Saturday, 22 December 2012 10:15

የምርጫ ቦርድ ሃላፊዎች ከአሜሪካ ምርጫ የተማሩትን ያሳዩን!

Written by  ኤልያስ
Rate this item
(3 votes)

የዛሬ ፖለቲካዊ ወጌን በጥያቄ ነው የምጀምረው (መልስ የማይፈልግ ጥያቄ እኮ ነው!) እኔ የምላችሁ … ከመቼው ክርክሩ ተጀመረ ? (የምርጫውን ማለቴ እኮ ነው!) ሰሞኑን ሦስት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከገዢው ፓርቲ ጋር “ሞቅ ያለ ክርክር” ሲያደርጉ አላያችሁም? (ኢቴቪ ውሎ ይግባ!) እናላችሁ --- በቲቪ መስኮት ሦስቱን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ብቻ ስመለከት የተቀሩት ተቃዋሚ ፓርቲዎች የት ገብተው ነው ብዬ ሳወጣ ሳወርድ ሰነበትኩላችሁ፡፡
(ባልጠፋ ተቃዋሚ ሶስት ብቻ!) ቆይ ግን ባለፈው ሰሞኑን ለጠ/ሚኒስትሩ ደብዳቤ ልናስገባ ነው ያሉት 33 ተቃዋሚዎች የት ገቡ? በምርጫው አይሳተፉም እንዳትሉኝና እንዳይገርመኝ! (የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ቀለጠ በሉኛ!) ለነገሩ ሰሞኑን ምርጫ ቦርድ በሰጠው መግለጫ፣ ከሚያዝያ ምርጫ ጋር ተያይዞ ያቀረቧቸው ቅሬታዎች በሙሉ ውድቅ መደረጋቸውን አስታውቋል፡፡
ለሞራላቸው ብሎ እንኳን ግማሹን ቅሬታ ቢቀበላቸው ምናለበት? (ልብ አድርጉ በቦርዱ እየፈረድኩ አይደለም!) ከሁሉም ያስገረመኝ ግን ምን መሰላችሁ? ተቃዋሚዎች ያቀረቡትን ጥያቄ ለመመለስ ቦርዱ ወር ሙሉ ተወያይቶ በስተመጨረሻ “በማስረጀ አልተደገፈም” የሚል ምላሽ መስጠቱ ነው፡፡

ይሄን ዓይነት ምላሽ ለመስጠት ወር ሙሉ ውይይት ትንሸ አልበዛም፡፡ በእርግጥ የጊዜ ችግር እንደሌለብን አውቃለሁ፡፡
አንድ ጥያቄ አለኝ - ለኢህአዴግ፡፡ ለምንድነው እንደራደር ወይም እንወያይ ሲባል ቅድመሁኔታ የሚያስቀምጠው፡፡ መቼም በአንድ ጉዳይ የምንስማማ ይመስለኛል፡፡ ውይይቱ ስለ አገር እንጂ የግል ጉዳይ አልመሰለኝም (ስለህዝብ ማለቴ ነው!) እናም ኢህአዴግ ህጋዊ ናቸው ከሚባሉት ተቃዋሚዎች ጋ ሁሉ መወያየትና መደራደር ነበረበት፡፡ ተቃዋሚ እየመረጡ መደራደርማ “ፌይር” አይደለም፡፡
እኔ የምለው ግን--- የምርጫ ስነ ምግባር ኮዱን ያልፈረመ ከኔ ጋር መደራደር አይችልም ማለት ተገቢ ነው እንዴ? (ኤርትራ ኮዱን ፈርማለች ማለት ነው?) …ለሚያዝያው ምርጫ በተጀመረው የቲቪ ክርክር ላይ ሦስት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ብቻ መሳተፋቸው ግን ምን ይባላል? እኛ እኮ ህጋዊ ፓርቲዎች በሙሉ ለክርክር ቀርበው “እጃችሁ ከምን?” ልንላቸው እንፈልግ ነበር፡፡
እናም የአገሬ ፓርቲዎች በሙሉ በተቻለ አቅም የየግል እልሃቸውን ወደ ጐን ትተው ለእኛ የሚጠቅመንን ብቻ ቢያደርጉልን ምስጋናችን ወደር የለሽ ነው፡፡ የምርጫ ቦርድ ደግም ከታዛቢነት ወደ ተንቀሳቃሽነት ቢሸጋገር መልካም ሳይሆን አይቀርም (ሥራው መታዘብ አይደለማ!) ለምሳሌ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ቅሬታዎችና ወቀሳዎች ሲቀርቡለት በፍጥነት ምላሽ ቢሰጥ እንደትልቅ ውለታ እንቆጥርለት ነበር (ስራው ቢሆንም!)
ምን እንደገረመኝ ታውቃላችሁ? 33 ተቃዋሚ ፓርቲዎች ለቦርዱ ላቀረቡት ጥያቄ ምላሽ ሳይሰጣቸው ለምን እንደቆየ በአንድ ጋዜጣ ላይ የተጠየቁ የቦርዱ ተወካይ፣ “የቦርዱ ሃላፊዎች የአሜሪካን ምርጫ ለመታዘብ ስለሄዱ ነው” ብለው ነበር፡፡ ታዝበው ብቻ ነው ወይስ ተምረውም ነው የመጡት? (የተማሩትን ያሳዩና!) ያለበለዚያ እኮ ለጉዞው የወጣው ወጪ ባክኖ ይቀራል፡፡ (አሜሪካ ስፖንሰር ቢያደርገውም እንኳን!)
በነገራችሁ ላይ ምርጫ ቦርድ አንዳንዴ ስህተት ሲሰራ ቢያምን እኮ ችግር የለውም፡፡ የመላዕክት ስብስብ አይደለማ!) እውነቴን እኮ ነው… ሁልጊዜ ለማስተባበል መከራውን ማየት የለበትም፡፡ ወደ ቅድሙ የድርድር አጀንዳ ልመልሳችሁ… ባለፈው ጊዜ ኢህአዴግ “መድረክ የስነ ምግባር ኮዱን ሳይፈርም ከእኛ አገር አይደራደርም” ማለቱን ስሰማ በጣም ነው የተናደድኩት፡፡ ራሱን እንደፈርጣማ ጐረምሳ ነው እንዴ የሚያስበው? … ከሆነ ችግር የለም… በዚሁ አቋሙ ሊቀጥል ይችላል (መቼም ሃይ የሚል የለም!) እኛ ግን እንደበሰለ ህዝብ፣ ለ21 ዓመት ስልጣን ላይ ከቆየ ፓርቲ ይሄን አንጠብቅም (አለመጠበቅ እኮ መብታችን ነው!) ተከታታይ ባለሁለት ዲጂት የኢኮኖሚ ዕድገት ማስመዝገቡ በእነ ዓለም ባንክ ከተረጋገጠለት ፓርቲም ፈፅሞ እልህ አይጠበቅም (ኢህአዴግን ምን ነካው!)
አያችሁ… ወንድ ልጅ ትዳር ሲመሰርትና ልጅ ሲወልድ እየሰከነ ይመጣል - ጉርምስናውና እልሁ እንደተረትና እንደ ትዝታ የሚወራ ይሆናል፡፡ ፓርቲም ለረዥም ዓመት ስልጣን ይዞ አገር ከመራ በኋላ ከላጤዎቹ ፓርቲዎች ጋር እልህና ፉክክር አይገጥምም፡፡ እንዲያ ካደረገም እንደ አንዳንድ ዋልጌ አባወራ ነው የሚቆጠረው፡፡ በዚህች አጋጣሚ በመጨረሻዋ የስልጣን መተካካት ሽግግር ላይ ያሉት የኢህአዴግ አመራሮች በምን ሊታወሱ እንደሚሹ (በታሪክ መዝገብ ማለቴ ነው) ከወዲሁ ቢያስቡበት አይከፋም እላለሁ፡፡ በጡረታ ዘመን ከመፀፀት አሁኑኑ ጠንቀቅ ቆንጠጥ ማለት አይሻልም? (ትዕዛዝ ሳይሆን ምክር እኮ ነው!) ይልቅስ ምን ደስ እንዳለኝ ታውቃላችሁ? እቺ መተካካት የምትለዋ የስልጣን ሽግግር ስትራቴጂ ወደተቃዋሚዎችም እየተጋባች መሆኗ ነው፡፡
(1ለ5 ግን ገና ነው!) እናላችሁ… የአንድነት ፓርቲ አመራር የነበሩት ዶ/ር ኃይሉ አርአያ በፈቃዳቸው ሃላፊነታቸውን እንደለቀቁ ሰምቼ ደስ አለኝ፡፡ የሳቸውን ቦታ የተረከበው ደግሞ new blood (ትኩስ ትውልድ!) መሆኑ የበለጠ አስደንቆኛል፡፡ የኢትዮጵያ ፖለቲካ እየተለወጠ ነው ልበል? (ኧረ ያድርግልን!)
ውይይትና ድርድርን በተመለከተ በአገራችን ፖለቲካ ላይ ጥናት ያደረጉ የውጭ አገር የፖለቲካ ጠበብቶች እንደሚሉት፤ የአገራችን ፖለቲካ ዋና ችግር በክብ ጠረጴዛ ዙሪያ ያለመወያየት ችግር ነው (ኢህአዴግ ሰሞቶ ይሆን?) እኔ የምለው ግን --- የአገራችን የፖለቲካ ሳይንቲስቶች መቼ ነው ስለኢትዮጵያ ፖለቲካ በነፃነት የሚተነትኑት? (የሶማሊያና የዳርፉር ፖለቲካ ሰለቸና!) መቼ ነው በኢቴቪ ቀርበው ስለ ገዢው ፓርቲና ተቃዋሚዎች ጥንካሬና ድክመት ሙያዊ አስተያየት የሚሰጡን? ችግሩ ከእነሱ ነው ከኢቴቪ? (ለመጠየቅ ያህል እንጂ መልሱንማ እናውቀዋለን!)
በቅርቡ የተጀመረውን የገዢው ፓርቲና የሦስት ተቃዋሚዎች የምርጫ ክርክር በኢቴቪ መስኮት የተከታተለ አንድ ወዳጄ ምን እንዳለኝ ታውቃላችሁ?
“አንተ ኢህአዴግ ገገማ ነው!”
“እንዴት?”
“በክርክሩም 1ለ5 ስትራቴጂን ተጠቅሟል!”
ወዳጄ ምን ማለቱ እንደሆነ ስላልገባኝ ነገሩን እንዲያብራራልኝ (እንዲያበራልኝ) ጠየቅሁት፡፡ ለካስ እሱ የሚያወራው በክርክሩ ወቅት ለፓርቲዎቹ ጥያቄ ስለሚያቀርቡት ታዳሚዎች ነው፡፡ ወዳጄ እንደሚለው ታዳሚዎቹም በጥቃቅንና አነስተኛ ተደራጅተው ነው ጥያቄያቸውን ለማቅረብ ወደ አዳራሹ የገቡት፡፡ (በ1ለ5 ሊል ፈልጐ እኮነው) እኔ ምን አልኩት መሰላችሁ? “ታዲያ 1ለ5 መደራጀት ሃጢያት ነው?” ለነገሩ እኔም እቺን ስታይል የኮረጅኳት ከአንድ የኢህአዴግ ባለስልጣን ነው፡፡ እሳቸው እንኳ እንዲህ ያሉት፣ ለትንሽዬ ጉዳይ ሳይሆን ለትልቁ የ“ሥልጣን” ጉዳይ ነበር፡፡ “ከ40-70 ዓመት አገር መምራት ምን ሃጢያት አለው?” ነው ያሉት እሳቸው (ምንም!) እስቲ አስቡት … አገሪቱን መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገራት ካላሰለፍኩ “ሞቼ እገኛለሁ” የሚል ቁርጠኛ ፓርቲ፣ ከ40-70 ዓመት ስልጣን ላይ ለመቀመጥ ቢመኝ ምኑ ላይ ነው ሃጢያቱ? (ኧረ ፅድቅ ነው!) ምናልባት ተቃዋሚዎች ሊቀየሙኝ ይችላሉ (ይቀየሙኛ!) እኔን ከሚቀየሙ ግን እንዴት ከኢህአዴግ እንደሚሻሉ ቢያሳዩን ይሻላቸዋል፡፡ ለምን መሰላችሁ? ገዢው ፓርቲ ከእኔ የተሻለ አማራጭ የለም ብሏላ (አበጀ!) እኛ የምንፈልገው ግን የተቃዋሚዎችን መልስ ነው፡፡ ዝም ካሉ እውነቱን ቢሆን ነው ብለን ኢህአዴግን እንቀበለዋለን (ታዲያ ምን እናድርግ?) በነገራችሁ ላይ … እኔም እኮ በኢቴቪ የምርጫ ክርክር ላይ ለፓርቲዎቹ ጥያቄዎችን ሲሰነዝሩ የነበሩትን ታዳሚዎች ተመልክቻቸዋለሁ፡፡ እናም በሆዴ ምን አልኩ መሰላችሁ? “ኢህአዴግ ፓርቲዎችንም ታዳሚዎችንም መርጦ ይችለዋል እንዴ?” (ሃጢያት ነው አልወጣኝም!) ሥራ እንዳይበዛበት ፈርቼ ነው! እኔ የምለው ግን… በዘንድሮ የአዲስ አበባና የአካባቢ ምርጫ ለምን ነፃነትን እስከ ጥግ ድረስ እንድናጣጥም አይፈቀድልንም? (ህገመንግስቱ እኮ ይፈቅድልናል!) ነፍሳቸውን ይማረውና የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ምን እንዳሉ ታስታውሳላችሁ?
ሥልጣንን ራሳችሁ ካልወሰዳችሁ ማንንም አይሰጣችሁም (We deserve it! በሉ ማለታቸው ነው) ምን አሰብኩ መሰላችሁ? የአሜሪካን ምርጫ ታዝበው የተመለሱ የምርጫ ቦርድ ሃላፊዎች፤ በሚያዝያው ምርጫ ለምን ተመክሮአቸውን ተግባራዊ አያደርጉትም? (የምርጫ ስርዓትና ደንብ መኮረጅ እኮ አያስጠይቅም) ለማንኛውም ግን ምርጫው ሌላው ቢቀር ሰላማዊ እንዲሆን እንደምንሻ ይታወቅልን (“እንከን የለሽ” ምርጫ በ97 ቀርቷል!) መልካም የምርጫ ዝግጅት በምርጫ ለሚሳተፉት!!

Read 3203 times