Administrator

Administrator

Saturday, 25 April 2015 11:04

የፍቅር ጥግ

(ስለውበት)
ውበት ሌላ ሳይሆን እውነታ በፍቅር አይን ሲታይ ነው፡፡
ራቢንድራናዝ ታጎር
ውበት፤ ዘላለማዊነት ራሱን በመስተዋት ሲመለከት ነው፡፡
ካሊል ጂብራን
ውበት ከወይን ጠጅ ይብሳል፤ ባለቤቱንም ተመልካቹንም ያሰክራል፡፡
አልዶስ ሁክስሌይ
ውበት፤ ጥሩ የትውውቅ ደብዳቤ ነው፡፡
የጀርመናውያን ምሳሌያዊ አባባል
ውበት በዕለት ሥራ ውስጥም ይገኛል፡፡
ማሚ ሲፐርት በርንስ
ውበት፤ የእግዚአብሔር የእጅ ፅሁፍ ነው፡፡
ቻርልስ ኪንግስሌይ
ሰዎች ውበት ውስጣዊ ነው ይላሉ፡፡ እኔ ግን ከቆንጆ ኩላሊት ይልቅ ቆንጆ ፊትን እመርጣለሁ፡፡
ያልታወቀ ምንጭ
ውበት የአፍቃሪ ስጦታ ነው፡፡
ዊልያም ኮንግሪቭ
ውበት የሚጠወልግ አበባ ነው፡፡
ምሳሌያዊ አባባል
አካላዊ ውበት እንደተመልካቹ ሊሆን ይችላል፤ ውስጣዊ ውበት ግን ከውስጥ የሚያበራ በመሆኑ ማንም ሊክደው አይችልም፡፡
ኒሻን ፓንዋር
የሴት እውነተኛ ውበት ያለው ቆዳዋ፣ ፀጉሯ ወይም ተክለ ሰውነቷ ላይ አይደለም … ልቧ፣ ነፍሷ፣ መንፈሷ ላይ እንጂ፡፡
አሌክሳ ዶልም
ለውስጣዊ ውበታችሁ ስትል የምትወዳችሁ ብቸኛዋ ሴት እናታችሁ ናት፡፡
ያልታወቀ ምንጭ
 በዙሪያችሁ ውበትን በፈጠራችሁ ጊዜ ሁሉ ነፍሳችሁን እያደሳችሁ ነው፡፡
አሊስ ዎከር
ሴቶች ሆይ፤ ውበት የሚተረጎመው በጂንስ ሱሪያችሁ ልክ አይደለም፡፡
ሮበርት እስካሌት


Saturday, 25 April 2015 11:00

የሰዓሊያን ጥግ

 በብሩሼ እሰብካለሁ፡፡
ሔነሪ ኦሳዋ ታነር
ስዕል ሃሳቦቼን የማያይዝበት ምስማር ነው፡፡
ጆርጅስ ብራኪው
እኔ ነገሮችን አልስልም፤ የምስለው በነገሮች መካከል ያለውን ልዩነት ብቻ ነው፡፡
ሔነሪ ማቲሴ
ስዕሎች በጣም መማረክ የለባቸውም፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኢመርሰን
ስዕል ማለቂያ የሌለው የሚመስል ጀብዱ ነው፡፡
ጃሶን
ስዕሎች ብዙ ጊዜ ግድግዳን ከማሳመር ይልቅ ያበላሻሉ፡፡
ዊሊያም ዎርድስ ዎርዝ
ሰዓሊ ሃሳቦቹን ከቆሻሻ ጋር እንዳይጥላቸው መጠንቀቅ አለበት፡፡
ቴሪ ጉይሌሜትስ
ለምንድን ነው የሞቱ ዓሳዎች፣ ሽንኩርቶችና የቢራ ብርጭቆዎች የምስለው? ልጃገረዶች እኮ እጅግ ውብ ናቸው፡፡
ሜሪ ሎውሬንሲን
ዓይኖቼ የተፈጠሩት የሚያስጠላውን ሁሉ ለመሰረዝ ነው፡፡
ራኦል ዱፊ
ማስታወቂያዎች የ20ኛው ክ/ዘመን የዋሻ ስዕሎች ናቸው፡፡
ማርሻል ማክሉሃን
ስዕል ቃላት አልባ ግጥም ነው፡፡
ሆራስ
ሰዓሊ፤ ሰዎች እንዲኖራቸው የማይፈልጉትን ነገር የሚፈጥር ነው፡፡
አንዲ ዋርሆል
ፎቶግራፍን ልዩ ፈጠራ የሚያደርገው የመጀመሪያ ጥሬ እቃዎቹ ብርሃንና ጊዜ መሆናቸው ነው፡፡
ጆን በርገር
ስዕል በተፈጥሮ አንፀባራቂ ቋንቋ ነው፡፡
ሮበርት ዴላዩናይ
ፀሐፊ በዓይኖቹ መፃፍ፣ ሰዓሊ በጆሮዎቹ መሳል አለበት፡፡
ጌርትሩድ ስቴይን
የሰው ልጅ ሁሉ ሰዓሊ ነው፡፡ የህይወትህ ህልም ውብ ስዕል መስራት ነው፡፡
ሚጌል ኤንጅል ሩይዝ
ስዕሎች የተንጠለጠሉበት ክፍል ሃሳቦች የተንጠለጠሉበት ክፍል ነው፡፡
ጆሹዋ ሬይኖልድስ

Saturday, 25 April 2015 10:46

የፖለቲካ ጥግ

በመንግሥት በጀት ትዳራቸውን የሚያስተዳድሩ ፕሬዚዳንቶች
በየዓመቱ አንድ ድንግል የሚያገባው መሪ

ምስዋቲ
የስዋዚላንዱ ንጉስ ምስዋቲ አስገራሚ ባህላዊ መሪ ናቸው - እንግሊዝ የተማሩ! በጐሳቸው ባህል መሰረት ብዙ ሚስቶችን ማግባት ይችላሉ (እችላለሁ ስላሉ ነው!) ለዚህም ነው 14 ሚስቶች አግብተው 24 ልጆችን ያፈሩት፡፡ ይሄ ብቻ ግን አይደለም፡፡ (ቢሆንማ በማን እድላችን!) በየዓመቱ በሚካሄደው የደናግል ኮረዶች ዳንስ፣ ንጉሡ አንድ ድንግል መርጠው ያገባሉ፡፡ ሚስቶቻቸው በ14 የተንደላቀቁ ቤተመንግስቶች ውስጥ የሚኖሩ ሲሆን እነሱን ለማስተዳደርም ከድሃዋ አገራቸው ዓመታዊ በጀት ላይ 31.7 ሚ. ፓውንድ ይወስዳሉ (ትዳር በመንግስት በጀት ይመቻል!)
ሁሉም ሚስቶቻቸው ደስተኛ ናቸው ለማለት ያዳግታል፡፡ (የንጉስ ወህኒ ቤት እኮ ነው!) ለምሳሌ ሦስቱ ሚስቶቻቸው (ለስሙ ንግስቶች ናቸው!) አካላዊና ስነልቦናዊ ጥቃት ደርሶብናል በማለት የንጉሱን ቤተመንግስት ጥለው ወጥተዋል፡፡ ለንጉስ ምስዋቲ በዓመት አንዴ የሚካሄደው የኮረዶች ባህላዊ የዳንስ ትርኢት ሁሌም በጉጉት የሚጠበቅ ነው፡፡ እ.ኤ.አ በ2012 ዓ.ም 80ሺ ደናግል ኮረዶች (እርቃነ-ጡታቸውን) ሆነው ለስዋዚላንዱ ንጉስ የዳንስ ትርኢት አሳይተዋል - በስቴዲየም። በዚህ ትርኢት ንጉሱ ይዝናናሉ፡፡ አንድ ድንግል መርጠውም ያገባሉ፡፡ አንዳንዶቹን ልጃገረዶች ደግሞ አልፎ አልፎ ለመቅበጥ ይፈልጓቸዋል፡፡
በንጉሡ ተመርጣ ሚስት የሆነች ኮረዳ ወዲያውኑ አንድ ቤተመንግስትና BMW አውቶሞቢል ይበረከትላታል፡፡ ለአንዲት ምስኪን የገጠር ኮረዳ ይሄ ምን ማለት እንደሆነ አስቡት! (ግን ድንግልናዋን ብቻ ሳይሆን ነፃነቷንም ተነጥቃ ነው!) ያለንጉሱ ፈቃድ የትም ንቅንቅ አትልም፡፡ (እስር በሉት!) በዓመት አንዴ ግን ሁሉም ሚስቶቹ አሜሪካ ሄደው እቃ እንዲሸምቱ ንጉሱ ገንዘብ ይሰጧቸዋል፡፡ በነገራችን ላይ አባታቸው ንጉስ ሶብሁዛ (ሁለተኛው) 70 ሚስቶች ነበሯቸው፤ 400 ልጆችም ወልደዋል፡፡ (የዘር ነዋ!)
ንጉስ ምስዋቲ የመጨረሻ ሚስታቸውን ያገቧት በ19 ዓመቷ ሲሆን በዳንስ ትርኢቱ ላይ ነው የመረጧት፡፡ ንጉሱ የሚያስተዳድሯት ስዋዚላንድ በጣም ትንሽ አገር ስትሆን የህዝቧ ቁር 2 ሚሊዮን እንኳን አይሞላም፡፡ 70 በመቶ ህዝቧ ግን ከድህነት ወለል በታች ነው የሚኖረው፡፡ የአፍሪካ የመጨረሻው ንጉስ ናቸው የሚባሉት ምስዋቲ ደግሞ የጠገቡ ሃብታም ናቸው - የ200 ሚ. ዶላር ጌታ! በአፍሪካ ቀዳሚ “ሴት አውል” ፕሬዚዳንት በሚል በአንደኝነት ተመርጠዋል፡፡
ጃኮብ ዙማ
ጃኮብ ዙማ የደቡብ አፍሪካ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው ካገለገሉ በኋላና የአገሪቱም ሆነ የአፍሪካ ናሽናል ኮንግረስ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ከመሆናቸው በፊት በአስገድዶ መድፈር ተከሰው ነበር፡፡ ዙማ ዘመናዊ መሪ (ድንቄም ዘመናዊ!) ቢመስሉም አራት ሚስቶች አሏቸው፡፡ ፕሬዚዳንት ጃኮብ እ.ኤ.አ በ2014 ዓ.ም “ውሃ አጣጪ” አምስተኛ ሚስታቸውን (ለእርጅና ዘመኔ ብለዋል!) ለማግባት ዝግጁ መሆናቸውን ጠቁመው ነበር፡፡ የ72 ዓመቱ ዙማ፤ (በደቡብ አፍሪካ በስንት ዓመት ነው አረጀሁ የሚባለው?) “ሚስቶች አሉኝ፤ ነገር ግን የመጨረሻይቱን በቅርቡ አገባለሁ” ብለዋል፡፡ (ለምን የመጨረሻ እንዳሉ አልገባኝም!!)
ለፕሬዚዳንቱ ቅርብ የሆኑ ሰዎች እንደመሰከሩት፤ ሰውየው ከሴት ሌላ ወሬ የላቸውም፡፡ 20 ገደማ ልጆች ያሏቸው ዙማ፤ ስድስት ጊዜ ያገቡ ሲሆን በእርግጥ አሁን በመንግስት በጀት የሚያስተዳድሯቸው አራት ሚስቶች ብቻ ናቸው ያሏቸው፡፡ (ሰውየው መደበኛ ትምህርት አልዘለቃቸውም ይባላል!) ጃኮብ አንድ ጊዜ በአስገድዶ መድፈርና በትዳር ላይ በመማገጥ ተከሰው ነበር - “አፍሪካ ክራድል” እንደዘገበው፡፡
ጋዳፊ
ሊቢያን ከ30 ዓመታት በላይ አንቀጥቅጠው የገዟት ኮሎኔል ሙአመር ጋዳፊ (መሬት ይቅለላቸውና!) ሁለት ሚስቶች ነበሯቸው - ሳፍያ ፋርካሽ እና ፋቲሃ አል-ኑሪ፡፡ ለብዙዎች የጋዳፊ ሞት የእሳቸው ዘመን ማብቃቱን ያረጋግጥላቸዋል። ለ5 ዓመት አስገድዶ ደፍሮኛል ለምትለው ሳፍያ ግን የኮሎኔሉ መንፈስ እድሜልኳን ሲያስበረግጋት ይኖራል፡፡ የፕሬዚዳንቱን በድን ምስል ባየችበት ወቅት የተደበላለቁ ስሜቶች እንደተሰማት ተናግራለች - ከደስታ እስከ ንዴት፡፡
እሷ ብቻ ግን አይደለችም የተደፈረችው፡፡ ጋዳፊ ሴት ጠባቂዎቻቸውንም (Body guards) አስገድደው ይደፍሩ ነበር፡፡ ይሄ ብቻ አይደለም። ይደበድቧቸውና በመድሃኒትም ያደነዝዟቸዋል፡፡ ከእኒሁ ሴት ጠባቂዎቻቸው ጋር በፕሬዚዳንታዊ መኖርያ ቤታቸው ውስጥ የቡድን ወሲብ ይፈፅሙ እንደነበርም “አፍሪካ ክራድል” ዘግቧል፡፡
ዘገባዎች እንደሚጠቁሙት፤ ሌሎች ልጃገረዶችም የኮሎኔሉን “አፈንጋጭ የወሲብ ፍላጐቶች” ለማርካት የቦዲጋርዶቻቸውን ያህል ተሰቃይተዋል፡፡ የአፍሪካና የአውሮፓ በተለይ የጣልያንና ቤልጂየም ልዕለ ሞዴሎች ዘወትር እየተመለመሉ የፕሬዚዳንቱን ፍላጐት በቡድን ያረኩ ነበር ተብሏል፡፡
”ሴቶቹ ስራቸውን ሲያጠናቅቁም ቦርሳቸውን በገንዘብ አጭቀው ይወጣሉ፤ የወሲብ ባሪያ ላደረጓቸው የሊቢያ ሴቶች ግን ጨርሶ ገንዘብ ሰጥተዋቸው አያውቁም” ይላሉ - ምንጮች። በእነዚህ ሁሉ ምክንያቶች የተነሳ ጋዳፊ 3ኛው “ሴት አውል” (ሴሰኛ ይሻላል!) የአፍሪካ መሪ በሚል ተመርጠዋል፡፡ (ቤተመንግስቱን የዝሙት ቤተ አድርገው ነበር!)
ጆን ማሃማ
የጋናው ፕሬዚዳንት ጆን ማሃማ “ሴት አውል” አይደለሁም ሲሉ ያስተባብላሉ፡፡ ነገር ግን ከትዳራቸው ውጭ መቅበጣቸውን አይክዱም!!” ልካድ ቢሉም አይችሉም፡፡ በርካታ ከትዳር ውጭ የተወለዱ ልጆች አሏቸው፡፡
“እኔን ሴት አውል አድርጐ የማሰብ ሁኔታ አለ፤ ይሄ ፈፅሞ እውነት አይደለም፡፡ በእርግጥ ከትዳሬ ውጭ ልጆች ወልጄአለሁ፡፡ ይሄን በተመለከተም ከሚስቴ ጋር ሰላም ፈጥሬአለሁ፡፡ እሷ ነገሩ የተከሰተበትን ሁኔታ በደንብ ተረድታለች፡፡ እኔም ለልጆቼ ሃላፊነት የሚሰማው አባት ነኝ፡፡” ብለዋል - ፕሬዚዳንቱ፡፡
ማሃማ ከትዳር ውጭ የተወለዱት ልጆች ቁጥር “ሰባት” መሆናቸውን በይፋ ገልፀዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ከሌላ ያልታወቀች ሴት (እሳቸውማ ያውቋታል!) የወለዷቸው ልጆች እንዳሉም ይታወቃል፡፡ ከአሁኑ ባለቤታቸው ከሎርዲና ጋር ከመጋባታቸው በፊት የወለዱት አንድ ወንድ ልጅም አላቸው፡፡ ምንጮች እንደሚጠቁሙት ግን ማሃማ ቢያንስ 5 ከትዳር ውጭ ግንኙነቶች ሲኖራቸው የልጆቹ ቁጥርም ከሰባት በላይ ነው (20 እንኳን አልሞላም እኮ!) እነዚህ ሁሉ ታይተው ጆን ማሃማ 4ኛው “ሴት አውል” ኛ የአፍሪካ ፕሬዚዳንት ተብለዋል፡፡
ያህያ ጃሜህ
የጋምቢያው ፕሬዚዳንት ያህያ ጃሜህ ሦስት ሚስቶች አሏቸው - አሊማ ሳላህ፣ ዘይነብ ሱማ ጃሜህ እና ቱቲ ፋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ፤ የነፃ ትምህርት እድል አሸናፊ ከነበረችው ፋቶ ጃሮል - ጃሜህ ጋር በነበራቸው ግንኙነት አስረግዘዋት ነበር፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ ግን ህፃኑ “ዳውን ሲንድሮም” (የአዕምሮ እድገት ዝግመት) እንዳለበት በምርመራ በመታወቁ ፅንሱን እንድታቋርጠው ተደረገ። በነገራችን ላይ የፕሬዚዳንቱ ሁለት ልጆችም በተመሳሳይ የጤና ችግር የተጠቁ ናቸው፡፡
ያህያ ጃሜህ የሰው ሚስት በመመንተፍ ይታማሉ፡፡ ከትዳራቸው ውጭም ልጆች ወልደዋል። እድሜ ለሃብታቸውና ለስልጣናቸው! ከወጣት ሴቶችና ኮረዳዎች ጋር እንዳሻቸው ይቀብጣሉ፡፡ ሰውየው በአፍሪካ 5ኛው “ሴት አውል” ፕሬዚዳንት ተብለው ተመርጠዋል፡፡
ወዳጆቼ፤ እንዳያችሁት የአንዳንድ የአፍሪካ መሪዎች ታሪክ በሴትና በወሲብ ገድል የተሞላ ነው። ስልጣን የሙጥኝ የሚሉት እኮ ወደው አይደለም፡፡ ለእነሱ ከኤደን ገነት እንደመባረር ነው - ከቤተ መንግስት መውጣት! ምስኪኑ የአፍሪካ ህዝብ ግን በድህነት ተቆራምዶ ኑሮውን ይገፋል፡፡ (“ወይ መዓልቲ!” አለ ትግሬ!)

    በአዲስ አበባ ከተማ በተለያዩ ሰዎች ሥም የሚጠሩ መንደሮችና መንገዶች ጥቂት የሚባሉ አይደሉም፡፡ “ወርቁ ሠፈር፣ የሺ ደበሌ ማዞሪያ፣ አባ ቦራ ቅያስ፣ ሞላ ማሩ አካባቢ፣ አባ ኮራን መንደር…” የሚባሉትን በማሳያነት ማንሳት      ይቻላል፡፡ የመንደርና የመንገዶቹ ስሞች በመንግስት የሚሰጡበት ጊዜ አለ፤ እንደ፣ “ቸርች ል ጎዳና”፡፡ በአካባቢው ታዋቂ ሥራ ከሚሰራ ተቋም ወይም ግለሰብ ጋር በተያያዘ ስያሜውን ያገኘ ይኖራል፤ እንደ “ባሻ ወልዴ ችሎት”፡፡ ህብረተሰቡም አብረውት ከሚኖሩት መሐል የተለየ አክብሮ ለለገሰው ሰው መጠሪያ እንዲሆን ዕውቅና የሚሰጠው አለ፤ እንደ “ዘውዴ ብራቱ መንገድ፡፡”
ከክፍለ ሀገር አውቶቢስ ተራ ወደ አብነት በሚያስኬደው አውራ ጎዳና ወደ አዲስ ከተማ መንደሮች ከሚያስገቡት ቅያሶች አንዱ በስማቸው የሚጠራው ቀኛዝማች ዘውዴ ብራቱ፤ መንገዱ እንዴት በስማቸው ሊጠራ እንደቻለ “የሕይወቴ ጉዞ” በሚል ርዕስ ካዘጋጁት የሕይወት ታሪክ  ጥቂቱን ለጋዜጣ በሚያመች መልኩ አሳጥረን አቅርበነዋል፡፡

  ወላጅ አባቴ ፊውራሪ ብራቱ ደጋጋ በተለያዩ የሥራ ኃላፊነቶች በተለያዩ ቦታዎች ህዝብና አገራቸውን አገልግለዋል፡፡ በማይጨው ጦርነት ተሳትፈዋል፡፡ የራስ አበበ አረጋይ ንብረት እንደራሴ ባለ አደራ ሆነው ነበር፡፡ ለራስ ሙሉጌታ ድረው በወንበርነት ሰርተዋል፡፡ “ወንበር” ማለት በፍርድ ቤት ወይም በአስተዳዳሪ ተሰይሞ የሚሰራ ሹመኛ ማለት ነው፡፡ በዚህ ሹመት በተለያዩ ክፍላጸ ሀገራት በመዘዋወር አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡ ከፍርድ ሚኒስቴር የጥብቅና ፈቃድ በመውሰድ በሙያው ሰርተዋል፡፡ በትውልድ መንደራቸው በአይመለል ክስታኔ ጉራጌ ዞን በግብርና ሥራ የተዳደሩበት ታሪክም አላቸው። እናቴ እመት ግምጃ ኢላላ የቤት እቤት ነበሩ፡፡ ወላጆቼ በትዳራቸው ካፈሯቸው ሸባጽ ልጆች እኔ ሦስተኛው ልጅ ነኝ፡፡
የተወለድኩት በአዲስ አበባ ከተማ፣ ሰባ ደረጃ ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ፣ ከራስ መኮንን ከፍ ብሎ ከሚገኘው “አባታችን ሰፈር” ውስጥ ሲሆን ዕለቱ ሚያዚያ 23 ቀን 1920 ዓ.ም ነው፡፡ በአሁን ወቅት በ87 ዓመት ዕድሜ ላይ እገኛለሁ፡፡ የተወለድኩበት መንደር “አባታችን ሰፈር” የሚል መጠሪያ ያገኘው የጳጳሳት መኖሪያ አካባቢ በመሆኑ ነበር፡፡
ትውልዴ አዲስ አበባ ቢሆንም በአባቴ አገር ሚልኮ የቤተክህነት ትምህርት መከታተሉን በ7 ዓመቴ ጀምሬ በተለያዩ ደረጃዎች በማለፍ 12 ዓመት ሲሞላኝ በሚልኮ ጥንታዊት ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን በድቁና ማገልገል ጀመርኩ፡፡
ከድቁና አገልግሎቴ ጎን ለጎን ቤተሰቦቼን በስራ እረዳ ነበር፡፡ የ17 ዓመት ወጣት ሳለሁ ከዛሬዋ ባለቤቴ ከወ/ሮ ትክክልወርቅ ሞጆ ጋር ጥር 7 ቀን 1937 ዓ.ም ትዳር መሰረትኩ። ትዳራችን 70 ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ አባቴ በሰጠኝ መሬት ላይ የራሴን ጎጆ ቀልሼ ትዳሬን ማስተዳደር ብችልም ተጨማሪ ትምህርትና ዕውቀት ማግኘት ስለምችልበት ሁኔታ ዘወትር በማሰብ እተጋ ነበር፡፡
በ1941 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሆኜ ዘመናዊ ትምሀርት እንድማር እንዲፈቅዱልኝ አባቴን በሽማግሌ ሳስጠይቃቸው፤ “ሚስቱን የት አድርጎ ነው የሚማረው?” ብለው ተቃውሞ አቅርበው ነበር፡፡ ባለቤቴ ወ/ሮ ትክክልወርቅ ሞጆ፤ አዲስ አበባ መጥታ መኖር ትፈልግ ስለነበር፣ የአባቴን ተቃውሞ ስትሰማ “ይማር እኔ እናቱ ጋ አገር ቤት እቀመጣለሁ” በማለቷ ትምህርት ቤት የመግባት ፍላጎቴ ተሳካ፡፡
በአዲስ አበባ ትምህርት የጀመርኩት በሊሴ ገብረ ማርያም ትምህርት ቤት ሲሆን በወር 5 ብር እከፍል ነበር፡፡ በዕድሜዬ፣ በቁመቴና በዕውቀቴ ተገምግሜ ሁለተኛ ክፍል በመመደብ ነበር ትምህርት የጀመርኩት፡፡ በቀኑ ክፍለ ጊዜ በሊሴ ገብረ ማርያም ፈረንሳይኛ እየተማርኩ፣ በማታው ክፍለ ጊዜ እንግሊዝኛ ቋንቋ ለመማር ካቴድራል ትምህርት ቤት ገባሁ፡፡ በቀጣዩ ዓመት ልዑል ወሰንሰገድ ትምህርት ቤት 3ኛ ክፍል በመግባት የዕውቀት ጥሜን ለማርካት ጥረቴን ቀጠልኩ፡፡ ከክፍል ወደ ክፍል በደብል እያለፍኩ በ1944 ዓ.ም 8ኛ ክፍል ደረስኩ፡፡
እኔ በአዲስ አበባ ሆኜ ትምህርቴን እንድከታተል ፈቃደኛ የሆነችው ባለቤቴ ወ/ሮ ትክክልወርቅ ሞጆን ማገዝ እንዳለብኝ ስለተሰማኝና አብረን መኖር እንዳለብን ስለወሰንኩ የአገር ግዛት ሚኒስቴር ባወጣው ማስታወቂያ ተወዳድሬ በስታቲስቲክ ክፍል ተቀጥሬ በወር 40 ብር እየተከፈለኝ መስራት ጀመርኩ፡፡ ከዚህ በኋላ ባለቤቴም አዲስ አበባ መጥታ አብረን መኖር ጀመርን፡፡
ከአገር ግዛት ሚኒስቴር በኋላ በቡታጅራ፣ በሱሉልታ፣ በአዲስ ኣለም፣ በአቃቂ በሰቃ፣ በሆለታ ገነትና መሰል ቦታዎች በመዘዋወር በተለያየ የኃላፊነት ቦታ እስከ 1957 ዓ.ም ድረስ ካገለገልኩ በኋላ በግል የጥብቅና ሙያ ለመሰማራት ስለወሰንኩ፤ እራሴን ከቅጥር ሥራ አሰናብቼ በ1958 ዓ.ም ከፍርድ ሚኒስቴር የጥብቅና ፈቃድ ወስጄ መስራት ጀመርኩ፡፡ በዚህ ዘርፍ ያለኝን ዕውቀት ለማሻሻልም ወደ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የህግ ፋኩልቲ በመግባት የህግ ትምህርት ተከታትዬ፣ ሐምሌ 8 ቀን 1961 ዓ.ም ከግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ እጅ በህግ ሰርተፍኬት ተቀብያለሁ፡፡
በ1962 ዓ.ም ፓርላማ መግባት የቻልኩት ምዕራብ አዲስ አበባን ወክዬ በመወዳደር በአንደኛ ደረጃ ማሸነፍ ስለቻልኩ ነበር፡፡ በውድድር ወቅት ለህብረተሰቡ ቃል በገባሁት መሰረት የህዝቡ ችግሮች ናቸው ያልኳቸውን ጉዳዮች በተደጋጋሚ ለፓርላማው አቅርቤያለሁ። ለምሳሌ በየጎዳናው ላይ ሱቅ በደረቴ የሚሰሩ ነጋዴዎች፤ ያለ አማራጭ የሥራ ቦታ በየዕለቱ እንዲባረሩ መደረጉ ስህተት መሆኑን ለፓርላማው አሳውቄ፣ ፓርላማውም አቤቱታውን ተቀብሎ መፍትሔ ይፈለግለት ብሎ አጽድቆታል፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ ዳቦ ሳይጠግብ በቁማር ሱስ እንዲጠመድ እየተደረገ ነው በማለት በአዲስ አበባ ከተማ የተስፋፋውን የቁማር ማጫወቻ ቤቶችና ማሽን ብዛት በማመልከት ለፓርላማው ያቀረብኩት አቤቱታም ምክር ቤቱ የጉዳዩን አስከፊነት ከተቸበት በኋላ የቁማር መጫወቻ ማሽኖች በ24 ሰዓት ውስጥ ከኢትዮጵያ እንዲወጣ ያሳለፈውን ውሳኔ የመወሰኛ ምክር ቤትም ተቀብሎ አጽድቆታል፡፡
በ1963 ዓ.ም ህዝቡን አስተባብሬ ኮሚቴ በማቋቋም ከአዲስ ከተማ ሰፈር እስከ አማኑኤል ቶታል እና ወደ ኮካኮላ የሚያስኬደው መንገድ ድረስ በማገኛኘት አስፓልት ሆኖ የተሰራ ሲሆን፡፡ የአዲስ አበባ ከንቲባ የነበሩት ዶ/ር ኃይለጊዮርጊስ ወርቅነህ እንዲመርቁልን አድርገናል፡፡ ህዝቡ በዚህ የመንገድ ስራ ወቅት አደርግ የነበረውን ጥረት አይቶ ወጪ ወራጁ ሁሉ “ዘውዴ ብራቱ መንገድ” ብሎ ሰይሞታል፡፡ መዋጮዬ ከማንም ያልበለጠ ቢሆንም፤ መንገዱ በስሜ ሲጠራ ስሰማ ደስ ይለኛል፡፡
የደርግ መንግስት በስልጣን ማብቂያው ዋዜማ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ጠርቶ በኢሰፓ አዳራሽ ሀገር አቀፍ ስብሰባ ባደረገበት ወቅት፤ ማን እንደጠቆመኝ ባላውቅም ምዕራብ አዲስ አበባን ወክዬ በኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያም ሰብሳቢነት በተካሄደው ጉባኤ ለአራት ቀናት ተሳትፌያለሁ፡፡
ኢህአዴግ አዲስ አበባን ከተቆጣጠረ በኋላም የሰላም እና መረጋጋት ኮሚቴ ሲቋቋም፣ የኮሚቴው ሊቀመንበር ሆኜ እንዳገለግል ህዝብ ስለመረጠኝ የተደረገልኝን ጥሪ ተቀብዬ በኃላፊነት የተሳተፍኩ ሲሆን ሰላምና መረጋጋት ሲረጋገጥ ወደ ተለመደው የሙያ ሥራዬ ተመልሻለሁ፡፡
በደቡብ ክልላዊ መንግሥት በጉራጌ ዞን ለሚገኘው የአይመለል ክስታኔ ህዝብ በልማት ዙሪያ የተለያዩ አስተዋጽኦዎች ለማድረግ ሞክሬያለሁ፡፡ የክስታኔ ጉራጌ ህዝብ የጎርዳና ሸንጎ ሊቀመንበር ሆኜ አገልግያለሁ፡፡ በመንገድ ሥራ፣ በጤና ጣቢያ ግንባታ፣ በአብያተ ክርስቲያናት ህንፃ ግንባታ፣ በትምህርት ቤት ማስፋፋት ሥራ ላደረግሁት አስተዋጽኦም ህዝቡ የቀኛዝማችነት ማዕረግ የሰጠኝ ሲሆን የልማት ስራዎቹን የረዱ የተለያዩ ተቋማትም የምስጋና የምስክር ወረቀት ሰጥተውኛል፡፡
በማህበራዊ ተሳትፎም አባል በሆንኩባቸው የተለያዩ ዕድሮች ውስጥ በኃላፊነት በመመረጥ አገልግያለሁ፡፡ ለዕድሮቹ ዕድገትም በህግ እውቀቴ ያለኝን ልምድ በማካፈል ለመርዳት ሞክሬያለሁ። የጥብቅና ሙያን መተዳደሪያዬ አድርጌ እስከ 1998 ድረስ በመስራት እኔንና ቤተሰቤን ብቻ ሳይሆን አገርና ሕዝብን ጠቅሜበታለሁ፡፡
በ1937 ዓ.ም ተመስርቶ 70 ዓመታት ባስቆጠረው ትዳራችንም 14 ልጆችን ያፈራን ሲሆን በርካታ የዘመድ ልጆችንም አሳድገናል። የልጅ ልጆችንም አይተናል፡፡ ልጆቻችን ተምረው ዶክተር፣ አካውንታንት፣ ነርስ፣ ፀሐፊ፣ ማርኬቲንግ ኦፊሰር… ሆነዋል፡፡ በህይወቴ የገጠመኝ መሪር ሀዘን ቢኖር በልጄ ቢኒያም ዘውዴ ሞት የደረሰብኝ ስቃይ ነው፡፡ በህክምና ትምህርት በዶክትሬት ለመመረቅ ሁለት ወር ሲቀረው ሚያዚያ 5 ቀን 1998 ዓ.ም በሞት ስለተለየኝ ጥልቅ ሀዘን ተሰምቶኛል፡፡
በአሁኑ ጊዜ እኔም ሆንኩ ባለቤቴ በአንፃራዊነት ጤናማ በሆነ ሁኔታ ላይ ነው የምንገኘው፡፡ ለዚህ የበቃሁትና ይህንን የታደልኩት ባለቤቴ ወ/ሮ ትክክልወርቅ ሞጆን ከመሰለች መልካም ጠባይና የዋህ ተፈጥሮ ካላት ሴት ጋር እግዚአብሔር ስላገናኘኝ ነው፡፡ 70 ዓመታት አብሮ መኖር መቻል ከእግዚአብሔር እንጂ ከሰው የሚገኝ ዕድል አይደለም፡፡ እኔም ኑሮዬ ተሟልቶ የመገኘቱ ምክንያት የባለቤቴ መልካም መሆን አስተዋጽኦ እንዳለበት እገነዘባለሁ፡፡ “መልካም ሴት ለባሏ ዘውድ ናት” የሚለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል በተግባር አሳይታኛለች፡፡
ከባለቤቴ ከወ/ሮ ትክክልወርቅ ሞጆ ጋር ለመንፈሳዊ ጉዞ ከአገር ውጭ ኢየሩሳሌም ቅዱስ መድኀኒዓለም ቤተክርስቲያን የሄድን ሲሆን በአገር ውስጥም በአራቱም ማዕዘን ወደተለያዩ አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማት ተጉዘናል። ልጆቻችን ወዳሉበት የአሜሪካን የተለያዩ ግዛቶች በመሄድ ለመጎብኘት ዕድል አግኝተናል።
የወር ደሞዝተኛ በነበርኩበት ጊዜ ሆነ በግል ሥራም ተሰማርቼ ስሰራ በየዕለቱ የሚገኘውን ገቢ በእቅድ የመምራት ችሎታ ስለነበረኝ፤ ኑሮዬ ሳይዛባ ለዛሬ ደርሻለሁ፡፡ በትዳር አጋሬ ብቻ ሳይሆን በልጆቼም ተባርኬያለሁ፡፡ ልጆቼ አስቀይመውኝ አያውቁም፤ ልጆቻቸውም የተባረኩ እንዲሆኑላቸው እመኝላቸዋለሁ። እኔንና ቤተሰቤን ጠብቆ ለዚህ ያደረሰን እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ህዝቧንም ይባርክ!!”  

Saturday, 25 April 2015 10:44

የፀሐፍት ጥግ

(ስለ መጠጥ)

ወይን ጠጅ የታሸገ ግጥም ነው፡፡
ሮበርት ሉዊስ ስቲቨንሰን
ስጠጣ አስባለሁ፤ ሳስብ ደግሞ እጠጣለሁ፡፡
ፍራንቶይስ ራቤላሲስ
በቀን 24 ሰዓት፣ በሳጥን 24 ቢራ፡፡ ግጥምጥሞሽ ነው?
ስቲቨን ራይት
ወይን ጠጅ በሌለበት ፍቅር የለም፡፡
ዩሪፒደስ
እነሆ የአልኮል መጠጥ፡- የህይወት ችግሮች ሁሉ መንስኤና መፍትሄ፡፡
The Simpsons
አልኮል የሰው ልጅ አስከፊ ጠላት ሊሆን ይችላል፡፡ መፅሀፍ ቅዱስ ግን ጠላታችሁን ውደዱ ብሏል፡፡
ፍራንክ ሲናትራ
እውነታ በአልኮል እጥረት የሚፈጠር ቅዠት ነው፡፡
ኤን.ኤፍ.ሲምፕሶን
መጀመሪያ መጠጥ ትወስዳለህ፤ ከዚያ መጠጡ መጠጥ ይወስዳል፤ በመቀጠል መጠጡ አንተን ይወስዳል፡፡
ኤፍ.ስኮት ፊትዝገራልድ
የቢራ ዋጋን የጨመረ መንግስት ይወድቃል፡፡
የቼኮች አባባል
ውስኪና ቢራ የሰው ልጅ ክፉ ጠላቶች ናቸው፡፡ ከጠላቶቹ የሚሸሽ ግን ፈሪ ነው፡፡
ዜካ ፓጎዲንሆ
(ብራዚላዊ የዘፈን ግጥም ፀሐፊ)
የአልኮልን ጣዕም አልወደውም፡፡ የምጠጣው ሬድ ቡል ነው፡፡
ፓሪስ ሂልተን
አልኮል የሰራተኛውን መደብና አያሌ ሰዎችን ይፈጃል፡፡
ማርቲን ስኮርሴስ
መጠጥ ቀኑን የማጠናቀቅያ መንገድ ነው፡፡
ኧርነስት ሄሚንግዌይ
ከስፖንጅ የበለጠ አልጠጣም፡፡
ፍራንሶይስ ራቤላይስ
የብልህ ሰው ብቸኛው መጠጥ ውሃ ነው፡፡
ሔነሪ ዴቪድ ቶሪዮ

ያለ ሰዓቱ ከተበረከተ ወርቅ፣ በሰዓቱ የተወረወረ ድንጋይ ይሻላል፡፡
ችግር አንበሳን ቀበሮ ያደርጋል፡፡
የተፈታ እንቆቅልሽ ቀላል ይመስላል፡፡
ሁሉም ሰው የእንጀራው ንጉስ ነው፡፡
ብልህ ሰው በራሱ ቀልድ መሳቅ ይችላል፡፡
የበዛ ሙገሳ ከስድብ ይቆጠራል፡፡
ገነት ያለው ከእናት እግር ሥር ነው፡፡
ከባዕድ ጋር ኤደን ውስጥ ከመቀመጥ ከወዳጆቹ ጋር ወህኒ ቤት መታሰር ይሻላል፡፡
ጓደኛና ግጥም አንድ ናቸው፡፡
ህፃናት የገነት ድልድይ ናቸው፡፡
ከጅል ጓደኛ ብልህ ጠላት ይሻላል፡፡
ደምን በደም ማጠብ አይቻልም፡፡
ጠብታ ሲጠራቀም ባህር ይሆናል፡፡
እስከ ንጋት ድረስ የሚበራ ላምባ የለም፡፡
ዓይነ ስውር በመላጣ ይስቃል፡፡
ልብ ለሌላቸው ልብህን አትስጥ፡፡
ድመት ልጆቿን መብላት ሲያምራት አይጦች ይመስላሉ ትላለች፡፡
ጥሩ ዓመት በፀደይ ያስታውቃል፡፡
ሁለት አዋላጆች የህፃን አንገት ይቀጫሉ፡፡

ከማልታ ባገኘሁት መረጃ፤ በቀደም ከተሰውት ወንድሞቻችን ጋር የነበረ፣ በእግዚአብሔር ቸርነት አምልጦ ትሪፖሊ የገባ ወንድም አግኝቼ ነበር፡፡ እርሱ እንደነገረኝ፤ “በአጅዛቢያና ቤንጋዚ መንገድ ላይ የአይሲስ አራጆች የሊቢያ መንግሥት ወታደሮችን ዩኒፎርም ለብሰው በዚያ የሚያልፉትን ለመያዝ ይጠብቃሉ፡፡
በአካባቢው ወደ ትሪፖሊ የሚጓዙ መንገደኞችን ሲያገኙ ይይዛሉ፡፡ ሱዳኖችና ሶማሊያውያን ሙስሊሞች ናቸው ብለው ስለሚያስቡ ወዲያው እንዲሄዱ ይለቋቸዋል። ኤርትራውያንና ኢትዮጵያውያንን ግን ለብቻ ይይዛሉ፡፡ ከዚያም ሙስሊሞችን ለብቻ፣  ክርስቲያኖችን ለብቻ ያሰልፏቸዋል፡፡ በመቀጠልም ክርስቲያኖችን በኮንቴይነር ውስጥ ከትተው ወዳልታወቀ ስፍራ ይወስዷቸዋል። ምግብ የሚሰጧቸው በየሦስት ቀን ነው፡፡ ሙስሊሞችን ደግሞ ይለቋቸዋል፡፡
በቀደም እለት አይሲስ በባህር ዳርቻ የሰዋቸው ክርስቲያኖች የመስቀል ማህተብ የነበረባቸውን መርጦ ነው፡፡ እነርሱን በተለየ ኮንቴይነር አስቀምጧቸው ነበር።” ይሄንን መረጃ የነገረኝ ሰው ሊገደሉ ተመርጠው ከተለዩት ወገን ነበረ፡፡ ሌሎች በኮንቴይነር ያስቀመጣቸው ክርስቲያኖችም አሉ። ምናልባት ከዚህ የከፋ ዜና እንሰማ ይሆናል። አምላክ ይጠብቀን።
አሁንም የአይሲስ አራጆች የመንግሥት ወታደሮችን ልብስ ለብሰው ሌሎች ስደተኞችን እየያዙ ነው፡፡ይሄ መረጃውን ያደረሰኝ ሰው ሊያመልጥ የቻለው ሌሎች ክርስቲያኖችን በጨለማ ወደ ኮንቴይነሩ ለማስገባት ኮንቴይነሩን በከፈቱበት ጊዜ ነው፡፡ የተወሰኑ ተያዦች አምልጠው ነበር። አንዳንዶች ተያዙ፡፡ ሦስቱ ግን አመለጡ። ሁለቱ የት እንደደረሱ አያውቅም፤ እርሱ ግን በእግዚአብሔር ቸርነት አምልጦ ትሪፖሊ ገብቷል፡፡
እባካችሁ ሰሞኑን ለመጓዝ የተነሱት ቢያንስ ለጊዜው ይታገሱ፡፡ ሱዳን ያሉትም ከሱዳን አይውጡ። መንገዱ በአይሲስ አራጆች ተይዟል። ለማታለልም የመንግሥት ወታደሮችን ልብስ ለብሰው ድንበር ጠባቂ ይመስላሉ፡፡
እግዚአብሔር በእጃቸው የተያዙትን እንዲታደግ እንፀልይ!!
 (ዲ/ን ዳንኤል ክብረት ከፌስ ቡክ የተገኘ)

ቅድስት ቤተክርስቲያን በሊቢያ ለተሰውት ወንድሞቻችን በቅዱስ ሲኖዶስ ደረጃ በቀኖናዋ የምትሰጠውን ስያሜና ክብር ስንጠባበቅ ነበር። ባለፈው ማክሰኞ ማታ ቤተ ክርስቲያኗ በEBC በሰጠችው መግለጫ፤ “ስለ ሃይማኖት የተጋደሉ መስተጋድላን” ብላቸዋለች።
በዘመናችን የሰማዕትነት ወግ ያሳዩንን የሃይማኖት ጀግኖች፤ ሠዓሊና የግራፊክስ ባለሙያ ወንድማችን ዘሪሁን ገ/ወልድ፤ በኢትዮጵያዊ የአሳሳል ዘዬ “በከመ ተወክፎሙ እግዚእነ ለሰማዕታተ ሊቢያ ዘተመትሩ በእንተ ስሙ” (ስለስሙ የተገደሉትን የሊቢያ ሰማዕታት ጌታችን እንደተቀበላቸው) የሚያሳይ ስዕል አዘጋጅቶልናል፡፡ ከቁጭታችን የተነሳ አሰቃቂ የሆነውን የሰማዕታቱን ቪዲዮና ፎቶዎች ፖስት ከማድረግ ይልቅ ይህንን ምስል መጠቀም እንችላለን። በደም የታጠቡት ምስሎች መሰራጨታቸው ለገዳዮቹ የፈለጉትን የማስታወቂያ ሥራ የሚሰራ ሲሆን ለሰማዕታቱ ቤተሰቦችና የቅርብ ወዳጆች ግን ከፍተኛ ሰቀቀን መሆኑን ልብ ልንል ይገባል። ሰሞኑን ሁለቱ ሰማዕታት ከኤርትራ ናቸው የሚል ዜና ተሰምቷል፡፡ ከኤርትራ ቀርቶ ከየትም ቢሆኑ ቤተክርስቲያን ምስክርነታቸውን እንጂ ፓስፖርታቸውን አትመለከትም፡፡ ቤተክርስቲያን በስንክሳር አምነው ሳይጠመቁ ለሰማዕትነት የበቁና በደማቸው የተጠመቁ ብዙ ሰማዕታት አሏት፡፡
የሰማዕታቱ ደምና መከራ ቅድስት ቤተክርስቲያናችንን ወደ መንፈሳዊ ተጋድሎ ዘመንዋ የሚመልሳትና አንድ የሚያደርጋት ይሁንልን፡፡ ከሃይማኖት የወጡ በምግባርም ያፈነገጡ፣ እረኛን በማጣት የተበተኑ ምእመናን የቤተ ክርስቲያን ልጆችንም የሰማዕታቱን ደም ምክንያት አድርጐ ወደ በረቱ ይመልስልን!
ተመስገን ዘገየ (አዲስ አበባ)

  • ከ2 ዓመት በላይ ወጣቷ የት እንደገባች አልታወቀም
  • ኤጀንሲው የተጣለበት የፈቃድ እገዳ ተግባራዊ አልሆነም

    ከሁለት ዓመት በፊት አል-ኢስማኤል በተባለ የውጪ አገር የግል ሥራና ሰራተኛ አገናኝ ኤጀንሲ በኩል በሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የሥራ ኮንትራት ውሏ ፀድቆ ወደ ሳውዲ አረቢያ የተላከችው ወጣት ደብዛ መጥፋት እያወዛገበ ነው፡፡ ወጣቷ ላለፉት 27 ወራት የት እንደገባች የሚያመለክት አንዳችም ፍንጭ አልተገኘም፡፡ ሀያት አሊ መሐመድ በሚል ስም የካቲት 27 ቀን 2005 ዓ.ም ወደ ሳውዲ የተጓዘችው ወጣቷ፤
ከአገር ከወጣችበት ጊዜ ጀምሮ ከቤተሰቦችዋ ጋር አንዳችም ግንኙነት  ባለማድረግዋ ቤተሰቦችዋ የትና በምን ሁኔታ ውስጥ እንዳለች ሊያውቁ እንዳልቻሉ ይገልፃሉ። ወደ ሳውዲ የላካት ኤጀንሲ ሀያት አሊ ያለችበትን ሁኔታና የት እንደምትገኝ እንዲያሳውቃቸው ቤተሰቦቿ ኤጀንሲውን ቢጠይቁም ኤጀንሲው ምላሽ ባለመስጠቱ ለሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ማመልከታቸውን ተናግረዋል፡፡ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱም ኤጀንሲው ወጣቷ ያለችበትን ሁኔታ በአፋጣኝ ተከታትሎ እንዲያሳውቅ ያሳስባል፡፡ ኤጀንሲውም ሳውዲ ድረስ ሄዶ ወጣቷን ለማግኘት ቢሞክርም እንዳልተሳካለት ለሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አሳውቋል፡፡ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱም ሀያት አሊ መሐመድ የተባለችው ወጣት በምን ሁኔታና የት እንደምትገኝ ተጣርቶ ምላሽ እንዲሰጠው ለውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ለቆንስላዎች ጉዳይ ክትትልና ድጋፍ ዳይሬክቶሬት ጥያቄ ያቀርባል፡፡
የቆንስላ ጉዳይ ክትትል ቢሮው በበኩሉ፤ ወጣቷ የምትገኝበት ሁኔታ ተጣርቶ እንዲገለፅለት ሪያድ ለሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጥያቄ ቢያቀርብም ከኤምባሲው ምላሽ ሊገኝ ባለመቻሉ የሃያት ቤተሰቦች እጅግ በከፋ ሃዘንና ሰቆቃ ውስጥ እንደሚገኙ  የወጣቷ እህት የኔነሽ አያሌው ለአዲስ አድማስ ገልፃለች፡፡ የወጣቷ ደብዛ መጥፋት በእጅጉ ያሳሰባቸው ቤተሰቦች፤ የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርን ጨምሮ ጉዳዩ ለሚመለከታቸው አካላት ሁሉ በተደጋጋሚ የአፋልጉን ጥሪ ቢያቀርቡም እስካሁን ምላሽ አለማግኘታቸውን የጠቆመችው የኔነሽ፤ ኤጀንሲው ተግባሩን በአግባቡ ባለመውጣቱ የሥራ ፈቃዱ እንዲታገድ በሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሐምሌ 24 ቀን 2006 ዓ.ም ትዕዛዝ ቢተላለፍበትም ኤጀንሲው አሁንም በስራ ላይ እንደሚገኝ ገልፃለች፡፡ ‹መንግስት ህገ ወጥ ስደትን እቃወማለሁ፤ ዜጎች በህጋዊ መንገድ ወደሚፈልጉበት አገር ለስራ መሄድ ይችላሉ› ባለው መሰረት፣ ዕድሉን ተጠቅማ በህጋዊ መንገድ የሄደችው እህቴ፤ ያለችበት ሳይታወቅ ሁለት ዓመት ከሶስት ወራት ማለፉ እጅግ የሚያሳዝንና ስጋት የሚፈጥር ነው ያለችው የኔነሽ፤
“የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ተረባርበው እህቴ ያለችበትን ሁኔታ እንዲያሳውቁንና ከስጋት እንዲያወጡን እማፀናለሁ” ብላለች፡፡ ስለጉዳዩ የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርን ለመጠየቅ ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ ሳይሳካልን ቀርቷል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ከመንግስት የቀረበበትን ውንጀላ ተቃውሟል

      በአሸባሪው ቡድን IsIs ታጣቂዎች አሰቃቂ ግድያ የተገፀመባቸው ኢትዮጵያውያን ሰማዕታትን ለመዘከርና ሽብርተኝነትን ለማውገዝ ባለፈው ረቡዕ መንግስት በጠራው ህዝባዊ ሰልፍ ላይ ተቃዋሚ ከፀጥታ ሃይሎች ጋር የፈጠሩት ግጭት የዓለም አቀፍ ሚዲጠያዎችን ትኩረት ስቧል፡፡በእለቱ በአልጀዚራ በተላለፈ ዘገባ፤ ህዝቡ በከፍተኛ ጩኸትና ቁጣ መንግስትን የሚተቹ መፈክሮችን እያሰማ ባለበት፣ በፀጥታ ሀይሎች የተወሰደው እርምጃ ታይቷል፡፡ ሰልፈኞች ሲደበደቡ የሚያሳዩ የተለያዩ ምስሎችም ተሰራጭቷል፡፡ የኢትዮጵያውያኑን በISIS ታጣቂዎች የመገደል አሰቃቂ ትዕይንት በተደጋጋሚ በምስል አስደግፎ ሲያቀርብ የነበረው ዩሮ ኒውስ፤ ረቡዕ እለት ምሽት ጀምሮ ሰልፉ ሲጀመር የነበረውን ሁኔታና በሰልፉ ማጠናቀቂያ ላይ ፖሊስ ከሰልፈኛው ጋር የተጋጨበትን ትዕይንት አሳይቷል፡፡ በዚህ አጭር የቪዲዮ ትዕይንት፤ መሬት ላይ የወደቁ ወጣት ሴቶች በፖሊስ ሲደበደቡ እንዲሁም አንድን ወጣት በርካታ ፖሊሶች መሬት ላይ በወደቀበት ሲደበድቡ ተስውሏል፡፡ ለረቡዕ እለቱ ሰላማዊ ሰልፍ ትኩረት ሰጥቶ የዘገበው ቢቢሲ በበኩሉ፤ ሰልፈኛው ያሰማውን ተቃውሞና
በመጨረሻም ፖሊስ የሃይል እርምጃ ሲወስድ የሚያሳይ ዘገባ አስተላልፏል፡፡ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ሰልፉ ከተከናወነ ከሰአታት በኋላ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ የታሰበው ሰልፍ በስኬት መጠናቀቁን ጠቁመው አንዳንድ ህገ ወጦች በሰልፉ ላይ ረብሻ ማስነሳታቸውንና ከዚህ ጀርባም የሰማያዊ ፓርቲ እጅ እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ ረብሻውን ተከትሎ በ7 የፌደራል ፖሊስ አባላት ላይ የመቁሰል አደጋ መድረሱን የጠቆሙት ሚኒስትሩ፤ በሰልፉ የተሳተፉ ሰዎች ላይ ጉዳት ስለመድረሱ የተናገሩት ነገር የለም፡፡ በእለቱ ሪፖርተራችን በመስቀል አደባባይ ተገኝቶ እንደተመለከተው፤ በተለይ በቅዱስ ዮሴፍ ት/ቤት አካባቢ በቡድን የተደራጁ ወጣቶች በከፍተኛ ጩኸት መንግስትን የሚያወግዙ መፈክሮች እያሰሙ
ሲቃወሙ እንደነበር ለመታዘብ ተችሏል፡፡ በሰላማዊ ሰልፉ ላይ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፤ ሽብርተኝነትን የሚያወግዘውን ንግግር እያደረጉ ሳለም ከፍተኛ ጩኸትና ተቃውሞ የተስተጋባ ሲሆን አንዳንዶችም ከፖሊስ ጋር ግጭት ፈጥረዋል፡፡ በመንግስት የተጠራውን ሰልፍ ተከትሎ፣ አብዛኞቹ የግልና የመንግስት መስሪያ ቤቶች ዝግ የነበሩ ሲሆን በከተማው አንዳንድ አካባቢዎች የታክሲ እጥረት ተፈጥሮ እንደነበርም ታውቋል፡፡  ፖሊስ ሰልፉን ለመበተን አስለቃሽ ጭስ የተጠቀመ ሲሆን በርካቶች በግርግርና በትርምስ መሃል ወድቀው ለጉዳት ተዳርገዋል፡፡ የቀይ መስቀል አምቡላንሶችም ተጎጂዎችን ወደ ዘውዲቱ መታሰቢያ ሆስፒታል ሲያመላልሱ የነበረ ሲሆን ቀላል ጉዳት የደረሰባቸው ግለሰቦች ከሰዓት በኋላ እየታከሙ

ከሆስፒታል ወጥተዋል፡፡ ፖሊስ በረብሻው መሃል ያገኛቸውን በርካታ ግለሰቦች በየቦታው በቡድን በቡድን ከሰበሰበ በኋላ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ሲያመላልስ እንደነበር የአይን እማኞች ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
መንግስት ተቃውሞውን አደራጅቷል ሲል የወነጀለው ሰማያዊ ፓርቲ፤ ረቡዕ ዕለት ማምሻውን ባወጣው መግለጫ፣ መንግስት የጠራውን ሰልፍ በመደገፍ አባላቱና ደጋፊዎቹ በሰልፉ ላይ እንዲገኙ ጥሪ ማስተላለፉንና ጥሪውን ተከትሎ እንደማንኛውም ዜጋ በሰልፉ ላይ የሄዱ የፓርቲው አመራሮችና አባላት ገና ወደ መስቀል አደባባይ ከመድረሳቸው በፊት እየታደኑ መታሰራቸውን አስታውቋል፡፡ ፓርቲው “መንግስታዊ ሽብር የህዝብን ቁጣ ያባብሳል እንጂ መፍትሄ አይሆንም” በሚል ባወጣው መግለጫው፤ “መንግስት በዜጎች ላይ የወሰደው የጭካኔ እርምጃ በእጅጉ የሚያሳዝንና በጥብቅ ሊወገዝ የሚገባው ነው” ብሏል፡፡ መንግስት፤ ረብሻውን ያነሳሳው ሰማያዊ ፓርቲ ነው ማለቱን አጥብቆ የተቃወመው ፓርቲው፤ “የመንግስትን ቸልተኝነት በተቃወሙ ሰዎች ላይ የተወሰደው እርምጃ ሳያንስ፣ ጉዳዩን ከአንዳንድ የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር አዛምዶ ተቃውሟቸውን ማጠልሸት በፍፁም ተቀባይነት የሌለው አፀያፊ ተግባር ነው፤ መንግስት ነኝ ከሚል አካል በፍፁም የማይጠበቅ ስህተት ነው” ብሏል፡፡ የፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች  የተገኙት እንደማንኛውም ዜጋ በሰልፉ ለመሳተፍ እንደሆነም ፓርቲው አስታውቋል፡፡ በእለቱም 8 ያህል የአመራር አባላቱ ከሰልፉ በፊት እና በኋላ ተደብድበው መታሰራቸውን ፓርቲው አስታውቆ፤ በየፖሊስ ጣቢያውም በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች መታሰራቸውን ለማረጋገጥ ችያለሁ ብሏል፡፡ሁለት የፓርቲው እጩ የምርጫ ተወዳዳሪዎችም ፖሊስ ጣቢያ ለታሰሩት የፓርቲው አመራሮች እራት ለማድረስና ለመጠየቅ በሄዱበት ወቅት መታሰራቸውን ፓርቲው አስታውቋል፡፡