መንግስት በአዲሱ የደሞዝ ጭማሪ ምክንያት ለ160 ቢለየን ብር ተጨማሪ ወጭ እንደሚዳረግ ገልጿል። እስኪ የጭማሪውን ፋይዳ ለመረዳት ቁጥሮችን በአንጻራዊ ስሌት እናጢናቸው።
ቋሚ ደሞዝተኛው ገንዘቡ ኪሱ ከመግባቱ በፊት በገቢ ግብር ምክንያት ዝቅተኛው ተከፋይ 15% ከፍተኛው ደግሞ 35% ይቆረጥበታል። ዝርዝሩ ውስጥ መግባት ስለሚያዳግት አማካዩን ቁጥር እንወሰድ።
አማካዩ (15+35)/2 = 25% ይሆናል። ወደፊት እድሜውና ጤናው ከፈቀደለት የጡረታ ተከፋይ የሚያደርገው ቢሆንም ዛሬ ላይ ለጡረታ 7% ከደሞዙ በቀጥታ ይቆረጥበታል። 25%+7% = 32% ይሆናል።
160,000,000,000*0.32= 51,200,000,000 ይሆናል። ይህ ማለት ሃምሳ አንድ ቢሊየን 200 ሚሊየን ብር የደሞዝ ጭማሪው ተቀጣሪው እጁ ከመድረሱ በፊት ወደ መንግስት ካዝና ይመለሳል። በደሞዝ መልክ የሚከፋፉለው ቀሪ 108,800,000,000 ብር ይሆናል።
ደሞዙ እጁ ላይ ከገባ በኋላ ደግሞ በሚሸምተው ቁሳቁስና በሚገዛው አገልግሎት ላይ 15% ቫት ይከፍላል። 108,800,000,000 *0.15 = 16,320,000,000 ይሆናል።
ይህ ማለት ደግሞ ከ160 ቢሊየን ብር ጭማሪ ውስጥ ደሞዝተኛውን ሳያገለግል በገቢ ግብር፣ በጡረታና በቫት ብቻ ወደ መንግስት ካዝና ተመልሶ የሚገባው ብር 67,520,000,000 ሲሆን ጭማሪው ደግሞ 92,480,000,000 ብር ይሆናል።
በመቀጠል ቀሪዎቹን ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆኑ የግብር ዓይነቶች እናንተው አስሏቸው። ፕሮፐርቲ ታክስ (1%)፣ ተርን ኦቨር ታክስ(2%)፣ ትራንዛክሽን ታክስ (0.1% እስከ 1.5%) .... ግሽበቱንና ሌላውን ቀጣይ ቅንስናሻ በሕሊናችሁ አክሉበት
ከዚህ ሁሉ ቅንስናሽ በኋላ የሚገኘው የደሞዝ ጭማሪ ኢሚንት ቢሆንም አይጠቅምም ማለት በእግሩ ተጓጉዞ፣ በቀን አንዴ ቀምሶ ከሚያተርፋት "ደሞዙ" ላይ በየእለቱ ለልጆቹ ደረቅ ዳቦ የማቅረብ ግዴታ የተጣለባትን ቋሚ ደሞዝተኛ ፈተናና መከራ በቅጡና በልኩ አለመረዳት ይሆናል።
ተወደደም ተጠላ፣ አነሰም ተከመረ ጭማሪው ጎዳን ለመውጣት እየተንደረደረ የነበረውን ቋሚ የመንግስት ደሞዝተኛ እንደሚደጉምና አንድ ቀዳዳ እንደሚደፍንለት ጥርጥር የለኝም። ደሞዝ መቼም በቂ ሆኖ አያውቅም። በቂ ካልሆነ ደግሞ ጭማሪው ይቅር ለማለት ቋሚ ደሞዝተኛውን እሱና ቤተሰቡን ከነ መከራው ሆኖ መገኘትን ይጠይቃል።
ሙሼ ሰሙ-
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…

