Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Saturday, 10 November 2012 14:56

የአማኑኤል በሮች

Written by 
Rate this item
(3 votes)

አማኑኤል ከገባሁ ዛሬ ልክ አንድ ወሬ ነው፡፡ ብዙም ያስገረመኝ እብድ አላየሁም፡፡ የተለመዱት አይነት ናቸው፡፡ ትንሽ አረቄው ከፈጠረብኝ አበሳ አገግሜ ግቢውን ስቃኝ አንድ ነገር አየሁ የሚገርም ነገር፡፡ የሆስፒታሉ ክፍሎች የበሮቹ መስታወቶች በሙሉ ረግፈዋል፡፡ በመጀመሪያ የገረመኝ እንዴት ሠው የእብዶች መታከሚያ የሆነ ሆስፒታል ሲሠራ መስታወት እንዲህ ያበዛል? እሱስ ይሁን ግን ማን ሠበራቸው? “ቆይ አሳይሃለሁ” አለኝ Substance 6፡፡ (በአልኮል፣ በሲጋራ፣ በጫት፣ በካናቢስና … በሚያመጧቸው ጣጣዎች እዚህ ሆስፒታል የገቡ ህመምተኞች ወይም “እብዶች” ሁሉ Substance ነው የሚባሉት፡፡ Substance abuse ያደረጉ ለማለት ነው፡፡) አልኮልንም ሆነ ሌላ ሱስ አስያዥ ነገር በወጉ፣ በመጠኑ እና በሥነ-ሥርዓት የሚጠቀሙ Substance Users ሲባሉ እንደኔ አረቄ ካልጠጣ መላ ሠውነቱ የሚንቀጠቀጥ ደግሞ Substance abuser ይባላል፡፡ (አሁን abuse የሆነው ማነው? Substance ወይስ እኔ?!) “ይኼውናልህ ልጁ፡፡” አለኝ Substance 6 አንድ ቀን፡፡ 6 የአልጋ ቁጥሩ ነው፡፡ “የቱ ልጅ?”“ያ የበሮቹን መስታወት የሚሠብረው”“የታለ?” በጉጉት ጠየቅሁኝ፡፡

“ያውልህ” አየሁት፡፡ በአሪፍ ሁኔታ አየሁት፡፡ ደስ የሚል ልጅ ነው፡፡ በምናቤ ልብሱን አውልቄ እንደ Petruvian Man ንድፍ አድርጌ አየሁት፡፡ ያምራል፡፡ ባለ 2 ሊትር የሀይላንድ ውሃ እየያዘ ነው የሚዞረው፡፡ ከገባ አራት ወሩ ነው አሉ፡፡ አንዲት ቃል ተናግሮ አያውቅም ይባላል፡፡ “ከተማው ውስጥ ያሉትን ባለ መስታወት በሮች ሰብሮ ሳይጨርስ ብለው አስገቡት፡፡ እዚህ ያለውን ጨረሰላቸው፡፡ አሁን ግን ትቷል” አለኝ Substance 6፡፡ “እንዴት ተወ?”“አንድ ቀን በደንብ አድርገው ቀጠቀጡት፡፡ ከዛ ሞዲኬት ወግተው አስተኙት፡፡ ከዛ በኋላ ተወ፡፡ ጨርሶ ግን አልተወም” “እንዴት ማለት?”“ከበር ጋ ምን እንዳያያዘው አይታወቅም፡፡ አሁን ደግሞ ግቢው ውስጥ ያሉትን በሮች ሁሉ ሲዘጋ ሲከፍት ነው የሚውለው”ተከታተልኩት፡፡        አንድ ነገር ታዘብኩ፡፡ ምንም አያወራም፡፡ ሌላ ነገር ታዘብኩ፡፡ በር ይወዳል፡፡ ሌላ ነገር ደግሞ ታዘብኩ፡፡ አንዲት በተለየ ስሜት፣ በጉጉት የሚያያት በር አለች፡፡ በፍቅር ነው የሚያያት፡፡ የካፊቴሪያው የውስጠኛ በር ናት፡፡ በረንዳውን አልፎ ሲገባ ያለችውን በር፡፡ ሌላም ነገር ታዘብኩ፡፡ የተዘጋ በር ካለ ይከፍታል ወይ ካለበት ሲወጣ በር ዘግቶ ይሄዳል እንጂ በጭራሽ እራሱ ላይ በር አይዘጋም፡፡ ልተዋወቀው ሞከርኩ፡፡ እምቢ አለኝ፡፡ ከአስታማሚው ጋር መቀራረብ ጀመርኩ፡፡ አስታማሚው አባቱ ናቸው፡፡ ሠላምታ ጀመርን፡፡ አንድ ቀን፡- “ቡና ልጋብዞት?” አልኳቸው፡፡ ሻይ ክበብ ሄድን፡፡ “ሻይ ነው የምፈልገው” አሉኝ፡፡ ሻይ እና አምባሻ አዘዝኩላቸው፡፡ ለራሴ ቡና፡፡ Small talk - ዋዛ ፈዛዛ እያወራን ቆየን፡፡ የተቀመጥነው ልጃቸው እየጎመዠ የሚያያት በር ጋ ያሉት ወንበሮች ላይ ነው፡፡ ስለ ልጃቸው እራሳቸው ወሬ ጀመሩ፡፡ “ስሙ ግን ማነው?” አልኩኝ እኔ፡፡ “ጎሣ” “የእርሶስ?”“ተክለማርያም”“በሽታው ምንድነው?”“ምኑ ታውቆ! በበር ነው የተለከፈው፡፡ ስንት እና ስንት      በር ሰብሮ ጨረሰ መሠለህ፡፡ በር አይወድም” እዚህ ጋ አቋረጥኳቸው፡፡ “ተሳስተዋል፡፡ በር አይጠላም፡፡ ይወዳል እንዲያውም፡፡” በመገረም አዩኝ፡፡ “አዎ እውነቴን ነው በር ይወዳል፡፡ አሁን ይህቺን በር …” በእጄ ነክቼ እያሳየሁዋቸው “በጣም ይወዳታል፡፡ እንዴት እንደሚወዳት እኔ አውቃለሁ”በመገረም አዩኝ፡፡ ጨዋታ ቀየርኩ፡፡ “ልተዋወቀው ፈልጌ አልቀርበኝ አለ” “አዎ ሠው አይቀርብም፡፡ መናገር ካቆመ ይኸው ድፍን አራት አመቱ” ይኼን እየተባባልን ጐሳ መጣ፡፡ አጠገባችን ያለውን ወንበር ስቦ ተቀመጠ፡፡ “አዎ ተክለማርያም… ይኼ ልጅ የሚለው እውነቱን ነው፡፡ በር እወዳለሁ” አለ፡፡ አባትዬው ደነገጡ፡፡ ትንፋሽ በሚመስል ድምፅ “በአራት አመቱ ዛሬ አወራ” አሉ፡፡ “ተክለማርያም፤ አንተ ሂድ እኔ ከእሡ ጋር ላውራ፡፡” አላቸው አባቱን፡፡ በማመንታት ተነስተው ሄዱ፡፡ “አደራህን” አይነት ጠቀሡኝ፡፡ ሳይነግረኝ በፊት ቡና አዘዝኩለት፡፡ በ “ብራቮ” አይነት እራሱን ነቀነቀ፡፡ Small talk አላስፈለገውም፡፡ “ስምህ ማነው?” አለኝ፡፡ “ሙአሊም”“ደስ የሚል ስም ነው፡፡ መአሊም ማ?”“አሸናፊ”“ሙአሊም አሸናፊ… ደስ ይላል” አለ፡፡ “አመሠግናለሁ፡፡ ያንተም ፊትህ ደስ ይላል፡፡” ያልኩትን ያልሠማ ይመስል፤ “በአረቄ እንደገባህ አውቃለሁ፡፡ ሠዎች ስላንተ ሲያወሩ እሠማለሁ፡፡ ሥራህ ምንድነው?” “መምህር”“አባቴን ስታዋራው የነበረው ስለ እኔ ነው አይደል?” “ስለ አንተ እና ስለ በር” ሁለታችንም በጉጉት የሚያያትን በር እኩል አየናት፡፡ ተሳሳቅን፡፡ “ይኼውልህ እኔን እየተከታተልከኝ ስለነበር ስለኔ የተወሠነ አውቀሃል፡፡ ማወቅ የምትፈልገው ግን ስለ በር ስለሆነ በአጭሩ ሁሉን ልንገርህ፡፡ ስህተቱ የሚጀምረው ከእናቴ ነው፡፡ እዚህ ጋ ተቀምጦ የነበረው ሠውዬ …” አባቱ የነበሩበትን ወንበር እየጠቆመ “…የእናቴ የህግ ባሏ ነው፡፡ የድንግልና ባሏ፡፡ በተክሊል ነው የተጋቡት፡፡ አንድ ቀን እናቴ ከሌላ ስትቀብጥ እኔን አረገዘች፡፡ ከዛ ወለደችኝ፡፡ ተክለማርያም የሱ እንዳልሆንኩኝ ያውቃል” ዝም አለ፡፡ “አዎ አትመሳሰሉም፡፡ እናትህ ቆንጆ ናቸው?” “ናት፡፡ ቆንጂዬ ናት፡፡ እኔ ግን የምመሥለው አባቴን ነው፡፡ ቆንጆ ነው እሱም፡፡ በጣም እንመሳሰላለን”“እና ከዛስ?”  “እናማ በሷ ጥፋት እኔን መበቀል፣ እኔን ማሠቃየት ያዘ፡፡ የምድር ሲዖል ታውቃለህ?”“አውቃለሁ፡፡” “እንደምታውቅ ታስታውቃለህ፡፡ እኔም አውቃለሁ በደንብ፡፡ ሌላ ሌላውን ተወው፡፡ የበሩን ልንገርህ፡፡ ለማንም ተናግሬ አላውቅም፡፡ ገበያ ሲሄዱ፣ መንደር ሲሄዱ፣ ማህበር ሲሄዱ፣ … የሚሄዱበት ደግሞ አበዛዙ … በቃ የትም ሲሄዱ በር ቆልፈውብኝ ነው፡፡ አንደኛ እሷ ከጐኑ እንዳትለይ አደረገ፡፡ ሁለተኛ እኔን ጨለማ ጎጆ ውስጥ እየቆለፈ ያሰቃየኛል፡፡ በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ አትልም፡፡” የሹፈት ሳቅ ሳቀ፡፡ “በቃ ይኼው ነው?”“ስታወራው በጣም ቀላል ይመስላል፡፡ ስትኖረው ገሃነም ነው፡፡” “ልክ ነው”ሁለታችንም ዝም አልን፡፡“ይኼን ለዶክተሩ አልነገርከውም?”“አልነገርኩትም፡፡ እኔ እሱን ብሆን ሳይነገረኝ አውቃለሁ፡፡ ደሞ ለምን አባቴ አይነግረውም?”“አልነገሩትም?”“አልነገረውም ባክህ ስራውን ያውቀዋላ፡፡ ምን ብሎ ያወራል! … ለዶክተሩ ብነግረው ምን ይፈይዳል? ምንም!”“You think so?”“Yes, I do!”“እና ምን ይሻልሃል?”“የኔ የመዳን ተስፋ በአንተ እና በእኔ እጅ ነው ያለው፡፡”“እንዴት?”“በኋላ እነግርሃለሁ”“ግን፣እንዴት አድርገህ እነዚህን በሮች ሁሉ ሠበርካቸው?”“እምወረውረው ከማይጠበቅ እርቀት እና አሳቻ ቦታ ሆኜ ነው፡፡ ወርውሬ አልስትም፡፡ ግራኝ ነኝ፡፡” ብሎ ሣቀ፡፡ “ይህቺን በር ትወዳታለህ አይደል?”“አዎ እወዳታለሁ”“ለምን?”“እሷን በር የሠበርኩ ቀን ነው የደበደቡኝ እና ሞዲኬት የወጉኝ፡፡ ከዚያ በኋላ በር መስበር ተውኩኝ፡፡ እና መክፈት እና መዝጋት ብቻ” በሀይለኛ ጉጉት አያት፡፡ “ዛሬ ልትዘጋት ትፈልጋለህ?”“አዎ”“ዝጋት”“ቢመቱኝስ?”“ጫፍህን አይነኩህም፡፡ እኔ አለውልህ፡፡” “እውነት በለኝ”“እውነት እውነት እልሃለሁ”“በር እላዬ ላይ ዘግቼ አላውቅም… አሁን አንተ ስላለህ አልፈራም፡፡ ልዝጋው?”“ዝጋው” ተነስቶ ጥርቅም አድርጐ ዘጋው፡፡ ብዙ ሠዎች ነበሩ፡፡ የሆስፒታሉ ሠራተኞች፣ የክበብ ሠራተኞች፣ በሽተኛ ጠያቂዎች፣ አዕምሮ ህመምተኞች…ብዙ ሰዎች ነበሩ፡፡ ሁሉም ሲያፈጡበት እና ሊከመሩበት ሲዳዱ፡- “አንድ ሠው እንዳይነካው!” ብዬ አምባረቅሁ፡፡ ሁሉም ደነገጡ፡፡ በደስታ መጥቶ አጠገቤ ተቀመጠ፡፡ የሆነ ነገር ቅልል እንዳለው ያስታውቃል፡፡ ወሬያችንን ቀጠልን፡፡ ጎሣ ሲያወራ ሲያዩ ሁሉም ተገረሙ፡፡ ወሬያችንን ቀጠልን፡፡ “ለምንድነው የመዳን ተስፋ ያለው በአንተ እና በእኔ እጅ ነው ያልከው?” ጠየቅሁት፡፡ በእርግጥም እንዲያ ማለቱ ገርሞኛል፡፡ እርግጠኝነቱ ነው የገረመኝ፡፡ “ና ዎክ እያደረግን እነግርሃለሁ፡፡” ብሎኝ በሩን ከፍቶ ወጣን፡፡ አሁን የሆነ ነገር የቀለለው መሠለ፡፡ ግቢው ውስጥ ዞርን፡፡ የሆስፒታሉ “ላይብረሪ” ጋ ስንደርስ፤- “ና ቆይ አንድ ነገር ላሳይህ” ብሎኝ እንደ ጦጣ የግቢው የድንጋይ አጥር ላይ እንጣጥ ብሎ ወጣ፡፡ በመገረም ሣየው ወዳለሁበት መሬት እየጠቆመ “ያቺን ድንጋይ አቀብለኝ፡፡” አለኝ፡፡ ወርውሬ አቀበልኩት፡፡ “ና …እኔ ወደ አለሁበት ውጣ፡፡”በመከራ ወጣሁ፡፡ “ያቺ ህንፃ ትታይሃለች?” ከአስፓልት ወዲያ ማዶ እየጠቆመ፡፡ “ትታይሃለች”“በግራ በኩል ያለችውን መውጪያ በር አየሀት?”“አየሁዋት”“ይኼውልህ!” አለ በጩኸት ግራ እጁን እያወናጨፈ፡፡ ክሽሽሽሽሽ … በድንጋጤ ዘልዬ ወረድኩ፡፡ ተከተለኝ፡፡“ማን እንደሠበረው መቼም አያውቁም፡፡ ሠይጣን የሠበረው ነው የሚመስላቸው፡፡” አለ “ሠይጣን ነህ?”“ከዛሬ ወዲህ በር አልሰብርም፡፡ መክፈት መዝጋቱንም እተዋለሁ” የምሩን ነው፡፡ “ዳንክ ማለት ነው?” “ማለት ነው፡፡ ጨርሶ ለመዳን ግን አንድ ነገር ይቀረኛል፡፡ ለሱ ደግሞ ያንተ ትብብር ያስፈልገኛል”“ጨርሶ ለመዳን ምንድነው የሚያስፈልግህ?” ነገረኝ፡፡ ዘገነነኝ፡፡ “አዎ ሁለቱንም በር ዘግቼ ባቃጥላቸው ደስ ይለኛል፡፡ ያኔ እድናለሁ” “አባትህስ ይሁኑ እሺ፡፡ እሱ ግን ምን አደረገ? ዶክተሩ ምን አደረገህ?” ግራ ተጋብቼ ጠየቅሁት፡፡ እያላበኝ ነው፡፡ “በነገራችን ላይ ሳልረሳው ልንገርህ… ነርሷን እወዳታለሁ፡ሠው ሣያየኝ ከሷ ጋር አወራ ነበር፡፡ … እና ዶክተሩ ምን አደረገ ነው ያልከው? ብዙ እብዶችን የበለጠ ያሳበዳቸው እሱ ነው፡፡ እሱ ነው እሱ ከቀናቴ ላይ ፀሀይቱን የሠረቀ፤ እሱ ነው እሱ በመንገዴ ላይ አሜኸላ ያፀደቀ” ያለው አሪፍ ገጣሚ ማን ነበረ? እና ደግሞ ሳቁን አልወደውም፡፡ ሁሌ እንደ ሳቀ ነው፡፡ ሲተኛም እየሳቀ ይሆናል፡፡ የውሸት ሳቅ ነው የሚስቀው፡፡ አልወደውም፡፡”“ለነገሩ እኔም አልወደውም፡፡ እጠላዋለሁ፡፡” አልኩት፤ እንደ ጎሳ በጥላቻ ተሞልቼ፡፡“ለምን?”“በአለም ላይ ከጌ ዳ ሞፖሳ ቀጥሎ ያለሁት እፁብ አጭር ልብ ወለድ ፀሀፊ እኔ ነኝ” ሥለው አሾፈብኝ፡፡ ሳወራ ሹፈቱ ቁልጭ ብሎ በአይነ ህሊናዬ እየታየኝ ነው፡፡ “ቆይ ዝም በል ዋጋውን ያገኛታል…ዋጋቸውን ያገኟታል” ተቃቀፍን፡፡ ስለ እቅዱ በዝርዝር አወራን፡፡ “መቼ ይሁን?” አልኩት፡፡ “ዶክተሩ የሚጎበኘን ሰኞ እና ሀሙስ ነው፡፡ ዛሬ እሮብ ነው፡፡ እና ነገ እናድርገው?”“እናድርገው”“ቤንዚኑን ዛሬ ታገኛለህ?”“አዎ አገኛለሁ፡፡ አረቄ የሚያስገባልኝ ልጅ እንዲያመጣልኝ አደርጋለሁ፡፡”ተቃቅፈን ተለያየን፡፡ ***እንቅልፍ አልተኛሁም፡፡ ጎሣም አልተኛም፡፡ ጠዋት ሳገኘው ፊቱ እንዳልተኛ ነገረኝ፡፡ በእጄ በባለ ሁለት ሊትር ሀይላንድ የያዝኩትን ቤንዚን ሲያይ ፊቱ ፈካ፡፡ ተቀበለኝ፡፡ “አንድ ነገር ቃል ግባልኝ” አልኩት፡፡ “ምን?”“ካስፈራራናቸው ይበቃል”ብዙ ካሠበ በኋላ “እሺ” አለኝ፡፡ ሁሌም እንደተለመደው ዶክተሩ በመጀመሪያ የሚያየው እሱን ነው፡፡ “ጐሳ ተክለማርያም” ብላ ፀይሟ ቆንጆ ነርስ ተጣራች፡፡ “አቤት” ብሎ ወደ እሷ ቀርቦ በስሱ ፀይም ጉንጯን ሳመ፡፡ አባቱ ደነገጡ፡፡ እሷ እየሳቀች ወደ ክፍሏ ገባች፡፡ እሱ እና አባቱ ተያይዘው ዶክተሩ ጋ ገቡ፡፡ ዶክተሩ የሆነ ነገር ሲያገላብጥ በመስኮት ይታየኛል፡፡ አሁንም እየሳቀ ነው፡፡ ጎሣ ገብቶ ምንም ያህል አልቆየም፡፡ በሚገርም ቅልጥፍና ቁልፉን ከውስጥ ነቅሎ በሩን ከውጪ ዘጋው፡፡ ከውስጥ አቶ ዶክተር እና አቶ ተክለማርያም በመገረም ሲተያዩ አቶ ጎሣ በመስኮት ብቅ ብሎ በሀይላንድ የያዘውን ቤንዚን ክፍሉ ውስጥ አርከፈከፈው፡፡ ከዚያ ክብሪት ጫረ፡፡ እሳት ነደደ፡፡ከሁሉም ቀድሜ እኔ ጮህኩ፡፡ ጎሣ መጥቶ አፌን አፈነኝ፡፡ ታግዬ ከጣልኩት በኋላ ቁልፉን ቀማሁት፡፡ ሮጬ በእሳት የተያያዘውን ክፍል በር ከፈትኩት፡፡ ሁለቱም እየተጓተቱ እየተጋፉ ወጡ፡፡ ዶክተሩ ጋዋኑንን አውልቆታል፡፡ የቻለውን ያህል ሮጠ፡፡ ግርግር፣ ጩኸት፣ ትርምስ … የእሳት አደጋ መኪና ሲጮህ ይሰማል፡፡ ዶክተሩን ፈለግሁት፡፡ እርቆ አንድ ጥግ ላይ በሁለት እጆቹ ጉልበቶቹን ተደግፎ ያስባል፡፡ ሄድኩ ወደ እሱ፡፡ “አይዞህ ዶክተር” አልኩት፡፡  “በጣም አመሰግናለሁ” አለኝ፡፡ በሩን ስከፍት አይቶኛል፡፡ “ዶክተር?” “እ?”“ከእኔ እና ከጌደ ሞፓሳ ማን ይበልጣል?”“እ?!” አይኑ ፈጧል፡፡ ደገምኩለት፡፡ “ከእኔ እና ከጌ ደ ሞፓስ ማን ይበልጣል?!” አልኩት ተናድጄ፡፡ (ተገርሜ፣ ተገርሜ ብሏል ዘፋኙ)“አንቱ፡፡ አይ አንተ ከማንም ትበልጣለህ” አለ የሞት ሞቱን፡፡ “አመሰግናለሁ”በአይኔ ጎሳን ፈለግሁት፡፡ አጥር ጥግ ላይ ቆሞ ይንከተከታል፡፡ ከዶክተሩ ጋ ምን እየተባባልን እንደነበር በደንብ ገብቶታል፡፡ በግርግሩ መሀል እኔና ጎሣ ከግቢ ወጥተን ጠፋን፡፡መውጫ በር፡-እኔና ጎሣ አሁን አብረን ነው የምንኖረው፡፡ አንድ ቀን ስለ Conditioning እያወራን ሳለ እንዲህ አልኩት፡- “የሆነ ቦታ ላይ ሳነብ በአለም ላይ ፈፅሞ Condition ሊደረጉ የማይችሉ ሁለት እንሥሣት አሉ የሚል አይቻለሁ፡፡ ስማቸውን እረሳሁት”“እኔ እና አንተ እንሆናለን… ሙአሊም እና ጎሣ፡፡”ተሳሳቅን፡፡ መግቢያ በር፡- ሳቃችንን ሳንጨርስ ወይም አውቀን አራዝመነው እያለ የቤታችን በር ተንኳኳ፡፡ በድንጋጤ ተያየን፡፡ ያንኳኳው ሠው ከፈተው፡፡ የአማኑኤሏ ነርስ በር ላይ ቆማለች፡፡ “ግቢ ወንጌላዊት” እኩል ነው የተናገርነው፤ እኔ እና ጐሳ፡፡ ገብታ መሀላችን ተቀመጠች፡፡ ማክሠኞ፣ መስከረም 22 ቀን 2005 ዓ.ም 

 

Read 4191 times Last modified on Saturday, 10 November 2012 17:07