Administrator

Administrator

በይግረም አሸናፊ የተፃፉ የልብወለድ እና ወጎች ስብስብ የያዘው “ክብሪት” ለገበያ ቀርቦ እየተነበበ ነው፡፡ በ137 ገፆች  20 ታሪኮችን ያካተተው መፅሃፉ፤ በብር 45.62 ለገበያ ቀርቧል፡፡

 “… ከገራገር ህይወቷ ላይ የሚከተላት ምሳሌ የፍስሃዋን በር የሚዘጋ ነገር አታጣም፡፡ በተፈጥሮ ያልሆነ በልጅ ሃሳብም ያልሆነ፣ በሴትነትም ያልሆነ የሚከተላት ጠልና ጥል እጇ ላይ ነጥሮ ይመጣል፤ አነጣጥሮ ይመታታል፡፡ በሩን ወደ ኋላ ዘጋችው። አይኖቿን ጨፍና አመታቱን አሰበች፡፡ ጠባሳዋን ቆጠረች፡፡ …”
(ከመፅሀፉ የተቀነጨበ)
በደራሲ ሊና ካሳሁን የተፃፉ ታሪኮችን ያካተተው “ፍቅር እና አደራ እና ሌሎችም” የተሰኘው መፅሃፍ ሰሞኑን ለአንባቢያን የቀረበ ሲሆን በዛሬው እለት ከቀኑ 9 ሰዓት ጀምሮ ከሬዲዮ ፋና ህንፃ ጀርባ በሚገኘው ወመዘክር አዳራሽ ይመረቃል፡፡
መፅሀፉ 11 ታሪኮችን የያዘ ሲሆን በ162 ገፆች እንደተቀነበበና በ40.50 ለገበያ መቅረቡ ታውቋል። የደራሲዋ ተከታይ ስራም “የእሳት እራት” የሚል ርዕስ ያለው እንደሚሆን ተጠቁሟል፡፡

  በደራሲና ዳይሬክተር ቴዎድሮስ ለገሰ ተፅፎ የተዘጋጀው “ያየ ይፍረደው” የተሰኘ የቤተሰብ ፊልም ባለፈው ማክሰኞ በአቤል ሲኒማ አዳራሽ ተመረቀ። በአልዩ ፊልም ፕሮዳክሽን የቀረበው ፊልሙ፤ የ1፡30 ርዝመት ያለው ሲሆን ፊልሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ 7 ወር እንደፈጀ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በፊልሙ ላይ ተዋንያን ቴዎድሮስ ለገሰ፣ አዚዛ አህመድ፣ ህፃን ማርያማዊት ፍፁም፣ ሔኖክ ብርሃኑና ሌሎችም አንጋፋና ወጣት ተዋንያን ተሳትፈውበታል፡፡

 ሀገሬ ሚዲያ ኮሙኒኬሽን፤ የደቡብ ጎንደር የቱሪዝም ማውጫ ዳይሮክተሪ አዘጋጅቶ አሳተመ፡፡ ማውጫው በ10 ወረዳዎችና በሁለት ከተማ አስተዳደሮች ግዛት ውስጥ የሚገኙ ከ100 በላይ ተፈጥሮአዊ፣ ባህላዊ፣ ታሪካዊና መንፈሳዊ መስህቦችን ያካተተ ነው ተብሏል። ከመስህቦቹ ውስጥ 80 በመቶው ከ250 ዓመት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረ ሲሆን ከ50 በመቶ የሚበልጡት ደግሞ ከ500 ዓመት በላይ ዕድሜ ያላቸው ታሪካዊ ቅርሶች እንደሆኑ ታውቋል፡፡
ማውጫው ሥፍራዎቹን ለመጎብኘት የሚያስችሉ መረጃዎች እንዲሁም የትራንስፖርትና ሌሎች አገልግሎቶች የሚገኙባቸውን አግባብ በሚጠቁም መልኩ መዘጋጀቱን የጠቆሙት አሳታሚዎቹ፤ ዳይሬክተሪው ከቱሪዝም ልማት ጋር ትስስር ላላቸው አካላት፣ ለቤተ - መፃህፍትና መንግስታዊና መንግስታዊ ላልሆኑ ተቋማት በነፃ እንደሚታደል ገልፀዋል፡፡
ሀገሬ ሚዲያ ኮሙኒኬሽን፤ በቱሪዝምና ባህል ላይ አተኩሮ የሚሰራ ተቋም ሲሆን ከዚህ ቀደም የሰሜን ሸዋ ዞን ቱሪዝም ዳይሮክተሪ፣ የኢትዮጵያ ተፈጥሮና ፓርኮች ማውጫ፣ የኢትዮጵያ ሙዚያም ማውጫና የኢትዮጵያ ፌስቲቫል ማውጫ አዘጋጅቶ ማሳተሙ ይታወቃል፡፡

ለአዘጋጁ የተሰጡትን መረጃዎች ለመሰብሰብ 7 ዓመት ፈጅቷል
                                          ዓለማየሁ ገላጋይ
     አንዳንድ ጊዜ ለወግ የማያመች ሁኔታ ይፈጠራል። ትዝ ይለኛል የዛሬ አስር ዓመት ገደማ ስለ ደበበ ሰይፉ ለመፃፍ ሳስብ ተማሪው ጀማነሽ ሰለሞንን በአጋጣሚ አገኘኋት፡፡ የደወለችልኝ ሌላ ጓደኛዬ ነበረች፡፡ ሶስና ዳንኤል ትባላለች፡፡ በወቅቱ የተለያዩ ቴአትሮች ላይ ትተውን ነበር፡፡ እሷን ለማግኘት ስሄድ ጀማነሽ አብራት ተቀምጣ አገኘኋት፡፡ ለዚህ አመክንዮአዊ ዓለም የማይዋጥ ገጠመኝ ነበር፡፡ አደግድጎ ሀሳብና ምኞታችንን የሚያደላድል አጋፋሪ አምላክ ይኖር ይሆን? አንዳንዴ በልባችን ያሰብነው ሰው ስልክ ይደውልልናል፣ ሌላ ጊዜ ያነሳነው ሰው አውግተን ሳንጨርስ ይመጣል …
ሶስና አስተዋወቀችን፡-
“እሱ አለማየሁ ይባላል፡፡ የኔሽን ጋዜጣ ጋዜጠኛ ነው፡፡ እሷ ደግሞ …
“እኔ እንኳን አውቃታለሁ” አልኩ፡፡
እኔን ማወቅህ አይደንቅም በማለት አይነት ዝም አለችኝ፡፡  በእርግጥም ስለመታወቋ የት? እንዴት? … ማለት አይጠበቅባትም፡፡ ጀማነሽ ናታ!
“ከልቤ ሳስብሽ ነው ያገኘሁሽ” አልኳት፡፡ ተዓምር የተመረኮዘ ባህታዊ ወይም ልዩ ትኩረት ፈላጊ ጉርባ እመስላት ይሆን?
በግርምት አየችኝ፡፡ አይኖቿ የአንደበቷን ያህል ውብ ድምፅ አላቸው፡፡ ከወፍ በመቀጠል ዘምረው ለመኖር ብቻ የተፈጠሩ ጥንዶች፤ ያለ ግብራቸው እንክብል ድምፆች እያነቡ ህይወትን ጨሌያማ አሸብራቂ የሚያደርጉ አይኖች----
 ስለ ምን በልቤ እንዳሰብኳት ነገርኳት፡፡
“ው … ይ፤ ስለ ጋሽ ደቤ ልትፅፍ ነው?” አለች፡፡ ያ በየሬዲዮውና በየመድረኩ የማውቀው ድምፅ መጣ፡፡ ይሄ ድምፅ ለብዙ ተዋናይ ሴቶች ተፅዕኖው አይሎባቸው ተናጥላዊውን የተፈጥሮ ችሮታ ንቀው፣በመምሰል መፍጨርጨር ውስጥ እንዲያልፉ አስገድዷቸዋል፡፡ ለምሳሌ መስታወት አራጋው….!!
ጀማነሽ፤ “ጋሽ ደቤ፣ ጋሽ ደቤ፣ ጋሽ ደቤ…” የበዛበት ጨዋታዋ ልቤን ወደ ሌላ መራው” ከመጣጥፍ ይልቅ መፅሐፍ ወደማዘጋጀት፡፡ ገጣሚው ደበበ፣ መምህሩ ደበበ፣ ተመራማሪው ደበበ፣ ፀሐፌ ተውኔቱ ደበበ … ከዚያ በላይ ደግሞ ሰው የሆነው ደበበ፡፡ ሐሜት የሚወጋው፣ ሽሙጥ የሚሸረክተው፣ አቃቂር የሚፈልጠው… ደበበ፡፡ አንዳንዴ የዩኒቨርሲቲ ግቢውንና ግቢኛዎቹን ምን እንዲህ አወረዳቸው? የሚያሰኝ ተራ ሐሜት፣ መናኛ ሽሙጥና የነተበ አቃቂር ይደመጣል፡፡ በተለይ ከወደ መንግሥቱ ለማ አቅጣጫ …
… እናም (ጀማነሽ ስትነግረኝ) ደበበ (ጋሽ ደቤ) በተለይ  ተማሪዎቹ የተራው ሐሜት ማስተጋቢያ መሆናቸው ይቆጨዋል፡፡ አንድ ቀን ከወትሮው በተለየ ስሜቱ ተጎድቶ ወደ ክፍል ገባ፡፡ ደበበ ሲያስተምር ከመደበኞቹ ተማሪዎች በተጨማሪ “ቃራሚዎቹም” ክፍሉን ይሞሉታል፡፡ ለተወሰነ ደቂቃ ዝም ብሎ ክፍሉን ሲመለከት ቆየ፡፡ ዘወር ብሎም ሁለት ቃላቶች ጥቁር ሰሌዳ ላይ ፃፈ፡፡ “ቀጭን” እና “ወፍራም” ይላል የፃፈው። በመቀጠል እንዲህ ሲል ጠየቀ፡፡ “እስቲ አንዲት ቀጭን ሴት የምትመሰገንበትና የምትወደስበትን ቃላት ንገሩኝ” አለ፡፡
ተማሪዎች ታዘዙ፡-
“ሐመልማል” አሉ
“ጥሩ!” አለ
“ቀጭን እመቤት”
“ሌላ?” ብሎ ቢጠብቅም አልተገኘም፡፡ “እሺ የምትሰደብበትን ንገሩኝ”
“በልታ የማትጠረቃ!”
“እሺ”
“ሲባጎ!”
“እሺ”
“አፍንጫዋን ቢይዟት የምትሞት!”
“ሌላ?”
“አንድ ሀሙስ የቀራት፣ ቀትረ ቀላል …”
ከሀምሳ በላይ ስድብ ተሰብስቦ በ “በቃ” ቆመ፡፡
“አሁን ደግሞ ወፍራሟን አሞግሱ”
“ድንቡሼ፣ ሞንዳላ፣ ሰውነተ ሙሉ…” ጥቂት ተብሎ መቀጠል ሳይችል ቀረ፡፡
“አሁን ደግሞ ስድቧን እንይ; አላቸው፡፡
“በርሜል፣ ድብኝት፣ ዘረጦ፣ ድብክብክ፣ ዝፍዝፍ፣ ሞፎ፣ ገንፎ …”
“በቃ! በቃ! አያችሁ፣ ባህላችን ለማወደስና ለማድነቅ ሽምድምድ ነው፡፡ ከዚያ ይልቅ ለስድብ፣ ለሽሙጥ፣ ለማንኳሰስና፣ ስሜት ለመጉዳት የበለፀገ ነው፡፡ እናንተ የዚህ ተሳታፊ ከመሆን ይልቅ ለመለወጥ መጣጣር ነበረባችሁ፡፡”
የዚያን ቀን ሳያስተምር ጥሎ ወጣ፡፡ ከዚህ በላይ ትምህርት አለ? ጀማነሽ ጥሩ አስተዋይ ብቻ ሳትሆን ግሩም ተርጓሚ ናት፡፡ ገጠመኞቹን በጥሬው ሳይሆን ከእነ ትርጓሜው ታወሳለች፡፡ የደበበ ሰይፉ ውጣ ውረድ እንደ ፎቶ ግራፍ ግለሰብ ወካይ ብቻ አይደለም፡፡ የህብረተሰብ ጥሪት ብሎም የሀገር ሀብት ሊሆን የሚችል ነው - የወል፡፡ ታዲያ እንዴት የዚህ ጉምቱ ገጣሚ ህይወትና ክህሎት ሳይጠናቀር ቀረ? በምን ቢያንስ? ወይም በምን ብናንስ?
ደበበ ሠይፉ ከህይወት ባሻገር በክህሎትም የሥነ ጽሑፉ ቁንጮ ነው፡፡ “የብርሃን ፍቅር” እና “ለራስ የተፃፈ ደብዳቤ” ከተሰኙ የግጥም መጽሐፍቱ ባሻገር በፀሐፌ ተውኔትነቱም ስድስት ያህል ሥራዎችን አበርክቷል። ባለ አንድ ገቢር ተውኔቶቹ፡- “ሳይቋጠር ሲተረተር”፣ “እነሱ እነሷ”፣ “ከባህር የወጣ ዓሣ”፣ “እናትና ልጆቹ”፣ “እድምተኞች” እና “ክፍተት” ይሰኛሉ፡፡ ከእነዚህ ስራዎቹ በተጨማሪ በግጥምም ሆነ በተውኔት ላይ ልዩ ልዩ ጥናቶችን አቅርቧል፡፡ ታዲያ ምኑ ከማን አንሶ፣ ህይወትና ክህሎቱ ሳይደርሰን ቀረ? በምን? ለምን?
ሰባት ዓመታት ያህል ወደ ኋላ ልመልሳችሁ ነው። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቋንቋዎች ጥናት ተቋም፣ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ጽሑፍ ክፍለ ትምህርት አንድ የጥሪ ደብዳቤ በትኖ ነበር፡፡ የደብዳቤው ዓላማ በደበበ ሰይፉ ሥራዎችና የሕይወት ታሪክ ላይ ውይይት በማድረግ እየተዘጋጀ ላለው መጽሐፍ ግብአት መሰብሰብ ነበር፡፡
ዓላማውም ግቡም የሚያስቀር አልነበረምና በዕለቱ (ሚያዝያ 14 ቀን 2000 ዓ.ም) ባህል ማዕከል ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ተገኘሁ፡፡ በደበበ ሰይፉ ሥራዎችና የህይወት ታሪክ ላይ የሚያተኩረውን መጽሐፍ የሚያዘጋጁት አቶ ገዛኸኝ ጌታቸው ወደ መድረኩ ወጡ፡፡ መጽሐፉን የማዘጋጀት ተግባሩ በመካሄድ ላይ እንዳለ በመግለጽ፣ የደረሱበትን ሁኔታ አስታወቁን፡፡ በደበበ ቤተሰቦች ድጋፍ ታፍሮና ተከብሮ የቆየው የደበበ የቤት ውስጥ ቢሮ ተከፍቶላቸው ግብአቶችን ማሰባሰባቸውን አወሱን። ሌላው ቀርቶ ደበበ አውልቆ የሰቀለውን ኮት ከስምንት አመት በኋላ እንዲፈትሹ የተፈቀደላቸው እሳቸው ብቻ መሆናቸውን ገለፁ፡፡ ቢሮው ውስጥ የተገኙት ወረቀቶች እጅግ ጠቀሜታ ያላቸውና ብቸኞችም እንደሆኑ በድፍኑ አስረዱን፡፡ አንዳንድ የተገኙ ወረቀቶች የደበበን ጉዳትና በደል የሚመለከቱ የግል ማስታወሻዎች ናቸው ተባልን። እነዚህ ማስታወሻዎችና ያልተላኩ ደብዳቤዎች ውስጥ የተጠቀሱ ታዋቂ ሰዎች ስማቸው ለተወሰኑ ዓመታት ተገድፎ ትውልድ ካለፈ በኋላ እንዲካተቱ መወሰኑን አወሱን፡፡
በዚህ ክብደት የተጀመረ ሌላ የህይወትና የጥበብ ሒስ መጽሐፍ እንዳለ እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ “የአረንጓዴው ዘመቻ” አይነት ዝግጅት፣“የቀይ ኮከብ ዘመቻ” አምሳያ መቆርቆርና ቁጭት ተንፀባረቀ፡፡ ታዳሚዎች ስለ ደበበ ያላቸውን ገጠመኝ ወረወሩ። በአደባባይ ለማይናገሩ ስልክ ቁጥር የሚሰፍርበት ቅጽ ተበተነ፡፡ ምን ይፈጠር ይሆን? አልን፡፡ የማይጠቀሱት የደበበ ደመኞች እነማን ይሆኑ? አልን፡፡ መጽሐፉ መቼ ይጠናቀቅ ይሆን? አልን--
ከአመታት ጥበቃ በኋላ የቀይ ኮከብ ዘመቻ አምሳያው የመጽሐፍ ዝግጅት በቀይ ኮከብ አምሳያነት ከሸፈ ተባልን፡፡ ፀሐፊውም በጓድ መንግሥቱ አምሳያነት ከአገር “ፈረጠጡ” ተባልን። እንዴት? ለምን?...ማንም ያወቀ ሰው አልነበረም፡፡
“የማያዛልቅ ማህበር በጠጅ ይጀመራል” ነው ነገሩ፡፡ ቀድሞውንስ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እዚህ ጉዳይ ውስጥ ገብቶ ማፈድፈድ ነበረበት? አንድ ሰው የአንድን ግለሰብ ታሪክ ሲጽፍ በራሱ አግባብ የራሱን መረጃ ያሰባስብ እንጂ ዩኒቨርሲቲው እንደ “አረንጓዴው ዘመቻ” ሰብስቦ መፈክር እንዲሰማ ማደላደል ነበረበት? ደግሞስ ተቋሙ እዚህ ውስጥ እጁን ካስገባ ፍፃሜውን የመከታተል ግዴታ የለበትም? ግለሰቡ ከየአቅጣጫው ያሰባሰቡትን መረጃ እና መዛግብት ይዘው ከሀገር ሲወጡ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አይጠየቅም ነበር? ብዙ የቁጭት ጥያቄዎች አሉ፡፡
በደበበ ህይወትና ሥራዎች ላይ የሚያተኩረው መጽሐፍ ከፉከራ ግብአትነት ሳያልፍ ሰባት አመት ከሦስት ወር አለፈው፡፡
ባለፈው ሐምሌ 5 የደበበን 65ኛ ዓመት የልደት ቀን በማስመልከት ወንድሙ ዘንድ ስልክ መትቼ ነበር፡፡ ለሰባት ዓመታት ድምፁ ጠፍቶ የቆየው የደበበ መጽሐፍ ጉዳይ አሁን ተስፋ እንዳለው ተነገረኝ፡፡
“እንዴት?” አልኩ፡፡
“የተሰባሰበውን ዶክመንት ለማግኘት በኢሜይልና በስልክ አፈላልገን ምላሽ አጥተን ቆይተን ነበር፡፡ በኋላ ቢቸግረን ካናዳ የሚኖር ዘመድ ልከን፣ መጽሐፉን የሚያዘጋጀውን ሰው በግንባር እንዲያናግረው አደረግን። በመጨረሻ ዶክመንቱ ተመልሶልን እኛ እጅ ይገኛል፡፡”
ይገርማል፤ የደበበ ቤተሰቦች ከሰባት ዓመታት በኋላ መጽሐፉን የሚያጠናቅር ሌላ ሰው በማፈላለግ ላይ ናቸው፡፡ ይሄ በደል አይደለም? በደልነቱ ከቤተሰብነት አልፎ የአገር አቀፍነት ንክኪ የለውም? ጉዳዩ የሚያሳስብስ አይሆንም? “እንጀራ” ይሉት ጢያራ እየነጠቀ በወሰደብን ምሁራን ስንት ውጥናችን ጨንግፎ ይሆን? መጽሐፍ ጽፎ ሃሳብ ከማድረስ፣ በባዕድ አገር ታክሲ እየነዱ ህዝብ ማመላለስ እንዴት በለጠ? በምን? እዚህ ውስጥ የክብር ጥያቄ የለም? የቃልስ? ይደክማል! የዘመኑ ነገር ይደክማል!!

Saturday, 18 July 2015 11:49

የኪነጥበብ ጥግ

 (ስለ ፊልም)
ይሄ ፊልም 31 ሚ.ዶላር ፈጅቷል፡፡ በዚህ ዓይነት ገንዘብ የሆነ አገር መውረር እችል ነበር፡፡
ክሊንት ኢስትውድ
ፀሐፊ መሆን ትፈልጋለህ? መፃፍ ጀምር፡፡ ፊልም ሰሪ መሆን ትፈልጋለህ? አሁኑኑ በስልክህ ምስሎችን መቅረፅ ጀምር፡፡
ማቲው ማክኮናሄይ
ፊልም የጦር ሜዳ ነው፡፡
ሳም ፉለር
ኮሜዲ ለመስራት የሚያስፈልገኝ፡- መናፈሻ፣ ፖሊስና ቆንጆ ልጃገረድ ብቻ ነው፡፡
ቻርሊ ቻፕሊን
መልዕክት ማስተላለፍ ከፈልግህ፣ ዌስተርን ዩኒየንን ሞክር፡፡
ፍራንክ ካፕራ
የፊልም መጨረሻ ሁልጊዜ የህይወት መጨረሻ ነው፡፡
ሳም ፔኪንፓህ
የምታየው የምታየው ፊልም በሲኒማ ቤት ውስጥ መቀመጥህን ማስረሳት አለበት፡፡
ሮማን ፖላንስኪ
እያንዳንዱ ዳይሬክተር በትንሹ 10 መጥፎ ፊልሞች አሉት፡፡
ሮበርት ሮድሪጉዝ
ፊልም ስትመለከት የዳይሬክተሩን የሃሳብ ሂደት ነው የምትመለከተው፡፡
ኦሊቨር ስቶን
እየተመፃደቅሁ አይደለም፤ ነገር ግን ፊልሞቼ ከ1ቢ. ዶላር በላይ ገቢ አስገኝተዋል፡፡
ስቲቭ ጉተንበርግ
እያንዳንዱ ድንቅ ፊልም ባየኸው ቁጥር አዲስ መምሰል አለበት፡፡
ፊልም ስቀርፅ እንዴት መቅረፅ እንዳለብኝ ፈፅሞ አላስብም፡፡ ዝም ብዬ ነው የምቀርፀው፡፡
ማይክል አንጄሎ አንቶኒዮ
ሰዎች ፊልም ት/ቤት ገብቼ እንደሆነ ሲጠይቁኝ፤ “በፍፁም አልገባሁም፤ እኔ የገባሁት ፊልሞች ውስጥ ነው” እላቸዋለሁ።
ኳንቲን ታራንቲኖ
በተለይ በአስፈሪ ፊልሞች ወስጥ ለገፀባህሪያቱ ካልተጠነቀቅህ፣ ተመልካቾችህን እንደምታጣ ይሰማኛል፡፡ ማንም ጉዳዬ አይለውም፡፡ እናም ፊልሙ ሰዎች ሲገደሉ የማየት ሂደት ይሆናል፡፡
ድሪው ጎዳርድ
ከፊልሞች ጋር ምርጥ ተሞክሮ ያገኘሁት ምን ዓይነት ፊልሞችን ማየት እንዳለብኝ በማላውቅ ጊዜ ነበር፡፡
ዣን ፓል ጋውልቲር
ህይወቴን ጨርሶ ከፊልሞች ውጭ ላስታውስ አልችልም፡፡
ኢሌ ፋኒንግ
እንደ ዕድል ሆኖ ፈፅሞ ዝነኛ ለመሆን ፈልጌ አላውቅም፤ ፍላጐቴ ፊልም መስራት ብቻ ነበር።
ሴዝ ሮጀን

- አወዛጋቢው የአገሪቱ ምርጫ ማክሰኞ ይካሄዳል ተብሎ ይጠበቃል
- ክልላዊው ፍርድ ቤት ግጭቱን ማጣራት ጀምሯል
       በመጪው ማክሰኞ ይከናወናል ተብሎ ከሚጠበቀው የብሩንዲ ምርጫ ጋር በተያያዘ በአገሪቱ የተቀሰቀሰውን ግጭት መፍታት የሚቻልበትን ሁኔታ ለመፍጠር የአገሪቱ የፖለቲካ ሃይሎች በኡጋንዳው ፕሬዚዳንት ዩሪ ሙሴቬኒ አደራዳሪነት ውይይት ሊያደርጉ ነው ሲል አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ለወራት የዘለቀውን የብሩንዲ ግጭት ለማስቆምና በፖለቲካ ሃይሎች መካከል የተፈጠረውን ችግር በድርድር ለመፍታት ሙከራ ቢያደርግም ሳይሳካለት ቀርቷል ያለው ዘገባው፤ ዩሪ ሙሴቬኒ የአገሪቱን መንግስትና የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችን ለማደራደር ባለፈው ማክሰኞ ቡጁምቡራ መግባታቸውን ገልጿል፡፡
አምስት የምስራቅ አፍሪካ አገራትን በአባልነት በያዘው የኢስት አፍሪካ ኮሚዩኒቲ ድርድሩን እንዲመሩ ባለፈው ሳምንት የተመረጡት ሙሴቬኒ፣ በመጪው ማክሰኞ ይካሄዳል ተብሎ የሚጠበቀውን አወዛጋቢ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሰላማዊ ለማድረግና ተልዕኳቸውን ለማሳካት የቻሉትን ሁሉ ጥረት እንደሚያደርጉ አስታውቀዋል፡፡ ሙሴቬኒ ባለፈው ማክሰኞ ከብሩንዲ ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ ጋር በጉዳዩ ዙሪያ መወያየታቸውንም ዘገባው ገልጿል። ክልላዊው የምስራቅ አፍሪካ የፍትህ ፍርድ ቤት በበኩሉ፤ በብሩንዲ የተከሰተውን ግጭት በተመለከተ ከሳምንታት በፊት የቀረበለትን ክስ በታንዛኒያ መዲና አሩሻ ባለፈው ማክሰኞ የምርመራ ሂደት መጀመሩን አስታውቋል፡፡
ፓን አፍሪካን ሎየርስ አሶሴሽንና ኢስት አፍሪካን ሲቪል ሶሳይቲ ፎረም የመሰረቱት ክስ፣ የብሩንዲ የህገመንግስት ፍርድ ቤት ለግጭቱ መንስኤ የሆኑት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ በምርጫው መሳተፍ ይችላሉ በሚል ያስተላለፈውን ውሳኔ እንዲሻር የሚጠይቅ ነው ተብሏል፡፡
ፕሬዚዳንት ንኩሩንዚዛ ባለፈው ሚያዚያ ወር ላይ ህገ መንግስቱ ከሚፈቅድላቸው ውጪ ለሶስተኛ ዙር በፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ለመወዳደር ማስታወቃቸውን ተከትሎ በአገሪቱ በተቀሰቀሰውና ለወራት በዘለቀው ግጭት ከ77 ሰዎች በላይ ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውንና ከ100ሺህ በላይ ዜጎችም ወደ ጎረቤት አገራት መሰደዳቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡

     ከ10 አመታት በላይ የፕሮስቴት ካንሰር ህክምና ተከታትለዋል
   ደቡብ አፍሪካዊው የኖቤል የሰላም ተሸላሚ ሊቃነ ጳጳስ ዴዝሞን ቱቱ ባለፈው ማክሰኞ ባጋጠማቸው ህመም ኬፕታውን ውስጥ በሚገኝ ሆስፒታል ገብተው ህክምና እየተደረገላቸው እንደሚገኙ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ምንነቱ በውል ባልተገለጸ በሽታ ተጠቅተው ሆስፒታል የገቡት የ83 አመቱ ዴዝሞን ቱቱ፤ ከአስር አመታት በላይ የፕሮስቴት ካንሰር ህክምና ሲደረግላቸው እንደቆየ ያስታወሰው ዘገባው፣ ወደ ሆስፒታል ያስገባቸው የሰሞኑ ህመም ግን፣ ከዚህ ጋር የተያያዘ መሆን አለመሆኑ አለመታወቁን ገልጿል፡፡ የዴዝሞን ቱቱ ልጅ ሞህ ቱቱ አባቷ ተገቢውን ህክምና በማግኘት ላይ እንደሆኑና በጥቂት ቀናት ውስጥ አገግመው ከሆስፒታል ይወጣሉ የሚል ተስፋ እንዳላት መናገሯን ዘገባው ጠቁሞ፣ ኢንፌክሽን ከመሆኑ ውጪ የህመማቸውን ምንነት በተመለከተ ዝርዝር መረጃ አለመገኘቱን ጠቁሟል፡፡
ከአስር አመታት በላይ በፕሮስቴት ካንሰር ህክምናቸውን ሲከታተሉ የቆዩት ዴዝሞን ቱቱ፣ ባለፈው ታህሳስ ወር ላይም ወደ ሮም ለመጓዝ ይዘውት ነበረውን እቅድ ህክምናቸውን ለመከታተል ሲሉ መሰረዛቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
የአፓርታይድ አገዛዝን በጽናት በመቃወም የሚታወቁት ዴዝሞን ቱቱ፤ እ.ኤ.አ በ1984 የኖቤል የሰላም ሽልማትን እንደተቀበሉና ከቀናት በፊትም ከባለቤታቸው ሊያ ጋር የጋብቻቸውን 60ኛ አመት በዓል ማክበራቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ባለፈው ግንቦት በምርጫ አሸንፈው ስልጣን የያዙት አዲሱ የናይጀሪያ ፕሬዚዳንት ሙሃማዱ ቡሃሪ፣ አሸባሪውን ቡድን ቦኮ ሃራም ለመደምሰስ የያዙትን ቀዳሚ እቅዳቸውን በአግባቡ ለማሳካት በሚል የቀድሞ የአገሪቱ የምድር ጦር፣ የባህር ሃይል፣ የአየር ሃይልና የመከላከያ መሪዎችን ከስልጣናቸው ማባረራቸውን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡
የቀድሞው የናይጀሪያ ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን ባለፉት ስድስት አመታት በአገሪቱ ሰሜን ምስራቃዊ አካባቢዎች 13ሺህ ያህል ዜጎችን ለህልፈተ ህይወት በዳረገውና 1.5 ሚሊዮን ዜጎችን ባፈናቀለው ቦኮ ሃራም ላይ ተገቢ እርምጃ አልወሰዱም በሚል በስፋት ሲወቀሱ እንደቆዩ ያስታወሰው ዘገባው፣ አዲሱ ፕሬዚዳንት ቡሃሪ የሽብር ቡድኑን ሙሉ ለሙሉ ለመደምሰስ እንደሚሰሩ ቃል መግባታቸውንና የጦር መሪዎችን ማባረራቸውም የዕቅዳቸው አንዱ አካል መሆኑን ገልጿል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ከስልጣናቸው ያባረሯቸው የጦር መሪዎች፡- ማርሻል አሌክስ ባዴህ፣ ሜጀር ጄኔራል ኬንዝ ሚናማህ፣ ሪር አድሚራል ኡስማን ጂብሪንና ምክትል ማርሻል አዴሶላ አሞሱ ናቸው ተብሏል፡፡
በምርጫው አሸንፈው ስልጣን ከያዙ፣ የመጀመሪያ ተልዕኳቸው የሚያደርጉት ቦኮ ሃራምን መደምሰስ እንደሆነ ሲገልጹ የነበሩት ቡሃሪ፣ ግንቦት ወር ላይ ስልጣን ከተረከቡ በኋላ፣ የአገሪቱን የመከላከያ ዕዝ መቀመጫ የአሸባሪ ቡድኑ መፈጠሪያ ናት ወደምትባለው ሜዱጉሪ ማዛወራቸውንና፣ ቡኮሃራምን ለመደምሰስ ያለመውን የአገራት ጥምር ሃይል ማዘዣ ጣቢያም በቻድ መዲና ጃሜና ማቋቋማቸውንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡

ጥርስ ድህነት አይታየውም፡፡
የማሳዮች አባባል
ትዕግስት ከሌለህ ቢራ መጥመቅ አትችልም።
የአቫምቦ አባባል
የእንቁላል ቅርጫት ተሸክመህ አትደንስ፡፡
የአምቤዴ አባባል
የአይጥ ልጅ አይጥ ናት፡፡
የማላጋሲ አባባል
ላልተወለደ ልጅ ስም ማውጣት አትችልም።
የአፍሪካውያን አባባባል
በሽምግልናህ የተቀመጥክበት ቦታ በወጣትነትህ የቆምክበትን ቦታ ያሳያል፡፡
የዩሩባ አባባል
የሚሸሽን ሰው አትከተለው፡፡
የኬንያውያን አባባል
ቤት ስታንፅ ምስማሩ ቢሰበርብህ፣ ማነፁን ትተወዋለህ ወይስ ምስማር ትቀይራለህ?
የሩዋንዳውያን አባባል
እናቱ የሞተችበት ጥጃ የራሱን ጀርባ ይልሳል።
የኬንያውያን አባባል
ንዴትና እብደት ወንድማማች ናቸው፡፡
የአፍሪካውያን አባባል
አንዲት ደስታ መቶ ሃዘኖችን ታዳብራለች፡፡
የቻይናውያን አባባል
 ፍቅር ለአሉባልታ ጆሮ የለውም፡፡
የጋናውያን አባባል
ሙሉ ጨረቃ ከወደደችህ፤ የክዋክብቶቹ ለምን ያስጨንቅሃል?
የቱኒዚያውያን አባባል