Saturday, 17 November 2012 11:36

ዲሞክራሲያችን “Made in …” ይለጠፍበት!

Written by  ኤሊያስ
Rate this item
(6 votes)

አርቲስቶች ከፖለቲካ የተፋቱት እስከ መቼ ነው?
የተለመደው የምርጫ ውዝግብ የተጀመረ ይመስላል - እዚህች ሸገር እምብርት ላይ፡፡ በእርግጥ የማስጀመርያው ተኩስ ገና አልተተኮሰም የጦቢያ ፓርቲዎች ግን እስኪተኮስ እንኳን አልጠበቁም፡፡ እናም በግንቦት ለሚካሄድ ምርጫ በጥቅምት ውዝግብ ተጀምሯል እያልኳችሁ ነው (በምርጫ ውዝግብ ሪከርድ ሳንሰብር አንቀርም!) ይሄ እንግዲህ ለአካባቢና ለአዲስ አበባ ምርጫ ነው፡፡ በ2007 ዋናው አገራዊ ምርጫ ላይ ምን እንደሚፈጠር የሚያውቀው አንድዬ ብቻ ነው (አይ የጦቢያችን ነገር!)

ለማንኛውም መራራውን የምርጫችንን እውነታ በቀልድ ትንሽ ጣፈጥ እናድርገው፡፡ ሁለት በምርጫ ዘመቻ ላይ ያሉ ፖለቲከኞች መንገድ ዳር ያለ ካፌ ጋ ይገናኙና ሻይ ቡና እያሉ ሊያወጉ ይስማማሉ፡፡ ከዚያም ተቀምጠው ብዙ አወጉ፤ ትኩስ ቡና ፉት እያሉ፡፡ ሊሄዱ ከመነሳታቸው በፊት ግን አንደኛው ፖለቲከኛ ከኋላ ኪሱ ቦርሳውን እየመዠረጠ “እኔን ለምን እንደሚመርጡኝ ታውቃለህ?” ሲል ጠየቀው ሌላውን ፖለቲከኛ፡፡ “በደግነቴ ነው፤ ሁልጊዜ ለአስተናጋጆቹ ዳጐስ ያለ ጉርሻ እሰጣቸውና እኔን እንድትመርጡኝ እላቸዋለሁ” በማለት ለአስተናጋጇ ብዙ ብሮች ጠቅልሎ በእጇ አስጨበጣት (ቲፕ ነው ጉቦ?) 
ሌላኛው ፖለቲከኛ ደግሞ ቀጠለ “እኔም እኮ ሁልጊዜ ላንተ ድምፅ እንዲሰጡ እወተውታቸዋለሁ … ግን ከአምስት ሳንቲም በላይ ቲፕ ሰጥቻቸው አላውቅም” አያችሁልኝ … የፖለቲካና የፖለቲከኞችን ተንኮል፡፡ እንዴ … ድምቡሎ ሰጥቶ ወዳጄን ምረጡልኝ ማለት እኮ እንዳትመርጡት ከማለት አይሻልም፡፡ ለነገሩ እሱም የፈለገው ያንኑ ሳይሆን አይቀርም፡፡ በነገራችሁ ላይ ይሄ ቀልድ የእኛ አይደለም፡፡ የአሜሪካኖቹ ነው፡፡ እኛማ መች በፖለቲካ ቀልድ እናውቃለን - ጠብ እንጂ! መች በፖለቲካ ሳቅ እናውቃለን - ለቅሶ እንጂ! መች በፖለቲካ መጨባበጥ እናውቃለን - ቡጢ እንጂ! መች በፖለቲካ ሰላም እናውቃለን - መቆራቆስ እንጂ! መች በፖለቲካ ፌሽታ እናውቃለን - ሃዘን እንጂ! ለዚህ እኮ ነው ምርጫችን “ቀውጢ” የሆነው፡፡ ለዚህ እኮ ነው ምርጫችን ውዝግብ ብቻ የሆነው፡፡ ለዚህ እኮ ነው ምርጫችን አስፈሪ የሆነው! ግን ደግሞ የቱንም ያህል ብንፈራው አይቀርልንም፡፡ ከምርጫና ከፖለቲካ ማምለጥ አይቻልም - ከደሙ ንፁህ ነኝ የለም፡፡
እኔ የምለው ግን … ለምንድነው አርቲስቶች የምርጫ ሰሞን ለኢህአዴግ ወይም ለተቃዋሚዎች ደግፈው የማይቀሰቅሱት? (አይቻልም እንዳትሉኝ!) እውነቴን ነው … በአሜሪካ ምርጫ ኦባማ ከፍተኛ የገንዘብ ድጋፍ ያገኙት ከሆሊውድ ዝነኞች እኮ ነው! እና ሲፈልጉ ሲንግል ለቀው፣ ካሻቸው በኮንሰርት አሊያም በፊልም ለምን ፖለቲከኞችን አይደግፉም? (ዜጐች አይደሉም እንዴ!) በእርግጥ ኢህአዴግ ሊከፋው ይችላል፡፡ ቢሆንም ግን አርቲስቶች ያሻቸውን የፖለቲካ ፓርቲ የመደግፍና የመምረጥ መብት ያላቸው ይመስለኛል (ተሳሳትኩ እንዴ?) እኔ የምለው … የምርጫ ህጋችንን ከየት አገር ነው የኮረጅነው? (ኩረጃ ማሳፈሩ ተረት ሆኗል ብዪ ነው)
ኢህአዴግን ጠልቼ የማልጠላው ለምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? ከኮረጀ የሚኮርጀው በዲሞክራሲም በኢኮኖሚም ከበለፀጉ አገራት እንጂ ከደከሙ አገራት አይደለም፡፡ ዝም ብዬ ላሞግሰው ፈልጌ እንዳይመስላችሁ! ሃቅ ስለሆነ ብቻ ነው፡፡ በኢህአዴግነት የምትጠረጥሩኝ ከሆነ ማስረጃ ላቀርብ እችላለሁ፡፡ ለምሳሌ … የፀረ ሽብር ህጉ ከየት ነው የተኮረጀው? የምርጫ ስነ ምግባር ኮዱስ? የሲቪክ ማህበረሰባትና የመያዶች አዲሱ አዋጅስ? ሁሉም እኮ በዲሞክራሲ የዳበረ ልምድ አላቸው ከተባሉ አገራት ቃል በቃል የተቀዳ ነው (መቼም ከቻይና አይቀዳ!) ይልቁንስ ምን እንደሚያስፈራኝ ልንገራችሁ … አብዛኞቹን ነገሮች ከዚህም ከዚያም እየኮረጅን አይደል! በተለይ ህግና መመሪያዎችን ከየአገራቱ ኢምፖርት አድርገን እዚህ እኮ ነው የምንገጣጥመው (ወይም የምንቀምመው) ለነገሩ ኢህአዴግ ጨዋ ስለሆነ መኮረጁን ነግሮን ነው እንጂ “Made in …” የሚል እኮ አይለጠፍበትም፡፡ ምን ሃሳብ እንደመጣልኝ ታውቃላችሁ (የተኮረጀ ግን አይደለም!) የአገራችን ዲሞክራሲ የተመረተበት አገር (Made in…) ቢለጠፍበት ጥሩ አይመስላችሁም? (የቻይናን ከአሜሪካው ለመለየት ብዬ እኮ ነው!) ያው የቻይና ዲሞክራሲ እንደ አንዳንድ ምርቶቿ ፌክ እኮ ነው፡፡ ትዝ ይላችኋል… ሴቶቻችንን ከቦይፍሬንዶቻቸው ሊያቀያይሟቸው የደረሰ የቻይና ጫማ መጥቶ ነበር እኮ (የሚያቃጥል!) የቻይና ዲሞክራሲ እንደዚያ ጫማ ነው (ፌክ!) ብቻ ሁሉ ነገር የተመረተበት አገር ስም ቢኖርበት ከመሸወድና ከመክሰር እንድን ነበር፡፡
እኔ የምለው… ገዢው ፓርቲ ለ21 ዓመታት የሙጥኝ ያለው “አብዮታዊ ዲሞክራሲ” ርእዮተ ዓለም አገሩ የት ነው? (የተመረበት ማለቴ ነው!) እርግጠኛ ነኝ አንድ ቀን ራሱ ኢህአዴግ የኮረጀበትን አገር ራሱ ይናዘዝልናል፡፡ የምርጫ (Election) ስታይላችንም የተመረተበት አገር ቢታወቅ ከብዙ ንትርክ ያድነን ነበር፡፡ ለምሳሌ… የ”ምርጫ” ስታይላችንን ኢምፖርት ያደረግነው ከቻይና ነው ከተባልን አርፈን እንቀመጣለን፡፡ (ፎርጅድ ናታ!)
አያችሁ …ሰሞኑን 34 ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከምርጫ ቦርድ ጋር ውዝግብ ውስጥ የገቡበት ምክንያት የምርጫ ስታይላችን ከየትኛው አገር ኢምፖርት እንደተደረገ (በኢህአዴግ ቋንቋ እንደተቀዳ) ባለማወቃቸው ነው፡፡ እስቲ አስቡት… የምርጫ ስርዓቱ “Made in China” ነው ቢባሉ በምርጫ ቦርድ ላይ ያላቸውን የገለልተኝነት ጥያቄ ሁሉ እርግፍ አድርገው ይተውት ነበር፡፡
እኔ የምለው ግን… ምርጫ በመጣ ቁጥር የፖለቲከኞችን ማለቂያ የሌለው ውዝግብ መስማት አለብን እንዴ? ለጊዜው ነው እንጂ የምርጫ ጊዜው ሲቃረብ ደግሞ ውዝግቡ ወደ ስድድብ፣ መዘላለፍ፣ መፈራረጅ፣ ከዛም ማስፈራራት መለወጡ አይቀርም እኮ! እንዴ… የታደሉትማ በምርጫ ሰሞን ከተፎካካሪ ፓርቲዎች የሚሰሙት አማራጭ ፖሊሲዎችንና በዕውቀትና በልምድ የበለፀገ፣ በሃላፊነት ስሜት የታጀበ፣ ለአገር መቆርቆር የሚንፀባረቅበት ክርክር ነው…እኛ ግን የፓርቲዎች የመዘላለፍና የመነቋቆር ሃራራ መወጪያ ሆነናል! (ዕድላችን ነው!)
ምን እንደገረመኝ ታውቃላችሁ? ልክ ምርጫ ሲደርስ ድምፃቸውን ሰምተናቸው የማናውቃቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሁሉ ከተፍ ይላሉ! (የተቃዋሚ ፓርቲዎች ችግኝ ማፍያ አለ እንዴ?) ደሞ እኮ እስከዛሬ ካየናቸው የተሻሉ ቢሆኑ በጄ እንል ነበር፡፡ ለነገሩ የምርጫ ሰሞን ብቻ ፖለቲከኛነታቸው ትዝ የሚላቸው ከሆነ ዋጋ የላቸወም (ኪራይ ሰብሳቢ ተቃዋሚ አለ እንዴ?) እኔ የምለው… አገርና ህዝብ ሊያስተዳድሩ ያሰቡት በፓርት ታይም (በትርፍ ጊዜያቸው) ነው ማለት ነው? (ሲያምራቸው ይቅር!) ኢህአዴግ እንኳንስ ለፓርት ታይም ፖለቲከኞች 21 ዓመት ሙሉ ከአጠገቡ ዞር ላላሉትም አልተቻለም፡፡ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ምን እንደጐደለ ታውቃላችሁ? creativity ፖለቲከኞቹ የፈጠራ ችግር አለባቸው፡፡ እስቲ አስቡት… 21 ዓመት ሙሉ እኮ የፖለቲካ ትግል ስትራቴጂያቸውን አለወጡም፡፡
እስካሁን ኢህአዴግን ለመርታት የተጠቀሙበት ዘዴ እንዳልሰራ አሳምረው ያውቃሉ…ግን ዛሬም ከትላንቱ ኮረኮንች መንገድ አልወጡም (የኮብልስቶንም መንገድ አለ እኮ!) በነገራችሁ ላይ ኮብልስቶንን እንድንጠላው ያደረገን የኢህአዴግ ችኮ ፕሮፖጋንዳ እንጂ ድንጋዩማ ጠቅሟል - ላነጠፉትም ላስነጠፉትም፡፡ ኢህአዴግ ነፍሴ ግን ሊያንጨረጭረን ስለፈለገ ለባለድግሪ ምርጥ የስራ ዕድል “እነሆ ኮብልስቶን!” እያለ እልሁን ተወጣብን፡፡ ይሄም ከተቃዋሚዎች የcreativity ችግር ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ እናላችሁ በግንቦት ወር ለሚካሄድ ምርጫ ከጥቅምት ጀምሮ ከምርጫ ቦርድ ጋር ንትርክ ጀምረዋል - ተቃዋሚዎች፡፡ ገና 6 ወር ገደማ እኮ ይቀረዋል - ምርጫው፡፡
እኔ የምለው… “የፖለቲካ ምህዳሩ ጠቧል”፣ “አባላቶቻችን እየተዋከቡ ነው”፣ “ገዢው ፓርቲ የህዝብ ንብረት በሆነው ሚዲያ ያሻውን እያደረገ ነው”፣ “ነፃ ፕሬስ ታፍኗል”፣ “ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች በሽብርተኝነት ስም ይታሰራሉ” ወዘተ… የሚለው ክስ መቼ ነው የሚቆመው? ልብ በሉ … ተቃዋሚዎች ሃሰት ነው የሚያወሩት አልወጣኝም፡፡ ግን እኒህን ክሶች ሲደረድሩ ዓላማቸው መፍትሔና ለውጥ ማምጣት ይመስለኛል (ድብቅ አጀንዳ ካላቸው አላውቅም) ባለፉት 20 ዓመታት በዚህ መንገድ ተጠቅመው ለውጥ አልመጣም፡፡ ስለዚህ ሌላ ስልት ይፈለጋ! እንዴ…የተቃውሞው መንገድ ካልሰራ እኮ የፍቅር መንገድም መጠቀም ወይም መሞከር ይቻላል፡፡
ከምሬ እኮ ነው…ስንት ዓመት ሙሉ ተቃውመውት፣ አንጓጠውት፣ ተችተውት፣ አውግዘውት፣ በህዝብ አስጠምደውት ወዘተ … የመጣ ለውጥ የለም አይደል (ኢህአዴግ ፍንክች ያባ ቢላዋ ልጅ እንዳለ ነው!)
ይሄ ደሄ ማለት ደግሞ የተቃውሞው መንገድ አላዋጣም ማለት ነው (ወይም አልቻሉበት ይሆናል) ስለዚህ ለምን በፍቅር አይሞክሩትም (በስታይል ይግቡበት ማለቴ ነው!) የጥላቻና የአክራሪነት ዜማ ሲያቀነቅን ለከረመ ፖለቲከኛ ከባድ ፈተና እንደሚሆን እረዳለሁ፡፡ ግን ፈተናውን ተጋፍጠው ማሸነፍ አለባቸው፡፡ ኢህአዴግን ለማሸነፍ ከመሞከራቸው በፊት ደግሞ ራሳቸውን ለማሸነፍ ይጣሩ፡፡ ራሳቸውን ሳያሸንፉ ግን እንኳን ኢህአዴግን ምርጫ ቦርድንም ማሸነፍ አይችሉም፡፡ እናም ከተሳካላቸው ኢህአዴግን በፍቅር (በስታይል) ለመርታት ይሞክሩ - (በማድነቅ፣ በማጨብጨብ፣ ጐሽ አበጀህ ወዘተ በማለት፡፡) ራሳቸውን ማሸነፍ ካቃታቸው ግን (በእልህና በጥላቻ) ከምርጫውም ከፖለቲካውም ራሳቸውን እንዲያገሉ ይመከራሉ፡፡ በነገራችሁ ላይ “ፍቅር ያሸንፋል” የተባለ የወጣቶች ተቃዋሚ ፓርቲ ለማቋቋም ስፖንሰር እያፈላለግሁ ነው፡፡ በተቃዋሚው ጐራም እኮ “መተካካት” ያስፈልጋል (በፍቅር!!)

 

Read 3530 times Last modified on Saturday, 17 November 2012 11:58