Administrator

Administrator

- ከመደበኛው 218 ሚ ዶላር መሸጫ ዋጋቸው በግማሽ ቅናሽ እንደሚሸጡ ይጠበቃል
 
ቦይንግ ኩባንያ ቀደም ባለ ሞዴል ካመረታቸው የመጨረሻዎቹ ቦይንግ 787 - 8 ድሪምላይነር አውሮፕላኖችን ውስጥ ስምንቱን ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ለመሸጥ ድርድር እያደረገ መሆኑን ብሉምበርግ ኒውስ ዘገበ፡፡
ኩባንያው አውሮፕላኖቹን ለእያንዳንዳቸው ከተመነላቸው የ218 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር መደበኛ የመሸጫ ዋጋ ላይ በግማሽ ያህል ቅናሽ አድርጎ ይሸጣቸዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፣ አውሮፕላኖቹን ለመግዛት ከኩባንያው ጋር ድርድር ከጀመሩት አየር መንገዶች መካከል፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተሸለ ድርድር በማድረግ ወደ መጨረሻው ምዕራፍ መዳረሱን አስታውቋል፡፡
ከዚህ ቀደም ተመሳሳይ አውሮፕላኖችን ከኩባንያው የገዙ ደንበኞች በዚህኛው ግዢ ላይ ለመሳተፍ አለመፈለጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ለዚህም በምክንያትነት የተጠቀሰው የአውሮፕላኖቹ ክብደት በጣም ከፍተኛ ከመሆኑን ጋር ተያይዞ የሚሸፍኑት የበረራ ክልል ውስን መሆኑ እንደሆነ ገልጧል፡፡
ቦይንግ በሚያመርታቸው ድሪምላይነር አውሮፐሮላኖች ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው የሙከራ በረራዎች፣ የተለያዩ ቴክኒካዊና የዲዛይን ችግሮች እንዳሉባቸው መረጋገጡን ተከትሎ፣ ቦይንግ ኩባንያ በአውሮፕላኖቹ ዲዛይንና አሰራር ላይ ለውጥ ለማድረግ ተገድዶ እንደነበርም ዘገባው ጨምሮ አስታውሷል፡፡


ለብዙ የአዲስ አበባ ነዋሪ አማራጭ እንደሆኑ በጥናት ሪፖርት ተገልጿል
በአዲስ አበባ የሚገኙ የጤና ተቋማት የሚሰጡት አገልግሎት በአመዛኙ በመንግስት ስር ካሉት ተቋማት የተሻለ ቢሆንም፣ ግማሽ ያህሉ ገና ከደረጃ በታች እንደሆኑ ተገለፀ፡፡ በመንግስትና በግል ጤና ተቋማት ያለው የክፍያ ልዩነት ከአራት እስከ አርባ እጥፍ ይደርሳል፡፡
የግል ህክምና ተቋማት በአዲስ አበባ የሚሰጡት አገልግሎት ላይ ጥናት የተካሄደው በ“ማህበራዊ ጥናት መድረክ” አማካኝነት ሲሆን፣ ትናንት ይፋ የሆነው የጥናት ሪፖርት ከአገልግሎት ጥራት በተጨማሪ የክፍያ መጠኖችንም በማነፃፀር ዳስሷል፡፡ የግል የጤና ተቋማቱ ከመንግስት የጤና ተቋማት ጋር ሲነጻጸሩ የተሻለ ደረጃ ላይ እንደሚገኙ የጥናት ሪፖርቱ ጠቅሶ፤ ይህ ማለት ግን የአገልግሎት ደረጃን ያሟላሉ ማለት እንዳልሆነ ገልጿል፡፡
አዳዲስ ሆስፒታሎችና ክሊኒኮች የስራ ፈቃድ የሚያገኙት በቅርቡ እንደ አዲስ በተዘጋጀው የጥራትና ደረጃ መስፈርት እንደሆነ በጥናቱ የተገለፀ ሲሆን በመስፈርቱ መሰረትም 34 የግል ሆስፒታሎች ላይ ዝርዝር ጥናት ተካሂዷል፡፡ የጥናቱ ሪፖርት እንደሚገልፀው፤ የጥራት ደረጃ መስፈርቶችን በአግባቡ ያሟላሉ ሆስፒታሎች ከሁለት አይበልጡም፡፡ 17 ያህል ሆስፒታሎች (ማለትም 50% ያህሉ) በመካከለኛ ሁኔታ ላይ እንደሆኑና ማሻሻያ እንደሚያስፈልጋቸው ጥናቱ ገልፆ፤ 15 ያህል ሆስፒታሎች ግን በዝቅተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙ ናቸው ብሏል፡፡
 ባለፉት አምስት አመታት የግል የህክምና ተቋማት እድገት ማሳየታቸውን ያመለከተው ጥናቱ፤ 42 በመቶ ለሚሆነው የከተማዋ ነዋሪ አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነና አገልግሎታቸው ለከተማው ሀብታሞች ብቻ ሳይሆን በዝቅተኛ ገቢ ለሚተዳደሩ ነዋሪዎችም ጭምር እንደሚደርስ ገልጿል፡፡
ጥናቱ የአገልግሎት ክፍያን በተመለከተ የግል የጤና ተቋማት ከሚሰጡት የአገልግሎት ጥራት ጋር ያልተመጣጠነ ከፍተኛ ክፍያ እንደሚጠይቁ አመልክቷል፡፡ በተለይ ከመንግስት የጤና ተቋማት ጋር ሲነጻጸር ክፍያው የትየለሌ መሆኑን የጠቆመው ጥናቱ፤ ለምሳሌ በኤክስሬይ የዋጋ ልዩነቱ 40 እጥፍ ገደማ ሲሆን በወሊድ አገልግሎትም በተመሳሳይ የክፍያ ልዩነቱ ወደ 40 እጥፍ ይጠጋል፡፡
በእርግጥ የግልና የመንግስት የጤና ተቋማት ክፍያ ተቀራራቢ ይሆናል ተብሎ የሚጠበቅ አይደለም፡፡ የመንግስት የጤና ተቋማት ስራቸውን የሚያከናውኑት ከክፍያ በሚያገኙት ገንዘብ ብቻ ሳይሆን ከታክስ ከሚሰበሰብ ገንዘብና ከውጭ ከሚመጣ እርዳታ በጀት እተመአበላቸው እንደሆነ ይታወቃል፡፡  

የአገልግሎት አይነት    የግል ሆስፒታል ክፍያ በአማካይ    የጤና ጣቢያ ክፍያ በአማካይ
የካርድ                        100           5
ኤክስሬይ                      180          35
በምጥ ማዋለድ               1940           50
በኦፕራሲዮን ማዋለድ         3550         140
የወንዶች ግርዛት                520          35
ትርፍ አንጀት ቀዶ ህክምና    2850          120
የአልጋ አንደኛ ደረጃ            850          90
የአልጋ ሶስተኛ ደረጃ           350          20

በግል የጤና ተቋማት ውስጥ እንደ ችግር ከተጠቀሱት መካከል ለባለሙያዎች ማበረታቻና ተከታታይ ስልጠና አለመሰጠቱ፣ በህክምና ዘርፍ የሚሰማሩ ባለሃብቶች የመሥሪያ መሬት ለማግኘት መቸገራቸው፣ የባለሙያዎች እጥረት፣ የብድር እጦት፣ የጉምሩክ ቢሮክራሲና የውጭ ምንዛሬ እጥረት ይገኙባቸዋል፡፡  





119ኛውን የአድዋን የድል በዓል ለማክበር ጥር 15 ቀን 2007 ወደ አድዋ የእግር ጉዞ የጀመሩት ስድስቱ ተጓዦች ዛሬ “እንዳአባ ገሪማ” የሚባል ቦታ በሰላም መድረሳቸው ታውቋል፡፡
ሲሳይ ወንድሙ፤ መኮንን ሞገሴ፣ ጽዮን ወልዱ፣ ግደይ ስዩም፣ ታምሩ አሸናፊና አዳነ ከማል የተሰኙት እኒህ ተጓዣች እስካሁን በጉዟቸው ምንም ችግር እንዳልገጠማቸውና ሴቷም ተጓዥ ብትሆን በጉዞዋ ከወንዶቹ እኩል መቀጠል እንደቻለች ምንጮች ጠቅሰዋል፡፡ በነገው እለት አድዋ ገብተው የሶሎዳን ተራራ ግማሽ ያህሉን ወጥተው ያድራሉ የተባሉት ተጓዦቹ ሰኞ በማለዳ ተነስተው ወደ ሶሎዳ ተራራ ጫፍ በመውጣት ባንዲራ ከሰቀሉ በኋላ ተራራውን ወርደው አድዋ ከተማ ውስጥ የሚከበረውን የአድዋ 119ኛ በዓል እንደሚታደሙ ታውቋል፡፡ አምና 118ኛውን የአድዋ በዓል ለመታደም አምስት ተጓዦች ለ40 ቀናት በእግራቸው ተጉዘው አድዋ መድረሳቸው የሚታወስ ሲሆን የዘንድሮውን ጉዞ ሴት ተጓዥ መቀላቀሏ ለየት ያደርገዋል ተብሏል፡፡

“ ሲአይኤና ሞሳድ አይሲስ እና ቦኮ ሃራምን ይደግፋሉ” አልበሽር
“ አይሲስን ለመዋጋት የጦር መሳሪያ ማዕቀብ ይነሳልኝ” ሊቢያ

ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ አይሲስ የተባለውን እስላማዊ ቡድን ጨምሮ ሌሎች ጽንፈኛ ቡድኖች በተለያዩ አገራት የሚፈጽሙትን የሽብር ተግባር ለመግታት የአለም አገራት ተባብረው እንዲሰሩ ጥሪ አቀረቡ፡፡
ኒውዮርክ ታይምስ እንደዘገበው፤ የ60 አገራት ተወካዮች በተገኙበትና በዋሽንግተን በተካሄደው በጽንፈኝነት ላይ ያተኮረ ስብሰባ ላይ ባለፈው ረቡዕ ንግግር ያደረጉት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፣ የአለም አገራት መንግስታት የእስላማዊ መንግስት መርህን አንግበው የሚንቀሳቀሱ ጽንፈኛ ቡድኖችን በተባበረ ክንድ መመከት ይገባቸዋል ብለዋል፡፡
የሱኒ ታጣቂ ቡድኖችን አስተሳሰብ ማዳከምና እንቅስቃሴያቸውን መግታት የትውልድ ፈተና ሆኖ ቆይቷል ያሉት ኦባማ፤ ቡድኖቹን በስኬታማ መንገድ ከእንቅስቃሴያቸው መግታት የሚቻለው በእስልምና እምነት ተከታዮች፣ በመንግስታት፣ በሃይማኖት መሪዎች፣ በማህበረሰቦችና በመሳሰሉት የተቀናጀ ርብርብ ብቻ ነው ብለዋል፡፡
ኦባማ አሜሪካ ጦርነት ውስጥ የገባችው ከእስልምና ጋር ሳይሆን የእስልምናን አስተምህሮት ከሚያዛቡ የጥፋት ሃይሎች ጋር ነው ማለታቸውን የዘገበው ሮይተርስ፤ እስላማዊ ታጣቂ ቡድኖች ምዕራባውያን በእስልምና ላይ ጦርነት አውጀዋል በማለት የሚያቀርቡትን ውንጀላ መሰረተ ቢስ ነው ሲሉ ማጣጣላቸውን ጠቁሟል፡፡ አሜሪካም እና ሌሎች ምዕራባውያን አገራት እስልምናን ለመጨቆንና በእምነቱ ላይ ጥላቻ እንዲስፋፋ ለማድረግ ይሰራሉ በሚል ከአንዳንድ አክራሪ ቡድኖች የሚሰነዘረውን ውንጀላ መሰረተ ቢስነት ለማረጋገጥ የእስልምና መሪዎች ጠንክረው መስራት ይገባቸዋል ብለዋል ኦባማ፡፡
አለማችን ከእስልምና አስተምህሮት ጋር ጸብ የላትም፣ አይሲስ እና አልቃይዳን የመሳሰሉ ቡድኖች ግን የሃይማኖት መሪዎች ሳይሆኑ በሃይማኖት ሽፋን ጥፋት የሚፈጽሙ  ሽብርተኞች ስለሆኑ እንታገላቸዋለን ማለታቸውንም ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በጠራው አስቸኳይ ስብሰባ ላይ የተሳተፈችው ሊቢያ በበኩሏ፤ አይሲስን እና ሌሎች ጽንፈኛ ታጣቂ ቡድኖችን በአግባቡ ለመመከት እንድትችል፣ የተመድ የጸጥታ ምክር ቤት የጣለባትን የጦር መሳሪያ ግዢ ማዕቀብ እንዲያነሳላት ጠይቃለች፡፡ ማዕቀቡ ከአራት አመታት በፊት እንደተጣለባት ያስታወሱት የሊቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሃመድ አል ዳሪ፤ በአገሪቱ ያለው የጸጥታ ሁኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን ጠቅሰው  የአገሪቱ ታጣቂ ቡድኖች ከአይሲስ ጋር ተባብረው የባሰ ጥፋት ሊፈጽሙ እንደሚችሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡ ለዚህም በቂ የጦር መሳሪያ መያዟ ወሳኝ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡
በቅርቡ  21 ዜጎቿ በአይሲስ ታጣቂዎች ተቀልተው የተገደሉባትና በቡድኑ ላይ የአየር  ላይ የአጸፋ ምላሽ የሰነዘረችው ግብጽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሽኩርም፣ በሊቢያ ያለው የጽንፈኛ ቡድኖች እንቅስቃሴ ከፍተኛ ችግር የሚፈጥር በመሆኑ፣ በአገሪቱ ላይ የተጣለው የጦር መሳሪያ ግዢ ማዕቀብ መነሳቱ ጠቃሚ እንደሆነ ጠቁመው  ሃሳቡን እንደሚደግፉት ገልጸዋል፡፡
የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኦማር ሃሰን አልበሽር በበኩላቸው፤ የአሜሪካና የእስራኤል የስለላ ተቋማት ሲአይኤና ሞሳድ ለአሸባሪዎቹ እስላማዊ ቡድኖች አይሲስ እና ቦኮ ሃራም በስውር ድጋፍ ይሰጣሉ ሲሉ መወንጀላቸውን  ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
አይሲስ ከቀናት በፊት በሊቢያ የኮፕቲክ ክርስቲያን አማኝ የሆኑ 21 ግብጻያውንን በመቅላት መግደሉን ተከትሎ ፕሬዚዳንቱ ከዩሮኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለመጠይቅ እንዳሉት፣ ይህን መሰሉን የጭካኔ ተግባር የሚፈጽም የእስልምና እምነት ተከታይ የለም፣ ይልቁንም ለዚህ ቡድን የጭካኔ ተግባር ድጋፍ የሚያደርጉት  ሁለቱ የስለላ ተቋማት ናቸው ብለዋል፡፡
መሰል የአሸባሪ ቡድኖችን ለመደምሰስ ሲባል የሚፈጸም ሃይል የተሞላበት እርምጃም ቡድኖቹ የከፋ የአጸፋ ምላሽ እንዲሰጡ የሚገፋፋ ሊሆን ይችላል ሲሉም አልበሽር አስጠንቅቀዋል፡፡ የሊባኖሱ ሂዝቦላህ መሪም ሲአይኤ እና ሞሳድ ከጽንፈኞቹ ቡድኖች በስተጀርባ ድጋፍ ያደርጋሉ ሲሉ መወንጀላቸውን አሶሼትድ ፕሬስ መዘገቡ ተጠቁሟል፡፡
የቱርኳ አንካራ ከተማ ከንቲባ ሜሊህ ጎኬክ በበኩላቸው፤ ሞሳድ በፓሪሱ የቻርሌ ሄቢዶ ጥቃት ውስጥ ተሳትፎ ነበረው ሲሉ መናገራቸውን ባለፈው ጥር ወር ለንባብ የበቃው ፋይናንሽያል ታይምስ ማስነበቡንም ዘገባው አስታውሷል፡፡ ከንቲባው በወቅቱ እንዳሉት፤ እስራኤል በእስልምና ሃይማኖት ላይ ጥላቻ እንዲነግስ በማሰብ ጥቃቱን በማቀነባበር ተሳትፎ አድርጋለች፡፡ በተደጋጋሚ አሰቃቂ ግድያዎችን መፈጸሙን አጠናክሮ የቀጠለው አይሲስ በያዝነው ሳምንትም፣ በ21 ግብጻውያን ላይ ከፈጸመው አንገት የመቅላት ግድያ በተጨማሪ በኢራቋ ከተማ አል ባግዳዲ 45 ሰዎችን በእሳት አቃጥሎ መግደሉ ተዘግቧል፡፡


በታሪክ ከፍተኛው ዝርፊያ ነው ተብሏል

የሩስያ፣ ዩክሬን፣ቻይና እና የአውሮፓ አገራት ዜግነት ያላቸው የኢንተርኔት አጭበርባሪዎች በተለያዩ የአለም አገራት በሚገኙ ከ100 በላይ ባንኮች ላይ በፈጸሙት ስርቆት በድምሩ 1 ቢሊዮን ዶላር መዝረፋቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ በኢንተርኔት ከተፈጸሙ መሰል የባንክ ዝርፊያዎች ከፍተኛው ገንዘብ የተሰረቀበት ነው የተባለው ይህ ዘረፋ፣ አጭበርባሪዎቹ በባንኮቹ ኮምፒውተሮች ላይ በጫኗቸው መረጃን የሚሰርቁ ሶፍትዌሮች አማካይነት የተከናወነ ሲሆን፣ በባንኮቹ ውስጥ የነበረው ገንዘብ አጭበርባሪዎቹ ወደከፈቱት የሃሰት አካውንት እንዲዘዋወር ተደርጓል፡፡
ካስፔርስኪ የተባለውን አለማቀፍ የኢንተርኔት ደህንነት ተቋም ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ አጭበርባሪዎቹ ከእያንዳንዱ ባንክ ከ2.5 ሚሊዮን እስከ 10 ሚሊዮን ዶላር ዘርፈዋል፡፡ እስከዛሬ ከተከናወኑት የባንክ ዘረፋዎች ሁሉ ፍጹም ውጤታማ እንደሆነ በተነገረለት በዚህ የኢንተርኔት ማጭበርበር ተግባር ሰለባ  የሆኑት ባንኮች ስም በይፋ ባይገለጽም፣ ባንኮቹ አሜሪካን ጨምሮ በተለያዩ 25 የአለማችን አገራት ውስጥ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡
ዝርፊያው አሁንም እንደቀጠለ የጠቆመው ኩባንያው፣ ባንኮች የኮምፒውተር ሲስተሞቻቸው በዚህ የአጭበርባሪዎች ሶፍትዌር እንዳልተጠቁ ማረጋገጥና አስፈላጊውን ፍተሻና ጥንቃቄ ማድረግ ይገባቸዋል ብሏል፡፡

*200ሺ ሰዎች አመልክተው 100 ለመጨረሻው ዙር አልፈዋል
*4 ሴቶችና 1 ወንድ በማርስ የሪያሊቲ ሾው ፕሮግራም ይሳተፋሉ

ኤድሞል በተባለው ኩባንያ የሚዘጋጀውና አምስት ተፎካካሪዎችን የሚያካትተው የ2024  የቢግ ብራዘር የቴሌቪዥን ሪያሊቲ ሾው ፕሮግራም በማርስ ፕላኔት ላይ ሊዘጋጅ ነው፡፡
ኩባንያው በድረገጹ ላይ ባወጣው  መረጃ እንደጠቆመው ፣ ማርስ ዋን በተሰኘው ፕሮጀክት አማካይነት ከ9 አመታት በኋላ ወደ ማርስ  ሊደረግ የታቀደው ጉዞ አካል በሆነው የቢግ ብራዘር ላይ ለመሳተፍ 200 ሺህ ሰዎች ያመለከቱ ሲሆን  ለመጨረሻው ዙር ያለፉት 100 ሰዎች ተለይተዋል፡፡
ከ100ዎቹ እጩ ተፎካካሪዎች መካከል 39 አሜሪካውያን፣ 31 አውሮፓውያን፣ 16 እስያውያን፣ 7 አፍሪካውያን እና 7 አውስትራሊያውያን እንደሆኑ ታውቋል፡፡ በማርስ ላይ በሚከናወነው የ2024 የቢግ ብራዘር ሾው ላይ የሚሳተፉት አራት ሴት እና አንድ ወንድ ተፎካካሪዎች እንደሚሆኑ የተገለጸ ሲሆን  ጉዞው 3.6 ቢሊዮን ፓውንድ እንደሚፈጅ  ታውቋል፡፡ በማርስ ላይ የሚከናወነው ቢግ ብራዘር  በየሁለት አመቱ እንደሚዘጋጅ የጠቆመው መረጃው፣ ወደ ማርስ የሚደረገው ጉዞ 200 ቀናትን ያህል እንደሚፈጅም አስታውቋል፡፡

Saturday, 21 February 2015 13:58

“ሽርሽር” ገበያ ላይ ዋሉ

 በጀሚል አክበር የተፃፈው “ሽርሽር” የተሰኘ የአጭር ልብወለዶች ስብስብ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡ በመጽሃፉ ውስጥ 18 ያህል ታሪኮች የተካተቱ ሲሆን በ28 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡  ፀሀፊው ከዚህ ቀደም “ካገር ፍቅር እስከ አዲሳባ” የተሰኘ በእስረኞች ታሪክ ላይ የተመሰረተ መፅሀፍ ለንባብ ማብቃቱ የሚታወስ ሲሆን ታሪኩም በሸገር ሬዲዮ እንደተተረከ ደራሲው አውስቷል፡፡

Saturday, 21 February 2015 13:39

የ100ሺ ብር ግጥም

ዳሽን ቢራ አክሲዮን ማኅበር የመጀመሪያውን ዓመት “ዳሽን የኪነ ጥበባት ሽልማት” ጥር 24 ቀን 2007 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ ማካሄዱ ይታወቃል፡፡ በዚሁ ወቅት በስነ - ግጥም ዘርፍ ለውድድር ከቀረቡ 157 ግጥሞች መካከል 1ኛ በመውጣት 100.000 ብር ሽልማት አሸናፊ የሆነው የሰለሞን ሞገስ ግጥም ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡

ሕልሞቻችሁን ፈልጉ

በንስር ጉልበቶቻችሁ በጉንዳን ጽኑ ሥርዓት፣
በቆሰለ ጅብ ተጋድሎ በሴቴ ሸረሪት ብልሃት፣
በረቂቅ የጣዝማ ጥበብ በአናብስት የወኔ ሙላት፣
ሕልሞቻችሁን ፈልጉ እስከ ከፍታችሁ አናት፡፡
    በየብስና በባህሩ፣
    በበረሃና በዱሩ፣
    በህዋው ላይ በጠፈሩ፣
    መቼም ይሁን የትም ሥፍራ፣
    በመሬት እንደ አደን ውሻ፤ በሰማይ እንደጆቢራ፣
የሰው ልጆች ሆይ ተነሱ!  
ያንቀላፋውን ማንነት ፍጥረታችሁን ቀስቅሱ፣
መክሊታችሁን ፈልጉ ሕልሞቻችሁን አስሱ፡፡
    የየመንገዱ ትብታብ ድር ክንፎቻችሁን ያሰረ፣
    እምቅ ወኔን የፈተተ የእልህ ጉልበት የጨመረ፣
    መገፋት፣ መውደቅ፣ መታሸት፣ መወቀጥን ያስተማረ፣
    እንኳንስ ኖረ ጨለማ እንኳን እሾህ ተፈጠረ፡፡
    አውራ ዶሮ እንኳ በአቅሙ አምፆ ባይሆን በቁጣ፣
    መች ያየው ነበር ዓለሙን ቅርፊቱን ሰብሮ ባይወጣ?
    ወትሮስ ጨለማ ከምንጩ፣ ፅልመት ፊቱን ባይፈጠር፣
    ብራው ቀን ጨለማ አልነበር?
    ወርቅም ዘመን እስኪያነሳው፣
    አፈር ላይ ነው የሚተኛው፡፡
    እና…
የውስጣችሁን ዝማሬ የነፍሶቻችሁን ቅኝት፣
የልባችሁን ተመስጦ የሕልሞቻችሁን ምሪት፣
የተፈጥሯችሁን ጥሪ የመሻታችሁን ትዕይንት፣
    የናፍቆት በገናችሁን የተስፋችሁን ነጋሪት፤
    የልባችሁን ውብ ቋንቋ፣
    የውስጣችሁን ሙዚቃ፤
    ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ አልሙ፣
    በእውቀት፣ በጥበብ ማማ ላይ  በኩራት፣ በክብር ቁሙ፡፡
        እንደ ሰንደቅ ዓላማ ክብር በከፍታ እንድታርጉ፣
        መደንዘዝ የሰወረውን መክሊታችሁን ፈልጉ፡፡
        በራስ ለራስ ዋጋ ማነስ ቅስማችሁን አታድቅቁ፣
        በተስፋ ማጣት ስብራት ስፍራችሁን አትልቀቁ፣
        ከአፈር፣ ከጭቃ መሃል ነው የሚገኘው እፁብ ወርቁ፡፡
        ጋንም እንደጥራጊ የትም መበተን ምን ይሆን?
        ዋርካ ሲቻል ሰንሰል መሆን፡፡
        በሉ እንጂ ጃል!            
በልባችሁ ላይ ያለውን ጭሱን፣ ጭጋጉን ጥረጉ፣
የነፍሳችሁን ብርሃን ሕልሞቻችሁን ፈልጉ፡፡
          ለአደን፣ ለግዳይ ተነሱ!
        እምቅ ብቃትን አስሱ!!
    የኑሮ ውጣ ውረዱ ቁልቁለትና ዳገቱ፣
    የብቸኝነት በረሃው ራብ፣ ጥምና እንግልቱ፣
    አሻጋሪ የለሽ ባህር የቀን ጨለማው ብርታቱ፣
    የአማሳኙ፣ የአዋሻኪው፣ የሸንጋዩ፣ የጽልመቱ፤
    ሕልም ካለ ይታለፋል!
ጉም፣ ጭጋጉ ይገፈፋል፡፡
ምሬት ገ’ተህ፤ እንባ አቁመህ፤ ሰበብ ጥለህ እልህ ጨምር፣
ብሶት ትተህ ማርሽ ቀይር፣
የነግ ፀሐይ ጎህ ሲወለድ፤ መጪው ዘመን አቤት ሲያምር!!
ስንት ንቀት ቢለጥፉ ስንት አሉታ ቢከምሩ፣
አበበ ነው ድል ያ’ረገው ይህን ዓለም በሌጣ እግሩ፡፡
አትሰወር!  አትደበቅ!  አንተም ንገስ በከፍታ፣
ተራራ  ሁን ወይ ኮረብታ፡፡
    ንሳ ጎበዝ!
    በጎ ተስፋ ካላለሙ ዕድሜ ከሆነ ሕልም የለሽ፣
    እንደ ደረቀ ቅጠል ነው የሰው ሕይወት ረብ የለሽ፡፡
    ራዕይ የሌለው አገር ሕልም የሌለው ትውልድማ፣
    ነፍስ የሌለው አሻንጉሊት መብራት የጠፋው ከተማ፡፡
    አዎን ጎበዝ!....
ዘመናችሁ እንዲከብር ዱካችሁ “ እከሌ” እንዲሰኝ፣
ሕይወታችሁ እንዲጣፍጥ ኑሯችሁ ትርጉም እንዲያገኝ፤
ስማችሁ በምርጦች ተራ በቀለመ - ወርቅ እንዲፃፍ፣
ፍሬያችሁ ከዘመን ዘመን እርሿችሁ ለትውልድ እንዲያልፍ፤
ተነሱ በአጭር ታጠቁ! ወገባችሁን ሸብ አ’ርጉ፣
መክሊታችሁን አስሱ ሕልሞቻችሁን ፈልጉ!!
የእናት አባት ብቻ አ’ደለም አምጦ የመፍጠር ግዱ፣
ሕልማችሁን ፀንሳችሁ እራሳችሁን ውለዱ፡፡
    የድል፣ የአርበኝነት ውሎን ለየራሳችሁ ንገሩ፣
    እንደ ያሬድ ሰባቴ ነው ወድቆ መነሳት ምስጢሩ፡፡
    መንገዳችሁ ላይ ከበራው አምፖል ከያዘው ሰማዩ፣
    ሕልም ይበልጣል ከፀሐዩ፡፡
    የሰው ልጆች ሆይ ተነሱ!
    ያንቀላፋውን ተፈጥሮ እምቅታችሁን ቀስቅሱ፣
    ጉልበታችሁን አበርቱ፤ ክንፎቻችሁን አድሱ፣
መክሊታችሁን ፈልጉ ሕልሞቻችሁን አስሱ፡፡

Saturday, 21 February 2015 13:31

የቀለም ቆጠራ ጉዳይ

የአማርኛ ሥነ ድምፀልሳን (ፎኖሎጂ) በአጠቃላይ፣ በተለይ ደግሞ የቀለም ቆጠራ በሙላት እና በቅጡ ያልተጠና በመሆኑ በዚህ መስክ እስካሁን ያለን ዕውቀት ያልተሟላ፣ ያልተደራጀና “ግልብ” ዓይነት ነው ማለት ሳይቻል አይቀርም። በአማርኛ ሥነግጥም የቀለም ቆጠራ መርህ በብዙ መልኩ የተዛባና አሳሳች ሆኖ በመቆየቱ፣ የግጥም ዓይነቶች ምደባችንም እንደዚሁ ቅጣንባር የሌለው ወደመሆኑ ተቃርቧል።
ይህንን መወናበድ ዮሐንስ ሰ. የተባሉ ጸሃፊ በጋዜጣችሁ ባቀረቧቸው መጣጥፎች ማለፊያ አድርገው አቅርበውታል። ጸሐፊው ነቅሰው ያወጡዋቸው ስህተቶችና መደናገሮች ትክክለኛ እና ተገቢ ሆነው አግኝቼአቸዋለሁ።
ዕውቀት እምነት አይደለም፤ ይመረመራል፤ ይፈተሻል፤ በየጊዜውም ይሻሻላል። ዕውቀትን በጭፍን ተቀብሎ አምልኮ ማድረግ ከጠማማና ከጽልመት ጎዳና አያወጣም። በቅጡ የተረዱትን ምርመራ በትሁት ድፍረት ማቅረብም ተገቢና የሕልውናም ጉዳይ ነው።
ስለ አማርኛ ሥነግጥም እስካሁን ከቀረቡት ሐተታዎች የመንግስቱ ለማ በብዙ መልኩ የተሻለው ነው፤ ጥቂት ማጠናከሪያ ግን ያስፈልገዋል። የብርሃኑ ገበየሁ፣ “የአማርኛ ሥነግጥም” በብዙ መልኩ የተሟላና  የተደከመበት ነው። ነገር ግን፣ በተለይ ቀለም ቆጠራንና፣ የግጥም ምደባዎችን በተመለከተ ብዙ እንከኖች አሉበት። መጽሐፉ ማስተካከያና እርማቶች ተደርገውበት፣ በሁለተኛ ኤዲሽን፣ ሊታተም ይገባ ነበረ። ነገር ግን ይሔን እንዳንጠብቅ የሚያደርገን አሳዛኝ ነገር አለ፤ አሁን ደራሲው በሕይወት የለም።
በየትኛውም መንገድ ቢሆን በአንድ የዕውቀት ዘርፍ ላይ አማራጭ መጻሕፍት የመኖራቸው ፋይዳ አሌ የሚባል አይደለም። በዚህ አጋጣሚ፣ በቅርቡ ለሕትመት የሚበቃ የአማርኛ ሥነግጥም መጽሐፍ በዝግጅት ላይ እንደሆነ ብገልጽም መልካም ነው።
በማጠቃለያውም፣ ዮሀንስ ሰ. የተባሉት ጸሐፊ፣ ላቀረቡት ማለፊያ ትንተና፣ ከልቤ ያደንቅኋቸው መሆኑን መግለጽ እወዳለሁ።
አብነት ስሜ፤ (የቋንቋና የሥነጽሑፍ መምህር፣ የ“ኢትዮጵያ ኮከብ” እና የ“ፍካሬ ኢትዮጵያ” ደራሲ)

Saturday, 21 February 2015 13:29

የፍቅር ጥግ

ማን እንደሚያደንቅህና እንደሚወድህ ንገረኝና ማንነትህን እነግርሃለሁ፡፡
ኢሪክ ፍሮም
የማያፈቅር ልብ ከሚኖረኝ ይልቅ የማያዩ ዓይኖች፣ የማይሰሙ ጆሮዎች፣ የማይናገሩ ከናፍሮች ቢኖሩኝ እመርጣለሁ፡፡
ሮበርት ቲዞን
ፍቅር፤ ለሁሉም እጅ ቅርብና በማንኛውም ወቅት የሚበቅል ፍሬ ነው፡፡
ማዘር ቴሬዛ
ሰዎች ኢ-ተጠያቂያዊ፣ በምክን የማይመሩና ራስ ወዳድ ናቸው፡፡ ሆኖም ውደዷቸው፡፡
ኬንት ኤም.ኪዝ
በህልምና በፍቅር ውስጥ የማይቻሉ ነገሮች የሉም፡፡
ዣኖስ አራኒ
አፍቅሮ ማግኘት ምርጥ ነው፡፡ አፍቅሮ ማጣት ሁለተኛው ምርጥ ነገር ነው፡፡
ዊሊያም ሜክፒስ ቻክሬ
ብዙ ጊዜ ፍቅር ይዞኛል … ሁሌም ካንቺ ጋር ነው፡፡
ማንነቱ ያልታወቀ ፀሓፊ  
ፍቅር ዓመታትን የመቁጠር ጉዳይ አይደለም … ዓመታቱን ትርጉም ያላቸው ማድረግ እንጂ፡፡
ሚሼል አማንድ
ገነት ሁሌም ፍቅር በከተመበት ስፍራ ይገኛል፡፡
ጆሃን ፖል ፍሬድሪክ ሪሽተር
እውነተኛ የፍቅር ታሪኮች ጨርሶ ማለቂያ የላቸውም፡፡
ሪቻርድ ባች
ለመፋቀር በተመሳሳይ መንገድ ማሰብ የለብንም፡፡
ፍራንሲስ ዴቪድ
ጨቅላ ፍቅር፤ “ስለምፈልግሽ እወድሻለሁ” ሲል፣
የበሰለ ፍቅር፤ “ስለምወድሽ እፈልግሻለሁ” ይላል፡፡
ኤሪክ ፍሮም