ 40 በመቶውን ለእናቱ እና ቀሪውን 20 በመቶ ለበጎ አድራጎት መለገሱ ሲታወቅ እናቱ ካተሪን ጃክሰን ከመየርሳቸውን ድርሻ ልጆቹ እንዲወርሱ መናዘዙን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ታዋቂው ራፐር 50 ሴንት በቀድሞ ፍቅረኛው ላይ አድርሷል በተባለ ጥቃት ሊከሰስ ነው፡፡ ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘ የአምስት አመት እስርና የ46ሺ ዶላር ካሳ እንዲከፍል እንደሚወሰንበት የቢልቦርድ ዘገባ አመልክቷል፡፡ 50 ሴንት ከሁለት ሳምንት በፊት ወደ ቀድሞ ፍቅረኛው የኮንዶሚኒዬም መኖርያ በመሄድ ጥቃት ማድረሱ ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል ከፈፀመው ፆታዊ ጥቃት ጋር በትችት መወጠሩ ሳያንሰው ራፐሩ በስልክና በፅሁፍ መልዕክት የ16 ዓመት ልጁን በማስፈራራቱም እየተብጠለጠለ ነው፡፡ ራፐሩ ከታዳጊ ልጁ ጋር በስልክ ባደረገው ንግግር “የእናትህ ልጅ እንጂ የእኔ አይደለህም፡፡ ገና የደም ምርመራ ሁሉ አደርጋለሁ፡፡ እንደ እናትህ እና እንደ ቤተሰብህ ከእኔ የምትፈልገው ስጦታ ብቻ ነው፡፡ ከእንግዲህ ግን ምንም እንዳትጠብቅ፡፡ ስልኬን ሰርዘው፡፡ ሁለተኛም እንዳትደውልልኝ” ብሎታል፡፡

ቢልቦርድ መፅሄት እንደዘገበው፤ ራፐሩ በቀድሞ ፍቅረኛው እና በልጁ ላይ የፈፀማቸው ተግባራት ገፅታውን እያበላሸበት ነው፡፡ በሌላ በኩል ፊፍቲ ሴንት ከሙዚቃው ባሻገር በተሰማራበት ንግድ እጅግ ትርፋማ እየሆነ መምጣቱን ያመለከተው ሂፖፕ ኒውስ፤ በ260 ሚሊዮን ዶላር ከአምስቱ የዓለም ሃብታም ራፐሮች አንዱ ሊሆን እንደበቃ ጠቁሟል፡፡ ለ50 ሴንት ሃብት ማደግ በዋናነት “ቪታሚን ዎተር” በተባለው የውሃ ምርት አምራች ኩባንያ ያዋለው ኢንቨስትመንት ትርፋማነት መሆኑን የጠቀሰው ዘገባው፤ ‹ጂ ዩኒት› በተባለው የፋሽንና የሙዚቃ ኩባንያው እንዲሁም በፊልም ስቱድዮው እና በተለያዩ የማስታወቂያ ስራዎችም የተወጣለት ነጋዴ መሆኑን አብራርቷል፡፡

• እናቶች ለእርግዝና ክትትል ወደጤና ተቋም በሚቀርቡበት ጊዜ ተመርምረው ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ከሆኑ ወዲያውኑ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መድሀኒቱን አንዲጀምሩ ይደረጋል፡፡ • ኤችአይቪ ቫይረስ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ይበልጥ የሚመረጠው እናቶቹ የእድሜ ልክ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ ነው፡፡ ኤችአይቪ ቫይረስ ከእናት ወደልጅ እንዳይተለሰለፍ ለመታደግ ሲባል የአለምአቀፉ የጤና ድርጅትን ጨምሮ በየአህጉሩ ያሉ ብሔራዊ ተቋማት እና ሌሎች አለምአቀፋዊ ድርጅቶችን ጨምሮ የተለያዩ ጥረቶች መደረግ ከጀመረ ሰንበትበት ብሎአል፡፡ የሚወለዱ ሕጻናት ከእናቶ ቻቸው የኤችአይቪ ቫይረስን እንዳይወስዱ ለማድረግ የሚያስችሉ ግኝ ቶች እና አሰራሮች በመዘርጋታቸው ከቫይረሱ ነጻ የሆኑ ሕጻናትን ማዋለድ ተችሎአል፡፡ ከእናት ወደ ልጅ የሚተላለፈው የቫይረሱ ስርጭት በእርግዝና ፣በምጥ ፣በመው ለድ ወይንም ጡት በማጥባት ሲሆን ስርጭቱም ከ25-45 % የሰፋ ነው፡፡

የኤችአይቪ ቫይረስን ስርጭት ለመግታት አስቸኩዋይ እቅድ የማወጣት ፕሮግራም ወይንም ደግሞ pepfar (ፔፕፋር) ተብሎ የሚጠራው ሰፊ ፕሮግራም ባወጣው መረጃ መሰረት የዛሬ አራት አመት ገደማ በአለም ላይ ወደ 390,000- (ሶስት መቶ ዘጠና ሺህ) የሚጠጉ ህጻናት ከቫይረሱ ጋር ተወል ደዋል፡፡ ከእነዚህ ህጻናት ውስጥ 90 % የሚ ሆኑት ከሰሃራ በታች ያሉ ሀገራትን ጨምሮ በ22/ ሀገሮች ውስጥ የተወለዱ ናቸው፡፡ ባደጉት ሀገሮች ውስጥ ከእናት ወደ ልጅ የሚተላለፈው የቫይረሱ ስርጭት ሙሉ ለሙሉ ተገትቶአል ማለት የሚያስችለው የ pepfar ጥናት በእርግዝና ጊዜ የጸረ ኤች አይቪ መድሀኒትን ትክለኛ የሆነ አጠቃቀምና ከወሊድ በሁዋላ ጡት ባለማጥባት ቀጥተኛ የሆነውን የቫይረሱን ስርጭት እስከ 5 % ድረስ መቀነስ ይቻላል ብሎአል፡፡ pepfar የዛሬ ሶስት አመት ባደረገው ዘመቻ መሰረት 9.8/ ሚሊዮን የሚሆኑ እር ጉዝ ሴቶች የኤችአይቪ ምርመራ እንዲያደርጉ ከእነዚያ ውስጥ 660,000/ያህሉ ቫይረሱ በደማ ቸው ተገኝቶ ነበር፡፡ እነዚህ እናቶች ቫይረሱን ወደልጆቻቸው እንዳያስተላልፉ ሲባል ART የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት እንዲወስዱ ተደርጎአል፡፡

ይህ በመሆኑ ከ200,000/ (ሁለት መቶ ሺህ .. በላይ የሆኑ ሕጻናት ከኤችአይቪ ነጻ ሆነው እንዲወለዱ እድሉ ተፈጥሮአል፡፡ ከእናታቸው በቀጥታ ቫይረሱን የተቀበሉ ሕጻናት በሕይወት የሚቆዩት ቢበዛ እስከ ሁለት አመት እድሜያቸው ድረስ ነው፡፡ ከኤድስ ነጻ የሆነ ትውልድን ለማፍራት የሚደረገው እርብርብ አ.ኤ.አ በ2015/ ለታቀደው የሚሊኒየም ግብ 90% የሚሆነውን ከእናት ወደልጅ የሚተላለፈውን የቫይረሱን ስርጭት ይገታል የሚል ተስፋ አለ፡፡ ሕጻናት የኤችአይቪ ቫይረስን ከእናታቸው እንዳይወርሱ ከሚያስችለው አለምአቀ ፋዊ ጥረት መካከል እርጉዝ የሆኑ እናቶች ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ከተገኘ በቀጥታ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒቱን እንዲወስዱ ማድረግ ይገኝበታል፡፡ ይህም በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን በተግባር ላይ እንዲውል የሚያስችል አሰራር የተዘረጋ ሲሆን ይህንን በሚመለከት ማብራሪያ እንዲሰጡን የጋበዝነው ዶ/ር ታደሰ ከተማ በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የእናቶች ጤና አማካሪ ናቸው፡፡ ዶ/ር ታደሰ እንደሚገልጹት በኢትዮጵያ ላለፉት አስር አመታት በላይ ኤችአይቪ ከእናቶች ወደ ልጆች እንዳይተላለፍ ለማድረግ የሚያስችል አሰራር በተግባር ውሎአል፡፡ አሰራሩን አስተማማኝ በሆነ መንገድ ለመለወጥና ከኤችአይቪ ነጻ የሆነ ትውልድ ለማፍራት እንዲያስችል የተለየ አገልግሎት በየጤና ተቋማቱ እንዲሰጥ በመደረግ ላይ ነው፡፡ ይህ አገልግሎትም ከአሁን ቀደም ቫይረሱ ያለባቸውን እርጉዝ ሴቶች በመለየት ለአጭር ጊዜ የሚቆይ ጸረኤችአይቪ መድሀኒት ይሰጥ የነበረ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ግን የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ለእድሜልክ እንዲሆን ተወስኖአል፡፡

የዚህ አላማም ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ከማድረግ ባሻገር እናት ከኤችአይቪ ጋር በተያያዘ ሌሎች ሕመሞችን እንዳትታመም እና የእራስዋን ጤንነት ለመጠበቅ እንዲያስችላት ነው፡፡ስለዚህም እናቶች ለእርግዝና ክትትል ወደጤና ተቋም በሚቀርቡበት ጊዜ ተመርምረው ፖዘቲቭ የሆኑት ወዲያውኑ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መድሀኒቱን አንዲጀምሩ ይደረጋል፡፡ እርጉዝ ሴቶችም ሆኑ ሌሎች ሰዎች በደማቸው ኤችአይቪ ቫይረስ የሚገኝ ከሆነ የሰውነታቸው የመከላል አቅም እና በሰዎቹ ላይ የተከሰተውን የተለያየ ሕመም መሰረት በማድረግ ቫይረሱ ያለበት ደረጃ ከታየ በሁዋላ ጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት መውሰድ የሚገባቸውንና የማይገባቸውን በመለየት መድሀኒቱ ይሰጥ እንደነበር ይታወሳል፡፡ አሁን ግን እናቶቹ የሰውነት የመከላከል አቅማቸው ያለበት ደረጃ በምርመራ እንዲታወቅ የሚደረግ ሲሆን ያ የሚደረገው ግን ፀረ ኤችአይቪ መድሀኒቱን ለመጀመር ሳይሆን የጤንነታቸው ሁኔታ ያለበትን ደረጃ ለማወቅ እና ክትትሉን ለማድረግ እንዲያስችል ሲባል ነው፡፡ ፀረ ኤችአ ይቪ መድሀኒትን ቀድሞ መጀመር ከኤችአይቪ ጋር ተያይዘው የሚመጡ የተለያዩ በሽታዎችን እንዳይኖሩ ከማድረግ በተጨማሪ እናቶቹ ለረጅም ጊዜ ጤንነታቸው ተጠብቆ እንዲኖሩ ፣የሚወልዱዋቸው ሕጻናትም ከቫይረሱ ነጻ ሆነው እንዲወለዱ ይረዳቸዋል፡፡ ዶ/ር ታደሰ ከተማ እንደገለጹት እናቶች የእድሜ ልክ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያደርገው አሰራር ኤችአይቪን በተመለከተ ልዩ ትኩረት ያስፈልጋቸዋል በተባሉ 22/ ሀገራት ተሞክሮ ውጤት ያስመዘገበ ሲሆን በተለይም ማላዊ የተሳካ ልምድ ያገኘችበት ነው፡፡

የአለም የጤና ድርጅት ለእናቶች ጤና ተገቢው እና ትክክለኛው ነው በሚል እንዲተገበር ብዙ አገራትን እያማከረ እና አቅጣጫን እያስያዘ ያለበት አሰራር በመሆኑ በኢትዮጵያም ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል፡፡ ኤችአይቪ ቫይረስ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ የሚሰጠው አገልግሎት በደረጃ ሊከፋፈል የሚችል ነው፡፡ •በእርግዝና ወቅት እናቶች የእርግዝና ክትትል እንዲያደርጉ ማድረግ፣ •የኤችአይቪ የምክርና የምርመራ አገልግሎት መስጠት፣ •እናቶች በጤና ተቋማት እንዲወልዱ ማድረግ፣ •ከኤችአይቪ ፖዘቲቭ እናቶች የተወለዱት ሕጻናት ክትትል እንዲያደርጉ ማድረግ፣ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ እናቶች የእርግዝና ክትትል የማድረጋቸው ሁኔታ ቀደም ካሉት ጊዜያት የተሸሻለ ደረጃ ላይ የሚገኝ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ወደ 20 % የነበረው የእር ግዝና ክትትል ዛሬ ወደ 80% ደርሶአል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ከ35 -45 % የማያንሱ እናቶች የኤችአይቪ የምክርና የምርመራ አገልግሎት ያገኛሉ፡፡ በአገሪቱ በአጠቃላይ ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ይሆናሉ ተብሎ ከሚገመቱት ወደ 34000/ እናቶች ውስጥ 42 % የሚሆኑት ቫይረሱ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡

ከተወለዱት ልጆችም የህክምና ክትትል እየተደረገላቸው የሚገኙ የመኖራቸውን ያህል በተለይም ቤተሰቦች ከተወሰነ ጊዜ በሁዋላ የሚያቋርጡ በመሆኑ እንደ አንድ ችግር የሚታይ ነው፡፡ አንዳንድ ኤችአይቪ ፖዘቲቭ የሆኑ እናቶችም የህክምና ክትትላቸውን በትክክል ሳያቋርጡ የማይከታተሉ በመሆኑ በዚህ ረገድ ገና ብዙ መሰራት የሚጠበቅበት ሆኖ ተገኝቶአል፡፡ ምንም እንኩዋን ከነበረበት ሁኔታ የተሸሻለ ነገር ይታያል ቢባልም በአጠቃላይ አላማው ከቫይረሱ ነጻ የሆኑ ልጆችን ማዋለድ ሲሆን ይህንን ግን በትክክል ለማወቅ የሚያስችል አካሄድ እስከአሁን ማግኘት አልተቻለም፡፡ እ.ኤ.አ በ2011/ የተሰራ አገር አቀፍ ጥናት እንደሚጠቁመው በኢትዮጵያ ውስጥ ቀደም ሲል የነበረው የቫይረስ ስርጭት እየቀነሰ መምጣቱን ያመላክታል፡፡

በዚህም ጥናት መሰረት ቀደም ሲል ወደ 3% የነበረው አሁን 1.5% በሚል ሊጠቀስ እንደሚችል ጥናቱ ያሳያል፡፡ ቀደም ሲል ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ይሆናሉ ተብለው የሚገመቱ እናቶች ቁጥር ወደ 80,000/ እና 90,000/ ገደማ የነበረ ሲሆን በዚህ ጥናት የታየው ግን ከ34,000 ብዙም የማይበልጡ እናቶች ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ይሆናሉ የሚል ግምት አለው፡፡ ይህም የግንዛቤ ማስጨበጥን ስራ እና በተለያዩ ተቋማት የሚሰሩ ስራዎችን ውጤታማ አካሄድ የሚያ ሳይ ሲሆን እነዚህ አካላት ወደፊትም ብዙ እንዲሰሩ የሚጠበቅበት ሁኔታ መኖሩ ግልጽ ነው ብለዋል ዶ/ር ታደሰ ከተማ፡፡ በእርግዝና ክትትል ወቅት ኤችአይቪ በደማቸወ ውስጥ የተገኘባቸው እናቶች ቁጥር እና ጸረ ኤችአይቪ መድሀኒትን ተጠቃሚ የሆኑት ቁጥር በፊት ከነበረበት 25% አሁን ወደ 42% ደርሶአል፡፡ ስለዚህ እናቶች ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ከተገኝ የእድሜ ልክ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ ይሁኑ ሲባል ቫይረሱ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይ ተላለፍ እና እናቶችም ጤንነታቸው በተጠበቀ ሁኔታ ሕይወታቸውን እንዲቀጥሉ ለማስቻል መሆኑን ሁሉም ሊረዳው ይገባል፡፡

ኢትዮጵያ በሚቀጥሉት ሶስት አመታት ውስጥ ኤችአይቪ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ ወይም መተላለፉን ለማጥፋት እቅድ ይዘው እየሰሩ ካሉ አገሮች ውስጥ አንዱዋ ነች፡፡ ስለዚህም ይህንን አለማ እውን ከማድረግ አንጻር ይህ የጸረ ኤች አይቪ መድሀኒት ለሁሉም ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ለሆኑ እርጉዝ ሴቶች በዘለቄታዊ መንገድ መስጠት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ዶ/ር ታደሰ ከተማ በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የእናቶች ጤና አማካሪ እንዳብራሩት፡፡

ከአስራ አምስት ዓመት በፊት ወደ ሙዚቃ ሙያ የገባው ድምፃዊ ሸዋንዳኝ ኃይሉ፣ ባለፈው ሳምንት “ስጦታሽ” የተሰኘውን ሁለተኛ አልበሙን ለአድማጭ ጆሮ አድርሷል፡፡ “ስቅ አለኝ” በተባለው የመጀመርያ ስራው ከህዝብ ጋር የተዋወቀው አርቲስቱ፤ እ.ኤ.አ በ2004 ዓ.ም በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው “ኮራ” የሙዚቃ ውድድር ላይ እጩ ሆኖ ለመመረጥ በቅቷል። የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው በአዲሱ አልበሙና በሙዚቃ ህይወቱ ዙሪያ አነጋግራዋለች፡፡

ስቱዲዮ በሄድኩ ቁጥር መብራት እየጠፋ ያስቸግረን ነበር
ስታይላችን ቢቀራረብም እኔም ራሴን ነኝ፣ ቴዲም ራሱን ነው
ፎቶውን ያነሳኝ አንቶኒዮ ፊዮሬቴ ነው፤ ተሰቅሎ ሳየው ደስ ብሎኛል

 አዲሱ አልበምህ ገበያው እንዴት ነው? 

የአገር ውስጥ ሽያጩን በተመለከተ አልበሙን አሣትሞ የሚያከፋፍለው ኤሌክትራ ሙዚቃ ቤት ነው፡፡ ባለቤቱ እንደነገሩኝ የመጀመሪያው ሕትመት ወዲያውኑ በመጠናቀቁ ሁለተኛውን አሣትመው ከስር ከስር እያከፋፈሉ ነው፡፡
የመጀመሪያው እትም ምን ያህል ቅጂ ነበር?
25 ሺህ ቅጂ ነው፡፡ ከዛ በኋላ ያለው ግን ከስር ከስር ስለሚሰራጭ ምን ያህል እንደታተመ የተጣራ መረጃ የለኝም፡፡
አልበምህ በወጣ በሦስተኛው ቀን በአዟሪዎች እጅ አልነበረም፡፡ እጥረት መፈጠሩ ጉዳት የለውም?
እጥረቱ የተከሰተው ለአንድ ቀን ቢሆንም ጉዳት ይኖረዋል፡፡ ይህን ያህል ጊዜ አልበሜን ለመስማት የጓጓው አድማጭ ሊገዛ ፈልጎ ገበያ ላይ በማጣቱ የመጀመሪያው ተጎጂ እኔ ነኝ፡፡ አሣታሚው የመጀመሪያውን ሕትመት ቁጥር ሲወስን በሦስት ቀን ውስጥ ያልቃል ብሎ አልገመተም፡፡ የሆኖ ሆኖ አሁን ችግሩ የተስተካከለ ይመስለኛል፡፡ የታተመው ከስር ከስር እየተሰራጨ ነው፡፡ እኔም ገበያው እንዲህ በመሆኑ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡
ማስተሩን ለኤሌክትራ ለመሸጥ ተዋውለህ የቅድሚያ ክፍያ የተቀበልከው ከስድስት ዓመት በፊት መሆኑን ሰምቻለሁ…
የመጀመሪያ አልበሜ አሣታሚና አከፋፋይ ዜድ ሙዚቃ ቤት ነው፡፡ አልበሙ በጣም በመወደዱ ውጭ አገር ኮንሰርት እንዳቀርብ ብዙ ግብዣዎች እየመጡልኝ ነበረኝ፡፡ አልበሜ በወጣ በዓመቱ ከረጅም የኮንሰርት ጉዞ ስመለስ ደግሞ የኤሌክትራ ሙዚቃ ቤት ባለቤት አቶ ተሾመ ጸጋዬ ጠርቶኝ፣ ያለምንም የጊዜ ገደብ ሁለተኛ አልበሜን ሠርቼ ማስተሩን እንድሰጠው የቅድምያ ክፍል ከፈለኝ። አልበሙ ቢዘገይም የወጣው ግን በዚህ ውል መሠረት ነው፡፡
ከሰባት ዓመት በፊት የተዋዋልክበት ክፍያ ከአሁኑ ጊዜ አንፃር አነስተኛ በመሆኑ ውልህን አፍርሰህ ሌላ ውል እንድትገባ ጥያቄዎች ቀርበውልህ እንደነበርና አንተም ፈቃደኛ እንዳልነበርክ መረጃ ደርሶኛል፡፡ ከቀድሞ ውልህ ከፍ ያለ ክፍያ አግኝተህ ነበር?
እንዳልሽው ውሉን ከፈጸምኩ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ እንደሚታሰበው የሚያረካ ባይሆንም የሙዚቃ ኢንዱስትሪው አካባቢ ትንንሽ ለውጦች አሉ፡፡ በተጨማሪም በዛን ግዜ የነበረው የገንዘብ መጠን ከአሁኑ ጋር ሲነጻጸር ዝቅ ያለ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት የተሻለ የሚባሉ ክፍያዎችን የያዙ ጥያቄዎች ቀርበውልኝ ነበር፡፡ ነገር ግን ቃል ከገንዘብ የላቀ ዋጋ ስላለው ውል ለማፍረስ አልፈለግሁም፡፡ ቢጂአይ ኢትዮጵያ ደግሞ የማስታወቂያ ሥራውን ለማከናወን የሚያስፈልገውን ወጪ በሙሉ ስፖንሰር በማድረግ ደግፎኛል፡፡ ለዚህም በጣም ላመሰግነው እፈልጋለሁ፡፡
ሁለተኛውን አልበም ለማውጣት ብዙ የዘገየህ ትመስላለህ …
በትክክል ሥራ የጀመርኩት የመጀመሪያውን አልበም ካወጣሁ ከሁለት ዓመት በኋላ ነው- የዛሬ ስድስት ዓመት ገደማ፡፡ የመዘግየቴ ምክንያት ደግሞ ሁሌም አዲስ ነገር ለማውጣት ከመጓጓትና በምሠራው ሥራ ካለመርካት የመነጨ ነው፡፡ የተለያየ ዜማና ግጥም እመርጥና ወድጄው ሠርቼ አስቀምጠዋለሁ፡፡ ሌላ ሠርቼ ደግሞ የቀደመውን መልሼ ሳዳምጠው አላስደስት ይለኛል፤ እንደገና ፈርሶ ሌላ ይሠራል፡፡ እኔ ጥቂት ድርሻ ቢኖረኝም ይህ ሁሉ የሚሆነው ከተለያዩ ዜማ እና ግጥም ደራሲዎች ጋር ነበር፡፡ ይልማ ገ/አብ፣ ሞገስ ተካ፣ቴዲ አፍሮ፣ ጌትሽ ማሞ፣ አለማየሁ ደመቀ፣ ብስራት ጋረደው፣ መሰለ ጌታሁን፣ ታደሰ ገለታ፣ አማኑኤል ይልማና ጌቱ ኦማሂሬ --- በአጠቃላይ አሥር የግጥማና የዜማ ደራሲያን በአልበሙ ላይ ተሳትፈዋል። የጠቀስኳቸው በአልበሙ ላይ አሻራቸውን ያሳረፉትን ነው፡፡ ሠርተውልኝ ያላካተትኳቸው ደግሞ በርካታ ናቸው፡፡ ሃያ አምስት ዘፈን ሠርቼ ነው አሥራ አምስቱን የመረጥኩት፡፡
አልበሙን ሠርቼ ካጠናቀቅሁ በኋላም በቅጂ መብት መከበር ዙርያ ችግር ነበር፣ በዚህ ሳቢያም በአሣታሚዎች ላይ የተፈጠረው ስጋት ቀላል የማይባለውን ጊዜ ወስዷል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የዛሬ ስድስት ዓመት ከሁለት ጓደኞቼ ጋር በከፈትነው “ፋራናይት ናይት ክለብ” ሙሉ ለሙሉ የአስተዳደሩን ሥራ የምሠራው እኔ ነኝ፡፡ በዚህ የተነሳም የጊዜ እጥረት ነበረብኝ፡፡ እንግዲህ እነዚህ ሁሉ ለአልበሙ መዘግየት ምክንያቶች ናቸው፡፡ ሌላው መታወቅ ያለበት ሙዚቃ የስሜት ሥራ ነው - የተመቻቸ ጊዜና ቦታ ይፈልጋል፡፡ ምቹ ጊዜ እና ቦታ ማግኘት ደግሞ ራሱን የቻለ ሥራ ነው፡፡ በዚህ በዚህ ነው የዘገየው፡፡
በአልበም ሥራህ ከሙዚቃ ባለሙያዎች ጋር የነበረህ የሥራ ግንኙነት ምን ይመስላል?
ሥራው አድካሚ፣አስደሳችና አስጨናቂም ነበር። ከባለሞያዎቹ ጋር የነበረኝ ግንኙነት የሥራ ብቻ ሳይሆን የጓደኝነትም ጭምር ቢሆንም ይመሩን የነበሩት የሚፈጠሩት ስሜቶች ናቸው፡፡ አልመጣ ሲለን ድካምና መሰላቸት ይኖራል፡፡ ጥሩ ስንሠራ ደግሞ ደስታና ጨዋታው አለ፤ በቃ በጣም ደስ የሚል ጊዜ እናሳልፋለን፡፡ በተሠራው ስራ ሳንግባባ ስንቀር ደግሞ ልዩነቶች ይፈጠራሉ፤ እንጣላለን፤ ለሌላ ጊዜ እንቀጣጠራለን፡፡ ከዚህ ውጪ ደግሞ ለምሳሌ አንድ ሰሞን አበጋዝ በሰጠኝ የጊዜ ሰሌዳ ሥራውን ለመሥራት ጓጉቼ ስመላለስ፣ እኔ እግሬ ስቱዲዮ በረገጠ ቁጥር መብራት ይጠፋ ነበር። ጠብቄ ጠብቄ ወደ ቤቴ ስመለስና ልክ እቤት ስገባ ይመጣል። አንዳንድ ግዜ ደግሞ ተመልሼ ልክ መንገድ ስጀምር መጣ ይባላል፡፡ ይህ በጣም አብሻቂ እና አስጨናቂ ጊዜ ነበር፡፡ እንግዲህ ከእነዚህ ስሜቶች ጋር በመጨረሻ በፍቅር ሠርተን አጠናቀናል፡፡ ሁሉም ባለሞያዎች ጎበዞችና ጥሩ ባህሪ ያላቸው ነበሩ፡፡
የአድማጩ ምላሽ ምን ይመስላል?
እንግዲህ ከወጣ ገና አንድ ሣምንቱ ነው። በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ የበርካታ ሰዎችን አስተያየት ማግኘት ባይቻልም ከዘመድ ጓደኞቼ፣ከአድናቂዎቼ፣ከአድማጮቼና ከፌስቡክ ጓደኞቼ ከተሰጡኝ አስተያየቶች፣ እንደ ዩቱዩብና ድሬ ቱዩብ ባሉ የምስል ማሳያ ዌብሳይቶች ላይ ከተጻፉ አስተያየቶች እንዳነበብኩት ከሆነ፣ እስካሁን ጥሩ አስተያየት እየተሰጠኝ ነው፡፡ በግጥምና ዜማ እንዲሁም በቅንብሩ ‹‹ጥሩ ነው የሰራኸው›› ተብያለሁ። በድምፅም እድገት አሳይተሃል ብለውኛል፡፡ እስከ አሁን ያለው የሚያበረታታ ቢሆንም ትክክለኛውን አስተያየት ለማግኘት አልበሙ በደንብ እስኪሰማ በቂ ጊዜ ሰጥቶ መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡
“የሸዋንዳኝ ድምፅ ውስጥ የቴዲ አፍሮን ድምፅ ማድመጥ ይቻላል” የሚሉ አድማጮች አሉ፤ አንተ ምን ትላለህ?
እኔ እና ቴዲ በሥራ ብቻ ሳይሆን የልብ ጓደኞችም ነን፡፡ ሥራዎችን የምንሰራው ተማክረን ነው፡፡ የቴዲን የግጥምና ዜማ ችሎታ እኔ መናገር ያለብኝ አይመስለኝም፡፡ በተለይ በመጀመሪያው አልበሜ ከጓደኝነትም ባሻገር ዘጠና በመቶ የሚሆነውን የግጥምና ዜማ ሥራ ሠርቶልኛል፡፡ በሁለተኛው አልበሜም ተሳትፎው እንደ መጀመሪያውም ባይሆንም ቆንጆ የሚባሉ ሥራዎችን ሰጥቶኛል፡፡
እኔና ቴዲ ስታይላችን ተቀራራቢ ነው እንጂ እኔም እራሴን ነኝ ቴዲም ራሱን ነው፡፡ እንዳልኩሽ በመጀመሪያው አልበሜ ላይ ቴዲ በርካታ ግጥምና ዜማ ስለሰጠኝ ሥራዎቼ በእርሱ ዓይን የመታየት ዕድላቸው ሰፊ ነበር፡፡ ለዚህ ነው እንደዚህ ዓይነት አስተያየት የሚሰጠው፡፡ በአዲሱ አልበሜ ከተለያዩ ደራሲዎች ዜማና ግጥም በመውሰድ ስሎው፣ ቺክቺካ፣ ሮክ፣ ሬጌ---የተካተቱበት አዳዲስ ስታይሎችን ሞክሬያለሁ፡፡ ወደ አማርኛ ሥራም የበለጠ ተጠግቻለሁ፡፡
አድማጭ ብትሆን ከአዲሱ አልበም ደጋግመህ ማድመጥ የምትመርጠው የትኛውን ዘፈን ነው?
ሁሉንም (ሳቅ) ለምሳሌ በጣም በተጣበበ ጊዜ ውስጥ ሁለት ዘፈኖች ብቻ ይከፈትልህ ከተባልኩ--- ከስራዎቼ ውስጥ ‹‹ስጦታሽ›› እና ‹‹ስለኔ››ን ልመርጥ እችላለሁ፡፡
ለአልበምህ ማስተዋወቂያ ከተማ ውስጥ የተሰቀለውን ቢልቦርድ ሰዎች ሲያደንቁት ሰምቻለሁ…
ባይገርምሽ ከብዙ የፎቶግራፍ ድካም በኋላ በአጋጣሚ የተገኘ ፎቶ ነው፡፡ ፎቶውን ያነሳኝ አንቶኒዮ ፊዮሬቴ ነው፡፡ ዲዛይኑ ‹‹ላይቭ ዲዛይን›› የሚባል ነው፡፡ ተሰቅሎ ሳየው ለእኔም ደስ ብሎኛል።
ለሙዚቃህ የቪዲዮ ክሊፖች አልሠራህም..
‹‹ስጦታሽ›› ለሚለው ዘፈን የቪዲዮ ክሊፕ ተሠርቶ ተጠናቋል፡፡ የሁለት ወይም የሦስት ዘፈኖች ቪዲዮ ክሊፖች ደግሞ በቅርቡ ተሰርቶ ይለቀቃል፡፡
ከአልበም ሥራዎች ውጭ ኮንሰርቶች የት አቅርበሃል..
የውጭ ጉዞ የጀመርኩት የመጀመሪያውን አልበም ከማውጣቴ ቀደም ብሎ ነው፡፡ ሙዚቃ ስጀምር የእንግሊዘኛ ዘፈን እና ጥቂት አማርኛ እጫወት ስለነበር ከአገር ውስጥ የመድረክ ሥራዎች በተጨማሪ ጣልያን፣ ጅቡቲ፣ ኬንያ እና ዱባይ ተጉዤ ሠርቻለሁ፡፡ አልበሙ ከወጣ በኋላም በአገር ውስጥ የተለያዩ የመድረክ ሥራዎችን አቅርቤአለሁ። ከኢትዮጵያ ውጪ ደግሞ ግብጽ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ባህሬን፣ ዱባይ፣ አቡዳቢ፣ እስራኤል፣ ስዊድን፣ እንግሊዝ፣ ኖርዌይ፣ ሆላንድ እንዲሁም በአሜሪካ ከአሥራ ሁለት ግዛቶች በላይ እና በሌሎች አገሮች በተደጋጋሚ ለኮንሰርት እየተጋበዝኩ ሠርቻለሁ፡፡ “ፋራናይት”ን ከከፈትኩ በኋላም በየሣምንቱ ሐሙስ እየተጫወትኩ ነው፡፡
ናይት ክለብ የምትጫወተው የራስህን ሥራዎች ብቻ ነው?
አይደለም፡፡ ከራሴ አልበም ውጪ በዋናነት የአርቲስት መሐሙድ አህመድን፣ የአርቲስት ንዋይ ደበበን፣ የአርቲስት ጌታቸው ካሣና ሌሎች ዘፋኞችን ሥራዎችም እጫወታለሁ፡፡
የዩኒቨርስቲ ትምሕርትህን አቋርጠህ ነው ወደ ሙዚቃ የገባኸው፡፡ ቤተሰብ አልተቃወመም?
ስሜቴ ወደ ሙዚቃ የተሳበው አስረኛ ክፍል ስደርስ ነበር፡፡ ያን ግዜ አሁን በሕይወት የሌለው አባቴ ከፍቶት ነበር፡፡ ዩኒቨርስቲ ስገባ ግን ዶርም ውስጥ አድር ስለነበር ነገሮች ምቹ ሆኑልኝ፡፡ እየተደበቅሁ በመውጣት ሙዚቃውን ገፋሁበት። እንዲህ እንደማደርግ አባቴ ባወቀ ጊዜም ደስተኛ አልነበረም፤ ሊደግፈኝም ፈቃደኛ አልሆነም። በመጨረሻ ቆርጬ ወደ ሙዚቃው መግባቴን ሲያውቅ ግን ምንም ሊለኝ አልቻለም፡፡
አዲሱ አልበም ከወጣ በኋላ የውጭ ኮንሰርቶች ግብዣ አልመጣልህም?
ውጭ አገር ከሚገኙ ፕሮሞተሮች ጋር ትውውቁም ጓደኝነቱም ስላለን ገና አልበሙን እንዳገኙ ነው መደወል የጀመሩት፡፡ በእኔ በኩል ግን ኮንሠርት ለመሥራት አልበሙ በደንብ መሰማቱን እና መወደዱን ማረጋገጥ አለብኝ፡፡
አሁን ደግሞ የሙስሊም ፆም ገብቷል (በዚህ አጋጣሚ ለእስልምና እምነት ተከታዮችና ለጓደኞቼ መልካም የፆም ጊዜ እመኛለሁ) ፆሙ ሲወጣ የአዲሱ አልበም ምርቃት ይኖረኛል፡፡ ኮንሠርት የመሥራት ዕቅዴም ከዚያ በኋላ የሚወሰን ይሆናል፡፡
ቤተሰብ አልመሰረትክም፤ ትዳርን ፈራኸው እንዴ?
ኧረ አልፈራሁም! አሁን የምር እያሰብኩበት ነው፡፡ በቅርብ አዲስ ነገር ይኖራል የሚል ተስፋ አለኝ፡፡

ለአገራቸው ነፃነት ከጣልያን ጋር የተዋጉ አርበኛ ታሪክ
ሁለት ልጆቻቸው በቀይ ሽብር ተገደሉ፡፡
ልጆቼን ልቅበር ሲሉ እስር ቤት ተወረወሩ፡፡
ሚስታቸው በሃዘን ብዛት ህይወታቸው አለፈ፡፡
አንድ የቀረቻቸው ልጅ የት እንደገባች አያውቁም፡፡
ስድስት ዓመት ታስረው ሲወጡ ቤታቸው ፈርሷል!

አቶ መኮንን ብሩ ይባላሉ - የ99 ዓመት አዛውንት ናቸው፡፡ በወሎ ክፍለሀገር አማራ ሳይንት ውስጥ የተወለዱት አቶ መኮንን፣ አምስት መንግስት አይቻለሁ ይላሉ፡፡ በ1928 ዓ.ም ፋሽስት ጣሊያን ኢትዮጵያን ሲወር የ20 ዓመት አፍላ ወጣት እንደነበሩ የሚያስታውሱት አዛውንቱ፤ በደርግ ዘመ ሁለት ወንድ ልጆቻቸው በቀይሽብር እንደተገደሉባቸው ይናገራሉ፡፡ ይሄም ሳያንስ ግን “ሬሳቸውን ወስጄ ልቅበር” በማለታቸው በማዕከላዊ እስር ቤት ለስድስት ዓመት ታስረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የሚኖሩት “የወደቁትን እናንሳ” በተባለ አዛውንትን ሰብሳቢ ማህበር ውስጥ ሲሆን የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ስለ ጣሊያን አርበኝነታቸው፣ ስለኖሩባቸው አምስት መንግስታትና ስለህይወታቸው ቃለምልልስ አድርጋላቸዋለች፡፡ ከ15 ዓመት በፊት የተመሰረተው “የወደቁትን እናንሳ” የተሰኘ ማህበር በበጐ ፈቃደኞች የሚደገፍ ሲሆን በአሁን ሰዓት 46 ሴትና እና 34 ወንድ አረጋዊያንን በመጠለያ፣ በምግብ፣ በህክምናና በእንክብካቤ እየደገፋቸው ይገኛል፡፡ በማህበሩ ከሚረዱት አዛውንቶች መካከል ከ25 ዓመት በላይ በመምህርነት ያገለገሉ፣ የፖሊስ ኦርኬስትራ የሙዚቃ አባል የነበሩ፣ በአርበኝነት ዘምተው የጣልያንን ወራሪ ኀይል የተፋለሙና በህግ ባለሙያነት ያገለገሉ ይገኙበታል፡፡ ለዛሬ ከ99 ዓመቱ አርበኛ አቶ መኮንን ብሩ ጋር ያደረግነውን ጨዋታ እነሆ፡፡

 በጣሊያን ወረራ ወቅት አርበኛ እንደነበሩ ሰምቻለሁ ---

እንዴታ! አምስት አመት ሙሉ ተዋግቻለሁ፡፡
እንዴት ነው የዘመቱት?
አባቴ ቀኝአማች ብሩ ሀይለኛ አርበኛ ነበሩ፡፡ በጦርነቱ ጣሊያኖች አባቴን ሲገድሉብኝ እጅግ ተቆጣሁ፣ ደሜ ፈላ፡፡ በወቅቱ የ20 ዓመት ወጣት ነበርኩ፡፡ ማቄን ጨርቄን የምለው አልነበረኝም፡፡ ጫካ ገባሁና መዋጋት ጀመርኩኝ፡፡
ከየት አካባቢ ነው ወደ ጦርነቱ የሄዱት?
የተወለድኩት ወሎ ውስጥ አማራ ሳይንት ነው፡፡ ጦርነቱን የተቀላቀልኩትም ከዚያ ሄጄ ነው፡፡
በላይ ዘለቀን ያውቁታል ይባላል፡፡ እውነት ነው?
አሳምሬ አውቀዋለሁ እንጂ እንዴት አላውቀውም!
አብራችሁ ዘምታችኋል እንዴ?
አብረን አልዘመትንም፡፡ እኔ እራያ አዘቦ፣ መሆኒ፣ ሸዋ፣ መንዝ፣ መራ ቤቴ፣ አህያ ፈጅ ዶባ እየተዘዋወርኩ ራያው ከፈለ ከተባለ የጦር መሪ ጋር ነው የተዋጋሁት፡፡ ጐበዝ የጦር መሪ ነበር፡፡ በላይ ዘለቀ ግን አባይ በረሃ ላይ ነበር፡፡ ግን ተገናኝተን እናውቃለን፡፡ በደንብ ነው የማውቀው!
ድል ካደረጋችሁ በኋላ ስለነበረው ሁኔታ ያጫውቱኝ-----
ጃንሆይ “አገርህን ለመጠበቅ በጫካ ያለህ ወደ እኔ ተሰብሰብ” ብለው ሲጣሩ፣ ከነበርኩበት ተነስቼ ከጓደኞቼ ጋር መጣሁ፡፡ እርሳቸው ውጭ አገር ከርመው መምጣታቸው ነበር፡፡ እናም አርበኛው ሁሉ በጠቅላላ አዲስ አበባ ገባና ተሰበሰበ፡፡ ጃንሆይ ጃን ሜዳ መጡ፣ በሬው ሁሉ ታረደ፣ ተደገሰ፡፡ ድግሱ ሲያልቅ እዚሁ ለትንሽ ጊዜ ቆዩ ተባልን፡፡ ግን ማንም የሰማቸው የለም፣ ሁሉም በየሀገሩ ሲበታተን እኔም አማራ ሳይንት ገባሁ፡፡
በወቅቱ ጡረታ ምናምን አልነበረም ? ከድል ስትመለሱ ማለቴ ነው---
ደሞ የዛን ጊዜ ጡረታን ማን ነገሬ ይለዋል! መሬት ሞልቷል፣ ገንዘብ ሞልቷል፣ ከብት እንዳፈር ነው፡፡ አሁን እኮ ነው ሁሉ ነገር ችግር የሆነው፡፡ እናም ዝም ብለን አገራችን ገባን፡፡
ታዲያ እንዴት አዲስ አበባ ተመለሱ?
ከተማ ልኑር ብዬ ነው የመጣሁት፡፡ ከዚያም ሚስት አገባሁ፣ ሁለት ወንድና እና አንድ ሴት ልጆች አፍርቼም በሜካኒክነት ሙያ እየሰራሁ ልጆቼን ማስተማር ጀመርኩኝ፡፡
ከዚያስ?
ከዚያማ --- ሁለቱ ወንዶች ልጆቼ 12ኛ ክፍልን ጨረሱ፣ ደረሱልኝ ስል ተቀጠፉብኝ፡፡
እንዴት?
በቀይሽብር ጊዜ ከጨርቆስ አምጥተው ከጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን አለፍ ብሎ ባለው እራስ እምሩ ቤት አጠገብ በሚገኘው ሜዳ ላይ አምጥተው ገደሏቸው፡፡ እያበድኩኝ ሄጄ የልጆቼን እሬሳ አንስቼ እቀብራለሁ ብል ተከለከልኩኝ፡፡ ከዚያም ሙግት ገጠምኩኝ፡፡ እምቢ ካልክማ አሉና --- ማዕከላዊ የሚባል ፖሊስ ጣቢያ ያለጠያቂ ለስድስት ዓመት ታሰርኩ፡፡
ባለቤትዎና ሴት ልጅዎስ?
ባለቤቴ በልጆቿ ሞት ሀዘን ገብቷት እህህ… ህ ስትል፣ እኔ እስር ቤት እያለሁ ሞተች፡፡ እናቷንና ወንድሞቿን በሞት፣ አባቷን በእስራት የተነጠቀችው ሴት ልጄ የት እንደገባች፣ ምን እንደበላት አላውቅም፡፡ በህይወት ትኑር ትሙት የማውቀው ነገር የለም፡፡ እስከዛሬም የእግር እሳቴ ናት፡፡ ስድስት አመት ታስሬ ስወጣ እንኖርበት የነበረው ቤት በመንገድ ስራ ምክንያት ፈርሶ አገኘሁት፡፡ መውደቂያ አጣሁ፣ ችግርና ቁስቁልናው ተስፋ አስቆርጦኝ ሜዳ ላይ ወደቅሁኝ፡፡ ለረጅም ጊዜ ሜዳ ላይ ዝናብና ፀሐይ ሲፈራረቅብኝ ነው የኖርኩት፡፡
አሁንስ? ወደ እዚህ ማህበር ከመጡ በኋላ ኑሮ እንዴት ነው ?
እዚህማ አለም ነው፡፡ እበላለሁ አጠጣለሁ፣ እታጠባለሁ፡፡ ሁሉም ነገር ጥሩ ነው፡፡ በደንብ ይንከባከቡኛል፡፡
አሁን እርግጠኛ 99 ዓመት ሞልቶዎታል?
እንዴ ምን ትላለች! ጣሊያን ሲወረን 20 አመቴ ነው እያልኩሽ! አምስት መንግስት አይቻለሁ እኮ ነው የምልሽ፡፡
አምስት መንግስት ሲሉ--- ከምኒልክ ጀምሮ ነው?
ከዘውዲቱ ጀምሬ አለሁ፡፡ ንግስት ዘውዲቱን አውቃታለሁ፡፡ የስፌት ባርኔጣ ነበር የምታደርገው፡፡ በጣም አደገኛ ሴት ነበረች፡፡
አደገኛ ናት ሲሉ ምን ማለትዎ ነው?
አይ የዛሬ ልጆች! በቃ አደገኛ ናት አልኩሽ አደገኛ ናት፡፡
አምስት አመት ሲዋጉ በጥይት ተመተው ያውቃሉ?
አንድም ቀን አልተመታሁም፡፡ ጥይቱ በግራ በቀኝ ሲያፏጭብኝ አንድም ቀን ተመትቼ አላውቅም፡፡
ኃይለኛ ውጊያ ውስጥ አልነበሩም ማለት ነው? እንዴት ሳይመቱ ቀሩ?
እኔ ምን አውቃለሁ፡፡ እየነገርኩሽ --- በደረቴ ላይ እየሄደ አይመታኝም ነበር፣ ይስተኛል፡፡ ምክንያቱን ግን አላውቀውም፡፡
እርስዎስ ይስታሉ ወይስ አልሞ ተኳሽ ነበሩ ?
ኧረረረ…ስለኔ አልሞ ተኳሽነት ጓደኞቼ በነገሩሽ እንዴት ጥሩ ነበር! (ከንፈራቸውን በተረፉት ጥርሶቻቸው እየነከሱ) ስሜ መኮንን ብሩ ነው ብዬሻለሁ፡፡ በኋላ ጓደኞቼ ቃኘው መኮንን የሚል ስም አወጡልኝ፡፡ ለምን አወጡልህ ብትይኝ --- ጦርነት ከመጣ ወደ ፊት መሄድ እንጂ ድል አርገናል ብዬ ወደ ኋላ አልመለስም፡፡ በቃ ወደ ፊት መግፋት ነው፡፡ ጥይቱ እየተንፏፏ እንኳን ቢሆን ዝም ብዬ እሄዳለሁ፡፡
ካዩዋቸው መንግስታት ጥሩ ነው፣ አስደስቶኛል የሚሉት የትኛው ነው?
እሱን አትጠይቂኝ! (በኃይለቃል) ይህን ቢያወሩት ምን ይሠራል! በቃ ወደ ሌላ ጨዋታ --- ወሬ ታለሽ!
አብዛኛዎቹ እርስዎ ያሉበት ክፍል ውስጥ ያሉት አረጋዊያን ራሳቸውን ችለው አይንቀሳቀሱም ፡፡ እርስዎ ግን ብቻዎን ይንቀሳቀሳሉ ---
እንዲህ ናትና--- በደንብ ነዋ! (ከተቀመጡበት አልጋ ላይ ተስፈንጥረው ወረዱ) አታይም እንዴ! ገና ጐረምሳ እኮ ነኝ! እንዴት ትቀልዳለች ይቺ ልጅ!
ድሮ በጣሊያን ወረራ ጊዜ ስትዋጉ ፉከራ፣ ሽለላና ቀረርቶ በሽበሽ ነበር፡፡ አሁን ካስታወሱት እስኪ ትንሽ ይፎክሩልኝ ----
ምን እባክሽ ---- ፉከራና ቀረርቶ ሞልቷል፡፡ ግን አሁን ምን ያደርግልኛል? ጉሮሮዬ ገጥሟል-- ሰውንም መረበሽ ነው--- ይቅር
ለእርጅና እጅ አልሰጥም--- ጐረምሳ ነኝ አላሉም እንዴ?
ታዲያ ያልኩ እንደሆነሳ! በቃ ፉከራና ሽለላ አሁን ይቅር ነው ያልኩት---የተኙትን ሰዎች እረብሻለሁ፡፡ ጉሮሮዬም ትንሽ ችግር አለው፡፡
ከዚህ በኋላ ስንት ዓመት መኖር ይፈልጋሉ?
አሁን ሞት መጥቶ ቢወስደኝ ደስታውን አልችለውም፡፡
ለምን?
ተይ የኔ ልጅ--- ከዚህ በላይ መኖር አይረባም፡፡ ምንም እንኳን አሁን የጎደለብኝ ነገር ባይኖርም እሰው እጅ ላይ ወድቆ አንሱኝ ጣሉኝ ማለት ትንሽ ደስ አይልም፡፡ እንዲሁ ቅልጥፍ እንዳልኩ ብሄድ ደስ ይለኛል፡፡
ግን ለምን ተስፋ ቆረጡ?
በቃ ቆርጫለሁ፡፡ ሞት ግን እኔን አልፈልግም አለ፡፡ መሬት ላይ ወድቄ እንዲህ እንደማያቸው ሰዎች (እርሳቸው ክፍል ውስጥ ያሉትን ተረጂዎች ማለታቸው ነው) ሳልሆን ብሞት ብዬ ፈጣሪን ብለምነው እምቢ አለ፡፡ ከዚህ በላይ ምን እንደምሠራለት አላውቅም፡፡ በቃ ሰው ራሱን እንደቻለ ነው መሞት ያለበት፡፡

 

“ግፈኞችን ስተታገል አንተም ወደ ግፈኞች አውሬ እንዳትቀየር ተጠንቀቅ”

“ታወር ኢን ዘ ስካይ” ይላል በቀድሞዋ የኢህአፓ አባል ህይወት ተፈራ የተፃፈው መፅሀፍ፡፡ ፍቅር፣ ጥላቻ፣ መተማመን፣ መካከድ እንዲሁም ግራ መጋባት ነፍስ ዘርተው የተተረኩበት መፅሃፉ፤ ኢህአፓ “አንጃ” በሚል ፍረጃ ህይወቱን በቀጠፈው ጌታቸው ማሩ መነሻነት የወቅቱን ሁኔታና የዚያን ዘመን ትውልድ ወለል አድርጐ ያሳየናል፡፡ ከየጌታቸው ማሩ ጓደኞች አንዱን “It remains a paradox to me that someone who believed so strongly in negotiation has been killed” (በውይይት ፅኑ እምነት የነበረው ሰው መገደሉ እንቆቅልሽ ነው እንደማለት ነው) የሚል ምላሽ እንደሰጣት የገለፀችው ህይወት ተፈራ፡፡ መፅሃፉን የፃፍኩበትም ምክንያትም ይኸው ነው ትላለች፡፡

“አንድ ሰው እንወያይ፣ የማያስፈልግ መስዋእትነት አንክፈል፣ ህይወት እናድን፣ ሃሳቤ ለመላው አባላት ይቅረብና የትግሉን አቅጣጫ እነሱ ይወስኑ ስላለ ለምን ይገደላል? ይህ ላለፉት በርካታ አመታት በውስጤ ሲብላላና መልስ ሳላገኝለት የቆየ ጥያቄ ነው” ብላለች፡፡ እስር ቤት እያለች ጀምሮ ታሪኩን ለመፃፍ ፍላጐት እንደነበራት ፀሃፊዋ አስታውሳ በተለያዩ ምክንያቶች ግን ሳልፅፈው ቀረሁ፤ በነዚህ ረጅም አመታት ግን ለራሴ የገባሁትን ኃላፊነት ባለመወጣቴ ከህሊናዬ ጋር ስጣላ ቆይቼ በመጨረሻ ከራሴ የተረከብኩትን ይሄን ከባድ ኃላፊነት ልወጣ በመብቃቴ ከፍተኛ የህሊና እረፍት ይሰማኛል ብላለች - መፅሃፉ ለህትመት በመብቃቱ፡፡ ጌታቸው ማሩ በተማሪዎች ንቅናቄ የማይናቅ ቦታ የነበረውና ከድርጅቱ መስራች አባላት አንዱ ሆኖ በአመራር ደረጃ ላይ የቆየ ቢሆንም ወደዚች ምድር መጥቶ እንደማያውቅ ተቆጥሮ መቆየቱን ሳይ ይቆጮኝ ስለነበር ጥብቅና ልቆምለት፣ ስሙን ላነሳት፣ ካለጊዜው በተዘጋው ልሳኑ ልናገርለት፣ ጉዳቱን ለመላው ኢትዮጵያዊ እና ለአለም ህዝብ ሁሉ ላሳውቅለት በመወሰኔ እነሆ “ታወር ኢን ዘ ስካይ” ፅፌያለሁ ብላለች - ባለፈው ሳምንት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በመፅሃፉ ላይ በተደረገው ውይይት ንግግር ያቀረበችው ህይወት ተፈራ፡፡

በመፅሃፉ ላይ ባለፈው ሰኞ በተካሄደው ምሁራዊ ውይይት ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ፣ ፕሮፌሰር ገብሩ ታረቀ፣ ዶ/ር ጌታቸው ሳህለማርያም፣ አምባሳደር ታደለች ኃይለሚካኤል፣ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ እና አቶ ወልደልዑል ካሳ በመፅሀፉ ላይ ያላቸውን እይታ ያቀረቡ ሲሆን ውይይቱን የመሩት ፕሮፌሰር ማስረሻ ነበሩ፡፡ የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ባህሩ፤ መፅሃፉን ከታሪካዊ ዳራው በመነሳት ከአራት ዋና ዋና ኩነቶች ጋር በማያያዝ አጭር ዳሰሳ አቅርበዋል፡፡ 1962 ዓ.ም በኢትዮጵያ የተማሪዎች ንቅናቄ ታሪክ ውስጥ ወሳኝ ስፍራ እንደነበረው እንዲሁም የመንግሥት ታጋሽነት፣ የተማሪዎች አይበገሬነት የታየበትና በመጨረሻም ኢህአፓ ህቡዕ የገባበት ዘመን መሆኑን ያስታወሱት ምሁሩ፤ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ጥያቄ እያየለ መምጣቱን እየጐለበተ የጥናት ክበቦች መጀመራቸውን፣ በመጨረሻም በተማሪዎች ንቀናቄ ውስጥ መከፋፈል እንዲሁም ስም የመለጣጠፍና ኢህአፓ “አንጃ” እና “ዋና” በሚል ለሁለት የተከፈለበትን ሁኔታ ቃኝተዋል፡፡ በእውነት ላይ የተመሰረቱና ውበት የተላበሱ መፃህፍት መፃፍ የሚችሉት የቀድሞ የኢህአፓ አባላት ብቻ እንደሆኑ የጠቀሱት ፕሮፌሰር ገብሩ ታረቀ፤ ብእሩ የኛ ነው በማለት የህይወት ተፈራን መፅሃፍ አወድሰዋል፡፡

ስለአብዮት አይነቶች፣ አብዮት መቼ እና እንዴት እንደሚፈነዳ ከመፅሃፉ ጋር አያይዘው ትንተና ያቀረቡት ፕሮፌሰሩ፤ መፅሃፉ ላይ በተጠቀሰው የሌኒን “It is possible to predict the time and progress of revolution. It is governed by its own more or less mysterious laws.” የሚል አባባል መነሻነት 45 አመት በፊት የማላደርገው ነገር ግን ዛሬ ላይ ተሳስቷል የምለው አባባል ነው ብለዋል፡፡ “ለዚህ ደግሞ ምክንያቴ የሰውን ልጅ ባህርይ መተንበይ ስለማይቻልና የማይታዩ ታሪካዊ ሁነቶች ስለሆኑ ነው በማለት በማስረጃ አስደግፈው አብራርተዋል፡፡ የአረብ እስራኤል ጦርነት ባይኖር እና የነዳጅ ማእቀብ ባይደረግ ለአብዮቱ ወሳኝ አስተዋፅኦ የነበረውን የታክሲ ሾፌሮች የስራ ማቆም አድማ ማየት አይቻልም ነበር፡፡ ይህን ታሪካዊ ሁነት ደግሞ ማንም ግምት ውስጥ ሊያስገባው አይችልም” በማለት፡፡ ፀሐፊዋም በዚህ ሃሳብ ትስማማለች፡፡

“We didn’t see it coming it caught us by surprise...” (ሲመጣ ስላለየነው በአግራሞት ተዋጥን እንደማለት) ስትል ገልፃለች፡፡ አብዮቶች ነፃነት ያመጣሉ? በሚል ላነሱት ሃሳብ የጆርጅ በርናርድ ሾውን “አብዮቶች የጭካኔን ቀንበር አቅልለው አያውቁም፣ ከአንድ ትከሻ ወደሌላ ያስተላልፋሉ እንጂ” አባባል የጠቀሱት ፕሮፌሰሩ፤ በኢትዮጵያ ሁኔታ ግን አብዮት ጭካኔውን አስተላልፎ አያውቅም፤ በኢትዮጵያ ህዝብ ጫንቃ ላይ እንደተደላደለ ነው ብለዋል፡፡ ይህቺ አለም በሰቆቃ፣ በረሀብ እና በነፃነት ጥያቄ እያለች አብዮት አይቀሬ እና ግዴታ ነው ያሉት ፕሮፌሰር ገብሩ፤ “ወደፊት የሚመጣው የወጣቱ ትውልድ አብዮት ኢትዮጵያ” ጨምሮ በሕዝባዊ አመፅ ሊሆን ይችላል?” በማለት ታዳሚውን ከጠየቁ በኋላ “ዝምታችሁ መልሱን ነግሮኛል” ሲሉ ራሳቸው መልሱን ሰጥተዋል፡፡ ትውስታ (Memoir) እንደ አንድ የስነፅሁፍ ዘርፍ እንዴት እንደሚታየ ያብራሩት ዶ/ር ጌታቸው ሳህለማርያም በበኩላቸው ስለዛ ዘመን እና ትውልድ የተፃፉ መፃህፍት ተችተዋል፡፡ “ከደሙ ንፁህ ነኝ በሚል ተፎካካሪ ድምፆችን ጨፍልቀው፣ አመልካች ጣታቸውን ወደፊት ቀስረው እውነት ያለችው እኛ ጋ ነው የሚሉና በእውነት ስም እውነትን በወገናዊ አተያያቸው ሊያጣምሟት የሞከሩ ናቸው” ብለዋል፡፡ “ታወር ኢን ዘ ስካይ” ግን በወገናዊነት ተጀምሮ ከወገናዊነት በላይ ያደገ፣ ስለዛ ትውልድ ገድል እንድናወራው ሳይሆን እንድንጠይቀውና ራሳችንን በጥብቅ እንድንመረምረው የሚያስገድደን መፅሀፍ ነው ሲሉ እይታቸወን አንፀባርቀዋል - ዶ/ር ጌታቸው፡፡

“በዚህ መፅሀፍ በቀዳሚት ትኩስነት (ለፍቅር፣ ለእውቀት፣ ለትግል)፣ ቀጥሎ የወጣቱን የመረረ ትግል እና መስዋእትነት፤ በተለይ በአገሪቱ ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምዕራብ እስከ ምስራቅ፣ ከመሃል እስከ ድንበር በደርግና በታጠቁ ድርጅቶች፤ የተማገደውን ወጣት እያንዳንዱ ድርጅት በውስጡ የጫረው ምህረት የሌለው ትንቅንቅ እንዲሁም ግንባሮች እና ድርጅቶች እርስ በርስ የተራረዱበትን አውዳሚው እልቂት - መኢሶን ከኢህአፓ፣ ኢህአፓ ከህወሓት፣ ህወሓት ከኢዲዩ፣ ሰደድ ከመኢሶን፣ ሻዕቢያ ከጀብሀ፣ ጀብሀ ከህወሓት” ፍንትው አድርጐ ያሳያል የሉት ምሁሩ፤ በዚህ ትግል አሸናፊና ተሸናፊ ነበር ለማለት እንደሚከብድ ገልፀዋል፡፡ “በሰብአዊነት ሚዛን ከለካነው ሁላችንም ተሸናፊዎች ነን፡፡ ይህን የተሸናፊነት ምክንያት የፌሬድሪክ ኒቼ አባባል ይገልፀው ይሆናል፡፡ “ግፈኞችን ስትታገል አንተም ወደ ግፈኛ አውሬ እንዳትቀየር ተጠንቀቅ” ብሎ ነበር ብለዋል፡፡ “ታወር ኢን ዘ ስካይ”ን ሲያገላብጥ ያገኘሁት ወጣት፤ ስለመፅሐፉ ምን እንደተሰማው ስጠይቀው “ለመሆኑ ያ ትውልድ ኢትዮጵያን ያውቃታል? አይመስለኝም” አለኝ - ያሉት ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም፤ የትውልዱ ትልቁ ችግር ጥያቄዎችን የሚመዘውም መልሱን የሚፈልገውም ከመፃህፍት ከፅሁፍ ነበር ይላሉ፡፡

ይህን እውነት ማስተባበል ይከብዳል፡፡ ምናልባትም የዛ ትውልድ ድክመትና ውድቀት አንዱ ምክንያት ለራስ ባእድ፣ ለጥቅስ ታማኝ የመሆኑ ጉዳይ ይመስለኛል፡፡ የትውልዱ ጥንካሬ ደግሞ የቁሳዊ ሃብትና የስልጣን ተገዢ አለመሆኑ ነው” ሲሉ ያስረዱት ምሁሩ፤ ስለ ህዝባዊው ድል እየዘመረ እንደ ጭድ የረገፈ፤ እኩልነት፣ ነፃነትንና ፍትህን ለማንገስ የነበረውን ህልም ለመተግበር ማንንም ሳይጠብቅ የታገለና የተሰዋ ነው ብለዋል፡፡ ምሁሩ ሌላው ያነሱት ነጥብ በመባነንና ራስን በመፈለግ ዙሪያ ያጠነጥናል፡፡ ፀሃፊዋ ውጣ ውረድ ከበዛው የትግል ተመክሮዋ ተነስታ Crowd mentality ወይም ስለጅምላ ስሪተ ህሊና ትገልኀለች፤ ፈላስፋው ዘርያዕቆብ “የልማድ እስረኞች ከመመርመር ይልቅ የሰሙትን ማመን የሚመርጡ ናቸው” ይላል፡፡ ጅምላ ስልተ ህሊና ከምክንያታዊና ሂሳዊ እውቀት ይልቅ ቡድኑን የሚገዙ እምነቶች የሚስተጋቡበት ስሪት ነው፡፡ ጅምላ መንገድም መዳረሻም ነው፡፡ ደራሲዋ የታሪኩን ጉዞ የደመደመችው በራሷ ላይ ያመጣችውን ለውጥ በመግለፅ ነው፡፡ ወደ ጅምላው ስሪተ ህሊና ለመደባለቅ መንገዱ ቀላል እና ግፊቱ ፈርጁ ብዙ ነው፡፡ የእድሜ እኩዮች ጫና፤ እውቅና የማግኘት ጉጉት፣ መጠጊያና መከታ ፍለጋ፤ የፕሮፓጋንዳ ሰለባ መሆን፤ በዘር መጓተት እና ሌሎችም፡፡

የመለያያው መንገድ ግን ቀላል አይደለም፡፡ ከጀማው ለመለየት የሚወስደው ጉዞ በአደጋ የታጠረ ነው፡፡ መገፋትን፣ መሳደድን፣ መገደልን፣ እንደ ከሀዲ መቆጠርን ያስከትላል፡፡ ከነዚህ አደጋዎች ውስጥ ራስን ቀና አድርጐ ለመውጣት ጠንካራ ሞራል፣ በራስ መተማመንና ሰፊና ጥልቅ የሆነ የእውቀት ስንቅን ይጠይቃል፡፡ የጅምላው አባላት ለጅምላው አላማ ከሚኖራቸው ታማኝነት ይልቅ ለመንጋው ያላቸው ተገዢት እጅግ የጠነከረ ነው፡፡ ትልቁ ቁምነገር አላማው ሳይሆን መለዮው ነው፡፡ ለዚህም ነው ከውጪ ጠላት ይልቅ መለዮውን ያጐድፋል ተብሎ የተጠረጠረውና በከሀዲነት የተፈረጀው የጌታቸው ማሩ እጣ ሞት የሆነው” ደራሲዋ በግል ነፃነትና በግለኝነት መሃል ያሰመረችው መስመር የደበዘዘውም ለዚህ ነው፡፡ ህይወት ያልተመለሱ ጥያቄዎችን ብቻ ሳይሆን ያልተጠየቁ ጥያቄዎችን አንግባ በህይወት መንገድ ረጅም ጉዞ ተጉዛ ትልቅ ማህበራዊ አንደምታ ያለው መፅሀፍ ይዛ መጥታለች፡፡ በዚህ ዘመን ለነበሩ ሌሎች ተዋናዮችም ይህን የመሰለ ድፍረት እንዲሰጣቸው እመኛለሁ፡፡ ያኔ ነው የአገራችን የፖለቲካ ዲስኮርስ ከዛ ትውልድ ጥላ ተላቆ እፎይታ የሚያገኘው፤ ይህ ትውልድ ካለፈው ትውልድ ተምሮ የወደፊት ራእዩን ከቂምና ከጥላቻ ውጪ መንደፍና እውን ማድረግ የሚችለው” ብለዋል - ምሁሩ፡፡

የፍልስፍና መምህሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ደግሞ መፅሀፉን በኤግዚስቴንሺያሊዝም መነፅር የተነተኑ የተራኪዋ አቀራረብ ከግል ህይወት ተመክሮዋ በመነሳት ሰፋ ወዳለው የአብዮትና ርዕዮተ ዓለም ዳሰሳ የሚሸጋገርና በመጨረሻ እስር ቤት ባለችበት ወቅት ግለሰቡ በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ወሳኝ ሚና እንዳለው በመደምደሟ ከኤግዚስቴንሺያሊስት ጋር ትዛመዳለች ብለዋል፡፡ መፅሃፉ የሰው ልጅ እጣ ፈንታ አንዴ ተበይኖ ያልተቀመጠና በምርጫ የሚወሰን መሆኑንና ምርጫው በፍርሃት እና በመርበድበድ የተሞላ እንደሆነም ያሳያል ብለዋል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ ታሪክ በእምነት የተጠቀጠቀ ነው ያሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤ ህይወት ጌታቸው፣ ማሩ መገደሉን ስትሰማ “የአሁኑን ሳይሆን የወደፊቱን ማየት ጀመርኩ፣ እውነት ነው ፓርቲው ልታገልልትና ልሞትለት የምፈልገው አይነት አልሆነም ነገር ግን ትግሉ ከሁሉም በላይ ነው” የሚል ሃሳብ እንደተፈጠረባት ጠቅሰዋል፡፡ የወጣቶቹ እምነትና ፅናት Indestructible እንደነበር ሲያስረዱም፤ “እነዛ ወጣቶች በሞት ጠርዝ ላይ የቆሙ ቢሆንም በአንድ ትልቅ ተስፋ የተሞሉ እና ጉዞ ላይ እንዳሉ ይታወቃቸው ነበር፡፡

በውስጣቸው ያለው ያለመበገርና ያለመሸርሸር ፅናት በፈታኝ ወቅት እንኳን አልከዳቸውም ብለዋል፡፡ አምበሳደር ታደለች ኃይለሚካኤል በበኩላቸው፤ ከደራሲዋ ጋር የነበራቸውን ቅርበትና አብረው የቆዩ መሆናቸውን በመጥቀስ መፅሀፉን በዛ መነሻ ቃኝተውታል፡፡ ንግግራቸውን ሲጀምሩም፤ “ይህ ውይይት በዶ/ር እሸቱ ጮሌ አዳራሽ በመከናወኑ ደስታዬ እጥፍ ድርብ ነው፡፡ ታዋቂው ምሁር እንደኛ እስረኛ ነበር፡፡ ስለመፅሀፍ መፃፍ ስናወራ ያጋጠመውን አጫውቶኝ ያውቃል፡፡ አራተኛ ክፍለ ጦር በጠዋት መጥተው የያዛችሁትን አስቀምጣችሁ ውጡ ተባሉ፡፡ ለአሰሳ የመጡ መስሎት በሁለት ደብተር የፃፈውን በጋቢው ስር ሸጉጦ ወደ መፀዳጃ ቤት በመሮጥ ቀድዶ ውሃ አፈሰሰበት፡፡ እንዳሰበው ሳይሆን የዛን እለት ጃንሜዳ ወስደው ፈቷቸው፡፡ በአራተኛ ቀን እቃቸውን ለመውሰድ ሲመለሱ እቃቸውን በሙሉ እንደተውት ሲያገኙት ቢናደድም እንደገና እንደማይፅፈው ሲያስብ በሀዘን ተዋጠ፡፡ ይህ የብዙ እስረኞች እጣ ነበር” ብለዋል፡፡ መፅሃፉ በእስር ዘመናችን እንወያይባቸው በነበሩና በማውቃቸው ጉዳዮች የተሞላ ቢሆንም ደጋግሜ አንብቤዋለሁ ያሉት አምባሳደሯ፤ “በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ አጥንትና ስጋ አልብሳ፣ እስትንፋስ ዘርታ ነው ያቀረበችው፡፡

ብርሃነ መስቀል እና ጌታቸው በህይወት እያሉ ሊያገናኙን ሞክረው ባይሳካላቸውም እነሱ ካለፉ በኋላ እስር ቤት ተገናኘን፡፡ እስር ቤት እያለሁ የተወለደችው ልጄ ትስስራችንን አጠናከረችው፤ ህፃኗ ከእስር ቤት እንድትወጣና ቤተሰብ እንድትቀላቀል የፈቀድኩትም ህይወት ስትፈታ ነው፡፡ ኑሮን ለመልመድና ለመረጋጋት… ያስቻለቻት እሷ ናት፡፡ መፅሃፉ ቀናነት የተመላው፣ ውይይትና መቻቻል እንዲመጣም ትልቅ አስተዋፅኦ የሚያበረክት ነው ብለዋል፡፡ አቶ ወልደልኡል ካሳ ከዩኒቨርሲቲ ወደ አሲምባ፣ ከአሲምባ ወደ አሜሪካን የሄዱ የኢህአፓ አባል ሲሆኑ፤ አሜሪካ በሄዱበት ወቅት ከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ ገብተው እንደነበር ተናግረዋል፡፡ ያስጨነቃቸውም እስር ቤት ያሉ ልጆች ጉዳይ ነበር፡፡ “የታሰሩት ምን ተስፋ ያደርጉ ይሆን? እስር ቤት ተሰብሮ ነፃ እንሆን ይሆን? ጓዶች ቀይ ባንዲራ ይዘው ይመጣሉ ብለው ይጠብቁን ይሆን?” የሚለው ያስጨንቀኝ ነበር ብለዋል፡፡ ከምሁራኑ የመፅሃፍ ዳሰሳ በኋላ በተካሄደው ውይይት የተለየዩ ጥያቄዎች የተነሱ ሲሆን የጅምላ ስሪት ህሊና (Crowd mentality) የሚለው ጉዳይ አብዛኞቹን የኢህአፓ አባላት ቱግ እንዲሉ አድርጓቸዋል፡፡ አንድ የቀድሞ የኢህአፓ አባል “መንጋ አልነበርንም፤ አውቀን ነው የገባንበት” ሲል ተቃውሞውን የገለፀ ሲሆን የዳሰሳው አቅራቢ ምሁር በሰጡት ምላሽ የጅምላ ስሪተ ህሊና የሚለው ከራሴ ያመጣሁት ሳይሆን የመፅሀፉ ደራሲ ከተጠቀመችበት በመነሳት ነው” ብለዋል፡፡

ያለፈው ትውልድ ጥያቄውንም መልሱንም የሚመዘው ከመፅሀፍት እና ከጥቅሶች ላይ ነው በሚል የቀረበው አስተያየትም የቀድሞ የኢህአፓ አባላት ቅንድብ ያስቆመ ነበር፡፡ የኮምፒዩተር ባለሙያውና የዳሰሳ አቅራቢ የነበሩት አቶ ወልደልዑል ሲመልሱ፤ “መፅሀፍ ላይ የመጣው ኩነኔ አይገባኝም፤ ታድያ ከየት ይምጣ ከመፅሀፍ እንጂ እንደድሮ ዶቃ አይመጣ” ያሉ ሲሆን ፕሮፌሰር ገብሩ ታረቀ በበኩላቸው፤ “ያ ትውልድ ኢትዮጵያን በደንብ ያውቃታል፡፡ የመሬት ላራሹ ጥያቄ የኢትዮጵያ የገበሬ ጥያቄ እንጂ ከመፅሀፍ ላይ የተወሰደ አይደለም” በማለት መልሰዋል፡፡ ይህ ትውልድ ከራሱ ጋር የሚታረቀው መቼ ነው በሚል ለቀረበው ጥያቄም ፕ/ር ገብሩ ታረቀ “የሃሳብ ልዩነት አለመግባባት ነበር እንጂ አልተጣላም” ብለዋል፡፡

በኢህአዴግ ዘመን የተተከለውን የሰማዕታት ሐውልት በተመለከተ ዶ/ር ዳኛቸው በሰጡት አስተያየት፤ “የኢህአዴግ ፍላጐት የወደቁትን የኢህአፓ ወጣቶችና መኢሶንንም ላለማስቀየም የማቻቻል ሁኔታ ያለበት ነው፡፡ ገና ሲገባ የመንግሥቱ ነዋይ ሀውልት ብሎ ነበር፤ አስራ አምስት ሰው ረሽኖ እንዴት ነው ሰማእት የሆነው?” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ “በአጭር የተቀጨ የረጅም ጉዞ፤ ታሪክ” በሚለው የመኢሶን መፅሃፍ ላይ “እኛን ለምንድን ነው ከፊውዳሎቹ ጋር እየጨመራችሁ የምትገድሉን” በሚል ለደርግ የፃፉት ደብዳቤ መኖሩን የጠቀሱት ዶ/ር ዳኛቸው “ፊውዳል መግደል ስፖርት ነው” ሲሉ ታዳሚውን አስፈግገዋል፡፡ ሌሎችም ጥያቄዎች ተነስተው ምላሽና ውይይት የተደረገባቸው ቢሆንም የቦታ ውሱንነት ከዚህ በላይ እንዳልቀጥል አስገድዶኛል፡፡

ኤዞፕ ከፃፈልን ተረቶች መካከል አንዱ እንዲህ ይላል፡- ከዕለታት አንድ ቀን ብዙ ጥንቸሎች ተሰብስበው ይመካከራሉ፡፡
አንደኛ ጥንቸል - “ጐበዝ እኔ ኑሮ መሮኛል፡፡ በየአቅጣጫው ጠላት እኛ ላይ እያነጣጠረ መግቢያ መውጪያ አሳጣን፡፡ በየጊዜው መደበቅ፣ ከሰው መሸሽ በጣም ነው ያስጠላኝ” አለች፡፡
ሁለተኛዋ ጥንቸል - “እኔ ደሞ በጣም የሰለቸኝ ከውሻ መሸሽ፡፡ ድንገት ብቅ ካለ እኮ ካለእኛ ጠላት ያለው አይመስለውም፤ ክፉኛ ያባርረናል፣ ያሳድደናል” አለች፡፡
ሦስተኛዋ ጥንቸል - “እኔ ደግሞ እንደኛው የዱር አራዊት የሆኑ አውሬዎች ናቸው እረፍት የነሱኝ፡፡ ምን እንደሚበጀኝ እንጃ” አለች፡፡
እንዲህ እንዲህ እያሉ ሁሉም ብሶታቸውን ተነጋገሩ፡፡ በመጨረሻም፤ “እንዲህ ስቃይ ከሚበዛብንና በየቀኑ የሰውም፤ የውሻም፣ የአዕዋፍም፣ የዱር አውሬም ምግብ ከምንሆንና ምንም አቅም የሌለን ፍጡራን ሆነን ከምንቀር በቃ ውሃ ውስጥ ሰጥመን ብንሞት ይሻለናል” አሉ፡፡
ከዚያም ሁሉም በአንድ ድምጽ “አሰቃቂውን ህይወታችንን ላንዴም ለሁሌም እንገላገለው” በሚል በአቅራቢያቸው በሚገኝ ሰፊ ኩሬ ውስጥ ሰምጠው ሊሞቱ ሩጫቸውን ቀጠሉ፡፡
በኩሬው ዳርቻ ብዙ እንቁራሪቶች ተቀምጠው ፀሐይ ይሞቃሉ፡፡ እንቁራሪቶቹ በርካታ ጥንቸሎች ወደነሱ እየሮጡ ሲመጡ ተመለከቱና፤
“ጐበዝ፣ ጥንቸሎች ሊዘምቱብን ወደኛ እየተንደረደሩ ነው፡፡ በጊዜ ብናመልጥ ይሻለናል” ተባባሉ፡፡
ወዲያው ከኩሬው ዳርቻ ወደ ውሃው ጡብ ጡብ እያሉ በጣም ወደታች ጠልቀው ተደበቁ፡፡
ይሄኔ ከጥንቸሎቹ መካከል ብልሁ፤
“ቆይ ቆይ ቆይ” ብሎ ሁሉንም ጥንቸሎች አስቆማቸው፡፡
ሁሉም በርጋታ እሱን ለማዳመጥ ዞሩ፡፡
ጥንቸሉም፤
“አያችሁ፤ ራሳችንን ማጥፋት የለብንም፡፡ ልብ ብላችሁ ካስተዋላችሁ፣ እነዚህ እንቁራሪቶች እኛን ፈርተው ውሃ ውስጥ ገቡ፡፡ እኛንም የሚፈራን አለ ማለት ነው፡፡ እኛ ሌሎችን ፈርተን ራሳችንን እናጥፋ አልን፡፡ በዓለም ላይ ግን ሁሉም የሚፈራው አለው፡፡ ስለዚህ ሌሎች ያጠፉናል ብለን መፍራት የለብንም፡፡ እኛም የምናጠፋው አለና” ብሎ ሁሉንም መለሳቸው፡፡
                                                        ***
ተስፋ ቆርጦ፣ ህይወት አበቃለት ከማለት በፊት ከእኔ የከፋም አለ ብሎ ማሰብ ትልቅ መላ ነው፡፡ ሁሉም የላይና የበታች አለው፡፡ የህይወት ሰልፍ ይህን ልብ እንድንል ያስገድደናል፡፡ ከጅምላ ውሳኔ መጠንቀቅ ደግ ነው፡፡ የተሻለው ካልተሻለው ጋር መክሮ ዘክሮ ካልተጓዘ አገር የጥቂቶች ብቻ ትሆንና ኑሮ በምሬት የተሞላ ይሆናል፡፡
የሀገራችን አሳሳቢ ጉዳዮች አያሌ ናቸው፡፡ በለውጥ ጐዳና ላይ አሳሳቢ ጉዳዮች ከበዙ ለውጡን ማዥጐርጐራቸው አይቀሬ ነው፡፡ ነባራዊ ሁኔታው በፈቀደው የሚከሰቱትን እንቅፋቶች ሁሉ ግን “ፀረ ልማት፣ ፀረ ዕድገት፣ ኪራይ ሰብሳቢነት” ወዘተ ብሎ ከመፈረጅ መጠንቀቅ ይገባል፡፡ ሩጫችን በፈጠነ መጠን “ችኩል ጅብ ቀንድ ይነክሳል”ን አለመርሳት ነው፡፡
የኦዲት ሪፖርትን በጥንቃቄ ማየት ተገቢ ነው፡፡ በመጨረሻው ሰዓት ምንጣፍ ለመግዛት ከመሯሯጥ አስቀድሞ በቅጡ ማቀድ ይሻላል፡፡ ፈሰሱ ሲበዛ ሜዳ የፈሰሰ እቅድ መኖሩን እንደሚያሳይ አንዘንጋ፡፡ በስንት ቢፒ አር፣ በስንት ግምገማ ተደግፎ ከእቅድ በላይ የተባለለት አፈፃፀም ኋላ በፈሰስ ሲመነዘር “አብዮቱ ግቡን መታ” እንደማያሰኝ እንወቅ፡፡ ሌላው አሳሳቢ ነገር የተጠርጣሪዎች መብዛት ነው፡፡ በቤት፣ በመሬት፣ በኤሌትሪክ ዕቃዎች፣ በጉምሩክ፣ በአገር ውስጥ ገቢ፣ ወዘተ እየጨመሩ ያሉ ተጠርጣሪዎች የሀገራችንን የሙስና ብዛትና ከፍተኛነት እየጠቆሙ ነው፡፡
ለዚህ ለምን አልተዘጋጀንም? ሊሠሩ የታሰቡ ነገሮች ምን መዘዝ እንደሚያመጡ ከወዲሁ ማስተዋል እንደምን ያቅታል፤ ጥፋተኝነታቸው የተነቃ ብዙ ሥራ ሲሰራ ብዙ እጅ ገንዘብ ውስጥ እንደሚገባ ጥርጥር የለውም፡፡ ሆኖም ባለሥልጣኖችሽ ሲነቃባቸው በቦሌ ሲወጡ ዝም ብሎ ማየት ተፈልጐ ነው ሳይታወቅ? ሄደው ቀሩ የሚባሉ ሰዎች ነገር ተድበስብሶ የሚታለፈው “ተገላገልነው” በሚል ስሜት ይሆንን?
ሙስና ከተወራ ብዙ ጊዜ ያስቆጠረ፣ ግባራዊ ገፁ ዛሬ የታየ ነው፡፡ ፀረ -ሙስና እርምጃው አለቃና ምንዝር ሳይል የሁሉንም በር ማንኳኳት ይገባዋል፡፡
ገና የሚንኳኩ በሮች ጀርባ የሚገኙ ሙሰኞች፤ “ግጥም ሞልቶን ነበር በስልቻ ሙሉ
አንዷ ጠብ ብትል ሁሉም ዝርግፍ አሉ” ዓይነት እንደሚሆን የሚያቅ ያቀዋል፡፡
ከሀገርና ከህዝብ ጥቅም አኳያ መታየት ያለባቸው፣ ግን እንደዘበት እየታዩ የሚታለፉ አያሌ ጉዳዮች አሉ፡፡ በጥንቃቄ ጊዜ ወስዶ ከልብ ሙስናን ፈልፍሎ ማውጣት ይበል የሚባል ቢሆንም፤ አላግባብ ጊዜ መስጠትም የዚያኑ ያህል ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ ጊዜው በረዘመ ቁጥር የወንጀሎች መደራረብ፣ የህዝብና የሀገር ጉዳት የዚያኑ ያህል ያበዛልና!
የትኩረት አቅጣጫ በአንድ ጉዳይ ዙሪያ ብቻ ሲሆን ሌሎች የተበላሹ ነገሮችን እንዳናይ ስለሚያደርግ ዕይታችን ይጠብብናል፡፡ ስለሆነም ጉዳዮች ሁሉ በአገር ዙሪያ ሲጠነጠኑ የራሳቸው ተያያዥ ድርና ማግ ይኖራቸዋልና ዘርፎቹን ሁሉ በቆቅ ዐይን አጣምሮ ማየት ይገባል፡፡ አለበለዚያ “ዘዴ የሌለው ወፍ ቅርንጫፍ በሌለው ዛፍ ላይ ያርፋል” እንደተባለው ይሆናል፡፡

በሻሸመኔ ከተማ እና አካባቢዋ ኪነጥበባት አፍቃሪዎች የተቋቋመው “ከአድማስ ፊት” የኪነጥበብ ማህበር 43ኛ ወርሃዊ ዝግጅቱን እና የተመሰረበትን አምስተኛ አመት እንደሚያከብር አስታወቀ፡፡ ነገ ከሰዓት በኋላ በከተማዋ ሁለገብ አዳራሽ በማህበሩ አባላት እና የአካባቢው ማህበረሰብ በተጨማሪ አርቲስት ሜሮን ጌትነት እና አርቲስት ዘላለም ኩራባቸው በክብር እንግድነት ይገኛሉ፡፡ በዝግጅቱ የማህበሩን የአምስት ዓመት ጉዞ የሚያሳይ ዘጋቢ ፊልም የሚቀርብ ሲሆን ሽልማት የሚያሰጥ የግጥም ውድድርም ይኖራል፡፡