Saturday, 15 December 2012 15:49

የኢትዮ ቴሌኮምና የፍራንስ ቴሌኮም ኮንትራት ትላንት ተጠናቀቀ

Written by  መታሰቢያ ካሳዬ
Rate this item
(1 Vote)

የቀድሞውን የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ኮርፖሬሽን ማኔጅመንት በመረከብ ከሁለት ዓመታት ከስድስት ወራት በፊት ኢትዮ ቴሌኮም ብሎ ሥራውን የጀመረው ፍራንስ ቴሌኮም፤ ኮንትራቱን ከትናንት በስቲያ አጠናቀቀ፡፡ ኩባንያው ኮንትራቱን በማጠናቀቁ ቢሰናበትም አራት የሥራ ኃላፊዎች ግን በኮንትራት እንዲቀጥሉ መደረጉን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡በ30 ሚሊዮን ዩሮ ክፍያ ሥራውን የጀመረው ፍራንስ ቴሌኮም ኮንትራቱን አጠናቆ እንዲሰናበት የተደረገበት ምክንያት ከብቃት ማነስ ጋር የተያያዘ እንደሆነ የጠቀሱት ምንጮች፤ መንግሥት ከኩባንያው ጠብቆት የነበረውን የኔትዎርክ አገልግሎት አሰጣጥ ጥራት ለማግኘት እንዳልቻለ ጠቁመዋል፡፡

ድርጅቱ የአገሪቱን የቴሌኮም ማኔጅመንት ሥራ ወስዶ ማስተዳደር በጀመረበት ወቅት ከ5ሺ በላይ ሠራተኞች በመቀነሳቸው ምክንያት ከፍተኛ ውዝግብ ተነስቶ የነበረ ሲሆን ኩባንያው በአዳዲስ ቴክኖሎጂዎችና በሙያው በቂ እውቀት ባላቸው ምሁራን አማካኝነት የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት ዝግጅቱን ማጠናቀቁን መግለፁ የሚታወስ ነው፡፡
የተባለው ጥራት ያለው አገልግሎት ለደንበኞች ሊደርስ ባለመቻሉ ኩባንያው ከመንግሥት ጋር ተደጋጋሚ ውይይቶች ሲያካሂድ እንደነበር ያወሱት ምንጮች፤ መንግሥት ኩባንያውን ወደ አገሪቱ አስመጥቶ ሥራ ባስጀመረበት ወቅት ይገኛል ብሎ ያሰበው ውጤት ሳይገኝ በመቅረቱ ኮንትራቱን ከማራዘም ይልቅ ማሰናበቱን እንደመረጠም ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጡን የኢትዮ ቴሌኮም ህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አብዱራሂም መሀመድን ለማግኘት ያደረግነው ሙከራ ስልጠና ላይ በመሆናቸው አቶ ብርሃኑ ለገሠን ተክተዋል በሚል ምላሽ ሳናገኝ ቀርተል፡፡ አቶ ብርሃኑ ለገሠን በስልክ ስለጉዳዩ ጠይቀናቸው ጥያቄያችሁን በፋክስ ልካችሁልን ለኃላፊዎች አሳይቼ ከተፈቀደልኝ ብቻ ነው ምላሽ የምሰጠው በማለታቸው ምክንያት ሳይሳካልን ቀርቷል፡፡

Read 3296 times