Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Saturday, 22 December 2012 09:55

በሩብ ዓመት ብቻ ከ72ሺ በላይ ዜጐች ወደ አረብ አገራት ተጉዘዋል

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ከ1ሺ በላይ ህገወጥ ኤጀንሲዎች አሉ ተባለ
ባለፈው ሩብ የበጀት ዓመት ከ72 ሺ በላይ ዜጐች ወደ አረብ አገራት እንደተጓዙ ተገለፀ፡፡ 72ሺ 438 ዜጐች ወደ ሳውዲ አረቢያና ኩዌት የተላኩ ሲሆን ከእነዚህ መካከል 68ሺ 474 የሚሆኑት ሴቶች ሲሆኑ 3ሺ 964 የሚደርሱት ደግሞ ወንዶች መሆናቸውን የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ በሚኒስትር መ/ቤቱ የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ግርማ ሸለመ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ በመ/ቤቱ ተመዝግበውና ህጋዊ ፈቃድ ወስደው ዜጐችን ወደተለያዩ የአረብ አገራት የሚልኩ ህጋዊ ኤጀንሲዎች ቁጥር 300 ሲደርስ ከ1ሺ በላይ በህገወጥ መንገድ ዜጐችን የሚልኩ ደላሎች አሉ፡፡

መ/ቤቱ ከተለያዩ ኤጀንሲዎች የጉዞ ፕሮሰሳቸውን አጠናቀው እና ባጅ ወስደው የመጡለትን ተጓዦች ተቀብሎ የሥራ ውላቸውን የማጽደቅና ስልጠና የመስጠት አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ታህሣስ 11 ቀን 2005 ዓ.ም በመ/ቤቱ በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ ከሃያ በላይ ዕድሜያቸው ከ13 እስከ 16 ዓመት የሆኑ ህፃናት የጉዞ ዝግጅታቸውን አጠናቀው ለስልጠናው ወደ ሚ/ር መ/ቤቱ መጥተው እንደተገኙ ተገልጿል፡፡
ህፃናቱ ዕድሜያቸው 26 ዓመትና ከዚያ በላይ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ፓስፖርት ይዘው መገኘታቸውን የጠቆሙት አቶ ግርማ፤ ሕፃናቱ በሰውነት አቋማቸውም ሆነ በስነልቡናቸው ለሥራ ዝግጁ የሆኑ አለመሆናቸው በመረጋገጡ ጉዟቸው እንዲሰረዝ ተደርጐ የማጣራት ሥራ እየተከናወነ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ኤጀንሲዎች ከሚ/ር መ/ቤቱ ፈቃድ በሚወስዱበት ወቅት ወደ ውጪ አገር ለሥራ የሚልኳቸው ዜጐች ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በላይ መሆናቸውንና ጠያቂው አገር በሚፈልገው የዕድሜ መጠን ላይ የደረሱ መሆናቸውን በማረጋገጥ መላክ ይኖርባቸዋል ያሉት ዳይሬክተሩ፤ ከህግና አዋጅ ውጪ ህፃናት ልጆችን ወደማያውቁትና መብታቸውን ለማስከበር ወደማይችሉበት አገር ለሥራ መላክ ህገወጥ አሠራር መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ይህ ተግባር በዜጐች ህይወት መቀለድ በመሆኑ ሚ/ር መ/ቤቱ አጥብቆ እንደሚቃወመውም ተናግረዋል፡፡
ህፃናቱን በመመልመል ለጉዞ ካዘጋጁአቸው ኤጀንሲዎች ጋር ግምገማ እያካሄዱ መሆኑንና ጉዳዩን በማጣራትም በቅርቡ እርምጃ እንደሚወሰድ፣ ቁጥጥሩም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አቶ ግርማ ተናግረዋል፡፡
ዜጐችን ወደተለያዩ አገራት የመላኩ ተግባር በከፍተኛ መጠን እየጨመረ ሲሆን ባለፈው አመት ብቻ 198ሺ 667 ዜጐች ወደተለያዩ አገራት ለሥራ እንደተላኩ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

Read 5803 times